Administrator

Administrator

“የሚስቅልህ ሰው ስለበዛ፣ ትክክል ነኝ ብለህ አታስብ”
(የእንግሊዞች አባባል)

ከዕለታት አንድ ቀን አንደ ቀንድ - አውጣ (Snail) ወደ አንድ ቡና ቤት ከመሸ በኋላ ይሄዳል፡፡ ከዚያም በሩን ያንኳኳል፡፡
ባለቡና ቤቱ፤ በሩን ዘጋግቶ እየጨራረሰ ነው፡፡
“ማነው?” ይላል የቡና ቤት ባለቤት፡፡
“እኔ ነኝ!” ይላል ቀንድ አውጣ፡፡
“ትንሽ መጠጣት ፈልጌ ነበር”
“መሸኮ! ከዚህ ወዲያ አላስተናግድም!”
“እረ በእግዚሃር አስተናግደኝ! ምንም ሄጄ እምዝናናበት ቦታ የለኝም፡፡ የት እንደምሄድም አላውቅም! እባክህ ተባበረኝ!”
“አያ ቀንዳውጣ! እየዘጋሁ ነው ስልህ ምንድን ነው ችግርህ? ትመለሳለህ ተመለስ አለበለዚያ ዋጋህን ታገኛለህ! ተግባባን?”
“ባለቡና ቤት፤ እኔ አንድ ነገር ሳልቀምስ ወደ መኝታዬ መሄድ አልችልም! ይገባሃል?”
“ቆይ እንግዲህ እንዲገባህ ምን ማድረግ እንደምችል አሳይሃለሁ!” እያለ የዘጋውን በር ይከፍትና ይወጣል፡፡
ቀንድ - አውጣው በሁኔታው ተደስቶና የበለጠውን ዕውነት አስረዳዋለሁ ብሎ ፍንድቅድቅ ብሏል፡፡
ሰውዬው ግን ንግግሩን ሁሉ አቋርጦ በንዴት ተወጥሮ ወደውጪ መጣና፤
“አንተ ማነኝ ብለህ ነው ይሄ ሁሉ ጉራ? ይሄ ሁሉ ያዙኝ ልቀቁኝ ማለት?” ሲል ጠየቀው፡፡
ቀንዳውጣውም፤
“ጌታዬ፤ ውሃ ጠምቶኝ ነው ያስቸገርኩህ፡፡ እባክህ…” ብሎ ሳይጨርስ፣ ባለሆቴሉ ባለ በሌለ ኀይሉ በቲራ ጠረገው፡፡ ቀንድ አውጣው ሩቅ ከመሽቀንጠሩ የተነሳ፤ የት ሄዶ እንደወደቀ እንኳን ያየው የለም!!
ከአንድ ዓመት በኋላ ቀንድ አውጣው ወደዚያው ሆቴል መጣ፡፡ ዛሬም ሰዓቱ በጣም ረፍዷል፡፡ ያ ባለ ሆቴል በሩ ሲንኳኳ፤
“ማነው?” አለ፡፡
“እኔ ነኝ!”
“ማ?”
“እኔ ቀንድ አውጣ!”
“አንተ ዛሬም ልትለክፈኝ መጣህ?”
“አይ፤ ዛሬስ አንድ ጥያቄ ብቻ ኖሮኝ ነው የመጣሁት”
ባለሆቴሉ ወጣና፤
“ምንድን ነው የፈለከው?”
ቀንዳውጣውም፤
“አንዲት ጥያቄ ብቻ ናት ያለችኝ፡፡”
“እሺ ተናገር?”
“ባለፈው ዓመት አሽቀንጥረህ ከጣልከኝ ቦታ እዚህ ለመድረስ ተጉዤ ተጉዤ፤ ይሄው ዛሬ ደረስኩኝ፡፡ ለመሆኑ ለምን ነበር እንደዛ በቲራ የመታኸኝ?!”
*    *    *
በየትኛውም ሰዓት ያረፈደ ሰው፤ ቅጣቱ እንደተጠበቀ መሆኑን አንርሳ፡፡ ማንም በመሸ ሰዓት ረግጦ ሊያሽቀነጥረን እንደሚችልም እንገንዘብ፡፡
ማዝገማችን፣ መንቀርፈፋችንና መዘግየታችን በራሱ መልክና ጊዜ ወደኛው ፊቱን አዙሮ እንደቀንድ አውጣው ሊያስመታን መቻሉ አይቀሬ ነው፡፡ ለምን ሆነ? ብለን በዓመቱ መጠየቅ ቢያንስ መሳቂያ ከመሆን አያሳልፈንም፡፡ ሌሎች ውቴላቸውን ዘግተው ሳይቆልፉ በፊት ነቅቶ መምጣት ብልህነት ነው፡፡
የሀገራችን ስሞች አስገራሚ ናቸው፡፡ በወትሮ ማዕረጉ የሹም/የንብረት ባለቤት የምንለው፤ ስሙ የኃደራ ስም ይባላል፡፡ ባላገር፣ ወታደር፣ ባላባት፣ ስደተኛ፤ ባለቤት እንዲሉ፡፡ የሀገር ባለኃደራነት መሆኑ ነው፡፡
የማኅደር ስም የሚባል አለ ደግሞ፡፡ አደራችንን አንዘንጋ የሚል የማደሪያ ስም ነው፤ ቃሉ፡፡ በየጊዜው ቃል ስንገባም “ዕውን እፈጽመዋለሁ? እንበል፡፡ የመሬት፣ የቦታ ርስት ወዘተ ንብረት ባለቤትነት ዶሴ እንደማለት ነው፡፡ የሚገርመው የማህደርም፤ የባለኃደራም ሌብነት ነበር፡፡ የዱሮ ዘመን ባለቤትነት ከዛሬ ሊለይ ይችላል፡፡ እንደ እውነቱ ግን ሁሉም ከላይ እየታዘዘ ከመፈፀሙ አኳያ፤ የቋንቋ ነገር ካልሆነ በቀር  ሁሉም ስሙ “ሙስና” ነው፡፡
የተቀብዖ ስም እንዲል መጽሐፍ ሹመት ብቻውን ፍሬ አያፈራም! የተቀባንበት፣ የተሾምንበት፣ ኃላፊነት የተቀበልንበት ስም ያው የተቀብዖ ስም ነው፡፡ ታዲያ “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋልን”፣ “ከሰው መርጦ ለሹመት፣ ከእንጨት መርጦ ለሹመት”ን እንደበቀቀን እያቀነቀንን፤ እስከመቼ እንጓዛለን? ምንም ዓይነት ኮርስ ልውሰድ፣ ዋናው ቁም ነገር፣ “ሹመቱ ለአገር እንዳገለግል፣ ኃላፊነቴን እንድወጣ ነው” እንላለን? ወይስ በሹምነቱ ዘመን ያልበላ፣ እየበላ ያለና ወደፊትም የማይበላ ማን ሹም አለ? ከበይው የሚይቋደስ፣ ባለ አላባ፣ ባለ ኮሚሽንስ ማን አለ?
ሐዲድ ተሠራ ስንል ሲመነቀል፣ አገር ያደነቀው ምሁር አፈራን ስንል፤ “አያሌው ሞኙ ሰው አማኙ” ሲለን፣ ውጪ አገር ወኪል አድርገን ስንልክ “አፍንጫችሁን ላሱ” ሲለን፤ ምን ዓይነት ተዓማኒነት ልናስተናገድ ነው?
“እያንዳንዱ አሣ አጥንት እንዳለሁ ሁሉ፤ እያንዳንዱ ሰው ስህተት አለው” ይላሉ አዋቂዎች፡፡ ሆኖም ይህን ብሂል መሠረት አድርገን ስንሳሳት፣ አውቀን ስንሳሳትና ለሁሉም ዋናው ሰበብ ማግኘት ነው ስንባል መክረማችን፤ አሳሳቢ ነው፡፡
“አንድ ‹ባሪያ› በምድር ላይ እየተጓዘ እስካለ ድረስ ያንተ ነፃ መሆን (ተዓምር) ፍፁም አልሆነም!” ይላሉ የፍልስፍና ሊቃውንት፡፡
ዕውነት ነው፡፡ የአስተሳሰብ ባርነት፣ የአመለካከት ባርነት፣ የጠባብነት ባርነት፣ የመላላት ባርነት፣ እኔን ከተከተልክ - ነፃ ነህ የመባል ባርነት፤ ዲሞክራሲን እንደፈለጉ በሚተረጉሙና በሚተገብሩ የፖለቲካ ባላባቶች መጠርነፍ ባርነት…ወዘተ ውስጥ መኮድኮድ እርግማን ነው፡፡ ስለሆነም እንዴት? ለምን? ብሎ መጠየቅ ታላቅ እርምጃ ነው!
“የመጨረሻው ከባድ የብረት በርም የሚከፈተው በትንሽ ቁልፍ ነው” (ቻርለስ ዲከንስ)
ቻርለስ ዲከንስ ትንሽ ነን ብለን ተስፋ አንቁረጥ፡፡ ችሎታና ዕውቀቱን ከያዝን የመጨረሻውን ከተምበሪ ልንከፍተው እንችላለን ሲል ነው፡፡ አንዱ የእኛ ፖለቲከኞች ችግር እራስን አሳንሶ ማየት የሚሆነው ለዚህ ነው!!
የሚከተለው አገርኛ ግጥም በልኩ ያስገነዝበናል፡፡
“ዓመት ነው?”
ዕድሜ ነው?
ስሜት ነው?
ተስፋ ነው መጪው ቀን?
ወይስ ኩራት እራት፣ ከውስጡ የቀረ፣ ትርጉም ይኖር ይሆን?”
ተስፈኝነት፣ አዎንታዊነት፣ ትዕግሥትና ጽናት ከሌሉ ለአገራችን ትግል አስተዋጽኦ አይዋጣልንም፡፡
ማርቲን ሉተር ኪንግ፤
“ዓለም ነገ ልታልቅ ነው ቢሉኝም፣ ዛሬ ዛፍ መትከሌን አልተውም” ያለን ለዚህ ነው፡፡
በአንፃሩ ትላንትም፣ አሁንም፣ ያለውን ሁኔታ እደግፋለሁ፤ አንደኛ የልማት አርበኛ ነኝ፤ አንደኛ “ኮብል ስቶኒስት ነኝ!”፤ አንደኛ አገራዊ ምሁርና የሚዲያ ተቆርቋሪ፤ የፖለቲከኛ ተንታኝ ነኝ የሚል ቢበዛ፤ ቆም ብሎ “ዕውን ነውን?” ማለት ያባት ነው! “የሚስቅልህ ሰው ስለበዛ፣ ትክክል ነኝ ብለህ አታስብ!” የሚለው የእንግሊዞች አባባል፤ ፍሬ - ጉዳይ አለው የሚባለው ለዚህ ነው፡፡


‘ሰላ በይልኝ’ በሚለው ነጠላ ዜማው ከህዝብ ጋር ተዋወቀው ድምጻዊ ጃኪ ጎሲ፣ የሙዚቃ ኮንሰርት ለማቅረብ ከታዋቂው የቢራ አምራች ኩባንያ ሄኒከን ጋር የአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ብር ስምምነት ሊፈራረም ነው፡፡
አድማስ ሬዲዮ ከአትላንታ እንደዘገበው፣ ወጣቱ ድምጻዊ ጃኪ ጎሲ ከሰሞኑ ከሄኒከን ጋር ያደርገዋል ተብሎ የሚጠበቀው ይህ ስምምነት በአዲስ አበባ ከተማ ለሚከናወን የሙዚቃ ኮንሰርት ነው፡፡ የሙዚቃ ኮንሰርቱ የሚቀርብበትን ትክክለኛ ጊዜ መናገር ባይቻልም ለመጪው የኢትዮጵያውያን አዲስ አመት ዋዜማ ሊሆን እንደሚችል ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡
በተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶችና የዓለም አገራት እየተዘዋወረ የሙዚቃ ኮንሰርቶችን በስፋት እያቀረበ የሚገኘው ድምጻዊው፣ ከወራት በፊት ከዝግጅት ክፍላችን ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ በአገር ውስጥም የሙዚቃ ኮንሰርቶችን ማዘጋጀት ዕቅድ እንዳለው መናገሩ ይታወሳል፡፡

Saturday, 14 June 2014 12:47

የፖለቲካ ጥግ

በህዝቦች ላይ ፅኑ እምነት አለኝ፡፡ እውነቱ ከተነገራቸው ማንኛውንም ብሄራዊ ቀውስ እንደሚጋፈጡት መተማመን ይቻላል፡፡ ዋናው ነገር ተጨባጩን ሃቅና ቢራውን ወደ እነሱ ማቅረብ ነው፡፡
አብርሃም ሊንከን
አንተ አንድ ካፒታሊስት አሳየኝና እኔ ደሞ መጣጩን አሳይሃለሁ፡፡
                            ማልኮልም ኤክስ
አብዮቱ ከጥበብ ጋር አስተዋወቀኝ፤ ጥበብ በተራው ከአብዮቱ ጋር አስተዋወቀኝ፡፡
አልበርት አንስታይን
ሰዎች በአንድነት በዝምታ አሲረው በተቀመጡበት ክፍል ውስጥ አንዲት እውነተኛ ቃል የሽጉጥ ተኩስ ትመስላለች፡፡
Czestaw Mitosz
ድምፅ መስጠት ልክ እንደጠብመንጃ ነው፡፡ ጠቃሚነቱ በተጠቃሚው ሰው ባህርይ ይወሰናል፡፡
ቴዎዶር ሩስቬልት
የሰው ልጅ የመጀመሪያ ሥራው ለራሱ ማሰብ ነው፡፡
ጆሴ ማርቲ
ታላቁ ዲሞክራሲያችን፤ አሁንም ድረስ ጅል ከብልህ የበለጠ ሃቀኛ ነው ብሎ የማሰብ አዝማሚያ ይታይበታል፡፡
በርትራንድ ራሰል
ምርጫ የህዝብ ነው፡፡ ውሳኔውም የእነሱ ነው፡፡ ጀርባቸውን ለእሳቱ ለመስጠትና መቀመጫቸውን ለማቃጠል ከወሰኑ፣ ቁስላቸው ላይ ለመቀመጥ ይገደዳሉ፡፡
አብርሃም ሊንከን
ዲሞክራሲ የነፃነት መገለጫ አይደለም፡፡ ዲሞክራሲ ሁለት ተኩላዎችና አንድ በግ ምሳቸውን ምን እንደሚበሉ ድምፅ መስጠት ነው፡፡ ነፃነት የሚመነጨው ተመልሰው ሊወሰዱ የማይችሉ የተወሰኑ መብቶችን ከማክበር ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ በ99 በመቶ ድምፅ እንኳን ዲሞክራሲ እውን አይሆንም፡፡
ማርቪን ሲምኪን

      ብራዚላዊው  ኔይማር ዳሲልቫ ሳንቶስ  ሮናልዶ እና ሜሲ ለዓለም ዋንጫው ድምቀት የሚሆኑ ምርጥ ተጨዋቾች ናቸው ሲል ተናገረ፡፡ በባርሴሎና ክለብ እስከ 2018 ለመጫወት የኮንትራት ውል የፈፀመው ኔይማር ዳሲልቫ ሳንቶስ በሁለት ጎሎች ዓለም ዋንጫውን መጀመሩ ለብራዚል 6ኛ የዓለም ዋንጫ ስኬት ከፍተኛ ተስፋ ያሳደረ ሆኗል፡፡ ሶስቱ ተጨዋቾች ብሄራዊ ቡድኖቻቸውን ለዓለም ዋንጫ ድል ለማብቃት ብቻ ሳይሆን በኮከብነት ለሚሰጡ ልዩ ሽልማቶች በዋና እጩነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
የ29 ዓመቱ ክርስትያኖ ሮናልዶ አገሩን በአምበልነት እየመራ በዓለም ዋንጫ ደማቅ ታሪክ የመስራት እድሉ ብራዚል ላይ የመጨረሻ ነው፡፡ ለ26 ዓመቱ ሊዮኔል ሜሲም ከዘንድሮ ዓለም ዋንጫ የተሻለ አጋጣሚ የለም፡፡
ለ22 ዓመቱ ኔይማር ዳሴልሻ ግን ይህን የስኬት ጣሪያ ለማስመዝገብ ሁለት ዓለም ዋንጫዎች ይቀሩታል፡፡
ሮናልዶና ሜሲ በክለብ ደረጃ የሚወዳደሩባቸውን ሊጎች በጎሎች  እያንበሸበሹ፤ ዋንጫዎችን እየሰበሰቡ፤ የቆዩ ሪከርዶችን እየሰባበሩና አዳዲስ እያስመዘገቡ፤ የኮከብ ተጨዋችነት ሽልማቶችን እየተፈራረቁ ሲጎናፀፉ ቆይተዋል። ብቸኛው የቀራቸው የስኬት ጣሪያ ዓለም ዋንጫ ብቻ ነው። ሁለቱም ተጨዋቾች በክለብ ደረጃ የተሳካላቸውን ያህል  በየብሄራዊ ቡድኖቻቸው የላቀ ውጤት አለማስመዝገባቸው ሁሌም  ለትችት ይዳርጋቸዋል፡፡
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ላይ ሮናልዶ ከፖርቱጋል፤ ሊዮኔል ሜሲ ደግሞ ከአርጀንቲና ጋር 3ኛውን የዓለም ዋንጫ ተሳትፏቸውን ያደርጋሉ፡፡ ሁለቱም ተጨዋቾች በዓለም ዋንጫው አገሮቻቸውን ተሸክመው የማራዶና፤ የፔሌን፤ የክሩፍና የዚዳን ስኬት ማምጣታቸው ቢጠበቅም  የሚሳካላቸው ግን አይመስልም፡፡ ከብራዚሉ 20ኛው ዓለም ዋንጫ በፊት በሁለት ዓለም ዋንጫዎች ለአርጀንቲና 571 ደቂቃዎች የተጫወተው ሜሲ ያስመዘገበው አንድ ጎል ብቻ ሲሆን ሮናልዶም ባለፉት ሁለት ዓለም ዋንጫዎች በፖርቱጋል ማልያ 754 ደቂቃዎች ተሰልፎ ያገባው ሁለት ብቻ ነው።  ሶስት የዓለም ዋንጫ ከተሳተፉት የቀድሞ ተጨዋቾች  ጋር ሲነፃፀር ሮናልዶና ሜሲ ምን ያህል ወደኋላ እንደቀሩ ያሳያል።
ዴንማርኩ ዳል ቶማሰን 5፤ የብራዚሎቹ ፔሌ 12 ሮናልዶ 15 እንዲሁም ዘንድሮ የምንግዜም ከፍተኛ ክብረወሰኑን ከሮናልዶ ይነጥቃል የተባለው ሚሮስላቭ ክሎስ 14 የዓለም ዋንጫ ጎሎች በስማቸው አስመዝግበዋል።
ሜሲ በባርሴሎና ክለብ 277 ጨዋታዎች አድርጎ 243 ጎሎች ሲያስመዘግብ ሮናልዶ ደግሞ በ3 ክለቦች ስፖርቲንግ ሊዝበን፤ ማን ዩናይትድና ሪያል ማድሪድ 386 ጨዋታዎች በማድረግ 264  ጎሎች አስቆጥሯል፡፡
በክለብ ደረጃ ሊዮኔል ሜሲ 6 የሊግ፤ 3 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ ሌሎች ተጨማሪ 4 ዋንጫዎችን ወስዷል፡፡ ሮናልዶም በ3 ክለቦች 4 የሊግ፤ ሁለት የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ እና ሌሎች 4 ዋንጫዎችን አግኝቷል፡፡ 4 ጊዜ በዓለም ኮከብ ተጨዋቾች የወርቅ ኳስ የወሰደው ሜሲ ለአርጀንቲና በ84 ጨዋታዎች 37፤ ሁለቴ የወርቅ ኳስ የተሸለመው ሮናልዶ ለፖርቱጋል በ110 ጨዋታዎች 49 ጎሎች አላቸው፡፡


  • አገር ሲፈርስ እንዲህ ነው? ኢራቅ ለሶስት እየተሰነጠቀች ነው
  • 1ሺ የአሸባሪ ቡድን ታጣቂዎች 30ሺ የኢራቅ ወታደሮችን አሸነፉ
  • በ3 ቀናት ውስጥ ትልልቅ ከተሞችን እየወረረ ከዋና ከተማዋ ደጃፍ ደርሷል
  • አሸባሪው ቡድን በሂሊኮፕተሮች፣ በታንኮች፣ በብረት ለበስ መኪኖች ተንበሻበሸ
  • ከመንግስት ባንክ 480 ሚሊዮን ዶላር የሚሆን ጥሬ ገንዘብ አግኝተዋል
  • በአንድ ቀን ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሞሱል ከተማ ነዋሪዎች ተሰደዱ

          የኢራቅ ሁለተኛዋ ትልቅ ከተማ ሰሞኑን ለአቡበከር ተንበርክካለች። በነዳጅ ሃብት የሚታወቁ ከተሞችና አካባቢዎችን ጨምሮ ቲክሪትሪትና ሳማራ፣ የመሳሰሉ ከተሞችም እንዲሁ አቡበከር በሚመራው አሸባሪ ቡድን (አይሲስ) ስር ገብተዋል፡፡ ማክሰኞ እለት በተጀመረው ወረራ ከሶሪያ ድንበር ተነስቶ በሦስት ቀናት ባግዳድ ደጃፍ ደርሷል የአቡበከር አይሲስ፡፡   የአቡበከር ታሪክ ብዙ ባይታወቅም፤ አላማው ግን ድብቅ አይደለም። ሶሪያን፣ ኢራቅንና ሊባኖስን አንድ ላይ ጨፍልቆ፤ ከቱርክ እና ከኢራን የተወሰነ አካባቢ ቆርሶ፣ ሳውዲ ዓረቢያንና ግብፅን ጭምር በመጠቅለል ሃይማኖታዊ መንግስት ለመመስረት የተቋቋመ ነው። ሊሆን የማይችልና የማይጨበጥ ከንቱ ቅዠት ይመስላል?
አስፈሪ ቅዠት መሆኑ ባያከራክርም፤ “ሊሆን የማይችል ነገር” አይደለም፡፡ የአይሲስ የሰሞኑ ዘመቻ ለዚህ ምስክር ነው፡፡
አንድ ሺ የሚሆኑ አክራሪው ቡድን ታጣቂዎች፣ በሞሱልና በአካባቢው ላይ በከፈቱት ጥቃት 30ሺ ገደማ የመንግስት ጦር ጨርቄን ማቄን ሳይል ሸሽቶ ሄዷል - አንድ የጦር ካምፕ ውስጥ ተቀምጠው የነበሩ 20 ታንኮችና 2 ሄሊኮፕተሮችን ጨምሮ በርካታ ብረት ለበስ መኪኖችና የጦር መሳሪያዎች በአክራሪው እጅ ገብተዋል። የመኪኖቹ ብዛት ቀላል አይደለም። በመቶ የሚቆጠሩ የጦር መኪኖች ናቸው የተማረኩት። ይህም ብቻ አይደለም። የአይሲስ ተዋጊዎች ሞሱል ከሚገኘው የመንግስት ባንክ ውስጥ 480 ሚሊዮን ዶላር የሚገመት ጥሬ ገንዘብ አፍሰው ወስደዋል።
ከአንድ የጦር ካምፕ ያን ሁሉ የጦር መሳሪያና ንብረት የማረኩ የአይሲስ ታጣቂዎች፤ ከሌሎች የጦር ካምፖች ምን ያህል ምርኮ እንደሰበሰቡ ቆጥሮ ለመጨረስ አስቸጋሪ ነው፡፡ 30ሺ ያህል ወታደሮችን አሰልፈው የነበሩ ሁለት የመንግስት ክፍለ ጦሮች፤ በአንድ ምሽት ብን ብለው ጠፍተዋል፡፡ ካምፖቻቸውን እየጣሉ፣ መሳሪያቸውን እየወረወሩ፣ ወታደራዊ ልብሳቸውን እያወለቁ የሸሹት የመንግስት ወታደሮች በየአቅጣጫው ተበታትነዋል። ማምለጥ አቅቷቸው በአሸባሪው ቡድን የተማረኩ በሺ የሚቆጠሩ ወታደሮች ደግሞ እንደ እንስሳ እየታገዱ ሲገረፉና ሲደበደቡ ታይተዋል፡፡
ድንበር ተሻጋሪ ሃይማኖታዊ መንግስት ለመመስረት ዘመቻ እያካሄደ የሚገኘው አይሲስ፣ ረዥም ታሪክ የለውም። በእርግጥ ተዋጊዎቹና መሪዎቹ አዲስ አይደሉም። በኢራቅ የአልቃይዳ ወኪል በመሆን ለአመታት ሽብር ሲፈጥሩ የነበሩ ናቸው። ከአልቃይዳ ተገንጥለው አይሲስ የተሰኘውን ቡድን የመሰረቱት ግን የዛሬ አመት ገደማ ነው። “አልቃይዳ ለዘብተኛ ነው በሚል ነው” የተገነጠሉት። በሌላ አነጋገር፤ የአይሲስ ተዋጊዎች ከአልቃይዳ የባሱ የሃይማኖት አክራሪዎች ናቸው፡፡
ሶሪያ ውስጥ በስተሰሜን ሰፊ ግዛት ለመቆጣጠር ሲዋጋ የከረመው አይሲስ፤ በኢራቅ በዋና ከተሞች በርካታ የሽብርና የፍንዳታ ጥቃቶችን ከመፈፀም ቦዝኖ አያውቅም፡፡ ሰሜናዊ የኢራቅ ግዛቶችን ለመቆጣጠር ዘመቻ የጀመረው ግን በዚህ ሳምንት ነው፡፡ ማክሰኞ እለት በትልቅነቷ ከባግዳድ ቀጥላ የምትጠቀሰው ሞሱል ከተማ በአይሲስ ተወረረች የሚለውን ዘገባ ለማመን የተቸገሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ አንድ ሺ የማይሞሉ የአይሲስ ተዋጊዎች እንዴት እንዴት 30ሺ የመንግስት ጦርን ያሸንፋሉ? ግን አሸነፉ፡፡ ጦሩ ካልተዋጋ ቁጥር ብቻውን ዋጋ የለውማ፡፡
ለነገሩ የአሸባሪው ቡድን ታጣቂዎችም እንዲያ በቀላሉ ማሸነፋቸው አስገርሟቸዋል። ከከተማዋ ባንክ ገንዘብ ዘርፈው፣ ከጦር ካምፖችም የጦር መሳሪያዎችን ማርከው ወደ ሶሪያ ለማምራት እቅድ የነበራቸው የአይሲስ ታጣቂዎች፤ በሞሲል ባገኙት ፈጣን ድል ተነሳስተው ዘመቻውን ለመቀጠል እንደወሰኑ ተዘግቧል። ጊዜ አልፈጀባቸውም፡፡ ረቡዕ እለት ከሰሜን ወደ ደቡብ በመገስገስ፣ የሳዳም ሁሴን የትውልድ ስፍራ የሆነችውንና በነዳጅ ምርት የምትታወቀውን ቲክሪትን ይዘዋል።
የአይሲስ ተዋጊዎች ሐሙስ እለት ትልቁ የኢራቅ ነዳጅ ማጣሪያ የሚገኝበት የባይጂ ከተማን እንደወረሩ የገለፀው ግሎብ ኤንድ ሜይል በበኩሉ፤ በ50 መኪኖች ተጭነው የመጡት ተዋጊዎች የነዳጅ ማጣሪያውን ያልወረሩት የመንግስትን ጦር ፈርተው እንዳልሆነ ጠቅሷል። ከአካባቢው የጎሳ መሪዎች ጋር ለመስማማት ያህል ነው ወደ ነዳጅ ማጣሪያው ያልገቡት። የመንግስት ጦርማ አካባቢውን ጥሎ ጠፍቷል፡፡
በዚያው እለት ይበልጥ ወደ ደቡብ አቅጣጫ በመጓዝ  ሳማራ የተባለች ከተማ የደረሱት የአይሲስ ተዋጊዎች፤ ዘመቻችን ወደ ባግዳድ ይቀጥላል ሲሉ ዝተዋል፡፡ በእርግጥም ባግዳድ ለመግባት 80 ኪሎሜትር ነው የሚቀራቸው፡፡ በአይሲስ ግስጋሴ የተደናገጠው የባግዳድ መንግስት፣ የጦር አውሮፕላኖችንና ሄሊኮፕተሮችን በማሰማራት ድብደባ አካሂዷል።
በሰሜን ምስራቅ በኩል “የኩርዶች መሬት” ብለው የከለሉ ባለስልጣናት እጃቸውን አጣጥፈው አልተቀመጡም። ከአክራሪው ቡድን ጋር ባይዋጉም፤ የኢራቅ ጦር ጥሏቸው የሄዱ የጦር ካምፖችንና የአየር ሃይል ጣቢያዎችን ተቆጣጥረዋል። ያ ሁሉ ጦር መሳሪያ በአክራሪዎች እጅ እንዳይገባ በመስጋት አካባቢውን እንደተቆጣጠሩ የኩርድ አስተዳደር ጦር ሃይል መኮንንን ለአሶሼትድ ፕሬስ ገልፀዋል። ኪርኩክ ከተማ ሙሉ ለሙሉ በኩርድ አስተዳደር ጦር (ፐሽመርጋ) እጅ ውስጥ መሆኗም ተዘግቧል።
በሃይማኖትና በጎሳ የተቧደነው የአገሪቱ ፖለቲካ፤ አክራሪውን ቡድን የመመከት አቅም ያለው አይመስልም። “የሺዓ ሃይማኖት ተከታይ” በሚል የተቧደኑ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች ይበዙበታል የሚባለው የአገሪቱ መንግስት፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አርቅቆ ለፓርላማ ቢያቀርብም ተቀባይነት አላገኘም። “የሱኒ ሃይማኖት ተከታይ” በሚል የተቧደኑ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች ተቃውመውታል። “የኩርድ ተወላጆች” በሚል በዘር የተቧደኑ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞችም እንዲሁ። የአገሪቱ መንግስት ምን ያህል በሃይማኖትና በዘር እንደተከፋፈለ ለመረዳት ፓርላማውን ማየት ብቻ ይበቃል፡፡ አገሪቱ እንዲህ እየታመሰች፤ ከ325 የፓርላማ አባላት መካከል፤ 130 ያህሉ ብቻ ናቸው ለስብሰባ የመጡት፡፡ ቢያንስ ቢያንስ 163 አባላት ካልተገኙ ፓርላማው ምንም አይነት ውሳኔ ማስተላለፍ አይችልም፡፡
የአክራሪው ቡድን ከሁሉም በፊት ማስጠንቀቂያ ያስተላለፈው ለመንግስት ወታደሮች፣ ፖሊሶችና የደህንነት አባላት ነው። “ንስሃ ግቡ” የሚለው የቡድኑ ማስጠንቀቂያ፤ የንስሃ ቦታዎች እንደተዘጋጁ ጠቅሶ፤ ንስሃ የማይገባ ወታደርም ሆነ ፖሊስ እንደሚገደል ገልጿል። በቀን አምስቴ መስገድ ግዴታ መሆኑን ቡድኑ አሳስቦ፤ አልኮል መጠጥና ሲጋራ ተከልክሏል፤ የአገሪቱን ባንዲራ መያዝም ወንጀል ነው ብሏል። ሴቶች ከላይ እስከ ታች የሚሸፍን ልብስ ማድረግ ግዴታቸው እንደሆነና ከቤት መውጣት እንደማይችሉ ተነግሯቸዋል።
የአይሲስ ተዋጊዎች ጥብቅ የሃይማኖት ህግ በማወጃቸውና የተማረኩ ፖሊሶችን ሲገድሉ በመታየታቸው ብዙ ነዋሪዎች አካባቢውን እየሸሹ ሲሰደዱ ሰንብተዋል። ባለፉት አመታት ግማሽ ሚሊዮን ነዋሪዎቿ በስደት የሸሿት ሞሱል፤ ሰሞኑን ደግሞ ተጨማሪ ግማሽ ሚሊዮን ነዋሪዎች ከተማዋን ጥለው እንደተሰደዱ ቢቢሲ ዘግቧል። ብዙዎቹ ስደተኞች የኩርድ ተወላጆች ወደሚበዙበት አካባቢ ነው የሸሹት፡፡ የኢራቅ ግዛት ቢሆንም፤ “የኩርዶች ክልል” የራሱን ጦር አደራጅቶ አካባቢውን የሚያስተዳድር ራሱን የቻለ መንግስት ነው ማለት ይቻላል፡፡
አሁን ደግሞ አይሲስ የሱኒ ሃይማኖት ተከታዮች የሚበዙባቸውን ከተሞች እየተቆጣጠረ ነው።  ኢራቅን ሙሉ ለሙሉ መቆጣጠር ባይችል እንኳ “የሱኒዎች ግዛት” በሚል የራሱን መንግስት ለማቋቋም እንደሚሞክር ይገመታል፡፡ በስተደቡብ ደግሞ የሺዓ ሃይማኖት ተከታዮች የሚበዙበት ሌላ ግዛት አለ። ኢራቅ እንዲህ በዘር እና በሃይማኖት ተሰነጣጥቃ እየፈረሰች ነው፡
ጐረቤት አገሮችና አሜሪካ ምን አስበዋል?
በሞሱል የቱርክ ቆንስላ ውስጥ የሚሰሩ ዲፕሎማቶች፣ የልዩ ሃይል አባላት፣ ተቀጣሪዎችና ቤተሰቦችን ጨምሮ 50 የቱርክ ዜጎች በአይሲስ ተዋጊዎች እንደተያዙበት የገለፀው የቱርክ መንግስት በታጋቾቹ ላይ አንዳች ጉዳት ቢደርስ መረር ያለ የአፀፋ እርምጃ እንደሚወስድ የቱርክ መንግስት አስጠንቅቋል።
“የአይሲስ ዘመቻ ሺዓን ለማጥፋት የሚካሄድ የአሸባሪ ሱኒዎች ሴራ ነው” ብሎ የሚያስበው የኢራን መንግስት፤ እነዚህ ሃይማኖት የለሽ አረመኔ አሸባሪዎችን ከኢራቅ ምድር ለማጥፋት ድጋፍ እሰጣለሁ ብሏል፡፡ የኢራን መንግስት በተፈጥሮው ሃይማኖታዊ መንግስት ቢሆንም፤ በሺዓ እምነት ላይ እንጂ በሱኒ እምነት ላይ የተመሰረተ ሃይማኖታዊ መንግስትን አይደግፍም - “ዋነኛ ጠላት” አድርጐ ነው የሚቆጥረው፡፡ የሳዑዲ መንግስት ደግሞ በተቃራኒው፤ የሺዓ እምነትን ይቃወማል፡፡ ለዚህም ነው በመካከለኛው ምስራቅ በሃይማኖት አክራሪነት የሚነሱ ግጭቶች ላይ ኢራንና ሳዑዲ አረቢያ በጠላትነት የሚሰለፉት፡፡
የአሜሪካ ነገርስ?....
በ25 ቢሊዮን ዶላር ወጪና በአሜሪካ እርዳታ የተቋቋመው የኢራቅ መንግስት ጦር፤ አንድ ሚሊዮን የሚደርስ ቢሆንም፣ ውጤታማ አልሆነም። ከ3 ዓመት በፊት ከኢራቅ ለቅቆ የወጣው የአሜሪካ ጦር፤ ለኢራቅ መንግስት ድጋፍ ከመስጠት አይመለስም። በአይሲስ ተዋጊዎች ላይ የጦር አውሮፕላን ድብደባ እንዲያካሂድ የኢራቅ መንግስት በተደጋጋሚ ለአሜሪካ ጥያቄ እንዳቀረበና እስካሁን ተቀባይነት ሳያገኝ እንደቆየ ግሎብ ኤንድ ሜይል ዘግቧል።


አቡበከር የሺዓ ሃይማኖት ተከታዮች ላይ በመዛት ለደጋፊዎቹ ያስተላለፈው ቅስቀሳ
“ነፃ የምታወጡት ምድር ላይ የሺዓዎች እግር እንዳይደርስ አድርጉ”
“ወደ ባግዳድ ገስግሱ፤ “የምናወራርደው ሂሳብ አለ” በማለት በከተማዋ ቅጥር ሺዓዎችን ግጠሟቸው፡
ለትንፋሽ እንኳ ጊዜ እንዳትሰጧቸው፡፡”
“ሺዓዎች የተሰናከሉ ህዝቦች ናቸው፤ ሰውንና ድንጋይን የሚያመልኩ ሃይማኖት የለሾች ናቸው፡፡
የሺዓ ሃይማኖት ተከታይ የሆኑትን ፕሬዚዳንት አልማሊኪን በተመለከተ አቡበከር ምን ይላል?
“ሙታንታ ሻጭ እንጂ ፕሬዚዳንትና የጦር ሃይሎች ጠቅላይ አዛዥ መሆን አትችልም
“ኢራቅን የመቆጣጠር እድል አምልጧችኋል”
“ሺዓዎች በህይወት እስካሉ ድረስ ይረግሟችኋል”
“በነጃሳዋ ካርባላና በጣኦት አምላኪዋ ናጃፍ ላይ እንዘምታለን” (ሁለቱ ከተሞች የሺዓ ቅዱስ ስፍራዎች ናቸው)

    በስፔን ርዕሰ ከተማ በማድሪድ ወደ 15ሺ ታክሲዎች ቢኖሩም፣ ረቡዕ እለት ለምልክት ያህል አንድም ታክሲ አልነበረም። የለንደን ታክሲዎችም ድምፃቸውን አጥፍተው ውለዋል፡፡ በመኪኖቹ ፋንታ ሾፌሮች ናቸው ሲጮሁ የነበሩት፡፡ 4ሺ የለንደን ባለታክሲዎች ቅሬታቸውን ለማሰማት በከተማዋ ዋና ዋና ጐዳናዎች የተቃውሞ ሰልፍ አካሂደዋል። በጀርመንም፣ በሺ የሚቆጠሩ የታክሲ ሹፌሮች በርሊን ከተማ በሚገኘው ኦሊምፒክ ስቴዲየም ዙሪያ ተሰብስበው ተቃውሟቸውን ገልፀዋል።
የፓሪሶቹ ባለታክሲዎች የባሰባቸው ናቸው። ወደ አውሮፕላን ማረፊያ የሚወስደውን መንገድ ዘግተው ነው የቆሙት። በሌሎች ጎዳናዎች ደግሞ ታክሲያቸውን በዝግታ እያንቀራፈፉ የትራፊክ ጭንቅንቅ ሲፈጥሩ ውለዋል። ማርሴ፣ ሚላን፣ ሮም፣ ኔፕልስ... ትልልቆቹ የጣሊያን ከተሞችም ከባለታክሲዎች አድማ አላመለጡም። ባለታክሲዎች ሰው ሲያመላልሱ ሳይሆን፣ የቅስቀሳ ወረቀት ሲበትኑ ቀኑን አሳልፈውታል፡፡
ለንደን፣ ፓሪስ፣ ሮም፣ በርሊን፣ ማድሪድ... በአውሮፓ ዋና ዋና ከተሞች፣ ባለታክሲዎች በአድማ ስራ ያቆሙት ለምን ይሆን? ተፎካካሪ ስለመጣባቸው ነው። ባለ መኪና ሁሉ ተፎካካሪያቸው ሆኗል - ኡበር በተሰኘ ኩባንያ ምክንያት።
“ኡበር” አስገራሚ ኩባንያ ነው፡፡ በአሜሪካም ሆነ በአውሮፓ ከተሞች፣ የታክሲ አገልግሎት ረዥም እድሜ አስቆጥሯል - ከ80 ዓመት በላይ። ኡበር ግን፤ ገና የ5 ዓመት ጨቅላ ነው። እንዲያም ሆኖ፤ በአለም ካሉት የታክሲ አገልግሎት ድርጅቶች ሁሉ ይበልጣል። ከታላቁ የእንግሊዝ አየርመንገድም ይልቃል። አይገርምም? የድርጅቱ ቢሮ የሚገኘው አሜሪካ ሳንፍራንሲስኮ ነው። ግን በአለም ዙሪያ በመቶ ከተሞች አገልግሎት ይሰጣል። ይሄስ ይገርማል? የታክሲ አገልግሎት የሚያቀርብ ኩባንያ ነው ቢባልም፤ ታክሲዎች የሉትም። አጃኢብ ነው፡፡ እና  የኩባንያው ስራ ምንድነው?
የኩባንያው ዋና ስራ፤ ባለመኪኖችንና ተሳፋሪዎችን፣  በኢንተርኔት አገናኝቶ “ማዳበል” ነው። አሁንማ ኡበር በከፈተው ቀዳዳ ሉሎች ኩባንያዎች እየገቡ፣ ነባሩ የታክስ አገልግሎት በአጭር ጊዜ ውስጥ መልኩ ተቀይሯል፡፡
ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ 11 ሰዓት ላይ፣ ሳሪስ አካባቢ ካለው ቢሮ ወጥተው፣ የአዲስ አበባ የተለያዩ ቦታዎችን... ጎተራን፣ መስቀል አደባባይን፣ መገናኛን አቆራርጠው ኮተቤ አካባቢ ወደሚገኘው መኖሪያ ቤትዎ እንደሚያመሩ ያውቃሉ እንበል። ቶዮታም ይሁን ቢኤምደብሊው…የግልዎ አስተማማኝ መኪና ይዘዋል። ግን የነዳጅ ወጪው አልቻሉትም። በየጊዜው ይወደዳል። ሰሞኑን የነዳጅ ዋጋ እንደገና ጨምሮ የለ! ወጪውን የሚጋራ ሰው ቢያገኙ ትልቅ ግልግል ይሆን ነበር። 11 ሰዓት ላይ እርስዎ በሚሄዱበት አቅጣጫ ታክሲ ለመሳፈር የሚፈልጉ ሰዎች መኖራቸው አያጠራጥርም። የትንንሾቹ ታክሲዎች ዋጋ ቀላል አይደለም። “አነስ ባለ ዋጋ የሚያሳፍረው ባለመኪና ባገኝ” እያለ ይመኛል መኪና ያልያዘ እግረኛ፡፡
ግን ምን ዋጋ አለው? ፈላጊና ተፈላጊ፣ ባለ መኪናና ተሳፋሪ እንዴት ይገናኙ? አስቸጋሪ ነው። ማለቴ... ድሮ አስቸጋሪ ነበር። አሁን ግን ችግር የለም። ከርስዎ የሚጠበቀው ነገር ቢኖር፤ መቼ  ወዴት እንሚጓዙ የሞባይል ስልክዎ ላይ መመዝገብ ብቻ ነው - ለምሳሌ “11 ሰዓት ላይ ወደ ኮተቤ” ብለው ይመዘግባሉ፡፡ መኪና የሌለውና ተዳብሎ መሄድ የሚፈልግ ሰው በበኩሉ፤ ሞባይሉን ከኪሱ አውጥቶ ... ኮተቤ መሄድ እፈልጋለሁ ብሎ ይመዘግባል። የስማርት ፎን አሪፍነት... ነካ ነካ በማድረግ መረጃ መለዋወጥና ትዕዛዝ ማስተላለፍ ይቻላል። ባለመኪናና ተሳፋሪ ፈላጊና ተፈላጊ መገናኘት የሚችሉበት ዘዴ ተፈጠረ ማለት ነው።
 ባለመኪናው የነዳጅ ዋጋን የሚጋራለት ተሳፋሪ ያገኛል። እግረኛው ደግሞ አነስ ባለ ክፍያ የሚያሳፍር ባለመኪና ያገኛል። የድሮውን ችግር የሚያስወግድ አዲስ ዘዴ የተፈጠረው ኡበር በተሰኘው ኩባንያ ነው። ቢዝነስ ማለት፣ ችግርን የሚያስወግድ ወይም የሚያቃልል መፍትሄ ማቅረብ ነዋ። እናም ከክፍያው 20% ይወስዳል። ተሳፋሪው ሃምሳ ብር ቢከፍል፣ አርባ ብር ለባለመኪናው፣ አስር ብር ደግሞ ለኡበር ይሆናል። ተመሰጋግነው መለያየት ነው። እናም ሁሉም ተደሰተ ይባላል።
“እኛ ደስተኛ አይደለንም” ባይ ናቸው - ባለታክሲዎች።
ከአምስት አመት በፊት የተመሰረተው ኡበር፣ ዛሬ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ደንበኞችን የሚያስተናግድ የ17 ቢሊዮን ዶላር ኩባንያ ሆኗል። በእርግጥ አንዳንድ የታክሲ ሾፌሮች ራሳቸው፣ የኡበር ደንበኛ ሆነዋል። ቆመው ተሳፋሪ ሲጠብቁ ከመዋል፣ በኡበር አማካኝነት ከተሳፋሪ ጋር በኢንተርኔት አማካኝነት መገናኘት ይሻላቸዋል። ብዙ የታክሲ ሾፌሮች ግን፣ ነባሩን አሰራር መተው አልፈለጉም።    “በከተማ የትራስፖርት ቢሮ ተመዝግበው ፈቃድ ያላገኙ መኪኖች የታክሲ አገልግሎት እንዳይሰጡ የከተሞቹ ህግ ይከለክላል። ኡበር ይህንን ህግ ይጥሳል” የሚሉት ባለታክሲዎች፣ አገልግሎቱ እንዲቋረጥ ጠይቀዋል - በተቃውሞ ሰልፍና በአድማ። ግን፤ እንዲህ አይነት አገልግሎቶችን ማስቆም አይቻልም በማለት የዘገበው ቢቢሲ፤ ከሁለት መቶ አመታት በፊት፣ የእንግሊዝ ሸማኔዎች የልብስ ፋብሪካዎችን ካላወደምን ብለው ያካሄዱ የተቃውሞ ሰልፍና አመፅ ብዙም አላዛለቀም ብሏል።

“ልቡን በላው”... ፈሊጣዊ አነጋገር እንዳይመስላችሁ። በደቡብ አፍሪካ የኬፕታውን ነዋሪ የሆነው የዚምባብዌ ተወላጅ እንደ አውሬ ነው፤ የባላንጣውን ልብ ሲበላ የተገኘው። አስደንጋጩ ወንጀል የተፈፀመው በቀድሞ ፍቅረኛው ቤት ውስጥ ነው።
የፀብ ምልክት አልነበረም ብላለች የቀድሞ ፍቅረኛው። ከተለያዩ ቆይተዋል። በድብቅ የተደረገ ነገር የለም። ከሱ ተለይታ ከ62 አመት አዛውንት ጋር መኖር ጀምራለች።  ባለፈው ረቡዕ እለት የቀድሞ ፍቅረኛዋ ቤቷ ድረስ ሲመጣ፤ ክፉ ነገር እንዳልጠረጠረች ገልፃ፤ መጠጥ ገዝቼ እንዳመጣ ገንዘብ ሰጥቶኛል ብላለች።
አፍታ አልቆየችም። መጠጥ ገዝታ ስትመጣ፤ ቤቱ ደም በደም ሆኗል። የ62 ዓመቱ አዛውንት በቀድሞ ፍቅረኛዋ ተወግተው ሞተዋል። አንገታቸው በስለት ቆስሏል። ፊታቸው ተነክሷል፤ በጥርስ ተቦጭቋል። ጩኸት ሰምተው የመጡ ጎረቤቶች ወደ ቤት መግባት እንዳልቻሉና በመስኮት ለማየት እንደሞከሩ ጠቅሰው፤ የአዛውንቱን ሆድ ቀድዶ ልባቸው ቆርጦ ሲበላ አይተናል ብለዋል። በድንጋጤ የተደናበሩት ጎረቤቶች ፖሊስ ከጠሩ በኋላ ነው ወንጀለኛው የተያዘው።

       ግንቦት 9 ቀን 2006 ዓ.ም በወጣው የጋዜጣችሁ ዕትም፣ ጤና ዓምድ ላይ “የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች በአሳሳቢ ደረጃ ላይ ናቸው ተባለ” በሚል ርዕስ ያወጣችሁትን ዘገባ የኢትዮጵያ የጥርስ ህክምና ባለሙያዎች ማህበር ተመልክቶታል፡፡
በጥርስ ህክምናም ሆነ በየትኛውም የህክምና ዘርፍ ያሉ ጉድለቶችን በማሳየት እርምት እንዲደረግና ህብረተሰቡ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኝ ማሳሰባችሁ አግባብነት ያለው ነው፡፡ ሆኖም የሰራችሁት ዘገባ ማህበረሰቡን ፍርሀት ውስጥ የሚከትና የተሳሳት መረጃ የሚሰጥ  ሆኖ አግኝተነዋል፡፡
ከሁሉም በላይ በማንኛውም ዜጋ ላይ እንዲደርስ የማንመኘው ችግር የደረሰባት እህታችን፤ የኛም ጉዳይ ነችና ህመሟ ይሰማናል፤ ችግሯም ይመለከተናል፡፡ ነገር ግን ባለሙያ ያልሆኑ ጥቂት ሰዎች በሚሰሩት የተሳሳተ ስራ /በእርግጥ የተባለው ታሪክ ከተከሰተ/ ምክንያት “አብዛኞቹ ክሊኒኮች” ተብሎ መዘገቡ በእጅጉ ያሳምማል፡፡
ለመሆኑ አንድ የጥርስ ህክምና ክሊኒክ ለመክፈት የሚያስፈልገውን መስፈርት አንብባችሁታል? ታዲያ ያን ሁሉ ገንዘብ አፍስሶ፣ የተሳሳተ ስራ በመስራት የሚደሰት ባለሙያ ይኖራል? ለመሆኑ የህክምና መሳሪያዎችን መቀቀያ ማሽን ዋጋው ስንት ነው? ደግሞስ ሃኪሙ ምን ያህል ሞኝ ቢሆን ነው በአግባቡ ንፅህናው ባልተጠበቀ መሳሪያ እየሰራ ከታካሚውም በላይ እራሱን ለበሽታ የሚያጋልጠው? እውነት እናውራ ከተባለ አይመስልም!!!
ዘገባውን የሰሩት ጋዜጠኛስ መሳሪያዎቹን “አየሁ አላየሁም” የሚሉት፣ ስለህክምና መሳሪያዎቹ እውቀት ኖሯቸው ነው ወይስ የነገሯቸውን ብቻ ይዘው ነው? መቼም ስለሚሰሩት ዘገባ መረጃ ቀድሞ መጠየቅ ግዴታ ይመስለናል፡፡ በእርግጥ ዕውቀቱ፣ ችሎታውና ልምዱ የሌለው በልምድ የሚሰራ ተራ ግለሰብ የህክምና ስህተት ሰራ ቢባል ያስኬዳል፡፡ ባለሙያ ያልሆነ ሰው ምን እንደሰራና ምን እንዳጠፋ ለይቶ አያውቅምና፡፡ እንዲህ ያለው ዘገባ፣ በአሁኑ ሰዓት የህክምና ባለሙያዎች ማህበረሰቡን በምን አይነት ሁኔታ ውስጥ ሆነው እያገለገሉ እንዳሉ ካለመረዳት ወይም ለመረዳት ካለመፈለግ የመነጨ በመሆኑ ማዘናችንን እንገልፃለን፡፡
የእህታችን ታሪክ የተገለፀበት መንገድና የተብራሩት ችግሮችን ለመተቸት እውነተኛውን ታሪክ ማግኘትና መገምገም ይጠበቅብናል፡፡ ሳናነሳ የማናልፈው ግን የጥርስ ህክምና ለመስጠት የሚችሉ የተለያዩ ባለሙያዎች መኖራቸውን እንድታወቁ ሲሆን ዘገባው የሚገልፀው አይነት የጥርስ አካል አለመኖሩንና በተጠቀሰው ሆስፒታል ውስጥ የጥርስ ህክምና ክፍል እንደሌለ እንዲሁም የጥርስ ሀኪም አለመኖራቸውን ነው፡፡ አስተያየት ሰጥተዋል የተባሉት የጥርስ ሀኪምም የማህበሩ አባል አይደሉም፡፡ በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎችን ጠይቀንም የሚያውቃቸው አንድም ሰው አላገኘንም፡፡ ከአንድ ባለሙያም ይህን አይነት አስተያየት እንደማይሰጥ ስለምናምን፣ የዘገባው አላማ ሌላ ሊሆን እንደሚችል ገምተናል፡፡
ህብረተሰቡ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኝ ማድረግ፤ ባለሙያውም ተገቢውን ስራ በተማረበት መስክ እንዲፈጽም ግዴታዎቹን በአግባቡ ተወጥቶ፣ መብቱም እንዲከበርለት መስራት የተቋቋምንበት ዋና ዓላማችን ነው፡፡ ለዚህም ሚዲያው ያለው ድርሻ ጉልህ መሆኑን ከልባችን እናምናለን፡፡ ነገር ግን የአገሪቱን አቅምና የባለሙያውን ሁኔታ ባለማጤን “አብዛኞቹ” ክሊኒኮች በሚል የወጣው ዘገባ፤ ለህብረተሰቡ የተሳሳተ መረጃ በማድረስ፣ ሥራችንን ካለውም በላይ ከባድና ውስብስብ ስለሚያደርግብን እባካችሁ በጥንቃቄ ዘግቡ እንላለን፡፡ በተረፈ ማናቸውንም መረጃዎች ለመስጠትና በዘርፉ ለሚከሰቱ ችግሮች አፋጣኝ የመፍትሔ እርምጃ ለመውሰድና በትብብር ለመስራት ፈቃደኞች መሆናችንን እንገልፃለን፡፡  

Saturday, 14 June 2014 12:22

ለማሸነፍ

ጋሻው በጠባቧ ስቱዲዮ ውስጥ በዘረጋት አነስተኛ አልጋ ላይ በጀርባው ተንጋሎ ይቃትታል፡፡ በእልህ ይቃጠላል ፣ በብሽቀት ይወራጫል፣ በምኞት ይንጠራራል . . .
እንደተንጋለለ ዓይኑን ፊት ለፊቱ በሰቀለው ፎቶ ግራፍ ላይ ወረወረ፡፡ እይታው እዚህ ትልቅ ባለቀለም ፎቶ ግራፍ ላይ ካረፈ በቀላሉ አይነሳም፡፡ ቀይ ዳማ ሴት፣  አንገቷን ቀለስ አድርጋ በዓይኖቿ ጠርዝ ታስተውለዋለች፡፡ ዛሬስ «አይ አሸናፊው» እያለች የምታሾፍበት መሰለው፡፡
ትልቁን የሀናን ፎቶ ግራፍ ዘወትር በዓይኑ እንዲዳብሰው ከሚጋብዙት ነገሮች ዋንኛው ዳሌዋ ነው ፡፡
ዳሌዋ ፣ልክ እንደ ዋንጫ ከላይ ሰፋ ብሎ ወደታች እየጠበበ መውረዱ ያስደንቀዋል፡፡
«ወይ የሰው ልጅ !»አለ ባግራሞት «ለካስ የዋንጫን ዲዛይን የኮረጀው ከውብ ሴቶች ዳሌ ነው።
አቤት ተንኮል ! ለካስ ለዋንጫ የመንሰፍሰፋችን ምስጢር ይህ ሆኗል? ሴቶቹም ቢሆኑ ለራሳቸው የአካል ቅርፅ ያላቸው ፍቅር ሳያውቁት ለዋንጫ እንዲሳቡ ያደርጋቸዋል፡፡ እኛም እንዲሁ ሳይገባን የወንድነታችን ስሜት በረቀቀ ሁኔታ ይማልላል. . . » እያለ ይፈላሰፋል፡፡
* * *
. . .  ሃና በፎጣ ተጠቅልላ ከባኞ ቤት እንደወጣች ወደ መኝታ ክፍሏ አመራች፣ ከውስጥ ሆና በሩን ዘጋች፡፡ ያገለደመችውን ፎጣ ከላይዋ ላይ ገፋ በመጠቅለል  ወረወረችው፡፡ ዕርቃኗን ሆነች ፡፡ እየተዟዟረች  ቁመናዋን  ገመገመች  ፣  በተፈጥሮዋ  ተደሰተች፡፡ «የሚሊኒየሙ አሸናፊ ሴት!»  አለችና ፈገግ ፣ ወዲያው ኮስተር፣ እንደመጸየፍ ደግሞ ፈገግ፣ አይኗን ቦዘዝ፣ ሰለምለም . . .   ይህን ጊዜ ጋሻው ወደ አዕምሮው ገባ ፡፡
አፈረች፡፡ እሮጣ  የወረወረችውን ፎጣ አነሳች፣ ተሸፋፍና ቆመች፡፡ ልቧ ደነገጠ፣ ሌሊት በህልሟ አይታዋለች፡፡ ጭልጥ ባለ የሳር ሜዳ ላይ ያገኛታል . . .
በህልሟ፡-
ይቀርባታል «ዛሬ ራቁትሽን ፎቶ ላነሳሽ ፈልጌ ነበር፡፡»
«ምንም ሳልለብስ?»
«አዎ! ዕርቃንሽን ትሆኚና እኔ በማሳይሽ ስታይል
አነሳሻለሁ፡፡ በዚህ ፎቶ የአለም «ሚስ ሞዴሊንግ»  አሸናፊዎች እንሆናለን!»
ትጓጓለች፣  ታቅማማለች፣  ይህን  ጊዜ  ጋሻው  ስውር ይልባታል «እሺ» ትላለች ዛሬ በእውኗ፡፡ ለሕልሙ አለም ጥያቄ በገሃዱ ዓለም መልስ ሰጠች። የሰማት ግን የለም፡፡ ብቻዋን ናት መኝታ ቤቷ ውስጥ፡፡
«እንዴ! ጋሻውንም ልወደው ነው?» ራስዋን በፍርሃት ጠየቀች፡፡ እሷን እንደመውደድ የሚያስፈራት ነገር የለም፡፡
ሰዓቷን ተመለከተች፡፡ ከቶማስ ጋር የመገናኛቸው ሰዓት! «የራሱ ጉዳይ!» አለች ብስጭት ብላ... ሦስት ጊዜ በተከታታይ ቀጥሯት መቅረቷን አልረሳችም፡፡ አሁን ደሞ አራተኛ መሆኑ ነው፡፡
«አሁንስ ያመራል»
«ያምርራ! ምን ያመጣል!» ከራስዋ ጋር ሙግት ገጠመች፡፡ በግቧ መሰረት ማንነቷን ማግኘት፣ የዓለም ምርጥ ሞዴሊስት በመሆን ራሷን፣ ቤተሰቧን፣ ሀገሯን ማኩራት ይጠበቅባታል፡፡ የዚህንም ጊዜያዊ የምስክር ወረቀት ከጋሻው እቅፍ ውስጥ መውሰድ ይኖርባታል፡፡
«የእኔ እጣፈንታ አለማቀፋዊ ዝና ነው! ከጋሻው በቀር የሚቀርቡኝ ወንዶች ሁሉ፣ ሚስት እንድሆናቸው፣ ምግብ እንዳበስልላቸው፣ ልጅ እንድወልድላቸው፣ ምናምን ነው የሚፈልጉኝ። ድንጋዮች! ከእንግዲህ እኔን ለእንዲህ  ዓይነቱ አነስተኛ ዓላማ ማጨቱ አበቃ፡፡
ዛሬ ሄጄ ከምንም በላይ ውድ የሆነ ዓላማዬን መስመር ማስያዝ አለብኝ፣ ሰማይ ጥግ ወደሚገኘው ዙፋኔ አስፈንጥሮ ለሚያደርሰኝ ለጋሻው በመውጣት፣ ፍቅርን በልቡ ማቀጣጠል፣ እሱን የሙጥኝ ይዤ አብሬው መተኮስ. . . »
እቅዷን በሃሳቧ እያውጠነጠነች ከመስታወቱ ዞር ብላ ልብስ መራረጠች፡፡ ከጉልበቷ በላይ የምትንጠለጠል ጉርድ ቀሚስ፣ እንበርቷን የምታሳየው ካኔተራ፣ ክፍት ጫማ፣ ከመስታወቱ ፊት ቆመች ቅልል ያለች ፍልቅልቅ ሴት «እምጵዋ!» የራሷን ምስል ሳመች ፡፡
ብር ብላ ከግቢያቸው ወጣች፡፡ ሚኒባስ ታክሲ መጣ፡፡ የጋቢናውን በር ከፍታ ገባች፡፡ ሹፌሩ ተነቃቃ፣ የሙዚቃውን ድምጽ ጨምሮ ተፈተለከ፡፡
የሞባይል ስልኳ በንዝረት መጥራት ጀመረች፣ ቁጥሩን ተመለከተችው፣ ቶማስ ነው! አላነሳችውም። ደጋግሞ ነዘራት፣ ዝም አለችው «ግፋ ቢል ያቺ ሳንቲሙ ነች የምትቀርብኝ ፣ ዘላለም በሱ ድጎማ እኖራለሁ እንዴ ? ገደል ይግባ !» እያጉረመረመች ወንበሯ ላይ ተመቻቸች፡፡
* * *
ጋሻው ከአስር ለሚበልጡ ዓመታት ፍላጎቱን ገድቦ፣ትዳር ሳይመሰርት፣ ንብረት ሳያካብት ፣ ትኩረቱን በሙሉ ሥራው ላይ በማድረግ ዓለማቀፋዊ አሸናፊነትን ለመቀናጀት ወጣ፣ ወረደ፣ አሸናፊነት እንደከበረ እንቁ ውድ ሆነችበት፡፡ ለበርካታ ጊዜያት፣ ተሳካልኝ ሲል ተንደባሏል፡፡
«አረ የድል ያለህ !» ውስጡ ጮኸ፡፡ እጁን ወደ ራስጌው አካባቢ ሰዶ አንድ ኤንቨሎፕ አወጣ፣ ሲውዲን ፣ እስቶኮልም ሚገኘው ዓለም አቀፍ የፎቶ ግራፍ ውድድር አዘጋጅ ማዕከል የተላከ ነው፡፡ በውስጡ መጽሔት ይዟል፡፡
አሱም የዚህ ውድድር ተካፋይ ነበር፡፡ በመጽሔቱ የላይኛው ሽፋን ላይ አሸናፊ የሆነው የዓመቱ ምርጥ ፎቶ ታትሟል፡፡ ምስሉ አክሊል የደፋች ንግስት በዙፋኗ ላይ እንደተቀመጠች ያሳያል፣ ድባቡ በጣም ደስ አለው፡፡ ፀጥታን ሳይቀር የመዘገበ ድንቅ የእንግሊዝ ሀገር ፎቶ ነው፡፡ ክብር፣ ውበትና ሰላም ይነበብበታል፡፡
መጽሄቱን ገለጠው፣ የሕንድ ቆንጆ! አሁንም
ገለጠው፣ እርጅና በአስፈሪ ክንዱ የደቆሳት የጀርመን አዛውንት! አረጋዊነትን ውብ አድርጎ አቅርቧል፡፡
አሁንም ገለጠው፣ የሩቅ ምስራቅ ልጃገረድ ዓይኗን ጭፍን አድርጋ ተንከተከተችበት! ቶሎ ገለጠው፡፡ አሁንም ገላለጠው! የሱ ሃና የለችም፡፡
እርር አለ! ወደ ፎቶ ግራፍ ሙያ የተሰማራበትን ቀን አስታውሶ ተፀፀተ፡፡ በመስራት ያሳለፋቸውን ከአስር የማያንሱ ዓመታትን ረገመ፡፡ አልቅሶ ቢወጣለት ተመኘ፣ ይህንንም አልቻለም!
በሩ ተንኳኳ. . . ከነ እልሁ፣ ከነብግነቱ ተነስቶ ከፈተው፡፡
ሃና ነች፡፡
ዓይኖቹ የጋለ ብረት መስለዋል፣ በመጀመሪያ ያረፋት በጡቶቿ ክፍላት ላይ ነው፣ ደነገጠ ፡፡
«አንድ» አለች በልቧ፡፡
ከዚያም  እይታው  ቁልቁል  ተንሸራቶ  ጭኖቿ  መሀል ተሰነቀረ፡፡
«ሁለት»
ወዲያው ሽቅብ አነጣጥሮ ከናፍሮቿን ቃኘ
«ሦስት» ፈገግ አለች፡፡
ከመቅጽበት ዓይኖቹን በዓይኖቿ ውስጥ ሰደዳቸው፣ ፍትወተ ሥጋ ቦግ ብሎ ታየው፡፡ አሁን እሱም ሳቀ፡፡ «ታድያስ ሃኒ» እጁን ዘረጋላት፡፡
የቀኝ ጉንጯን አስጠጋችለት፡፡
ሳመው፡፡
የግራ ጉንጯን ሰጠችው፡፡ ደገመው፡፡
ጉንጮቿ የተቀደሱላት መሰላት፡፡ እፎይታ ተሰማት፡፡
ወደ ውስጥ እንድትዘልቅ ጋበዛት፡፡ ሰተት ብላ ገባች . . .
ከሴቶች ጋር የሚኖርህ ቀረቤታ ላይ ጥንቃቄ ማድረግህን አታላላ፡፡ ሴቶቹን ሳይሆን እነሱን ተከትሎ የሚመጣው ትኩረትህን የሚሰርቅህን ስሜት ፍራው፣ ጥላው ሽሸው! ይህ ስሜት ባንተ ላይ ሲበረታ፣ስራ አስፈትቶ በሐሳብ ሲያናውዝ አይተኸዋልና የገዛ ህሊናው አንሾካሾከለት፡፡
ሃና ከስቱዲዮና   መኝታ ቤቱ ጋር በተያያዘችው ጠባብ ሳሎን ውስጥ ነግሳለች፡፡
«ዋው. . . ደረትህ እንዲህ ፀጉር በፀጉር አይመስለኝም
ነበር»
አሁን ይሄ ምን ያስደንቃል? በውስጡ ተቃወመ።
«ወደ ዓርባ ምንጭ እሄዳለሁ ያልከው መቼ ነበር?»
«ነገ ጠዋት አስራ ሁለት ሰዓት ገደማ ከዚህ እወጣለሁ»
ዓይኖቹን ማስቀመጫ እንዳጣለት ዕቃ እያንከራተተ መለሰላት፡፡
«ለምን እኔም አብሬህ አልሄድም? ወደ ደቡብ  እኮ ምንም ሀገር አላውቅም» በዓይኖቿ ቀስፋ ይዛው ትማፀነዋለች፡፡
«በእውነት?»
«ጋሻዬ ሙት ስልህ» ገላዋ ሁሉ በራ፡፡
«እነ ላንጋኖ፣ ሻላ፣ አዋሳ ሐይቆችን አታውቂያቸውማ?»
«የት አባቴ ሄጄ? »
«አዞ፣ ጉማሬ፣ ሰጎን  አይተሸ አታውቂማ?»
«ጋሻዬ ስሞትልህ?» ቅላፄዋ ሊያስፈነጥዘው ደረሰ፡፡ ሁለንተናው ሞቀ «በይ እንግዲህ ለለሊት 12 ሰዓት ተዘጋጂ ፣ እወስድሻለሁ»
«በጣም አመሰግናለሁ ጋሻዬ!»  ተወርውራ ተጠመጠመችበት፤ ዓይኖቹ ከስቱዲዮ ጋር ከተያያዘችው የመኝታ ቤቱ በር ላይ ተጣበቁ፡፡ የተገዛለት አላማ ተፈተነ፡፡
* * *
እሁድ፡፡
ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት፡፡
2000 ዓ.ም
በደቡቡ የኢትዮጵያ ክፍል፣ ከጂንካ ወጣ ብላ የምትገኝ፣ ቃቆ የምትባል ቦታ ላይ ፡-
«ከምድር እኩል የተፈጠረው ንፁህ አየር ይኸውልሽ» አለ ጋሻው እንደ ጥላ የምትከተለው ሃናን እያየ፡፡
«እንዴት ደስ ይላል ! የተራራው አቀማመጥ፣ የዛፎቹ አቋቋም፣ የወንዞቹ አወራረድ» ዙሪያ ገባውን አደነቀች፡፡
«በዚህች ቃቆ በምትባል አካባቢ በና የሚባል የጎሳ መጠሪያ ያላቸው ኢትዮጵያን ይኖራሉ፡፡ ወዲያ ማዶ ደግሞ ማሊ የሚባሉ አሉ ! የሁለቱም ጎሳ አባላት ልብስ የሚባል ነገር አያውቁም፣ እንዲያው ሀፍረታቸውን ለመሸፈን ያህል ብቻ ትንሽዬ ቆዳ ያንጠለጥላሉ. . .»
«አ . .  ሃ . . . ከቡስካ በስተጀርባ የተባለው መጽሀፍ
ውስጥ እንዳሉት ሀመሮች?»
«አዎ፡፡ አንብበሽዋል?»
«እንዴ? ለዛውም ደጋግሜ ነዋ»
«ብራቮ ሃኒ »
ዛሬ በመካከላቸው ከፍተኛ የመሳሳብ ስሜት አለ፣ በየደቂቃው ትደገፈዋለች፣ በየምክንያቱ ያቆላምጣታል፣ ብዙ ያወራሉ፣ በጋራ መምጣታቸውን ወደዱት፡፡
ረጅሙን የዙም ሌንስ በዘመናዊ ካሜራ ላይ እየገጠመ «አሁን እስከ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት   ማንሳት እችላለሁ!» አላት፡፡
በጣም ተደነቀች፡፡
ካሜራውን ለመግዛት ያየውን ፍዳ እየተረከላት፣ ወንዙ ዳር ያለችው ዛፍ ላይ ወጣና ወዲያ ማዶ ደን ላይ አነጣጠረ፡፡ ምንም የለም፡፡ ወዲህ አነጣጠረ እንደዚያው ነው፡፡ ዱብ ብሎ ወረደ፡፡
በዛፍና ቅጠላ ቅጠሉ መሃል እየተሽሎኮለኩ፣ በሳቅ እየተፍነከነኩ ገላጣ ቦታ ላይ ብቅ አሉ፡፡
አፍረቷ አካባቢ ብቻ ሦስት ማዕዘን ቁርበት ጣል ካደረገች የበና ልጃገረድ ጋር ተፋጠጡ፡፡ ደንግጣ እንደሐውልት ድርቅ አለች የበናዋ ቆንጆ። ጡቶቿ ለመተኮስ የተወደሩ ሮኬቶች ይመስላሉ፡፡ በቀይ አፈር የታሸው ፀጉሯ ቁልቁል ይጥመዘመዛል። ከቀላጭ ብረት የተሰሩ ሦስት ቀለበቶች በአንገቷ ዙሪያ ተጠምጥመዋል፡፡
ሃና አፏን ከፈተች፡፡ የበናዋ ቆንጆ ተክለሰውነት ትንግርት ሆኖባታል፣ ጠይምነቷ ወከክ ያደርጋል፡፡
ጋሻው ቀስ ብሎ ጣቶቹን ከካሜራው ጋር አገናኘ። ልጃገረዲቱ ሃናን በዓይኖቿ ወጋቻት፡፡ ጆሮዎቿም ትልልቅ ሎቲዎችን አንጠልጥለዋል፡፡ ክንዶቿ ከላይ እስከታች በመዳብና ቀላጭ ብረቶች አጊጠዋል፡፡
የጋሻው፣ የሃና፣ የበናዋ ጉብል የልብ ትርታ ቆሟል። የዓይን እርግብግቢት ሳይቀር ተቋርጧል። ፀጥታውን የሚያደፈርስ ጠፋ፣ የበና አሞሮች ክንፋቸውን ሳይቀዝፉ በርቀት ቁልቁል ያስተውላሉ...
የበናዋ ቆንጆ ፊት ላይ ታሪክ ይነበብ ጀመር፡፡ ቁጣ፣ ድፍረት፣ ግርምት!
ጋሻው  ካሜራውን  ዓይኑ  ላይ  ሳያደርግ  በግምት  በማንሳት ተክኗል፡፡ የበናዋ ጉብል አፈገፈገች። የሃና ዓይኖች ልጃገረዲቱ ባዶ እግሮች ላይ አረፉ። አልቦዎቿ አንፀባረቁባት፡፡ ጉብሊቱ አፈገፈገች፡፡ ጋሻው የካሜራውን መምቻ ተጫነ፡፡ ቀጭ!
ቱር አለች እንደሚዳቋ፡፡
«ወይኔ ጋሻዬ አመለጠችህ?» ሃና ጮኸች፡፡
የበና አሞሮች ክንፋቸውን አማቱ፡፡ እነሱም አንቋረሩ ለቆንጇቸው!
ጋሻው ዘሎ ከፍታ ላይ ወጣ፡፡ ካሜራውን ዓይኑ ላይ ነው፡፡ በሌንሱ ውስጥ የጉብሊቱ ምስል ይርመሰመሳል፡፡
«ከሞን!» ይላል ጋሻው ሌንሱን ዞር፣ ቀጭ! ዞር ቀጭ! በተከታታይ የካሜራውን መምቻ ተጫነው፡፡ ፊልሙ ሲያልቅ ቆመ፡፡ በፍጥነት ቀይሮ አነጣጠረ፡፡
የበናዋ ቆንጆ የለችም፡፡
ካሜራውን ለቀቀው፣ አንገቱ ላይ ተንጠለጠለ። ሁለት እጁን ወደ ቃቆ ደመና ወጠረ፣ አምላኩን ማመስገን ሲፈልግ ሁለት እጁን ወደላይ ይወጥራል፡፡
ከከፍታው ላይ ዱብ እንዳለ ካሜራውን ወደ ጀርባው አዞረና ሀናን አቀፋት፡፡
የበና አሞሮች ሌላ ትእይንት ያዩ ጀመር፣ መቅዘፋቸውን ትተው ቁልቁል አሰገጉ. . .
በመጪው ዓመት ካናዳ ቶሮንቶ ውስጥ በሚካሄደው ዓለም አቀፍ የፎቶ ግራፍ ውድድር አሸናፊነቱን ደመነፍሱ ከወዲሁ ሹክ
አለችው፡፡ ስለዚህ ሀናን እንዳቀፋት አንገቷ ሥር ይስማት ጀመር፡፡ የበናዋ ጉብል በስቱዲዮ የታጨቁ ፎቶ ግራፎቹን ነፃ ስታወጣለት ታየው፡፡
ሀና ከናፍርቷን ወደ ከናፍርቱ በመስደድ ላይ ነች፣ ጡቶቿ እስኪፈርጡ ተለጥፋበታለች፡፡
«ሄይ . . . ሄይ . . . ሄይ . . . ጃላ . . .  ጃላ . . .!» ይላል አንድ ሸካራ ድምጽ እንደብራቅ ጮሆ፡፡
ጋሻው ሀናን ለቆ ዞር አለ፡፡
የበናው ወጣት ቁራጭ ቁርበቱን እንዳገለደመ በግራ እጁ ቅቤ የጠጣ በርኮታ፣ በቀኝ ክንዱ የእባብ መርዝ የተለወሰ ቀስቱን እንዳነገበ በኩራት ቆሟል፡፡
ሀና የዓለሟ ፍፃሜ የሆነ መሠላት፡፡
የጋሻው ፊት እንደ በና ፀሐይ አበራ፣ ቅንድቦቹ ሽቅብ ተነሥተው ፀጉሩ ውስጥ ተወሸቁ፡፡ ዓይኖቹ ከመበልጠጣቸው የተነሣ ወልቀው የሚወድቁ እንክብሎች መሰሉ፡፡ ልክ እንደበና አሞሮች ክንፉን ዘረጋ «ሃይ ሃይ ጃል» ብሎ አጸፋውን መለሰ ድምጹ በበና ግዛት ውስጥ አስተጋባ፡
አሞሮቹ ግራ ገባቸው፡፡
ሮጦ አቀፈው የበናውን ወጣት፡፡
እሱም ቀስትና በርኮታውን ቁልቁል ለቀቃቸው፣ ሳሩ ውስጥ ሰጠሙ፡፡
የበናው ወጣት ፈነደቀ ፣ጋሻው ቀልቡን ሳተ «የክፍለ ዘመኑን ፎቶ አገኘህ» እያለች ደመነፍሱ ደስታውን አበዛችለት፡፡
ሀና ራሷን ጠዘጠዛት፣ እያዞራት ነው፡፡
የበናው ወጣት እግሩ ሥር ያስቀመጠውን ቅል ከሳሩ ውስጥ አወጣና ለጋሻው ሰጠው፡፡
ጋሻው አላቅማማም ግጥም አድርጎት ጠጣ፣ ዞሮ ሀናን ያናግራታል «ሀኒ ነይ ወዲህ፣ ይህ ጃላዬ ነው። ተዋወቂው፡፡ በበናዎች ቋንቋ ጃላ ማለት ጓደኛዬ ማለት ነው፡፡ እንዴት ያለ ወዳጄ መሰለሽ . . . » እያለ ቅሉን ይሰጣል «ቅመሺው!»
ጎንጨት ታደርገዋለች፡፡ ቆመጠጣት ቀና ብላ አየችው፡፡
«ዋጭው  ምንም  አይልሽም፣  የማሽላ  ቦርዴ  ነው፣  ጨቃ ይባላል»
ነጭ ነገር ተፋች፡፡
የበናው ወጣት ሳቀ . . .
ጋሻው የበነዋ ጉብል ባሳደረችበት ብሩህ ተስፋ ተነቃቅቷል፡፡ ያለውን ገንዘብ አሟጦ፣ ከሚያውቃቸው ሁሉ ተበድሮ፣ ካነሰውም ንብረቱን በሙሉ ሽጦ፣ ተጨማሪ ፎቶ ግራፎችን ከወሎ፣ ትግራይና ሐረር ማንሣት አለበት፡፡ ከነዚህ መካከል መርጦ በሚልከው በአንዱ ማሸነፉ አይቀርም! ካሸነፈ ሽልማቱ የሃናን ዳሌ የመሰለ ዋንጫ አይደለም፡፡
በአወዳዳሪው  ድርጅት  ስፖንሰር  አድራጊነት  ዓለም  አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ኢግዚቢሽን እንዲያዘጋጅ እድል ይሰጠዋል፡፡ የዕድሜውን አጋማሽ ለሚክል ጊዜ የሰበሰባቸው ፎቶ ግራፎች ቀን  ወጣላቸው  ማለት  ነው፡፡  ተወዳጅ  የሆኑት በጨረታ ይቸበቸባሉ። ያልተሸጡትም ቢያንስ የሀገሪቱን ወርቃማ ባህል፣  ጀግንነት፣ ውበትና ማንነት ለዓለም ሕዝብ በጣፋጭ ለዛቸው ይሰብካሉ።
በኢግዚቢሽኑ የሚያገኘውን ክብር፣ ቱጃር የሚያደርገው ረብጣ ዶላር፣ በቀጣይ ዘመኑ የሚኖረውን የሙያ መሣሪያዎች፣ ያሠራር ደረጃና፣ የአሸናፊነት ሌሎች ፀጋዎች ሁሉ ታዩት፡፡ የጨበጣቸው ያህል እየቋመጠ፣ በቁሙ እያለመ ሳለ ጀምበር በስተ ምሥራቅ እርቃኗን ብቅ አለችለት፡፡ የመጨረሻው ፎቶ ሆና  በካሜራው ጠቀሳት፡፡
ወዲያው   የተከራያት   መኪናን   በመጣችበት   ፍጥነት እያስወነጨፈ ወደ አዲስ አበባ መመለስ ጀመሩ...
ለሊቱን ሙሉ በበናዎች የእሳት ዳር ጨዋታ ሲዝናና ያደረው ጋሻው፣ እጎኑ እንቅልፍ እየጣለ የሚያነሳት ሃናን እረሳ፡፡ ሃሳቡን ከመሪው ጋር እየጠመዘዘ፣ ምኞቱን ከነዳጅ መስጫው ጋር እየተጫነ ያልማል፡፡
እሷ  የሁለት  ዓመት  ምኞትዋ  መና  እንደማይቀር  እርግጠኛ ሆናለች፡፡ አልፎ አልፎ የሽርደዳ ሚመስው ፈገግታዋን ብልጭ አያረገች ትመለከተዋለች፡፡
እሱ እዚህ የለም፡፡ በሃሳብ ጠፍቷል፡፡
ሁለቱን የአሸናፊነት ጥማት ያቃጠላቸውን ተጓዦች የያዘችው መኪና የሶዶ፣ የሻሸመኔ፣ የዝዋይ አየርን ሰንጥቃ ሞጆ ደረሰች፡፡
ተፋላሚዎቹ  የደብረዘይት  ከተማን  ከሩቅ  ሲመለከቱ  ከሃሳብ ጎሬያቸው በመውጣት ተያዩ። አንዳቸው በሌላኛው ዓይን ውስጥ እንግዳ ነገርን አስተዋሉና ተሳሳቁ፡፡
ሁለቱም ድክም ብሏቸዋል፡፡ ማረፍ ይፈልጋሉ፣ ደብረዘይት ምቹ ናት፡፡ ከመኪናው ወርደው ቡና ጠጡ፡፡
«ሳሎኑ ተደፍሯል፡፡ የጉዞ  እቅዶቹ ተካፋይ ሆኛለሁ፣ የስቱዲዮ በር ቀላል ነው ፡፡
የመኝታ ቤቱ ቁልፍ ከተከፈተ አልጋ አለ፣ እዛ ላይ ከወደቅን አለቀ! ይወደኛል፡፡ ይህ ደግሞ ከባድ አይደለም ጊዜ ብቻ ያስፈልገዋል አንጂ. . . » የጣቷን  ጥፍር  በጥርሷ እየከረከመች እራሷን አረጋጋች፡፡
አዲስ አበባ ሲገቡ መሽቷል፡፡ ቤቷ በር ላይ አደረሳት። ጉንጩን ስማው ወረደች፡፡ እንደ እርጥብ ስጋ ቀዘቀዘው፡፡
* * *
ወራት እንዳአቃጠላቸው ፊልሞች ላይመለሱ ጋዩ። በቁርጠኝነት የዘመተበት ውድድር ካሰበው በላይ መስዋት አስከፍሎታል፡፡ የነበረውን ገንዘብ አሟጧል፡፡ ያችኑ ጥቂት ቁሳቁስ ሸጧል፣ የተበደራቸውንም ብሮች በተባለው ጊዜ ባለመመለሱ ቅሬታን አትርፎ መንገድ አጥቷል፡፡
አሁን ጠባቧ ስቱዲዮ ውስጥ፣ ብረት እንደታጠረበት አቦሽማኔ ይንቆራጠጣል፡፡ ከካናዳ ቶሮንቶ የተላከው የተወዳዳሪዎች ውጤት ማስታወቂያ መጽሔት እንደታሸገ ደርሶታል። ኢንቨሎፑን የሚከፍትበት አቅም አጥቶ ይሽከረከራል፡፡
በርግጥ  ኢትዮጵያን  ከዳር  እስከ  ዳር  አካልሎ  ብርቅዬ አእዋፍቷን፣ ድንቅ የመልካ ምድር አቀማመጧን፣ አስገራሚ ቅርሶቿን፣ ታሪካዊ መስህቦቿን ሁሉ ደረጃውን በጠበቀ ብቃት አንስቷል፡፡
አቅሙ የፈቀደውን ሁሉ ቢያደርግም፣ የማሸነፍ ሚስጥሩ የሚፈታው አቅም የፈቀደውን ሁሉ በማድረግ ሳይሆን ጉዳዩ ሊያስከፍል የሚገባውን ዋጋ መክፈል በመቻል ብቻ መሆኑን ማወቁ አስጨንቆታል፡፡
የታሸገው የውጤት ማሳወቂያ ኢንቨሎፕ ውስጥ ያ መፅሔት አለ፡፡ የመፅሄቱ ፊተኛ ሽፋን ላይ ያሸናፊው ፎቶ ይኖራል፡፡ እዚህ አሸናፊ ቦታ ላይ የበናዋ ጉብል ከሌለች ጋሻው ያከትምለታል! በቀጣዩ ጊዜ ስራውን በአግባቡ የሚያከናውንበት የመንቀሳቀሻ አቅም ያጣል፣ ይሰደዳል! አበዳሪዎቹ የቀረውን ካሜራና አንዳንድ ቁሳቁስም ይነጥቁት ይሆናል . . .
በዚህም አለ በዚያ በቀላሉ ለማያንሰራራበት የሞራል ውድቀት፣ የስሜት ስብራት፣ ብሎም መሰረታዊ ፍላጎቶችን ማሟላት የማይችልበት የድህነት ማጥ ውስጥ ይዘፈቃል፡፡
ጭንቀቱን የሚጋራው አጣ፡፡ ላቡ ችፍ አለ በፊቱ ላይ፡፡ በህይወት ዘመኑ የዛሬውን ያህል ጠንካራ ውጥረት ገጥሞት አያውቅም፡፡ አድርጎ የማያውቀወን ቤተአምልኮ ጎራ ማለት አማረው፡፡ እዛ ሄዶ ኢንቨሎፑን ሊከፍት አሰበ፡፡ የበናዋ ጉብል በሚፈልገው ቦታ ከሌለችስ ? እግዚኦ በሉልኝ ! ልል ነው? በራሱ ላይ ዘበተ፡፡
«ቀድሞውንም በዚህች ደሃ ሀገር ውስጥ እየኖርኩ፣ የፎቶ ግራፍ ጥበቡ የመጠቀበት ዓለም ላይ ካሉ ባለሙያዎች ጋር  መወዳደር አልፎ፣ ተርፎም ለማሸነፍ መጎምጀቴ እንዴት
አልፎ፣ ተርፎም ለማሸነፍ መጎምጀቴ እንዴት ያለ ቅዠት ነበር ?» አለ ለራሱ፡፡
ሀይሌ ገብረ ስላሴ በአዕምሮው ተከሰተ፣ የምፀት ፈገግታውን እንደ ካሜራው ፍላሽ ብልጭ አደረገበት፡፡ ዞሮ ፈለገው፣ ድንቅ ፎቶውን በስቱዲዮ ሰቅሏል፡፡ እግሩ  ስር ወድቆ ጭንቀቱን ሊያካፍለው ዳዳውና ፎቶው ፊት ቆመ፡-
«ባላሸንፍስ?»  ጠየቀው፡፡
«ትሸነፋለሃ! »
«መሸነፍ ምንድን ነው?»
«መታገልና ተረትቶ መውደቅ!»
«ማሸነፍስ?»
«ከውድቀት መነሳት!»
«በቃ?»
«አልበቃም»
«ሌላ ማሸነፍ አለ ?»
«አዎ?»
«እባክህ ንገረኝ »
«በውድቀትህ ውስጥ ባለህበት ጊዜ ፣ይህን ውድቀትክን በማሸነፍ እንደምትተካው በፍፁም እምነት ማመን»
«ማመን ብቻ?»
«አሂሂ . . .  ውጤቱ አስኪመጣ ደጋግሞ መሞከር ያስፈልጋል . . .  ይኸውልህ ምን መሠለህ . . . »
እንዳያብድ ሰጋ! ቀልቡን ሰብሰብ  አድርጎ ወደ ኢንቨሎፑ አመራ፡፡
ግድግዳውን ያጣበቡት ፎቶ ግራፎች፣ መደርደሪያው ላይ የተሰቀሉት ካሜራና ሌንሶች ሸምቅቅ እንዳሉ ኢንቨሎፑ ያመጣውን መልዕክት የሚጠባበቁ መስለው።
መንቆራጠጡን ቆም አደረገና አፈፍ አደረገው ኢንቨሎፑን፡፡ ይከብዳል፡፡ በፍጥነት ሊሸረክተው ቆነጠጠ፡፡ አይ! አይ!» ካሜራና ሌንሶቹ ሲንጫጩ ተሰማው፡፡
ፎቶ ሲያድን «ሰላይ!» ተብሎ የታሰረና የተንገላታበት ወቅት፣ በሌሊት ሲማስን በማጅራት መቺ የተዘረፈበትን፣ ጫካ ለጫካ ሲያስስ ከአውሬ መንጋጋ ለጥቂት ያመለጠበትን፣ ገንዘብ እያጠረው የተራበበትን፣ አዕምሮው ጥበቡ ላይ ተጣብቆ ገላው ያደፈበት ልብሱ የመነቸከበትን፣ ጊዜያት አስታወሰ፡፡
የአሸናፊት ጎዳናን የማይሽር የመንፈስ ደዌ  አድርጎ ቆጠረው! ለአመታት የታተረለት አሸናፊነትን ደጋግሞ ረገመው፡፡
የማይቀርለትን ጽዋ ለመጎንጨት ኢንቨሎፑን አነሳ፣ ጠበቅ አድርጎ ከያዘው በኋላ ጥርሱን ነክሶ አይኑን እንደጨፈነ ስቦ አወጣው፡፡ እንደበረደው ህንፃ አገጩ ተርገበገበ፣ ችፍ ያሉት ላቦቹ ተድበልብለው ወደቁ . . .
እንደጨፈነ መጽሔቱን ወደ ኢንቨሎፑ ሊመልሰው አሰበ፡፡ አላደረገውም! ዓይኑን ገለጠው። ከበናዋ ጉብል ጋር ተፋጠጡ! ፊቷ ላይ ታሪክ ይነበባል፡፡ ቁጣ፣ ድፍረት፣ ግርምት! ጋሻው አፈገፈገ የስቱዲዮ ግድግዳ አገደው፡፡ ህልም እንዳይሆን ሰጋ፡፡
መጽሔቱን ወደ ዓይኑ አስጠጋ፣ ሮኬቶቿ አነጣጡሩበት፣ በቀይ አፈር የታሸው ጥምዝ ፀጉሯ፣ የአንገት ቀለበቷ፣ ሁሉም
አሉ፡፡  በእጁ  ዳበሳት  አልደነበረችም፡፡  እቅፍ  አደረጋት፡፡  ሰላም ሰጠችው፡፡
«አላልኩህም»  እያለች ጮኸች ደመነፍሱ «በል ሳማት»
አዘዘችው፡፡
መጽሔቱን ሳመው፡፡ የስቱዲዮ በር ተበረገደ፡፡ አቅሉን ስቶ ወጣ፣ አስፋልት አቋረጠ፣ ታክሲ ያዘ፣ ርቆ ወረደ በተለያዩ ቅያሶች እያሰባበረ ገስግሶ እነ ሃና ሳሎን፣ በሃና ፊት ተገኘ፡፡
ሃና ጆሮ የሚበጥስ ጩኸት አሰማች፡፡ እናቷ ተንደርድረው ገቡ፡፡
መጽሔቱን እያሳየች የሆነው ሁሉ አነበነበችላቸው፡፡
ከቁብ ሳይቆጥሯት ገርምመዋት ወጡ፡፡
መጽሔቱን ገለጠችው፡፡ የግሪክ እመቤት!
ጋሻው ከጥይት ያመለጠ መሰለው፡፡
አሁንም ገለጠችው፣ የአርመን ኮረዳ ፡፡
ሃና ደነዘዘች፡፡ ገለጠችው የሩስኪ ውብ፡፡ ገለጠችው የህንድ…
የበናዋ ጉብል ናፈቀችው፡፡ መጽሔቱን ከሃና ቀማትና ወደ ሽፋኑ መለሰው፣ ሮኬቶቿን ወደረችበት። መጽሔቱን ሳመው፣ ፆታዊ ፍቅር ተፀነሰበት፡፡
«አገባታለሁ! » ሲል ተናገረ፡፡
«ምን»
«ሚስቴ አደርጋታለሁ!»
«ም . . .  ምን አልክ ጋሻዬ? » “እቺ ናት ሚሰቴ፣ አ ገ ባ ታ ለ ሁ”
«እውነት የምትለውን ታደርገዋለህ? አንተእኮ… እኔ…» የምትናገረው ጠፋት፡፡ «ይሆናል የኔ ጌታ? በመካከላችሁ ያለውን ሰፊ የባሕል ፣ የአኗኗር፣ የስልጣኔ፣ ልዩነት አላስተዋልከውም? ይህን ያህል የተራራቀ ልዩነት ያላቸው ሰዎች በትዳር ሊጣመሩ ይችላሉ? ጋሻዬ? ይቻላል ጋሻዬ?. . . »
ሀይሌ ገብረስላሴ ፈገግ አለ፡፡ ያ ህያው ምስል በጋሻው ሕሊና ደግሞ ተከሰተ፡፡ ጋሻውም እሩቅ እያለመ፣ እሩቅ እያሰበ አብሮት ፈገግ አለ፡፡
ሃና ይህን የመሰለው በረከት ተቋዳሽ ባለመሆኗ ከልቡ አዘነላት፡፡ በጓደኝነት ስሜት ጠልቆ መረመራት፣ ጉድለቷን አስተዋለ፡፡ ከሕይወት ፍልስፍናው ይበልጥ ሊያካፍላት፣ እምነቱን ሊተክልባት ወሰነ። «ይሄውልሽ ሃንዬ. . . ጉዳዮችኮ ቀላል ወይም ከባድ ስለሆኑ አይደለም የሚሳኩልን፣ ልናሳካቸው በቆራጥነት ስንወስንና ያላማቋረጥ ስንጥር ብቻ ነው የሚሳካልን፡፡» የግል እምነቱን አሰረፀባት፡፡
ምንም እንኳን ጋሻውንና ያልጨበጠችውን ዓለማቀፋዊ ዝናን፣ ተስፋ አድርጋ የቶማስን ንፁህ ወዳጅነት ብትረግጥም፣ መልሳ ልታገኘውና እስከ መጨረሻውም በፍቅሩ ውስጥ ልትሆን እንደምትችል አመነች፡፡ ልታደርገውም ወሰነች፡፡
ወዲያው በአይነ ህሊናዋ እንዲህ ይታያት ጀመር።
የበና ማኅበረሰብ ገላቸው በልብስ ተሸፍኖ። በምሽት፣ መስክ ላይ በሚያነዱት እሳት ዙሪያ ተሰባስበው፣ በርኮታቸው ላይ ቁጢጥ እንዳሉ፣ አረቄያቸውን እየተጎነጩ ሲጨዋወቱ . . .
ጨረቃ ፍልቅልቅ ብላ ቁልቁል ስታስተውላቸው...
እሷ እና ቶማስ ጎን ለጎን እንደተቀመጡ፣ እሳቱን እየሞቁ በሹክሹክታ ሲያወጉ. . .
የበናዋ ጉብል   ጠይሙ ፊቷን በፈገግታ አስጊጣ፣ በዘመናዊ የቆዳ ጃኬት የተሸፈኑ ውድር ሮኬቶችዋን በማስቀደም  ወደ ጋሻው
ስትርብ . . .
ጋሻውም በርኮታው ላይ ጉብ እንዳለ ፣በነበልባሉ ውስጥ አሻግሮ እየተመለከታት በነደደ ስሜት ሲጠብቃት. . .
ጨረቃም እየተቅለሰለች ደመናው እቅፍ ውስጥ ስትሸሸግ . . .

Saturday, 14 June 2014 12:20

የጸሐፍት ጥግ

ጭንቅላቴን ባዶ ለማድረግ መፃፍ አለብኝ፡፡ ያለዚያ አቅሌን እስታለሁ፡፡
ሎርድ ባይረን
በመፃፍ ካልተነፈስክ፣ በመፃፍ ካልጮህክ ወይም ካልዘመርክ አትፃፍ፡፡ ምክንያቱም ባህላችን ለፅሁፍ ቦታ የለውም፡፡  
አናይስ ኒን
ከሌላ ፀሃፊ ባለሁለት ቃላት ሃረግ ከምሰርቅ ሙሉ ባንክ ዘርፌ ብያዝ እመርጣለሁ፡፡
ጃክ ስሚዝ
ፅሁፍ ከዝምታ ጋር የሚደረግ ትግል ነው፡፡
ካርሎስ ፉንቴስ
ህትመት የሰውን አዕምሮ ለጨረታ ማውጣት ነው፡፡
ኤሚሊ ዲኪንሰን
የደራሲ ሁለቱ እጅግ ማራኪ ጥንካሬዎች፣ አዳዲስ ነገሮችን የተለመዱ ማድረግና የተለመዱትን አዲስ ማድረግ ናቸው፡፡
ሳሙኤል ጆንሰን
ለመፃፍ የተገደድክበትን ምክንያት እወቀው፡፡ ስሩን በልብህ ውስጥ ማሰራጨቱንም አረጋግጥ። መፃፍ ብትከለከል ብቸኛ አማራጭህ ሞት እንደሆነ ለራስህ ተናዘዝ፡፡
ሬይነር ማርያ
ጥሩ ልቦለድ የዋና ገፀ ባህሪውን እውነት ሲነግረን፣ ቀሽም ልቦለድ የደራሲውን እውነት ይነግረናል፡፡
ጂ.ኬ.ቼስቴርቶን
በአንድ ሰው አዕምሮ ውስጥ በሺዎች የሚቆጠሩ ሃሳቦች ይኖሩታል፡፡ ያ ሰው ብዕሩን አንስቶ እስኪፅፋቸው ድረስ ግን እኒያ ሃሳቦች መኖራቸውን አያውቅም፡፡
ዊሊያም ሜክፒስ ታክሬይ
በእያንዳንዱ ጭንቅላት ውስጥ ያለውን የትራፊክ መጨናነቅ የሚያስወግዱ መፃህፍት መፃፍ እፈልጋለሁ፡፡
ጆን አፕዳይክ
ሰዎች በደምስሮቼ ውስጥ ቀለም፣ በትየባ ማሽኔ ቁልፎች ላይም ደም ማግኘታቸው አይቀርም፡፡
ቴሪ ጉይሌሜትስ
መፃህፍቱ ራሳቸው እንዲወለዱ ፈለጉ እንጂ እኔ አልፈጠርኳቸውም፡፡ ወደ እኔ መጥተው “እንዲህና እንዲያ ሆነን ካልተፃፍን” ብለው ወትውተውኝ ነው፡፡
ሳሙኤል በትለር