Administrator

Administrator

- በብጥብጡ ከ70 በላይ ሰዎች ሞተዋል
ከሁለት አመታት በፊት አልማስሪ እና አልሃሊ በተባሉት የግብጽ እግር ኳስ ቡድኖች ደጋፊዎች መካከል በፖርት ሲቲ ስቴዲየም የተከሰተውንና ከ70 በላይ ሰዎች የሞቱበትን ብጥብጥ በማነሳሳት የተከሰሱ 11 ግብጻውያን የሞት ቅጣት እንደተጣለባቸው ሲ ኤንኤን ዘገበ፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በካይሮ የተሰየመው ችሎት በግብጽ የእግር ኳስ ታሪክ አስከፊው የተባለለትንና ህጻናትን ጨምሮ ለህልፈተ ህይወት የተዳረጉበትን ይህን ብጥብጥ በማነሳሳታቸው የሞት ቅጣት ከጣለባቸው ከእነዚሁ 11 ግለሰቦች በተጨማሪ፣ በብጥብጡ ተሳትፈዋል ባላቸው ሌሎች 40 ሰዎች ላይም የእስር ቅጣት ጥሏል፡፡
ተመልካቾቹ እርስበርስ በድንጋይ፣ በካራና በገጀራ በአስከፊ ሁኔታ የተጨፋጨፉበት ይህ ከፍተኛ ብጥብጥ መከሰቱን ተከትሎ፣ ግብጽ የእግር ኳስ ደጋፊዎች ስታዲየም እንዳይገቡ እገዳ መጣሏንና ጨዋታዎች በዝግ ስቴዲየም ሲከናወኑ መቆየታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ በሂደትም የተወሰነ ቁጥር ያላቸው ተመልካቾች ብቻ ወደ ስቴዲየም እንዲገቡ መፈቀዱን ገልጧል፡፡
በግብጽ ከዚያ በኋላም የእግር ኳስ ደጋፊዎች ብጥብጥ መከሰቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው የካቲት ወር ላይም የዛማሌክ እግር ኳስ ክለብ ደጋፊዎች ባስነሱት ብጥብጥ 19 ሰዎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን አክሎ ጠቁሟል፡፡

      ከትናንት በስቲያ በድምቀተ የተከፈተው 3ኛው ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2007 የሆስፒታሊቲ ቱሪዝም ፎረምና ኤክስፖ ነገ ይዘጋል ሲሉ የኦዚ ቢዝነስና ሆስፒታሊቲ ግሩፕ መስራችና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አስታወቁ፡፡
ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ አቶ ቁምነገር ተከተል በተለይ ለጋዜጣው ሪፖርተር በሰጡት መግለጫ፤ ነገ ለአካባቢ ጥበቃ የሚቆረቆሩና የሚጨነቁ ሆቴሎች ተወዳድረው አሸናፊውን በመሸለም የንግድ ትርኢትና ኤክስፖው ይዘጋል ብለዋል፡፡
ለሦስተኛ ጊዜ ከሰኔ 4 ጀምሮ በሚሊኒየም አዳራሽ ሲካሄድ የቆየው የንግድ ትርኢትና ኤክስፖ  ዓላማ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው፣ በአፍሪካ ታዋቂ የሆነና በኢትዮጵያዊ ባህላዊ መሠረት ላይ የተገነባ የሆስፒታሊቲና የቱሪዝም መድረክ መፍጠር ነው ያሉት አቶ ቁምነገር፤ ባለድርሻ አካላት መድረክ ፈጥረው በዓለም አቀፍ መስፈርት መሰረት በአገር ውስጥ የሚታዩ ኢንዱስትሪ ነክ ጉዳዮችን ለመዳሰስ፣ አዳዲስ አሰራሮችን ለመጋራትና ለልምድ ልውውጥ አመቺ ሁኔታ መፍጠር እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በ3ኛው ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ ከኢጣሊያ፣ ፈረንሳይ፣ ዩ.ኤስ.ኤ፣ ታይላንድ፣ ቱርክ ደቡብ አፍሪካ፣ ግብፅ፣ ዱባይና ቻይና የመጡ 145 አዳዲስ የቴክኖሎጂ ውጤቶች፣ የቢዝነስ ሀሳቦች (አይዲያ) የያዙና የገበያ አፈላላጊ ኩባያዎች እየተሳተፉ እንደሆነ ታውቋል፡፡
በንግድ ትርኢትና ኤክስፖው ላይ ሁለት ጥናታዊ ጽሁፎች እንደሚቀርብ የጠቀሱት ማኔጂንግ ማናጀሩ፣ ትናንት ቤልጂየማዊው የ “ሄድ ኳተር ማጋዚን” ማኔጂንግ ዳይሬክተር፣ የኢትዮጵያን የሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪ ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገር በሚል ርዕስ ጥናታዊ ፅሑፍ ማቅረባቸውን፣ ዛሬ ደግሞ ደቡብ አፍሪካዊው የቢዝነስ ቱሪዝም  ኩባንያ ፕሬዚዳንት፤ የኢትዮጵያ የስብሰባ የኢንሼዬንቲቭ፤ (ኮንፈረንስ፣ ኤግዚቢሽን ወይም ኤቨንት) እምቅ የቱሪዝም ገበያ ዕድሎችና አጠቃቀማቸው በሚል ርዕስ ጽሑፍ ያቀርባሉ፡፡ እስካሁን በኢትዮጵያ ስብሰባዎች የሚካሄዱት በመንግስት አዘጋጅነት ብቻ ሳይሆን ቢዝነሱ ራሱ ወደ ኢትዮጵያ መምጣት እንዳለበት ጠቅሰው፤ ለምሳሌ ቢልጌት 2 ሚሊዮን ዶላር መድቦ በኤድስ ላይ ዓለም አቀፍ ጉባኤ እንዲያዘጋጅ ዕድሉ ለግል ኮንፈረንስ አዘጋጅ ድርጅቶች ቢሰጥ፣ የአዘጋጅቱን ኃላፊነት የወሰደው ድርጅት በኤድስ በብዛት የተጎዳችው አፍሪካ ስለሆነች ስብሰባውን በአፍሪካ ለማድረግ ወስኖ በየትኛዋ አገር ይካሄድ? ብሎ ሲፈልግ፣ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ኮንፈረንስ ማዘጋጀት እንደምትችል ታውቆ ከቢዝነሱ የሚገኘው ገቢ (ማይስ MICE) መጠቀም በምትችልበት አሰራር ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀርባሉ ብለዋል፡፡  የንግድ ትርኢቱና ኤክስፖው በተከፈተበት ሥነ-ሥርዓት በሚቀጥለው ዓመት በመጋቢት ወር ስራ የሚጀምረው የስብሰባ፣ ኢንሴንቲቭ፣ ኮንፈረንስ (ኮንግረስ) ኤግዚቢሽን (ኢቨንት) አዘጋጅ ማይስ MICE ምሥራቅ አፍሪካ 2008 ፎረምና ኤክስፖ መቋቋሙን የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ሚኒስትር ክቡር ሬድዋን ሁሴንና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ተወካይ አቶ ተወልደ ወ/ማርያምን በመወከል አቶ ኢሳያስ ወ/ማርያም ይፋ አድርገዋል፡፡
ነገ ቨ3ኛው ሆቴል ሾው ኢትዮጵያ 2007 የንግድ ትርኢትና ኤክስፖ ከመዘጋቱ በፊት በተለያዩ ሆቴሎችና ሪዞርቶች መካከል የሙያ ውድድርና የልምድ ለውውጥ እንደሚካሄድ፣ እንዲሁም በዲዛይንና ግንባታ ወቅት ለአካባቢ ጥበቃ ክብካቤ ከፍተኛ ትኩረት በሰጡ ሆቴሎችና ሪዞርቶች መካከል ውድድር ተካሂዶ አሸናፊዎቹ እንደሚሸለሙ አቶ ቁምነገር ተከተል አስታውቀዋል፡፡  

ኮካኮላ ኢትዮጵያ ከተለያዩ የአዲስ አበባ ት/ቤቶች ከተውጣጡ 50 ታዳጊ ተማሪዎች ጋር “በራስ ለመተማመን ቢሊዮን ምክንያቶች አሉን” በሚል መርህ ባለፈው ረቡዕ በሻላ መናፈሻ ዘመቻ ጀመረ፡፡
“በራስ ለመተማመን ቢሊዮን ምክንያቶች” በሚል መሪ ቃል ኮካኮላ በመላው አፍሪካ የጀመረው ዘመቻ አካል ሲሆን ዓላማውም ወጣት አርቲስቶች የተለያዩ ችግሮችን አልፈው ለስኬት የበቁበትን ተሞክሮ ለታዳጊዎች በማካፈል የአህጉሩን ቀና አስተሳሰብና አስደናቂ ታሪኮች በመሰብሰብ፣ የአፍሪካን ልዩ ታሪኮች ለማክበር መንገድ መክፈት እንደሆነ የኮካኮላ ኢትዮጵያ ማናጀር ሚ/ር ኬንጐሪ ማቻሪያ ገልፀዋል፡፡
ድርጅቱ ከተለያዩ የሕይወት ዘርፎች አራት ተፅዕኖ ፈጣሪ አርቲስቶች ያጋጠሟቸውን ፈታኝ ችግሮች እንዴት አልፈው ለስኬት እንደበቁ ለኢትዮጵያ ታዳጊዎች እንዲያካፍሉ የመረጠ ሲሆን እነሱም በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ያተረፈችው ዲዛይነር ማኅሌት አፈወርቅ (ማፊ)፣ በኢትዮጵያ የሬጌ አልበም ያወጣው ስኬታማ ሙዚቀኛ ዮሐንስ በቀለ (ጆኒራጋ) ከፍተኛ እውቅና ካላቸው ሴት ዲጄዎች አንዷ የሆነችው የሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጅ ማርሼት ፍሰሐ (ዲጄ የሚ) እና አካል የሚያደክም በሽታ ቢኖርበትም በፅናት ተቋቁሞ ለስኬት የበቃውና በአነቃቂ ንግግሮቹ የሚታወቀው ሰዓሊ ብሩክ የሺጥላ ናቸው፡፡
በዝግጅቱ ወቅት ታዳጊዎች በተለያዩ ምድቦች ተከፋፍለው እንዲሁም በግለሰብ ደረጃ ከተፅዕኖ ፈጣሪዎቹ ዝነኞቹ ጋር ተነጋግረዋል፡፡ ይህም ታዳጊዎች ውጤታማ አርአያ ሞዴሎች ለማግኘት ልዩ ዕድል የፈጠረላቸው ከመሆኑም በላይ የሥራ ፈጠራ፣ ከባድ ሥራ፣ የሕይወት ተድላና ስኬት በቀላሉ እንደማይገኝ የሚያሳይ እውነታ ተምረውበታል ብለዋል የኮካኮላ ኃላፊ፡፡

Saturday, 13 June 2015 14:56

ልጅቷ የምን ተማሪ ነች?

       እግር ጥሎኝ ምሳ ልበላ አዲስ አበባ ውስጥ ወደሚገኝ ወደ አንድ ፋስት ፉድ ቤት ጎራ አልኩኝ። በረንዳው ላይ ልቀመጥ ፈለግሁኝ፡፡ ይሁንና ከአንድ አነስተኛ ጠረጴዛና አራት ኩርሲዎች በስተቀር ማስተናገድ የማትችለዋ በረንዳ በደንበኞች ተይዛለች፡፡ አማራጭ አልነበረኝምና ወደ ውስጥ ገባሀኝ፡፡
እየገባሁ ግን እንደልማዴ ሰዎቹን ገርመም አደረግኋቸው፡፡ ሁለት ወንዶችና አንዲት ሴት፡፡ ሕጻን ልጅም ይዘዋል፡፡ ዓይኔ ሴቷ ላይ ትንሽ ቆየ። ቀይ፣ ነጥብ እንኳን የሌለው ጥርት ያለ ፊት፡፡ ያለ ሊፕስቲክ እንዲሁ በተፈጥሮ የቀላ ቀጭን ከንፈር። 17-18-19 ቢሆናት ነው፡፡ ከኩርሲዎቹ በአንዱ ለይ ተቀምጣ፣ ግድግዳውን በመደገፍ፣ አንደኛውን እግሯን ማዶ ካለው የበረንዳው አጥር ላይ እንደ መስቀል አድርጋለች፡፡ ምቾት ፍለጋ እንጂ የቅምጥል አይደለም፡፡ “መለሎ መሆን አለባት፡፡ በዚያ ላይ የደረቷ ሙላት!” ስል ተደመምኩኝ፡፡  
ቤቱ ውስጥ የተወሰኑ ሰዎች አሉ፡፡ ልብ አላልኳቸውም፡፡ ፈጣኑ አስተናጋጅ ገና ከመቀመጤ ሜኑ ይዞ መጣ፡፡ ሜኑውን ማየት ሳያስፈልገኝ “ቺዝ በርገር፣” አልኩኝ፡፡
“የሚሄድ ነው ወይስ…” ጠየቀኝ ጎንበስ ለማለት እየሞከረ፡፡
“አይ፣ እዚሁ የሚበላ፣” ብዬ ሞባይሌን አወጣሁኝና ፌስ ቡክ ከፈትኩኝ፡፡ ምንም አዲስ ነገር የለም፡፡ “አክቲቭ ፍሬንድስ” ላይ ተጫንኩኝ። የተለመዱ ሰዎች እንደተጣዱ ናቸው፡፡ ትቼ ወጣሁኝ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ለምን ፌስ ቡክ ውስጥ ዘልዬ እንደምገባ አላውቅም፡፡ “ምን ለማግኘት? ምን ለመጠቀም? በከንቱ ጊዜና ገንዘቤን በ 3ጅብ ለማስበላት?! እንድያው ምን ባደርግ ይሻለኛል?”
ድንገተኛ ዝናብ ካዘዝኩት ምግብ ጋር እኩል መጣ፡፡ “እንኳንም ውስጥ ገባሁኝ፡፡” በረንዳው ላይ የነበሩ ሰዎች ፒዛቸውን እንደያዙ ገቡና ከፊት ለፊቴ ያለውን አነስተኛ ጠረጴዛ ከበው ሰፈሩ፡፡ ልጅቷና አንደኛው ሰውዬ ጀርባቸውን ሰጥተዉኝ ተቀመጡ። ያኛው ሰውዬ ህጻኗን እቅፍ አድርጓት ከፊት ለፊት ለፊታቸው ተቀመጠ፡፡ አባቷ ሳይሆን አይቀርም፡፡ በጣም ይመሳሰላሉ፡፡
“ይሄኛውስ ሰውዬ ለዚህችኛዋ ቆንጆ ምኗ ይሆን?” ስል አሰብኩኝ፡፡ “መቼም ጓደኛዋ አይሆንም፤ ምክንያቱም ሰፊ የእድሜ ልዩነት ይታየኛል፡፡ የሱ ቢያንስ የሷ ሲባዛ ሁለት ሲደመር አንድ ይሆናል፡፡ … እንዴ፣ እኔ ምን አገባኝ…? ለምን ባሏ አይሆንም? …. ደግሞስ ፍቅርን ዕድሜ  ይወስናል ያለው ማን ነው? ጀኒፈር ሎፔዝ በ42 ዓመቷ የ18 ዓመት ወጣት “ጠብሳ” አልነበረም እንዴ? እኛስ ጎረቤት ጋሽ አህመድ አዲሷን ሚስታቸውን በ41 ዓመት ይበልጧት የለምን? ማን ናቸው ባላምባራስ….” እያልኩኝ ነገሩንና በርገሩን አንድ ላይ ሳላምጥ ጎርነን ያለ ድምፅ ከሃሳቤ አባነነኝ፡፡
“አስራ ሁለተኛ ክፍል’ኮ ነች፤ አታውቅም እንዴ? ኢንትራንስ ተፈታኝ ነች፣” ልጅቷ አጠገብ ያለው ሰውዬ ነበር፡፡
“አስራ ሁለተኛ? ከመቼው? እኔኮ ዘጠነኛ ወይ አስረኛ መስላኝ ነበር፣” አለ የህጻኗ አባት፡፡
“ምን የዘመኑ ልጆች እንደሆኑ ይገርማሉ፡፡ ገና ትምህርት ቤት ከመግባታቸው ሚኒስትሪ ደርሰው ታያለህ፡፡ ያ ሲገርምህ ድንገት ይጠፉብሃል፡፡ “የት ሄደው ነው?” ስትል ዩኒቨርሲት ገቡ ትባላለህ፡፡”
“በእውነት እኔ ኢንትራንስ ተፈታኝ ትሆናለች ብዬ አልገመትኩም ነበር፡፡”
“እንዴት ነው ግን ጥናት?” አለ አጠገቧ ያለው ሰውዬ ወደ ልጅቷ ዞሮ፡፡
ልጅቷ ሾል ያለውን የፒዛውን ጫፍ በትንሹ ገመጥ አድርጋ ትከሻዋን ከፍ ዝቅ አደረገች፡፡
“እንዴ?!” አለ ሰውዬው፡፡ “ፒዛ የተጋበዝሽው’ኮ ሳይኮሎጂካሊ ለፈተናው ዝግጁ እንድትሆኚ ነው፡፡ ደርሷል’ኮ”
ፈገግ አልኩኝ፤ በሆዴ፡፡ እርግጠኛ ነኝ ዘመዷ መሆን አለበት፡፡ አቀማመጣቸውና አነጋገሩ እንደዚያ ዓይነት ፍንጭ ይሰጣል…፡፡
“ተናገሪ እንጂ… እያጠናሽ ነው?” አላት፡፡
የህፃኗ አባት ልጁን ሚሪንዳ በጠርሙስ እያስጎነጫት ተራ በተራ ያያቸዋል፡፡
“እንዴ አዋ… እያጠናሁ ነው” አለች፡፡ ለስለስ ያለ ድምጽ አላት፡፡
 “እንደዚያ ከሆነ እስቲ ጥያቄ ልጠይቅሽ” አለና ማሰብ ጀመረ፡፡
“ኢንትራንሱ ተጀመረ” አልኩኝ ጥያቄው እንዳያመልጠኝ ማኘኬን ቆም አደረግሁኝ፡፡ ምን ዓይነት ጥያቄ ይሆን?
“እ… የአድዋ ጦርነት መቼ ተካሄደ?”
አሃ፤ የማህበራዊ ሳይንስ ተማሪ መሆን አለባት፡፡ ወደ ልጅቷ ዞርኩኝ፡፡ ጀርባዋን ሰጥታኝ ስለተቀመጠች ፊቷን ማንበብ አልቻልኩም፡፡ ግን ልጅቷ ከኋላም ቆንጆ ነች፡፡ ከወገቧ ቀጠን ብላ ከመቀመጫዋ ሞላ ብላለች፡፡ “ናኑ ናኑ ነዬ” ትዝ አለኝ፡፡
ትንሽ አሰብ ካደረገች በኋላ፣ “1984” አለች፡፡
“እህ…?!!” የሚል የስቅታና የድንጋጤ ዓይነት ድምጽ ሰማሁኝ፡፡ ሰው ቤተ መጻህፍት ውስጥ ሆኖ ድንገት ሳያስበው ከኋላው በቀዝቃዛ ሹል ነገር ወጋ ቢደረግ የሚያወጣው ዓይነት ድምጽ ነው፡፡
አብሯቸው ያለው ሰውዬ ድንገት አገጩን ጣለና አፉ ውስጥ ያለው ምግብ ታየኝ፡፡ ዓይኖቹ ወጣ ወጣ ብለው ልጅቱ ላይ ተተክለዋል፡፡
ማን ነው ግን ያን ድምጽ ያወጣዉ? እኔ ነኝ እንዴ? ማለቴ ሰው ምግብ ሲውጥ ቢደነግጥ፣ እንደዚያ ዓይነት ድምጽ ሊያወጣ ይችላል? በሃፍረት ዙሪያዬን ቃኘት አደረግሁኝ፡፡ ዞሮ የሚያየኝ የለም። ተመስጌን!
“አስራ-ዘጠኝ-ሰማኒያ-አራት?” አላት ዘመዷ እያንዳንዷን ቃል ረገጥ እያደረገ፡፡
ልጅቷ ዝም አለች፡፡
ወዲያው የሆነ አጋጣሚ ትዝ አለኝ፡፡ ለአንድ ከዩኒቨርሲቲ ለተመረቀ ሰው ከጠቅላላ ዕውቀት በመነሳት ስለ ሶላር ሲስተምና ፕላኔቶች በፀሐይ ዙሪያ ስለሚያደርጉት ዑደት ገለጻ እያደረግኩኝ ሳለ የአንደኛዋ ፕላኔት ስም ጠፋብኝ፡፡ “ማን ነበረች…? ማን ነበረች…? ማታ ማታ እኮ ፀሐይ እንደጠለቀች ሰማዩ ላይ ጎልታ የምታበራዋ ኮከብ ነች፡፡ እንዴ…” እያልኩኝ ሳስብ ሳሰላስል ሰውየው ሊያስታውሰኝ ፈልጎ “ኦዞን?” አለኝ፡፡
ይህችኛዋ ልጅ የባሰች ናት፡፡ አድዋ የተካሄደው አስራ ዘጠኝ ሰማኒያ አራት ነው ትበል?
“አድዋ፣ አስራ-ዘጠኝ-ሰማኒያ-አራት?” አለ ዘመዷ እንደገና፡፡
“አዋ፣” አለች ልጅቱ፡፡ “እንደዚያ መሰለኝ፡፡”
አይ… በቃ ይህቺ ልጅ በርግጠኝነት የማህበራዊ ሳይንስ ተማሪ አይደለችም፡፡ ብትሆን ኖሮ ሂስትሪ ትምህርት ላይ ስለምትማር  ሰማኒያ ስምንት ዓመት ቀንሳ አትናገርም ነበር፡፡  የፈረንጆቹን የዓመት አቆጣጠር ከተጠቀመች ማለቴ ነው፡፡
“እንዴ አስራ ዘጠኝ ሰማኒያ አራትማ አይደለም።” አላት ዘመዷ፡፡
ልጅቷ ትከሻዋን ከፍ ዝቅ አደረገች፣ በግድ-የለሽነት፡፡
ቢጨንቀው ነው መሰለኝ የህፃኗ አባት “በኢትዮጵያ ነው በፈረንጅ?” ብሎ ጠየቃት፡፡ ሳቄን ያዝ አደረግሁት፡፡
አፏን በሶፍት እየጠረገች፣ “በኢትዮጵያ” አለች፡፡
አሁን እንኳን አልቻልኩም፡፡ የያዝኩትን አስቀምጬ ከት ብዬ ሳቅሁኝ፣ ምንም እንኳን በሆዴ ቢሆንም፡፡
“በኢትዮጵያ 1984 ማለት’ኮ ትላንት ነው፤ ምናልባት አንች ተወልደሽ ሊሆን ይችላል” አላት የህጻኗ አባት፡፡
ልጅቷ መልስ ሳትሰጥ ህጻኗን ከፒዛው እየቆነጠረች ማጉረስ ጀመረች፡፡
“የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪ ትሆናለች፤ ለምን በታሪክ ጥያቄ ያስጨንቋታል?” ስል አሰብኩኝ፡፡
“ቆይ ከ1984 ወዲህ ስንት ዓመት ነው?” ብሎ ጠየቀ የህጻኗ አባት፡፡ እስካሁን ግርምቱ አልለቀቀውም፡፡ ግን አገጩ ወደ ትክክለኛው ቦታ ተመልሷል፡፡ እሱ ይሆን እንዴ የቅድሙን ድምፅ ያወጣው?
ጎሽ! እንደዚህ ሂሳብ ነክ ጥያቄ ይሻላል፣ ከትምህርቷ ጋር የሚሄድ”… ስል አሰብኩኝ። “ግን የአድዋን ጦርነት ዓመት እቅጩን እንኳን ባያውቁ፣ እንዲያው ተቀራራቢ ግምት ለመስጠት የግድ የሕብረተሰብ ሳይንስ ወይም የታሪክ ተማሪ መሆን ያስፈልጋል እንዴ? በየዓመቱ የካቲት 23 መታሰቢያው ይከበር የለ?”
ልጅቷ ከ1984 ወዲህ ስንት ዓመት እንደተቆጠረ ለመመለስ አይኗን ጣሪያው ላይ ተከለች፡፡ እኔም አይኖቿን ተከትዬ ጣሪያው ላይ አንጋጠጥኩኝ፡፡ ልክ እንደ ግድግዳው ሁሉ ጣሪያውም በበርገርና በፒዛ ስዕሎች አሸብርቋል፡፡ የትኛውን መምረጥ እንዳለባት የተቸገረች ይመስል አይኖቿን ከአንደኛው ስዕል ወደ ሌላኛው ታንከባችልላለች፡፡
ጨነቀኝ፡፡ መቶ ዓመት እንዳትል ብዬ ፈራሁኝ፡፡
በመጨረሻም ዓይኖቿን ከጣሪያው ላይ አንስታ ጠያቂዋ ላይ አኖረች፡፡ አውጥታ አውርዳ ያገኘችውን መልስ ነገረችው፤ “ከ1984 ወዲህ… እኔ እንጃ ፡፡ ስንት ዓመት ነው?”
“የባሰው መጣ!! ቆይ ይህቺ ልጅ የምን ተማሪ ናት? ታሪክ ካላወቀች የህብረተሰብ ሳይንስ ተማሪ ላትሆን ትችላለች፡፡ ሂሳብ ላይ ዜሮ ከሆነች የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪ አይደለችም ማለት ነው፤ ምክንያቱም እንዲህ ዓይነት የሂሳብ ችሎታ ይዞ ሳይንስ የሚደፍር የለም፡፡”
“አንቺ ልጅ በዚህ ሁኔታ ነው ኢንትራንስ የምትፈተኚው? ማጥናት’ኮ አለብሽ!” አላት ዘመዷ፡፡
“እያጠናሁ ነኝ፡፡”
“እያጠናሽ ነው?” አለ በፌዝ ቅላፄ፡፡ “እንደዚያ ከሆነ እሽ ሌላ ጥያቄ ልጠይቅሽ፡፡ የሁለተኛው የዓለም ጦርነት ከመቼ እስከ መቼ ተካሄደ?”
“ይሄ ደግሞ ምኑ ጦረኛ ነው?” አልኩኝ ለራሴ፡፡ “ሌላ ጥያቄ የለውም?”
ልጅቷ እንዳልሰማች ህጻኗን ማጫወት ጀመረች።
“መልሽ እንጂ”
“እያሰብኩ ነው”
“ይሄ’ኮ ማሰብ የሚያስፈልገው አይደለም። በአንዴ ተረክ የሚደረግ ነው፡፡” አላት ዘመዷ እንዳያሳፍራት ሳቅ እያለ፡፡
“በ1911 ነው የተጀመረው፣” መለሰች፡፡
“አይደለም፡፡ የሁለተኛው የዓለም ጦርነት የተካሄደው፣ ትሰሚያለሽ፣ ከ 1939 እስከ 1945 ነው።” አላት ቃላቶቹን ረገጥ እያደረገ፡፡ ልጅቷ ዝም አለች፡፡ “እሺ ለጦርነቱ መጀመር ዋናው ምክንያት ምንድነው፣ አጣዳፊውስ ምክንያት ምንድነው?”
ዝም፡፡
“ማን ተገድሎ ነው ጦርነቱ የተጀመረው?”
ዝም፡፡
ምናልባት እዚህ ጋ ሰውዬው የኦስትሪያውን አልጋ ወራሽ የፍራንሲስ ፈርድናንድን መገደል አስቦ ከሆነ ተሳስቷል ማለት ነው፣ ምክንያቱም ይሄ ለአንደኛው የዓለም ጦርነት መለኮስ አጣዳፊው ምክንያት ነው እንጂ ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ጋር አይገናኝም፡፡
“እሺ ዘመነ መሳፍንት ከስንት ዓመተ ምህረት እስከ ስንት ዓመተ ምህረት ተካሄደ?”
ዝም፡፡
“እሺ ዘመነ መሳፍንትን ያስቆመው ንጉስ ማን ነው?” እነዚህንና የመሳሰሉትን ጥያቄዎች ከኢትዮጵያና ከዓለም ታሪክ እያቀላቀለ ጠየቃት። ልጅቷ ግን አንዱንም እንኳን ስትመልስ አልሰማሁም። ሰውዬው ግን የተወሰነ የታሪክ ዕውቀት እንዳለው ተገንዝቤአለሁ፡፡
“አንቺ ልጅ ዋ! ዩኒቨርሲቲ ሳትገቢ ትቀሪና!”
“እንዴ! እገባለሁ፡፡ ኮራ ብዬ ነው ለዛውም”
እስከ ጆሮዎቼ ድረስ ፈገግ አልኩኝ፡፡ ከሕፃኗ አባት ጋር ዓይን ለዓይን ተጋጨን፡፡ ፈገግ አለ እሱም። አፍሬ ዓይኔን ጣሪያው ላይ ተከልኩኝ፡፡ ወዲያው ሃሳብ ይዞኝ ሄደ፡፡ ይህቺ ልጅ አሁን ምንና እንዴት ተምራ ነው እስከዚህ የደረሰችው? የትምህርት ቤቷንና ሀገር-አቀፍ ፈተናዎችን እንዴት አልፋ ነው ዩኒቨርሲቲ ለመግባት አንድ ሐሙስ የቀራት? ምንስ ብትተማመን ነው ዩኒቨርሲቲ እንደምትገባ እርግጠኛ ሆና የምትናገረው?
በርግጥ በእነዚህ ጥያቄዎች ብቻ ስለ ልጅቷ ዕውቀትና ትምህርት ጠለቅ ያለ ግንዛቤ ማግኘት ባይቻልም፣ መሠረታዊ የሒሳብ ዕውቀት ከሌላት፣ ስለ ወሳኝ የዓለምና የሀገራችን ክስተቶች መሠረታዊ ግንዛቤ ከሌላት፣ ሌላ ምን ማለት ይቻላል?
“ወንድም ይቅርታ… ልወጣ ስለሆነ ሒሳብ ትሰጠኛለህ?... ካላስቸገርኩህ?”
ከሀሳቤ ተመለስኩኝ፡፡ “ኧረ ችግር የለውም፡፡”
ሰዎቹ የሉም፡፡ ዞር ብዬ ወደ ውጭ አየሁኝ፤ ዝናቡም ቆሟል፡፡ እንዴ መቼ ወጡ?

Saturday, 13 June 2015 14:51

የፀሐፍት ጥግ

የመፃፍ  ጥበብ የምታምንበትን የማግኘት ጥበብ ነው፡፡
ጉስታቬ ግሎበርት
ለእኔ የመፃፍ ታላቁ እርካታ የሚፃፈው ጉዳይ አይደለም፤ ቃላቱ የሚፈጥሩት ውስጣዊ ሙዚቃ ነው፡፡
ትሩማን ካፖቴ
ሃያሲ መገምገም የሚችለው ፀሐፊ የፃፈውን ሳይሆን እሱ ያነበበውን መፅሃፍ ብቻ ነው፡፡
ሚኞን ማክላውግህሊን
መፃፍ ከዝምታ ጋር የሚደረግ ትግል ነው፡፡
ካርሎስ ፉንቴስ
ፅሁፍ የዝምታና የብቸኝነት ውጤት ነው፡፡
ዋርዊክ ዩኒቨርሲቲ (1997)
ራሱን የማይመግብ አዕምሮ ራሱን ይበላል፡፡
ጎሬ ቪዳል
ማንም ቢሆን በፅሑፉ የቃለ አጋኖ ምልክት መጠቀም የለበትም፡፡ ያንን ማድረግ በራስህ ቀልድ እንደ መሳቅ ነው፡፡
ማርክ ትዌይን
ከሌላ ፀሃፊ ላይ ባለ ሁለት ቃላት ሃረግ ሰርቄ ከምያዝ ባንክ ስዘርፍ ብያዝ እመርጣለሁ፡፡
ጃክ ስሚዝ
እያንዳንዱ ቃላት ከውስጣዊ ፍላጎት ነው የሚወለደው፡፡ ፅሑፍ ፈፅሞ ከዚህ ውጭ መሆን የለበትም፡፡
ኢቲ ሂሌሱም
በፅሁፍ ሃብታም መሆን ከፈለግህ፣ ለራሳቸው ሲያነቡ ከንፈራቸውን ለሚያንቀሳቅሱ ሰዎች የሚሆን ነገር ፃፍ፡፡
ዶን ማርኪውስ
የመጀመሪያ ረቂቅህን በልብህ ፃፈው፡፡ ከዚያም በእጅህ ደግመህ ፃፈው፡፡
“Finding Forrester”
ከተሰኘው ፊልም
በልብ ወለድና በእውነታ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው? ልብ ወለድ ስሜት መስጠት አለበት፡፡
ቶም ክላንሲ
ሰውም ሆነ እግዚአብሔር ምን መፃፍ እንዳለብኝ አይነግሩኝም፡፡
ጄምስ ቲ.
ከፅሁፍ ገንዘብ ማግኘት የሚቻለው በአንድ መንገድ ብቻ ነው፤ ይኸውም የአሳታሚ ሴት ልጅ በማግባት፡፡   
ጆርጅ ኦርዌል

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ በአለቃው የተመረረ ቻይናዊ፣ ቢሮ ይገባና ለአለቃው እንዲህ ይላቸዋል፡-
“ከእንግዲህ እንደ በረዶ ዳክዬ ወደሩቅ አገር መሄድ ይሻላል”
አለቅዬውም፤
“ምን ለማለት ፈልገህ ነው?” ይሉታል፡፡
ቻይናዊው እንዲህ ሲል መለሰ፣
“አውራ ዶሮን ልብ ብለው ተመልክተዋል? የአምስት ምግባረ ሰናይ ተምሳሌት ነው፡-
ጭንቅላቱ ላይ ያለው ጉትያ የጥሩ ዜግነት ምልክት ነው፡፡
የእግር ጥፍሮቹ የኃይለኛነትና የጥንካሬ ምልክት ናቸው፡፡
ማንኛውንም ጠላት ለመጋፈጥ ያለው ቁርጠኝነት የድፍረት ምልክት ነው፡፡ ምግብ ባገኘ ሰዓት ለሌሎች ለማካፈል መቻሉ የደግነትና የቸርነት ምልክት ነው፡፡
በመጨረሻም በየሌሊቱ ሰዓቱን አክብሮ የሚጮህልን ደግሞ የዕውነተኝነት ተምሳሌት ነው፡፡
እነዚህን የመሰሉ አምስት ተምሳሌትነት ያለውን ዶሮ፣ እኛ የገበታ ሳህናችንን ለመሙላት ስንል በየቀኑ እናርደዋለን፡፡ ይሄ ለምን ይመስልዎታል? ከእዚሁ ቅርብ፣ አጠገባችን ስለምናገኘው ነው፡፡ በሌላ በኩል የበረዶ ዳክዬ በሺ ኪሎ ሜትር የሚቆጠር ርቀት ውቂያኖስ አቋርጣ ትበርራለች፡፡ ሲሻት በየአትክልቱ ማህል ታርፋለች፡፡ ሲሻትም በየወንዙ ዳር አሣ ታድናለች፡፡ ቢሻት ደግሞ ትናንሽ የውሃ ዔሊ ትመገባለች፡፡ ሌላ ጊዜ ደግሞ የእርሻ ማሽላ ትበላለች፡፡ እንደ አውራ ዶሮ አምስት ምግባረ ሰናይ ባይኖራትም ትልቅ ዋጋ እንዳላት አድርገን እናደንቃታለን። ለምን? በእጃችን ስለሌለች! ይሄ ስለሆነ እኔም የበረዶ ዳክዬ ሆኜ መብረርን መረጥኩ”
*             *            *
“በእጅ ያለ ወርቅ እንደ መዳብ ይቆጠራል” እንደማለት ነው፡፡ በቅርባችን እጃችን ውስጥ ያለን ሀብት እንዴት እንደምንገለገልበት አለማወቅ ብቻ ሳይሆን አጎሳቁለንና ከአግባቡ ውጪ ስለምናዛባው ለድህነት ራሳችንን እናጋልጣለን፡፡ የበላይ ኃላፊዎች የበታች ሰራተኞችን ማጉላላትን የሥልጣን ማሳያ ካደረጉት መልካም አስተዳደር ስም ብቻ ሆኖ ይቀራል፡፡ በእጃችን ያለውን የሰው ኃይል ማባከንን የሚያህል የድህነት መነሾ የለም፡፡ ከአያያዝ ይቀደዳል ነው፡፡ ጉዳቱ እያደር የሚታወቀው፤ የመልካም አስተዳደር መጥፋት፣ ባለብን ድህነት ላይ ሲደረብ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ነው፡፡ በየውስጣችን አገርን የማሰብ ጥንካሬ ከሌለ፣ ላይ ላዩን ብቻ ማውራት እስክንጋለጥ ብቻ ነው የሚያበላን፡፡
ሾፐንአወር፤ “አዕምሮ ወደ ውስጥ አስቦ የመጠንከር ጉዳይ እንጂ ወደ ውጪ የመስፋፋት ጉዳይ አይደለም” ይለናል፡፡ አንጎል የተሰጠን ውስጣችንን እንድናጠናክርበት ነው ማለት ነው፡፡
በአካባቢያችን ያለውን አዕምሮ በቅጡ ካልተገለገልንበት ኑሮ ውሃ ወቀጣ ይሆናል፡፡ ራዕይ ይሟጠጣል፡፡ ምሁሮቻችንን አናርቃቸው፡፡ አንግፋቸው። ይልቁንም በአግባቡ እንጠቀምባቸው፡፡ የሚቆጨን፤ ጊዜው ካለፈና አዋቂዎች ከራቁ በኋላ ነው፡፡ ላሮቼፎኮ የተባለ ፀሐፊ፤
“በቅርብ አለመገኘት ትናንሽ መውደዶችን የባሰ ያሳንሳቸዋል፡፡ ትላልቆቹን ግን ያቀጣጥላቸዋል፡፡ ልክ ንፋስ ሻማን እንደሚያጠፋውና ትላልቅ ቃጠሎን ግን እንደሚያራግበው፡፡” ይለናል፡፡ በተቻለ መጠን የመቻቻልን ዕሳቤ ማስፋት ተገቢ ነው፡፡ ሆደ ሰፊነት ከብዙ አባዜ ያድናል፡፡ ሩቅ ለመጓዝም ዋና መሳሪያ ነው። የፖለቲካችን ውሃ ልክ የመቻቻልንና የዲሞክራሲን ባህሪ በቅጡ ማወቅ ነው፡፡ ይህ ዕውቀት ነው፤ ከተንኮል፣ ከበቀልና ከማናለብኝ አካሄድ የሚገላግለን፡፡ “ቆይ ነገ ባልሰራለት!” ዓይነት አስተሳሰብ፤ ከየትኛውም ወገን ቢመጣ ደግ አስተሳሰብ አይደለም፡፡
ስትራቴጂያችንን የሰመረ የሚያደርገው በወቅቱ ስንጀምረው ነው፡፡ በቅንነት፣ በጠዋት ካልተንቀሳቀስን ማታ መቸገራችን አይቀሬ ነው፡፡
“…. ያለንን ኃይል/አቅም አሰባስበን በአትኩሮት ወደሥራ እንደመግባት ኃያል ስትራቴጂ የለም” ይለናል፤ ካርል ፎን ክላውስዊዝ፡፡ በተለይ በምርጫ ማግሥት እንዲህ ማሰብ መልካም ነው፡፡ በሁሉም ወገን ያለው ችግር በራስ አለመቆም ነው። መደጋገፍ ትልቅ ፋይዳ ያለው ይሁን እንጂ ሁሌ ደግፉኝ ግብ አይደለም፡፡ ሁሌ ተሸከሙኝም ጤና አይሆንም፡፡ የሚመረጠው በራስ መተማመን፣ በተግባር ራስን ማወቅና በራስ መቆም ነው፡፡ አለበለዚያ “አንገቷን ደግፈው ቢያስጨፍሯት ያለች መሰላት” የሚለው ተረት ዕውን ይሆናል፡፡  

መኖሪያ ቤታቸውን በ15 ቀን ውስጥ እንዲለቁ ታዘዋል

 “እኔ ሣላውቅ በስሜ በታተመ መፅሃፍ ሃሳቤን ተዘርፌያለው” ያሉት የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሠፋ፤ መብቴን ለማስከበር በፍ/ቤት ክስ እመሰርታለሁ አሉ፡፡ መሐመድ ሀሰን በተባለ ፀሐፊ አማካኝነት “የዳኛቸው ሃሳቦች” በሚል ርዕስ ታትሞ በ80 ብር እየተሸጠ ነው የተባለው መፅሃፍ፤ ላለፉት 7 ዓመታት በተለያዩ የስልጠና መድረኮች፣ በሬዲዮ፣ በጋዜጦችና መፅሄቶች ያቀረቧቸው ሃሳቦች መሆናቸውን የጠቆሙት ምሁሩ፤ የመጽሐፉ አዘጋጅ “ትንታኔ” የሚል ቁንፅል አረፍተ ነገሮችን እየጨመረ ሃሳቦቼን ገልብጦ አትሞታል ሲሉ ከሰዋል፡፡ በመፅሃፉ ውስጥ ያሉት ሃሳቦች በሙሉ በ7 አመታት ውስጥ የተናገርኳቸው ናቸው ያሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ ግጥሞቹ ሳይቀሩ የራሳቸው እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ መፅሃፉ በግልፅ የኔን ሃሳብ በመዝረፍ የተዘጋጀ ነው የሚሉት ዶ/ሩ፤ “ከህግ ባለሙያዎች ጋር ተማክሬ በፍ/ቤት ካሣ እጠይቅበታለሁ፤ ይህን መሰል የሃሳብ ዝርፊያ እንዳይፈፀምም ለሌላው መቀጣጫ እንዲሆን እፈልጋለሁ” ብለዋል፡፡”
መፅሀፉ የታተመበት ማተሚያ ቤት አይታወቅም የሚሉት ምሁሩ፤ የኔን ፎቶግራፍ ለጥፎ፣ ‹የዳኛቸው
ሃሳቦች› ብሎ ማውጣት ትልቅ ወንጀል ነው ሲሉ ወቅሰዋል፡፡ዶ/ር ዳኛቸው፤ የራሳቸውን መፅሃፍ ለማሳተም ከአሳታሚዎች ጋር ተዋውለው እንደነበር ጠቁመው የዚህ መፅሀፍ በስማቸው መውጣት ሊያሳትሙ ባቀዱት መፅሃፍ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ሊያሳድር ይችላል የሚል ስጋት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡በሌላ በኩል ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መባረራቸውን ተከትሎ ላለፉት 7 ዓመታት ዩኒቨርሲቲው ሰጥቷቸው ይኖሩበት የነበረውን መኖሪያ ቤት በ15 ቀን ውስጥ ያለባቸውን 3300 ብር ውዝፍ እዳና የመብራትና ውሃ አገልግሎት ክፍያ ፈፅመው እንዲለቁ የዩኒቨርሲቲው አስተዳደር ባለፈው ግንቦት 28 በፃፈላቸው ደብዳቤ ያስታወቀ ሲሆን ዶ/ር ዳኛቸው በበኩላቸው፤ በዩኒቨርሲቲው ያስተማሩበትንና የምርምር ስራዎች የሰሩበትን ወደ 56 ሺህ ብር ክፍያ ቢፈፀምላቸው እዳቸውን ከፍለው መልቀቅ እንደሚችሉ ጠቁመው የተሰጣቸው የጊዜ ገደብም በቂ አለመሆኑን ገልፀዋል - ለዩኒቨርሲቲው በደብዳቤ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡   

በጎተራ የሚገነባው መንደር 4 ቢሊዮን ብር ተመድቦለታል
           ሲኖማርክ የተባለው የሪልስቴት አልሚ ኩባንያ፤ በኢትዮጵያ ትልቁን የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክት በአዲስ አበባ ሊጀምር መሆኑን አስታወቀ። ኩባንያው በ4 ቢሊዮን ብር ወጪ ጎተራ አካባቢ ሊያስገነባው ያቀደው የሪልስቴት መንደር “ሮያል ጋርደን” የሚል ስያሜ ያለው ሲሆን፣ እያንዳንዳቸው 20 ወለሎች ያሏቸው 14 ህንፃዎች እንደሚኖሩት የኩባንያው ማርኬቲንግ ማኔጀር አቶ ተስፋዬ ገ/የሱስ ተናግረዋል፡፡
ጥራታቸውን የጠበቁ ዘመናዊ መኖሪያ ቤቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለኢትዮጵያውያን የማቅረብ አላማ
እንዳለው የገለጸው ኩባንያው፣ የሪልስቴት መንደሩ የመዋኛ ገንዳዎች፣ የህፃናት መጫወቻዎች፣ የስፖርት ማዘውተሪያ ማዕከላትና የንግድ ዞን እንደሚኖረውና አገር በቀሉ ሳባ ኢንጂነሪንግ በግንባታው ንደሚሳተፍበት አስታውቋል፡፡ሪል እስቴቱ የሚያስገነባቸው ህንፃዎች የየራሳቸው ሁለት ሁለት ሊፍቶች፣ ጀነሬተርና የውሃ ማጣሪያ ማሽኖች የሚኖራቸው ሲሆን የሪልስቴት መንደሩ ግንባታ በሶስት አመት ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅም ተጠቁሟል፡፡ የቤቶቹ ዋጋ የፊታችን ሰኞ ይፋ ይደረጋል ተብሏል፡፡ ሲኖማርክ ሪልስቴት ላለፉት 7 አመታት በቻይናና በሌሎች አገራት የተለያዩ ታላላቅ የኮንስትራክሽን ፕሮጀክቶችን በተሳካ ሁኔታ በማከናወን የሚታወቀው የቻይናው ሲንቹዋን ሄንግያንግ
ኢንቨስትመንት እህት ኩባንያ ነው፡፡

       ጆቫጎ የተሰኘው አለማቀፍ የመንገደኞች የሆቴል ቀጠሮ አስያዥ ድረገጽ ከውጭ አገራት ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ፣ ወደ ውጭ አገራት የሚጓዙና በአገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ መንገደኞችን በተመለከተ የሰራውን ጥናት ይፋ ማድረጉን ሜል ኤንድ ጋርዲያን ከትናንት በስቲያ ዘገበ፡፡በውጭ አገራት የሚኖሩ ትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ በርካታ አለማቀፍ መንገደኞች ወደ ኢትዮጵያ እንደሚጓዙ የጠቆመው ጥናቱ፣ ወደ ኢትዮጵያ በርካታ መንገደኞች የሚመጡባቸው ቀዳሚዎቹ አምስት አገራት አሜሪካ፣ እንግሊዝ፣ ጀርመን፣ ደቡብ አፍሪካና ኬንያ ናቸው ብሏል፡፡  ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ጎብኝዎች ቁጥር ባለፉት አምስት አመታት ከፍተኛ እንደነበር የገለጸው ጥናቱ፣ እ.ኤ.አ በ2010 በድረ ገጹ አማካይነት በኢትዮጵያ የሆቴል ቀጠሮ ያስያዙ መንገደኞች 468 ሺህ እንደነበሩና ይህ ቁጥር በ2013 ወደ 681 ሺህ ከፍ ማለቱን ገልጾ፣ ቁጥሩ እስከ 2017 ከ1.2 ሚሊዮን በላይ እንደሚደርስ ያለውን ግምት አስቀምጧል፡፡ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት በድረገጹ አማካይነት የሆቴል ቀጠሮ ካስያዙ መንገደኞች፣ በከፍተኛ ርቀት ላይ የተገኘው የጃፓኗ ቶክዮ ከተማ መንገደኛ እንደነበርና ቀጠሮውን ያስያዘው በ10ሺህ 89
ኪሎሜትሮች ርቀት ላይ ሆኖ እንደነበር ጠቁሟል፡፡ በድረገጹ በኩል ቀጠሮ አስይዘው ወደተለያዩ አገራት የሚሄዱ ኢትዮጵያውያን መንደገኞችን በተመለከተም፣ ኢትዮጵያውያን መንገደኞች በብዛት የሚሄዱባቸው አገራት ኬንያ፣ ታንዛኒያ፣ አይቬሪኮስት፣ ጅቡቲና የተባበሩት አረብ ኢሜሬትስ ናቸው ብሏል ጥናቱ፡፡
በአገር ውስጥ የሚደረገውን የመንገደኞች ዝውውር በተመለከተም፣ አዲስ አበባ ከአገሪቱ ከተሞች በአገር ውስጥ መንገደኞች መዳረሻነት ቀዳሚነቱን መያዟንና ከመንገደኞቹ መካከል 13 በመቶ ሽፋን እንዳላት የገለጸው ጥናቱ፤ ጎንደር በ10 በመቶ፣ ላሊበላ በ9 በመቶ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን እንደያዙ ጠቁሟል፡፡ ከሃገር ውስጥ ጎብኝዎች 6 በመቶ የሚሆኑት ሃዋሳን ምርጫቸው አድርገዋል  ብሏል፡፡ ወደ ሌሎች የአገሪቱ ከተሞች በመጓዝ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች 60 በመቶውን ሲይዙ፣ የሃዋሳ ነዋሪዎች 2 በመቶ፣ የተቀሩት የአገሪቱ ከተሞች ደግሞ 38 በመቶውን ድርሻ ይይዛሉ ተብሏል፡፡

     በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን÷ ከሙስና እና ብልሹ አሠራር መንሰራፋት፣ ከመልካም  አስተዳደር እና ፍትሕ ዕጦት፣ ከአስተምህሮ እና ሥርዐት መጠበቅ ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት እና በየሰንበት ት/ቤቶች መካከል የተቀሰቀሰው ውዝግብ እንደቀጠለ ነው፡፡
በሀገረ ስብከቱ ገዳማትና አድባራት÷ ሌቦች እየተበራከቱ፣ ጎጠኝነት እየተስፋፋ፣ በመናፍቅነታቸው የተወገዱ ግለሰቦች ተመልሰው እየተቀጠሩና አስተምህሮውን እየተፈታተኑ መሆናቸውን ሰንበት ት/ቤቶቹ ይገልፃሉ፡፡ ‹‹ሕገ ወጥ ሰዎችን አልደግፍም›› የሚለው ሀገረ ስብከቱ በበኩሉ፤ ካህናት ሙሰኞች ናቸው  ብሎ ንደማያምን ጠቁሞ፤ ‹‹ሰዎችን ሰረቃችሁ ለማለት ማስረጃ ያስፈልጋል›› ብሏል፡፡በሀገረ ስብከቱ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ የሚመሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ የሰንበት ት/ቤት አባላት፣ ባለፈው ማክሰኞ ከሀገረ ስብከቱ የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ አባላት ጋር በሀገረ ስብከቱ ይፈፀማል በተባለው ብልሹ አሠራር ላይ ያካሄዱት ውይይት ባለመግባባት ተቋጭቷል፡፡ ሙስና እና ብልሹ አሠራርን በማጋለጣቸው ‹‹የፖሊቲካ ድርጅቶች ደጋፊዎች እና ሁከት ቀስቃሾች ናቸው፤ ፓትርያርኩን ይቃወማሉ›› በሚል እየታሰሩ እንደሆነ በውይይቱ ላይ የተናገሩት የሰንበት ት/ቤቶቹ፤ በሰሚት መካነ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን አሠራሩን የተቃወሙ በፖሊስ ጣቢያ ታስረው ክሥ እንደተመሠረተባቸው፤ ካህናትም የንስሐ አባት እንዳይኾኗቸው በደብዳቤ መመሪያ እንደተሰጣቸው ተናግረዋል፡፡በሀገረ ስብከቱ ባለሥልጣናት የሚመኩና የጥቅም ትስስር ያላቸው የአድባራትና የገዳማት ሓላፊዎች ከሦስት እስከ አራት ሺሕ ብር ያልበለጠ ደመወዝ እየተከፈላቸው ውድ ዋጋ ያላቸውን መኪኖችን እንደሚነዱና ቤት እንደሚገዙ ጠቁመው ገንዘቡ ከየት እንደመጣ ሊጣራ ይገባዋል ብለዋል። ሀገረ ስብከቱ የሙዳዬ ምጽዋት ቆጠራ በካሽ ካውንተር እንዲከናወን ማድረጉን ቢደግፉም በፐርሰንት አከፋፈል፣ በቦታ እና በሕንፃ ኪራይ፣ በሠራተኞች ቅጥርና ዝውውር ረገድ በጥቅም ትስስር የሚፈጠሩ ችግሮች እንዲፈቱ፤ በየአጥቢያው የሚታየው የጎጠኝነት መከፋፈል መፍትሔ እንዲያገኝ
አበክረው ጠይቀዋል፡፡ ሰንበት ት/ቤቶቹ ለዘረዘሯቸው በርካታ ችግሮች  ምላሽ የሰጡት የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ ሰዎችን ሰረቃችሁ ለማለት ማስረጃ እንደሚያስፈልግ ጠቅሰው፤ ‹‹ካህናት ሙሰኞች ናቸው ብለን አናምንም፤ መኪና ቢኖራቸው ቪላ ቤት ቢኖራቸው ደስ ይለናል፡፡ ካህናት የሀብት ችግር አለባቸው እንጂ ታማኞች ናቸው›› ሲሉ ተናግረዋል፤ ከሙዳይ ምጽዋት ጥገኝነት ይልቅ በልማት ሥራ መሠማራት እንደሚመረጥም አብራርተዋል፡፡ በሀገረ ስብከቱ የሠራተኛ ቅጥር እየተፈጸመ ያለው በውድድር እንደሆነና ለውጡ ባይጠናቀቅም መጀመሩ መልካም ነው ያሉት ዋና ሥራ አስኪያጁ፤ በቤተ ክርስቲያን ጎጠኝነትን ጨምሮ ሙስናን በሁለንተናዊ ገጽታው መዋጋት ይገባል ብለዋል፡፡