Administrator

Administrator

- የፊሊፒንሳውያንን ያህል አሜሪካን የሚወድ የለም
- አሜሪካን በመጥላት የዮርዳኖስ ህዝቦች ይመራሉ

አሜሪካን በተመለከተ ያላቸውን አመላካት ለመለካከት ታስቦ በ39 የተለያዩ የዓለማችን አገራት ላይ የተሰራ አንድ ጥናት፣ ኢትዮጵያውያን አሜሪካን በመውደድ 3ኛ ደረጃ እንደያዙ መረጋገጡን ዘ ቢዝነስ ኢንሳይደር ዘገበ፡፡ፒው ሪሰርች ሴንተር የተባለው የምርምር ተቋም በሰራው በዚህ ጥናት፣ አሜሪካን አጥብቀው
በመውደድ ቀዳሚዎቹ የፊሊፒንስ ዜጎች ሲሆኑ፣ ጋናውያንና ኢትዮጵያውያን ይከተላሉ ብሏል፡፡በጥናቱ ከተካተቱ ፊሊፒንሳውያን መካከል 85 በመቶው አሜሪካን እንደሚወዱ ሲናገሩ፣ በጋና 83 በመቶ፣ በኢትዮጵያ ደግሞ 75 በመቶ የሚሆነው ህዝብ ለአሜሪካ ፍቅር እንዳለው ለማወቅ ተችሏል፡፡አሜሪካን በመውደድ ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ አገራት ህዝቦች ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዙ የጠቆመው ጥናቱ፣ አብዛኞቹ የአውሮፓ፣ የእስያና የላቲን አሜሪካ አገራት ህዝቦችም ለአሜሪካ በጎ አመለካከት እንዳላቸው ማረጋገጡን ጠቁሟል፡፡
በአንጻሩ ደግሞ አሜሪካን በመጥላት የዮርዳኖስ ህዝቦች ቀዳሚ ሆነው ተገኝተዋል፡፡ በጥናቱ ከተካተቱ የአገሪቱ ዜጎች 83 በመቶ ያህሉ አሜሪካን እንደማይወዱ ተናግረዋል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ አሜሪካን የሚጠሉት ደግሞ ሩስያውያን ሲሆኑ በተለይ  ከቅርብ አመታት ወዲህ አሜሪካን የሚጠሉ ሩስያውያን ቁጥር እየጨመረ መምጣቱንም ጥናቱ አረጋግጧል፡፡

   ሰሞኑን ‹‹የዳኛቸው ሐሳቦች›› በሚል ርዕስ ያሳተምኩትን መጽሀፍ ተከትሎ በየቦታው አቧራ ተነስቶ ከርሟል፡፡ በርካቶችም የአቧራውን ጭስ ብቻ በመከተል ተቧድነዋል፡፡ እኔም እውነታው ብዙ ነገር ስለሚያናጋ ይህንን ጽሁፍ እስከምጽፍበት ጊዜ ድረስ አተካራ ውስጥ ላለመግባት ሞክሬያለሁ። በሌላ በኩል ከእውነታውና ከምጠብቀው ፍጹም የተቃረነ ነገር ስለገጠመኝ መደናገጤን መሸሸግ አይቻለኝም። ለዶክተር ዳኛቸው የነበረኝ አክብሮት፣ ያልተፈተሸ ፍቅር ብሎም አሁን ያሉበት ሁኔታም መልስ ከመስጠት እንድቆጠብ ካደረጉኝ ምክንያቶች ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡ ይሁን እንጂ ዝምታዬ አንዳንድ ሰዎችን ወደ ገደል ሲመራም አስተውያለሁ፡፡ ከዶክተር ዳኛቸው ጋርም አሁን ባለበት ሁኔታ በንግግር መግባባት አልቻልንም፡፡ በመሆኑም ነገሩ የህልውና ጉዳይ እየሆነና በሚያስደነግጥ ሁኔታ መልኩን እየቀየረ ስለመጣ በአቧራው ጭስ የተሸፈነውን እውነት
ለመገላለጥና ለተሰነዘሩብኝ እጅግ ሰቅጣጭ ውንጀላዎች መልስ ለመስጠት እግረ መንገዴንም በአንባቢዎቼ ላይ የተጋረዱትን ብዥታዎች ለማጥራት ስል ይህን ጽሁፍ ለማዘጋጀት ተገድጃለሁ፡፡ዛሬ ላይ ለውዝግብ የተዳረገው መጽሀፌን አስመልክቶ በግልጽ ከተናገርኩኝ አንድ ዓመት ከስድስት ወር አለፈው፡፡ ረቡዕ ታህሳስ 16 ቀን 2006 ዓ.ም በወጣችው “ኢትዮ-ምህዳር” ጋዜጣ ላይ ‹‹በዳኛቸው ላይ የተሰነዘረ መርህ አልባ ትችት›› በሚለው ጽሁፌ ውስጥ በሚከተለው መልኩ ነበር የስራዬን መጠናቀቅ የገለጽኩት፡- ‹‹... ዶ/ር ዳኛቸው ተነቦ የማያልቅ መጽሀፍ ነው፣ በሀሳቦቹ ውስጥም የኢትዮጵያን ችግሮች ማየትና መመርመር ይቻላል፣ ታሪክንም ሆነ ፍልስፍናን ጠንቅቆ ያውቃል፣... በግል ተነሳሽነት ሀሳቦቹን መርምሬ በመጽሀፍ መልክ እያዘጋጀኋቸው እገኛለሁ፡፡ ሌላው ወገን ደግሞ ከፈለገ ተቃራኒውን ሀሳብ አንስቶ በምክንያት መሞገት ይችላል፡፡... ›› ከላይ
የጠቀስኩት ጽሁፍ ለህትመት በበቃበት ቀን የዕለቱ ጽሁፌን ዶ/ር ዳኛቸውን ጨምሮ በዙሪያው የነበሩ ፕሮፌሰሮችና ወዳጆቹ በጣም እንደወደዱትና ከመጽሀፌ ጋር በተያያዘ ይፋ ያደረግሁት ነገርም እንዳስደሰታቸው ዳኛቸው እራሱ በደስታ ስሜት ውስጥ እንዳለ ነበር ደውሎ የነገረኝ፡፡ በወቅቱ እኔ ከአዲስ አበባ ውጪ ስለነበርኩ በተደጋጋሚ የተገናኘነው በስልክ ነበር፡፡ ጽሁፉንም በኢሜል እንድልክለት ጠይቆኝ ልኬለታለሁ፡፡ በቅርቡም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከተባረረ በኋላ ለኢሳት ሰጥቶት የነበረውን ቃለ መጠይቅ እንዳስደምጠው በጠየቀኝ መሰረት፤ ይዤለት እቤቱ ሄድኩና ተገናኘን፡፡ ፕሮግራሙንም ይዤለት የሄድኩት በኮምፒውተሬ ነበር። ሰምቶ እንደጨረሰም እዛው በተቀመጥንበት ከኮምፒውተሩ ላይ ለህትመት ዝግጁ የሆነውን ስራ በጋራ እያሳለፍንና እያወራንበት አየነው፡፡ አይቶ እንደጨረሰም ካልተሳሳትኩኝ የአምቦ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆነ ወዳጁ ጋር ይደውልና እጅግ በተገረመ ስሜት ውስጥ ሆኖ ‹‹ስማ እንጂ... ያ ጉደኛ ልጅ አንዴት አድርጎ መሰለህ መጽሀፉን የሰራው! ... የሚገርም ነው መቼም እልሀለው፤ ስንገናኝ አወራሀለሁ....›› ነበር ያለው፡፡ እነዚህን ሁለት ማሳያዎች ዳኛቸው ከመጽሀፌ መውጣት ጋር ተያይዞ ከሰጠው ሀሳብ ጋር አነጻጽሩት፡፡ እነዚህን ነጥቦች የማነሳቸው ዳኛቸው ለሰጠው አስተያየትም ሆነ አብዛኞቻችሁ ለምታነሱት ጥያቄ ምላሽ እንዲሰጥልኝ እንጂ እኔ በግሌ የዳኛቸው ሀሳቦች ላይ ትንታኔም ሆነ ትችት ለመስራት የግዴታ እሱ ማየትና መፍቀድ አለበት ብዬ አላምንም፡፡ ምክንያቱም ብዙዎች መጽሀፉን ሳያነቡ ከድምዳሜ
ላይ እንደደረሱት መጽሀፉ የእሱ ሃሳቦች ስብስብ ሳይሆን በዳኛቸው ሀሳቦች ላይ ትንታኔ የሚያቀርብ
ነው፡፡ ይህንንም ዘግየት ብዬ በአስረጂ ማሳያ እመለስበታለሁ፡፡መጽሀፉ ገበያ ላይ ሊውል አንድ ቀን እስኪቀረው ድረስም አንድም ተቃውሞ ከዶክተሩ ተቀብዬ አላውቅም፡፡ መጽሀፉ ሊወጣ አንድ ቀን ሲቀረው ዳኛቸው ጋ ሁኔታውን ልነግረው ስደውል ደሴ መሆኑን ነገረኝ፡፡ እኔም የመጽሀፉ ህትመት መጠናቀቁን ላበስረው እንደደወልኩኝ ስገልጽለት፤ ‹‹ልጅ መሐመድ ባለፈው ሳምንት የቀጠርኩህ እኮ በጉዳዩ ላይ እንድናወራ ነበር፤... ፐብሊሸሬ ኮንሰርን አለው፤ ብናወራ ጥሩ ነበር፤...›› ካለኝ በኋላ በነጋታው እንደሚመለስ ገለጸልኝ፡፡ እኔም መጽሀፉን እቤት ይዤለት እንደምመጣ ከተነጋገርን በኋላ በሰላም ተለያየን፡፡ በነጋታውም ዶክተር ደወለና ‹‹ ፐብሊሸሬ ኮንሰርን አለው፤ ደጋግሞ እየደወለልኝ ነው ›› ሲል ከሌላው ጊዜ ጠንከር ባለ ድምጸት አወራኝ፡፡ እኔም በዚህ ስራ ላይ የሱ አሳታሚን የሚያሳስበው ነገር እንደሌለ ስገልጽለት፣ ‹‹እንዴት
ነው የማይመለከተው፤ የኔን ስብስብ እኮ ላሳትመው ነው›› ሲለኝ ‹‹እና ምን ችግር አለው? የኔ ስብስብ ስራ አይደል፤ አንተ አታውቀውም እንዴ?›› አልኩት፡፡ ‹‹ነው እንዴ! ስብስብ ነው ብለውኝ እኮ ነው›› ብሎ ሲለኝ እንደዛ በማሰቡና ሌሎችን በማመኑ ቅሬታዬን ገልጬለት ስልኩ ተዘጋ፡፡ ልብ አድርጉ! እንግዲህ እዚህ ሀገር ጠልፎ የሚጥለው ብዛቱ! መጽሀፉ ገና እኔ እጅ እንኳን ሳይገባ ስብስብ ስራ ነው እያሉ የሚያወሩ ነበሩ፡፡ መጽሀፉ እንደወጣም እቤቱ ሄጄ አስቀምጬለት ወጣሁ፡፡ መጽሀፉን ወደቤት ተመልሶ ገና ሳያገኘው አሁን የምንሰማውን ቅሬታ በዛኑ ዕለት ማታ መሰማት ጀመረ፡፡ ስለብቃቴ፣ መጽሀፌ መዉጣት፣... ያወደሱ አንደበቶች ወደዘለፋ ለመቀየር ጊዜና ማስተዋል አላስፈለጋቸውም፡፡ መጽሀፉን ሳያነቡ ወቀሳውን የሚያስተጋቡት ሌሎችም ነበሩ፡፡ ከዓመት በፊት የታወጀን እውነታ ካለማንበብ የተነሳ አለማወቅ አንድ ነገር ሆኖ ሳለ አሁንም መጽሀፉን ሳያነቡ በቲፎዞነት የተሰለፉ በርካቶች ነበሩ፡፡ በዚሁ አጋጣሚ በማስተዋል ውስጥ ሆናችሁ እኔንም ሆነ ሌሎችን ለማረጋጋት አስተውሎቱ የነበራችሁ ጥቂት የፌስቡክ መንደር ታዳሚዎች የምር ክብር ይገባችኋል፡፡ በቲፎዞነት ዓለም ውስጥ ለዋተታችሁ አብዛኞች ደግሞ ማስተዋልና ልቦናን ከክብር ጋር
ተመኘሁ!የጠሉትን መውረስ!ዳኛቸው አጥብቆ የሚነቅፋቸውን የስርዓቱ ተግባራት ለመፈጸም ጊዜ አልፈጀበትም። በኔው ስራ እኔኑ ከመጠየቅ ይልቅ ምርጫው ያደረገው ጀርባዬን ማጥናት ነበር፡፡ የጠላቸውንና የጠረጠራቸውን ሁሉ ከኔ ጋር ያጣብቃቸዋል፡፡ በውል እንኳን ከነመፈጠራቸው የማላውቃቸውን ሰዎች ስም እየጠራ ከጀርባህ እነከሌ ስላሉ እውነቱን አውጣ ማለቱን ተያያዘው፡፡ ከመጽሀፌ ጋር በተያያዘ ለተፈጠረው
ውዝግብ ዋነኛ ማጠንጠኛውም ይሄው ነጥብ ይመስለኛል፡፡ አንዳንዶችም ለክብራቸው በማይመጥን መልኩ መሰሉን የመሸታ ቤት ሀሜት ሰምተው፣ በአደባባይ የግለሰቦችን ክብር የሚነካና በወንጀልም ጭምር ሊያስጠይቃቸው የሚችል ጽሁፍ ጽፈዋል፡፡ የዚህ ከጀርባዬ የሌለን ሰው የመፈለጉ ሽኩቻ በግላዊ ፀብ፣ በፖለቲካዊ ጥንስስ፣ በማፊያዎቹ ኣሳታሚዎች ፍላጎት፣... ወዘተ ሊሆን ይችላል፡፡ እርግጠኛ ስላልሆንኩኝ ከጀርባ ስላለው ነገር አላወራም። የምፈልገው እከሌን እንጂ አንተን አይደለም፣ እናም መስክር፣ ... አይነት የፍረጃ ተግባሮች ሲተቹ የኖሩትን ስርዓት መንገድ መከተል ይመስላል፡፡ አስራት አብርሀምን እንኳን ካወቅሁት አንድ ወር አይሞላኝም፤ ግንኙነታችንም እሱ በሚካፈልበት ኤግቢሽን ላይ መጽሀፎቼን ለአንባቢም ሆነ ለነጋዴዎች እንዲሸጥልኝ ከማድረግ የዘለለ አይደለም፡፡ ሌላው ከነመፈጠራቸው የማላውቃቸው ሰዎች ስም እየተጠራልኝ ‹‹ከኋላህ አሉ!.. እራስህን ነጻ አውጣ... ሞኝ አትሁን...›› ዓይነት ማስፈራሪያ አዘል ንግግሮችም በጣም አስገራሚ ነበሩ። ከዚህም በላይ ለመጥቀስ የማይመቹ ዝርዝር ጉዳዮች እየተነሱ በማላውቀውና በማልጠብቀው አሳዛኝ ጉዳይ ውስጥም ተዘፍቄ ነው የከረምኩት፡፡ አስራትም ሆነ የሚጠሩልኝ ሰዎች የዶክተሩ እንጂ የኔ ወዳጆች አይደሉም፡፡ ከላይ ካነሳሁት ተግባር ጋር የሚመሳሰለው ዶክተሩ በዚሁ ጋዜጣ ላይ ‹‹መሐመድ ይቅርታ ጠይቆኛል...›› በሚል ያነሱት ነጥብ ነው፡፡ ዶክተሩን ወደ አደባባይ ያወጣቸውና ተቀባይነትም ያስገኘላቸው ከብርቱካን እስር ጋር ተያይዞ ይህንን የይቅርታ ጠይቆኛል አባዜ፣ በከፍተኛ ሁኔታ
ማውገዛቸውና ጠንካራ አስተያየትም ማቅረባቸው ነበር፡፡ ከሰሞኑ ግን ዶክተሩ ይህንኑ ተግባር እንደልጄ አይሀለው በሚሉኝ እኔ ላይ በከፍተኛ ጭካኔ ተግባራዊ አድርገውታል፡፡ መመስገንና መሸለም ሲገባኝ በከፍተኛ ሁኔታ የሞራል ኪሳራ የሚያደርሱ ጽሁፎችና ወሬዎች ሲያናፍሱ ከቆዩና በኋላም ክስ መስርተው ሲያበቁ በወጉ እንኳን ባልተስማማንበት የአንድ ቀን ግንኙነት ይቅርታ ጠይቆኛል አሉ፡፡ እኔ ዶክተሩን አስቀይሜ ይቅርታ ብጠይቃቸው እንኳን ካለን ቀረቤታ አንጻር እሳቸውን ደረት አስነፍቶ በአደባባይ የሚያስፎክር፣ የኔንም አንገት የሚያስደፋ አይደለም። የነበረውን ሁኔታ በግልጽ ላስቀምጠው፡፡ እኔና ዳኛቸው ከውዝግቡ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በአካል የተገናኘነው ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ስድስት ኪሎ አካባቢ ካለ አንድ ግሮሰሪ ውስጥ ነበር፡፡
ግንኙነታችንም ከሳቸው በተነሳ ጥያቄ መሰረት ሚስጥራዊ እንዲሆን ብንስማማም በወቅቱ ያነሳናቸውን ጉዳዮች በተዛባ መንገድ እያነሱ ዛሬም ድረስ በስልክ የሚረብሹኝ ሰዎች አሉ፡፡ በወቅቱ ስንገናኝ የነበረው ሁኔታ ሚዲያው ላይ በሚራገበው መጠን ብዙም ውጥረት የበዛበት አልነበረም፡፡ በሂደት ሁለታችንም በሚያግባባን አንድ ነጥብ ላይ ማውራት ስላልቻልን ስሜቴ መረበሹ አልቀረም፡፡ ሆኖም ግን የምናወራው እንደ አባትና ልጅ ነበር፡፡ በኋላም በደረሰብኝ ነገር ሁሉ ስሜቴ ክፉኛ እንደተጎዳ፣ አስካሁን ከደረሰብኝ ጉዳት የባሰ ነገር በክሱም ቢሆን እንደማይገጥመኝ፣ ስራውንም ለገንዘብ ብዬ እንዳልሰራሁት፣ ወዘተ ካስረዳሁ በኋላ በዶክተሩ ፍላጎት እንዲወሰኑ ሁለት አማራጮችን አቀረብኩኝ። የመጀመሪያው አማራጭ እስካሁን የተበተነው መጽሀፍ የተበደርኩትንና መጽሀፉን ያሳተምኩበትን ወጪ ብቻ ከሸፈነ ቀሪዎቹን መጽሀፎች እንዲሰበሰቡ የሚል ሲሆን፤
ሁለተኛው አማራጭ መጽሀፉን ደግሞ የማሳተም ፍላጎት እንደሌለኝና አሁን የታተመው ግን ከኛ ቁጥጥርም ጭምር ዉጪ በመሆኑ ተሸጦ እንዳለቀ ለኔ የሚደርሰኝን ገንዘብ አምጥቼ ለዶክተር ልሰጥና፣ እሳቸውም በገንዘቡ ላይ የፈለጉትን ውሳኔ እንዲያሳልፉ የሚል ነበር፡፡ ይህንን በልመና ጭምር የታገዘውን አማራጭ ሳቀርብ አሁን የተፈጠረው አተካራ ማናችንንም እንደማይጠቅመን በማስረዳት ጭምር ነበር፡፡ በዚህ ላይ ለመወሰንም ለአርብ ጠዋት ቀጠሮ ይዘን ተሰነባበትን፡፡ የነበረው ነገር ይህ ነው፡፡ ገና ባልተቋጨ ጉዳይ ላይ ነው እንግዲህ “ይቅርታ ጠየቀኝ” በሚል መግለጫ የሰጡት። ታዲያ የቀጠሯችን ቀን አርብ ሲመጣ ከሳቸው በስልክ የደረሰኝ ውሳኔ ሳይሆን ቀደም ብዬ ከላይ ያነሳሁት የተጠናከረ ፍረጃ ነበር፡፡ ሌላውን ለማጥቃት እኔን መግደልም እንዴት
ምክንያታዊ እንደሚሆን አልገባኝም። እውነታውን በማስረጃ ለሚዲያው ፍጆታም ሆነ ሽያጭ ከኔ ይልቅ የዳኛቸው ፊት ገጽ ላይ መውጣት ሚዛን እንደሚደፋ እርግጥ ነው፡፡ ለዚህም ይመስላል ከሰንደቅ ውጪ የትኛውም ሚዲያ ዘገባውን ሲሰራ ወደኔ በመደወል እውነታውን ለማጣራት ያልሞከረው፡፡ ባለፈው ሳምንት በወጣው የአዲስ አድማስ ዜና ላይም ዶክተር ዳኛቸው የመጽሀፉ 95 ከመቶ የሚሆነው ሀሳብ ከሳቸው እንደተወሰደ ተናግረዋል፡፡ የሆነው ሆኖ አንባቢ በእውነታው መካከል ያለውን ልዩነት አይቶ፣ የራሱን ፍርድ ይስጥ፤ እኔ ግን እውነታውን በቁጥር አስደግፌ ላስፈር፡፡ መጽሀፌ 236 ገጾች አሉት፡፡ በነዚህ ገጾች ውስጥ የዶክተሩ ሀሳቦች አስፈላጊ በሆኑበት ቦታ ላይ በሩብ፣ በግማሽ እና በሙሉ ገጽ ላይ እንደወረዱ የሰፈሩባቸው ቦታዎች አሉ፡፡ እነዚህ እንደወረዱ የተጠቀምኳቸው የዶክተሩ ሀሳቦች ተደማምረው ወደ 76 ያህል ገጽ ናቸው፡፡ ልብ አድርጉ 236 ገጽ ካለው መጽሀፍ ውስጥ 76 ገጽ ምን ያህል ፐርሰንት እንደሚሆን አስቡት፤ ወደ 32 ከመቶ ገደማ ነው፡፡ ከዚህ በቀጥታ የዶክተሩን ሀሳብ እንደወረደ ካሰፈርኩበት 76 ገጽ ውስጥ ደግሞ ወደ 30 ያህል ገጽ የሚሆነው ከኔው ጋር የቃለምልልስ ቆይታ በነበራቸው ወቅት የሰጡኝ ሀሳብ ነው፡፡ በተቀረው ገጽ ላይ የሰፈሩት ሀሳቦች የኔው ትንታኔዎች፣ ማብራሪያዎች እና አቶ ጌታቸውን ጨምሮ የሌሎች ሰዎች አጋዥ ስራዎች ናቸው፡፡ ይህንን ቁጥር እሳቸው ካሉት 95 ከመቶ ጋር ማነጻጸር ነው እንግዲህ፡፡ ይህንኑ እውነታ በሌላ ተጨባጭ ማስረጃ ለማስቀመጥ ያህል ሌላ ማሳያ ላምጣ፡፡ በመጽሀፉ እስከ 27ኛው ገጽ ድረስ የሳቸውን ሀሳብ እንደወረደ የተጠቀምኩት ሁለት ቦታ ላይ ከራሴው ጋር ካደረጉት ቆይታ ውስጥ ነው፡፡ ሽፋኑም ተደምሮ በገጽ ሲገመት አንድ ገጽ ከግማሽ ነው፡፡ ... ከገጽ 30 እስከ 35 ድረስ አንድ ቦታ ላይ ሩብ ገጽ ያህል ከ “ኢትዮጵያን ማን ይታደጋት” ላይ በቀጥታ ተወስዶ የሰፈረ ሀሳብ አለ፡፡... እንዲህ አድርገን ስንደምረውና በተለይም ከብርቱካን ጋር በተያያዘ የጻፉት ጽሁፍ፣ ለሰራሁት ትንታኔ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ አብዛኛው ክፍል በመግባቱም ጭምር ነው ከላይ የጠቀስኩትን ያህል ቁጥር የመጣው፡፡ በመጨረሻም ከአንደኛው ገጽ ያልዘለለ ንባብና በስማ በለው በቲፎዞነት መሰለፍ ውጤቱን አደገኛ ያደርገዋል፡፡ መጽሀፉን ማንበብ ብቻ ወደትክክለኛው መንገድ ደርሰናል፡፡ አንብቦ ስራው አይረባም ማለት ይቻላል፡፡ ድምዳሜውን ለአንባቢያኑ መተው ይሻላል፡: በተረፈ ግን በቀሪ አተካራዎች ላይ ገብቶ መዋጀቱ ትንሹ እድሜዬ ሳይሆን በልበሙሉነት
የምናገርለት የሞራል ልዕልናዬ አይፈቅድልኝም፡፡ እውነቱ ይህ ነው! ትዕግስትም፣ ዝምታም፣
አክብሮትም ልክ አለው!!

ከአይሁዳውያን ተረት ውስጥ እንዲህ የሚል ይገኝበታል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ብቸኛ ጫማ ሰፊ በአንድ ከተማ ይኖር ነበር፡፡ የዚያ ጫማ
ሰፊ አንድ ደንበኛ ጫማ ሊያሰራ መጥቶ ሳለ፤
“ጫማዬን በትክክል አልሰፋህልኝምና አልከፍልህም” ይለዋል፡፡
ጫማ ሰፊውም፣
“ከዚህ በላይ ልሰፋልህ አልችልም፡፡ የሰፋሁልህን ያህል ልትከፍለኝ ይገባሃል” አለው፡፡
“አልከፍልም”
“ትከፍላለህ!”
ግብ ግብ ገጠሙ፡፡ ጫማ ሰፊው ደምበኛውን በመዶሻ አናቱን ብሎ ገደለው፡፡
ተይዞ እከተማው ዳኛ ፊት ቀረበ፡፡
የከተማው ዳኛም፤
“ደምበኛህን ሆነ ብለህ በመዶሻ መትተህ በመግደልህ ሞት ይገባሃል፡፡ ይኸውም ሞት
በስቅላት መልክ የሚፈፀም ይሆናል፡፡” ሲሉ ፈረዱ፡፡ ፍርዱ ባደባባይ ተነበበ፡፡ ፍርዱን
ከሚያዳምጠው ህዝብ መካከል አንድ ሰው ተነስቶ፤
“የተከበሩ ዳኛ! እነሆ በከተማችን አለን የምንለውን አንድ ጫማ ሰፊ እንዲገደል
ፈርደዋል፡፡ ሆኖም ያለን ብቸኛ ጫማ ሰፊ እሱ ስለሆነ ከእንግዲህ ማን ጫማችንን
ይሰራልናል? ለህዝቡ ሊታሰብለት ይገባል!”
ሲል ሀሳብ አቀረበ፡፡ ሌሎችም ሰዎች በተራ በተራ እየተነሱ፤
“አስተያየት ይደረግልን”
“አስተያየት ይደረግልን”
“ያለን እሱ ብቻ‘ኮ ነው ምን ይውጠናል?” አሉ፡፡
የህዝቡ ሁኔታ የከተማው ዳኛ ሀሳባቸውን እንደገና እንዲያጤኑ አደረጋቸውና፤
“የከተማችን ህዝብ ሆይ በሀሳባችሁ እስማማለሁ፡፡ ያላችሁትም ዕውነት ነው፡፡ አንድ
ልብስ ሰፊ ቢኖረን እሱኑ መግደል ትክክል አይሆንም፡፡ በከተማችን ሁለት ጣራ ሰሪዎች
ናቸው ያሉት፡፡ ስለዚህ ከሁለቱ አንደኛው እንዲሞት ወስኛለሁ! ፍርዱ በስቅላት የሚፈፀም
ይሆናል!” ሲሉ ፈረዱ፡፡
* * *
አንዱን አድን ብሎ አንዱን ከሚያስገድል፣ በፍርደ - ገምድልነት ከመፍረድና በህዝብ
ከመገፋት ይሰውረን! በትናንሽ ጠብ - ያለሽ በዳቦ ከመናቆርም ያድነና፡፡ የፍርድ ሂደት
በቲፎዞና በግፊት ከሆነ የህግ መንፈስ ጨርሶ ጥያቄ ውስጥ መውደቁ አይቀሬ ነው፡፡ ህግ
ስነ-ሥርዓት አክብሮ የሚኖር ዜጋ ወገናዊነትንና ፍርደ - ገምድልነትን መቃወሙ ያለ፣
የነበረና ወደፊትም የሚኖር ነው፡፡
“ለመቶ አምሣ ጌታ
ስታጠቅ ስፈታ
ነጠላዬ - አለቀ በላዬ”፤ ያለችው ጭሰኛ ይሄንኑ የፍትህ መዛባትና የጌታ - የሎሌ ግንኙነት
አባዜ ስትግልጥ፣ ብሶቷንም ስታሰማ ነው፡፡ ዜጋ ቅሬታውንና በደሉን ማሰማቱ፣ ምንም
ቢዘገይ፣ አይቀርምና የፍትሕ አካላት ለሚያዛቡት ማናቸውም ፍርድ ተጠያቂነታቸው
አሌ አይባልም፡፡
በየትኛውም ሥርዓት ውስጥ ሥልጣን ላይ የሚቀመጡ ሹማምንት ከየት እንደመጡ፣
የት እንዳሉና ወዴት እንደሚሄዱ የዘነጉ ዕለት የጥፋት ህይወታቸው ይጀምራል፡፡ የበለጠው
ጥፋታቸው ደግሞ ጥፋታቸውን አለማመናቸው ነው፡፡ ከዚያ ቀጣዩ ደግሞ የአብዬን ወደ
ዕምዬ ማላከካቸው ነው፡-
ሥልጣን ላይ ያሉ ሰዎች የሚዋረዱት በሚሰሩዋቸው ስህተቶች
አይደለም፡፡ ይልቁንም፤ ስህተቶቻቸውን በሚይዙበት መንገድ
ምክንያት ነው” ይለናል ሮበርት ግሪን፡፡ (The way they deal with
their mistakes እንዲል)
“የአብዬን እከክ ወደ እምዬ ልክክ” የሚለው አባባል፣ Scapegoat የሚሉት በእንግሊዝኛ
መሰረታዊ - አመጣጡ በዕብራውያን ምክንያት ነው ይባላል፡፡ ይኸውም ለተሰራ ጥፋት
የፍየል መስዋዕት በማድረግ አገራቸውን ለማዳን ይሞክሩ በነበረበት ዘመን ነው፡፡ ከዚያም
ቢሆን ይሰውረን የዲሞክራሲ ጠር ነውና! ዲሞክራሲ እንደየአገሩ ፈሊጡም፣ አካሄዱም
እንደሚለያይ ማስተዋል ዋና ቁም ነገር ነው፡፡
ፋሪድ ዘካሪያ እንዲህ ይለናል፡-
… የበለጠ “ዲሞክራሲ” አለ በሚባልበት በአሜሪካ ሥርዓት ከዚህ
ቀደሙ የበለጠ ሥርዓተ - ነገሥታት (dynasties) አይተናል፡፡ የተከበሩ
ሹማምንት አይተናል፡፡ ሆኖም የፖለቲካ ፓርቲዎች እየተዳከሙ
ሲሄዱ፤ ሀብታም መሆን እና/ ወይም ዝነኛ መሆን፤ ለከፍተኛ ተመራጭ
ሹማምንት ተራ፣ የአዘቦት ጉዳይ ይሆናል፡፡
እኛ ሀገርም ከፊውዳሊዝም አብራክ ወጥቶ፣ በሶሻሊዝም አቋርጦ፣ አሁን ከካፒታሊዝም
ጋር በመፈጣጠም፣ እንውለደው እያልን የምናማምጠው ዲሞክራሲ፣ ከሌላ ከማናቸውም
አገር የተለየ ቢሆን አይገርምም፡፡ ተዋንያኑ አዋላጆች ግን ዛሬም እኛ ነን፡፡ የእኛ ማንነት
ደግሞ ንጥረ ነገሩ አንድ ነው፡፡ ታሪካችን፣ ባህላችን፣ ፖለቲካችን መሰረቱ አንድ ነው፡፡
ድንገት በአንድ ጀንበር አይለወጥም - “ከእትብት ጋር የወጣ አመል፣ ከከፈን ጋር ይቀበራል”
የሚባለው ተረት ዕውነት የሚሆነው ለዚህ ነው

 ለ11 ዓይነት በሽታዎች ፍቱን መድሃኒት አለኝ ይላሉ
     በዕፅዋትና የባህል መድሃኒት ዘርፍ ለ25 ዓመታት ምርምር አድርገዋል
     ከጫት ወይን የሚሰራበትን መንገድ በምርምር ማግኘታቸውን ይናገራሉ
           ለዓመታት በተማሩበትና በሰለጠኑበት የማህፀንና ፅንስ ህክምና ሙያ በተለያዩ የመንግስትና የግል ሆስፒታሎች ረዘም ላለ ጊዜያት አገልግለዋል፡፡ ከዘመናዊው የህክምና ሙያ ጐን ለጐን በባህላዊ መድሃኒትና በዕፅዋት ዙሪያ የተሰሩ ጥናቶችንና ጽሑፎችን ይከታተሉ ነበር፡፡ በመከታተል ብቻ ግን አልተገደቡም፡፡ ከ25 ዓመታት በላይ በዕፅዋት ምርምር ላይ መስራታቸውንም ይናገራሉ፡፡ በምርመራቸውም ከአስራ አንድ ለሚበልጡ የተለያዩ ህመሞች ፈዋሽ የባህል መድሃኒቶችን እንዳገኙና በዚህም ወገኖቻቸውን ለመርዳት ፅኑ ፍላጐት እንዳላቸው ይገልፃሉ፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መታሰቢያ ካሳዬ ከእኚህ የባህል መድሃኒት አዋቂ ከዶክተር ኢያሱ ኃ/ስላሴ ጋር በዕፅዋቶች ላይ ስለአደረጓቸው ምርምሮች፣ ስለባህል ህክምናቸውና የወደፊት ዕቅዳቸው ተከታዩን ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡

   እንዴት ነው ወደ ዕፅዋት ምርምር ዘርፍ የተሳቡትና ወደ ሙያው የገቡት?
ስለዕፅዋት የተፃፉ ጽሑፎችንና የምርምር ሥራዎችን የማንበብ ፍላጐትና ዝንባሌ ነበረኝ። ይህ ነገር ወደ ዕፅዋት ምርምር እንድሣብ፣ ስለ ‹0ፅዋቶች ዝርያ፣ አመጣጥና ጠቀሜታ ለማወቅ ፍላጐት እንዲያድርብኝ አድርጐኛል፡፡ ናይጀሪያ እየሰራሁ በነጀረበት ወቅት ፕሮፌሰር ላምቦ ከሚባል የታወቀ ሣይካትሪስት ሐኪም ጋር አብሮ የመሥራት ዕድል አግኝቻለሁ፡፡ ይህ ፕሮፌሰር ብዙውን ጊዜ በዕፅዋቶች ላይ ምርምር ሲያደርግና ሲጠቀም አየው ነበር፡፡
ይህ ሁኔታ እኔ ውስጥ ፍላጐት አሳደረብኝና ከእሱ ጋር እየዋልኩ ሁኔታውን ማጥናት ጀመርኩ። ናይጀሪያዎች በአንጐል መናወፅና ከሚጥል በሽታ ጋር በተያያዘ ብዙ ችግሮች ነበሩባቸው፡፡ በዚህ ፕሮፌሰር አማካኝነት ስለ እነዚህ በሽታዎች ብዙ ትምህርት አገኘሁ፡፡ እንግሊዝ አገር በነበርኩበት ጊዜም ለሪሰርች አንድ ትልቅ ላይብረሪ ስገባ የኢትዮጵያ ኸርባል ጥናቶች መጽሐፍ አገኘሁ፡፡ በአፄ ቴዎድሮስ ጊዜ እንግሊዞች ወስደውት እዛው ያስቀሩትና በብራና የተፃፈው “መፅሐፈ መድሃኒት” የተባለውን በዚህ ላይብረሪ ውስጥ አግኝቼ ፎቶ ኮፒ በማድረግ ወሰድኩት፡፡ እነዚህን መጽሐፎች ሳነብ፣ በአገራችን በዕፅዋት ላይ የተደረጉ ምርምሮች እምብዛም አለመኖራቸውን ስመለከት ወደሙያው የበለጠ እንድሣብና እንዳጠና ተገፋፋሁ፡፡ ወደ አገሬ ከተመለስኩም በኋላ በዚሁ ዘርፍ ላይ የበለጠ መመራመርና የተፃፉ ነገሮችን ማንበብ ማዘውተሬ ወደ ሙያው እንድገባ የተገፋፋሁበት ምክንያቶች ናቸው፡፡
በአገራችን ያለው የባህል ህክምና ዕድገት ምን ይመስላል? በዘርፉ በቂ ጥናትና ምርምር ተደርጓል ብለው ያስባሉ?
በአገራችን በባህል መድሃኒቶች ምርምር ላይ የተሰማሩ ሰዎች እምብዛም የሉም፡፡ ሙያውን በዘመናዊ መንገድ ለማሳደግና ባለሙያዎችም ሙያቸውን ለትውልድ እንዲያስተላልፉ ለማድረግ የሚሰራ ሥራ የለም፡፡ “ኢትዮጵያን ኸርባል ሂስትሪ ውስጥ ተፅፎ እንዳገኘሁት፣ በአገራችን እስከዛሬ ከ80ሺ በላይ የሚሆኑ የባህል መድሃኒት አዋቂዎች አሉ፡፡ እነዚህ የባህል መድሃኒት አዋቂዎች ሙያውን የሚተገብሩበት ሁኔታ ግን አሳዛኝ ነው፡፡ ባለሙያዎቹ በአብዛኛው መድሃኒቱን የሚሰሩት ከሰው ተደብቀው ነው፡፡ ጓሮ ገብተው ተደብቀው ሰርተው ነው ለሰው የሚሰጡት፡፡ ይህ ደግሞ የመድሃኒቱን ንፅህና በማሳጣት ህመምተኛውን ለከፋ ችግርና አደጋ የሚያጋልጥ ይሆናል፡፡
ከዚህ ሌላ ደግሞ ባለሙያዎቹ ሙያውን ለሰዎች ለማሳየት አይፈልጉም፡፡ ምኑ ከምኑ ጋር ተዋህዶ መድሃኒት እንደሚሆን ማሳወቅ ፈጽሞ አይፈልጉም፡፡ ልጅ ካላቸው ለልጃቸው አሊያም በጣም ለሚወዱት ሰው ነው ሙያውን የሚያወርሱት፡፡ ያለበለዚያ ሲሞቱ ሙያው አብሮአቸው ይሞታል፡፡ ይህ ደግሞ ሙያው እንዳያድግና የተሻለ ደረጃ ላይ እንዳይደርስ አድርጐታል፡፡ በየገዳማቱ፣ በየቤተክርስቲያናቱና በየመስጊዱ ውስጥ ተፅፈው የተቀመጡ የባህል ህክምናዎች አሉ፡፡ እነዚያን አውጥቶና አጥንቶ በግልጽ ህብረተሰቡ አንዲጠቀምበት የሚያደርግም ሆነ የሚያስተምር የለም፡፡
የኢትዮጵያ ምግብ ጥናት ድርጅት በዚህ ጉዳይ ላይ ሊያስመሰግነው የሚችል ተግባር አከናውኗል። በዚህ ጉዳይ ላይ በርካታ ጥናቶችን በማድረግ መጽሐፍም አሳትመዋል፡፡ ይህ ድርጅቱ ለህብረተሰቡ ያበረከተውን እጅግ ጠቃሚ የሆነ ነገር ነው፡፡ እዚያ መፅሐፍ ውስጥ የሌለ ነገር የለም፡፡ እኔ መጽሐፉን እንደማጣቀሻ ዋቢ (reference) ነው የምጠቀምበት። ኢትዮጵያ ውስጥ በየትኛውም አቅጣጫ ያሉ ብዙ ዓይነት ቅጠሎች ከፍተኛ የመፈወስ አቅም ያላቸው ናቸው፡፡ ይህንን ማጥናትና ማወቅ፣ ህብረተሰቡ የሚጠቀምበትን መንገድ ማመቻቸት… ለዘርፉ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብዬ አምናለሁ፡፡
የባህል ህክምና ከዘመናዊው ህክምና እኩል መሰጠት አለበት ብለው ያስባሉ? በሁለቱ መካከል ያለውን ልዩነትስ እንዴት ይገልፁታል?
የባህል መድሃኒት አሠራሩና ሁኔታው ከዘመናዊው ጋር ይመሳሰላል፡፡ ልዩነቱ የሚወስደው መድሃኒት መጠንና መድሃኒቱ የሚቀመምበት ሁኔታ ነው፡፡ የባህል መድሃኒቶች ክብራቸውን ይፈልጋሉ፡፡ ዕፅዋቶቹ የየራሳቸው ተፈጥሮአዊ ባህርይ ስላላቸው መድሃኒቶቹ የሚወዱትና የሚጠሉት ነገር አለ። መድሃኒቱን ስትወስድ፤ “ይህንን አታድርግ” ይህንን አድርግ ሊባል ይችላል፡፡ በዘመናዊም ይህ ነገር ያለ ነው፡፡ መድሃኒቶቹን ያረክሳል እየተባሉ የሚገልፁ ነገሮች አሉ፡፡ ዘመናዊ መድሃኒቶች በፋብሪካ ተዘጋጅተው የሚወጡ ስለሆነ ንፅህናቸው አስተማማኝ ነው፡፡ የባህል መድሃኒቶች ቅድም እንዳልኩሽ ተደብቀው የሚሰሩ በመሆናቸው የንፅህናቸው ጉዳይ አስተማማኝ የማይሆንበት ጊዜ ይኖራል፤ ሌላው የባህል መድሃኒቶች እንደ ዘመናዊዎቹ ሁሉ ከነርቭ ጋር ለተያያዙ ህመሞች በማሸትና በማሞቅ መፍትሔ ሊያስገኙ ይችላሉ። ለምሳሌ እኛ በማግኔቲክ ሲስተም፣ በሙቀትና ከዕፅዋት በተገኙ መድሃኒቶች በማሸት ብቻ ለወገብ ህመም መፍትሔ እያስገኘን ነው፡፡ ሴሎቹ እንዲከፈቱ እንዲፍታቱና ሥራቸውን በአግባቡ እንዲሰሩ ለማድረግ የሚያስችል ህክምና እየሰጠን ነው፡፡
ህክምናውን ለህመምተኞች ለመስጠት የሞከሩበት ሁኔታ የለም?
የመጀመሪያ ጥናትና ምርምር ያደረግሁት በወገብና በእግር ነርቮችና በአስም በሽታ ላይ ነበር፡፡ ይህንን አጥንቼ እንደጨረስኩ “ክርስቲና” በሚባለው የማህፀንና ፅንስ ህክምና ክሊኒኬ ውስጥ ህክምናውን መስጠት ጀመርኩ፡፡ ህክምናው የሚሰጠው በመቀባት ብቻ ነበር፡፡ የሚጠጣም ሆነ ሌላ ነገር አልነበረንም። የአስም ህሙማን መድኀኒቱን በአፍንጫቸው በመሳብ ብቻ ከህመማቸው የሚፈወሱበት መንገድ ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት የታካሚው ቁጥር እየጨመረ መጣ፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ በማህፀንና ፅንስ ክሊኒኩ ውስጥ መጨናነቅን ፈጠረ፡፡ ህክምናውን በተለየ ክሊኒክ ውስጥ መስጠት እንደምንችል የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ቢነግረንም በወቅቱ ይህንን ማድረግ ባለመቻላችን፣ ክሊኒኩ ለተወሰነ ጊዜ እንዲዘጋ ተደረገ፡፡ ከዚያ በኋላ የማህፀንና ፅንስ ክሊኒኩ በድጋሚ ተከፍቶ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር የባህል ህክምናውን ለጊዜው አቆምነው፡፡
እስከዛሬ ለምን ያህል ሰዎች ህክምናውን ሰጣችሁ? ለምን ያህል ህሙማን የፈውስ መፍትሄ አስገኝተናል ብላችሁ ታስባላችሁ?
 በወገብ፣ በሪህ፣ በአስምና ተጓዳኝ ህመሞች ተይዘው ይሰቃዩ ለነበሩ ከ800 በላይ ለሚሆኑ ህሙማን ህክምናውን ሰጥተን ፈውስ አስገኝተናል፡፡ በእኛ የባህል መድኀኒት ታክመው ለዓመታት የቆየና ነቀርሳ የሆነ በአንገት ላይ የነበረ ከፍተኛ ቁስለት ሙሉ በሙሉ እንዲድንና ታማሚው ከችግሩ እንዲፈወስ አድርገናል፡፡ ይህ በህይወቴ ውስጥ ትልቅ ደስታን የሚሰጠኝና ሙያውን የበለጠ እንድወደው የሚያደርገኝ ጉዳይ ነው፡፡
አሁንስ ለምን ያህል በሽታዎች ፈውስ የሚሰጡ መድኀኒቶች አሏችሁ? መድኀኒቶቹ የሚወሰዱት በምን መልኩ ነው? የመድኀኒቶቹ አስተማማኝነትስ ምን ያህል ነው?
አስራ አንድ ለሚሆኑ የተለያዩ በሽታዎች መድኀኒቶች አሉን፡፡ መድኀኒቶቹ የሚወሰዱት ራስን ለችግር በማያጋልጥና በቀላል መንገድ ነው። እኛ የምንሰጠው መድኀኒት የሚበላ፣ የሚጠጣ፣ በሰውነት ውስጥ የሚገባ አይደለም፡፡ በአንገት .ላይ የሚደረጉ መድኀኒቶችም አሉን፡፡ ይህ እንግዲህ የሥነ ፍጥረት ምስጢር ነው፡፡ ዘመናዊ ሳይንስ ሊመልሰው የማይችል ነው፡፡ በተለያዩ የሰውነት ክፍሎች ላይ በመቀባት፣ በማሸት የሚሰጥ ህክምናም አለን፡፡ ከወይራ ዘይት ጋር እየተቀላቀሉ የሚሰሩ መድኀኒቶች አሉ፡፡ መድኀኒቶቻችን በሙሉ ግን የሚበሉ፣ የሚጠጡ አይደሉም፡፡ ወደሰውነት ውስጥ የሚገቡ መድኀኒቶች የሉንም፡፡
ይህንን ህክምና ለመስጠት የሚያስችል ፍቃድስ አግኝታችኋል?
አዎን! በማህበራዊና የግል አገልግሎት ዘርፍ ህክምናውን ለመስጠት የሚያስችለን ፈቃድ አግኝተናል፡፡ ለህክምናው መስጫ የሚሆን ክፍልም አዘጋጅተን ለህሙማን መድኀኒት እየሰጠን እንገኛለን፡፡
ለአገልግሎታችሁ የምትጠይቁት ክፍያ እንዴት ነው?
እኛ ቀድሞውኑ አላማ አድርገን የተነሳነው ከህሙማን ገንዘብ መሰብሰብን አይደለም። በዘመናዊ ህክምና መፍትሄ ያላገኙ ህሙማን በባህላዊ መድኀኒት መፈወስ የሚችሉበትን መንገድ ለማመቻቸት ነው፡፡ ለምንሰጠው ህክምና የምንጠይቀው ክፍያ እጅግ አነስተኛና ማንም ሰው በቀላሉ ሊከፍለው የሚችለውን ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በርካታ ህሙማንን ያለምንም ክፍያ በነፃ ስናክም የቆየንበት ሁኔታ ሁሉ ነበር፡፡ የእኛ ዓላማ ህብረተሰቡ በባህላዊ መድኀኒት በቀላሉ ጤናውን ማግኘት እንደሚችል ማሳየት፣ ስለባህል መድኀኒት በሚገባ እንዲያውቅና መድኀኒቱን በራሱ መጠቀም እንደሚችል ማሳወቅ፣ ስለዕፅዋቱ ምንነት፣ ጠቀሜታቸውና አሰራሩ፣ የሚያስከትሏቸውን የጎንዮሽ ጉዳቶች ሁሉ በዝርዝር ለህብረተሰቡ ማሳወቅ ነው፡፡
በዕፅዋትና ባህላዊ መድሃኒቶች ላይ ያደረጓቸውን ጥናትና ምርምሮች አስመልክተው ያዘጋጁት ፅሁፍ አለ?
አዎ፡፡ በዘርፉ ያደረግሁትን ምርምርና ጥናት ሁሉ በፅሁፍ የማስቀመጥ ልምዱ አለኝ፡፡ እንደውም “ባህላዊ መድኀኒትና የጤና አጠባበቅ” በሚል ርዕስ ስር ያዘጋጀሁትና ለህትመት ዝግጁ የሆነ ሦስት ጥራዝ ፅሁፍ አለኝ፡፡ አሁንም እያጠራቀምኩ ነው፡፡ ጊዜው ሲደርስ ወደ መፅሃፍነት ተቀይሮ ህብረተሰቡ እንዲያነበው፣ እንዲማርበትና በቀላሉ ጤናውን ለመጠበቅ የሚችልበትን መንገድ እንዲያውቅበት ለማድረግ እየተዘጋጀሁ ነው፡፡
በአገራችን የባህል መድኀኒቶች በስፋት የሚገኙባቸው አካባቢዎች የትኞቹ ናቸው? በቀላሉ ከሚገኙና ለጤና ጠቃሚ ከሆኑ ባህላዊ መድኀኒቶች መካከል ጥቂቶቹን ቢገልፁልን?
በአገራችን በአብዛኛው የወይንአደጋ አካባቢ ባህላዊ መድኀኒቶች በስፋት የሚገኙባቸው አካባቢዎች ናቸው። በቆላና በደጋ አካባቢዎችም የሚገኙ መድኀኒቶች አሉ። በደብረዘይት ናዝሬትና አካባቢው መድኀኒቶቹ በስፋት ከሚገኙባቸው ቦታዎች የሚጠቀሱ ናቸው። እንደልብ ከሚገኙና በቀላሉ መፍትሄ ከሚሰጡን መድሀኒቶች መካከል ደግሞ እነ ዳማከሴ፣ ጤናአዳምና መሰል ነገሮች ይጠቀሳሉ፡፡ ለምሳሌ ሰናፍጭ ሁላችንም በቀላሉ የምናገኘው ለእባጭ ፍቱን የሆነ መድኀኒት ነው፡፡ እነዚህን በቀላሉ አግኝቶ በመጠቀም ብዙ ገንዘብ ሊያስወጡ ከሚችሉ ቀላል የጤና ችግሮች መፍትሄ ማግኘት ይቻላል።
ዕፅዋቶቹን በኮስሞቲክስ ደረጃ ለመሥራትና ጥቅም ላይ ለማዋል ያደረጋችሁት ሙከራ አለ?
ዕፀዋትን በኮስሞቲክስ ደረጃ ለማዘጋጀት የሚያስችል ጥናት አድርገናል፡፡ ለተለያዩ የቆዳ ችግሮችና ለማድያት የሚውሉ መድኀኒቶችንም ሰርተናል፡፡ ይህን በዘመናዊ መንገድ በኮስሞቲክስ ደረጃ ለመስራትና ጥቅም ላይ ለማዋል ሃሳቡ ቢኖረኝም መሟላት የሚገባቸው በርካታ ጉዳዮች ስላሉ አሁን ባለንበት ሁኔታ ይህንን ማድረግ አልቻልንም፡፡
በአንድ ወቅት ከጫት የወይን መጠጥ ሰርተው ከፍተኛ አድናቆትን አትርፈው ነበር? እሱ ጉዳይ የት ደረሰ?
ልክ ነው፡፡ እሱ ጉዳይ በአጋጣሚ የተደረገ ነበር፡፡ ለመድኀኒት የሚሆን ዕፅዋት ፍለጋ ወደ ደብረዘይት ስሄድ በአጋጣሚ አግኝቼ የገዛሁትን ጫት ወደ ወይን ለመለወጥ የሚያስችል ጥናት አድርጌና የተለያዩ መንገዶችን ተጠቅሜ እጅግ በጣም ጥሩ ጣዕም ያለው ወይን ለመስራት ችዬ ነበር፡፡ ጉዳዩ በወቅቱ ብዙ ትኩረት ስቦ ነበር፡፡ ዶክተር በጫት ወይን ሰርቶ ህዝቡን ሊያሳብደው ነው ሁሉ ብለውኝ ነበር፡፡ የተሰራው መጠጥ ልዩ ጣዕም የነበረው ቆንጆ ነበር፡፡ ወይኑን የቀመሱ በርካታ ሰዎችም የሰጡኝ አስተያየት ይኸው ነበር፡፡ ግን ሥራው የሚሰራው በእጅ (ያለምንም ማሽን) በመሆኑ እጅግ አድካሚና ከፍተኛ ጥንቃቄን የሚጠይቅ ነበር፡፡ እንደውም ወይኑ በተመረተ ሰሞን ከአሜሪካን አገር ስለዚሁ ጉዳይ ሊያነጋግሩኝ ሰዎች መጥተው ነበር፡፡ ስለአሰራሬ በደንብ ከጠየቁኝና ካጠኑ በኋላ ወደአገራቸው ሄደው ጫትን ወደ መርፌነት በመቀየር ከፍተኛ የአዕምሮ መናወፅ ላጋጠማቸው ህሙማን በመስጠት ህሙማኑ ከተያዙበት የጭንቀትና ድብርት ስሜት እንዲወጡ ለማድረግ ችለዋል፡፡ አሁን ከምን አደረስከው ላልሽኝ ሥራው ከፍተኛ ድካምና ጥንቃቄን የሚጠይቅ ሥራ በመሆኑ ለጊዜው እምብዛም አልገፋሁበትም፡፡
የማህፀንና ፅንስ ህክምና ሙያው በቃ ቀረ ማለት ነው?
ኧረ አልቀረም፡፡ ለምን ይቀራል፡፡ ለዓመታት የተማርኩበትና የሰለጠንኩበት ሙያማ አይቀርም፡፡ እሱንም እሰራለሁ፡፡ ግን ህብረተሰቡን ሴት ወንድ ሳይል ላገለግልበት የምችልበት ሙያ የባህል ህክምናው በመሆኑ በዚህ ሙያ የበለጠ ለመስራት እፈልጋለሁ፡፡  
የባህል መድኀኒት ዕውቀትና ጥበብ እንዲስፋፋ፣ ለመጪው ትውልድም እንዲተላለፍ መንግስት ምን ማድረግ አለበት ብለው ያስባሉ? በእርስዎስ በኩል ምን እያደረጉ ያሉት ጥረት አለ?
ኢትዮጵያ ውስጥ ከ80 ሺ በላይ የባህል መድኀኒት አዋቂዎች ያሉ ቢሆንም በማህበር ተደራጅተው ያሉት ግን ከዘጠኝ ሺህ የሚበልጡ አይደሉም፡፡ ይህ ነገር በስፋት ሊሰራበት የሚገባና ህብረተሰቡን፣ መንግስትንም ሆነ አገርን ሊጠቅም የሚችል ትልቅ ተግባር በመሆኑ ትኩረት ተሰጥቶት በአግባቡ ሊሰራ ይገባል ሌሎች አገራት ከባህል ህክምና እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ እያገኙ ነው፡፡ ለምሳሌ ጀርመን በዓመት ከ380 ሚሊዮን ዩሮ በላይ ከባህል መድኀኒት ገቢ ታገኛለች፡፡ በአፍሪካ ውስጥ በስፋት የሚሰራባቸው አገራት ደቡብ አፍሪካና ሞሪሺየስ ዋንኞቹ ናቸው፡፡ እኛ ዕፅዋቱ እያለን፣ ሃኪሙ እያለን አልተጠቀምንበትም፡፡ ስለዚህ ይህን ዕድል በስፋት ለመጠቀም የሚያስችል ሁኔታ ማመቻቸት፣ ሙያው ለትውልድ እንዲተላለፍ ማስተማር፣ በፅሁፍ ማቆየት ያስፈልጋል፡፡ በግሌ ህብረተሰቡን ለማስተማርና በርካታ ፅሁፎች፣ በመፃፍ ሙያውን ለትውልድ እንዲተላለፍ ለማድረግ ጥረት በማድረግ ላይ ነኝ፡፡

በአገር ውስጥ ባለሀብት በአቶ አዲስ ገሠሠና በሆላንዳዊው ባለሀብት በሚ/ር ሚሪያም ቫን አልፈን በአክሲዮን በዱከም ከተማ ኢንዱስትሪ ዞን በ2.5 ሚሊዮን ዶላር ያቋቋሙት ቢ ኮኔክትድ ፕሪንቲንግና ቢ ኮኔክትድ ሌብሊንግ የተባሉ ፋብሪካዎች ሰሞኑን ተመረቁ፡፡
ፋብሪካዎቹን የመረቁት የኢንዱስትሪ ሚ/ር ዴኤታ ዶ/ር መብራህቱ መለስ፣ ፋብሪካዎቹ በኢትዮጵያ በዓይነታቸው የመጀመሪያ እንደሆኑ ጠቅሰው ሁሉም የአገር ውስጥ የጨርቃጨርቅ ፋብሪካዎች በምርት ሰንሰለት ሂደት የጎደላቸውን ፕሪንትና ሌብል በማድረግ እሴት ጨምረው ኤክስፖርት የሚያደርጉትን መጠን እንዲጨምሩ ይረዳቸዋል ብለዋል፡፡
ፕሪንቲንግ ማለት በነጭ ቲ -ሸርት ላይ የተለያየ ምስልና ጽሑፍ በማተም ወደ ውጭ መላክ ሲሆን ሌብሊንግ ደግሞ ከውጭ በሚገቡ ሸሚዞች አንገት ላይ ተሰፍቶ የምናገኘውን የሸሚዙን ቁጥር፣ የተሰራበትን አገር፣ ስሙና (ሞዱን) እንዲሁም በሸሚዙ የጎን ስፌት ላይ የሚገኘውን ሸሚዙ ከምንና ምን ድብልቅ እንደተሰራ፣ እንዴት መታጠብ፣ መድረቅ መተኮስ፣ … እንዳለበት የሚገልፀው የፀሐይ፣ የዳመና፣ የካውያ … ምልክቶች ያሉበት ጨርቅ ማለት ነው፡፡
ምርቶቻቸውን ወደ ውጭ አገር የሚልኩ ሁሉም ፋብሪካዎች ሌብሉን ከውጭ አገር በውጭ ምንዛሪ እንደሚገዙ የጠቀሱት የቢ ኮኔክትድ ኢንዱስትሪየል ጀኔራል ማናጀር ሚ/ር ቫን አልፈን፣ የፋብሪካቸው አጠቃላይ የኤክስፖርት መጠን እንደሚጨምር እናምናለን ብለዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በመላው ዓለም ከሚሸጡ ቲ-ሸርቶች ውስጥ ከመቶ 70 ህትመት ያለባቸው ሲሆኑ በነጭነታቸው የሚሸጡት ከመቶ 30 መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
እጅግ ዘመናዊ የሆነው የህትመት ፋብሪካችን 800 ሜትር ርዝመት ባለው ስክሪን ጠረጴዛና ከፍተኛ ደረጃ ባለው እንግሊዝ ሰራሹ ሞላላ መሳሪያ በቀን 80, 000 ያትማል ያሉት ጀነራል ማናጀሩ፣ የሌብሊንግ መሳሪያቸው ደግሞ በዓለም ታዋቂ በሆነው ስዊዘርላንድ ሰራሹ ሙለር መሳሪያ የተለያዩ የሽመና ሌብሎች እንደሚያመርቱ ተናግረዋል፡፡
የፋብሪካዎቹ ዋና ዓላማ ከትርፍ ባሻገር የእውቀት ሽግግር ነው ያሉት አቶ አዲስ፣ በተለያዩ የኢንጂነሪንግ ዘርፎች በኤሌክትሪካል፣ በኬሚካል፣ በማሽነሪ፣ … ዘጠኝ ኢንጂነረች ወደ ቤልጂየም፣ ስዊዘርላንድና ቻይና ልከው ስለመሳሪያዎቹ አጠቃቀምና ጥገና በሚገባ ሰልጥነው ወደ አገራቸው ተመልሰው እየሰሩ ስለሆነ በቀሰሙት እውቀት ሌሎች 400 የፋብሪካው ሰራተኞች እንደሚያሰለጥኑ ገልፀዋል፡፡
አቶ አዲስ፣ ሸሪካቸው ሚ/ር ቫን አልፈን የሚያንቀሳቅሱት የቤተሰብ ኩባንያ እንደሆነ ጠቅሰው በተለያዩ የኤስያ አገራት ሰባት ፋብሪካዎች እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ ይህኛው በአፍሪካ የመጀመሪያው ሲሆን ባለሀብቶቹ ኢትዮጵያን ስለወደዱ ከባንክ ሳይበደሩ በራሳቸው ገንዘብ በ5 ወራት የፋብሪካዎቹን ግንባታ አጠናቀው ማስመረቃቸውን አስረድተዋል፡፡
ሚ/ር ቫን አልፈን በተለያዩ ኩባንያዎች ከ50 በላይ ፈቃድ ስላላቸው ቢ ኮኔክትድ ኢንዱስትሪያል እቅዱ መቶ ፐርሰንት ኤክስፖርት ቢሆንም የአገር ውስጥ ፋብሪካዎች በቀጥታም ባይሆን የምርቱ ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተገልጿል፡፡

 ዲፊድ ፕሮጀክቱ ተጽዕኖ ፈጣሪ መሆኑ በመረጋገጡድጋፍ ይገባዋል ብሏል

    የእንግሊዝ አለም አቀፍ የልማት ድርጅት (ዲፊድ)በኢትዮጵያ የልጃገረዶችን አቅም ለመገንባት ታስቦ
ተግባራዊ በመደረግ ላይ ለሚገኘው “የኛ” ፕሮጀክትሁለተኛ ምዕራፍ ማስፈጸሚያ ሊሰጠው ያሰበው
ተጨማሪ የ16 ሚሊዮን ፓውንድ የገንዘብ ድጋፍተቃውሞ እንደገጠመው ዴይሊ ሜይል ዘገበ፡፡ገንዘቡን የሚረዳው ዲፊድ በበኩሉ፤ በፕሮጀክቱ ላይባደረገው ግምገማ አዎንታዊ ተጽዕኖ እያሳደረና ተጨማሪልጃገረዶች ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ እያበረታታቸውመሆኑን የሚያሳዩ ውጤቶች ማግኘቱን ገልጾ፣ ገንዘቡመሰጠቱና ፕሮጀክቱ በቀጣይነት መደገፉ አግባብነትአለው ብሏል፡፡ዲፊድ 54 ሚሊዮን የእንግሊዝ ፓውንድለተመደበለት የገርል ሃብ ፕሮጀክት ሁለተኛ ምዕራፍማስፈጸሚያ የሚውል ተጨማሪ 16 ሚሊዮን ፓውንድለመስጠት መወሰኑን በይፋ ለመግለጽ በዝግጅትላይ መሆኑን የጠቆመው ዴይሊ ሜይል፤ የእርዳታተጽዕኖዎችን የሚያጠና አንድ የአገሪቱ ገለልተኛኮሚሽን ግን፣ የፕሮጀክቱ የስራ ሃላፊዎች የፕሮጀክቱንውጤታማነት በተጨባጭ ማሳየት እስካልቻሉ ድረስየገንዘብ ድጋፉን እንዲያቋርጡ ለሚመለከታቸውሚንስትሮች ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል ብሏል፡፡ገለልተኛ ኮሚሽኑ ከትናንት በስቲያ ያወጣውንሪፖርት ጠቅሶ ዴይሊ ሜይል እንደዘገበው፤ ዲፊድ የገርልሃብን ውጤታማነት ሚያረጋግጥና ተጨማሪ የገንዘብድጋፍ ለማድረግ የሚያስወስነው ከገለልተኛ አካል የተገኘማስረጃ የለውም ብሏል፡፡ፕሮጀክቱ በናይጀሪያ በተለያዩ ምክንያቶች ውጤታማአለመሆኑ በሁሉም አካላት ዘንድ መታመኑን የገለጸውሪፖርቱ፣ በ ኢትዮጵያ ወ ይም በ ሩዋንዳም የ ፕሮጀክቱን ውጤታማነት በተመለከተ የሚቀርቡ ማስረጃዎችአስተማማኝ አይደሉም ብሏል፡፡የእንግሊዝ የግብርከፋዮች ማህበር ዋና ስራ አስፈጻሚ ጆናታን አይሳቢበበኩላቸው፣
የእንግሊዝ ባለስልጣናት ተገቢነታቸውአጠያያቂ በሆኑ የሌሎች አገራት ፕሮጀክቶች ላይይሄን ያህል ከፍተኛ ገንዘብ እንዲባክን መተባበራቸው፣የአገሪቱን ግብር ከፋዮች እጅግ የሚያስደነግጥ አስገራሚጉዳይ ነው ማለታቸውን ዘገባው ገልጿል፡፡ ገርል ሃብከናይኪ ፋውንዴሽን ጋር በጥምረት የሚተገበር መሆኑንና
እስካሁንም ከእንግሊዝ ግብር ከፋዮች የተሰበሰበ 27.1ሚሊዮን ፓውንድ በድጋፍ ማግኘቱን ስታወሰውሪፖርቱ፣ የፕሮጀክቱ አስተዳደር እንደሚያሳስበው ጠቅሶ፣ናይኪ ሃላፊነቱን በአግባቡ መወጣቱም አጠያያቂ ነውብሏል፡፡ የፕሮጀክቱ ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ ፕሮጀክቱየአፍሪካውያን ልጃገረዶችን ህይወት ለማሻሻል ታስቦመተግበር ከጀመረበት እ.ኤ.አ 2010 ጀምሮ፣ በሚሊዮኖችየሚቆጠሩ በድህነት ውስጥ የሚኖሩ ልጃገረዶችን፣ ወጣትወንዶችንና አዋቂዎችን ተጠቃሚ ያደረጉ የማህበራዊናየግንዛቤ ለውጥ ስራዎችን አከናውነናል ብለዋል፡፡“ለአብነትም በኢትዮጵያ በመተላለፍ ላይ የሚገኘውንየኛ የሬዲዮ ድራማና ቶክ ሾው ከሚከታተሉ ልጃገረዶች መካከል 84 በመቶው በራስ መተማመናቸውንለማሳደግ እንደረዳቸው ማረጋገጣቸውንና 76 በመቶየሚሆኑትም ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ እንዳነሳሳቸውመመስከራቸውን መጥቀስ ይቻላል” ብለዋል ቃል

  በደራሲ ተወልደ ሲሳይ የተፃፈው “77” የተሰኘው በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተ ልብወለድ መፅሃፍ ሰሞኑን ለገበያ ቀረበ፡፡ መፅሃፉ መቼቱን በ1977 በኢትዮጵያ በተከሰተውና በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ዜጎችን በፈጀው ድርቅና ረሃብ ላይ ያደረገ ነው ተብሏል፡፡
ደራሲው የመፅሃፉን መታሰቢያነት በ1977 ድርቅና መከራ ምክንያት ህይወታቸው ላለፈ፣ ህይወት ለተመሰቃቀለባቸውና በአጠቃላይ የወቅቱ ሰለባ ለሆኑ ኢትዮጵያውያን አድርጓል፡፡ በ 363 ገፆች የተቀነበበው መጽሐፉ፤ ለአገር ውስጥ በ75 ብር፣ ለውጭ አገር በ20 ዶላር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡

በፊልም ጥበብ ባለሙያው ሰለሞን በቀለ ወያ የተዘጋጀው “የፊልም ዝግጅት ቴክኒክና ጥበብ” 1ኛ መፅሃፍ በትላንትናው ዕለት በጀርመን ባህል ተቋም (ገተ ኢንስቲቲዩት) ተመርቋል፡፡
መፅሃፉ በፊልም አሰራር፣ ቴክኒካዊ ጥበብና በፊልም አዘገጃጀት ዙሪያ የቀረበ ትምህርታዊ መፅሃፍ ሲሆን ደራሲው በዘርፉ የካበተ የማስተማር ልምድ ያላቸው መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
ደራሲው በሃገር ውስጥና በውጭ ሃገር ዩኒቨርሲቲዎች ከፊልምና ከስነፅሁፍ ጋር የተያያዙ ትምህርቶችን በተለያዩ የዲግሪ ደረጃዎች የተማሩ ሲሆን ታዋቂ በሆኑ አለማቀፍ የፊልም ፌስቲቫሎች ላይም በዳኝነት መስራታቸው ተገልጿል፡፡
ባለሙያው ለበርካታ ዓመታት በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር ጥናታዊ ፊልሞችን የሰሩ ሲሆን በሀገሪቱ የመጀመሪያው እንደሆነ የሚነገርለትን “አስቴር” የተሰኘውን ባለ 35 ሚ.ሜ ልብ ወለድ ፊልም በደራሲነት እና በዳይሬክተርነት አዘጋጅቶ በማቅረብና በሲኒማ ቤቶች ለረጅም ጊዜያት እንዲታይ በማድረግም ውጤታማ ስራ መስራታቸው ተጠቅሷል፡፡
በአሁን ሰዓት ደራሲው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሂውማኒቲስ ኮሌጅ የውጭ ቋንቋዎች ክፍል በዘመናዊ የአውሮፓ ቋንቋዎች ዩኒት ውስጥ በማስተማር ላይ የሚገኙ ሲሆን የተለያዩ የፊልም ጥበብ ስልጠናዎችን እንደሚሰጡም ታውቋል፡፡

 በደራሲ እያዩ ደባስ የተፃፈው “ሁለት ገፅ” የተሰኘ ረዥም ልቦለድ መፅሃፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ ደራሲው በመግቢያው ላይ ባሰፈረው መልዕክት፤ “ተረጋጉ፤ አትረበሹ፤ አትጨነቁ፡፡ ስለማንም ቢሆን ክፉ አታስቡ፡፡ መልካምነት ከጉያችሁ ስር ያለ ቅርባችሁ ነው፡፡ በእናንተ ውስጥ ትልቅ ኃይልና መሰጠት አለ፡፡ ያንን ፈልጉ፡፡ ሰዎችን አትመልከቱ፡፡ ራሳችሁን እዩ…” እያለ ይቀጥላል፡፡
በ171 ገፆች ተሰናድቶ የቀረበው መፅሃፉ፤ በማራኪ የታሪክ ፍሰትና አወቃቀር ተሰናስሎ የቀረበ መሆኑን ደራሲው ጠቁሟል፡፡ ከሚቀጥሉት ሥራዎቹ ቀዳሚ ያላቸውንም “የሶርዲኒያሞቹ ምዛዥ”፣ “ቤንዚኒስ” እና “አሽዶዳውያን” በሚል ጠቅሷል፡፡

“ግጥም ሙዚቃና ስዕል፤ ልዩነትና ተዛምዶ” በሚል ርዕስ በነገው ዕለት በብሔራዊ ቤተ መፅሐፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ከቀኑ 8 ሰዓት ተኩል ጀምሮ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ አስታወቀ፡፡
ለውይይት መነሻ ሃሳብ የሚያቀርበው ገጣሚ ኤፍሬም ስዩም ሲሆን በዝግጅቱ ላይ ገጣሚያን፣ ደራሲያን የሙዚቃ ባለሙያዎችና የጥበብ ቤተሰቦች እንደሚገኙ ተጠቁሟል፡፡
የውይይት ፕሮግራሙን ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ከኢትዮጲስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር ያሰናዳው ሲሆን ከውይይቱ በተጨማሪ የመፃሕፍት ንባብ መርሃ ግብርም የዝግጅቱ አካል እንደሆነ ታውቋል፡፡