Administrator

Administrator

ብዙ ወላጆች ቀኛቸው የልጅ ፍቅር ፣ግራቸው ልብን የሚያደማ ህመም ላይ የተቸነከረበት ከባድ የፈተና መስቀል፤ ኦቲዝም። ብዙሀኑ እስካልደረሰበት በዝምታ በቸልተኝነት የሚያልፈው ጉዳይ። ኦቲዝም። ሲደርስባቸው የሚይዙ የሚጨብጡትን የሚያሳጣ ውጣ ውረድ።
ልጆቻችሁ ልጅነታቸው በመገለል ሲያልፍ እንደማየት ስቃይ የለም! መደበኛው ኑሮ ልጆቻችሁን ገፍቶ ወደዳር ሲጥል ህዝብ ሁናችሁ አገር፣ መንግስት፣ ሕዝብ፣የዕምነት ተቋማት ሸክማችሁን ብቻችሁን ማሸከማቸው አንሶ በባህል፣ በሲስተም በእምነት ስም ሲገፋችሁ ነፍስ ድረስ የዘለቀ ነው ህመሙ።
ሁሉም ያልተዘጋጀበት ግን ማንም ላይ ሊደርስ የሚችል ሩቅ መሳይ የቅርብ እውነት። ብዙ ወላጆች ይህን ፈተና ለብቻቸው ተሸክመው ዋጋ እየከፈሉ ነው። ከአካላዊ ድካም አልፎ የማህበረሰቡ አመለካከት፣ነፍስን የሚያሰቃይ የእሳት ጅራፍ ሆኖ በየቀኑ በዝምታ እየተቀበሉት ይኖራሉ። ይህች ብርቱ እናትያውም ፋታ የማይሰጠው የውጭ አገር ኑሮ ጋር እየታገለች የተፈተነችበትን መንገድ ፅፋ አሳትመዋለች።
የማይናገረው ልዑል ብዙወች ስለማይናገሩት ፈተና የሚያትት መፅሐፍ ነው። መፅሐፉ ዛሬ ጁን 6 ሲያትል ውስጥ ከ9:00 pm- 7:pm ይመረቃል። ሁላችሁም ተገኙ። አድራሻው ካርዱ ላይ አለ። Mesi Haile ብርቱ ሴት ፣ ላለፍሽው ውጣ ውረድ ለብዙዎች አይን ገላጭ ለሆነ ለዚህ ስራሽም ትመሠገኛለሽ። ብዙዎችን ድንገት ከሚመጣ ግራ መጋባት ቢያንስ ከየት እንደሚጀምሩ መንገድ ጠቁመሻል። Melaku Berhanu በዚህ ጉዳይ መታተርህ ለትውልድ ትርፉ ብዙ ነው።
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
ቢሊየነሩ የስራ ፈጣሪ ኢሎን መስክ አፍሪካ ለገጠማት የድህነት ችግር ተጠያቂው የቅኝ ግዛት ታሪክ ነው የሚለውን የቆየ አመለካከት ውድቅ አድርጓል። መስክ ይህንን አስተያየት የሰጠው ቅዳሜ ዕለት በኤክስ ማህበራዊ ገጽ ላይ የኢትዮጵያንና የቬትናምን የምጣኔ ሀብት ታሪክ በማነፃፀር ለቀረበ ፅሁፍ ምላሽ በሰጠበት ወቅት ነው።
ፅሁፉን ያጋራው ተጠቃሚ እንደገለጸው፥ ኢትዮጵያ በታሪኳ አብዛኛውን ዘመን በቅኝ ግዛት ሳትገዛ የቆየች ቢሆንም ለብዙ ዓመታት ከአፍሪካ ድሃ ከሚባሉ ሀገራት ተርታ መሰለፏን፤ በአንጻሩ ቬትናም በፈረንሳይ ቅኝ ግዛት ስር ወድቃና ለበርካታ አስርት ዓመታት በጦርነት ስትታመስ ቆይታ አሁን ላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ እድገት እያስመዘገበች መሆኑን ጠቅሷል።
እንደ ማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚው ገለጻ ከሆነ፥ የሁለቱ ሀገራት ተቃራኒ የኢኮኖሚ ጉዞ በአፍሪካ ለሚታየው የኢኮኖሚ ፈተና ዋናው ምክንያት ቅኝ ግዛት ነው የሚለውን መከራከሪያ ዋጋ ያሳጣል። ተጠቃሚው በትዊተር ገጹ ባሰፈረው መልዕክት፥ “ኢትዮጵያ በጭራሽ በቅኝ ግዛት አልተገዛችም። ነገር ግን በታሪኳ አብዛኛውን ጊዜ ከአህጉሪቱ ድሃ ሀገራት አንዷ ነበረች። በሌላ በኩል፥ ቬትናም በፈረንሳይ ተገዝታ፣ በአስርት ዓመታት ጦርነት ወድማ፣ አሁን ግን ወደ እውነተኛ የኢኮኖሚ ብልጽግና እየገሰገሰች ነው። የአፍሪካ ድህነት ምክንያት ቅኝ ግዛት ከሆነ ኢትዮጵያ ሀብታም፣ ቬትናም ደግሞ ደሃ መሆን ነበረባት። ነገር ግን ሁለቱም አልሆኑም። እባካችሁ ይህንን ሰበብ ልናቆመው እንችላለን?” ሲል ጠይቋል።
የቴስላ እና የኤክስ ባለቤቱ ኢሎን መስክ ይህንን መከራከሪያ በመደገፍ መልዕክቱን በራሱ ገጽ ላይ መልሶ ያጋራው ሲሆን፣ ከላይ ለቀረበው ሃሳብ ያለውን ሙሉ ስምምነት ለመግለጽ “አዎ” (Yes) የሚል አጭር መግለጫ አስፍሮበታል። ይህ የቢሊየነሩ አስተያየት በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በአፍሪካ የኢኮኖሚ ታሪክ እና በቅኝ ግዛት ተፅዕኖ ዙሪያ አዳዲስ ክርክሮችን ቀስቅሷል።
በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ወልመራ ወረዳ ችሎት ውስጥ በተተኮሰ ጥይት ሕይወታቸው ያለፈውን የዳኛ ወርቄ ፈከንሳን ግድያ አስመልክቶ የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን ገልጿል። ፍርድ ቤቱ ድርጊቱን በፅኑ ያወገዘ ሲሆን፣ ይህ ጥቃት በአንድ ዳኛ ላይ ብቻ የተፈጸመ ሳይሆን በሕግ የበላይነት፣ በዳኝነት ነጻነት እና በፍትሕ ሥርዓቱ ላይ የተቃጣ ከባድ ጥቃት መሆኑን አስገንዝቧል። ዳኞች ከማንኛውም ዓይነት ዛቻ፣ ጫና ወይም ጥቃት ነጻ ሆነው የሕግ ተግባራቸውን ማከናወን እንዳለባቸውና የዳኞች ደኅንነትና ነጻነት ለፍትሕ ሥርዓቱ መሠረታዊ ዋስትና መሆኑንም ፍርድ ቤቱ አጽንዖት ሰጥቷል።
በመሆኑም በዳኞችና በፍትሕ ሥርዓቱ ተዋናዮች ላይ የሚፈጸሙ የኃይል ድርጊቶች የሕግ የበላይነትን ለማዳከም የሚደረጉ ተግባራት በመሆናቸው፣ የሚመለከታቸው የሕግ አስከባሪ አካላት ጉዳዩን በፍጥነት፣ በተሟላ እና በግልጽ ሁኔታ እንዲያጣሩ ፍርድ ቤቱ አሳስቧል። ጥፋተኞችን ለሕግ ለማቅረብ በሚደረገው ጥረት ላይ አስፈላጊው እርምጃ እንዲወሰድ የጠየቀው ፍርድ ቤቱ፣ በቀጣይም በዳኞች እና በፍትሕ ዘርፍ ባለሙያዎች ላይ ተመሳሳይ ጥቃቶች እንዳይፈጸሙ ጥብቅ የጥበቃ እርምጃዎች እንዲተገበሩ በጥብቅ አሳስቧል።
የሶማሊላንድ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር አብዲራህማን ዳሂግ ባካል ከሪፖርተር ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ ሀገራቸው በባሕር በር ዙሪያ ከኢትዮጵያ ጋር ለመተባበር አሁንም ሙሉ ዝግጁነት እንዳላት ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የባሕር በር የማግኘት መብት እንዳላት ሶማሊላንድ በጽኑ እንደምታምን የጠቆሙት ሚንስትሩ፣ ኢትዮጵያ የበርበራን ወደብ በፈለገችው መንገድ መጠቀም እንደምትችል አረጋግጠዋል።
ሆኖም ኢትዮጵያ በበርበራ ወደብ አግኝቻለሁ ያለችው የ19 በመቶ የባለቤትነት ድርሻ ምን ደረጃ ላይ እንዳለ ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ ባካል ኢትዮጵያ ወደቡን በሙሉ አቅሙ እስካሁን አልተጠቀመችበትም የሚል አጭር ምላሽ መስጠታቸውን ተገልጧል።
በተጨማሪም ሚንስትር ባካል ኢትዮጵያ የሶማሊላንድን ቁልፍ አጋርነት ከግምት ውስጥ በማስገባት አንድ ቀን እውቅና እንደምትሰጣቸው እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል። ነገር ግን ሶማሊላንድ ይህንን እውቅና እንድታገኝ በኢትዮጵያ ላይ ምንም ዓይነት ግፊት ማድረግ እንደማትፈልግና ጉዳዩን ለራሷ ለኢትዮጵያ እንደምትተወው አስገንዝበዋል። ይህ መግለጫ በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለው የዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ ትብብር ቀጣይነት ባለው መልኩ ሊመራ እንደሚችል አመላካች ሆኗል።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ ዚምባብዌ፣ ኦስትሪያ፣ ኪርጊዝስታን፣ ፖርቹጋል፣ እንዲሁም ትሪኒዳድ እና ቶቤጎን ከጥር 1 ቀን 2027 ጀምሮ ለሁለት ዓመታት የሚያገለግሉ የጸጥታው ምክር ቤት ቋሚ ያልሆኑ አባላት አድርጎ መርጧል። በዚህ ብርቱ ፉክክር በተስተዋለበት ታሪካዊ ምርጫ ወቅት መቀመጫውን ለማግኘት ከፍተኛ ቅስቀሳ ስታደርግ የነበረችው ጀርመን በቂ ድምፅ ሳታገኝ ከውድድሩ ውጪ ሆናለች። በተመሳሳይ በእስያ-ፓስፊክ ቡድን ስር በፊሊፒንስ እና በኪርጊዝስታን መካከል የተደረገው ፍልሚያ እስከ አራት ዙር የዘለቀ ሲሆን፥ በመጨረሻም ኪርጊዝስታን ፓኪስታንን ለመተካት የሚያስችላትን የመጀመሪያውን ታሪካዊ ድል አረጋግጣለች።
ማዕቀብ የመጣልና የኃይል እርምጃ የመፍቀድ ሕጋዊ ሥልጣን ያለው ይህ የ15 አባላት ምክር ቤት፥ አምስት ቋሚ አባላትና በየዓመቱ አምስቱ እየተቀያየሩ የሚመረጡ 10 ቋሚ ያልሆኑ አባላት አሉት። በዚህም መሠረት አዲሶቹ ተመራጮች ሶማሊያን፣ ፓናማን፣ ዴንማርክንና ግሪክን የሚተኩ ሲሆን፤ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ላይቤሪያ ደግሞ እስከ 2027 ማብቂያ ድረስ በምክር ቤቱ መቆየታቸውን ይቀጥላሉ። በሌላ በኩል የተመድ ጠቅላላ ጉባኤ የባንግላዲሽን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካሊሉር ራህማንን በመስከረም ወር ለሚጀምረው ለ81ኛው የጉባኤው ክፍለ-ጊዜ ፕሬዝዳንት አድርጎ መምረጡ ታውቋል።
በኦሮሚያ ክልል ወለንኮሚ መንደር በገበሬ ቤተሰብ ውስጥ ያደጉትና የእናታቸው የትምህርት ፍላጎት መሠረት ሆኗቸው እዚህ ደረጃ የደረሱት ፕሮፌሰር ገቢሳ እጄታ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ስማቸው በጉልህ የሚጠቀስ ታላቅ ሳይንቲስት ናቸው። መደበኛ ትምህርታቸውን በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ካጠናቀቁ በኋላ፣ በአሜሪካው ፑርዱ ዩኒቨርሲቲ በዕፅዋት ዘረ-መል (Plant Breeding and Genetics) የማስተርስና ዶክትሬት ዲግሪያቸውን አግኝተዋል። በአሁኑ ወቅት በዚሁ ታዋቂ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በክብር ፕሮፌሰርነትና በዓለም አቀፍ የግብርና ምርምር ማዕከል በአማካሪነት በማገልገል ላይ ይገኛሉ።
ፕሮፌሰር ገቢሳ በዓለም ላይ ካስመዘገቧቸው ድንቅ ስኬቶች መካከል ዋነኛው "ስትራይጋ" የተባለውንና የማሽላ ሥርን በመጥባት ሰብልን የሚያጠፋውን አስከፊ አረም መቋቋም የሚችል የማሽላ ዝርያ ማበልጸጋቸው ነው። በላብራቶሪ ምርምር አረሙ ከማሽላው ሥር ጋር እንዳይጣበቅ የሚያደርገውን ባዮ-ኬሚካላዊ ሂደት በመለየት፣ ድርቅንና አረምን በአንድነት የሚቋቋም ከፍተኛ ምርት የሚሰጥ አዲስ ዝርያ ፈጥረዋል። ይህ ታሪካዊ ግኝታቸው በኢትዮጵያ፣ ሱዳን፣ ኒጀርና በሌሎች ከሰሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ ሀገራት የሚኖሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ሕይወት ከረሃብ የታደገ ታላቅ የፈጠራ ሥራ ሆኗል።
Ethio Agri News

ግንቦት 27 ቀን 2018 ዓ.ም በፊንላንድ በተካሄደውና የዓለም አትሌቲክስ የወርቅ ደረጃ በሰጠው የፓቮ ኑርሚ ኮንቲኔንታል ቱር ውድድር ላይ የኢትዮጵያ አትሌቶች ደማቅ ድል አስመዝግበዋል። በሴቶች 3000 ሜትር መሰናክል ውድድር አትሌት አለምናት ዋለ ድንቅ ብቃት በማሳየት ውድድሩን በ9፡16.18 በሆነ ሰዓት በአንደኝነት አጠናቃ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች።

በተመሳሳይ የወንዶች 3ሺ ሜትር መሰናክል ላይ የተሳተፈው አትሌት አብርሃም ስሜ በ8:14:09 ሁለተኛ በመውጣት የብር ሜዳሊያ ሲያሸንፍ፣ በወንዶች 5000 ሜትር ውድድር ላይ የተሰለፈው አትሌት ጌትነት ዋለ በ13፡03.95 4ኛ ደረጃን ይዟል።

በሌላ በኩል በሴቶች 1500 ሜትር ውድድር ላይ የተሳተፈችው አትሌት ኬና ቱፋ ውድድሯን በ9ኛ ደረጃ አጠናቃለች። በአጠቃላይ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ልዑካን ቡድን በፊንላንድ ባደረገው የዓለም አትሌቲክስ ኮንቲኔንታል ቱር ውድድር ላይ ሀገራቸውን በደመቀ ሁኔታ በማስጠራት አበረታች ውጤት ማስመዝገብ ችለዋል።

በምሥራቅ አርሲ ማንነትንና ሃይማኖትን መሠረት ባደረገ ጥቃት በርካታ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች መገደላቸውን፣ ቤተክርስቲያን መቃጠሉንና ዜጎች መፈናቀላቸውን የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) አስታወቀ። ፓርቲው ባወጣው መግለጫ፣ ለዚህ ዓይነቱ ዘግናኝ ጥቃት ዋነኛው ምንጭ የአገሪቱ ፖለቲካ በማንነት ላይ የተመሠረተ መሆኑ እንደሆነ የገለጸ ሲሆን፣ መሰል ጥቃቶችን የመከላከል ቀዳሚ ኃላፊነት ያለባቸው የአካባቢው አስተዳደርና የኦሮሚያ ክልል መንግሥት በተደጋጋሚ ተፈትነው መውደቃቸውን በጥብቅ ተችቷል።
ኢዜማ በዚህ ኢሰብአዊ ጥቃት ሕይወታቸውን ላጡ ዜጎች የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን በመግለጽ፣ መንግሥት በአስቸኳይ አስፈላጊውን ማጣራት በማድረግ ጥፋተኞችን ለይቶ አስተማሪና ሕጋዊ የእርምት እርምጃ እንዲወስድ አሳስቧል። አክሎም፣ በማንነት ላይ የተመሠረተው ፖለቲካ አገርን ጨርሶ አንድ በአንድ ሳይበትን ዘላቂ መፍትሔ ማበጀት የሁሉም ባለድርሻ አካላት ቀዳሚ የቤት ሥራ ሊሆን እንደሚገባ ፓርቲው በብርቱ አስገንዝቧል።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ በአርሲ ሀገረ ስብከት በኦርቶዶክሳውያንና በቅድስት ቤተክርስቲያን ላይ የደረሰውን አሰቃቂ ጥቃት ተከትሎ ጠንከር ያለ አባታዊ የኀዘንና የማሳሰቢያ መልእክት አስተላልፈዋል።
“የጸጥታ አካላትና ኃላፊዎች ከምንም በላይ በታሪክ የሚጠየቁት በሥልጣን ዘመናቸው ለዜጎች ደኅንነት በሚከፍሉት ዋጋ” መሆኑን ያስገነዘቡት ፓትርያርኩ፤ በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች የተፈጸመውን ድርጊት በተሰበረ ልብ እንደሰሙት ገልጸዋል።
መቶ ዓመታት ያስቆጠረው የጠላታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተቃጠለበት፣ እንዲሁም የካራ ኩፍቴና መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በተዘረፈበት በዚህ ክፉ ቀን፤ በርካታ ምእመናን በግፍ መሰዋታቸውና በመቶዎች የሚቆጠሩ ወገኖች ከቀዬአቸው መፈናቀላቸው ቤተ ክርስቲያንን በእጅጉ ያሳዘነ ክስተት መሆኑን ጠቅሰዋል።
ፓትርያርኩ አክለውም፣ ቤተ ክርስቲያን በምድራዊ መከራ ውስጥ ያሉትን ምእመናን በምታጽናናበት በዚህ ወቅት ራሷ በፈተና ውስጥ ሆና ከመቸገሯም በላይ፣ በአርሲ ምድር በተደጋጋሚ የሚስተዋለው በደልና ግፍ በሁላችንም ልቡና ውስጥ “እስከ መቼ?” የሚል የቁጭት እና የኀዘን ጥያቄን መፍጠሩን አስረድተዋል።
ቤተ ክርስቲያን ለሰላም፣ ለይቅርታና ለሰው ልጆች ክብር ሁል ጊዜ የምትቆም መሆኑን የገለጹት አቡነ ማትያስ፣ መላው ኢትዮጵያውያንና ምእመናን በወንድማማችነት መንፈስ ተጋግዘው የተፈናቀሉ ወገኖችን በቁሳቁስና በጸሎት እንዲደግፉ ጥሪ አቅርበዋል። በመጨረሻም ፈጣሪ ይህንን የኀዘን ሰዓት በምሕረቱ ያሳልፍ ዘንድ፣ በግፍ የሞቱትን ነፍሳት በመንግሥቱ እንዲቀበልና የተጎዱትንም በቸርነቱ እንዲያጽናና አባታዊ የጸሎት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።
አንዳንዶች የኦርቶዶክሳዊያንን ሞት በሰሙ ቁጥር ጣታቸውን ቅዱስ ሲኖዶሱ ላይ ሲጠቁሙ አያለሁ፡፡ በእኔ ዕይታ እነዚህ ወገኖች ሁለት ስህተት እየሰሩ ነው፡፡ ቀዳሚው ቅዱስ ሲኖዶሱ ለምን ዝም ይላል ሲሉ ከዚህ ቀደም ሲታገል የኖረ ከማስመሰላቸው ይያያዛል፡፡
አቡነ ገብርኤል "የማውቀውን እናገራለሁ" በተሰኘ መጽሐፋቸው እንደነገሩን፤ የዘመናችን መራራ እውነት ኢትዮጵያዊያን ኦርቶዶክሶች እውነተኛ ሲኖዶስ የሌለን እጓለ ሙዑታን መሆናችን ነው፡፡
ስለሆነም ሲኖዶሱ ለሚጠብቃቸው በጎች ጥሩ እረኛ አልሆነም ፤ በጎቹ ሲገደሉ ለምን ዝም ይላል፤ የቤ/ክ ቴሌቭዥን ድምጹ ጠፋ ወዘተ ብለው የሚተቹ ሰዎችን ሳይ ቢያንስ እረኛ አለ ብለው በማመናቸው እገረማለሁ፡፡ የሟቾችንም ሀዘን በተለመደና የመነቸከ ወቀሳ ውስጥ እያቀለሉት እንዳይሆን እሰጋለሁ::
ዛሬ የዘመን ምጸት ሆነና ኦርቶዶክሳዊያን እየታገሉ ያሉት ከሚያሳድዷቸው ጋር ብቻ ሳይሆን ከራሳቸውም አባቶች ጋር ነው፡፡ ሩቅ ሳንሔድ ከወር በፊት የምስራቅ ወለጋ አገረ ስብከት የፃፈውን ደብዳቤ እናስታውስ፡፡ ይህ ደብዳቤ በጨዋ ቋንቋ የአገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሩፋኤል የተረከቡትን በወርቅ የተለበጠ ጥንታዊ ጽላት ሰውረዋል አልያም ሰርቀዋል ሲል ይከሳል፡፡ የሚያስደነግጠው ተራው ምዕመንና አባቶች ቦታ መቀያየራችን ብቻ አይመስልም፡፡ ትልቁ ዜና፤ ጥያቄው የደረሰው ቅዱስ ሲኖዶስ የሌባ እናት ልጇን አታማም ብሎ ነገሩን አለባብሶ መያዙ ነው፡፡
እንደ መውጫ
የቤተ-ክርስቲያን አስተምሮ መልከ ብዙ ነው፡፡ ቀነኗና ሕግጋቷም ጥልቅ ነው፡፡ ይህም ሆኖ አባቶችን አትናገሩ እያሉ ሕግ እያጣቀሱ ሊያስተምሩ የሚሞክሩ ሰዎች አይገቡኝም፡፡ ወዳጄ፤ አባቶች ከቤተ-ክርስቲያን በላይ አይደሉም፡፡ ቤተ-ክርስቲያን የምዕመናን ሕብረት ናት፡፡ ቤተ-ክርስቲያን ዐቢይ መልኳ ሰው ነው፡፡ ሰው ሲታረድ እየሞተች ያለችው ቤተ-ክርስቲያን ናት፡፡ አንዳንድ የቤተ-ክሕነት ጥቅም ተጋሪዎች ግን ቤተ-ክርስቲያን ትሙት አባቶች ግን ይዳኑ ይሉናል፡፡ እንዴት ሆኖ?
ሌሎችማ ጭራሽ በከፋው ጊዜ አንገታቸውን እንደ ሰጎን ቀብረው ግርግሩ ሲያልፍ አባቶች ላይ አፍ የሚከፍት ትውልድ መጣ ብለው ይዘባበቱብናል፡፡ እውነታችሁን ነው?
በነገራችን ላይ ከመቶ በላይ ሰው አጠመቅን የሚሉን የመስቀል አደባባይ ሐዋርያትና ተቋማት አዕላፍት ሲሞቱ የት እየተደበቁ ነው ሲያልፍ ከፊት የሚመጡት? ደግሞስ ሕንፃ ቤተ-ክርስትያን ለማሰራት በየቦታው ወንበር ዘርግተው ራሳቸው ቀድመው በሀብት የሰሩትስ የትኛው ጎሬ ውስጥ ተወሽቀው ነው ሰሞኑን የማይታዩት? የደጀሰላም በር ዘግተው ለሰው ነፍስ ድኅነት እንሰራለን የሚሉት የጉዞ ማኅበራትስ ምን ዋጣቸው?
በማእረግ ጌታቸው-
Page 1 of 807