Administrator

Administrator

“...እኔና ባለቤቴ ከተጋባን እነሆ ሀምሳ ሶስት አመታችን ነው፡፡ የመጀመሪያ ልጃችን ሴት ስትሆን እሱዋም እድሜዋ ወደ ሀምሳ ሁለት ደርሶአል። በጠቅላላውም ወደ አስራ አንድ ልጅ የወለድን ሲሆን የመጨረሻ ልጃችን ሀያ አምስት አመት ሆኖአታል፡፡ በነበረው ሁኔታ ከቤተሰብ የተወረሰ ሀብት እና እኛም በየበኩላችን የሰራነው ተጨማምሮ ልጆቻችንን በደንብ አሳድገን ዛሬ ሁሉም የየራሳቸውን ሀብትና ንብረት ይዘዋል፡፡ እንዲያውም ከግማሽ በላይ የሚሆኑት በውጭ ሀገራት ኑሮአቸውን መስርተዋል፡፡ ሀገር ውስጥ ያሉትም ቢሆኑ ያገቡትም አግብተው ያላገቡትም ቢሆኑ ቤት እየተከራዩ ወጥተው እነሆ ዛሬ እኔና ባለቤቴ ብቻችንን እንኖራለን፡፡ በስልክም ይሁን በአካል እንደጠያቂ ከመጠየቅ ወይንም ስንፈልጋቸው አቤት ከማለት ውጭ በቀጥታ የምናገኘው ልጅ የለንም፡፡ ሁሉም የራሳቸውን ኑሮ መስርተዋል፡፡ እናም ጊዜው አልፈቅድ ብሎ እንጂ ልጅ ምንጊዜም አይጠላም። ታዲያ ...አሁን ...ልጆቻችንን ስንጠይቅ እኛ እንደእናንተ ጊዜ ብዙ ልጅ አንወልድም ዛሬ ጊዜው ተሸሽሎአል...በልክ ነው የሚወለደው...ይሉናል፡፡ በእርግጥ አጥግቦ አብልቶ...አልብሶ እና አስተምሮ ማሳደግ ካልተቻለ ዝም ብሎ መውለድም አስቸጋሪ ይሆን ይሆናል...”
ወ/ሮ ይርገዱ ተዋበ ከአዲስ አበባ
ወ/ሮ ይርገዱ የሰባ  አመት እድሜ ባለጸጋ ናቸው፡፡ ዛሬ ለሚመለከታቸው ግን ምናልባት ወደ ሀምሳዎቹ መጨረሻ እንጂ ሰባ አመት አይመስሉም። ምክንያቱንም ሲጠየቁ የሰጡት መልስ “...እኔ ልጆቼን ለማሳደግና ቤቴን ለማስተዳደር ስል እስከዛሬ ድረስ ያለእረፍት እንቀሳቀስ ነበር፡፡ ምናልባትም እሱ እንደ ስፖርት ሆኖ ይሆናል...” የሚል ነበር መልሳቸው፡፡ በእርግጥም አልተሳሳቱም፡፡ ብዙ ልጅ እንደመውለዳቸውም ስለአለመጎዳታቸውን ሲገልጹ ...ምንጊዜም ልጅ የሚወልዱት በሆስፒታል እንጂ በቤት ውስጥ አለመሆኑን እና የተማሩ በመሆናቸውም እራሳቸውን ለመርዳት አለመቦዘናቸውን ነው፡፡ ወ/ሮ ይርገዱ የሊሴ ፍራንሴ እና የንግድ ስራ ኮሌጅ ተማሪ ነበሩ፡፡ በእርግጥ አሉ ወ/ሮ ይርገዱ “...በእርግጥ ወደመጨረሻ የተወለዱትን ሁለት ልጆች ስወልድ ችግር ገጥሞኝ ነበር፡፡ አንዱዋም በሰባት ወርዋ የተወለደች ስትሆን ሌላዋ ደግሞ የተለያዩ የጤና ጉድለቶች ነበሩባት። እናም በከፍተኛ ሁኔታ እንክብካቤ ተደርጎ እና በሐኪሞችም ያላሳለሰ ክትትል ሰው ሆነው ዛሬ ጥሩ አቋም ላይ ይገኛሉ” ብለዋል፡፡
ከወ/ሮ ይርገዱ ታሪክ መለስ በማለት በዘመኑ ያሉትን ወላዶች አነጋግረናል፡፡ በክሊኒክ ክትትል ሲያደርጉ ካገኘናቸው መካከል የምትከተለው እናት ትገኝበታለች፡፡
“...ወ/ሮ ኤልሳቤጥ እባላለሁ፡፡ አሁን አንድ ልጅ አለኝ፡፡ የወለድኩት  በኦፕራሲዮን ስለሆነ ለመውለድ የሚፈቀድልኝ ጊዜ ገና ስለሆነ እንጂ እኔ ልጅ መውለድ እፈልጋለሁ፡፡
ጥ/    እስከስንት ልጅ መውለድ ትፈልጊያለሽ?
መ/    እኔ እስከ አራትም ይሁን አምስት ልጅ ብወልድ ደስተኛ ነኝ፡፡
ጥ/    ባለቤትሽ በዚህ ይስማማል?
መ/    በእርግጥ እሱ እስከሶስት ይላል... እኔ ግን ልጅ እወዳለሁ፡፡
ጥ/    የማሳደግ ሁኔታውስ እንዴት ነው?
መ/    እኔ እማምነው ልጆች በረከት ናቸው በሚለው ነው፡፡ ልጅ ሲወለድ የራሱን ነገር ይዞ ይመጣል በሚለው ስለማምን ብወልድ ደስ ይለኛል።
ጥ/    ይህ ስሜት ከምን የመጣ ይመስልሻል?
መ/    አባቴ ቀደም ብሎ ስለሞተ እኛ ቤት እኔና ወንድሜ ብቻ ነን የተወለድነው፡፡ በአንድ ወቅት ወንድሜ ሲታመም እኔ የማዋራው ሰው እንኩዋን አጥቼ ነበር፡፡ እህት ወንድም ቢኖረኝ ኖሮ እያልኩ አስብ ነበር፡፡ እናም ከዚያ በመነሳት ልጄ ብቻዋን እንድትሆን ስለማልፈልግ ይመስለኛል፡፡  
ሌላው እንግዳችን አባት ነው፡፡ የእርሱ ሀሳብ ደግሞ በፍጹም ከወ/ሮ ኤልሳቤጥ ይለያል፡፡
“...እኔ ቢኒያም ጌታቸው እባላለሁ፡፡ አንድ ልጅ አለኝ፡፡ እድሜውም ወደሶስት አመት ደርሶአል፡፡ እኔ ልጅ እንዲበዛ አልፈልግም፡፡
ጥ/    ለምን?
መ/    የልጅን ቁጥር መወሰን አስፈላጊ ነው። ልጅን መውለድ ማለት ወልዶ በማሳደግ ደረጃ ብቻ መወሰን ያለበት አይመስለኝም፡፡ ለምሳሌ ወደ ወላጆቻችን አኑዋኑዋር ስንመለስ የምንታዘበው ነገር አለ፡፡ እነእርሱ በዘመናቸው መሬት... ቤት... ሌላም ሌላም ሀብት የነበራቸው ሲሆን ልጅ እየወለዱ ያለሀሳብ አስተምረው አሳድገው ሲያልፉም ለእኛ መቋቋሚያ አውርሰው ይሆናል፡፡ በእርግጥ ይህ የሁሉም ሰው አኑዋኑዋር ባይሆንም በነበረው ልምድ የጎረቤት ልጅ የራስ ልጅ ተደርጎ የሚወሰድበት ሁኔታ ስለነበር ሀብታሙ ከደሀው ጋር ተጋግዞ እንዲሁም አንዱ አንዱን እረድቶ በሚያሰኝ ሁኔታ አድገናል፡፡ ዛሬ ግን ያለው ሁኔታ ፈጽሞ የተለየ ነው፡፡ ወላጅም እንደድሮው ያለ አኑዋኑዋር የለውም...እርስ በእርስ መተጋገዙም ቢሆን እስከዚህ የሚታይ አይደለም፡፡ ስለዚህ አንድ ወላጅ የሚያሳድገውን ብቻም ሳይሆን ወደፊት የወለደው ልጅ እንዴት እንደሚኖር ማሰብም ይጠበቅበታል ብዬ አምናለሁ፡፡
ጥ/    ልጅን በኑሮው ማቋቋም አስፈላጊ ነው ብለህ ታስባለህ?
መ/    ቢያንስ ቢያንስ የወለድኩት ልጅ በደንብ ተምሮ አድጎ ...ወደፊት ምን ሊሰራ እንደሚችል ማመላከት ...ምናልባትም የስራ ፈጠራን ማሳየት... ብችል እራሴ ስራ ፈጥሬ የወለድኩት ልጅ እንዲያስፋፋው ማድረግ ይጠበቅብኛል ብዬ አምናለሁ፡፡
ጥ/    በአንድ ልጅ ተወስኖ መቅረት ነው? ወይንስ?
መ/    አ.አ.ይ፡፡ አንድ ልጅ ጨምረን ሁለት እንደሚሆኑ ከባለቤቴ ጋር ተስማምተናል፡፡
ሌላዋ እንግዳ ወ/ሮ ሳራ ትባላለች፡፡ ያገኘናት ለእራስዋ የህክምና ክትትል ለማድረግ ከሄደችበት ክሊኒክ ነው፡፡
“...እኔ ሁለት ልጆች አሉኝ፡፡ እድሜያቸውም ትልቅዋ ስምንት አመት ሲሆን ትንሹ ደግሞ ስድስት አመቱ ነው፡፡
ጥ/    ከባለቤትሽ ጋር ...ሁለት ልጅ ይበቃናል ብላችሁ ወስናችሁዋል?  
መ/    ልጅ ብንጨማምር ደስ ይለን ነበር፡፡ ነገር ግን የማሳደግ ሁኔታው እጅግ አስመርሮናል፡፡
ጥ/    ኢኮኖሚው ነው... ወይንስ?
መ/    አ.አ.ይ... ኢኮኖሚውን እንደብልሀቱ ልናደርገው እንችል ነበር፡፡ ነገር ግን የሚረዳኝ ሰው በማጣቴ ሁለቱን ልጆች ለማሳደግ በጣም ተሰቃይቻለሁ፡፡ ሰራተኛ እንደልብ አይገኝም። ቢገኙም ባልታሰበ ሁኔታ ትተው ይሄዳሉ፡፡ ስለዚህ ...ግማሽ በግማሽ ከስራዬ እየቀረሁ ማለት በሚያስችል ሁኔታ ልጆቼን አሳድጌያለሁ፡፡ ከዚህ በሁዋላ ያ ሁኔታ እንዲደገም አልፈልግም እንጂ ቢያንስ ቢያንስ አንድ ሴት ልጅ ብደግም እፈልግ ነበር፡፡
ጥ/    ልጆችን ለመንከባከብ ከስራ መቅረት ያንቺ ብቻ ድርሻ ነበር ወይንስ የባለቤትሽም?
መ/    እንደሁኔታው ሁለታችንም እየተጋገዝን ነው ልጆቻችንን ያሳደግነው፡፡ እንደስራው ክብደትና ሁኔታ እየተነጋገርን ነበር ያንን የምናደርገው፡፡ ከእኔና እሱ በተጨማሪም ቤተሰቦቻችንም እያገዙን ነው የተወጣነው።
በመቀጠል ሀሳቡን የሰጠን አባት ነው፡፡ አቶ ክፍሎም ገብረሕይወት ይባላል፡፡ የአንድ ልጅ አባት ነው፡፡ ልጁ ወደሶስት አመት ይሆነዋል፡፡
ጥ/    አንተ እና ባለቤትህ ሌላ ልጅ የመውለድ እቅድ አላችሁ?
መ/    ልጅ መውለድ እንፈልጋለን፡፡ ነገር ግን እራሳችንን ማደራጀት ስላለብን ቆም ማለት ፈልገናል፡፡
ጥ/    እራስን ማደራጀት ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/    የምንወልዳቸውን ልጆች በሚገባ አስተምረን በብቃት ለማሳደግ እንድንችል እራሳችንን ማስተማር... ኑሮአችንን ማደራጀት... የመሳሰሉት ስለሚያስፈልጉን ባለቤቴም ሁለተኛ ዲግሪዋን እኔም ሶስተኛውን ዲግሪዬን በመስራት ላይ እንገኛለን፡፡ ይሄንን ካስተካከልን እኛ እያደግን ስለምንሄድ የምንወልዳቸውም ልጆች በጥሩ ሁኔታ ያድጋሉ የሚል እምነት አለን፡፡
በስተመጨረሻ የተነሳውን ፍሬ ሀሳብ የሚጠቀልሉልን የህክምና ባለሙያ ዶ/ር ዳንኤል አስፋው ናቸው፡፡
የቤተሰብ እቅድ ዘዴን መጠቀም የሚያስፈልገው በተለያዩ ምክንያቶች ነው፡፡ የቤተሰብ እቅድ አገልግሎት እንደሚያስረዳው ልጆችን አራርቆና ጤናማ በሆነ መንገድ ለማሳደግ ቤተሰብ የተወሰኑ ልጆችን የመውለድ እቅድ እንዲኖረው ያስፈልጋል፡፡ በሕክምናው፣ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚው እና ከወቅቱ ሁኔታ ጋር በተያያዘ አስገዳጅ ነገሮች መኖራቸው ልብ ሊባል ይገባል፡፡ ከኢኮኖሚ አቅም በላይ መውለድ የልጆችን አስተዳደግ ጥራት ሊቀንስ ይችላል፡፡ በሌላ አቅጣጫ ደግሞ ገንዘብ አለን ተብሎም ስፍር ቁጥር የሌላቸውን ልጆች መውለድም አይመከርም፡፡ ይሄም ከህክምናው አገልግሎት ይሁን ከኢኮኖሚው እንዲሁም ወቅታዊ ሁኔታ ጋር የማይታረቅ ውሳኔ ይሆናል፡፡ የቤተሰብ እቅድ ሲባል አለምአቀፋዊ ትኩረት ያለው አሰራር ነው፡፡ ቤተሰብ ሲባል ደግሞ አንድ ተቋም ሲሆን ያ ተቋም የራሱ የሆነ ቪዥን እና ሚሽን ያለው እንዲሆን ይጠበቃል፡፡ የዚህም ውጤት በትዳር አለም በእቅድ የተወሰኑ ልጆችን ወልዶ አስተምሮ እና አንጾ በማሳደግ ለሀገር ብቁ ዜጋን ማስረከብ ነው። በቀጣይም የመልካም ዜጋ መተካካት በሀገር ላይ እንዲፈጠርና ወገን እንዲጠቀም ...ሀገር እንድታድግ የሚያስችል አካሄድ ነው፡፡

   የኢትዮጵያ ብሔራዊ የባህል ማዕከልና ኤልሰን ፕሮሞሽን በመተባበር ያዘጋጁት “የጀበና ሙሽሮች” የተሰኘ የቡናና የኪነጥበብ ፌስቲቫል በትላንትናው እለት በብሔራዊ ቴአትር የተከፈተ ሲሆን ፌስቲቫሉ እስከ ነገ እንደሚቆይም ታውቋል፡፡ የተለያዩ ክልሎች የቡና አፈላል ስርዓታቸውን ከነ አቀራረቡና ሙሉ ስርዓቱ ወክለው በተገኙበት በዚህ ፌስቲቫል ላይ የኢፌድሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሙሉጌታ ሰኢድ እና የቀድሞው የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ክቡር ዶ/ር ግርማ ወ/ጊዮርጊስ በክብር እንግድነት ተገኝተዋል፡፡ “”ቡና ከእለት የእለት ህይወታችን ጋር የተገናኘ ቢሆንም በደንብ አናውቀውም፤ ይህን ቡና ለራሳችን በደንብ ለማስተዋወቅ ታስቦ የተዘጋጀ ፌስቲቫል ነው” ብሏል - ፕሮሞተር ዮናስ ታደሰ፡፡ በአሜሪካ የአቦል ቡናና የመርካቶ ገበያ መስራች የሆኑት አቶ ታምሩ ደገፋና ከፈረንሳይ የመጡት ወ/ሮ አለም ፀሐይ ንባብ፤ የኢትዮጵያን ቡና በያሉበት እንዴት እንደሚያስተዋውቁ በፌስቲቫሉ መክፈቻ የገለፁ ሲሆን፤ አቶ ታምሩ ደገፋ በአሜሪካ ለታዋቂው ሙዚቀኛ ለማይክል ጃክሰን በአንድ ወቅት ስለ ኢትዮጵያ ቡና ሰፊ ማብራሪያ እንዳደረጉለት ተናግረዋል፡፡ ፌስቲቫሉ እስከ ነገ የሚቆይ ሲሆን የአማራ፣ የትግሬ፣ የኦሮሞ፣ የጉራጌና የሌሎች ብሔሮች የቡና ስርዓት ለእይታ ቀርቦ እየተጐበኘ ነው፡፡   

ዩኒቲ ዩኒቨርስቲ ዓመታዊ የጥናትና ምርምር ጉባኤውን በትላንትናው ዕለት የጀመረ ሲሆን፤ ዛሬ እንደሚጠናቀቅ ለማወቅ ተችሏል፡፡ መቻሬ ሜዳ በሚገኘው ሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ኮርፖሬት ሴንተር የሚካሄደው ይሄው ጉባኤ፤ ዘንድሮ ለ13ኛ ጊዜ እየተካሄደ ሲሆን በተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የሚሰሩ ምሁራንና የምርምር ተቋማት የሰሯቸው የተመረጡ የጥናትና ምርምር ውጤቶች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል ተብሏል፡፡ በየአመቱ የሚካሄደው ይሄው “Multidisciplinary Research Conference” በትላንትናው እለት ከጠዋቱ 2፡30 ሰዓት ተጀምሮ በተለያዩ ምሁራን እየቀረበ ሲሆን የምርምር ውጤቶቹም የማህበረሰቡን ችግር በመፍታትና በማቃለል ረገድ ጉልህ ሚና ይኖራቸዋል ተብሏል፡፡

ካለፈው መጋቢት ወር ጀምሮ “በማቭሪክ ፊልሞች የኢትዮጵያ” አማካኝነት በኢቲቪ ቻናል ሶስት ሲተላለፉ ከነበሩ 12 ፊልሞች ሶስቱ ባለፈው ረቡዕ ምሽት በኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ተሸለሙ፡፡ ማቭሪክ ፊልሞች የኢትዮጵያ በሚል መጠሪያ በቻናል ሶስት የኢትየጵያ ፎልሞችን ቅዳሜ ምሽት ከ4፡30 ሰዓት ጀምሮ የሚያስተላልፈው ድርጅት ፊልሞቹን ከማስተላለፍ በተጨማሪ በባለሙያዎችና በአዘውታሪ ተመልካቾች የተመረጡና ከ1 እስከ 3 የወጡ ፊልሞችን አወዳድሮ የመሸለም ዓላማ እንደነበረውም የፕሮግራሙ ዳይሬክተር ወ/ሪት ፌቨን ታደሰ በእለቱ ገልፃለች፡፡ ለተከታታይ 12 ሳምንታት ከተላለፉት 12 የአማርኛ ፊልሞች ውስጥ በ2001 ዓ.ም ለእይታ የበቃው “አልተኛም” ፊልም አንደኛ በመውጣት የ20ሺህ ብር ተሸላሚ ሲሆን በ2001 ዓ.ም የተሰራው “የታፈነ ፍቅር” ሁለተኛ በመውጣት የ10 ብር ሽልማት አግኝቷል፡፡ በ2004 ዓ.ም የተሰራው “አየሁሽ” ፊልም ሶስተኛ በመውጣት የአምስት ሺህ ብር ተሸላሚ ሆኗል፡፡
በእለቱ የኢቲቪ የስራ ኃላፊዎች፣ የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች፣ የማቭሪክ ፊልሞች የኢትዮጵያ ስፖንሰር የሆነው ፍሊንት ስቶን ሆምስ ባለቤቶችና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የተገኙ ሲሆን አርቲስት ስለሺ ደምሴ (ጋሽ አበራ ሞላ) በሙዚቃው ታዳሚዎቹን ሲያዝናና አምሽቷል፡፡

    በደራሲ ብርሃኑ አበጋዝ የተፃፈው “ጥምር ቁስል” ልብወለድ መጽሐፍ ሰሞኑን ገበያ ላይ ዋለ፡፡ መጽሐፉ ትኩረት የደረገው በኢትዮ - ኤርትራ ጦርነትና በሁለቱ ሀገራት ህዝቦች ቁርኝት ላይ ሲሆን የኢትዮጵያና የሶማሊያ ጦርነትም በልብወለዱ ውስጥ ተዳስሷል፡፡ በ161 ገጽ የተቀነበበው ልብወለዱ፤ 37 ክፍሎች ያሉት ሲሆን ታሪኩ በሃሳብ ደረጃ ከተፀነሰ 14 ዓመታት፣ መፃፍ ከተጀመረ ደግሞ ሰባት ዓመታትን እንዳስቆጠረ ደራሲው በመግቢያው ላይ ገልጿል፡፡ ታሪካዊ ልብ ወለድ መጽሐፉ ዛሬ ከቀኑ በ10፡30 በኢዮሃ ሲኒማ የሚመረቅ ሲሆን በ40 ብር ከ60 ሳንቲም እየተሸጠ ይገኛል፡፡

የኢትዮጵያን ፊልም 50ኛ ዓመት በዓል ምክንያት በማድረግ በኢዮሃ ሲኒማና በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የተዘጋጀው የፊልም ስልጠና ረቡዕ ተጠናቀቀ፡፡ ስልጠናው የተሰጠው ወደ 60 ለሚጠጉ የፊልም ባለሙያዎችና ጋዜጠኞች ሲሆን በፊልም መመሪያና ስነ ምግባር፤ በፊልም ዝግጅት፣ በፊልም ስክሪፕት አፃፃፍና በፊልም ትወና ላይ ያተኮረ እንደነበር በማጠናቀቂያው ላይ ተገልጿል፡፡
ለአራት ቀናት በቆየው በዚህ ስልጠና ላይ ዮናስ ብርሃነ መዋ፣ ብርሃኑ ሽብሩ፣ ሄኖክ አየለ እና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የመጡ የስነ ልቦና ባለሙያዎች በአሰልጣኝነት መሳተፋቸውም ታውቋል፡፡

የገጣሚ ሶልያና አብዲ “ሼም ይናፍቅሃል” የተሰኘ የግጥም መድበልና ሲዲ ዛሬ ከ3ሰዓት ጀምሮ በጣይቱ ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ ይመረቃል፡፡
በመድበሉ ውስጥ የተካተቱት ግጥሞች በሴቶች ጥቃት፣ በህገወጥ ጉዞ አስከፊነት፣ በወጣትነትና በፍቅር ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ሲሆን የግጥሙ ሲዲ ደግሞ በኢትዮጵያ ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድኖች (ዋሊያዎቹና ሉሲዎች) ጀግንነት ላይ የሚያተኩር ነው ተብሏል፡፡ 94 ያህል ግጥሞችን የያዘው መድበሉ በ30 ብር ለሽያጭ ቀርቧል፡፡

“በሰው ለሰው” ድራማ የአዱኛን ገፀ - ባህሪ ወክሎ በመጫወት እና በበርካታ ስራዎቹ አድናቆትን ያተረፈው አርቲስት ይገረም ደጀኔ፤ “ቆምኩኝ ለምስጋና” የተሰኘ የምስጋና የመዝሙር ሲዲ ያወጣ ሲሆን፤ ሰኞ ገበያ ላይ እንደሚውል ተገለፀ፡፡ አርቲስቱ ለመዝሙሩ ከተከፈለው 40ሺህ ብር ላይ 20ሺህ ብሩን ለሜቄዶንያ አረጋዊያን መርጃ በእርዳታ ሲሰጥ ቀሪውን እያገለገለ ላደገበት ሰንበት ት/ቤት መለገሱን ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡
በመዝሙር ሲዲው ውስጥ 11 መዝሙሮች የተካተቱ ሲሆን፤ አምስቱን ለብቻው ሁለቱን ከዘማሪ ዲያቆን ፍቃዱ አዱኛ ጋር በጋራ መስራቱንና ቀሪዎቹ አራት መዝሙሮች በዘማሪ አዱኛ እንደተሰሩ ይገረም ገልጿል፡፡
“የዘመርኩት ማመስገን ስለምወድ” ነው ያለው አርቲስቱ፤ ሌሎችም የተሰጣቸውን ፀጋ ተጠቅመው የድርሻቸውን እንዲያበረክቱ ለማነቃቃት በስራው ላይ መሳተፉን ተናግሯል፡፡  
“ወደፊት ከእኔ ጋር በበጎ ስራዎች ላይ ለመሰማራት የሚፈለግ ሰው ካለ አብሬ ለመስራት ዝግጁ ነኝ” ብሏል - አርቲስት ይገረም ደጀኔ፡፡ አርቲስቱ ከዚህ ቀደም ለአቡነ መልከፀዴቅ ገዳም ለገቢ ማሰባሰቢያ የሚውል የመዝሙር ቪሲዲ ከሙያ አጋሮቹ ጋር መስራቱ ይታወሳል፡፡  

Saturday, 21 June 2014 14:58

የፍቅር ጥግ

(ስለጋብቻና ፍቺ)
አባት ለልጆቹ ሊያደርግ የሚችለው ትልቁ ነገር፣ እናታቸውን ማፍቀር ነው፡፡
ቴዎዶር ኼስበርግ
ሰዎች በትዳር የሚዘልቁት፣ ስለፈለጉ ነው እንጂ በሮች ስለተቆለፉባቸው አይደለም፡፡
ፖል ኒውማን
ፍቺ አካልን እንደመቆረጥ ነው፡፡ አንዳንዴ አስፈላጊ ሊሆን ይችላል፡፡ ከተቻለ ግን ባይሆን ይመረጣል፡፡ ምክንያቱም ዘላቂ አካል ጉዳተኝነትን ያስከትላል፡፡
ቢል ዶኸርቲ
ፍቺ ለልጆች እንዲሁም ለሌሎች ህይወት ያላቸው ነገሮች ሁሉ ጤናማ አይደለም፡፡
ዲያኔ ሶሊ
የተሻለ ነገር እስኪመጣ ድረስ ጋብቻን እንደተቋምከእነችግሮቹ  እደግፈዋለሁ፡፡
ዴቪድ ብላንከንሆርን
(የአሜሪካ እሴቶች ተቋም)
እያንዳንዱ ፍቺ የትንሽዬ ስልጣኔ ሞት ነው፡፡
ፓት ኮንሮይ
የህብረተሰብ የመጀመሪያው ማሰሪያ ጋብቻ ነው፡፡
ሲሴሮ
በማህበራዊ ጥናት አንድ አባባል አለ፡- “እናት በመላው ህይወትህ ሁሉ እናት ናት፡፡ አባት ግን አባት የሚሆነው ሚስት ሲኖረው ብቻ ነው”
ሊህ ዋርድ ሲርስ
(የጆርጅያ ጠ/ፍርድ ቤት ዋና ዳኛ)
ድሮ ወላጆች ብዙ ልጆች ነበራቸው፡፡ አሁን ልጆች ብዙ ወላጆች አሏቸው፡፡
ጉሮ ሃንሰን ሄልስኮግ
አንዳንዴ ባልና ሚስት መጣላታቸው አስፈላጊ ነው፡፡ የበለጠ እርስ በርስ እንዲተዋወቁ ያደርጋቸዋል፡፡
ገተ
ትክክለኛውን ፍቅር ከመፍጠር ይልቅ ትክክለኛውን አፍቃሪ በመፈለግ ጊዜያችንን እናጠፋለን፡፡
ቶም ሮቢንስ

    ያልተቋረጠ የሽብር ጥቃት ከራሳቸው ላይ አልወርድ ብሎ እጅግ ግራ የተጋቡ ሁለት የአፍሪካ ሀገራት አሉ ከተባለ ከኬንያና ናይጀሪያ ውጭ ሌላ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ ያላባራ የሽብር ጥቃት ሰለባ የሆነችው ኬንያ፤ ባለፈው እሁድና ሰኞ በተከታታይ የወረደባት የሽብር መአት የጦርነት ቀጠና አስመስሏታል፡፡
የአልሸባብ አባላት ሳይሆኑ እንዳልቀረ በሰፊው የተጠረጠሩ ሽብርተኛ ታጣቂዎች ባለፈው እሁድ የሱማሊያ አዋሳኝ የኬንያ ግዛት ከሆነችው የላሙ ደሴት አቅራቢያ በምትገኘው የምፒኪቶኒ ከተማ ላይ ድንገት አደጋ ጥለው አርባ ስምንት ኬንያውያንን ገድለዋል፡፡ እሁድ እለት ማታ ላይ ከተፈፀመው ከዚህ ጥቃት ያመለጡ የአይን እማኞች፤ ሽብርተኛ ታጣቂዎቹ ቤት ለቤት እየዞሩ የቤቱ አባወራ ሙስሊም መሆኑንና የሶማሊያ ቋንቋ ተናጋሪ መሆን አለመሆኑን ያጣሩ እንደነበረ ጠቁመው በተለይ ሆቴል ውስጥ ካገኟቸው ወንዶች ውስጥ ሙስሊም ያልሆኑትን ብቻ ለይተው በማውጣት፣ሚስቶቻቸው ፊት በጥይት ደብድበው እንደገደሏቸው አስረድተዋል፡፡
የምፒኪቶኒ ከተማ ነዋሪም ሆነ መላ ኬንያውያን የዚህ ጭካኔ የተሞላበት ጭፍጨፋ ድንጋጤ ገና በወጉ እንኳ ሳይለቃቸው ሰኞ እለት ከከተማዋ በቅርብ ርቀት ላይ በምትገኘው የማጂምቤኒ ከተማ እነዚሁ ሽብርተኛ ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት የአስር ኬንያውያንን ህይወት ቀጥፈዋል፡፡
ድፍን አለሙም ሆነ መላ ኬንያውያን እንደጠረጠሩት፣ የሶማልያው ሽብርተኛ ቡድን አልሸባብ ኬንያ በሶማልያ ላይ ለፈፀመችው ወታደራዊ ጣልቃ ገብነትና በሙስሊሞች ላይ ላደረሰችው በደል ሁለቱንም ጥቃቶች በማድረስ የእጇን እንደሰጣት በመግለፅ ሃላፊነቱን ወስዷል፡፡
የኬንያው ፕሬዚደንት ኡሁሩ ኬንያታ ግን አልሸባብ የሰጠው መግለጫ ፈጽሞ ሊዋጥላቸው አልቻለም፡፡ በሽብር ጥቃቱ ከተገደሉት አብዛኞቹ የእሳቸው ብሔር አባላት የሆኑ ኪኩዩዎች መሆናቸውን መሰረት በማድረግ ሃላፊነቱን ከወሰደው አልሸባብ ይልቅ በዘረኝነት የታወሩ ባሏቸው ኬንያውያን ፖለቲከኞች ላይ ጣታቸውን በመቀሰር ተጠያቂ አድርገዋቸዋል፡፡ የፕሬዚዳንቱን ውንጀላ ተከትሎም የኬንያ ፖሊስ በሽብር ጥቃቱ እጃቸውን አስገብተዋል ያላቸውን በርካታ ኬንያውያንን ከያሉበት ለቃቅሞ ወህኒ ከርችሟቸዋል፡፡