Administrator

Administrator

በድምፃዊ ዘለቀ ገሰሰና በአቶ አዲስ ገሰሰ የተሰራው የታዋቂው የሬጌ አቀንቃኝ የቦብ ማርሌ ሐውልት ከሁለት ወር በኋላ በሚደረግ ታላቅ ሥነ-ስርዓት እንደሚቆም አዘጋጆቹ ገለፁ፡
ድምፃዊ ዘለቀ ገሰሰ ለአዲስ አድማስ እንደተናገረው፤ ሐውልቱ ቀደም ሲል የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ በነበሩት አቶ አርከበ እቁባይ በተሰየመውና ገርጂ ኤምፔሪያል ሆቴል ፊት ለፊት በሚገኘው የቦብ ማርሌ አደባባይ ላይ ለማቆም ዝግጅቱ ተጠናቋል፡፡
ሚያዚያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም የዳግማይ ትንሳኤ ዕለት በሚደረገው ታላቅ ኮንሰርትና የሀውልት ማቆም ሥነ-ስርዓት ላይ ሪታ ማርሌን ጨምሮ የቦብ ማርሌ ሁለት ልጆች እንደሚገኙና ልጆቹ በኮንሰርቱ ላይ እንደሚዘፍኑ ተገልጿል፡፡
ቀደም ሲል ሃውልቱ በሚከበረው የቦብ ማርሌ የልደት በዓል ወቅት እንዲቆም ታስቦ የነበረ መሆኑን የተናገረው ድምፃዊ ዘለቀ ገሰሰ የቦብ 70ኛ ዓመት የልደት በዓል በጃማይካ ኪንግስተን ከተማ እንዲከበር በመወሰኑና የቦብ ቤተሰቦችም ለበዓሉ ወደ ስፍራው በማምራታቸው ፕሮግራሙ ተሰርዞ ለዳግማይ ትንሳኤ እንዲካሄድ መወሰኑን አስታውቋል፡፡ የቦብማርሌ 70ኛ ዓመት የልደት በዓል ዓመቱን ሙሉ በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበርም ድምፃዊው ጨምሮ ገልጿል፡፡  

በእውነት ፊልም ፕሮዳክሽን የተሰራውና በወንድወሰን ይሁብ ተደርሶ በእውነት አሳሳህኝና በደራሲው የተዘጋጀው “የገጠር ልጅ” የተሰኘው ፊልም ነገ ከቀኑ 11፡30 በብሔራዊ ቲያትር በሚካሄድ ሥነ ስርአት ይመረቃል፡፡ ቤተሰቦቿን ለመርዳት ወደ አረብ አገር በስደት ሄዳ ወደ ሀገሯ የተመለሰች አንዲት ወጣት የሚደርስባትንና የሚያጋጥማትን አሳዛኝ የህይወት ፈተና የሚያሳየው ልብ አንጠልጣይ ፊልም ሙሉ ቀረፃው የተካሄደው በአዲስ አበባ ከተማና ሰንዳፋ አካባቢ መሆኑን የፊልሙ ፕሮዲዩሰሮች ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ በፊልሙ ላይ ተሻለ ወርቁንና ሰለሞን ሙሔን ጨምሮ ከ90 በላይ ወጣትና አንጋፋ ተዋንያን የተሳተፉበት መሆኑ ተገልጿል፡፡

በደራሲ ቃልኪዳን ኃይሉ የተፃፈውና “ለምን አትቆጣም?” የተባለው አዲስ መፅሐፍ ዛሬ ከቀኑ 10 ሰዓት በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል እንደሚመረቅ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር አስታውቋል፡፡

ከአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት ላይ በምትገኘው ሰንዳፋ ከተማ “ዋን ስቶፕ ሲኒማ” የተሰኘ ዘመናዊ ሲኒማ ቤት ባለፈው ሳምንት ተመርቆ አገልግሎት ጀመረ፡፡ ሲኒማ ቤቱ በ1.7 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባ ሲሆን ለከተማዋና ለአካባቢው ነዋሪዎች አማራጭ የመዝናኛ ማዕከል ይሆናልም ተብሏል፡፡ ሲኒማ ቤቱ እስከ 500 የሚደርሱ ተመልካቾችን የመያዝ አቅም እንዳለው ተገልጿል፡፡ በከተማው ከንቲባ አቶ ዘገዬ ካሳ የዛሬ ሳምንት ተመርቆ የተከፈተው ዋን ስቶፕ ሲኒማ፤ ለአገሪቱ የፊልም ኢንዱስትሪ እድገት የበኩሉን ድርሻ እንደሚያበረክት የድርጅቱ ባለቤት አቶ ዘላለም ተመስገን ተናግረዋል፡፡

Saturday, 24 January 2015 13:27

ሞኝ እንደነገሩት

ሞኝ እንደነገሩት
“ፍቅር ያሸንፋል” ስትለኝ አምኜህ
በጦርነት ሁሉ ልሰለፍ አብሬህ
ደብተሬን ቀድጄ
አድርቄ ወጥሬ ጋሻ ሰርቼበት
ብዕሬን ፈልፍዬ ጦር አስቀርጬበት
ጠላትን ወግቼ
ለፍቅር ደምቼ…
ካቀረቀርኩበት ቀና ብል የለህም
ያሸንፋል ባልከኝ አንተ አልተሸነፍክም
እኔ ነኝ ብቻዬን ፍልሚያውን አውጄ
ጦሬን አበጅቼ
እኔው ተማርኬ ራሴን የሰጠሁ
ሙሉው ጦርነቴን
ሙሉ መሸነፌን
ሙሉ መሰጠቴን
ያንተ ድርሻ ቢኖር ልቤን የሰወረው
“ፍቅር ያሸንፋል” ማለትህ ብቻ ነው፡፡
    (ከብሩክታዊት ጐሳዬ “ፆመኛ ፍቅር”
    የተሰኘ የግጥም መድበል የተወሰደ)

Saturday, 24 January 2015 13:24

ፀሎቴ

እንዳላዝን … እንዳልባባ
ለኔ ሲሉ፡- እያነቡ
የኔን ዕንባ
 እኔኑ
በኔው፡- ዕንባ
እያሉኝ እሹሩሩ … እሹሩሩ
ለኔ ሲሉ ፡- ሁልዜም እንደኖሩ
እስከዛሬም .. የሚኖሩ  
ነበሩ፡፡
እንዳላዝን … አባብለውኝ
እንዳልስቅም ፡- አዝነውልኝ
ከርቱዕ አንደበታቸው
ዕንባዬ ፈሶ ከዕንባቸው
ለኔ ብለው
እውነት ለኔ ብለው
የኔን ቁስል ቆስለውልኝ
የኔን ህልም ታመውልኝ፣ ታመውልኝ፡፡
ሞቴንም እንዳይሞቱልኝ
ፀሎት ላይ ነኝ
ለኔ ሲሉ፡- ያልሆኑትን እንዳይሆኑልኝ
(1994 ዲላ)

Saturday, 24 January 2015 12:51

የፖለቲካ ጥግ

ፖለቲካ፤ ለፖለቲከኞች ሊተው የማይችል ትልቅ ቁምነገር ነው     ወደሚል ድምዳሜ ደርሻለሁ፡፡
ቻርልስ ደጐል
* በዲሞክራሲ ሥርዓት አንደኛው ፓርቲ ሁልጊዜ ዋና ጉልበቱን     የሚያውለው ሌላኛው ፓርቲ አገር ለመምራት ብቁ አለመሆኑን     ለማረጋገጥ በመሞከር ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ሁለቱም ይሳካላቸዋል፡፡ ደግሞም     ትክክል ናቸው፡፡
ኤች ኤል ሜንኬን
* ዲሞክራሲ በመጠኑ የምትጠላውን     እጩ እንድትመርጥ የሚፈቅድልህ ሥርዓት ነው፡፡
ሮበርት ባይርኔ
* ፖለቲከኞችና ዲያፐር (የሽንት ሁለቱም በተመሳሳይ ምክንያት በየጊዜው መለወጥ አለባቸው፡፡
ያልታወቀ ፀሐፊ
* ፖለቲከኛ ነገ፣ በሚቀጥለውሳምንት፣ በሚቀጥለው   ወር፣ በሚቀጥለው ዓመት የሚከሰተውን ነገር የመተንበይ ችሎታ ያስፈልገዋል፡ከዚያም በኋላ ያልተከሰተበትን ምክንያት የማስረዳት ችሎታ ሊኖረው ይገባል፡፡
ዊንስተን ቸርችል
* የፖለቲካ ቀልድ ችግሩ፣ የቀለድንባቸው ፖለቲከኞች መመረጣቸው ነው፡፡
ያልታወቀ ግለሰብ
* ፖለቲካ፤ ውሳኔዎች አስፈላጊነታቸው እስኪያበቃ ድረስ የማቆየት ጥበብ     ነው፡፡
ሔንሪ ኪውይሌ
* ልታሳምናቸው ካልቻልክ አደናግራቸው፡፡
ሃሪ ኤስ ትሩማን
* ሰላማዊ ትግል እውን እንዳይሆን የሚያሰናክሉ፣ የትጥቅ ትግልን አይቀሬ ያደርጉታል፡፡
ጆን ኤፍ ኬኔዲ
* ፖለቲካ እጅግ ውድ እየሆነ ከመምጣቱ የተነሳ ለመሸነፍ እንኳን ብዙ ገንዘብ ይፈልጋል፡፡
ዊል ሮጀርስ

Saturday, 24 January 2015 12:47

አስገራሚ የቃላት ፍቺዎች

ተሞክሮ
 ሰዎች ለስህተታቸው የሚሰጡት ስም
አቶሚክ ቦምብ
 ሁሉንም ፈጠራዎች የሚያወድም ፈጠራ
አድርባይ
ድንገት ወንዝ ውስጥ ቢገባ ገላውን መታጠብ የሚጀምር ሰው
ወንጀለኛ  
ከመያዙ በቀር ከሌላው ሰው የማይለይ
ሃኪም
 በሽታህን በክኒን ገድሎልህ፣ አንተን በክፍያ የሚገድልህ ሰው
አለቃ
 ስትዘገይ ቀድሞህ የሚገባ፣ ስትቀድም የሚዘገይ
ኮሚቴ  
በግላቸው ምንም መስራት የማይችሉ ሰዎች በጋራ ምንም መስራት እንደማይቻል ለመወሰን በአንድ ላይ የሚቀመጡበት
ክላሲክ
ሰዎች የሚያወድሱት ግን የማያነቡት መፅሃፍ
የጉባኤ አዳራሽ
 ሁሉም ሰው የሚናገርበት፣ ማንም የማያዳምጥበትና በመጨረሻም ሁሉም የማይስማሙበት ስፍራ
ተስፈኛ
 ከአይፍል ማማ ላይ እየወደቀ ሳለ መሃል ላይ “አያችሁ ገና አልተጎዳሁም” የሚል ሰው
ስስታም
ሃብታም ሆኖ ለመሞት በድህነት የሚማቅቅ ሰው
ፈላስፋ
ሲሞት እንዲወራለት በህይወት ሳለ ራሱን የሚያሰቃይ ጅል
ወዘተ
ሌሎች በትክክል ከምታውቀው በላይ ታውቃለህ ብለው እንዲያምኑ ማድረጊያ ዘዴ

Saturday, 24 January 2015 12:44

የአዘቦት ቀን ጀግኖች

የ14 ዓመቱ ኮሊን ስሚዝ በደረሰበት የመኪና አደጋ መላ ሰውነቱ በድን (ፓላራይዝድ) ከሆነ በኋላ ሃኪሞች የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን የማጠናቀቅ ዕድሉ 20 በመቶ እንደሆነ አርድተውት ነበር፡፡ ኮሌጅ ገብቶ መማርማ እርሳው ነበር ያሉት፡፡ ሆኖም ከ8 ዓመት በኋላ ቢኤ ድግሪውን በኮሙኒኬሽን ከሃይ ፖይንት ዩኒቨርስቲ ለማግኘት ቻለ፡፡ ኮሊን ፈጽሞ የማይታሰበውን ማሳካት የቻለው በዕድሜ 50 ዓመት በሚበልጡትና ጨርሶ በማያቃቸው ደግ አዛውንት እርዳታ ነበር፡፡
እ.ኤ.አ በ2005 ዓ.ም እንዳጋጣሚ ሆኖ ጡረተኛው ኧርነስት ግሪኒና ባለቤታቸው ካትሪን፣ ኮሊንስና ወላጆቹ በሚያመልኩበት በኖርዝ ካሮሊና በሚገኘው የአሼቦሮ ባፕቲስት ቤ/ክርስቲያን ያመልኩ ነበር፡፡ በእርግጥ እኒህ ቤተሰቦች ትውውቅ አልነበራቸውም፡፡ ምክንያቱም የግሪን ቤተሰብ ወደ አካባቢው ከመጣ ዘጠኝ ወር ያህል ቢሆነው ነው፡፡ ሆኖም ኧርነስት በወሬ ወሬ ኮሊን ስለደረሰበት አደጋና ወላጆቹ የሙሉ ጊዜ እንክብካቤ ሊያደርጉለት አለመቻላቸውን ሰሙ፡፡ ይሄ ለእሳቸው የተላከ ጥሪ መስሎ ታያቸው፡፡
“ፈጣሪ እንድረዳው መራኝ” ይላሉ - ኧርነስት ግሪኒ፡፡ እናም በነበራቸው ትርፍ ጊዜ ኮሊንስን ሊረዱት ቆርጠው ተነሱ፡፡
መጀመሪያ የኮሊንን ቤተሰብ በመቅረብ፣ እነሱ ወደ ሥራ በሚሄዱ ወቅት ልጃቸውን ለመንከባከብ ፈቃደኛ መሆናቸውን ተናገሩ፡፡ የኮሊን ወላጆች አላቅማሙም፡፡ እርዳታውን በደስታ ተቀበሉ፡፡ አሁን 23ኛ ዓመት እድሜው ላይ የሚገኘው ኮሊን፤ እንዴት ጨርሶ የማላውቀው ሰው እኔን ለመርዳት መላ ህይወቱን እርግፍ አድርጐ እንደተወ ልረዳ አልቻልኩም ነበር ብሏል፡፡
አዛውንቱ ኧርነስት በቀጥታ ወደ እርዳታ አልገቡም፡፡ መጀመሪያ ለኮሊን እንዴት እርዳታ ማድረግ እንደሚችሉ መጠነኛ ስልጠና ወሰዱ፡፡ ከዚያም ወላጆቹ የሥራ ቀናቸውን በሚጀምሩበት አንድ ሰኞ ማለዳ ላይ እነኮሊን ቤት ከተፍ አሉ፡፡ ኮሊንን ከአልጋ ሲነሳ፣ ሲለባብስና ሲተጣጠብ ያግዙትም ጀመር፡፡ ቁርሱንም ሲመገብ እንዲሁ ይረዱታል፡፡ ከዚህም በላይ በራሳቸው መኪና ት/ቤት ያደርሱታል፡፡ በየቀኑ 9 ሰዓት ላይ ደግሞ ወደ ቤት ይመልሱታል፡፡ ወላጆቹ ከስራ እስኪመለሱም ወይ እሳቸው አሊያም ባለቤታቸው እያጫወቱ ይጠብቁታል፡፡
በዚያ ሰዓት ውስጥ ከኮሊን ጋር ብዙ ያወጉ እንደነበር ኧርነስት ያስታውሳሉ፡፡ መጀመሪያ ላይ በመሃላቸው የነበረው የዕድሜ ልዩነት ፈተና ሆኖባቸው እንደነበር አልሸሸጉም፡፡ በሁለት ትውልዶች መካከል የሚከሰት ልዩነት ነበር፡፡ ለምሳሌ አንዳቸው ራፕ ሲወዱ ሌላኛቸው ምርጫቸው አልነበረም፡፡ ነገር ግን ተቻችሎ መኖርን ተማሩ፡፡
“አዛውንቶች ዕድሜያቸው የገፋ እኛ ማለት ናቸው” የሚለው ኮሊን፤ “ድንቅ ታሪክ ያላቸው የእኛው ዓይነት ሰዎች” ሲል ይገልፃቸዋል፡፡
አንዳንድ ቀናት ከሌሎቹ የተሻሉ ነበሩ፡፡ “ምንም ነገር ራሱን ችሎ ማከናወን ስለማይችል ብዙ ሊያደክም ይችላል” ይላሉ ኧርነስት፡፡ ነገር ግን ፈታኝ ጊዜያትን ለማለፍ ያስቻለው የራሱ የኮሊን ጠንካራ ቁርጠኝነት መሆኑን ኧርነስት ይመሰክራሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ ኮሊን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ከቀሩት የክፍል ጓደኞቹ ጋር በአጥጋቢ ውጤት አጠናቆ በአቅራቢያቸው በሚገኘው ሃይ ፓይንት ዩኒቨርስቲ ለመግባት ቻለ፡፡ በእያንዳንዱ የትምህርት ክፍለ ጊዜ ኧርነስት ከአጠገቡ አይለዩም ነበር፡፡ “የመጀመሪያው ዓመት አስደሳች ነበር” ሲሉ ያስታውሳሉ - ኧርነስት፡፡ “ኮሊን ከሌላው ጐልቶ መታየት አይፈልግም ነበር” ግን ደግሞ ያገኘውን ዕድል በአግባቡ ይጠቀም ነበር - አስተማሪ ሲያስተምር ማስታወሻ ይይዛል፤ ብዙ ጊዜም ክፍል ውስጥ አስተያየት ይሰጥ ነበር፡፡
በምረቃ ቀን ታዲያ ኮሊን ብቻ አልነበረም ዲግሪውን የተቀበለው፡፡ አዛውንቱ ኧርነስትም ላከናወኑት ሰብዓዊ ተግባር ዩኒቨርሲቲው የክብር ዲግሪ ሰጥቷቸዋል፡፡ ያልጠበቁት ስለነበር ትንግርት እንደሆነባቸው ይናገራሉ፡፡
ኮሊን ግን ጨርሶ አልተገረመም፡፡ “ኧርነስት ሰው እንዴት መኖር እንዳለበት መለኮታዊ ምሳሌ የሚሆኑ ሰው ናቸው - ዝምተኛና ትሁት” በማለት ይገልፃቸዋል፡፡
ኮሊን ዛሬ በዚያው ሃይ ፖይንት ዩኒቨርሲቲ፣ የቅርጫት ኳስ ረዳት አሰልጣኝ ሲሆን ዕውቅና በተሰጠው ልዩ የእንክብካቤ ባለሙያ በየቀኑ ድጋፍ ያገኛል፡፡ አዛውንቱ ኧርነስትም አብዛኛውን ጊዜያቸውን ከቤተሰባቸው ጋር ያሳልፋሉ፡፡
አሁን ሁለቱ የተለያየ ትውልድ ጓደኛሞች እምብዛም አይገናኙም፡፡ “ነገር ግን ኮሊንና እኔ ሁልጊዜም ግንኙነታችን ይቀጥላል” ይላሉ - ኧርነስት፡፡ ኮሊንም በዚህ ይስማማል፡፡ “በቀን ከ14-16 ሰዓታት አንድ ላይ ነበር የምናሳልፈው” ሲል ያስታውሳል፡፡ ማሳለፍ ብቻ ሳይሆን አስቸጋሪ ፈተናን በጋራ ተወጥተዋል፡፡ ለዚያም ነው የአዘቦት ቀን ጀግኖች የሚባሉት፡፡
(ሪደር ዳይጀስት - የፌብሯሪ 2015 እትም)

እንዴት ከረማችሁሳ!
በዓላቱ በሰላም አለፉ! በበዓላት ቀናት የሚታይብንን ፈገግታና ደስታ ለሁለም ቀናት ያድርግልንማ!
ስሙኝማ…ህዝቤ ይገለብጠው የለ እንዴ! መቼም ‘አንደኛ’ የምንወጣባቸው ነገሮች እየበዙ አይደል…ከዚህ በፊት እንዳወራነው ትንሽ ቆይቶ በ‘ሲፑም’ ዓለምን ባናስከነዳ ምን አለ በሉኝ፡፡ (“ልጆቼን የማበላው አጣሁ፡፡ ወር ላይ የምመልስልህ አንድ ሁለት መቶ ብር አበድረኝ…” የሚለው ሰው አዲስ ‘ብራንድ’ ቢራ በመጣ ቁጥር “…ተጋፍቶ የሚጠጣው ከየት አምጥቶ ነው!” ምናምን አይነት ጥያቄ መጠየቅ ትተናል፡፡ ልክ ነዋ…አይደለም እኛ ሳይንስም እኮ ገና ያልደረሰባቸው ብዙ ነገሮች አሉ!)
ይቺ ከተማ እኮ እንደ ድሮ በልደታና በአቦ ሳይሆን…ወሩን ሁሉ ‘ሲፕ’ ቤቶቹ ጢም እያሉ የሚጠጣባት ከተማ ሆናለች!
ስሙኝማ…መቼም ‘የቢራዎች ፍልሚያ’ እየተጧጧፈ ነው፡፡ (ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ምን አለ በሉኝ የቢራ ዋጋ ‘እንደዛኛው ዘመን’ በጠርሙስ ብር ከስሙኒ ምናምን ባይገባ፡፡ አሀ…እነኚህ አዳዲስ የሚባሉት ፋብሪካዎች ሁሉ ገበያ ሲገቡ እንዴት አድርገን ነው ያንን ሁሉ ጠጥተን የምንጨርሰው!)
አሁን፣ አሁን አብዛኞቹ ዝግጅቶች ስፖንሰር የሚደረጉትና፣ በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ የሚተላለፉት አብዛኞቹ ማስታወቂያዎች የቢራዎቹ ናቸው፡፡ እሰይ… እንኳንም ኪነ ጥበባዊ ዝግጅቶችን እንደዚሀ ስፖንሰር የሚያደርጉ ድርጅቶች በዙልንማ! ግን አንዳንድ ጊዜ ነገሮች ሲበዙ… አለ አይደል…እነኚህ ነገሮች በአእምሮ ያልበሰሉት ላይ ሊፈጥሩ የሚችሉ ነገሮች ያሳስባችኋል፡፡ አለ አይደል… ‘ቢራ መጠጣት’ አይነት ነገሮች ‘የደስታ ጥግ’ ተደርገው ሲቀርቡ ዕድሜያቸው ያልደረሱ ህጻናት አእምሮ ላይ የተሳሰቱ መደምደሚያዎች እንዳይፈጥሩ የማስታወቂያዎቹ አቀራረብ ይታሰብባቸውማ! ስልጣኔያችን በዝቶ  የሰማንያ ምናምን ዓመት አያትም፣ የዘጠኝ ዓመት የልጅ ልጅም እኩል ቁጭ ብለው እስከ እኩለ ሌሊት ቴሌቪዥን የሚያዩባት አገር መሆኗ አይረሳማ፡፡
እኔ የምለው…የቢራን ነገር ካነሳን አይቀር… ‘ከ18 ዓመት በታች የማይሸጥ’ የሚለው የሆነ ነገር የሚጎድለው አይመስላችሁም! አለ አይደል…ማተኮር ያለበት ከ18 ዓመት በታች ያሉ ታዳጊዎች… እነሱ ገዙትም ማንም ገዛው ‘መጠጣት እንደማይችሉ’ ነው፡፡ እናላችሁ…በዚህ በበዓላት ሰሞን በከተማው ብዙ ቦታዎች ያያነው ነገር ቢኖር አሥራዎቹን ያላገመሱ ልጆች ተሰብስበው ሲጠጡ ነው…ያውም አላፊ አግዳሚው እያያቸው! በቀደም ሰብሰብ ብለው ‘የሎዋን ሲገጩ’ ያየናቸው ታዳጊዎች… አለ አይደል… የሁሉም ታላቅ የሆነችው አሥራ አምስት ዓመት ቢሆናት ነው፡፡
እኔ የምለው…የዘንድሮ ወላጅ…አለ አይደል…የሆነ ‘ፈርስት አሜንድመንት’ ምናምን ነገር ያለው ይመስላል፡፡ የልጆቻቸውን ነፃነት ምናምን የሚገድብ ህግ ‘ማውጣት’ አይችሉማ! ቂ…ቂ…ቂ…
የምር ግን…አለ አይደል…ዘንድሮ በርከት ያሉ ወላጆች በልጆቻቸው አስተዳደግ ላይ ያላቸው አዎንታዊ ተሳትፎ እየቀነሰ ነው ይባላል፡፡ በቃ… የሚበሉትና የሚጠጡት ካቀረቡላቸው፣ ካሽቀረቀሯቸው፣ ለፈለጉት ነገር ሁሉ ገንዘብ ከሰጧቸው የወላጅነት ግዴታቸውንና ኃላፊነታቸውን የተወጡ ይመስላቸዋል፡፡
ስሙኝማ…የተሳትፎ ነገር ካነሳን አይቀር…“በስፖርት ዋናው ነገር መሳተፉ ነው”… የምትባል ነገር አለች፡፡ ይሄ እንግዲህ ያኔ ስፖርት ፈረንካ በማያመጣበት ዘመን ነው፡፡ ዘንድሮ…ልጄ…ያውም በጦቢያ ኳስ… “እከሌ አንድ ሚሊዮን ሦስት መቶ ሺህ ብር ተሸጠ…” የሚባልበት ዘመን ደረስን አይደል! (እንትና… እስቲ የእግር ኳስ ‘ኤጀንትነት’ ምናምን ሞክርማ፡፡ “ምናለ አንድዬ እንደው አንድ ጊዜ ገንዘቡን ዝርግፍ ቢያደርግልኝ…” ስትል የከረምከው ሊሳካልህ ይችላላ!)
ስሙኝማ…የእግር ኳስ ነገር ከተነሳ አንድ ግርም የሚለኝ ነገር አለ…እግር ኳስ ተጫዋቾች ሜዳ ሲገቡ ሲጸልዩ ታዩዋቸዋላችሁ፡፡ የምር…‘ለውሳኔ’ እኮ አስቸጋሪ ነው፡፡ አሀ…ሁሉም… “ዛሬማ ጉድ አታደርገኝም!” እያለ የሚገባ ከሆነ ለማን ‘ሊፈረድ’ ነው፡፡
ኮሚኩ ነገር ምን መሰላችሁ… ገና ሜዳ ሲገባ አራት፣ አምስት ጊዜ የሚያማትበው ተጫዋች ሀያ ደቂቃ ሳይሞላ የተጋጣሚውን ተጫዋች እግር ‘ቀልጥሞ’ ቀይ ካርዱን ይከናነባል፡፡ እኔ የምለው…“እንደው ደህና አድርጌ የምቀለጥመው እግር አመቻችትሀ አቅርብልኝ…” ብለው ነው እንዴ የሚለማመኑት!
እናላችሁ…ኮሚክ ነገር እኮ ነው…ስንኮርጅ እንኳን አያምርብንም፡፡ ‘ሰለጠኑ’ ብለን እየኮረጅናቸው ያሉ አገሮች እኮ ወጣቶቻቸውን ለመከላከል መአት ‘መጠበቂያ’ ህጎች አሏቸው፡፡ ህጎች በወረቀት የሰፈሩ ብቻ ሳይሆኑ በተግባርም የሚፈፀሙ ናቸው፡፡ “አሥራ ስምንት ዓመት ላልሞላቸው ታዳጊዎች መጠጥ አቅርበሀል…” ተብሎ የተጠየቀ ሰው አለ!  “ዕድሜሀ ሳይደርስ መጠጥ ስትጠጣ ተደርሶብሀል…” ተብሎ የተጠየቀ ታዳጊ አለ!
እናላችሁ…የአሥራ አምስት ዓመት ህጻናት የአስተማሪዎቻቸውን ‘የበጀት ጉድለት የሚሞሉባት’ አገር እየሆነች ነው፡፡
ለሁሉም ወላጆች በዓለም ቆንጆዎቹ ልጆች የእነሱ ልጆች ብቻ ናቸው፡፡ እናማ…የሚያጠፉት ይወደድላቸዋል፡፡ የሌላ ሰው ልጅ ሲያጠፋ ግን... አለ አይደል… “ምናለ ቢቆነጥጡት! ምናምን ይባላል፡፡ የራሳቸው ልጆች ሲያጠፉ ግን...“ቢያጠፋስ ምናለበት፣ ልጅ አይደለም እንዴ…” ምናምን ይባላል፡፡ እናማ…ዘንድሮ ነገሮችን የእኛ ልጆች ሲፈጽሟቸውና የሌሎች ልጆች ሲፈጽሟቸው የሚሰጣቸው ትርጉሞች የተለያዩ  ናቸው፡፡
ክብርና ምስጋና ልጆቻቸውን በተገቢው ስነ ስርአት ላሳደጉና ለሚያሳድጉ ወላጆች!
ስሙኝማ…መቼም በምንም ባህል ስለ አማቶች መአት ነገር ይባላል፡፡ እንደውም ከብዙ ትዳሮች መፍረስ ጀርባ ‘የአማቶች እጅ’ አለበት ይባላል፡፡ ባህር ማዶ ያሉት ወገኖቻችን ግን ከአማቶች ጋር ፍቅር የያዛቸው ነው የሚመስለው፡፡ ልክ ነዋ…ስንትና ስንት እናቶች ወልድው፣ አሳድገው፣ “ያውልህ ውሰዳት…” ብለው ሰጥተው በማረፊያቸው ጊዜ እንደገና የልጅ ልጅ “አሳድጉ…” እየተባሉ አይደል እንዴ የሚሄዱት!
የአማቶች ነገር ከተነሳ ይቺን ስሙኝማ…
ሰውየው ለጓደኛው እያማከረው ነው፡፡
“እባክህ ጭንቀት ይዞኛል፡፡”
“ምነው፣ ደህና አይደለህም እንዴ!”
“እኛ በሌለንበት አማቴን ጠላፊዎች ወሰዷት፡፡ 30,000 ዶላር ክፈሉ አሉን፡፡”
“አሀ… 30,000 ዶላር ከየት አመጣለሁ ብለህ ነው የተጨነክኸው!”
“እሱ አይደለም ያስጨነቀኝ፡፡”
“ታዲያ ምንድነው?”
“ገንዘቡን ካልከፈላችሁ መልሰን ቤት እናመጣታለን ስላሉኝ ነው፡፡”
አሪፍ አይደል! ስለ አማቶች ጭማሪ…
ባል ሆዬ ከሚስቱ ተጣልቶ ለጓደኛው እያማከረው ነው፡፡ “እናቴ ቤት እሄዳለሁ አለችኝ፡፡ እኔም… ዛቻ ነው፣ ቃል መግባትሽ ነው ብዬ ጠየቅኋት፣” ይለዋል፡፡ ጓደኝየውም “ምን ልዩነት አለው?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ባል ሆዬ ምን ቢል ጥሩ ነው… “ወደ እናቷ ተመልሳ የምትሄድ ከሆነ ይህ ቃል መግባት ማለት ነው፡፡ እናቷን እኛ ቤት የምታመጣ ከሆነ ግን ዛቻ ነው…”  አለና አረፈው፡፡
የአማቶች መብት አስጠባቂ ማህበር ነገር ይቋቋምልንማ!
እናላችሁ…ስለ ልጆች አስተዳደግ የምር መታሰብ ያለበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ ስለ ልጆቹ መጻኢ ህይወትና ስለነገው ህብረተሰብም ማሰቡ መልካም ነው፡፡ ልጆችን የሚያሳስቱ ነገሮች እየተበራከቱ ባሉበት ሰዓት ወላጆች ከልጆቻቸው ትንሽ ሻል ብለው ማሰብ የሚኖርባቸው አይመስላችሁም!
ይቺን ስሙኝማ…ህጻናት ወንድምና እህት እየተጫወቱ ነው፡፡ እናማ… እህትየው ብቻ ነች የምትጮኸው፡፡ ወንድሟ ምንም ነገር አይተነፍስም፡፡ እናትየውም… “ማሚቱ፣ አንቺ ብቻ ለምን ትጮሂያለሽ! እሱም አንዳንዴ ይናገር እንጂ…” ትላታለች፡፡ ህጻኗ ምን ብትል ጥሩ ነው… “እኔ አንቺ ነኝ፣ እሱ ደግሞ አባዬ ነው…”  ብላት አረፈች፡፡ በቃ ለእሷ የእናት ሥራ አባት ላይ መጮህ፣ የአባት ሥራ ደግሞ ዝም ብሎ ማዳመጥ ሆኗላ! አባት እኮ ዝም ብሎ የሚያዳምጥ እያስመሰለ በሆዱ ይሄኔ ስንትና ስንት እርግማን አውርዶባታል! “እኔ ሚስት አገባሁ ብዬ… ለካስ ያገባሁት ምላስና ሰንበር ነው!” ብሎ ሊሆን ይችላል፡፡ ቂ…ቂ…ቂ….
እኔ የምለው…“አጅሬ፣ እያስመሰልክ የልብህን ትናገራለህ!” ያላችሁኝ ወዳጆቼ…አልገባኝም፡፡ እንዴት ነው ነገሩ…“እንደ ሰዉ አንተም ታስመስላለህ…” “አስመሳይ ነህ…” ምናምን እያላችሁኝ ከሆነ… አለ አይደል…እስቲ ‘ስታተሴን’ መለስ ብዬ አየዋለሁ፡፡ ቂ…ቂ…ቂ… ወይ ‘ማስመሰል!’
እናማ…ልጆች ወደተሳሳተ መንገድ ከመሄድ የሚጠብቃቸው ህጎች በተግባር ላይ ይዋሉማ! “ከአሥራ ስምንት ዓመት በታች የተከለከለ…” የሚሉ አይነት ህጎች ‘ባዶ ቃላት’ መሆናቸው ቢበቃ አሪፍ ነው፡፡
ደህና ሰንብቱልኝማ!