Administrator

Administrator

አሳታሚዎች፣ መፃሕፍት ሻጮችና መገናኛ ብዙኃን የሚሳተፉበት “ኢትዮ አለም አቀፍ የመፃህፍት አውደ ርዕይ እና የሚዲያ ኤክስፖ” በትላንትናው እለት በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል የተከፈተ ሲሆን ዝግጅቱ እስከ ፊታችን  ሰኞ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ታውቋል፡፡
ዝግጅቱ የንባብ ባህል እንዲዳብር፣ የመፃህፍት ገበያ እንዲጎለብት፣ የአሳታሚና የህትመት ኢንዱስትሪው እንዲጠናከር ታልሞ የተሰናዳ እንደሆነ አዘጋጆቹ በላኩት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡ “በእውቀትና በመረጃ ለበለፀገ ህብረተሰብ መፃህፍትና ሚዲያ በአንድ ስፍራ” በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው አውደ ርዕይና የሚዲያ ኤክስፖ ላይ የተለያዩ አዝናኝ ዝግጅቶች እንደሚቀርቡም ታውቋል፡፡
ትላንትን ጨምሮ ለአምስት ቀናት በሚዘልቀው ዝግጅት ላይ ከ60 በላይ አሳታሚዎች፣ መፃሕፍት ሻጮች፣ የግልና የመንግስት መገናኛ ብዙኃን፣ የጠፉና የማይገኙ መፃሕፍት አቅራቢዎች ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡

የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ በሆነው ሀብታሙ አያሌው የተፃፈው “ሀገርና ፖለቲካ” የተሰኘ መፅሀፍ ሰሞኑን  ለንባብ በቃ፡፡ በ18 ምዕራፍና በ272 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ ስለ ኢትዮጵያ አመሰራረት፣ ስለ ኢትዮጵያ ስያሜ፣ ስለ ፖለቲካና ሃይማኖት፣ ስለ ቀደምት ኢትዮጵያ አፄዎችና ሌሎች በርካታ ርዕሰ ጉዳዮች ተነስተውበታል፡፡ የመፅሀፉ አዘጋጅ አቶ ሃብታሙ አያሌው፤ የኢህአዴግ መንግስት ለታሪክና ለሀገር ያለው እጅግ የመረረ ጥላቻና አፍራሽ ተልዕኮ መፅሀፉን ለመፃፍ እንዳነሳሳው በመግቢያው ላይ ገልጿል፡፡ መፅሀፉ በ54 ብር ከ99 ሳንቲም እየተሸጠ ነው፡፡

“ህልፈተ አንጃ ወ ክሊክ ዘ ኢህአፓ” በሚል ርዕስ በኃይለማርያም ወልዱ የተዘጋጀው መፅሀፍ ከሰሞኑ በገበያ ላይ ውሏል፡፡ “ማን ነው ኢህአፓን ያፈረሰው?” ሲል የሚጠይቀው መፅሀፉ፤ መልሱን በውስጥ ገፁ ያብራራል፡፡ በ18 ክፍሎች እና በ387 ገፆች ተመጥኖ የተሰናዳው የተቀነባበረው  መፅሃፉ ትኩረቱን ከኢህአፓ አመሰራረት እስከ መፍረሱ እንዲሁም በመኢሶን እንቅስቃሴ ላይ ያደረገ ሲሆን ለአገር ውስጥ በ150 ብር፣ ለውጭ በ20 ዶላር ለሽያጭ ቀርቧል፡፡

በደራሲ ዮሀንስ ፀጋዬና አብዲሳ ምትኩ ተፅፎ በስንታየሁ አባይ የተዘጋጀው “የሞግዚት ልጆች” ፊልም ነገ ከቀኑ 8፡30 ሰዓት ጀምሮ በሁሉም ሲኒማ ቤቶች ለእይታ ይቀርባል፡፡ በያሬድ ፊልም ፕሮዳክሽን ፕሮዲዩሰርነት የቀረበው ይሄው ፊልም፤ የ1፡45 ሰዓት ርዝመት ያለው ሲሆን የሮማንስ ኮሜዲ ዘውግ እንዳለውም ለማወቅ ተችሏል፡፡
በፊልሙ ላይ አርቲስት አዳነች ወ/ገብርኤል፣ ታሪኩ ብርሀኑ (ባባ)፣ ሚካኤል ጆርጅ፣ ምህረት አበበና ሌሎችም ተዋንያን ተሳትፈውበታል፡፡ የፊልሙ አቅራቢ ያሬድ ፊልም ፕሮዳክሽን ከዚህ ቀደም “ክስተት” እና “አሜን” የተሰኙ ፊልሞችን ማቅረቡ ይታወቃል፡፡

የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ነገ “ሰኔ 30 የንባብ ቀን” በሚል መሪ ቃል ልዩ ፕሮግራም ያካሄዳል፡፡ የፕሮግራሙ አላማ በንባብ ላይ አገር አቀፍ መነሳሳትን መፍጠር መሆኑን የገለፀው ማህበሩ፤ ፕሮግራሙ ነገ ከጠዋቱ 4 ሰዓት ጀምሮ መነሻውን አራት ኪሎ አደባባይ፣  መድረሻውን አምስት ኪሎ ቴክኖሎጂ ፋኪልቲ የሚያደርግ የእግር ጉዞ እንደሚያካትት አስታውቋል፡፡
በእግር ጉዞው ላይ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር አባላት፣ የመንግስት ተወካዮች፣ የተለያዩ ድርጅቶች ሰራተኞች፣ የኢትዮጵያ ስካውት ማህበር አባላትና ሌሎችም የሚሳተፉ ሲሆን የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ካሳ ተክለብርሃንና የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሙሉጌታ ሰኢድ በክብር እንግድነት ተገኝተው ንግግር ያደርጋሉ ተብሏል፡፡ የዝግጅቱ ዋነኛ አላማ ሰኔ 30ን የንባብ ቀን አድርጎ ለመሰየም እና አገር አቀፍ የንባብ መነቃቃትን ለመፍጠር እንደሆነ ከማህበሩ መግለጫ ለማወቅ ተችሏል፡፡  

“ፕሬዚዳንት ኦባማን
ሳልከሳቸው አልቀርም”

“ፕሬዚዳንቱ የሀገሪቱን ህጎች በታማኝነት እያስፈፀሙ አይደለም፤ ስለዚህ ክስ መስርቼ ፍርድ ቤት ሳልገትራቸው አልቀርም፡፡” ሲሉ የተናገሩት የአሜሪካ ኮንግረስ አፈጉባኤ ቦህነር ናቸው፡፡
በኦባማ የመጀመሪያው አራት አመት የፕሬዚዳንትነት የስልጣን ዘመን አጋማሽ ላይ በተደረገው የኮንግረስ ምርጫ ሩፐብሊካኖች አሸንፈው አብላጫውን መቀመቻ እንደተቆጣጠሩ የኮንግረንሱ አፈጉባኤ በመሆን የተመረጡት ሪፐብሊካኑ ፖለቲከኛ ቦህነር ከፕሬዚዳንት ኦባማ ጋር አንድም ቀን እንኳ ኮከባቸው ገጥሞ አያውቅም፡፡ አንዳቸው ላንዳቸው ያላቸውን ጥላቻም ደብቀውት አያውቁም፡፡
ፕሬዚዳንት ኦባማም የማወጣቸው እቅዶችና ፕሮግራሞች በኮንግረሱ ተቀባይነት አግኝተው ስራ ላይ እንዳይውሉ አላስፈላጊ ችግር እየፈጠረ ስራዬን ይበጠብጣል በማለት አፈጉባኤ ቦህነርን በተደጋጋሚ ይነቅፋሉ፡፡
አፈጉባኤ ቦህነር በበኩላቸው ደግሞ “ፕሬዚዳንት ኦባማ እንደ አሜሪካ ፕሬዚዳንትነታቸው የሀገሪቱን ህጎች በታማኝነት ሥራ ላይ እያዋሉ አይደለም፤ እንዲያውም ይባስ ብለው በአሜሪካ ህዝብና በኮንግረሱ ላይ ልክ እንደ ንጉስ በግል ስልጣናቸው መንቀሳቀስ ጀምረዋል፡፡” ሲሉ በጥላቻ የታሸ ስሞታቸውን በተደጋጋሚ ያቀርባሉ፡፡
ሰሞኑን ግን አፈጉባኤ ቦህነር፤ በፕሬዚዳንት ኦባማ ላይ ስሞታ በማቅረብ ብቻ አልተወሰኑም፡፡ ባለፈው ረቡዕ በሰጡት መግለጫ በፕሬዚዳንት ኦባማ ድርጊት ቆሽታቸው እንዳረረና ክስ ሊመሰርቱባቸው እየተዘጋጁ እንደሆነ በይፋ አስታውቀዋል፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ አፈጉባኤ ቦህነር ፕሬዚዳንት ኦባማን ልን እንደ ንጉስ የግል ስልጣናቸውን በመጠቀም መንቀሳቀስ ጀምረዋል እንዲሉና በንዴት እንዲንጨረጨሩ ያደረጋቸው ዋነኛው ምክንያት፣ ፕሬዚዳንት ኦባማ የሚያወጧቸውን አንዳንድ እቅዶችና የሚወስዷቸውን ውሳኔዎች ያለ ኮንግረንሱ ፈቃድና ስምምነት የግል ፕሬዚዳንታዊ ስልጣናቸውን (Executive order) በመጠቀም ስራ ላይ እንዲውሉ በማድረጋቸው ነው፡፡
በእርግጥም ይህ ሁኔታ አፈጉባኤ ቦህነር የፕሬዚዳንት ኦባማን ውሳኔዎች ኮንግረንሱ እንዳያፀድቀው በማድረግ፣ የአፈጉባኤነት ስልጣናቸውን ማሳየት እንዳይችሉ አድርጓቸዋል፡፡ ፕሬዚዳንት ኦባማ ደግሞ “ከእሱና በሪፐብሊካኖች ከተሞላው ኮንግረንስ ጋር አጽድቁ አታጽድቁ እያልኩ ምን አዳረቀኝ” ባይ ናቸው፡፡
የሆኖ ሆኖ በርካታ የአሜሪካ የዜና አውታሮች የአፈጉባኤ ቦህነርን ውሳኔ በሰፊው አራግበውላቸዋል፡፡ በርካታ የህግ ባለሙያዎች ግን ለቢራ ቤት ወሬ ማዳመቂያ ከመሆን ያለፈ አንዳችም ህጋዊ መሰረትና ፋይዳ የሌለው ነው በማለት አጣጥለውታል፡፡ የካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ የኤርቪን ህግ ትምህርት ቤት ዲን ኤርዊን ቸመሪንስኪ፤ “አፈጉባኤ ቦህነር እንዳለው ፕሬዚዳንታዊ ስልጣኑን ለምን ተጠቀመ በሚል በፕሬዚዳንቱ ላይ ክስ ከመሠረተ የአሜሪካንን ህገ መንግስት ጨርሶ አያውቀውም ወይም አልገባውም ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለእርሱ ብቻ ሳይሆን በአፈጉባኤነት ለሚመራው ለአሜሪካ ኮንግረስ እጅግ ከባድ ሀፍረትና ውርደት ነው፡፡” ብለዋል፡፡

ከሀያ ስምንቱ የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት ውስጠ ህብረቱን አምርራ የምትጠላ፣ አባልነቱንም የማትፈልግ አንዲት ሀገር ብትኖር እንግሊዝ ብቻ ናት፡፡
እንግሊዝ ከዛሬ ሶስት ዓመት በፊት ከአውሮፓ ህብረት አባልነታቸው ለመውጣት ህዝበ ውሳኔ ካካሄዱት ሀገራት አንደኛዋ ናት፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮንና በስልጣን ላይ ለው የወግ አጥባቂ ፓርቲ በርካታ ባለስልጣናትና አንጋፋ አባላት እንግሊዝ የአውሮፓ ህብረት አባልነቷን ለቃ እንድትወጣ ከፍተኛ ፍላጎት አላቸው፡፡ በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዴቪድ ካሜሮን፤ በቀጣዩ ምርጫ በድጋሚ መመረጥ ከቻሉ፣ በ2017 ዓ.ም እንግሊዝ ከአውሮፓ ህብረት አባልነቷ እንድትወጣ ለማድረግ፣ ህዝበ ውሳኔ እንደሚያካሂዱ ቀደም ብለው ቃል ገብተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮን ባለፈው ግንቦት ወር በተካሄደው የአውሮፓ ፓርላማ ምርጫ የእንግሊዙን ዩኬአይፒ ፓርቲን ጨምሮ ፀረ አውሮፓ ህብረት የሆኑ ብሔርተኛና አክራሪ ፓርቲዎች ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገባቸው አልተከፉም፡፡
በአንፃሩ ደግሞ የአውሮፓ ህብረት ጠላት የሆኑት የሀገራቸው መራጮች ከሳቸው የወግ አጥባቂ ፓርቲ ይልቅ ዩኬአይፒ ፓርቲን በአንደኛ ደረጃ በከፍተኛ ድምጽ መምረጣቸው፣ በቀጣዩ ዓመት ግንቦት ወር ላይ በሚደረገው ምርጫ በድጋሚ የመመረጣቸውን እድል አጠራጣሪ በማድረግ ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ ከቷቸዋል፡ላለፉት ዓመታት የአውሮፓ ህብረት ያጋጠሙትን በርካት ችግሮችና ፈተናዎች እንዲወጣ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱት በአፍቃሬ አውሮፓ ህብረት አቋማቸው የታወቁት አንጋፋ ፖለቲከኛና የቀድሞው የሉክሰምበርግ ጠቅላይ ሚኒስትር የዦን ክሎድ ዩንከር የአውሮፓ ህብረት ጠንካራ ክንድና የስራ አስፈፃሚ አካል የሆነውን የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽንን የወቅቱን ፕሬዚዳንት ፖርቹጋላዊውን ማኑኤል ባሮሶን በመተካት ግንባር ቀደም እጩ ሆነው መቅረባቸው ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮን በቀላሉ የማይቋቋሙት በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ነበር፡፡
መጠጥ በመድፈር የታወቁ ጣጤ ከመሆናቸው በስተቀር ለብቃታቸው አንዳችም አቃቂር የማይወጣላቸው ሉክዘንበርጌው አንጋፋ ፖለቲከኛ ዦን ክሎድ ዮንከር፣ የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን አዲሱ ፕሬዚዳንት ሆነው ከተመረጡ የአውሮፓ ህብረት የስራ አስፈፃሚ አካል የሆነውን የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን የሚታማበትን ችግሮች በተለያዩ የተሀድሶ እርምጃዎች በማስተካከል ከመቸውም ጊዜ በበለጠ ጠንካራ ኮሚሽን እንደሚያደርጉት በርካቶች እምነታቸውን የጣሉባቸው ሰው ናቸው፡፡ ይህንን ሁኔታና የሚያስከትለውን ፖለቲካዊ ጣጣ በሚገባ የተረዱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩንም የዥን ክሎድ ዬንከርን ከቻሉ እጩነታቸውን ለማስቀረት፣ ይህን ማድረግ ካልቻሉ ደግሞ በቂ ድምጽ አግኝተው እንዳይመረጡ ለማድረግ ዙሪያ መለስ ቅስቀሳቸውን የጀመሩት ገና በማለዳ ነበር፡፡
ከፊንላንድ እስከ ስፔይን፣ ከፖርቹጋል እስከ ዴንማርክ ድረስ ባደረጉት ፀረ ዦን ክሎድ ዮንከር ቅስቀሳ የአብዛኞችን የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት መሪዎች ድጋፍ ማግኘት በመቻላቸው የልባቸውን እንዳደረሱ በመተማመን፣ የተወዳዳሪው ቀንደኛ ደጋፊ በሆኑት የጀርመኗ ቻንስለር አንጌላ መርክል ላይ የለበጣ ሳቅ ስቀውባቸው ነበር፡፡ ባለፈው አርብ ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም ሃያ ስምንቱ የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት መሪዎች አዲሱን የህብረቱ ኮሚሽን ፕሬዚዳንት ለመምረጥ ስብሰባ እንደተቀመጡም፤ የእንግሊዝ ጠቅላይ ምኒስትር በከፍተኛ የድል አድራጊነትና የእርካታ ስሜት ተሞልተው ከዚህ በፊት አድርገውት በማያውቁት ሁኔታ አጠገባቸው ተቀምጠው ከነበሩት ከሮማንያና ከስፔይን መሪዎች ጋር ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ያወሩ ነበር፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮን የብራ መብረቅ የወረደባቸው የምርጫውን ውጤት ሲሰሙ ነው፡፡ በድንጋጤ በተቀመጡበት ክው ያሉት ዴቪድ ካሜሮን ያዩትንም ሆነ የሰሙትን ማመን አልቻሉም። አንጋፋው ፖለቲከኛ ዦን ክሎድ ዩንከር ከሃያ ስምንቱ የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት የሀያ ስድስቱን ድምጽ በማግኘት፣ አዲሱ የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን ፕሬዚዳንት ሆነው ተመረጡ። ከሀንጋሪው ጠቅላይ ሚኒስትር ቪክቶር ኦባን በስተቀር ለጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮን ዦን ክሎድ ዩንከርን እንደማይመርጡ ቃላቸውን ሰጥተዋቸው የነበሩት መሪዎች ሁሉ ቃላቸውን በማጠፍ ለሰውየው ድምፃቸውን ሰጡ።
ኢትዮጵያዊያን “የፈሩት ይደርሳል፣ የጠሉት ይወርሳል፡፡” የሚሉት ተረት እነሆ በዴቪድ ካሜሮን ላይ ደረሰና ዦን ክሎድ ዩንከር ተመረጡ። የጠሏቸው እኒሁ ሰውም የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽንን በአዲስ ፕሬዚዳንትነት ወረሱባቸው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮን አጠገባቸውና ፊት ለፊታቸው የተቀመጡትን መሪዎች በትዝብት አይን እያዩ “የፈፀማችሁብኝ ታላቅ ክህደት ነው!” አሉና በለሆሳስ ተናገሩ፡፡ሁሉም ነገር አልቆ በመውጣት ላይ እንዳሉ ከቻንስለር አንጌላ መርከል ጋር ተገናኙ፡፡
በሰውየው መመረጥ አንጀታቸው ቅቤ የጠጣው አንጌላ መርከል፤ የለበጣ ሳቅ በመሳቅ ብድራቸውን ለመመለስ አልሞከሩም፡፡ ይልቁንም የዴቪድ ካሜሮንን ጀርባ መታ መታ በማድረግ “አይዞህ! እንግዲህ መቻል ነው እንጂ ምን ይደረጋል!” በሚል አይነት አጽናንተዋቸው አለፉ፡፡   

የተለያዩ ሀገራት እንደሚከተሉት የኢኮኖሚ ፖሊሲ አይነት የተለያየ የኢንቨስትመንት አሠራሮችን ይከተላሉ፡፡ በተለይ የውጭ ኢንቨስትመንትን በተመለከተ በየሀገሮቻቸው ባሉ የኢንቨስትመንት እድሎች ለውጪ ባለሀብቶች የተፈቀዱና የተከለከሉትን በግልጽ ለይተው ያስቀምጣሉ፡፡
በእኛ ሀገር ለምሳሌ የፋይናንስ፣ የቴሌኮሙኒኬሽንና የኢነርጂ ሴክተሮች ለውጪ ኢንቨስትመንት ዝግ ሲሆኑ የእርሻው ሴክተር ግን ክፍት ነው፡፡ በዚህ የተነሳም ኢትዮጵያ ሶስት ሚሊዮን ሄክታር የእርሻ መሬት ለውጪም ሆነ ለሀገር ውስጥ ኢንቨስትመንት አዘጋጅታለች፡፡
እንደ ኢትዮጵያ ሁሉ ሌሎች ታዳጊ ሀገራትም በሚሊዮን ሄክታር የሚቆጠር ሰፊ የእርሻ መሬቶችን ለውጪ ባለሀብቶች ይሰጣሉ፡፡ የአካባቢና የቀደምት ነዋሪ ማህበረሰቦች መብት ጥበቃ ተሟጋች ተቋማትና ግለሰቦች፣ ሀገራት ሰፋፊ የእርሻ መሬቶችን ለውጪ ባለሀብቶች ኢንቨስትመንት የሚሰጡበትን አሠራር “የመሬት ቅርምት” (Land - grabbing) ይሉታል፡፡
የመብት ተሟጋቾቹ የወቅቱ “የትግል አጀንዳ” ይህን “የመሬት ቅርምት” አጥብቀው መቃወም ነው፡፡ እነዚህ ወገኖች ለተቃውሟቸው የሚያቀርቡት ዋነኛ መከራከሪያ፣ የቀደምት ነዋሪ ማህበረሰቦችን ጥንታዊ የአኗኗር ዘይቤ ያዛባል፣ ከአካባቢያቸው እንዲፈናቀሉና ለባሰ ችጋር እንዲጋለጡ ያደርጋል፣ የአካባቢ ጥበቃንም ያባብሳል፣ ባጠቃላይ የሀገሪቱን ነዋሪዎች ወደ ባሰ ድህነት ይከታል የሚል ነው፡፡
ሰሞኑን በአሜሪካ የቨርጂኒያ ዩኒቨርስቲ አማካኝነት የተደረገ ጥናት ግን የመብትና የአካባቢ ጥበቃ ተሟጋቾችን ተቃውሞ ፉርሽ የሚያደርግ መረጃ ይዞ ወጥቷል፡፡ በቨርጂኒያ ዩኒቨርስቲ የአካባቢ ጥናት ሳይንቲስት ፓውሎ ዲኦዶሪኮና በኢጣሊያ የሚላኖ ፖሊ ቴክኒክ ተቋም ከፍተኛ ተመራማሪ ማሪያ ክርስቲና ሩሊ የተደረገው ጥናት፣ በ “መሬት ቅርምት” ከለማ እርሻ በሚገኝ ምርት ቢያንስ ሶስት መቶ ሚሊዮን ሰዎችን አጥግቦ መመገብ እንደሚቻል ይፋ አድርጓል፡፡
ተመራማሪዎቹ ከዚህ ውጤት ላይ ለመድረስ እንደ አውሮፓ አቆጣጠር ከ2000 ዓ.ም ወዲህ በታዳጊ ሀገራት የተደረጉ ከ200 ሄክታር በላይ የእርሻ የውጭ ኢንሽትመንት ስምምነቶችን እንዳጠኑ ተናግረዋል። ለውጪ ኢንቨስትመንት ከተሰጡ የእርሻ መሬቶች በተገኘ ምርት በኢንዶኔዢያ፣ በማሌዢያ፣ በፓፑዋ ኒው ጊኒና በሱዳን የሚገኙ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጐችን በሚገባ መመገብ እንደተቻለ መረጋገጡን አክለው ገልፀዋል - ተመራማሪዎቹ፡፡

ፓርኪንሰን የተባለው በሽታ ስያሜውን ያገነው ከተመራማሪው ሚስተር ፓርኪንሰን እንደሆነ ይነገራል፡፡ ቀደም ሲል በሽታው በአገራችን ብዙ ትኩረት ያላገኘና ብዙ ሰው የማያውቀው ነበር፡፡ ሆኖም ከጊዜ ወደ ጊዜ የታማሚዎቹ ቁጥር እየበረከተ በመምጣቱ ከሶስት ዓመት ወዲህ መጠነኛ ትኩረት ሊያገኝ ችሏል፡፡  በ32 ዓመታቸው በበሽታው የተጠቁት ወ/ሮ ክብራን፤
“የፓርኪንሰን ታማሚዎች ማህበር” መስርተው ታማሚዎችን ለመርዳት እየተንቀሳቀሱ
ይገኛሉ፡፡ ስለበሽታው ምንነት ህብረተሰቡ እንዲያውቅ፣ ለጤና ባለሙያዎች ለሚዲያ ሰዎችና ለበጎ ፈቃደኞች ስልጠና ይሰጣል፡፡ ማህበሩ የመድኃኒትና የገንዘብ እርዳታ በማፈላለግና ህብረተሰቡን በማንቃት በበሽታው ተይዘው እቤት የቀሩትን ሰዎች ወደ ህክምና ለማምጣት እየተጋም ይገኛል፡፡ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ በብሄራዊ ሆቴል ለጋዜጠኞች በተሰጠው የግማሽ ቀን የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ላይ የተገኘችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ የማህበሩ በጎ ፈቃደኛ ከሆኑት ከዶክተር ዳዊት ክብሩ ጋር በፓርኪንሰን ህመም መንስኤዎችና መፍትሄዎች ዙሪያ ተከታዩን ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡  

ፓርኪሰን የሚባለው በሽታ ምንድን ነው?
በሰውነት ውስጥ “ኒውሮ ዲጀነሬቲቭ” የሚባሉ በሽታዎች ይከሰታሉ፡፡ ዝግመታዊ በሆነ ሂደት አዕምሮ ውስጥ የሚገኝ “ባዛል ጋንግሊያን” የሚባል ክፍል ውስጥ የሚኖሩ የነርቭ ሴሎች አሉ፡፡ እነዚህ ሴሎች “ዱፓሚን” የሚባል ንጥረ ነገር ያመነጫሉ። እነዚህ ሴሎች ሲሞቱ ደግሞ ንጥረ ነገሩ መመረት ያቆማል፡፡ሰ የዚህ ንጥረ ነገር ማነስ ወይም አለመኖር ለፓርኪንሰን በሽታ ያጋልጣል፡፡
“ዱፓሚን” የተባለውን ንጥረ ነገር ዋነኛ ጥቅሙ ምንድን ነው?
ንጥረ ነገሩ ዘርፈ ብዙ ጥቅም አለው፡፡ ዋነኛው ጥቅሙ ግን በሞተርነት የጡንቻዎችን እንቅስቃሴ ማቀላጠፍና ማነቃቃት ነው፡፡ ዱፓሚን ሲያንስ ግን የበሽታው ዋና ዋና ምልክቶች መታየት ይጀምራሉ፡፡
ምልክቶቹን ቢጠቅሱልኝ?
ለምሳሌ መንቀጥቀጥ፣ የጡንቻ መገታተር፣ የእንቅስቃሴ ፍጥነት መፍዘዝና የራስን ሚዛን አለመጠበቅና የመሳሰሉት ዋና ዋና ምልክቶች ናቸው፡፡
ዱፓሚን የተባለው ንጥረ ነገር የሚያንሰው አምራች ሴሎች ሲሞቱ ነው ብለውኛል፡፡ ሴሎቹ የሚሞቱበት ምክንያትስ ምን ይሆን?
ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ “ኻዛል ጋንግሊያ” የሚባለው የአዕምሮ ክፍል ውስጥ የሚገኙ ዱፓሚን አምራች ሴሎች ምክንያቱ ባልታወቀ ምክንያት ቀስ በቀስ ይሞታሉ፡፡ ከ80 በመቶ በላይ ሲሞቱ ደግሞ የንጥረ ነገሩ እጥረት ይከሰትና የበሽታው ምልክቶች መታየት ይጀምራሉ፡፡
በሽታው በአብዛኛው በየትኛው የእድሜ ክልል ያሉ ሰዎችን ያጠቃል?
እድሜያቸው ከ60 በላይ የሆኑ ሰዎች በብዛት በበሽታው ይጠቃሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ግን በ20 እና በ30 አመት ዕድሜ የሚገኙ ሰዎችም በበሽታው የሚጠቁበት ጊዜ አለ፡፡ ከ90 በመቶ በላይ ግን ከ60 ዓመት በላይ የሆኑ ሰዎች ላይ ይከሰታል፡፡
በሽታው በሴቶች ላይ ይበረታል ወይስ ወንዶችን ያጠቃል?
ከሴቶች በበለጠ ወንዶችን የሚያጠቃ ሲሆን ከተማ ከሚኖሩ ገጠር የሚኖሩት ላይ ይበረታል፡፡
በአገራችን ተላላፊ ያልሆኑት በሽታዎች የሚባሉት እንደ ስኳር፣ ኩላሊት፣ ደም ግፊትና የመሳሰሉት ውስጥ ፓርኪንሰን ሊመደብ ይችላል? በአገራችንስ በሽታው ምን ያህል ይታወቃል?
በቅርብ ጊዜ በአገር አቀፍ ደረጃ በፓርኪንሰን ላይ የጠተና ጥናት የለም፡፡ አንድ ጥናት ከ30 ዓመት በፊት በፕሮፌሰር ረዳ ተሰርቶ ነበር፡፡ ያኔ ጥናቱ ሲሰራ የኢትዮጵያ የእድሜ ጣሪያ 43 ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት ግን የኢትዮጵያዊያን የእድሜ ጣሪያ 65 ዓመት ደርሷል እየተባለ ነው፡፡ በመሆኑም የበሽታው ተጠቂዎች ቁጥር እየጨመረ ነው የሚሄደው፡፡ ያደጉት አገራት በፓርኪንሰን የሚጠቁት የእድሜ ጣሪያቸው ትልቅ ስለሚሆን ነው፡፡ በአገራችን በሽታው እንደ በሽታ ትኩረት ማግኘት የጀመረው ከሶስት ዓመት ወዲህ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ የፓርኪንሰን ተጠቂዎች ቁጥር ምን ያህል እንደሆነ ይታወቃል? ከነርቭ ህመምስ በምን ይለያል?
ቀደም ሲል እንደነገርኩሽ በቅርብ የተጠና ጥናት ስለሌለ ቁጥራቸውን የሚያውቅ የለም። ታማሚዎቹም መራመድ፣ መናገር፣ መንቀሳቀስ ስለማይችሉ ወደ ህክምና አይመጡም፡፡ ስለዚህ ምን ያህል ናቸው የሚለው አይታወቅም፡፡ በእርግጥ አሁን አሁን የሰው ግንዛቤ እየጨመረ በመምጣቱ፣ ሰዎች ምልክቱን ሲያዩ ወደ ህክምና እየመጡ ነው። ከነርቭ በሽታ በምን ያለያል ላልሽው ነርቭን የሚያጠቁ በርካታ በሽታዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ ስትሮክ የነርቭ በሽታ ነው፣ ኦሜንሺያ (የመርሳት ችግርም) እንዲሁ ነርቭን የሚያጠቃ በሽታ ነው፡፡
ስለዚህ አንድ ራሱን የቻለ የነርቭ በሽታ የለም፡፡ ፓርኪንሰንም ነርቭን ከሚያጠቁ በሽታዎች አንዱ ነው፡፡ በሽታው እንደነገርኩሽ የራሱ ምልክቶችና ባህሪዎች አሉት፡፡
በበሽታው ህክምና ላይ ስፔሻላይዝ አድርገው የሚሰሩ ባለሙያዎችና የጤና ተቋማት አሉ?
ባለሙያዎቹ የነርቭ ስፔሻሊስቶች ናቸው፤ ጤና ተቋማትም አሉ፡፡ ህክምናው በመንግስት ሆስፒታሎች የሚሰጥ ሲሆን በጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድና በዘውዲቱ ሆስፒታል ይሰጣል፡፡ ታማሚዎች በእነዚህ ተቋማት መታከም ይችላሉ፡፡
ፓርኪንሰን በህክምና ይድናል ወይስ አብሮ የሚኖር ነው?
በሽታውን የሚያጠፋ መድኃኒት የለም፤ የሚያስታግስ እንጂ፡፡ ለምሳሌ የስኳር ታማሚዎች ኢንሱሊን በተደጋጋሚ እንደሚሰጣቸው ሁሉ መድኃኒቱን እድሜ ልክ በቋሚነት በመውሰድ ረጅም ጊዜ ይኖራሉ፡፡ ፓርኪንሰን በራሱ ገዳይ አይደለም፡፡
ለሌሎች በሽታዎችስ ያጋልጣል?
አዎ ለሌሎች ጉዳቶች ያጋልጣል፡፡ ለምሳሌ ለመሰበር አደጋ ያጋልጣል፡፡ ሚዛን መጠበቅ ስለማይችሉ ይወድቃሉ፤ ያን ጊዜ ስብራት ይመጣል። በሌላ በኩል ለሳንባ ምች በተደጋጋሚ ያጋልጣል፡፡ የፓርኪንሰን ታማሚዎች በአብዛኛው ለሳንባ ምች ይጋለጣሉ፡፡
ህክምናው በምን መልኩ ነው የሚሰጠው? መድኃኒቱስ?
ዘርፈ ብዙ ህክምና ነው ያለው፡፡ የክኒን ህክምና አለ፣ የስራ ቴራፒ ይሰጣል፡፡ የንግግር ቴራፒና የቡድን ቴራፒ ይሰጣል፡፡ በሽታው ንግግር፣ መዋጥ ሁሉ ይከለክላል፡፡ የንግግር ቴራፒ፣ ምግብ የመዋጥ ቴራፒ ሁሉ ይሰጣል፡፡ አገራችን ውስጥ በዋናነት ያለው የፊዚዮ ቴራፒና የክኒን ህክምና ነው፡፡
በሽታው በጡረታ እድሜ ላይ ያሉትን ነው የሚያጠቃው፡፡ መድኃኒቶቹ የጡረተኞችን አቅም አይፈትኑም?
በአገራችን ሁለት አይነት ክኒኖች አሉ፡፡ 600 እና 700 ብር ናቸው፡፡ እንዳልሽው ለጡረተኛ ውድ ናቸው፡፡ ይከብዳቸዋል፡፡ ምንም የገቢ ምንጭ እንደሌላቸው ካስመሰከሩ በመንግስት ሆስፒታሎች በነፃ የሚታከሙበት እድል አለ፡፡ ነገር ግን አንዳንዴ መድኃኒቱ ከአገር በሚጠፋበት ጊዜ የግድ ወደ ግል ፋርማሲዎች ሄደው ለመግዛት ይገደዳሉ፡፡
በሽታው የመጨረሻ ደረጃ ላይ ሲደርሱ ታማሚዎቹ ምን ይሆናሉ?
ይህ እንግዲህ ስቴጅ ፋይቭ (ደረጃ አምስት) ይባላል፡፡ ታማሚዎች እዚህ ደረጃ ላይ ሲደርሱ ዊልቸር ላይ ይቀራሉ፣ ንግግር ያቅታቸዋል፣ ምግብ መዋጥ አይችሉም፤ የአልጋ ቁራኛ ይሆናሉ ማለት ነው፡፡
ታዲያ እዚህ ደረጃ ሲደርሱ በምን መልኩ ይረዳሉ?
የንግግር ቴራፒስቶች የንግግርና የአዋዋጥ ስልጠና ይሰጧቸዋል፣ ይህን ሲያደርጉ ብዙ ትንታና ሳል የሚይዛቸው ከሆነ በቀዶ ህክምና ሆዳቸው ላይ ቲዩብ ገብቶላቸው፣ ምግብ በዚያ በኩል እንዲያገኙ ይደረጋሉ፡፡ ይህ እንዲህ የመጨረሻው ደረጃ ላይ ሲደርስ ነው፡፡
የዚህ በሽታ ተጠቂዎች በአማካኝ ምን ያህል እድሜ ይኖራሉ?
ከዋናው የእድሜ ጣሪያ ሁለት ወይም ሶስት አመት ቢቀንሱ እንጂ በደንብ ይኖራሉ፡፡ እንደነገርኩሽ ፓርኪንሰን በራሱ ገዳይ አይደለም፡፡ ለምሳሌ የኖርማል ሰው የእድሜ ጣሪያ 65 ዓመት ከሆነ እነሱ 62 ወይም 63 ዓመት መኖር ይችላሉ፡፡ ዋናው ችግር ግን ተጠቂዎቹ እድሜያቸውን ሙሉ መሥራትና ምርታማ አለመሆናቸው ነው፡፡
ዋናው የበሽታው መንስኤ እድሜ ነው ተብሏል አንዳንዴ በ30ዎቹ ውስጥም ያሉት ይጠቃሉ፡፡ ለምሳሌ የፓርኪንሰን ታማሚዎች ማህበር መስራች የሆነችው ወ/ሮ ክብራን በ32 ዓመቷ በበሽታው መጠቃቷ ከአኗኗር ዘይቤ ጋር ይገናኝ ይሆን?
በሽታው ለምን እንደሚከሰት አይታወቅም፡፡ ዋናው የዱፓሚን እጥረት ነው እጥረቱ የሚከሰተው አምራች ሴሎች ሲሞቱ ነው፡፡ ሴሎቹ ለምን እንደሚሞቱ አይታወቅም፡፡ ሴሎቹ የሰውየው እድሜ ሲጨምር ይሞታሉ ቢባል እንኳን በ30ዎቹ እድሜ ያሉትን ለምን እንደሚያጠቃ የሚታወቅ ነገር የለም፡፡
እዚህ አገር ለፓርኪንሰን በሽታ ህክምና የሚሰጥ ራሱን የቻለ ስልጠና አለ?
የፓርኪንሰን ስፔሻሊስት ለመሆን የሚሰጥ ስልጠናና ትምህርት እዚህ አገር የለም፤ ነገር ግን አንድ ባለሙያ በነርቭ ህክምና ላይ ስፔሻላይዝ ካደረገ በኋላ “Movement disorder” ወይም የእንቅስቃሴ መታወክ ሰብስፔሻሊቲ ስልጠና አለ፡፡ እሱን ወስደን ነው የምንሰራው፡፡

መድኃኒት ቤት (ፋርማሲ) ሄደው ሐኪም ያዘዘልዎትን የመድኃኒት መግዣ ወረቀት ሲሰጡ ፋርማሲስቱ፣ አወሳሰዱን በብልቃጡ ኮሮጆ ወይም ክኒኑን በጠቀለለበት ወረቀት ላይ ‹በቀን አንድ ጊዜ› ብለው ይሰጣሉ፡፡ ስህተቱ መድኃኒቱን ያዘዘው ሐኪም ይሁን ወይም የፋርማሲስቱ አይታወቅም እንጂ ልክ አይደለም፡፡ መድኃኒቱስ ‹በቀን አንድ ጊዜ› ይወሰድ። ግን መቼ? ጧት፣ ቀን፣ ማታ ወይስ ሌሊት? ግልጽ አይደለም፡፡
መድኃኒቶቹ የሚወሰዱበት ሰዓት ካልታወቀ ችግር አለው፡፡ ምክንያቱም ውጤታማ የሚሆኑባቸው ሰዓት አላቸው፡፡ ያለበለዚያ፣ ማሻላቸውንና ማዳናቸው ቀርቶ ጉዳት ሊፈጥሩ ይችላሉ፡፡ እንዴት? ቢባል እንስሳትም ሆኑ ተክሎች እንቅልፍ የሚተኙበት፣ ሆርሞን የሚያመርቱበት፣ ሌሎች ሂደቶችን የሚቆጣጠሩበት ተፈጥሯዊ የሰዓት ዑደት አላቸው፡፡
ብዙ መድኃኒቶች መወሰድ ባለባቸው ሰዓት ካልተወሰዱ ጥቅም ላይሰጡ ይችላሉ፡፡ “በተሳሳተ ሰዓት ከተወሰዱ፣ ድርጊቱን ዝም ብለው በቸልታ አይመለከቱትም፡፡ መልሳቸው መጥፎ ሊሆን ይችላል” ይላሉ በቴክሳስ አውስተን ዩኒቨርሲቲ የባዮሜዲካል ኢንጂነሪንግ ክፍል ረዳት ፕሮፌሰር የሆኑት ሚሼል ሰለንስኪ፡፡ “መድኃኒቶቹ በጭራሽ ዋጋ የላቸውም ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን ውጤታቸው በጣም ዝቅተኛ ይሆናል ወይም ድርጊቱን በቸልታ ላይመለከቱ ይችላሉ፡፡ ‹ባዕድ አካል መጣብን› ብለው መድኃኒቱን የሚያከሽፍ ነገር ሊያዘጋጁ ይችላሉ” ብለዋል ምሁሩ፡፡
በአሁኑ ወቅት የሚወሰዱት መድኃኒቶች ከፍተኛ ጥቅም እንዲሰጡ ወይም የሚያስከትሉት የጎንዮሽ ጉዳት ዝቅተኛ እንዲሆን drug chronotherapy advocats cyncing የተባለ የመድኃኒት አወሳሰድ ዘዴ መጥቷል፣ በዚህና በሌሎች ዘዴዎች ላይ ተመስርቶ ለተለያዩ ሕመሞች የሚታዘዙ መድኃኒቶች መወሰድ ያለባቸውን ሰዓት (ጊዜ) እንዲህ አቅርበናል። (ማሳሰቢያ፡- በፍፁም ሐኪምዎን ሳያማክሩ ወይም መድኃኒት የሚሸጥልዎትን ባለሙያ ሳያነጋግሩ መድኃኒት የሚወስዱበትን ጊዜ እንዳይለውጡ!!)
በጧት መወሰድ ያለባቸው መድኃኒቶች
የድብርት መድኃኒት፡- የተወሰኑ ሰሮቶኒን (Cerotonin) የተባሉ ነርቭ አነቃቂ ኬሚካሎች፣ የድብርት (ድባቴ) ሕመም ያለባቸው ሰዎች ጥሩ እንቅልፍ እንዳይተኙ (እንዳያገኙ) ያደርጋሉ፡፡ ስለዚህ ሕሙማኑ ጧት ሲነሱ ድብር ይላቸዋል፡፡ ለዚህ ነው ባለሙያዎች ብዙ ጊዜ ሕሙማኑ ከእንቅልፍ ሲነሱ መድኃኒታቸውን እንዲወስዱ የሚያዙት፡፡
የአጥንት መሳሳት መድኃኒቶች፡- ይህ የአጥንት በሽታ አብዛኛውን ጊዜ ያረጡ ሴቶችን አጥንት በጣም በመቦርቦር፣ በቀላሉ እንዲሰበርና በዝግታ እንዲያብጥ የሚያደርግ ነው፡፡ ሰውነታችን ታዲያ ለዚህ በሽታ የሚታዘዙትን እንደ ቦኒቫ እና ፎሳማክስ (Boniva and Fosamax) ያሉ መድኃኒቶችን በቀላሉ አይቀበልም፡፡
ስለዚህ ሐኪሞች ሕሙማኑ፣ ጧት በማለዳ ምንም ሳይቀምሱ ባዶ ሆዳቸውን መድኃኒታቸውን በአንድ ብርጭቆ ከዋጡ በኋላ፣ ምንም ሳይበሉ፣ ሳይጠጡ ወይም ሌላ መድኃኒትም ሆነ በተጨማሪነት የሚወሰዱ ሳፕሊመንቶችን ሳይወስዱ ለአንድ ሰዓት እንዲቆዩ ይመክራሉ፡፡
በእራት ሰዓት አካባቢ
ለቃር የሚወሰዱ መድኃኒቶች፡- ሆድ ከቀኑ 10 ሰዓት እስከ ሌሊቱ 8 ሰዓት ባለው ጊዜ ውስጥ፣ ከማንኛውም የዕለቱ ጊዜ (24 ሰዓት) ከሁለት እስከ ሦስት ጊዜ የበለጠ አሲድ ያመነጫል፡፡ እንደ ፔፕሲድ (Pepcid) ወይም ዛንታክ (Zantac) ያሉ አሲድ የሚቀንሱ መድኃኒቶች የሚወስዱ ከሆነ እራት ከመብላትዎ 30 ደቂቃ በፊት ይውሰዱ፡፡
ሆድ ከፍተኛውን የአሲድ መጠን የሚያመነጨው በሌሊት ስለሆነ መድኃኒቶቹ በዚህ ሰዓት ሲወሰዱ ለመቆጣጠር ይረዳቸዋል፡፡
የአለርጂ መድኃኒቶች፡- አብዛኛውን ጊዜ የመተንፈሻ አካላት ይብስ የሚታፈኑትና የበለጠ አጣዳፊ ሆነው የበሽታ መከላከያ ሴሎች የሚያመነጩት የሽታው ቀስቃሽ የሆነው ሄስታሚን (Histamine) የተባለ አፋኝ ምልክት መጠን ከፍተኛ የሚሆነው በጧት ማለዳ ነው፡፡
እንደ ክለሪቲን (Claritin) ያሉ የአለርጂ መድኃኒቶች በቀን ውስጥ አንዴ ከተወሰዱ የመከላከል ኃይላቸው ከፍተኛ ደረጃ ላይ የሚደርሰው ከስምንት እስከ 12 ሰዓት ባለው ጊዜ ነው፡፡ መድኃኒቱን በእራት ጊዜ መውሰድ፣ በማለዳ የሚከሰተውን ማፈን (የአለርጂ ምልክቶች) የበለጠ ለመከላከል ይረዳል፡፡ ስለዚህ የአለርጂ መከላከያ የሆነውን ፀረ ሄስታሚን በቀን ሁለት ጊዜ ጧትና ማታ ይውሰዱ፡፡
III.  በመኝታ ሰዓት የሚወሰዱ
የኮሌስትሮል መድኃኒት - በጉበት ውስጥ የሚፈጠረው የኮሌስትሮል (ስብ) ምርት መጠን ከፍተኛ የሚሆነው እኩለ ሌሊት ላይ ነው፡፡ ዝቅተኛ ምርት የሚኖረው ደግሞ ጧትና ከእኩለ ቀን ብዙም ሳይረፍድ ነው፡፡ ስለዚህ እንደስታቲን (Statin) ያሉ ደም ውስጥ ያለ የስብ መጠን የሚቀንሱ መድኃኒቶች መወሰድ ያለባቸው ከመኝታ ሰዓት በፊት ነው፡፡
የደም ግፊት መድኃኒቶች - አብዛኛውን ጊዜ የደም ግፊት መጠን ከፍ የሚለው ቀን ላይ ነው፡፡ ዝቅ የሚለው ደግሞ ሌሊት በመኝታ ጊዜ ነው፡፡ ነገር ግን ከፍተኛ የደም ግፊት ያለባቸው ብዙ ሰዎች በተለይ ዕድሜ እየጨመረ ሲሄድ ይህን የሌሊት ደም ግፊት ዝቅ ማለት በትክክል አያረጋግጡም፡፡ ከፍተኛ የደም ግፊት ደግሞ ለስትሮክ፣ ለልብ ሕመም (ኧርት አታክ) ለኩላሊት በሽታ መፈጠር መንስኤ ይሆናል፡፡
እንዴት መሰላችሁ? ሌሊት፣ የደም ግፊት አነስተኛ ነው ብለው ስለሚያስቡ፣ ሲተኙ፣ ምንም ዓይነት የደም ግፊት መቀነሻ መድኃኒት አይወስዱም፡፡ የደም ግፊቱ መጠን ከቀን ይቀንሳል ተባለ እንጂ አለ፡፡ ለዚህ ነው አንዳንድ ሰዎች የደም ግፊታቸው በዝቶ እንዳሸለቡ በዚያው የሚቀሩት፡፡
ስለዚህ ሐኪሞች የሌሊት የደም ግፊት መጠን ከቀኑ ጋር ተመሳሳይ እንዲሆንና የተጠቀሱት የበሽታ ስጋቶች እንዳይፈጠሩ፣ በመኝታ ሰዓት፣ የደም ግፊት መቀነሻ መድኃኒት መወሰድ እንዳለበት እያሳሰቡ ነው።
 IV. የሕመም ምልክት ሲሰማ የሚወሰዱ -
የመጋጠሚያ ሕመም - እንደ የፈረንሳይ ተመራማሪዎች እንደሚሉት፤ ከሆነ ብዙ ጊዜ ለመጋጠሚያ ሕመም ማስታገሻ በስፋት የሚወሰዱት እንደ ናፕሮክሲን (Naproxen)፣ ኢቡፕሮፊን (ibuprofen) ያሉ መድኃኒቶች፣ ሕመሙ ከፍተኛ ደረጃ ከመድረሱ 6 ሰዓት በፊት ቢወሰዱ፣ በትክክለኛው ሰዓት ሕመሙን ያስቆማሉ፡፡
ከሰዓት በኋላ ሕመሙ የሚያጠቃዎት ከሆነ በ5 ሰዓት ገደማ፣ ለምሽት ሕመም መከላከያ 10 ሰዓት አካባቢ፣ ለሌሊት ሕመም፣ ከእራት ጋር ማስታገሻዎቹን ቢወስዱ ጥሩ እፎይታ ያገኛሉ፡፡
ምንጭ - (“Readers digest – July 2014
USA” የተወሰደ)