Administrator

Administrator

የአለም የጤና ድርጅት ባወጣው መረጃ በአለማችን ላይ እድሜያቸው ከ15-49 የሆነ 340/ ሚሊዮን
ሰዎች በመራቢያ አካላት ኢንፌክሽን እንዲሁም በተለያዩ የአባላዘር በሽታዎች እንደሚያዙ ቁሟል። ይህ የመራቢያ አካላት ኢንፌክሽን እንደኛ ባሉ ታዳጊ ሀገራት ትልቁን ቁጥር የሚሸፍን የስነተዋልዶ ጤና ችግር እንደሆነም በተለያየ ግዜ የሚወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡የመራቢያ አካላት ልክ እንደ ሌሎች የሰውነት ክፍሎቻችን ሁሉ በተለያየ ግዜ እና አጋጣሚ ተለያዩ በሽታዎች ሊጠቁ ይችላሉ፡፡ በተለያየ ምክንያት የሚፈጠሩ ኢንፌክሽኖች ወይም በህክምናው ሳይንስ RTIs (Reproductive tract infections)  ለዚህ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ዛሬው ፅሁፋችን በእነዚህ በመራቢያ አካላት ላይ በሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች እንዲሁም የአባላዘር ሽታዎች ዙሪያ ባለሙያ አነጋግረን ያገኘነውን ምላሽ እንዲህ ልናስነብባችሁ ወደናል፡- ለዛሬ ያነጋገርናቸው ባለሙያ ዶክተር መብራቱ ጀንበር ይባላሉ፡፡ ዶክተር መብራቱ በብራስ የእናቶች እና ህፃናት ሆስፒታል የማህፀንና ፅንስ ሀኪም ናቸው። የምናወራው በመራቢያ አካላት ላይ
በሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች ዙሪያ ነውና በአጠቃላይ የስነተዋልዶ አካላት ስንል የትኛውን የሰውነት ክፍል የሚያጠቃልል ነው? ብለን በቅድሚያ ላነሳንላቸው ጥያቄ የሚከተለውን ማብራሪያ ሰጥተውናል፡፡
“...የስነተዋዶ አካል ስንል በሴት በኩል የሴት ብልትን እና የማህፀን ክፍሎችን ባጠቃላይ እንዲሁም ልጅ  ከተወለደ በኋላ ወተት በማመንጨት የሚያገለግሎ ጡቶችንም ይጨምራል፡፡ በወንድ በኩል ደግሞ የወንድ ልጅ ብልት አለ የዘርፍሬዎች እንዲሁም ሌሎች ሆርሞን በማመንጨት የሚያገለግሉ እጢዎች አሉ፡፡ እነዚህ በሙሉ ከስነተዋልዶ ጋር  ቀጥተኛ የሆነ ግንኙነት ያላቸው የሰውነታችን ክፍሎች ናቸው፡፡” የስነተዋልዶ አካላትን የሚያጠቁ ኢንፌክሽኖች በብዛትም ሆነ በአይነት እጅግ በርካታ ሲሆኑ በእነዚህ የሰውነት ክፍሎች ላይ በሚፈጠር ባክቴሪያ መንስኤነት የሚከሰቱ እና በግብረስጋ ግንኙት አማካኝነት የሚተላለፉ የአባላዘር በሽታዎች በሚል በሁለት እንደሚከፈሉ ባለሙያው ይናገራሉ፡፡ “...የስነተዋልዶ አካላትን የሚያጠቁ የኢንፌክሽን አይነቶች በጣም ብዙ ናቸው ነገር ግን በዋናነት በሁለት ከፍለን ልናያቸው እንችላለን፡፡ አንደኛው በጥገኛ ህዋስ ወይም ባክቴሪያ አማካኝነት የሚመጣ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ በግብረስጋ ግንኙነት የሚተላለፉ የበሽታ አይነቶች ወይንም sexually  transmitted infections ተብለው የሚጠሩት ናቸው፡፡”ምንም እንኳን ሁሉም አይነት ኢንፌክሽኖች የተለያየ የጤና ችግር የሚያስከትሉ ቢሆንም ትልቁ ትኩረት መሰጠት ያለበት በግብረስጋ ግንኙት አማካኝነት ሊተላለፉ የሚችሉት የበሽታ አይነቶች ላይ ነው ይላሉ ዶክተር መብራቱ፡፡ ለዚህም በምክንያትነት የሚያነሱት እነዚህኞቹ የኢንፌክሽን አይነቶች ብዙውን የህብረተሰብ ክፍል የሚያጠቁ እና በግብረስጋ ግንኙነት አማካኝነት ተላላፊ መሆናቸውን ነው፡፡ ስለዚህም ይላሉ ዶክተር፡-
“..ስለዚህ sexually transmitted infections  ወይንም በግብረስጋ ግንኙነት አማካኝነት ሊተላለፉ የሚችሉ የበሽታ አይነቶች የትኞቹ ናቸው? እንዴትስ መከላከል ይቻላል? በሚሉት ጉዳዮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ መስራት እና በህብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤ መፍጠር ያስፈልጋል፡፡”አንዳንዶቹ የኢንፌክሽን አይነቶች ከማህፀን ውጨኛው ክፍል አንስቶ በተለያዩ የማህፀን ክፍሎች ላይ ሊዛመቱ የሚችሉ ሲሆን በማህፀን ውጫዊ ክፍል ላይ ብቻ ተከስተው በህክምና ክትትል ወዲያው ሊጠፉ የሚችሉም አሉ፡፡  “...vulval area ወይንም ደግሞ የብልት የውጨኛውን ክፍል ሊያጠቁ የሚችሉ ወይም ቆዳው ላይ ብቻ የሚወጡ አንዳንድ ኢንፌክሽኖች አሉ፡፡ ነገር ግን ከእነዚህ የውጪውን አካል ከሚያጠቁ ኢንፌክሽኖች መካከል የውስጠኛውን ክፍልም ሊያጠቁ የሚችሉ ይኖራሉ፡፡ ለምሳሌ ፈንገስ የምንለው የውጪውን ክፍል ከማሳከኩ እና ከማቅላቱ በተጨማሪ የውስጠኛው ክፍል ላይም ከፍተኛ የሆነ የማሳከክ ስሜት ያመጣል፡፡ በተጨማሪም ነጭ የሆነ አይብ የመሰለ ፍርፍር የሚል አይነት ፈሳሽ ይኖረዋል፡፡ ይህ በብዛት የሚከሰት የፓራሳይት አይነት ሲሆን በተለይ በእርግዝና ሰአት በጣም ይበዛል፡፡     በተቃራኒው ደግሞ በውስጠኛው የማህፀን ክፍል ላይ የሚከሰቱ የኢንፌክሽን አይነቶችም  አሉ፡፡ ለምሳሌ የግብረ ስጋ ግንኙነት በመልካም ሁኔታ እንዲካሄድ ሊያደርጉ የሚችሉ እርጥበት የሚያወጡ እጢዎች መውጫ በር ላይ የሚፈጠሩ የኢንፌክሽን አይነቶች አሉ። በዚህም ምክንያት የፈሳሽ መውጫ ቀዳዳው ይጠባል ወይም ይዘጋል፡፡ ይህም በብልት አካባቢ እብጠት ለሚያመጣው Bartholin’s cyst ወይም Bartholinitis  ለሚባለው ኢንፌክሽን መፈጠር ምክንያት ይሆናል፡፡”ሌሎች በቫይረስ አማካኝነት  የሚተላለፉ የኢንፌክሽን አይነቶችን ሲያብራሩም፡-  “ሌሎች ልክ እንደ chancroid, wart  ወይም ደግሞ papillomavirus  ወይም ኪንታሮት በመባል የሚጠራው አይነት  በቫይረስ አማካኝነት የሚተላለፉ  ኢንፌክሽኖች አሉ፡፡ እንዲሁም ደግሞ Herpes zoster  ወይም ደግሞ Herpes simplex የሚባል አለ፡፡ ይህም በቫይረስ የሚተላለፍ ሲሆን የብልት ውጨኛውን አካባቢ ያቆስላል፡፡” በባክቴሪያ አማካኝነት ከሚከሰቱት ይልቅ በግብረስጋ ግንኙነት አማካኛነት የሚመጡት ኢንፌክሽኖች  በይበልጥ ወንዶችን ያጠቃሉ ይላሉ ዶክተር መብራቱ፡፡
“...በወንዶች ላይ ባክቴሪያል ኢንፌክሽን የተለመደ አይደለም፡፡ ነገር ግን ወንዶች በግብረስጋ አማካኝነት በሚተላለፉ የኢንፌክሽን አይነቶች በብዛት ሲጠቁ ይስተዋላል፡፡ በተለይ Gonorrhea እና syphilis,  የምንላቸው የአባላዘር በሽታዎች ዋነኞቹ ናቸው። በተጨማሪም ከርክር ወይም chancroid, wart  እንዲሁም ደግሞ papillomavirus     የምንላቸውም ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡”በፈረንጆቹ 2008 በናይጄሪያ የተደረገ አንድ ጥናት የግብረ ስጋ ግንኙነት እንዲሁም ደካማ የሆነ የንፅህና አጠባበቅ 44.6% የሚሆነውን የበሽታው መተላለፊያ መንገድ እንደሚይዝ ጠቁሟል፡፡“...መተላለፊያ መንገዱ አብዛኛውን ግዜ የሰውነት አቅም መድከም ነው፡፡ በተጨማሪም ከፍተኛ የጣፋጭ ይዘት ያላቸው ምግቦች ወይም መጠጦች ማዘውተር እና አብዝቶ መጠቀም በሽታው የሚኖረውን ተጋላጭነት ሊጨምር ይችላል፡፡ እንዲሁም አዘውትረው ብልታቸውን የሚታጠቡ ሴቶች ይህ ችግር ሊያጋጥማቸው ይችላል። የብልት ተፈጥሯዊ እርጥበት ታጥቦ መወገድ የለበትም
ምክንያቱም ብልት የእራሱ የሆነ በሽታ ተከላካይ ፈሳሽ አለው፡፡ ይህ መከላከያ ደግሞ አላስፈላጊ
ፓራሳይቶችን ያጠፋል፡፡ ስለዚህ የብልት አካባቢ ቢያንስ በቀን ሁለት ግዜ ጠዋትና ማታ ከታጠበ በቂ ነው፡፡ ሌሎቹ የኢንፌክሽን አይነቶች ደግሞ ቀደም ሲል እንደ ገለፅኩት በግብረስጋ ግንኙነት አማካኝነት የሚተላለፉ     ናቸው፡፡ ለዚህም እንደ Gonorrhea, syphilis, Trichomoniasis እንዲሁም papillomavirus የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላ፡፡” አብዛኞቹ በባክቴሪያ አማካኝነት የሚመጡት ኢንፌክሽኖች ከግል ንፅህና ጉድለት ወይም ተገቢውን የንፅህና አጠባበቅ ባለመከተል የሚከሰቱ መሆናቸውንም ጨምረው ይገልፃሉ፡-
“ከሰገራ ጋር የሚወጡ በጣም አጥቂ የሆኑ ህዋሳቶች አሉ በጣም በብዛት የሚገኘው Escherichia coli  ወይም E. coli  የምንለው  የባክቴሪያ አይነት ነው፡፡ ይህ ባክቴሪያ በማህፀን አካባቢ ሲገኝ የማህፀን ኢንፌክሽን እንዲሁም የሽንት መተላለፊያ ቱቦ ኢንፌክሽኖችን ያመጣል፡፡ ስለዚህ በተቻለ መጠን የግል ንፅህና አጠባበቅ ስልቱን ማወቅ ያስፈልጋል ወይም ደግሞ የጤና ባለሙያ ጋር በመሄድ እንዴት ባደርግ ነው እነዚህን ኢንፌክሽኖች መከላከል የምችለው የሚለውን በተመለከተ የምክር አገልግሎት መቀበሉ በጣም ጥሩ ይሆናል፡፡” የዚህ አይነት የስነ ተዋልዶ ጤና ችግሮች ተገቢው ህክምና ካልተደረገላቸው ለመሀንነት፣ ከመሀፀን ውጪ ለሚፈጠር እርግዝና ብሎም ለኤች አይቪ ቫይረስ የማጋለጥ እድላቸው ከፍተኛ ነው፡፡ ችግሩ እየተባባሰ ከሄደም ለሞት መዳረጋቸው አይቀሬ ነው ብለዋል ዶ/ር መብራቱ ጀምበር፡፡ “...እነዚህ ኢንፌክሽኖች እስከ ሞት ደረጃም ሊያደርሱ ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም ኢንፌክሽኑ ሀይለኛ እየሆነ በሄደ ቁጥር ወደ ሌሎች የሰውነታችን ክፍሎች መዛመቱ አይቀርም፡፡ ሌላው ያልጠቀስነው ደግሞ ኤችአይቪም ነው፡፡ ኤች አይቪም እንደዚሁ በግብረስጋ ግንኙነት ነው።  ምንም እንኳን የግብረስጋ ግንኙነት ብቻ የመተላለፊያ መንገዱ ባይሆንም በግብረስጋ ግንኙነት የመተላለፍ ሀይሉ ከፍተኛ ነው፡፡ ስለዚህ ችግሩ እየጠና ሲሄድ     ህክምና በወቅቱ ካልተገኘ የመሞት አጋጣሚም ይኖራል።”

Monday, 11 May 2015 09:02

የፍቅር ጥግ

ከሁሉም ጣፋጩ ድምፅ ያፈቀርናት ሴት ድምፅ ነው፡፡
ዣን ዲላ ብሩዬር
የመጀመሪያ ዕይታዬ የሚያርፈው በልብሽ ላይ ነው፡፡
ጆሃን ኤፍ ሲ ሺለር
አበባ ያለ ፀሐይ ብርሃን እንደማያብበው ሁሉ፣ ሰውም ያለ ፍቅር መኖር አይችልም፡፡
ማክስ ሙለር
ለዓለም አንድ ሰው ነሽ፤ ለእኔ ግን ዓለሜ ነሽ፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
አፍቅሪኝ፤ ያኔ ዓለም በሙሉ የእኔ ትሆናለች።
ዴቪድ ሪድ
አንድ ቃል ከህይወት ሸክምና ስቃይ ነፃ ያወጣናል፡፡ ያ ቃል “ፍቅር” ነው፡፡
ሶቅራጦስ
ህይወትን ውደዳት፤ ህይወት መልሳ ትወድሃለች፡፡ ሰዎችን ውደዳ    ቸው፤ እነሱም መልሰው

ይወዱሃል፡፡
አርተር ሩቢንስቴይን
መሳሳም ጨዋማ ውሃ እንደ መጠጣት ነው። በጠጣህ ቁጥር ጥምህ ይጨምራል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ስሞሽ (Kissing) የፍቅር ፊርማ አይደለምን?
ሔነሪ ፊንክ
ደስተኛ ትዳር ያፈቀርነውን ስናገባ ይጀምራል፤ ያገባነውን ስናፈቅር ደግሞ ያብባል፡፡
ቶም ሙሌን
የደስታን ሙሉ ጣዕም ለማግኘት፣  የምታካፍሉት ሰው ሊኖራችሁ ይገባል፡፡
ማርክ ትዌይን
በጣቶቻችሁ መካከል ያሉት ክፍት ቦታዎች የተፈጠሩት በሌሎች ጣቶች እንዲሞሉ ነው፡፡
ማንነቱ ያልታወቀ ፀሐፊ
በህይወት ውስጥ አንድ ደስታ ብቻ ነው ያለው፡፡ ይኸውም ማፍቀርና መፈቀር ነው፡፡
ጆርጅ ሳንድስ
መውደድን የምንማረው በመውደድ ብቻ ነው፡፡
አይሪስ ሙርዶክ
ፍቅር ሰዎችን ይፈውሳል - ሰጪውንም ተቀባዩንም፡፡
ካርል ኤ. ሜኒንገር
ጥላቻ በጥላቻ አይሻርም፤ በፍቅር ብቻ እንጂ፡፡ ይሄ ዘላለማዊ ህግ ነው፡፡
ቡድሃ
በፍቅር ለሚወድቁ ሰዎች ስበት ተጠያቂ አይደለም፡፡
አልበርት አንስታይን
ፍቅር ህይወት ነው፡፡ ፍቅር ካመለጠህ፣ ህይወትም ያመልጥሃል፡፡
ሊዮ ቡስካግልያ

Monday, 11 May 2015 08:55

መርዶ ባደባባይ

በአገራችን ባህል እኛ የምናውቀው፡-
    በሌሊት ነበረ ሰው ለቅሶ ‘ሚያረዳው,
    ተረጂው ሳይሰማ፣ በምስጢር ተይዞ ጎረቤት መክሮበት
    ለዚሁ እሚመጥን አንጋፋ ተመርጦ ዕድር ያመነበት፤
    በሥርዓት ነበር፣ ሰው መርዶ እሚረዳው
    ሃዘንተኛም ሰምቶ በወጉ ነበረ እርሙን የሚያወጣው፡፡
        ዛሬ ወግ ተሸሮ፣ ባህል ተሸርሽሮ
        ሉላዊነት (ግሎባላይዜሽን) ገኖ በዕድገት ተስፈንጥሮ
        እርም ባደባባይ ኦን-ላይን አወጣን
        የሟቾችን ሲቃ በፌስ ቡክ እያየን፡፡
        በዕድገት ኋላ ቀርተን፣ በመከራ ቀድመን
        በዘመን ተሳቀን፣ ዓለም ተሳልቆብን
        እንደ ሰው ተፈጥረን፣ አጉል ሞት እየሞትን
        በጉደኛው ዘመን እንደጉድ እየኖርን
        ይሄው ለዚህ በቃን! ይኸው ለዚህ ደረስን!!
    የጉድ ቀን አይመሽም፣ ፍርጃ እቤት አይውልም
    መከራ ሲመክር አስተዋይ አዕምሮ ቀና ልብ የለውም፣
    አገር መርዶ አረዳች፣ አገር እርም አወጣች በጠራራ ፀሐይ
    ሰቆቃ ዘነበ … በረዶ ወረደ … በአገሬ ሰማይ ላይ
    ህዝቡ ደረት ጣለ፣ ሳር ቅጠሉ አዘነ በእንባ ተጥለቅልቆ
    ሀዘን ቅጡን አጣ፤ ከል ለበሰ አገር ባንዲራ አዘቅዝቆ
    ድህነት በፊናው፣ ያሰበው ሞላለት ኮራ ግዳይ ጥሎ
    በወገን ደም ግብር የሱ ቆሌ ረካ፣ የእኛ ፅዋ ጎድሎ፡፡
***
    “ድህነት ወንጀል አይደለም” ይላል አዳሜ እንደዋዛ
    ከወንጀል-ወንጀልም እንጂ ጣጣ መዘዙ የበዛ፡፡
    ማጣት የሃጢያት ሥር ነው፣ የገዛ እርምን ያበላል
    የሰው ፊት የቋያ እሳት ነው፣ ከሩቁ ይለበልባል
    “ችግር በቅቤ ያስበላል”፣ ይሉት የአበሻ ጅል ተረት
    የስላቅ የፌዝ - መርፌ ነው፣ የነፍስ ግርዛት ሸለፈት
    አጅሬ ችግር ዱር አውሬ እንኳንስ ቅቤ ሊያበላ
    አየነው ለጉድ ተፈጥረን፣ በካራ አንገት ሲያስቀላ፡፡
    የድህነትን ጅብ ሸሽቶ - ቢወጣ ካገር ተሰዶ
    ጥርሶቹን ስሎ ጠበቀው፣ አይምሬው የባህር ዘንዶ፡፡
    ምስካየ ሕዙናን ነበርን፣ ለተሰደዱት አለኝታ
    ለሰቅጣጭ “የርድ” ሞት በቃን፣ አቤቱ የማታ ማታ!
    ፅናቱን ይስጥሽ አገሬ፣ ይከብዳል መርዶው የልጅ ሞት
        በተለይ እጅሽ አጥሮበት
        ሪቅሽ እየራቀበት
        ሌማትሽ ሲራቆትበት…
        የኑሮ ሚዛን ተዛብቶ
        በቀየሽ ልጅነት ጎልቶ …
    … ቢጨንቀው ስደትን መርጦ …
    ሲኳትን በረሃ አቋርጦ …
    በባዕድ ቀላድ ቀላውጦ …
    ተስፋውን ሊወልድ አምጦ!
    ካቀደው ሳይደርስ ምኞቱ
    በሰደፍ ሲቀላ አንገቱ
        ይከብዳል ለእናት ስሱ አንጀት
        ይዳብስሽ አምላክ በምህረት!
    ፅናቱን ይስጥሽ ኢትዮጵያ! ያድንሽ ከዳግም ውርደት
    በብልፅግና ፅደቂ! ገሃነም ይውረድ ድህነት!
    ገናናነትሽ ይመለስ - አይታይ ክብርሽ ኮስሶ
        ጥቃት አንገት ያስደፋል!
        ማጣት አንገት ያስቀላል!
        ይመራል ልክ እንደ ኮሶ!
    የሐዘን ማቅሽ ይቀደድ! ያቁምሽ በፈውሱ ማማ
    ሙሾ ወረዳው አብቅቶ - ህዳሴሽ በዓለም ይስማ!!
ደመቀ ወልዴ
22/08/2007 (በሊቢያ በሥደት ሳሉ
አይኤስአይኤስ በተባለ ቡድን በግፍ ለታረዱ ወገኖቻችን)

ድር ቢያብር አንበሳ ያስር፡፡
የኢትዮጵያውያን አባባል
ብዙ እጆች ሥራን ያቀላሉ፡፡
የታንዛንያውያን አባባል
ሁለት ጉንዳኖች አንድ አንበጣን ለመጐተት አያንሱም
የታንዛንያውያን አባባል
አንድ አምባር ለብቻው አይንሿሿም፡፡
የኮንጐአውያን አባባል
አንድ እንጨት ይጨሳል እንጂ አይነድም፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
በፍጥነት ለመጓዝ ከፈለግህ ብቻህን ሂድ፤ ሩቅ ለመጓዝ ከፈለግህ በህብረት ሂድ፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
ቤተሰብ እንደዛፍ ነው፤ ይጐብጣል እንጂ አይሰበርም
የዩቴ አባባል
የቅርብ ወዳጅ የቅርብ ጠላት ይሆናል፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
ጓደኛ ማጣት ከመደህየት እኩል ነው፡፡
የታንዛንያውያን አባባል
ለከብቶችም እንኳን ወጣትነት ውበት ነው።
የግብፃውያን አባባል
ቁንጅና ተሸጦ አይበላም፡፡
የናይጄሪያውያን አባባል
ቡናና ፍቅር የሚጣፍጠው በትኩሱ ነው፡፡
የኢትዮጵያውያን አባባል
ፍቅር ባለበት ጨለማ የለም፡፡
የቡሩንዲያውያን አባባል
ከአንተ የሚበልጥ እግር ያላት ሴት አታግባ።
የሞዛምቢካውያን አባባል
ትዕግስት ሁሉንም ችግሮች የሚፈታ ቁልፍ ነው፡፡
የሱዳናውያን አባባል
ስለሮጡ ብቻ ይደረሳል ማለት አይደለም፡፡
የስዋሂሊ አባባል
ትዕግስት ድንጋይ ያበስላል፡፡
የአፍሪካውያን አባባል

Sunday, 10 May 2015 15:38

የነፃነት ጥግ

ነፃነት፤ ሰዎች መስማት የማይፈልጉትን የመናገር መብት ነው፡፡
ጆርጅ ኦርዌል
ሃላፊነት ለነፃነት የሚከፈል ዋጋ ነው፡፡
ኢልበርት ሁባርድ
መንግስት ገደብ ካልተበጀለት በቀር ሰው ነፃ አይሆንም፡፡
ሮናልድ ሬገን
ነፃነት የነፍሳችን ኦክሲጅን ነው፡፡
ሞሼ ዳያን
በመናገር ነፃነት አምናለሁ፤ ነገር ግን በመናገር ነፃነትም ላይ ሃሳባችንን የመግለጽ መብት ሊኖረን ይገባል ብዬ አምናለሁ፡፡
ስቶክዌል ዴይ
ነፃነት ካልተጠቀሙበት የሚከስም ነገር ነው፡፡
ሃንተር ኤስ.ቶምፕሰን
የመፃፍና የመናገር ነፃነት ሰዎችን የማብሸቅ ነፃነትን ይጨምራል፡፡
ብራድ ቶር

የብሩንዲው ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ የአገሪቱ ህገ-መንግስት ከሚፈቅደው ውጭ ለሶስተኛ ዙር በምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸው ህገወጥነት እንደሆነና ውሳኔውን አጥብቆ እንደሚቃወመው የአፍሪካ ህብረት አስታወቀ፡፡
የፕሬዚዳንቱ ውሳኔ በአገሪቱ የቀሰቀሰው ህዝባዊ ቁጣ እየተባባሰ መምጣቱ፣ ምርጫውን በሰላማዊ መንገድ ለማካሄድ አመቺ አይደለም ያለው የአፍሪካ ህብረት፣ የምርጫ ታዛቢ ቡድኑን ወደ አገሪቱ እንደማይልክም አስታውቋል፡፡ከስልጣናቸው እንዲወርዱ በአሜሪካ እየተደረገባቸው ያለውን ጫና የተቃወሙት ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ በበኩላቸው፤ ቀጣዩ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ መከናወን እንዲችል ህዝቡ ተቃውሞውን እንዲያቆም ጥሪ አቅርበው፣ ለአራተኛ ዙር አገሪቱን ለመምራት እንደማይፈልጉና ከዚህ በኋላ በምርጫ እንደማይወዳደሩ ቃል ገብተዋል፡፡
ፖሊስ የአገሪቱን ዜጎች ደህንነት ለመጠበቅ ሲል በተቃውሞው የተሳተፉትን ሰዎች በማሰር ላይ እንደሚገኝና፣ ዜጎች ከመሰል ድርጊታቸው የሚታቀቡና ተቃውሞው የሚቆም ከሆነ የአገሪቱ ፖሊስ በቁጥጥር ስር ያዋላቸው ዜጎች በሙሉ እንደሚፈቱም ፕሬዚዳንቱ አስታውቀዋል፡፡በብሩንዲ ያለው ሁኔታ አደገኛ ነው፡፡ ምርጫውን ለመታዘብ አንችልም፡፡ ፕሬዚዳንቱ ለሶስተኛ ዙር መወዳደራቸውም አግባብነት የለውም፤ የአገሪቱ ህገመንግስት ሊከበር ይገባል ብለዋል የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽነር ንኮዛና ድላሚኒ ዙማ፤ ከቻይናው ሲሲቲቪ ቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ከትናንት በስቲያ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ፡፡አገሪቱን በመምራት ላይ የሚገኘው ሲኤንዲዲ-ኤፍዲዲ ፓርቲ ከሁለት ሳምንታት በፊት የወቅቱን የአገሪቱ ፕሬዚደንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ በመጪው ምርጫ በዕጩነት ማቅረቡን ተከትሎ በተቀሰቀሰው ተቃውሞ ከ15 ሰዎች በላይ መሞታቸውንና በርካቶች መቁሰላቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ተቃውሞው ተጠናክሮ መቀጠሉን ጠቁሟል፡፡ሮይተርስ በበኩሉ፤ ከትናንት በስቲያ በአገሪቱ መዲና ቡጁምቡራ ለተቃውሞ የወጡ ዜጎች የገዢው ፓርቲ የወጣቶች ክንፍ አባል ነው ያሉትን አንድ ግለሰብ በእሳት አቃጥለው መግደላቸውንና የተለያዩ ሱቆችን ማጋየታቸውን ዘግቧል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ለሶስተኛ ዙር ምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸው የህግ ጥሰት ነው ያሉት የአገሪቱ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና የሲቪል ማህበረሰብ ቡድኖች፣ የአገሪቱ ህገመንግስት አንድ ፕሬዚዳንት በመሪነት መቆየት የሚችለው ለሁለት ዙር ብቻ እንደሆነ ቢወስንም፣ ፕሬዚዳንቱ ግን ህገመንግስቱን በጣሰ ሁኔታ በስልጣን ላይ ለመቆየት እየተዘጋጁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
የፕሬዚዳንቱን የምርጫ ተሳትፎ አግባብነት በተመለከተ ጉዳዩን ሲመረምር የቆየው የብሩንዲ ህገመንግስታዊ ፍርድ ቤት በበኩሉ ባለፈው ሰኞ ይፋ ባደረገው ውሳኔው፣ ፕሬዚዳንቱ የመጀመሪያውን ዙር በፓርላማ እንጂ ቀጥታ በህዝቡ ተመርጠው ስልጣን ባለመያዛቸው እንደ አንድ ዙር አይቆጠርባቸውም፣ በዘንድሮው ምርጫ መወዳደር ይችላሉ ብሏል፡፡
የፍርድ ቤቱ ምክትል ፕሬዚዳንት ሳላይሬ ኒምፓጋሪትሴ ግን፣ ከመንግስት በተደረገ ጫና የተላለፈ ውሳኔ ነው በሚል ተቃውመው፣ ፊርማዬን አላስቀምጥም በማለት አገር ጥለው የተሰደዱ ሲሆን የአገሪቱ መንግስት ቃል አቀባይ በበኩሉ፤ ግለሰቡ ውሳኔውን እንዲያስተላልፉ ምንም አይነት ጫና እንዳልተደረገባቸው መግለጻቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ለአመታት የዘለቀው ከ300 ሺህ በላይ ዜጎችን ለህልፈተ ህይወት የዳረገው የአገሪቱ ደም አፋሳሽ የእርስ በእርስ ጦርነት እ.ኤ.አ በ2005 ከተቋጨ ወዲህ አስከፊው የተባለውንና ከሰሞኑ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞና አመጽ ተከትሎ፣ በአገሪቱ ውጥረት መንገሱንና 40 ሺህ የሚደርሱ የአገሪቱ ዜጎች ለደህንነታቸው በመስጋት ወደ ሩዋንዳ፣ ታንዛንያና ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኦፍ ኮንጎ መሰደዳቸውንም ዘገባው አስታውቋል፡፡
ለፕሬዚዳንትነት የሚወዳደሩት ኦዲፋክስ ንዳቢቶሪየ የተባሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል ባለፈው ረቡዕ  አመጹን አነሳስተዋል በሚል በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ ከተደረገባቸው በኋላ መለቀቃቸውን እንዲሁም በአገሪቱ መዲና ቡጁምቡራ ከትናንት በስቲያ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ በቁጥጥር ስር ለማዋል ፖሊስ በወሰደው እርምጃ አንድን ግለሰብ ተኩሶ መግደሉንና ሶስት ዜጎችንም ማቁሰሉን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

መስራቾቹ ትርፋማ እንደሚሆኑ እርግጠኛ ሆነዋል
ሶስቱ ሰራተኞች በሶስት ሽፍት ይሰራሉ
ታላላቅ ኩባንያዎች ምርቶቹን ለመግዛት ተመዝግበዋል


ክላውድ ዲዲኤም የተባለውና በባለሶስት አውታር ህትመት ዘርፍ ላይ ተሰማርቶ ለመስራት ዝግጅቱን ያጠናቀቀው  የአሜሪካ ኩባንያ፣ በ3 ሰራተኞች ብቻ በሚያከናውነው የምርት እንቅስቃሴ ትርፋማ ስራ እንደሚያከናውን መስራቾቹ በእርግጠኝነት መናገራቸውን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
በአይነቱ የመጀመሪያው የሆነውና ሙሉ ለሙሉ በማሽን አማካይነት የሚሰራው ይህ ኩባንያ፣ የዘመናዊ ቴክኖሎጂ ውጤት በሆኑ 100 ባለ ሶስት አውታር ማተሚያ ማሽኖቹ አማካይነት በሳምንት ለ 7 ቀናት ለ24 ሰዓት የማምረት ስራውን የሚያከናውን ሲሆን፣ እያንዳንዳቸው በሶስት ሽፍት ለ8 ሰዓታት የሚሰሩ 3 ሰራተኞች ብቻ እንዳሉትም ገልጽዋል፡፡
ከኩባንያው መስራች አንዱ የሆኑት ሚች ፍሪ ባለፈው ረቡዕ ለሲኤንኤን እንደገለጹት፣ ኩባንያው የምርት ስራውን በማተሚያ ማሽኖቹና በሶስቱ ሰራተኞች አማካይነት በተቀላጠፈ ሁኔታ እያከናወነ ሲሆን፣ ምርቶቹን የማሸግና ለደንበኞች የማድረስ ስራውን ደግሞ ዩፒኤስ የተባለ አጋር ድርጅት እያከናወነው ይገኛል፡፡
ኩባንያው የተለያዩ ቁሳቁሶችን በባለ ሶስት አውታር ማተሚያ ማሽኖች አማካይነት በማምረት ለደንበኞቹ የሚያቀርብ ሲሆን አሰራሩ የተቀላጠፈ በመሆኑ ለማምረት አንድ ሳምንት ያህል ጊዜ የሚወስዱ ዕቃዎችን በ24 ሰዓታት ውስጥ ሰርቶ ማጠናቀቅ የሚችልበት ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ሚች ፍሪ ገልጸዋል፡፡
ኩባንያውን ለማቋቋም 1 ሚሊዮን ዶላር ወጪ መደረጉን የጠቆመው ዘገባው፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ በርካታ ደንበኞችን ማፍራት መቻሉንና በቀጣይም የባለ ሶስት አውታር ማተሚያ ማሽኖቹን ቁጥር ወደ አንድ ሺህ ከፍ ለማድረግ ዕቅድ ይዞ በቅርቡ ወደ ስራ እንደሚገባ አስታውቋል፡፡
ተቀማጭነቱ በኒውዮርክ የሆነው ሁማንስኬል የተባለ የቤት ዕቃዎች አምራች ኩባንያ፣ ታዋቂው የቅንጦት የእጅ ሰዓቶች አምራች ኩባንያ ዴቮን ዎርክስ እንዲሁም ግዙፉ ፍሌክስትሮኒክስን ጨምሮ በርካታ ድርጅቶች ከዚህ በአይነቱ የተለየ ኩባንያ ምርቶችን ለመግዛት ደንበኝነት መመስረታቸውንም አስታውቋል።

ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ የመፃሕፍት ንባብ እና ውይይት ፕሮግራም በነገው ዕለት “ዘ ማሳካር ኦፍ ደብረ ሊባኖስ ኢትዮጵያ 1937” በተሰኘው የደራሲ ኢያን ካምፔል መጽሐፍ ላይ በነገው ዕለት በብሔራዊ ቤተመፃሕፍትና ቤተመዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ ውይይት ያካሂዳል፡፡
ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ የሚያቀርቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና መምሕር የሆኑት ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ሲሆኑ የሥነ ፅሁፍ ቤተሰቦች በዚህ ውይይት ላይ እንዲታደሙ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጋብዟል፡፡
ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ለ6 ወራት ያህል በየ15 ቀኑ የሚያደርገውን የመፃህፍት ውይይት አቋርጦ እንደነበር ይታወሳል፡፡

ደራሲው ዘውዱ ደስታ የምንድስና ባለሙያ ሲሆን በዘርፋ በሃገራችን ውስጥ ትልልቅ ፕሮጀክቶች ላይ ሰርቷል፡፡ እየሰራም ይገኛል፡፡ደራሲው የህይወት ልምዱን ፤የንባብ ክህሎቱን ፤የብዙ ጊዜ ገጠመኞቹን ፤ትዝብቱንም ጭምር  ሳንሱሲ ውስጥ ከትቧል፡፡
ቀድሞ ሳንሱሲን እንዲያነቡ እድሉን ያገኙ ፀሀፊያን ከሶስት  በላይ አንኳር ጉዳችን  ደራሲው በመፅሀፋ እንዳስቀመጠና እንዲህም ሆኖ ግን ቁምነገሮቹ ተደጋጋፊና ተመጋጋቢ በመሆናቸው ለአንባቢያን የአይን መግለጫ ነው ብለዋል፡፡
ደራሲው ዘውዱ ደስታ ከአዲስ አበባ ምዕራብ  መዝለቂያ በሆነችው ሳናሱሲ ላይ መቼቱን አድርጎ የፈጠራቸው የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገር ገጸባህርያት ፤አንዳንዶቹ በልባችን ሙቀትና ቁመት ሲጎልምሱ አንዳንዶቹ ሰንፈው ሲፈርሱ በአጠቃላይ እንድንወዳቸው እንድንጨክንባቸው እና እንድንወያይባቸው ያደርጋል፡፡
ሳንሱሲ መጽሀፍን ማግኘት ለምትሹ አንባቢያን በተለያዩ መጽሃፍት መደብሮች ቀድሞ ይሸጥ ከነበረው  136 ብር  ደራሲው ዋጋውን አስተካክሎ በ96 ብር አቅርቦታል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አውራዶሮና ሚስቱ በአንድ ቄስ የእህል መጋዘን አጠገብ ሲጓዙ አውራዶሮው አንድ ባቄላ አግኝቶ ሲውጥ፤ አነቀውና፤ ውጪ ነብስ ግቢ ነብስ ሆነ፡፡ ሚስቲቱ ዶሮ የምታደርገው ብታጣ ውሃ ፍለጋ ወደ ወንዝ ወረደች፡፡
“ወንዝ ሆይ! እባክህ ባለቤቴ ባቄላ አንቆት፣ መተንፈስ አቅቶት ሊሞትብኝ ነው፡፡ ትንሽ ውሃ ስጠኝና ነብሱን ልታደገው?” አለችው፡፡
ወንዝም፤ “ወደ ሎሚ  ዛፍ ሄደሽ አንድ የሎሚ ቅጠል ካመጣሽልኝ ውሃ እሰጥሻለሁ” አላት፡፡
ዶሮይቱ ወደ ሎሚ ዛፍ ሄደችና፤
“ሎሚ ዛፍ ሆይ! ባለቤቴ ባቄላ አንቆት መተንፈስ አቅቶት፣ ሊሞትብኝ ነው ብዬ ወንዝን ውሃ ስጠኝ ብለው፤ “የሎሚ ቅጠል ካመጣሽ እሰጥሻለሁ” አለኝ፡፡ እባክህ አንዲት ቅጠል ስጠኝ?” አለችው፡፡
የሎሚ ዛፍም፤
“ወደ ቄሱ ቤት ሠራተኛ ሄደሽ የመርፌ ክር ካመጣሽልኝ እሰጥሻለሁ” አላት፡፡
እመት ዶሮ ወደ ቄሱ ቤት ሠራተኛ ሄዳ ጉዳይዋን አስረዳች፡፡
የቤት ሠራተኛዋም፤ “ወደ ላም ሄደሽ ትንሽ ወተት ካመጣሽልኝ ክሩን እሰጥሻለሁ” አለቻት፡፡
እመት ዶሮ ወደ ላም ሄዳ “ትንሽ ወተት ስጪኝ ባክሽ” ብላ ጉዳይዋን ሁሉ ዘረዘረችላት፡፡
ላምም፤ “ወደ አጫጆቹ ዘንድ ሄደሽ ትንሽ ጭድ ካመጣሽልኝ እሰጥሻለሁ” አለቻት፡፡
እመት ዶሮ እንደፈረደባት ወደ አጫጆቹ ሄዳ “እባካችሁ ትንሽ ጭድ ስጡኝ” አለቻቸው፡፡
አጫጆቹም “ወደ ቀጥቃጮች ሄደሽ ትንሽ ማጭድ ከሰጡሽ ጭዱን እንሰጥሻለን” አሏት፡፡
እመት ዶሮ ወደ ቀጥቃጮቹ ሄዳ ለመነቻቸው፡፡
ቀጥቃጮቹ ደግሞ “ወደ ከሰል አክሳዮቹ ጋ ሄደሽ አንድ አራት ራስ ከሰል አምጪልንና የጠየቅሽንን እንሰጥሻለን” አሏት፡፡
ወደ ከሰል አክሳዮቹ ላዕያውያን (Laians) ምርር ባለ ምስኪን ቃና አስተዛዝና፤
“ከሰል አክሳዮቹ ሆይ፤ ባለቤቴ አውራዶሮ ባቄላ አንቆት፣ መተንፈስ አቅቶት ሞት አፋፍ ቢደርስ፣ አንድ ጉንጭ ውሃ ወንዝን ብጠይቀው፣ የሎሚ ቅጠል ከሎሚ ዛፍ አምጪ፤ የሎሚ ዛፍ ጋ ብሄድ ከቄሱ ሠራተኛ የመርፌ ክር አምጪ፤ የቄሱ ሠራተኛ ከላም ወተት አምጪ፤ ላም ጋ ብሄድ ከአጫጆቹ ጭድ አምጪ፤ አጫጆቹ ጋ ብሄድ ከቀጥቃጮች ማጭድ አምጪ፤ ቀጥቃጮቹ ዘንድ ብደርስ ከላዕያውያን ከሰል ካመጣሽ እንሰጥሻለን አሉኝ፡፡ እባካችሁ እናንተ እንኳ እሺ በሉኝ፡፡”
ከሰል አክሳዮቹ ራሩላትና ከሰሉን ሰጧት፡፡
እመት ዶሮ እየከነፈች ከሰሉን ይዛ ለቀጥቃጮቹ ሰጠች፡፡ ማጭድ ተቀብላ ለአጫጆች፤ ከነሱ ጭድ ተቀብላ ለላም፤ ከላም ወተት ወስዳ ለቄሱ ሰራተኛ፤ ከሷ የመርፌ ክር ተቀብላ ለሎሚ ዛፍ፤ ከሎሚ ዛፍ ቅጠል ተቀብላ ወደ ወንዙ በረረች፡፡ ከወንዙ ውሃ ተቀብላ ወደ አውራ ዶሮ ባሏ ከነፈች፡፡
አውራ ዶሮ ባሏ ግን ለአንዴም ለሁሌም ፀጥ ብሏል፡፡ ሞት ቀድሟታል፡፡
*   *   *
ችግር ሠንሠለቱን ሲተረትር ሰው በማህል ያልቃል፡፡ አያድርስ ነው፡፡
ገጣሚ ደበበ ሰይፉ፤ በ “አክሱም ጫፍ አቁማዳ” ግጥሙ ትግራይ ለሸዋ፣ ለአርሲ ለሲዳሞ፣ ለወለጋ፣ ለጐንደር፣ ለኤርትራ እህል ተለማምነው፤ የተላከችው አቁማዳ አንዳችም እህል ሳይገባባት ተመልሳ ለባለቤቱዋ ለትግራይ ባዶዋን ትመጣለች፡፡
“…አክሱም ላይ ሠቀላት
ከባዶ አቁማዳ ነው፣ እሚዛቅ ፍቅራችን” ብሎ ይደመድማል፡፡ አንድምታው ብዙ ነው፡፡ የችግሩ መጠን ይለያያል እንጂ በየሠንሠለቱ ቀለበት ላይ ችግር አለ፡፡ ቢሮክራሲያችንም እንደዚያው ነው! ሁሉም ለየግብዓቱ ጥሬ ዕቃውን ይጠይቃል፡፡ ይሄን ሠንሰለት ሙስና ብንለውም፤ ወይም የቅብብሎሽ ሂደት፤ አሊያም ዱላ ቅብብሎሽ፤ ዞሮ ዞሮ የታነቀው ህዝብ ለአንዲት ፍሬ መሞቱ አሳዛኝ ሀቅ ነው!
የችግሮቻችን ብዛት የመፍትሔዎቻችንን ውስብስብ ገፅታ ከወዲሁ ጠቋሚ ነው፡፡ የቆዩ ችግሮች መፍትሔ ሳያገኙ፤ አዳዲሶቹን ለመፍታት መጣራችን ራሱ አንድ ተጨማሪ ችግር ይሆንብናል፡፡ የሀገራችን ቁልፍ ጉዳይ ችግርን በሌላ ችግር መፍታት መሆኑ አሳሳቢ ከሆነ ቆይቷል፡፡ አብሮ መታየት ያለበት ግን ችግርን የመገንዘብ አቅማችንም አናሳ መሆን ነው፡፡
አንድ ፈላስፋ እንዳለው፡-
“The Problem is us; the Solution us” (ችግሩም እኛ፤ መፍትሔውም እኛ እንደማለት) ስለዚህ “እንዳልተመለሰው ባቡር” ያልተመለሱ ጥያቄዎች ሲደመሩ አዲስ ጥያቄ እያረግን ማሰብ ይበጃል፡፡
ሀ+1= ለ
ሀ= የዱሮ ችግር፣ “1” = አዲሱ ችግር፤ “ለ” = ያሁኑ ሁኔታ፤ እያልን ማስላት ነው፡፡ የዱሮ ችግር ብለን በመዝገብ የተያዙ ሂሳቦችን ካላወራረድን ነገ ኦዲተር አይለቀንም!
ከዲሞክራሲ ምን ጐሎ ነበር? ከፍትሕ ምን ጐሎ ነበር? ከሙስና መፍትሔ ምን ጐሎ ነበር? ከመልካም አስተዳደር ምን ጐሎ ነበር? ከሹምሽር ሥራ ምን ጐሎ ነበር? ህዳሴውስ ተመርምሯል ወይ? ከምርጫ ዝግጅት አሁን ምን ጐሎዋል? ከዱሮ ምርጫዎችስ ምን ጐሎ ነበር? በዚህ ሁሉ ድምር ሂሳብ ዛሬ ምን ላይ ነን? በአየር ጊዜ ክርክር አድማጩ ህዝብ እየረካ ነው? ምርጫው የተበላ ዕቁብ ነውን? የሚለው አስተሳሰብ መክኗል ወይስ በየልቡ ያኮበኩባል፡፡
በተፅዕኖ ከመምረጥ ጀምሮ አንዳንዱን ጠፍቶ ድንገት የመጣ ተመራጭ “አፋልጉኝ” እስከማለት የደረሰ፤ በስላቅ በሚኖር ህብረተሰብ ውስጥ ምርጫው አድሎ የሌለውና ዕውነተኛ (ነፃ) [Fair and Free] ነው ብሎ ለመኩራት፣ ለመተማመንና “አሹ!” ለማለት ከባድ ነው፡፡ “ዐባይን ጭብጦዬን ከወሰደብኝ በኋላ አላምነውም!” ያለውን ባላገር ደግመን ደጋግመን እንድናስብ የሚያደርገን ፖለቲካዊም ባህላዊም ተፈጥሮ ያለን ነንና እንዴት ይሆን ወደፊት የምንገፋው ማለት አመላችን ነው!
“አይሠግሩም ተብሎ
ፈረስና በቅሎ፤
አይሮጡም ተብሎ
ፈረስና በቅሎ፤
እንዲያው በጥላቻ:-
ትመረጥ ይሆናል ኤሊ ለኮርቻ!” የሚለው አገርኛ አባባል፤ ጥቂት ቆም ብለን እንድናስብ ዐይናችሁን ክፈቱ ይለናል፡፡