Administrator

Administrator

Monday, 03 November 2014 09:06

የፀሃፍት ጥግ

ስለ ወህኒ ቤት

የትምህርት ቤትን በር የሚከፍት ሰው፣ በሌላ እጁ የወህኒ ቤትን በር ይቆልፋል፡፡
ቪክቶር ሁጐ
አሜሪካ ሁለተኛ ዕድል የምትሰጥ አገር ናት፡፡ የወህኒ ቤት በር ሲከፈት፣ ፊት ለፊት የተዘረጋው መንገድ ወደተሻለ ህይወት የሚመራ መሆን አለበት፡፡
ጆርጅ ደብሊው ቡሽ
ፍፁም ደህንነት ከፈለግህ ከርቸሌ ሂድ፡፡ እዚያ ትቀለባለህ፣ ትለብሳለህ፣ ህክምና ታገኛለህ…ወዘተ፡፡ ከርቸሌ የሌለው ነፃነት ብቻ ነው፡፡
ድዋይት ዲ. አይዘንአወር
በእኔ አገር መጀመሪያ እንታሰራለን፤ ከዚያ ፕሬዚዳንት እንሆናለን፡፡
ኔልሰን ማንዴላ
ወህኒ ቤት ፈጣሪን እንድፈልገው አላደረገኝም፤ ሁሌም አጠገቤ አለ፡፡ እስር ቤት ውስጥ ሊከረችሙብኝ ይችላሉ፤ ነገር ግን መንፈሴና ፍቅሬ በእስር ቤት ግድግዳዎች ሊታጠሩ አይችሉም፡፡
ሊል ዋይኔ
በአንድ ወቅት ወህኒ ቤት ያገኘሁትን ሰውዬ ምን ሰርቶ እዚያ እንደመጣ ጠየቅሁት፡፡ ጫማ ሰርቆ መታሰሩን ነገረኝ፡፡ የባቡር ሃዲድ ብትሰርቅ ኖሮ የአሜሪካ ሴናተር ትሆን ነበር አልኩት፡፡
ሜሪ ሃሪስ ጆንስ
ሴቶች አሁን ብዙ ምርጫዎች አሏቸው፡፡ ማግባት ወይም አለማግባት፣ ሥራ መያዝ ወይም አለመያዝ፣ ልጆቻቸውን ይዘው እንዳገቡ መኖር ወይም ሳያገቡ ከልጆቻቸው ጋር መኖር፡፡ ወንዶች ግን ሁሌም የነበረው ተመሳሳይ ምርጫ ነው ያለን - ሥራ ወይም ከርቸሌ፡፡

ቲም አለን
     

በመጪው ጥር ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ይደረጋል
ከደ/አፍሪካው ዴክለርክ በኋላ የመጀመሪያው ነጭ አፍሪካዊ መሪ ናቸው

        ዛምቢያን ላለፉት ሶስት አመታት ያህል ያስተዳደሩት ፕሬዚዳንት ሚካኤል ሳታ፤ ባለፈው ማክሰኞ በ77 አመታቸው ከዚህ አለም በሞት መለየታቸውን ተከትሎ፣ አገሪቱ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ በነጭ ጊዜያዊ መሪ መተዳደር መጀመሯን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ለንደን ውስጥ በሚገኝ ሆስፒታል ህክምናቸውን ለሳምንታት ሲከታተሉ የቆዩት ሳታ መሞታቸውን ተከትሎ  የዛምቢያ መንግስት ምክር ቤት በጠራው አስቸኳይ ስብሰባ፣ በአገሪቱ ህገመንግስት በተቀመጠው መሰረት በቀጣዮቹ ሶስት ወራት ውስጥ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ማካሄድን ጨምሮ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር በሚደረግበት ሁኔታ ላይ የመከረ ሲሆን፣ ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው ሲሰሩ የቆዩትን ጋይ ስኮት ጊዜያዊ መሪ አድርጎ መርጧል፡፡
ሟቹ ፕሬዚዳንት በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ ለህክምና ወደ እንግሊዝ ሲሄዱ፣ አገሪቱን በተጠባባቂነት የመምራቱን ሃላፊነት ለመከላከያ ሚኒስትሩ ኤድጋር ሉንጉ ሰጥተው እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ ሞታቸውን ተከትሎ ግን፣ በሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ ምርጫ እስከሚካሄድና አዲስ ፕሬዚዳንት እስኪመረጥ ድረስ፣ ጋይ ስኮት አገሪቱን በጊዜያዊነት እንዲመሩ ተመርጠዋል፡፡እ.ኤ.አ በ2001 “ፓትሪዮቲ ፍሮንት” የተባለውን ፓርቲ በመቀላቀል በወቅቱ በተካሄደው ምርጫ በምክትል ፕሬዚዳንትነት ተመርጠው ሲሰሩ መቆየታቸውን ያስታወሰው ቢቢሲ፣ የስኮትላንድ ዝርያ ያላቸውና ወላጆቻቸው ከዛምቢያ ውጭ የተወለዱ በመሆናቸው የአገሪቱ ህገመንግስት ስለሚከለክላቸው በመጪው ጥር በሚካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ላይ ላይሳተፉ እንደሚችሉም ገልጿል፡፡
የ60 አመቱ የካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ ምሩቅ ጋይ ስኮት፣ ከደቡብ አፍሪካው መሪ ዴክለርክ በኋላ አንድን የአፍሪካ አገር ለመምራት የቻሉ የመጀመሪያው ነጭ መሪ እንደሆኑ ተነግሯል፡፡
ሟቹ ፕሬዚዳንት ሳታ ላለፉት አራት ወራት ከአደባባይ መራቃቸውን ተከትሎ፣ የከፋ ህመም ላይ ወድቀዋል የሚል ወሬ በስፋት ሲናፈስ መቆየቱን ዘገባው አስታውሶ፤ ፕሬዚዳንቱ በመስከረም ወር አጋማሽ በተከናወነው የአገሪቱ ፓርላማ የመክፈቻ ስነስርአት ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፣ የከፋ የጤና ችግር ላይ ናቸው በሚል በስፋት የተሰራጨውን ወሬ በተመለከተ ዘና ያለ ምላሽ ሰጥተው ነበር - “እስካሁን አልሞትኩም” በማለት፡፡ከዚህ የመክፈቻ ስነስርዓት በኋላ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የኒውዮርክ ጽህፈት ቤት ሊያደርጉት የነበረው ንግግር መሰረዙን ተከትሎ በአሜሪካ ባረፉበት ሆቴል ውስጥ ህክምና እየተደረገላቸው እንደነበር ፖሊስ አስታውቶ ነበር፡፡የአገሪቱ መንግስት ፕሬዚዳንቱ በውጭ ሃገር እየታከሙ እንደሚገኙ ከመግለጽ ባለፈ፣ የት አገር እንደሚገኙ ሳይጠቁም መቆየቱንና የዛምቢያ ተቃዋሚ ቡድኖችም ፕሬዚዳንቱ አገሪቱን የመምራት ብቃት እንደሌላቸው ሲናገሩ እንደነበር ዘገባው አስታውቋል፡፡
የተባ አንደበት ባለቤት ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ በአገሬው ዘንድ ‘ንጉስ ኮብራ’ በሚል የቅጽል ስም የሚጠሩትና በተቃዋሚ ፓርቲ አባልነት ለፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ለሁለተኛ ጊዜ ተወዳድረው በ2011 ስልጣን የያዙት አምስተኛው የዛምቢያ ፕሬዚዳንት ሳታ፤ ታጋሽነት የሚጎላቸው መሪ ናቸው” በሚል ሲተቹ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ፕሬዚዳንቱን ለሞት የዳረጋቸው ህመም ምን እንደሆነ የታወቀ ነገር የለም፡

ባለፈው ማክሰኞ በምስራቃዊ ቨርጂኒያ ውስጥ ከሚገኝ ማዕከል ተነስታ ወደ ህዋ ጉዞ በጀመረች በሰከንዶች ጊዜ ውስጥ የፍንዳታ አደጋ የደረሰባት ሰው አልባ ሮኬት ስብርባሪዎች በሰዎች ላይ የጤና ጉዳት ስለሚያደርሱ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባ ባለሙያዎች አስጠነቀቁ፡፡
የጠፈር ምርምር ቁሳቁሶችን ወደ አለማቀፉ የጠፈር ጣቢያ ለማጓጓዝ አወዛጋቢ በሆነ ሁኔታ ከናሳ ጋር ስምምነት ላይ የደረሰው “ኦርቢታል ሳይንስስ” የተባለው ተቋም ምክትል ፕሬዚዳንት ፍራንክ ከልቤርስቶን፤ በድንገተኛ ፍንዳታ በእሳት የጋየችውን ሮኬት ስብርባሪ መንካት፣ ሮኬቷ ጭናቸው በነበሩ አደገኛ ቁሳቁሶች ምክንያት ለጤና እክል የሚያጋልጡ ስለሆኑ አስፈላጊው ጥንቃቄ እንዲደረግ መምከራቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
“አደጋው በተከሰተበት አካባቢ ለሚንቀሳቀሱ ሁሉ የማስጠንቀቂያ መልዕክቴን አስተላልፋለሁ፡፡ አደጋ የደረሰባት ሮኬት በርካታ አደገኛ ቁሳቁስ ጭና ነበር፡፡ ስብርባሪዎችን ፍለጋ ወደ ስፍራው መንቀሳቀስ አደጋ አለው፡፡” ብለዋል ከልቤርስቶን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፡፡
ማንም ሰው በአካባቢው ወድቆ ያገኘውን ማንኛውንም አይነት ቁስ ከመንካት እንዲቆጠብና ሌሎችም ከአካባቢው እንዲርቁ በማድረግ፣ ለሚመለከታቸው የስራ ሃላፊዎች ጥቆማ እንዲሰጥም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
2ሺ 200 ኪሎ ግራም የሚመዝን ጭነት የያዘ መንኮራኩር ይዛ ጉዞ የጀመረችውን ሮኬት ለአደጋ ያጋለጣት ምክንያት እስካሁን አልታወቀም፡፡ ሮኬቷና መንኮራኩሩ 123 ሚሊዮን ፓውንድ እንደሚያወጡ ዘገባው ገልጿል፡፡

Monday, 03 November 2014 08:11

የአዳም ረታ ሃሳቦች

ስለስኬታማ ደራሲነት

         ስኬታማ ደራሲ ላልከው አንፃራዊነት ለሚንከባከቡ፣ ከጥናትም ይሁን ከግል ስሜትና ፍላጎት ተነስተው ለሚፈርዱ ወይም ለሚያደሉ ቦታውን ብለቅ ይሻላል፡፡ ስኬታማ የሚለውን ቃል ሙሉ ፍቺ አይናአፋር የተጠየቅ ቅንፍ ውስጥ ልክተተው፡፡
ስኬታማነት ተነቃናቂ ኢላማ ነው፡፡ ማታ ላይ አጠናቅቄ በሰራሁት ድርሰት ረካሁ ብዬ ብተኛም፣ ሲነጋ ቅር የሚሉኝ ነገሮች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ከአመታት በፊት በፃፍኩት ዛሬ ላልደሰት እችላለሁ፡፡ የስኬታማነት መለኪያዎች አስራ አስር ናቸው፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው አገሩ ውስጥ መኖሩን ወይም አለመኖሩን የስነ-ፅሁፍ ስኬታማነት መገምገሚያ ማድረግ ምስፋርን/ስፍራን (place) ብቻ የብቃት መለኪያ ማድረግ ነው፡፡ ይሄ ነጠላ ብቆታ በአብዛኛው ከውጤቱ ወይም ከድርሰቱ ውጭ ያለ ነው፡፡ የተለያዩ የስፍራ መደቦች አሉ፡፡ የግል ስፍራ አለ (Personal space)፣ የቤትህ፣ የቀበሌህ ስፍራ፣ ወዘተ … አለ፡፡ በተጨማሪም ደራሲው በኢምንትነቱ የሙሉኩሌው ወይም የወተትማው መንገድ አባል ነው፡፡ ግንባሩ በሶላር ፍሌርስ ይግላል፣ በበጋ በሚመጣ ዝናብ የሚከረስስ ቆዳ አለው፡፡ በምድር የመግነጢስ መረብ ይረግባል፣ ይወጠራል፡፡
አንድ ደራሲ ዋናው መሳሪያው ምናቡ ነው፡፡ ግን ነባር ልዩ ቦታህ በነበርክ ጊዜ በስርነቀል ልምድ ውስጥ እንድታልፍ ደንብ መሰለኝ (ይሄ ልምድ ፖለቲካ ብቻ መሆን የለበትም፡፡ ብዙ ጊዜ አንድ የልምድ ዝርያ ላይ ብቻ በማተኮርና ለዛም የማይገባውን ክብደት ብቻ በመስጠት በልምድ የመብሰል መለኪያ ሊደረግ ይሞክራል፡፡ ይሄ አድልኦ ነው፡፡)
ትተኸው (በእርግጥ ትተኀዋል ወይ?) የሄድከው ህብረተሰብ ውስጡ ምን ይመስል እንደነበር በመጠኑም ቢሆን መረዳት አለብህ፡፡ የትኛው ክስተትና ዕውነታ ነው ውዝፍ? (constant) የትኛው ነው ተለዋዋጩ? የቱ ነው ፈዞ/ተለውጦ የሚጠብቅህ? አለዋወጡ የሚገዙት የግንጵሊት ንጥረ ነገሮቹ (elements of metamorphosis) ምንድናቸው? ወዘተ…
ብዙ ብሑት (innovators) የሚባሉ የባዕድ ደራሲዎች ትልልቅ ድርሰቶቻቸውን የፃፉት ከትውልድ አገራቸው ውጭ ሆነው ነው፡፡ እንደውም አንዳንዴ ስለ ራሳቸው አገር በጠለላቸው አገር ቋንቋም ይፅፋሉ፡፡ ወሳኙ ያሳለፍከው የልምድ ስፋትና ጥልቀት፣ ለዚያም ያለህ ግንዛቤና በንቁነት ወይም በኢ-ንቁነት የምታነሳቸው ንፅፅሮች ናቸው እንጂ አካላዊ ዕርቀትና ቅርበት መለኪያ አይደለም፡፡
በራስህ ከምትገነዘበው፣ ተገንዝበህ የምታሰላስለው፣ አሰላስለህ መደምደሚያ የምትወስድበት፣ አንድ ተራ የመሰለ ድርጊት/ገጠመኝ ሰዎችን በግል ብቻ ሳይሆን ስርአት ውስጥ ያላቸውን ባህርይ እንድትረዳ ሰፊም ይሁን ጠባብ መንገድ ይከፍትልሃል፡፡ በስደት ስኖር በእርግጥ አዲስ የረቀቀ የስነፅሁፍ መሰረተልማት (Infrastructure) ውስጥ እገባለሁ፡፡ እነዚያ መኖራቸውን ታያለህ ግን ለእኔ ስራ መመጠናቸውን ማመዛዘን አለብኝ፡፡ ንፅፅር ያልኩት ይሄንን ነው፡፡
ባዕድ አገር ሆኜ ኢትዮጵያ ውስጥ ስላለ የቄስ ትምህርት ቤት ዘመን ብፅፍ በግል ተዘክሮዬ ይዤው የመጣሁት የመረጃ ወይም የዕውነታ አንኳር አለ፡፡ ዝርዝሩ ምናብ ነው፡፡ ጥቂት የሚታወሱ ነጥቦች አንስተህ እነዚያን ሚዛን በመጠበቅ የማያያዝና ጊዜ - ዘላይ ጭብጥ የማስነከስ ነው፡፡ ከልጅነቴ አርባ አመታት እርቄአለሁ በሚል ስለ ልጅነት ልብወለድ የመፃፍ መብቴን አላነሳም፡፡ የተወለድኩት አዋሳ ነው፣ አዲስ አባ መጥቼ ለምን ስለ አዋሳ እፅፋለሁ? ብዬ በቦታ መሸጋሸግን ወሳኝ አላደርግም (በአገር ውስጥ ስደት)፡፡ ይሄን መሰረታዊ ነጥብ ሃያሲው ከሳተ የቀረበው ትችት ሳይሆን ስህተት ፍለጋ ነው፡፡ የልጅነታችን ቦታዎችና ጊዜዎች ኢትዮጵያ ውስጥ እንኩዋን ብንሆን ሁሉንም ትተናቸው ሄደናል፡፡ ሁሉም ደራሲ ላለፈው ዘመንም ይሁን ቦታ/ስፍራ በሆነ ደረጃና መልክ ባዕድ ነው፡፡ ቦታዎችም እንደ ሰው ይለወጣሉ፡፡ እንደ ደራሲው እንደ ራሱ እና እንደ ገፀባህርያት፡፡ ልበወለድ ዶክመንታሪ አይደለም፡፡

ስለግንዛቤውና አፃፃፉ
የተወሳሰቡ ልምዶች አሳልፌአለሁ፡፡ በእኔ የተፈጠሩ ወይም በሌሎች ተየሰጡኝ፡፡ (ምርቃትም ይሁን እርግማን) አስከፊም ይሁን ደስ የሚሉ፡፡ እነዚህን ልዘረዘርልህ አልችልም፡፡ ብዙም ናቸው፤ ጥቂትም ናቸው፡፡
በባህርዬ በደንብ አያለሁ፡፡ አድልዖ አላደርግም፡፡ ይሄ ሁኔታዎች በነፃነት ለእኔ እንዲከሰቱ ያደርጋል፡፡ በጣም የሚሞቅ ፀሐያማ ቀን ባልወድም ፀሐይ ውስጥ እቆማለሁ፣ አለመውደዴን አጠናለሁ፡፡ እሱንም አወጣና አወርደዋለሁ፡፡ የሆነ የዜን ዝንባሌ (zen attitude) እይዛለሁ፡፡ ያለ ይሉኝታ (ምን መሆኔ ነው? ሰዎች ምን ይሉኛል?) ሳልል ለማየው ህያው ወይም ጎፍ (physical) አለም ራሴን በመስጠት ነው፡፡
ቅን መሆን አለብህ፡፡ ይሄን ደሞ አስበህ አታመጣውም (የሚያደርጉትይኖራሉ፡፡) ጥንቁቅ አይደለሁም፡፡ ዕቅድ የለህም፡፡ መረጃዎችን ብቻቸውን ሳይ (መገንዘገብ) ከፍፁም ግንኙነት አርቃቸዋለሁ ማለትም አይደለም፡፡ ያኔውኑ በፍጥነት ሊከሰትባቸው የሚችሉ አውታሮችን አስባለሁ፣ ወይም በትካቴ ይመጣሉ፡፡ በቀለ የተባለ ረዥም ልጅ ስልክ እንጨት ሊያስታውሰኝ ይችላል፡፡ ስልክ እንጨቱን ሳይ በቀለ ትዝ ሊለኝ ይችላል፡፡ አልማዝን ሳይ ቄጤማ ትዝ ሊለኝ ይችላል፡፡ የትርሲትን ድምፅ ስሰማ ሚጥሚጣ፣ ቁሶቹን ሳይ ደሞ አልማዝና ትርሲት፡፡ ዝርው የመሰለው ነገር በተለዋጭና በንፅፅር ስርአት ውስጥ ይገባል፡፡ ነጠላነትና ውህድነት በአያዎነት ይተገበራሉ፡፡ የመገንዘብ አድልኦ (Cognitive bias) ብዙ ነገር የመፃፍ ግላዊ ነፃነትህን ሊጋፋ ይችላል፡፡ በእኛ አገር ያልተነገረለት ሳንሱር ይሄ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ወሳኝም ይሆናል፡፡
እነዚህ በእንግሊዘኛው ተሳፋሪነት (bandwagon effect) ፣ የጥማድ ህልዮ (group think) የጂም ባህርይ (herd behavior) ፣ ምናምን የሚባሉ ናቸው፡፡
ይሄ ወደ ስሜት ህዋስ አድልዖ (observational bias) ወይም የፅንሰ ሃሳብ አድልዖ (Conceptual bias) ይወስዳል፡፡ ብዙ ሰው ስለሚያደርገው ላድርገው ብዬ ማድረግ፣ ያለ ዝርዝር ብቆታ መርጬ ማየት፣ እኔ ነገሩ ገብቶኛል ብዬ ከመጀመሪያው የማየውን ነገርና የምሰማውን ወስኜ በራሴም ይሁን በሌሎች ትርጓሜ መጥኜ ማስቀመጥና የግል/የቡድን እሴቴን ወይም ሕልዮዬን የማየው/የምገነዘበው/ ጉዳይና ነገር ላይ በጫና ማሸጋገር ከእውነታው ስለሚያሸሹኝ አልጠለልባቸውም፡፡
ሁሉ ነገር ለደራሲ መረጃ ነው፡፡ መረጃ ስል በተጨባጭ የማየው (በራሴ የስሜት ህዋሶች)፣ ከሰው የምሰማው፣ የማነበው፣ በህልሜ የማየው፣ የምቃዠው ሊሆን ይችላል፡፡ ለእኔ ክብደትና መራሂነት ያለው የመጀመሪያው ነው፡፡ አንዳንድ የመረጃ አንኩዋሮች ጥቅጥቅ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እሴታቸው ቸኩሎ ላይከሰት ይችላል፡፡ ዛሬ ያነጫነጨኝ ልምድ ነገ ሊያስቀኝ ይችላል፡፡ ትናንት አደገኛ ያልመሰለህ ልምድ ቆይቶ አደገኛነቱ ይከሰታል፡፡ ዛሬ አደገኛ የመሰለ ልምድ ነገ ምቹ ሊሆን ይችላል፡፡ የአንዳንዱ ተራ የመሰለ ተፅዕኖ ወደ ድንጋግ የለሽ (ዳርቻ የለሽ) መረጃ ሊፈነዳ ይችላል፡፡ የማደርገው ከፈነዳ በሁዋላ የተበታተኑ የኩነት ፍንጣሪዎችን ወይም ዛላዎችን በማያያዝ መስራት ነው፡፡ …

ቅርፅና ይዘትን በተመለከተ
ዘመናዊ ደራሲዎች በየትም አገር በተለያየ መልክ የአገራቸውን የጥንት ተረቶች ለድርሰቶቻቸው ቅርፅና ይዘት መስሪያ ተጠቅመውባቸዋል፡፡ ይሄ መሸጋገር (translation) ብዙ ጊዜ ግን ከትረካ ወደ ትረካ ነው፡፡ ከድርሳን ወደ ድርሳን ነው፡፡ ከተረት ወደ ተረት ነው፡፡
“ግራጫ ቃጭሎች” የተባለው የመጀመሪያ ልብወለድ እዚህ ይመጣል፡፡ ይሄ መጽሐፍ ዋናውን ታሪክ በሚያጅቡ ንዑስ ታሪኮች በህዳግ ማስታወሻዎች፣ በቁርጥራጭ መረጃዎች፣ በአንዳንድ  የቁዘማ ውጤቶች አጀብ የተሰራ ነው፡፡ ይሄ ቅርፅን ለማደን መጣር አይደለም፡፡ ሁልጊዜ በደቡላወዊ (dualistic) ስልት ስለምናስብ እንጂ፣ ቅርፅና ይዘት የተናጠል ቦታ የላቸውም፡፡ እዚያና እዚህ አይደሉም፡፡
አንድ ላይ የሚተገበሩ ናቸው፡፡ በፍልስፍናም ይሁን ሃይማኖቶቻችን በምድራሶቻቸው (hermeneutics) ሁልጊዜ ባለቤትና ተሳቢ (Subject – object) ክፍፍል ላይ ስለሚያተኩሩ ከዚያ የተበደርነው ይሆናል፡ እንጀራ ጠንካራ የልዋጭነት እሴት አለው (metaphorical value)፡፡ ለመፃፊያ ሞዴልነት ለመጠቀም ይመቻል፡፡
ሞዴል ሲደረግ ከእንጀራነት ይላቀቅና ንፁህ ጂኦሜትሪ ይሆናል፡ ብዙ ጊዜ ሞዴሎች ከሚያጠኑት ጉዳይ የበለጠ ወይም የሚስተካከል ውስብስብነት ይኖራቸውና ራሳቸው መልሰው ችግር ይሆናሉ፡፡ እንጀራ እንደ ሞዴል የቀላልነቱ ምክንያቶች እነዚህ ናቸው፡፡
1/እንጀራ የተሟላ አይነት ውክልና አለው፡፡ ይታያል (እንደ ስዕል)፣ ይነካል፣ ይቀመሳል፣ እናም ይበላል፡፡ የመጨረሻው ፀባዩ የተለየ ያደርገዋል፡፡ እንደ ብዙ ቁሳቁስ በሩቅ የሚታይ አይደለም፡፡ ከሳብጀክቱ (የሰው ልጅ) ጋር ይዋሃዳል (embodied)፡፡
2/ የትውስታም ሰሌዳ ነው፡፡ አርኪዮሎጂስቶች በጥንት ጊዜ የተሰራ ቁስ አግኝተው በመሳሪያቸው መርምረው የእነዚህን ቁሶች ምንነታቸውን ያነባሉ፡፡ ተፎካካሪ ወይም የሚጋጭ ትርጉም ቢሰጣቸውም መረጃ ይሆናሉ፡፡ አፄ ሰንደቅአላማ የፈጠረው ጤፍ ተፎካካሪዎች የሚሻሙበት ጽላት (Icon) ነው፡፡ እንጀራ በሆነ መልክ ወገናዊነትን ያመልጣል፡፡ ተፎካካሪዎች ሁለቱም ይሽቱታል፡፡ በልቶ የማያድር የለም፡፡ የድንጋይ ላይ ጽሑፎች ሲጠፉ፣ ሲቃጠሉ፣ ሲዘረፉ፣ ከቦታ ቦታ ተላልፈው ሲጠፉ፣ እንጀራን ማንም ሊያሸሸው ባለመቻሉ እዚህ ደርሷል፡፡ ብዙ ዘመን የኖረው ሰንደቅአላማ መቃብር ላይ መገኘቱ ረዥም ዕድሜ ከእሱ መዋሱ ምሳሌ ይሆን?
በአሁኑ ወቅት ለምሰራው ስራ መረጃ ስለምፈልግ ብዙ ጊዜ ኢንተርኔት ላይ ነበርኩ፡፡ የግጥም ባሕር፣ የመጣጥፍ ሃይቅ በዛ አለ፡፡ ፌስ ቡክ በመጠቀም ብቸኛ ደራሲ መሆኔን አንተ ነህ የነገርከኝ፡፡ “ፍሬንዶች” ለሚያቀርቡልኝ አንዳንድ ጥያቄዎች መልስ ለመስጠት ግን ብዙ ጊዜ አረፍዳለሁ፡፡ ከእኔ ይልቅ የአገራችንን ስነፅሁፍ ወደ መርበትብተ - ኤሌክትሮኒክ ያመጡት ወጣቶች ሊመሰገኑ ይገባል፡፡ የእነሱ የድርጊት ሕልውና ስለሚቀድም ልፋታቸው የገነነ ነው፡፡ ስለ ራሴም እንዳውቅ ገፋፍተውኛል፡፡ ልክ እንደ ጠንቋይ፣ ደራሲ ስለራሱ አያውቅም፡፡
ምናልባት ወጣቶቹ የበዙት ደራሲያን ማንሳት ይገባቸዋል የሚሏቸውን እስከ ዛሬ የተሳቱ ጉዳዮች ስላነሳሁ ይሆናል፤ ወይም ገና ወጣትነቴ አልከሰመምና (እስከ አሁን ድረስ ከምኑም ከምኑም እየተላተመ መጥቶ ከተረፈ፣ በተአብነት ይመዘገባል) እኔን የሚመዘምዘኝ ጉዳይ እነሱንም ይመዘምዝ ይሆናል፡፡ እነዚህ ግምቶቼ ናቸው፡፡ በግምት ደግሞ እርቀት አይኬድም፡፡

ስለአስገራሚ ገጠመኙ
በብዙ ነገር ተገርሜ የጨረስኩ ይመስለኛል፡፡ ድሮ የገረሙኝ ነገሮችን ዛሬ ሳስባቸው ለዛሬ አስገራሚ ሆነው አይታዩኝም፡፡ የሚያስቅ? ሎል (lol) ከመጣች ጀምሮ መንተክተክ ሳይቀንስ አልቀረም? (ለማሾፍ ይፈቀድልኛል?)  

Monday, 03 November 2014 08:17

እስቲ ይሞክሩት

እስቲ ይሞክሩት
1. ዓለም አቀፍ የገንዘብ ፈንድ (IMF)
ዋና መ/ቤት የት ነው የሚገኘው?
2. ፒልስነር ቢራ የተፈጠረበት አገር
የት ነው?
3. ስክሪው ድራይቨር የሚባለው
ኮክቴል የሚሰራው በምንድነው?
4. እ.ኤ.አ በ1925 ጆን ሎጊ ባየርድ
የፈለሰፈው ምንድነው?
5. ወደ ጨረቃ የመጀመርያውን
የስልክ ጥሪ ያደረገው ማነው?

መልስ
1. ዋሺንግተን ዲሲ
2. ቼክ ሪፐብሊክ
3. በቮድካና በብርቱካን ጭማቂ
4. ቴሌቪዥን
5. ሪቻርድ ኒክሰን

Monday, 03 November 2014 08:15

የፍቅር ጥግ

መዝፈን ህይወቴ ነው፡፡ እስከዛሬም ህይወቴ ነበር፡፡ ወደፊትም ህይወቴ ሆኖ ይቀጥላል፡፡
ሴሊያ ክሩዝ
የዛሬ ሦስት ዓመት ገደማ ነው መዝፈን የጀመርኩት፡፡ በአካባቢያችን ስትራትፎርድ አይዶል በተባለ የዘፈን ውድድር ውስጥ ገባሁ፡፡ ሌሎቹ ተወዳዳሪዎች የአዘፋፈን ትምህርትና የድምጽ ስልጠና ይወስዱ ነበር፡፡ በወቅቱ እምብዛም ከቁምነገር ስላልቆጠርኩት ቤት አካባቢ ብቻ ነበር የምዘፍነው፡፡ ገና 12 ዓመቴ ነበር፤ እናም ሁለተኛ ወጣሁ፡፡
ጀስቲን ቢበር
የሻማ መደብሩ ሲቃጠል ትዝ ይለኛል፡፡
ሁሉም ዙሪያውን ቆሞ “መልካም ልደት” የሚለውን መዝሙር ሲዘምር ነበር፡፡
ስቲቨን ራይት
ከመዝፈን የሚሻል ብቸኛ ነገር የበለጠ መዝፈን ነው፡፡
ኢላ ፊትዝገራልድ
በዓለም ላይ ትልቁ መግባቢያ ሙዚቃ ነው፡፡ ሰዎች የምታቀነቅንበትን ቋንቋ ባይረዱት እንኳን ሸጋ ሙዚቃን ሲሰሙ ያውቁታል፡፡
ሌዩ ራውልስ
ፀሐይ ስትጠልቅ ከተመለከትክ፣ አንድ ትርጉም ሊኖረው ይገባል? አዕዋፍ ሲዘምሩ ከሰማህ፣ መልዕክት ማስተላለፍ አለበት?
ሮበርት ዊልሰን
ዘፈን ሁልጊዜም እጅግ ትክክለኛው ሃሳብን የመግለጫ መንገድ ነው፡፡ በጣም ግብታዊ ነው፡፡ ከዘፈን ቀጥሎ ደሞ ቫዮሊን ይመስለኛል፡፡ እኔ መዝፈን ስለማልችል ሸራዬ ላይ እስላለሁ፡፡
ጆርጂያ ኦ’ኪፌ
በዝናብ ውስጥ እየዘፈንኩ ነው፤ ዝም ብዬ በዝናብ ውስጥ እየዘፈንኩ፡፡ እንዴት ደስ የሚል ስሜት ነው! አሁንም እንደገና ደስተኛ ነኝ፡፡
አርተር ፍሪድ  

         ብሩክ ኢትዮጵያ በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል በሃላባ ልዩ ወረዳ በ1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባቸውን የሃላባ ቁሊቶ ከተማና አካባቢው የጋማ እንስሳት ደህንነት ጥበቃና ስልጠና ማዕከልና የጋማ እንስሳት ውሃ ማጠጫ ገንዳዎችን አስመረቀ፡፡
በርካታ የጋማ እንስሳት በሚስተናገዱበት በሃላባ ከተማ ዋና የገበያ ስፍራ ላይ የተገነባው ማዕከል፤ ከእንስሳት እንክብካቤ ጋር የተያያዘ ስልጠና ከመስጠት ባለፈ፣ እንስሳቱ ተገቢውን መኖና ውሃ እያገኙ በምቹ ሁኔታ የሚቆዩበት ሲሆን እንስሳቱን ከስርቆት በመከላከልና ከሚደርስባቸው ስቃይ በማዳን ረገድ ጠቀሜታው የጎላ እንደሆነ ተነግሯል፡፡
በልዩ ወረዳው ለሚገኙ የመንግስት ክሊኒኮችና የእንስሳት ህክምና መስጫ ማእከላት የአቅም ግንባታ ድጋፎችን የሚያደርገው ብሩክ ኢትዮጵያ የአካባቢውን የጋማ ከብቶች የጤና እንክብካቤ ለማሳደግ ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በቁሳቁስ፣ በመድሃኒትና በህክምና መሳሪያዎች ማሟላቱን የድርጅቱ ሃላፊ አቶ ጥበቡ ደበበ ተናግረዋል፡፡
ህክምናውን ለማሻሻል የእንስሳት ሀኪሞችንና የህብረተሰብ የእንስሳት ጤና ሰራተኞችን አቅም በስልጠና በዘላቂነት ከማጎልበትና ለህብረተሰቡ ግንዛቤ በማስጨበጥ የተሻሉ የጋማ ከብት አያያዝ ልማዶችን ከማዳበር ባሻገር፣ በልዩ ወረዳዋ በሚገኙ ክሊኒኮችና የጤና ኬላዎች አስተማማኝ የጋማ እንስሳት መድሃኒት አቅርቦት እንዲኖር ለማስቻል በ370 ሺህ ብር የመድሃኒትና የክትባት ተዘዋዋሪ በጀት አሰራር ቀይሶ እንደሚሰራም ገልጸዋል፡፡
በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የሃላባ ልዩ ወረዳ የመንግስት ተወካይ፤ አቶ መሐመድ ኑር ሳኒያ በወረዳው ያሉት ከ39 ሺህ በላይ የጋማ ከብቶች ለህብረተሰቡ ከፍተኛ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቁመው፣ ይሄም ሆኖ ግን የጋማ እንስሳትን ጤንነትና ደህንነት ከማስጠበቅ አንጻር ችግሮች እንደነበሩ ገልጸዋል፡፡ “ብሩክ ኢትዮጵያ” በልዩ ወረዳው እያከናወናቸው የሚገኙ ስራዎች የአካባቢውን የጋማ ከብቶች ደህንነት ለማስጠበቅ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርጉም ተናግረዋል፡፡
“ብሩክ ኢትዮጵያ” የተቀናጀ የጋማ ከብት ደህንነት ትብብር ፕሮግራም በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል ጉራጌ፣ ሃዲያ፣ ወላይታና ጋሞ ጎፋ ዞኖች እንዲሁም ከአማራ መልሶ ማቋቋምና ልማት ድርጅት ጋር በመተባበር በሰሜን ጎንደር ዞን ፕሮጀክቶችን ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡


ባለፉት 15 ዓመታት በዓለም የማራቶን ውድድሮች መድረክ  የምስራቅ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ የበላይነት ሲያሳዩ ቆይተዋል፡፡ ከ5 ዓመታት ወዲህ ግን በተለይ የኬንያ ወንድ አትሌቶች ከኢትዮጵያውያኑ ከፍተኛ ብልጫ እያገኙ ናቸው፡፡ በአንፃሩ በማራቶን ከኬንያ አቻዎቻቸው በመፎካከር እየተሳካላቸው  የሚገኙት የኢትዮጵያ ሴት አትሌቶች ሆነዋል፡፡ የዓለም ማራቶን ሜጀር ሲሬዬስ አካል በሆኑ ትልልቅ ማራቶኖችና ሌሎች ውድድሮች እንዲሁም፤ በዓለም የማራቶን ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ ሰንጠረዦች በአጠቃላይ ኬንያውያን በሁለቱም ፆታዎች  በውድድር ዘመኑ ከኢትዮጵያውያን የተሻለ ስኬት ነበራቸው፡፡ በተለይ በወንዶች ምድብ በማራቶን ውጤት የኬንያ አትሌቶች ከኢትዮጵያውያን ተቀናቃኞቻቸው ጋር ያላቸው ልዩነት እየሰፋ መጥቷል፡፡
በተያያዘ ነገ የኒውዮርክ ማራቶን በታሪኩ ለ44ኛ ጊዜ ሲደረግ በሁለቱም ፆታዎች ፉክክሩ በምስራቅ አፍሪካ አገራት አትሌቶች እንደሚወሰን ቢጠበቅም የተሻለውን ግምት ኬንያውያን ወስደዋል፡፡ የኒውዮርክ ማራቶን እስከ 51 ሺ ተሳታፊዎች ፤ እስከ 2 ሚሊዮን ተመልካቾች የሚያጅቡት ትልቅ ውድድር ነው፡፡ ከኢትዮጵያውያን ማራቶኒስቶች መካከል በኒውዮርክ ማራቶን በወንዶች ምድብ በ2010 እኤአ ላይ አሸናፊ የነበረው ገብሬ ገብረማርያም እና በሴቶች ምድብ ደግሞ ለሁለት ጊዜያት ያሸነፈችው ፍሬህይወት ዳዶ ይሳተፋሉ፡፡ በሌላ በኩል የ2013/14 የዓለም 6 ማራቶኖች ሜጀር ሲሪዬስ “ማራቶን ሊግ” የደረጃ ሰንጠረዥ በመሪነት አጠናቅው 1 ሚሊዮን ዶላር ሽልማትንየ ሚካፈሉት አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች ኬንያውያን ናቸው፡፡ የማራቶን ሊጉ ነገ በሚካሄደው የኒውዮርክ ማራቶን ሲያበቃ ሲሆን በተለይ በወንዶች ምድብ አሸናፊውን የሚለይ ነጥብ ሊመዘገብበት ይችላል፡፡ የዓለም ማራቶን ሪከርድ ዘንድሮ ያስመዘገበው ኬንያዊ ዴኒስ ኪሜቶ የማራቶን ሊጉን እየመራ ቢሆንም ፤ የማራቶን ሪከርዱ የተሰበረበት የተሰበረበት ዊልሰን ኪፕሳንግ በነገው የኒውዮርክ ማራቶንን ካሸነፈ የማራቶን ሊጉን በአንደኛነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር የመሸለም እድል ይኖረዋል፡፡
ለነገሩ ከወር በፊት ከተካሄደው የቺካጎ ማራቶን በኋላ በ2013/14 የውድድር ዘመን የማራቶን ሊግ ፉክክር  በሁለቱም ፆታዎች ኬንያውያን ማሸነፋቸው የተረጋገጠ ይመስላል፡፡  በተለይ በሴቶች ምድብ የቺካጎ ማራቶንን ያሸነፈችው ኬንያዊቷ ሪታ ጄፕቶ በውድድር ዘመኑ የማራቶን ሊግ አሸናፊነቷን ያረጋገጠችው ከኒውዮርክ ማራቶን በፊት ነው፡፡  ኬንያዊቷ ሪታ ጄፕቶ በሴቶች ምድብ የማራቶን ሊጉን 100 ነጥብ በመምራቷ የ500ሺ ዶላር ሽልማት ትወስዳለች፡፡
በ2014 የዓለም ማራቶኖች በወንዶች ኬንያ፣ በሴቶች ኢትዮጵያ
በ2014 እኤአ ላይ ኢትዮጵያውያን ሴት አትሌቶች በርካታ የማራቶን ውድድሮችን አሸንፈዋል፡፡  ትልቁ ድል የተመዘገበው የዓመቱን ማራቶን ፈጣን ሰዓት ባስመዘገበችው እና የበርሊን ማራቶንንን ባሸነፈችው አትሌት ትርፌ ፀጋዬ ነው፡፡ የትርፌ ፀጋዬ የዓመቱ ፈጣን የማራቶን ሰዓት 2 ሰዓት ከ20 ደቂቃዎች ከ18 ሰከንዶች ሲሆን በበርሊን ማራቶን አሸናፊነቷ ያስመዘገበችው ነው፡፡ ይሁንና በለንደን ፤ በቺካጎ፤ በቦስተን እና በፓሪስ ማራቶኖች የኬንያ ሴት አትሌቶች የበላይነት ማሳየታቸው በማራቶን ሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ከፍ አድርጓቸዋል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ  ሴት አትሌቶች በማራቶን ሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ በየጣልቃው ኬንያውያንን ለመፎካከር የበቁት በማራቶን ሊግ ውድድሮች ባይሆንም በሌሎች በርካታ ማራቶኖች ከወንዶቹ ኢትዮጵያውያን በተሻለ ብዛት አሸፊና በመሆናቸው ነው፡፡  ኢትዮጵያውያኑ  ሴት አትሌቶች በበርሊን ማራቶን ተከታትለው መግባታቸው አንፀባራቂው ስኬተ ነው፡፡ በሌሎች በዓለም ዙርያ በተካሄዱ ውድድሮችም በተመሳሳይ ሁኔታ ብልጫ ለማሳየት አሸንፈዋል፡፡ ከእነሱም መካከል ማሬ ዲባባ የሻይናሜን ማራቶንን በቻይና፤ ትርፌ ፀጋዬ በየነ የቶኪዮ ማራቶንን በጃፓን ፤ ፍሬህይወት ዳዶ  የፕራግ ማራቶንን፤ ትእግስት ቱፋ የኦታዋ ማራቶንን በካናዳ ፤ ሙሉ ሰበቃ የዱባይ እና የዳጋኖ ማራቶኖችን በማከለኛው ምስራቅ እና በቻይና፤ አበበች አፈወርቅ የሂውስተን ማራቶንን በአሜሪካ፤ ማርታ ለማ  የሙምባይ ማራቶንን በህንድ፤ መስታወት ቱፋ የዶንግ ያንግ ማራቶንን በደቡብ ኮርያ እንዲሁም አማኔ ጎበና የሎስ አንጀለስ ማራቶንን በአሜሪካ ማሸነፋቸው ከሴት ማራቶኒስቶች አስደናቂ ስኬት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያዊ ወንድ ማራቶኒስቶች በአንፃሩ በ2014 ብቻ ሳይሆን ባለፉት አምስት አመታት ውጤታቸው ከኬንያውያኑ በጣም አየራቀ እና እየወረደ መጥቷል፡፡ በዓመቱ ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ ኢትዮጵያ ወንድ ማራቶኒስቶች በበላይነት በቅርብ ጊዜ የሚመለስ አይሆንም፡፡ እነዚህን ደረጃዎች የያዟቸው ኬንያውያን ናቸው፡፡ ከ6 የማራቶን ሊግ ውድድሮች አንዱንም ኢትዮጵያዊ አትሌት ሊያሸንፍ ያልቻለበት የውድድር ዘመንም ነበር፡፡
በኦል አትሌቲክስ ድረገፅ የ2014 ከፍተኛ ውጤት በማስላት በወጣ የደረጃ ሰንጠረዥ መሰረት በወንዶች ማራቶን አንደኛ ደረጃ የያዘችው በ3994 ነጥብ ኬንያ ናት፡፡ ኢትዮጵያ በ3901 ነጥብ፤ ጃፓን በ3618 ነጥብ ፖላንድ በ3523 ነጥብ እንዲሁም ኤርትራ በ3509 ነጥብ እስከ አምስት ያለውን ደረጃ አከታትለው ይወስዳሉ፡፡ በሴቶችም ኬንያ በ934 ነጥብ መሪ ናት፡፡ ኢትዮጵያ በ3910 ነጥብ ትከተላታለች፡፡ ጃፓን በ3629 አሜሪካ በ3576 እንዲሁም ጣሊያን በ3503 እስከ አምስት ያለውን ደረጃ ይወስዳሉ፡፡ በዚሁ ድረገፅ በቀረቡ አሃዛዊ መረጃዎች ለመንገዘብ የሚቻለው በዓመቱ ምርጥ የማራቶን ብቃት እና ፈጣን ሰዓት ሁለቱንም የመሪነት ስፍራዎች የተቆናጠጡት ኬንያውያን ናቸው፡፡ ሪታ ጄፔቶ እና ዴኒስ ኪሜቶ 1340 እና 1456 ነጥብ እንደየቅደም ተከተላቸው በማስመዝገብ ነው፡፡ በዚሁ ደረጃ በሴቶች ምድብ እስከ 20ኛ ባለው እርከን ኢትዮጵያውያን ቢያንስ ከስምንት በላይ ናቸው፡፡ በወንዶች ግን ያሉት ከ3 አይበልጡም፡፡
የኬንያ ወንድ አትሌቶች የበላይነት በርግጥም ከፓሪስ፤ ከበርሊን  እና ከቦስተን ማራቶኖች በኋላ ከወር በፊት በተደረገው የቺካጎ ማራቶንም በግልፅ ታይቷል፡፡  የቺካጎ ማራቶንን ያሸነፈው በረጅም ርቀት የትራክ ውድድሮች የቀነኒሳ ተፎካካሪ ሆኖ የቆየው ኬንያዊ ኤሊውድ ኪፕቾጌ ነበር፡፡ ኪፕቾጌ ወደ ማራቶን ፊቱን ካዞረ ወዲህ አራት ጊዜ ተወዳድሮ ለ3 ጊዜ በአንደኛነት መጨረሱ አስደንቋል፡፡ በቺካጎ ማራቶን ሲያሸንፍ ያስመዘገበው ሰዓት ደግሞ  2 ሰዓት ከ04 ደቂቃዎች ከ15 ሰከንዶች ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ሳሚ ኪርሞ በ2 ሰዓት 04 ከ18 እንዲሁም በሶስተኛ ደረጃ ዲክሰን ቺምቦ በ2 ሰዓት 04 25 በሆነ ጊዜ የጨረሱ ሌሎቹ የኬንያ አትሌቶች ናቸው፡፡ በወንዶች እስከ 10ኛ ባለው ደረጃ አንድ ኢትዮጵያዊ ብቻ ሲመዘገብ 7 ኬንያውያን ነበሩ፡፡ ያ ኢትዮጵያዊ ደግሞ ሁለተኛ የማራቶን ውድድር ለመሮጥ የበቃው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በቺካጎ ማራቶን ላይ ቀነኒሳ በ4ኛ ደረጃ ውድድሩን ያጠናቀቀ ሲሆን ሰዓቱ 2 ሰዓት ከ05 ደቂቃዎች ከ51 ሰከንዶች ነው፡፡ ቀነኒሳ በውድድሩ 2 ሰዓት ከ5 ደቂቃዎችን ርቀቱን ለመሸፈን በቻለበት ብቃት እንደረካ በወቅቱ ተናግሮ ነበር፡፡  የግሉን ፈጣን ሰዓት ለማስመዝገብ ከጅምሩ ማቀዱ አልቀረም ነበር፡፡ እንደውም ሌትስራን ድረገፅ እንደዘገበው ያቀደው ጊዜ  2 ሰዓት ከ3 ደቂቃዎች ከ13 ሰከንዶች ነው፡፡ በእርግጥ ከቀነኒሳ በፊት የነበሩት ታላቅ የረጅም ርቀት ሯጮች በመጀመርያ ሁለት የማራቶን ውድድራቸው ፖል ቴርጋት በ2 ሰዓት ከ08 ደቂቃዎች ሃይሌ ደግሞ 2 ሰዓት ከ06 ደቂቃዎች ነበር ያስመዘገቡት፡፡ እንደ ጆስ ሄርማንስ አስተያየት ቀነኒሳ በቀለ በቺካጎ ማራቶን በውድድሩ አይነት ለሁለተኛ ጊዜ የተሳተፈው ልምድ ለማዳበር እና ማራቶንን ለመማር ነው፡፡
የቺካጎ ማራቶን ከመካሄዱ በፊት ማራቶንን በ2 ሰዓት እና ከ2 ሰዓት በታች ይገባል ተብሎ የተጠየቀው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ የሰው ልጅ ያን ያህል መፍጠን አይችልም በሚል መልስ ሰጥቷል፡፡‹‹ ምናልባት ወደፊት ማን ያውቃል ሳይንቲስቶች ልዩ የሰው ልጆች ካልፈጠሩ በቀር…›› ነው ያለው ቀነኒሳ፡፡ የአትሌቱ ማናጀር የሆኑት የ64 ዓመቱ ሆላንዳዊ ጆስ ሄርማንስ ግን በተቃራኒው በሰጡት አስተያየት‹‹ ቀስ በቀስ ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች እንደሚገባ አስባለሁ… ምናልባትም ከ20 ዓመታት በኋላ›› ብለዋል፡፡ ለጆስ ሄርማንስ ለዚህ ብቃት ዋና እጩ የተደረገው ራሱ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ነው፡፡ በማራቶን ስልጠናው እና ልምምዱ ላይ ስርነቀል መሻሻሎች እንደሚያስፈልጉ ጎን ለጎን አስረድተዋል፡፡‹‹ ብዙ ለውጦች ያስፈልጋሉ፡፡ በልምምድ፤ በህክምና ድጋፍ እና በጤንነት አጠባበቅ፤ በፊስዮቴራፒ ያሉትን ሁኔታዎች ማሻሻል ይገባል፡፡ በቀለ በጣም ተፈጥሯዊ ብቃት የታደለ አትሌት ነው፡፡ መልቲ ቫይታሚን ወስዶ እንኳን አያውቅም›› በማለት ጆስ ሄርማንስ በአትሌቱ ላይ ስላላቸው ተስፋ መናገራቸውን ሌትስራን ድረገፅ ዘግቦታል፡፡ አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ለቺካጎ ማራቶን ባደረገው ዝግጅት ለውጦች ማድረጉ ግድ ነበር፡፡ የመጀመርያ ማራቶኑን በፓሪስ ከመሮጡ በፊት የሰራው ልምምድ ምንም እንኳን በውድድሩ በምንጊዜም የማራቶን ፈጣን ሰዓት 6ኛ ደረጃ አስመዝግቦ ቢያሸንፍም በወቅቱ 27ኛው ኪሎሜትር ላይ ለገጠመው የጉዳት ስሜት ምክንያቱ የልምምድ ስርዓቱ ነበር፡፡ ለፓሪስ ማራቶን ሲዘጋጅ በሳምንት ከ180 እስከ 200 ኪሎሜትሮችን ሮጦ ነበር፡፡ ለቺካጎ ማራቶን የተዘጋጀው ግን ከ160 እስከ 180 ኪሎሜትሮችን ነው፡፡የዓለም የማራቶን ሪከርድ በኬንያዊ አትሌት ሲሰበር የዘንድሮው ለሶስተኛ ጊዜ ሲሆን በዴኒስ ኪሜቶ የተያዘው 2 ሰዓት ከ02 ደቂቃዎች ከ57 ሰከንዶችን በሚቀጥሉት 15 ዓመታት በ177 ሰከንዶች በማሻሻል በሰው ልጅ ብቃት ማራቶንን 1 ሰዓት ከ59 ደቂቃዎች መግባት እንደሚቻል ሳይንቲስቶች ይገልፃሉ፡፡ ከምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ይህን በማሳካት ደግሞ ኬንያውያን ወንድ አትሌቶች ከኢትዮጵያውያን እጅግ በላቀ ሁኔታ ግምት አግኝተዋል፡፡
ቺካጎ ላይ በሴቶች ምድብ  ያሸነፈችው ኬንያዊቷ ሪታ ጄፒቶ ስትሆን ርቀቱን በ2 ሰዓት ከ24 ደቂቃዎች ከ35 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ በመሸፈን ነበር፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ ሴት አትሌቶች በውድድር ዘመኑ እንዳሳዩት ስኬት በቺካጎም ዋና ተፎካካሪዎች ነበሩ፡፡ ቺካጎ ላይ ኢትዮጵያዊቷ ማሬ ዲባባ በ2 ሰዓት ከ25 ደቂቃዎች ከ37 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ርቀቱን በመሸፈን ሁለተኛ ደረጃን ስታገኝ፤ 3 የወጣችው የኬንያዋ ፍሎረንስ ኪፕላጋት ናት፡፡ በሴቶች ሌሎቹ ኢትዮጵያውያን በ2 ሰዓት ከ27 ደቂቃዎች ከ02 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ብርሃኔ ዲባባ አራተኛ እንዲሁም ገለቴ ቡርቃ በ2 ሰዓት ከ34 ደቂቃዎች ከ17 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ ስምንተኛ መውጣታቸው ይጠቀሳል፡፡

በ8 የማራቶን ሊጎች በወንዶች ኬንያ  7 ኢትዮጵያ 1፤ በሴቶች ኬንያ 3 ኢትዮጵያ 1
ማራቶን ሊግ “ዎርልድ ማራቶን ሜጀር ሲሪዬስ”  በሚል ስያሜ ዘንድሮ የተካሄደው ለስምንተኛ ጊዜ ነው፡፡ በማራቶን ሊግ ላይ በስድስት ትልልቅ ማራቶኖች  በሚመዘገብ ውጤት መሰረት 1ኛ ሆኖ መጨረስ በሁለቱም ፆታዎች በነፍስ ወከፍ የ500ሺ  ዶላር ሽልማት ይገኝበታል፡፡ ማራቶን ሊጉ ዘንድሮ የተጀመረው   በቶኪዮ ማራቶን ሲሆን የመጨረሻው ውድድር ነገ በኒውዮርክ ማራቶን ይሆናል፡፡
የዘንድሮ ማራቶን ሊግ በኒውዮርክ ማራቶን ከመጠናቀቁ በፊት በተለይ በሴቶች ምድብ በአንደኛነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር እንዳሸነፈች ያረጋገጠችው ኬንያዊቷ ሪታ ጂፔቶ ሆናለች፡፡ ሪታ ጄፕቶ በ2013 እኤአ የቺካጎ እና የቦስተን ማራቶኖችን ለማሸነፍ የበቃች ሲሆን በ2014 እኤአ ደግሞ መልሷ በሁለቱም ማራቶን ውድድሮች በተከታታይ ዓመት በማሸነፍ በማራቶን ሊጉ 100 ነጥብ አስመዝግባለች፡፡ በ213 በዓለም ሻምፒዮና 1ኛ፤ በለንደን ማራቶን ሁለተኛ እንዲሁም በ2014 በለንደን ማራቶን ያሸነፈችው ኤድና ኪፕላጋት በ65 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ አግኝታለች፡፡ በ2013 እኤአ ላይ በቦስተን ማራቶን 3ኛ ደረጃ የነበራት እና በ2014 እኤአ የቶኪዮ እና የበርሊን ማራቶኖችን ያሸነፈችው ትርፌ ፀጋዬ በ51 ነጥብ 3ኛ ደረጃ በማግኘት በውድድር ዘመኑ በማራቶን ሊግ በኢትዮጵያዊ የተመዘገበውን ከፍተኛ ውጤት አግኝታለች፡፡
በሌላ በኩል በማራቶን ሊጉ የወንዶች ምድብ በነጥብ ብልጫ በአንደኛነት በመጨረስ የ500ሺ ዶላር ተሸላሚ የሚሆን አትሌት የሚታወቀው ነገ  በሚደረገው የኒውዮርክ ማራቶን ሊሆን ይችላል፡፡ በዚህም የኬንያውያን አትሌቶች እድል የሰፋ ነው፡፡ ሊጉን በአንደኛነት የሚመራው ከሳምንታት በፊት በበርሊን ማራቶን አዲስ የዓለም ክብረወሰን በማስመዝገብ ያሸነፈው እና በ2013 እኤአ ላይ በቶኪዮ እና ቺካጎ ማራቶን ላይ ያሸነፈው ዴኒስ ኪሜቶ በ75 ነጥብ ነው፡፡ በ2ኛ ደረጃ በ65 ነጥብ ይከተል የነበረው በ2013 በዓለም ሻምፒዮና አራተኛ ደረጃ በለንደን ማራቶን አንደኛ እና በኒውዮርክ ማራቶን 2ኛ ደረጃ እንዲሁም በ2014 በለንደን 3ኛ በቺካጎ አራተኛ ደረጃ ያስመዘገበው ኢትዮጵያዊ ፀጋዬ ከበደ ነው፡፡ በማራቶን ሊጉ የዴኒስ ኬሚቶን ደረጃ በመቀናቀን ከኒውዮርክ ማራቶን ውጤት በኋላ ለማሸነፍ እድል የሚኖረው የቀድሞ የማራቶን ክብረወሰን ባለቤት ዊልሰን ኪፕሳንግ ብቻ ይሆናል፡፡
በማራቶን ሊጉ ለአትሌቶች እስከ አምስተኛ ደረጃ በሚመዘገብ ውጤት  ነጥብ የሚያስገኙ ዓለም አቀፍ 6 ማራቶኖች  በቶኪዮ፤ በቦስተን፤ በለንደን፤ በበርሊን፤ በቺካጎ እና በኒውዮርክ የሚካሄዱት ናቸው፡፡ የኦሎምፒክ እና የዓለም ሻምፒዮና የማራቶን ውድድሮችም በሚካሄዱባቸው የውድድር ዘመናትም ነጥብ ይገኝባቸዋል፡፡ አንድ የማራቶን ሊግ የውድድር ዘመን በ2 የውድድር ዓመታት ውስጥ የሚወሰን ሲሆን በእዚህ ጊዜ ውስጥ የሊጉ አካል የሆኑ ቢያንስ 12 ማራቶኖች አሉ፡፡ በእነዚህ ውድድሮች ቢበዛ በ4 ማራቶኖች በመሳተፍ ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡ አትሌቶች በደረጃ ሰንጠረዡ በአንደኝነት በመጨረስ 500ሺ ዶላር በየፆታ መደቡ ለመሸለም  ሰፊ እድል ይኖራቸዋል፡፡ በማራቶን ሊግ  ውድድሮች ለአንደኛ ደረጃ 25 ነጥብ ፤ ለሁለተኛ ደረጃ 15 ነጥብ ፤ ለሶስተኛ ደረጃ 10 ነጥብ ፤ ለአራተኛ ደረጃ 5 ነጥብ  እንዲሁም ለአምስተኛ ደረጃ 1 ነጥብ ይሰጣል፡፡ ከ2006 በእኤአ ወዲህ  በተካሄዱት 7 የማራቶን ሊግ የውድድር ዘመናት ኬንያውያን በከፍተኛ ብልጫ ኢትዮጵያውያን እየራቁ መሄዳቸው ይስተዋላል፡፡ የዎርልድ ማራቶንስ ሜጀር ሲሪዬስ ወይንም የማራቶን ሊግ ከተጀመረ ወዲህ 129 ውድድሮች ተደርገው ማሸነፍ ከቻሉ 102 የአፍሪካ አትሌቶች 93 የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ናቸው፡፡ የአንበሳው ድርሻ ደግሞ የኬንያውያን ነው፡፡ከቺካጎ ማራቶን በኋላ በዓለም የማራቶን ሊግ ውስጥ በሚካሄዱ 6 የማራቶን ውድድሮች ከ1989 እኤአ ወዲህ የምስራቅ አፍሪካ በተለይ  የኬንያ እና የኢትዮጵያ አትሌቶች  በወንዶች 72.6 በመቶ በሴቶች 90 በመቶ አሸናፊዎች ናቸው፡፡
ከ1990 ወዲህ በሁለቱም ፆታዎች በቶኪዮ ማራቶን ኬንያ 9 ኢትዮጵያ 1 ፤ በቦስተን ማራቶን ኬንያ 14 ኢትዮጵያ 4፤ በለንደን ማራቶን ኬንያ 12 ኢትዮጵያ 3 ፤ በበርሊን ማራቶን ኬንያ 13 ኢትዮጵያ 4 ፤ በቺካጎ ማራቶን ኬንያ 12 ኢትዮጵያ 2፤  እንዲሁም ከነገው ውድድር በፊት በኒውዮርክ ማራቶን ኬንያ 10 ኢትዮጵያ 2 አሸናፊዎች አስመዝግበዋል፡፡
ባለፉት ስምንት የማራቶን ሊግ የውድድር ዘመናት የደረጃ ሰንጠረዡን በአንደኛነት በመጨረስ  የተሳካላቸው በወንዶች 7 ጊዜ የኬንያ አንድ ጊ. የኢትዮጵያ እንዲሁም በሴቶች ሶስት ጊዜ የኬንያ፤ እያንዳንዳቸው ሁለት ጊዜ የጀርመን እና የራሽያ እንዲሁም አንድ ጊዜ የኢትዮጵያ አትሌቶች በነፍስ ወከፍ የ500ሺ ዶላር ሽልማት አግኝተዋል፡፡ የማራቶን ሊጉን በማሸነፍ የተሳካላቸው ሁለት የኢትዮጵያ አትሌቶች ናቸው፡፡ በወንዶች ምድብ ባለፈው ዓመት በ75 ነጥብ የሊጉን ፉክክር በአንደኛነት በመጨረስ ያሸነፈው ፀጋዬ ከበደ ፤ እንዲሁም በሴቶች በ2006 እና 2007 ላይ በመጀመርያው የማራቶን ሊግ በ80 ነጥብ ያሸነፈችው ጌጤ ዋሚ ናቸው፡፡

Monday, 03 November 2014 07:56

ኢቦላ በአሃዝ ሲገለፅ

የዓለም ጤና ድርጅት በቅርቡ ያወጣው ሪፖርት እንደሚያመለክተው፤ የኢቦላ በሽታ ስርጭት በአስደንጋጭ ሁኔታ እየጨመረ ነው፡፡ የድርጅቱ ሪፖርት ቀጣዮቹን መረጃዎች ይፋ አድርጓል፡፡
8.033       እስከ አሁን በኢቦላ ቫይረስ የተያዙ ሰዎች
3865     በኢቦላ በሽታ ምክንያት ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች
233    በኢቦላ በሽታ ህይወታቸውን ያጡ የጤና ባለሙያዎች
400     በበሽታው የተያዙ የጤና ባለሙያዎች
21    በኢቦላ ቫይረስ የተጠቃ ሰው የበሽታውን ምልክቶች የሚያሳይባቸው ቀናት
        ***        
የየአገራቱ የጤና በጀት
በአሜሪካ የነፍስ ወከፍ አመታዊ የጤና በጀት     $ 8895
በላይቤሪያ     “    “    “    $ 65
በሴራሊዮን     “    “    “$ 96
በጊኒ        “    “    $ 32
በኢትዮጵያ     “    “    $ 18        
የዓለም ጤና ድርጅት ሌሎች መረጃዎች
በኤችአይቪ በየሳምንቱ - 4795 ሰዎች ይሞታሉ
በተቅማጥ    በየሳምንቱ -2828   ሰዎች ይሞታሉ
በኢቦላ     በየሳምንቱ -10ሺ ሰዎች ይሞታሉ ተብሎ ይታሰባል፡፡   

        በኢትዮጵያ ከ104 ሺ በላይ ኤርትራውያን ስደተኞች ይገኛሉ
         የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት፣ በየዕለቱ ከ200 በላይ ኤርትራውያን ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ እንደሚገቡ መግለጹን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
በኤርትራ መንግስት አስተዳደር የተማረሩ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ የአገሪቱ ዜጎች አገራቸውን ጥለው መሰደዳቸውን ያስታወሰው የተመድ ሪፖርት፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን አደገኛ ድንበር እያቋረጡ በህገወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ስደተኞች ቁጥር ካለፈው መስከረም ወር አንስቶ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ነው ብሏል፡፡ ባለፉት ሁለት ወራት ብቻ ከ3ሺህ 500 በላይ ኤርትራውያን ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ መግባታቸውን የገለጸው የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ትብብር ቢሮ ሪፖርት፣ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች ቁጥር ከ104 ሺህ በላይ መድረሱን አስታውቋል፡፡
የስደተኞችን ቁጥር እንዲጨምር ያደረገው ምክንያት በሪፖርቱ እንዳልተገለጸ የጠቆመው ዘገባው፤ይሄም ሆኖ ግን አንዳንድ የመብት ተሟጋች ቡድኖች ኤርትራውያን በአገሪቱ መንግስት የሚደርስባቸው ጭቆና እየከፋ መምጣቱ ለስደቱ መባባስ በምክንያትነት እንደሚያስቀምጡት ገልጧል፡፡