Administrator

Administrator

አድናቂዎች ለዕጩዎቹ ድምጽ መስጠት ይችላሉ

ኢትዮጵያውያኑ ድምጻውያን አስቴር አወቀና ጃኪ ጎሲ፣ “አፍሪካን ሚዩዚክ ማጋዚን አዋርድስ” (አፍሪማ) ለተባለው ታላቅ አህጉራዊ የሙዚቃ ሽልማት በተለያዩ ዘርፎች በእጩነት ቀረቡ፡፡
አፍሪማ ሰሞኑን ይፋ ባደረገው የ2014 ሽልማት እጩዎች ዝርዝር ላይ እንደተጠቀሰው፣ ድምጻዊት አስቴር አወቀ በ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ሴት ድምጻዊት”፣ ጃኪ ጎሲ ደግሞ በ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ወንድ ድምጻዊ” ዘርፍ በእጩነት የቀረቡ ሲሆን፣ የሌሎች የአፍሪካ አገራት ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ቡድኖች፣ ማኔጀሮች፣ ዳይሬክተሮች፣ ፕሮዱዩሰሮች፣ ዲጄዎች፣ የዳንስ ቡድኖችና የሙዚቃ ቪዲዮዎችም በተለያዩ 26 ዘርፎች ለሽልማት ታጭተዋል፡፡
አስቴር አወቀ በታጨችበት የ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ሴት ድምጻዊት” ዘርፍ፣ ሌሎች ሁለት የኡጋንዳ፣ ሁለት የኬኒያና አንድ የታንዛኒያ ታዋቂ ድምጻውያን በእጩነት የቀረቡ ሲሆን፤ ጃኪ ጎሲ በቀረበበት የ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ወንድ ድምጻዊ” ዘርፍ ደግሞ፣ ሌሎች ሁለት የታንዛኒያ፣ ሁለት የኡጋንዳና አንድ የኬኒያ ድምጻውያን በእጩነት ቀርበዋል፡፡
አድናቂዎች http://afrimma.com/afrimma-nominees-2014/ በሚለው የድረ-ገጽ አድራሻ በመጠቀም ለሚፈልጓቸው እጩ ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ቡድኖችና ሌሎች እጩዎች ድምጻቸውን በመስጠት፣ አሸናፊ እንዲሆኑ የራሳቸውን ድጋፍ ማድረግ እንደሚችሉ የሽልማቱ አዘጋጆች ተናግረዋል።
በመጪው ሃምሌ ወር አጋማሽ በአሜሪካ ቴክሳስ ግዛት፣ ሪቻርድሰን ውስጥ በሚከናወነው የሽልማት ስነስርዓት ላይ፣ በአለማቀፍ ደረጃ እውቅናን ያተረፉ የተመረጡ አፍሪካውያን ድምጻውያን፣ ማኔጀሮች፣ ፕሮዲዩሰሮች፣ ዲጄዎች፣ ባህላዊ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች በክብር ይሸለማሉ ተብሏል፡፡ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ከተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች የተጋበዙና ከ17 የአፍሪካ አገራት በክብር እንግድነት ተጋብዘው የሚመጡ ታላላቅ ጀግኖች ይታደማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የአፍሪካን ሙዚቃ የማስተዋወቅ አላማ ያለውና በየአመቱ በሚከናወን ደማቅ ስነስርኣት ለአሸናፊዎች የሚበረከተው ይህ ሽልማት፤ በዘርፉ ከሚሰጡ ታላላቅ አህጉራዊ ሽልማቶች አንዱ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ የሆኑ ድምጻውያንና የሙዚቃ ቡድኖች ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡበትና በቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት ለእይታ የሚበቃውን የዘንድሮውን የአፍሪማ የሙዚቃ ሽልማት ስነስርዓት ስፖንሰር ያደረጉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ፓዎር ሃውስ ኢንተርናሽናል ኤርላይንና አክሴስ የተባለው የአሜሪካ ሶፍትዌር አምራች ኩባንያ መሆናቸውንም የሽልማት ድርጅቱ መስራች አንደርሰን ኦቢያጉ በድረ-ገጻቸው ላይ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል፡፡

ውድ እግዚአብሔር-
ስለአንተ ሥራ አስተማሪያችን  ነግራናለች፡፡ አንተ እረፍት ስትወጣ ግን  ማነው የሚሰራልህ?
ዴቪድ-የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡ አንተስ?
ቤቢ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
ትምህርት ቤት ስንማር፣ መብራት የፈጠረው ቶማስ ኤዲሰን ነው ተብለን  ነበር፡፡ ሰንበት ት/ቤት ደግሞ አንተ እንደፈጠርከው ነገሩን፡፡ ኤዲሰን ያንተን ሃሳብ ሰርቆብህ ነው አይደል ?
ዮኒ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
ህፃን ወንድም ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ እኔ ግን የጠየኩህ የምታምር ቡችላ እንድትሰጠኝ ነበር፡፡
ቤቲ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
ስለእኔ እንዳታስብ እሺ፡፡ ሁልጊዜ መንገድ ስሻገር ግራና ቀኙን በደንብ አይቼ ነው፡፡
ዳኒ-የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
እሁድ እለት ቤተክርስትያን የምትመጣ ከሆነ አዲሱን ጫማዬን አሳይሃለሁ፡፡
ሚኪ-የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
በዓይን የማትታየው ሰማይ ሩቅ ስለሆነ ነው አይደል?
ሳሚ- የ4 ዓመት ህፃን

Saturday, 24 May 2014 15:00

የፀሐፍት ጥግ

አንድ ፅሁፍ ያለልፋት በቀላሉ ከተነበበ፣ ሲፃፍ በእጅጉ ተለፍቶበታል ማለት ነው፡፡
ኤንሪክ ጃርዴይል ፓንሴላ
እውነተኛ ፀሐፍትን ተስፋ ማስቆረጥ አይቻልም፡፡ ምንም ብትሏቸው ደንታ  ሳይሰጣቸው ይፅፋሉ፡፡
ሲንክሌይር ልዊስ
በእጄ ላይ ብዕር ይዤ እንቅልፍ ከጣለኝ ብዕሬን አትንኩብኝ፣ በእንቅልፍ ልቤ ልፅፍ እችላለሁ፡፡
ቴሪ ጉሌሜትስ
የመፃፍ ተሰጥኦ እንደሌለኝ ለማወቅ አሥራ አምስት ዓመት ፈጅቶብኛል፡፡ ፅሁፍን ማቆም ግን አልቻልኩም፡፡
 ምክንያቱም ያኔ  ዝነኛ ፀሃፊ ሆኛለሁ፡፡
ሮበርት ቤንችሌይ
የምንፅፈው አሁናችንን በኋላ ለማስታወስ ነው፡፡
 ቴሪ ጉሌሜትስ
ማንም ሰው  የፃፈውን ነገር ለሴት ሳያነብ መፅሃፍ ማሳተም የለበትም፡፡
ቫን ዊክስ ብሩክ
ሃኪሜ የምትኖረው ለስድስት ደቂቃ ብቻ ነው ቢለኝ በፍርሃት አልርድም፤ ፍጥነቴን
 ጨመር አድርጌ እፅፋለሁ እንጂ፡፡
አይሳክ አሲሞቭ

ዊሊያም ዎርድስዎርዝ (1770-1850)
እንግሊዛዊው ገጣሚ ዎርድስዎርዝ  ገና 15 ዓመት ሳይሞላው ነበር ወላጆቹን በሞት ያጣው፡፡ እንዲያም ሆኖ በእንግሊዝ የተሳካላቸውና ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሚባሉት ገጣምያን ተርታ ከመሰለፍ ያገደው ነገር አልነበረም፡፡ ግጥሞችን መፃፍ የጀመረው ገና ተማሪ ሳለ ቢሆንም 23 ዓመት እስኪሞላው ድረስ ግን አንድም የግጥም ሥራው አልታተመለትም ነበር። ዎርድስዎርዝ  የፃፋቸውን ግጥሞች የሚያነበው ለውሻው ሲሆን  ውሻው በተነበበለት ነገር ከጮኸ ወይም ከተበሳጨ፣ ዎርድስዎርዝ ግጥሙን ማሻሻልና እንደገና መፃፍ እንዳለበት ተገንዝቦ ወደ ሥራው ይገባል፡፡
ዲክ ኪንግ-ስሚዝ (1922-2011) በእንስሳት ላይ የተመሰረቱ የህፃናት መፃህፍትን በመፃፍ ይታወቅ የነበረው እንግሊዛዊው ደራሲ ዲክ ኪንግ- ስሚዝ፤በሙያ ዘመኑ ከ100 በላይ መፃህፍትን ፅፏል፡፡ ዝናን ያጎናፀፈው መፅሃፉ The Sheep Pig የተሰኘው ሲሆን ይሄ ሥራው Babe በሚል ርዕስ ወደ ፊልም ተቀይሮለታል፡፡ የመጨረሻ መፅሃፉ በ2007 እ.ኤ.አ የታተመለት ሲሆን The Mouse Family Robinson ይሰኛል፡፡ ደራሲው የፃፋቸው ታሪኮች አሁንም ድረስ በመላው ዓለም በሚገኙ ህፃናት ዘንድ በፍቅር እንደሚነበብለት ይነገራል፡፡


ከ800 ሚሊዮን በላይ መፃሕፍቶችን የቸበቸበችው የረዥም ልብወለድ ፀሐፊዋ ዳንኤላ ስቲል፤ የመጀመርያ ረቂቅ ፅሁፏን እስክታጠናቅቅ ድረስ በጥንት የትየባ ማሽን ላይ በቀን ለ20 ሰዓታት ትፅፋለች፡፡ በአንድ መፅሃፍ ላይ አተኩሮ ከመስራት ይልቅ በአንድ ጊዜ ከ4-5 የሚደርሱ መፃሕፍት ላይ በመስራትም ትታወቃለች፡፡
ጥቂት የማይባሉ የደራሲዋ ልብወለዶች ወደ አማርኛ ተተርጉመው ለአገራችን አንባቢያን መቅረባቸው የሚታወቅ ሲሆን ወደ ፊልም የተቀየሩ ሥራዎቿም በቅዳሜ የታላቅ ፊልም ፕሮግራም ላይ ለተመልካች  ይቀርቡ ነበር፡፡


ስቲፈን ኪንግ
ከ350 ሚሊዮን በላይ ኮፒዎች የተሸጡለት ይሄ አሜሪካዊ ደራሲ፤ ምንም ሳያስተጓጉል በየቀኑ ስድስት ገፆች ገደማ  ይፅፋል፡፡ በቀን ከ4 እስከ 6 ሰዓታት ማንበብና መፃፍ የማይችል ሰው ታላቅ ፀሐፊ የመሆን ህልሙን ይርሳው ሲልም ደራሲው ያስጠነቅቃል፡፡  
የድርሰት ትምህርት አንድን ሰው የመፃፍ ክህሎት ያስታጥቀዋል ብሎ የማያምነው ስቲፈን ኪንግ፤ ደራሲነት ከተፈጥሮ የሚገኝ ፀጋ ነው ባይ ነው፡፡ የመጀመርያ ድርሰቱን በ7 ዓመት እድሜው የፃፈው ኪንግ፤ ይሄን ድርሰት በ18 ዓመቱ ለአንድ መፅሄት እንደሸጠው ተዘግቧል፡፡ Carrie የተሰኘውን የመጀመርያ ልብወለዱን ከፃፈ በኋላ በተወዳጅ አስፈሪ (horror) ልብወለዶቹ እየታወቀ የመጣ ሲሆን የመጀመርያ አስፈሪ መፅሃፉም The Shining ይሰኛል፡፡  

አሜሪካዊው የልብ አንጠልጣይ ረዥም ልብወለዶች ደራሲ ዳን ብራውን፤ በሳምንት ለ7 ቀናት ሳያሰልስ በመፃፍ ይታወቃል - ከሌሊቱ 10 ሰዓት ጀምሮ፡፡  ይሄ የቀድሞ የእንግሊዝኛ መምህር፤ ዳቪንቺ ኮድ በተባለው ከፍተኛ ሽያጭ ያስመዘገበ ልቦለድ መፅሐፉ የሚታወቅ ሲሆን ይሄ ልቦለድ  በዚሁ ጋዜጣ ላይ በተከታታይ እየተተረጎመ ሲወጣ እንደነበር ይታወሳል፡፡  

    ዮናስ አብርሃም - የ“ትንንሽ ፀሀዮች” ደራሲና አዘጋጅ    

  “የትንንሽ ፀሐዮች” ተከታታይ የሬድዮ ድራማ በድንገት መቋረጡን በተመለከተ ባለፈው ሳምንት የአዲስ አድማስ ዕትም“ጥበብ” አምድ ላይ ቃለ-መጠይቅ እንደተደረገልኝና የጣቢያው ተወካይም ምላሽ መስጠታቸው ይታወሳል፡፡
በቅድሚያ ሀሳባችንን ለማስተናገድ ዕድል ስለተሰጠን አዲስ አድማሶችን ላመሰግን እወዳለሁ። በማያያዝም፣ ከጣቢያው የተሰነዘረው ምላሽ ከዕውነታው የራቀ በመሆኑ መልስ ለመስጠት ተገድጃለሁ፡፡
ድራማውን ማቋረጥ ያስፈለገው በሁለት ምክንያቶች መሆኑ ተጠቅሷል፡፡ አንዱ ምክንያት፡- “እንደማንኛውም ድራማ የሆነ ጊዜ ተጀምሮ ማለቅ ስላለበት ነው” ተብሏል፡፡ ይህ ምክንያት በመልስነት መቅረቡ ትዝብት ላይ ይጥላል፡፡ ታስቦበት የተጀመረ ስራ በታሰበበት መንገድ መጠናቀቅ ነበረበት። ‘ማለቅ’ የሚለው ቃል ደስ አይልም፡፡ ለሕዝብ የቀረበ ትልቅ ስራ እንዲያልቅ ስለተፈለገ በጣቢያው ውሳኔ ብቻ ‘ማለቅ’ የለበትም፡፡ እንዲቋረጥ ከተፈለገ ብዙ ቀና መንገዶች አሉ፡፡ ጊዜውንና ፈቃዱን ለሰጠ አድማጭ ስሜት ማሰብ ግድ ነው፡፡ ተቀባይነት ካገኘ በኋላ ሕዝቡ ባለቤት መሆኑ አይካድም፡፡ እኔ በማይመቹ ሁኔታዎች ውስጥ ስሰራ የቆየሁት፣ አድማጩንና የሙያ ስነምግባርን አክብሬ እንጂ የሚያጓጓ ጥቅም ስላገኘሁ፣ ወይም ሌላ ዕድል አጥቼ አልነበረም፡፡
የከፈልኩትን መስዋዕትነት፣ ያደረግሁትን ልዩ ጥረት… በቅርብ ያሉ ሁሉ ይረዱታል፡፡ ሠፊው አድማጭም የሚመሰክረው ሀቅ ነው፡፡ ‘ማለቅ ስላለበት’ ብቻ ‘አልቋል’ ተብሏል፡፡ ለነገሩ “ጉመደው፣ አስወግደው” የሚሉ ቃላት አዲስ አይደሉም፡፡
ሁለተኛው ምክንያት፡- “ድራማውን ከአድማጭ በሚመጣ አስተያየት እንገመግመዋለን፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜ ይዘት አልባ ሆነ የሚሉ አስተያየቶች ተበራከቱ” የሚል ነው፡፡ ‘ይዘት አልባ’ የሚለው ግምገማ ግልፅ አይደለም፡፡ ከጣቢያው ምስረታ ማግስት ጀምሮ በጋዜጠኝነትና በድራማ ፀሐፊነት (Playwright) የሠራ ሰው ‘ይዘት አልባ’ ስራ ይዞ አድማጭ ፊት አይቀርብም፡፡ ድራማዎች ሁሉ አንድ ዓይነት አይደሉም፡፡ አስተያየቱ አንድ ናቸው ከሚል ድምዳሜ የመጣ ይመስላል፡፡ የዚህ ዓይነቱን አፃፃፍ በራሴ ጥረት አንብቤ የጀመርኩት እንጂ ቴክኒኩና ፈጠራው ከጣቢያው አልተሰጠኝም፡፡ ድራማው በእኛ ካላንደር (ቀን መቁጠሪያ) ከእኛ ጋር የሚራመድ ታሪክ ስለሆነ እንጂ ዝግ ብሎ መሄዱ በስንፍና የመጣ አይደለም፡፡
በገፀ-ባህርያት ላይ የተመሠረተ ወቅታዊ ድራማ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ‘ይዘት አልባ’ ፕሮግራም መስራትን ጣቢያው አላስተማረኝም፡፡ ሚዛናዊነት አንዱ የጋዜጠኝነት ማዕዘን ነው፡፡ ሚዛናዊነቱ ለእኔ ካልሰራ ምንም ማድረግ አልችልም፡፡ ከዚህ ይልቅ ሌላ ምክንያት ቢፈለግ ጥሩ ነበር። “በቃ! አልፈለግነውም” ማለት ከባድ አይደለም። በመላ ሀገሪቱ ድራማውን በጉጉትና በአድናቆት የሚከታተሉት አድማጮች ጊዜያቸውን የሠጡት ‘ይዘት አልባ’ ለሆነ ነገር ከሆነ፣ በዕድሜና በዕውቀት የሚበልጠንን ሠፊ አድማጭ አለማክበር ነው፡፡
በመሠረቱ፣ እኔ የአለቆችን ስሜት እያነበብኩ የምሰራ ሰው አይደለሁም፡፡ እንደ ጣቢያው ሁሉ፣ የእኔም መለኪያ ሕዝብ ነው፡፡ ፈራጁ ተደራሲው ስለሆነም ስሜቱን በትኩረት እከታተላለሁ፤ ባለኝ መረጃ መሠረትም በጥሩ አቋም ላይ ነበርኩ፡፡ እነማን ምን እንዳሉ እኔ አላውቅም፡፡ በእኔ በኩል ግን… ሕዝብ ያልወደደውን ነገር በግድ ለመጋት ምን ምክንያት ይኖረኛል? ብዙ የጥቅም ዕድሎችን ሰውቼ ባልተመቸ ሁኔታ ውስጥ የቆየሁት፣ ደመወዝ ከፋዩ ሕዝብ ስለሆነ ውዴታውን አክብሬ፣ ለፍላጎቱ ተገዝቼ ነው፡፡
‘ይዘት የለውም’ ከሚባል ‘ዘይት የለውም’ ቢባል በአክብሮት እቀበል ነበር፡፡ ያለ እረፍት ለአምስት ዓመታት በየቀኑ እየፃፉ፣ በየሣምንቱ እየቀረፁ መዝለቅ ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ማሰብ አለመፈለግ ለደራሲው ያለውን ስሜት ያሳያል፡፡ ሕዝብ ግን ያውቀዋል፤ አድናቆትን ብቻ አይደለም ምርቃትም ስቀበል ኖሬአለሁ፡፡
“ተዋንያኑ እየለቀቁ በመሄዳቸው ድራማው ተዳከመ” የሚል አስገራሚ አስተያየት ተሰንዝሯል። ብቸኛው ደራሲና አዘጋጅ ችግር ገጥሞኛል ብሎ ካላመለከተ፣ ችግሩ ከቁጥጥር ውጪ አይደለም ማለት ነው፡፡
ተመስገን መላኩ (ቅቤው) ወደ አሜሪካ እንደሚሄድ የተነገረው ከሦስት ዓመት በፊት ነበር። በተለያየ ምክንያት ዘግይቶ ከስድስት ወራት በፊት ለስራ ሄደ፡፡ ስለዚህ ድራማው እንዳይጎዳ በቂ ጊዜ ነበረኝ ማለት ነው፡፡ እኔ ደራሲ ነኝ፣ ደራሲ ችግሮቹን ለመፍታት ብዙ መንገድ እንዳለው የሚፅፍ ሰው ያውቀዋል፡፡ የሚወደዱ ገፀ-ባህርያት ከስራው ገለል ሲሉ መናፈቃቸው ያለ ቢሆንም ገፀ-ባህርያቱ ግን ከደራሲው ሀሳብ ስር ናቸው፡፡ ከተፈለገ፣ ግድ የሚል ችግር ቢመጣም - ባይመጣም ከድራማው የሚወጡበት አሳማኝነት ያለው ጥበባዊ መብት በደራሲ እጅ እንዳለ ይታወቃል፡፡
በረከት በላይነህ (አመዶ)፣ ‘ድራማው አይመጥነኝም ብሎ መውጣቱን’ የሰማሁት ጣቢያውን ወክለው ከተናገሩት ኃላፊ ነው፡፡ እሱ፤ አላለም - አይልም፤ ለዚህ ደግሞ መላው የድራማው አባላት ምክንያቱን ያውቃሉ፡፡ ድራማው በጥድፊያ ‘አለቀ’ ተብሎ በተነገረ በሣምንቱ በረከት (አመዶ) የሰጠውን አስተያየት ማድመጥ ይቻላል፡፡
ለጥቂት ሣምንታት ድም    ፁ ባይኖርም፣ እኔ ሊፈጠሩ የሚችሉ ችግሮችን አስቀድሜ በማሰብ ጥንቃቄ ስለማደርግ፣ ሲጀመር ከነበረው ታሪክ ጋር ተያይዞ እንዲሄድ ተደርጓል፡፡ “አመዶ የት ሀገር ነው የሄደው… ለምንድነው የሄደው?” ብዬ በመጠየቅ ‘ይዘት አልባ’ ሆነ የሚሉትን ትዝብት ውስጥ ለመክተት አልፈልግም፡፡
ዋናዋ እና ተወዳጇ ገፀ-ባህሪ ሠብለ ተፈራ (እማማ ጨቤ) ለስራ ጉዳይ እንግሊዝ ስትሄድ፣ ድራማው ጣዕሙን እንደጠበቀ አቆይቼዋለሁ፡፡ ይህንን አድማጮች ይመሰክራሉ፡፡ የእማማ ጨቤን ክፍተት ለመሙላት በጥንቃቄ ተቀርፀው የገቡት እህታቸው (እትየ ጩጩባ) በጥቂት ሣምንቶች ውስጥ ተወዳጅ መሆን የቻሉት ስላላሰብኩበት አይደለም፡፡  
እውነቱን ለመናገር ጣቢያው በእኔ ስራዎች ላይ እምነት አጥቶ፣ ጥርጣሬ አድሮበት አያውቅም። እኔ የሚጠላ ባህርይ አለኝ ብዬ ባላስብም አልተወደድኩም ብዬም አላዝንም፡፡ እንዴት መወደድ እንደሚቻል ግን አውቃለሁ፡፡
“ድራማው ካለቀ ዓመት አልፎታል” ተብሏል። ለእኔ ሲባል ከሆነ የቆየው ስህተት ነው፡፡ አንድ ግለሠብ ከመላው አድማጭና ሕዝብ አይበልጥም። ዓመት ሙሉ በሕዝብ ጆሮ ላይ ‘ይዘት አልባ’ የሆነ ድራማ ማስተላለፍ የማይመስል ነገር ነው።    ሌላው፡- “ዓመቱን ሙሉ ደብዳቤ እየፃፍን ቆይተናል” ለተባለው ደብዳቤውን ማን እንደተቀበለልኝ አላውቅም፡፡ ሁለት መልስ መስጠት ያልፈለግሁባቸው ደብዳቤዎች በግዳጅ እንደተሰጡኝ አልካድኩም፡፡
“… በነገራችን ላይ ተከታታይነት ያለው ታሪክ የያዘ ድራማ አይደለም፡፡ በየሣምንቱ አዳዲስና የተለያዩ ታሪኮችን ይዞ የሚመጣ ድራማ ነው። ስለሆነም እርሱ ቅን ቢሆንና ቢያስብበት በሦስት ሣምንት ለማጠቃለል የሚያስቸግር ነው ብዬ አላስብም” ብለዋል - የጣቢያው ተወካይ፡፡ ለዚህ ምን መልስ መስጠት ይቻላል? ብዙ ዓይነት ድራማዎች አሉ፡፡ የእኔ ድራማ ምን ዓይነት ባህሪ እንዳለው አድማጭ በሚገባ ይረዳል፡፡ “አዳዲስ ሃሳቦችን ይዞ የሚመጣ ድራማ ነው” ከተባለ በኋላ ‘ይዘት አልባ’ ነው መባሉን አትዘንጉብኝ፡፡
በሀገራችን አዲስ ባህሪ ያለው ረጅምና ተከታታይ ድራማ መሆኑን ማድነቅ ባይቻል በአግባቡ ማወቅ ግን ተገቢ ነበር፡፡ “ቅን ቢሆንና ቢያስብበት…” ለተባለው ለማቋረጥ ምን ቅንነት ያስፈልጋል፡፡ ማሰብ የነበረብኝስ ምንድን ነው?
በበኩሌ ሀሳቤን ለመሰንዘር የተነሳሁት ባሰብኩት መንገድ አልጨረስኩትም ለማለት ብቻ ነው፡፡ ቅንነትን ልጠየቅ የምገባው እኔ አልነበርኩም። ለእያንዳንዱ ነገር መልስ መስጠት ቢቻልም ቃለ ምልልሶቹን ያነበቡ ሰዎች ራሳቸው ስለሚፈርዱ ማብራሪያ ከመስጠት ተቆጥቤያለሁ፡፡
በጣም ያስገረመኝ ነገር ግን አለ፤ ለእኔ መልስ ለመስጠት የተወከሉት የፕሮግራም ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር መሆኑን አስምሩልኝ፡፡ አንድ ድምፅ ይዘው የመጡ የጣቢያው አፍ መሆናቸውን “እኛ” እያሉ በሰጡት ምላሽ ተገንዝቤያለሁ፡፡ ይሁን እንጂ በወቅቱ ስለ ስራው የሚያውቀው ማን ነበር? በስተኋላ የመጡት የአስተያየት ሰጪው የስራ ድርሻ ከዚህ ጉዳይ ጋር ባይገናኝም፣ “እኛ… የድራማው ደራሲ እሱ መሆኑን አናውቅም ነበር። … ያኛው ሰው ደራሲ ነኝ ብሎ መጥቶ ገንዘብ ይወስዳል… ይህንን ሁሉ ያወቅነው ከጋዜጠኝነት ስራው ከፋና ከለቀቀ በኋላ ነው፡፡” የሚያሳፍር ስህተት ብቻ አይደለም፡፡ ስምን አጉድፎ ስብዕናን ዝቅ ለማድረግና ለመወንጀል የታለመ ንግግር ነው። የባለቤትነትን መብት ለማጣረስ የተፈበረከ ውዥንብርና ውንጀላ ነው፡፡
የዚህ መልስ አጭርና ግልፅ ነው፡፡ “ያ-ሰው” የሚባል ፀሐፊና ገንዘብ ወሳጅ አልነበረም። የለፋሁበትን ፈርሜ የምወስደው እኔው ራሴ ነበርኩ፡፡ ይህንን ድራማ ለማስጀመር ከብቸኛ ስፖንሰር አድራጊው ዲኬቲ ኢትዮጵያ ጋር ድራማውን በተመለከተ ብዙ ስብሰባዎች የተካሄዱበትን ድርድር ከሽያጭ ክፍል ሠራተኞች ጋር በመሆን የተወጣሁት እኔ ነኝ፡፡ ሲኖፕሲስ (አፅመ-ታሪክ) አቅርቤ፣ የድራማውን ባህሪ አስረድቼ፣ ድራማው ተደማጭና ተጠቃሚ እንደሚሆኑ አብራርቼ … አየር ላይ ውሏል፡፡ ድራማው ካለቀና አለመግባባት ከተፈጠረ በኋላ በዚህ ዓይነት ስም ማጥፋት በአደባባይ መቅረብ ተገቢ አይደለም፡፡  
ድራማው እንዴት እንደተጀመረ፣ በምን መንገድ እንደተጀመረ፣ ሲጀመር ለትንሽ ጊዜ በብዕር ስም ለምን እንደፃፍኩ… እዛው ቢጠይቁ ኖሮ መልስ ያገኙ ነበር፡፡ በብዕር ስም ፅፌ ክፍያዬን ስቀበል ይኼ የመጀመሪያዬ ነው እንዴ? እኔስ የመጀመሪያው ሰው ነኝ?! አይደለሁም፡፡
ምንም እንኳን ለውስጥ ሰራተኞች ተጨማሪ ክፍያ የማይታሰብ ቢሆንም በጋዜጠኝነት እየሰራሁ ለድራማው ‘በደቂቃ 20 ብር’ ይከፈለኝ የነበረው ልዩ ተሰጥዖን የሚጠይቅ ስራ ስለሆነ ነው፡፡ የመስሪያ ቤቱ  ባልደረባ የመዝናኛ ክፍል ኃላፊ ሆኜ ድራማውን መፃፍና ማዘጋጀት ስጀምር፣ ከደመወዜ በተጨማሪ 1,800 ብር የሚከፈለኝ በጋዜጠኝነት እንጂ በደራሲነት ስላልተቀጠርኩ ነው፡፡ ከ70ኛው ክፍል በኋላ ድርጅቱን ለቅቄ ስወጣ፣ በደቂቃ 80 ብር እንዲከፈለኝ ተስማምተናል፡፡ የመጨረሻዎቹን አስራ ስድስት ወራት አካባቢ ደግሞ ክፍያዬ በደቂቃ 100 ብር ደርሷል፡፡ በጠቅላላ በወር 10 ሺህ ብር ማለት ነው፡፡
ለተሰጥኦ (Talent) ብዙ እንደሚከፈል መንገር አይገባኝም፡፡ ተወካዩ ከፍተኛ ገንዘብ ያሉት ይህንን ከሆነ፣ ውጪ ያለውን ገበያና ክፍያ አያውቁትም ማለት ነው፡፡  
ሠብለ ተፈራ በእማማ ጨቤ ገፀ-ባህሪ ተዋናይነቷ፣ በኋላ ላይ ጭማሪ ተደርጎላት እንኳ በወር የምትወስደው 2 ሺህ ብር አይሞላም፡፡ ሁላችንም ስለ ገንዘብ ሳይሆን ስለ ሙያው ፍቅር እንደምንሰራ ጣቢያው አልተረዳም፡፡
“ድራማው የኛ ነው” ማለት በጣም ያስገምታል፡፡ ጣቢያው በድራማው ላይ ያለውን ባለቤትነት ማወቅ ካስፈለገ… ወጪ ስላወጣበት እና ገንዘብ ከፍሎ ስላሰራ ብቻ ነው፡፡ ይሄ ማለት ደግሞ እስካሁን በተቀረፁት ላይ ሙሉ ባለቤትነት እንዳለው ግልፅ ነው፡፡ መረዳት የሚያስፈልገው ነገር የአንድ ደራሲ የአዕምሮ ፈጠራ ውጤት እንደመሆኑ፣ ቢያስፈልግ ፅሁፉን በሌላ ስቱድዮ በራስ ወጪ በመቅረፅ መጠቀም ይቻላል፡፡
በቀጥታ ያልተዋዋልንበት የስራ ግንኙነት ተቋርጧል፡፡ ለአመታት የተላለፉትን መደምሰስ ከተፈለገ ችግር የለም፡፡ ገፀ-ባህሪያቱን ግን ማክሰም አይቻልም፡፡ የአዕምሮዬ ውጤት የሆኑት ገፀ-ባህሪያት ባለቤት እኔው ብቻ ነኝ፡፡
ጣቢያው ትልቅ ቢሆንም ከዕውነትና ከሕግ በላይ ሊሆን አይችልም፡፡ አሁንም እላለሁ፡- “በእኔ በኩል ድራማውን ፅፌ አልጨረስኩም!!”          

በአሜሪካ ፊላዴልፊያ ውስጥ በሚገኘው የቴምፕል ዩኒቨርሲቲ የህክምና ትምህርት ቤት በማስተማር ላይ የሚገኙት ኢትዮጵያዊው ዶክተር ኤልያስ ሲራጅ፣ በሙያቸው ላበረከቱት ጉልህ አስተዋጽኦ ከአሜሪካ ክሊኒካል ኢንዶክሪኖሎጂስትስ ማህበር የላቀ አገልግሎት ሽልማት አገኙ፡፡
በኢንዶክሪን ህክምናና በአጠቃላይ ጤና መስፋፋት ዘርፍ የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱና በአሜሪካም ሆነ በሌሎች አገራት የሚገኙ በቂ የጤና ግልጋሎት ያላገኙ ህዝቦችን በአመራር ሰጪነት፣ በማያሰልስ ቁርጠኝነት፣ በራዕይ፣ በፈጠራና ተጽዕኖ በሚፈጥር መልኩ በማገልገል፣ ብቃታቸውን ላሳዩ የተመረጡ ባለሙያዎች የሚሰጠው ይህ ሽልማት፣ ባለፈው ሳምንት ላስ ቬጋስ ውስጥ ለዶክተር ኤልያስ ተበርክቷል፡፡
“በቂ የህክምና ግልጋሎት ያላገኙ በርካታ ዜጎች ካሉባት አገር እንደመውጣቴ፣ በቻልኩት መንገድ ሁሉ ህብረተሰቡን የማገልገል ሃላፊነት እንዳለብኝ ይሰማኛል። ማህበሩ በአገሬ በኢትዮጵያና በአሜሪካ የሚኖሩ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ላከናወንኳቸው ተግባራት እውቅና ሰጥቶ ሽልማቱን ስላበረከተልኝ ክብርና ኩራት ይሰማኛል።” ብለዋል ዶ/ር ኤልያስ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ፡፡ ዶ/ር ኤልያስ የህክምና ተማሪዎችን፣ ማህበረሰቡንና በኢትዮጵያ በሚገኙ አምስት የህክምና ትምህርት ቤቶች ውስጥ የነበሩ ተለማማጆችን ተጠቃሚ ያደረጉ ስራዎችን ማከናወናቸውና በአገሪቱ የመጀመሪያውን የኢንዶክሪኖሎጂ ስልጠና ፕሮግራም በማስጀመር ረገድ ቁልፍ ሚና መጫወታቸው ይነገራል፡፡  
በአሁኑ ሰዓት በቴምፕል ዩኒቨርሲቲ የህክምና ትምህርት ቤት በመምህርነትና በዩኒቨርሲቲው የኢንዶክሪኖሎጂ ፌሎውሺፕና የዲያቤቲስ ፕሮግራሞች ዳይሬክተርነት በማገልገል ላይ የሚገኙት ዶ/ር  ኤልያስ፤ ለታካሚዎች ነጻ እንክብካቤ በመስጠት፣ በኢትዮጵያ ያለውን የስኳር በሽታ በተመለከተ ጉልህ ምርምር በማካሄድና በኢትዮጵያና በአሜሪካ የህክምና ተቋማትና ባለሙያዎች መካከል ያለውን ትብብር ለማጠናከር የሚሰሩ ድርጅቶችን በመምራት ይታወቃሉ፡፡
በጎንደር የህክምና ሳይንስ ኮሌጅ ትምህርታቸውን ተከታትለው ከጨረሱ በኋላ፣ ነጻ የምርምርና የስልጠና ዕድል አግኝተው ወደ ጀርመን በማምራት ሊፕዚንግ ዩኒቨርሲቲን የተቀላቀሉት ዶ/ሩ፤ በመቀጠልም ወደ አሜሪካ በማቅናት በክሌቭላንድ ክሊኒክ በተግባር የታገዘ ስልጠና ወስደዋል፡፡
በኢንዶክሪኖሎጂና የውስጥ ደዌ ህክምና የብቃት ማረጋገጫ ያላቸው እኒህ ዶ/ር፣ በተለያዩ የሙያ ማህበራት ውስጥ በአባልነትና በቦርድ አባልነት ንቁ ተሳትፎ በማድረግና በተለያዩ አለማቀፍ መድረኮች ላይ እየተጋበዙ ሙያዊ ንግግሮችን በማቅረብ ይታወቃሉ። በርካታ የህክምና ምርምር ጽሁፎችን ለህትመት ያበቁ ሲሆን በቴምፕል ዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው በመምህርነት ባበረከቱት አስተዋጽኦ የላቀ የመምህርነት ሽልማት ከዩኒቨርሲቲው ተቀብለዋል፡፡

ውድ የጤና አምድ አዘጋጅ:-
የሰላሳ ሁለት ዓመት ሴት ነኝ፡፡ ከስምንት ዓመት በፊት ከመሰረትኩት ትዳሬ ሶስት ልጆችን አፍርቻለሁ፡፡ በትምህርቴ እምብዛም ባለመግፋቴ፣ የእኔ የምለው ቋሚ ሥራ የለኝም፡፡ የቤተሰባችን መተዳደሪያ የባለቤቴ ወርሃዊ ደመወዝ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ኑሮአችን ብዙም የሚያወላዳ አይደለም፡፡ የቤተሰባችን ቁጥር ከዚህ በላይ እንዲጨምር ጨርሶ አንፈልግም፡፡ ስለዚህ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ተጠቃሚ ከሆንን አመታት አስቆጥረናል፡፡ የተለያዩ አይነት የወሊድ መከላከያ ዘዴዎችን ስጠቀምም ቆይቻለሁ፡፡ ባለፈው ታህሳስ ወር በአቅራቢያዬ ወደሚገኘው ጤና ጣቢያ ሄጄ፣ በክንድ ውስጥ የሚቀበረውን የእርግዝና መከላከያ መድኃኒት አስቀብሬ ወደ ቤቴ ተመለስኩ፡፡ ከሶስት ወራት በኋላ በተደጋጋሚ የህመም ስሜቶች ስለአጋጠሙኝ ወደ ሆስፒታል ሄጄ ተመረመርኩ፡፡ ውጤቱም የሶስት ወር ፅንስ በሆዴ መያዜን አረዳኝ፡፡ በእውነቱ ይሄ ለእኔ አምኜ ልቀበለው የማልችለው ትልቅ ዱብዕዳ ነበር፡፡ አስተማማኝነቱ በየሚዲያው የሚነገርለትን የወሊድ መከላከያ መድኃኒት ከትክክለኛው ቦታ፣ በትክክለኛው ጊዜዬ መውሰዴን አውቃለሁ፡፡ የወር አበባዬ መቅረቱን ተከትሎ ሁኔታው ስላሳሰበኝ ወደ ጤና ጣቢያው ሄጄ ጉዳዩን ነግሬአቸው ነበር። የባለሙያዎቹ ምላሽ ግን “የመከላከያው ባህርይ በአንዳንድ ሴቶች ላይ የወር አበባ እንዳይታይ ያደርጋል” የሚል ሆነ፡፡  መከላከያ መድኃኒቱ በክንዴ ውስጥ በተቀበረ በሦስተኛው ወር ግን ሐኪሞች መፀነሴን ነገሩኝ፡፡ አሁን ለዚህ ችግር ተጠያቂው ማነው? የወሊድ መከላከያ እየተባሉ የሚሰጡት መድሃኒቶች ፎርጅድ ናቸው ማለት ነው? አስተማማኙ የወሊድ መከላከያስ የትኛው ነው? እባካችሁ  ባለሙያ አነጋግራችሁ ምላሽ ስጡኝ፡፡
ሰናይት- ከአዲስ አበባ
ውድ በክንድ ውስጥ የሚቀበረውን የእርግዝና መከላከያ መድሃኒት ተጠቅመሽ ያለፍላጎትሽ ያረገዝሽ አንባቢያችን - በመጀመሪያ ድንገት ሳታስቢው ለተከሰተብሽ ችግር ከልብ ማዘናችንን ልንገልፅልሽ እንወዳለን፡፡ ግን እንዲህ ያሉ አጋጣሚዎች በየጊዜው ይከሰታሉ፡፡ የወሊድ መከላከያ መድኃኒቶች መቶ በመቶ እርግዝናን ሊከላከሉ ወይንም ሊያስቀሩ እንደማይችሉ የህክምና ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
  በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የፅንስና የማህፀን ሃኪም የሆኑት ዶክተር አብርሃም ሲሳይ እንደሚሉት፤ ያልተፈለገ እርግዝና እንዳይፈጠር የሚያደርጉና አስቀድሞ ለመከላከል የሚያስችሉ የተለያዩ ሰው ሰራሽና ተፈጥሮአዊ ዘዴዎች አሉ፡፡ ከእነዚህ መካከልም መታቀብ፣ የወር አበባ መምጫ ጊዜን በመቁጠር መጠቀም፣ በግብረ ስጋ ግንኙነት ወቅት የወንዱን የዘር ፍሬ ከሴቷ ብልት ውጪ ማፍሰስ፣ በኮንዶም መጠቀም፣ በየዕለቱ የሚወሰዱ ክኒኖችን መዋጥ፣ መርፌ፣ በክንድ ውስጥ የሚቀበር ሆርሞን፣ በማህፀን ውስጥ የሚቀመጥ ሉፕ መጠቀምና ማህፀን ማስቋጠር (ቲውባል ላይጌሽን) እንዲሁም ለወንዶች የዘር ቱቦን ማስቋጠር (ቫሌክቶሚ) ዋንኞቹ ናቸው። እነዚህን አማራጮች ማንኛዋም ዕድሜዋ ከ15-49 ዕድሜ ክልል ውስጥ ያለች ሴት እንደ ምርጫዋ ልትጠቀምበት ትችላለች፡፡ ሆኖም አንዳንድ ጊዜ ባለሙያዎች ከሴትየዋ የጤና ሁኔታ፣ ከዕድሜዋና ከአቋሟ ጋር ሊስማማ የሚችለውን የወሊድ መከላከያ አይነት ሊያዙ እንደሚችሉ ሃኪሙ ይገልፃሉ፡፡
በአሁኑ ወቅት በአለማችን በአማራጭነት የቀረቡት በርካታ የወሊድ መከላከያ ዘዴዎች፣ የየራሳቸው የጎንዮሽ ጉዳትና የየራሳቸው ችግሮች እንዳሉባቸው የሚናገሩት ባለሙያው፤ ይህ ሁኔታም ከሰው ሰው እንደሚለያይና የጎንዮሽ ጉዳት መጠንም እንደሴቲቱ በሽታን የመቋቋም የተፈጥሮ አቅም ሊለያይ እንደሚችል ያስረዳሉ፡፡
ከወሊድ መከላከያ ዘዴዎች መካከል መቶ በመቶ አስተማማኝ ናቸው የሚባሉት ከግንኙነት መታቀብ፣ የማህፀን ቱቦን ማስቋጠር (ቲውባል ላይጌሽን)፣ የወንድ የዘር ቱቦ ማስቋጠር (ቫሎክቶሚ) ብቻ እንደሆኑ  የሚናገሩት ሃኪሙ፤ ሌሎቹ የመከላከያ ዘዴዎች መቶ በመቶ እርግዝናን ይከላከላሉ ማለት እንደማይቻል ጠቁመዋል፡፡ የእርግዝና መከላከያ መንገዶቹ ከ90-96 በመቶ እርግዝናን ይከላከላሉ ተብሎ እንደሚታመንና የመከላከያ ዘዴዎቹን የምንጠቀምበት ሁኔታና ጥንቃቄ የመከላከል ብቃቱን ከዚህም ሊቀንሱት እንደሚችሉ ተናግረዋል። “ኮንደምን ብንወስድ በአያያዝ ጉድለት ሊበላሽ፣ በአጠቃቀም ችግር ሊቀደድ ወይንም የመከላከል ብቃቱን ሊያጣ ይችላል፡፡ በየዕለቱ የሚወሰዱ ክኒኖችም ለአንድ ቀን እንኳን ቢዘነጉ የመከላከል አቅማቸው በእጅጉ ይቀንሳል” - ብለዋል ሃኪሙ፡፡
በክንድ ውስጥ የሚቀበረው የወሊድ መከላከያ አስተማማኝነታቸው ከ90-95 በመቶ ብቻ ከሆኑት የሚመደብ እንደሆነ የገለፁት ዶ/ር አብርሃም፤ መከላከያውን በትክክልና በአግባቡ ከወሰዱ 100 ሴቶች መካከል ከ5-10 የሚሆኑት እርግዝና ሊከሰትባቸው እንደሚችል ይናገራሉ፡፡
በተለያዩ ምክንያቶች መድኃኒቶቹ ለብልሽት ሊጋለጡ ይችላሉ ያሉት ባለሙያው፤ ከአያያዝ ጉድለትና ከመጠቀሚያ ጊዜ ማለፍ የተነሳ፣ መከላከያዎቹ ከጥቅም ውጪ የሚሆኑባቸው ጊዜያት እንዳሉ ያስረዳሉ፡፡ ይሄኔ የታለመላቸውን አገልግሎት አይሰጡም ይላሉ - ሃኪሙ፡፡  የእርግዝና መከላከያ መድኃኒት እየተወሰደ ወይም ለተወሰኑ ጊዜያት የሚያገለግል ቋሚ የእርግዝና መከላከያ መድኃኒት በሰውነት ውስጥ እያለ በሚፈጠር እርግዝና ፅንሱ ጤናማ ሆኖ የመፈጠሩ ወይንም ጤናማ ሆኖ የመቀጠሉ ሁኔታ አጠራጣሪ እንደሆኑ የጠቆሙት ባለሙያው፤ የአካልና የአዕምሮ ችግር ያለባቸው ህፃናት ሊፈጠሩ አሊያም ፅንሱ ያለጊዜው ሊቋረጥ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
የትኛው የወሊድ መከላከያ ዘዴ በቋሚነት ወሊድን ያስቀራል? የትኛውስ ለምን ያህል ጊዜ ከመውለድ ሊታደገን ይችላል የሚለውን ጉዳይ በጥልቀት ማየትና የመረጡትን የወሊድ መከላከያ ከወሰዱ በኋላ መቶ በመቶ አስተማማኝ ለማድረግ ኮንደምን በተጨማሪነት መጠቀም እንደሚገባ ዶክተር አብርሃም ጨምረው ገልፀዋል፡፡
 - ከአዲስ አበባ
በክንድ ውስጥ የሚቀበረውን የእርግዝና መከላከያ መድሃኒት ተጠቅመሽ ያለፍላጎትሽ ያረገዝሽ ውድ አንባቢያችን በመጀመሪያ ድንገት ሳታስቢው ለተከሰተብሽ ችግር ከልብ ማዘናችንን ልንገልፅልሽ እንወዳለን፡፡ ግን እንዲህ ያሉ አጋጣሚዎች ይከሰታሉ፡፡ የወሊድ መከላከያ መድኃኒቶች መቶ በመቶ እርግዝናን ሊከላከሉ ወይንም ሊያስቀሩ እንደማይችሉ የህክምና ባለሙያዎች በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የፅንስና የማህፀን ሃኪም የሆኑት ዶክተር አብርሃም ሲሳይን እንደሚሉት፤ ያልተፈለገ እርግዝና እንዳይፈጠር የሚያደርጉና አስቀድሞ ለመከላከል የሚያስችሉ የተለያዩ ሰው ሰራሽና ተፈጥሮአዊ ዘዴዎች አሉ፡፡ ከእነዚህ መካከልም መታቀብ፣ የወር አበባ መምጫ ጊዜን በመቁጠር መጠቀም፣ በግብረ ስጋ ግንኙነት ወቅት የወንዱን የዘር ፍሬ ከሴቷ ብልት ውጪ ማፍሰስ፣ በኮንዶም መጠቀም፣ በየዕለቱ የሚወሰዱ ክኒኖችን መዋጥ፣ መርፌ፣ በክንድ ውስጥ የሚቀበር ሆርሞን፣ በማህፀን ውስጥ የሚቀመጥ ሉፕ መጠቀምና ማህፀን ማስቋጠር (ቲውባል ላይጌሽን) እንዲሁም ለወንዶች የዘር ቱቦን ማስቋጠር (ቫሌክቶሚ) የተባሉት ዋንኞቹ ናቸው። እነዚህን አማራጮች ማንኛዋም ዕድሜዋ ከ15-49 ዕድሜ ክልል ውስጥ ያለች ሴት እንደ ምርጫዋ ልትጠቀምበት ትችላለች፡፡ ሆኖም አንዳንድ ጊዜ ባለሙያዎች ከሴትየዋ የጤና ሁኔታ፣ ከዕድሜዋና ከአቋማ ጋር ሊስማማ የሚችለውን የወሊድ መከላከያ አይነት ሊያዙ እንደሚችሉ ሃኪሙ ይገልፃሉ፡፡
በአሁኑ ወቅት በአለማችን በአማራጭነት የቀረቡት በርካታ የወሊድ መከላከያ ዘዴዎች የየራሳቸው የጎንዮሽ ጉዳትና የየራሳቸው ችግሮች እንዳሉባቸው የሚናገሩት ባለሙያው፤ ይህ ሁኔታም ከሰው ሰው እንደሚለያይና የጎንዮሽ ጉዳት መጠንም እንደሴቲቱ በሽታን የመቋቋም የተፈጥሮ አቋም ሊለያይ እንደሚችል ያስረዳሉ፡፡
ከወሊድ መከላከያ ዘዴዎች መካከል መቶ በመቶ አስተማማኝ ነው ሊባል የሚችለው ዘዴ ከግንኙነት መታቀብ፣ የማህፀን ቱቦን ማስቋጠር (ቲውባል ላይጌሽን)፣ የወንድ የዘር ቱቦ ማስቋጠር (ቫሎክቶሚ) ብቻ መሆናቸውን የሚናገሩት ሃኪሙ፤ ሌሎቹ የመከላከያ ዘዴዎች መቶ በመቶ እርግዝናን ይከላከላሉ ማለት እንደማይቻል ጠቁመዋል፡፡ የእርግዝና መከላከያ መንገዶቹ ከ90-96 በመቶ እርግዝናን ይከላከላሉ ተብሎ እንደሚታመንና ይህ አሃዝ የመከላከያ ዘዴዎቹን የምንጠቀምበት ሁኔታና ጥንቃቄ የመከላከል ብቃቱን ከዚህም ሊቀንሱት እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡ “ኮንደምን ብንወስድ በአያያዝ ጉድለት ሊበላሽ፣ በአጠቃቀም ችግር ሊቀደድ ወይንም የመከላከል ብቃቱን ሊያጣ ይችላል፡፡ በየዕለቱ የሚወሰዱ ክኒኖችም ለአንድ ቀን እንኳን ቢዘነጉ የመከላከል አቅማቸው በእጅጉ ይቀንሳል” - ብለዋል ሃኪሙ በምሳሌ ሲያስረዱ፡፡
በክንድ ውስጥ የሚቀበረው የወሊድ መከላከያ አስተማማኝነታቸው ከ90-95 በመቶ ብቻ ከሆኑት የሚመደብ እንደሆነ የገለፁት ዶ/ር አብርሃም፤ መከላከያውን በትክክልና በአግባቡ ከወሰዱ 100 ሴቶች መካከል ከ5-10 የሚሆኑት እርግዝና ሊከሰትባቸው እንደሚችል ይናገራሉ፡፡
በተለያዩ ምክንያቶች መድኃኒቶቹ ለብልሽት ሊጋለጡ ይችላሉ ያሉት፡፡
ባለሙያው፤ ከአያያዝ ጉድለትና ከመጠቀሚያ ጊዜ ማለፍ የተነሳ፣ መከላከያዎቹ ከጥቅም ውጪ የሚሆኑባቸው ጊዜያቶች እንዳሉ ያስረዳሉ፡፡ ይሄን የታለመላቸውን አገልግሎት አይሰጡም ይላሉ - ሃኪሙ፡፡  የእርግዝና መከላከያ መድኃኒት እየተወሰደ ወይም ለተወሰኑ ጊዜያት የሚያገለግል ቋሚ የእርግዝና መከላከያ መድኃኒት በሰውነት ውስጥ እያለ በሚፈጠር እርግዝና ፅንሱ ጤናማ ሆኖ የመፈጠሩ ወይንም ጤናማ ሆኖ የመቀጠሉ ሁኔታ አጠራጣሪ እንደሆኑ የጠቆሙት ባለሙያው፤ የአካልና የአዕምሮ ችግር ያለባቸው ህፃናት ሊፈጠሩ አሊያም ፅንሱ ያለጊዜው ሊቋረጥ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
የትኛው የወሊድ መከላከያ ዘዴ በቋሚነት ወሊድን ያስቀራል የትኛውስ ለምን ያህል ጊዜ ከመወለድ ሊታደገን ይችላል፡፡ የሚለውን ጉዳይ በጥልቀት ማየትና የመረጡትን የወሊድ መከላከያ ከወሰዱ በኋላ መቶ በመቶ አስተማማኝ ለማድረግ ኮንደምን በተጨማሪነት መጠቀም እንደሚገባ ዶክተር አብርሃም ጨምረው ገልፀዋል፡፡

“ዳኞች አጥፊን ባህር ውስጥ ይጥሉታል፡፡
ከሰመጠ ንፁሕ ነው ይሉታል፡፡
ካልሰመጠ ጠንቋይ ነው ብለው ይቀጠቅጡታል፡፡”
                 - የግብፅ ፍርድ
አንድ የጥንት የኢትዮጵያ ጀግና ወደ ጦር ሜዳ ሊሄዱ እየተዘጋጁ ሳሉ፤ ሠፈር - ጐረቤቱ መጥቶ የበኩሉን የስንብት፣ የድጋፍና የማበረታታት መንፈስ ያላብሳቸዋል፡፡
“እርሶ የገቡበት ጦርነት መቼም ሁሌ ድል ነው፡፡ ሁሌ ጉሮ ወሸባዬ ነው! ሁሌ ምሥራች ነው” አሉ አንድ ጐምቱ የሰፈሩ ሰው፡፡
“መጠርጠሩስ!” ይላሉ ሌላው፡፡
ቀጠሉ ሌሎቹ፤
“እንዲያው እርሶ ጦር ሜዳ ታይተው ጠላት እፊትዎ ሊቆም? አይደረግም!”
“እረ ጠላት አይደለም ሣር ቅጠሉ ያረግዳል! የጌቶችን የሚያህል ጀግንነት እግር እስኪዝል ቢሄዱ አይገኝምኮ!”
“እረ በዓለም በታሪክ ሲነገር የሰማነውም እሳቸውን የሚያህል ጀግና የለም!”
በመጨረሻ አንድ ትንሽ ልጅ፤ “አጐቴ አሁን ሁሉንም ተዉትና ንግግር አድርጉልንና ሂዱ”
ሁሉም፤ “ይናገሩ! ይናገሩ” አሏቸው፡፡
“እስኪ እንዳፋችሁ ያድርግልኝ፡፡ እኔ ስገባበት ውስጡ ሆኜ የማደርገውን አላውቀውም። ያኔ በቦታው የማደርገውን አሁን በንግግር መግለፅ አይሆንልኝም፡፡ እንዲያው ‘ይቅናህ!’ ያላችሁኝ ምርቃት ብቻውን ብዙ ስንቅ ይሆነኛል፡፡ የጣሊያን ጥላቻዬ ሁለተኛ ስንቄ ነው። ሌላውን ስንመለስ እናወራለን” ብለው ሁሉን ተሰናብተው ወጡ፡፡ የሚሸኟቸው፤ መንገድ ድረስ ሸኝተዋቸው ተመለሱ፡፡
ጀግናው ሲደርሱ፤ ጦር ሜዳው ቀውጢ ሆኗል፡፡ ከዛም ከዚህም ወገን፣ ሰው ይረፈረፋል። ጀግናውም እንደገቡ ጥይቱን እንደጉድ ያንጣጡት ጀመር፡፡ ጦርነቱ በጣም ተፋፋመ፡፡ ጀግናው እጅግ በርካታ ጠላት ረፈረፉ፡፡ ግን አልረካ አሉ፡፡
አልረካ ያሉበት ምክንያት “የምገለው ጠላት ሁሉ ራሱ ፈረንጅ በሠራው ጥይት ነው እየወደቀ እማየው፡፡ ከዚህ ደቂቃ በኋላ ግን፤ ፈረንጅ በሰራው ጥይት አልገድልም፡፡ የራሴን እጅ ነው መቅመስ ያለበት” አሉ፡፡ ጠመንጃቸውን ወርውረው በጨበጣ ገቡበት፡፡ “ተዉ ጌታዬ ሌላው በጥይት ይመታዎታል!” ቢባሉ፤ “በጭራሽ! እጄን ይቅመስ!” አሉ፡፡ በኋላ ግን፤ ሰው ናቸውና ወደቁ፡፡
*       *       *
በስሜታዊነት፣ በዕልህና በግትርነት የትም አንደርስም፡፡ ግትርነት ለማመዛዘን እድል አይሰጥም፡፡ ግራ ቀኝ ለማየት ጊዜ አይሰጥም፡፡ የአብዛኞቻችን ዓይነተኛ ችግር ከስሜታዊነት የሚመነጭ ኃይለኛ ግትርነት ነው፡፡ ግትርነት እያለ ዲሞክራሲ ይፋፋል ማለት ደግሞ ዘበት ነው፡፡ ከግትርነት በላይ ቃል ቢኖር እንጠቀምበት ነበር፡፡ (እንግሊዞች የግትር ግትር ለማለት “Stiff upper lip” የሚሉት አይነት መሆኑ ነው፡፡) ሌላ ብዙ ቅፅል፣ ብዙ ጭራና ቀንድ እየቀጠልን ለግትርነታችን ምክኑ ያ ነው እንበል እንጂ አብረን ያደግነውን ግትርነት የሚያክል ባላንጣ የለንም፡፡ እኔ ያልኩት ብቻ ነው ትክክል ማለት፤ ግትርነት ነው፡፡  ጠላቴ ያለበት አንድ ጥግ፣ እኔ ያለሁት ሌላ ፅንፍ፣ ብሎ መፈጠምም ግትርነት ነው፡፡ ሀብትን ማከማቸት አልጠግብ ማለትና ምንም ጥቅም ላይ ባላውለውም በእኔ እጅ ይሁን፤ ማለትም ግትርነት ነው። “ሀብት ሲሰበስብ ከርሞ ሳይጠቀምበት የሚቀር በርሀብ ይሞታል” የሚል የአፍሪካውያን አባባል ይሄንኑ ይነግረናል፡፡ በአንፃሩ ሁሌ በማባከን መለከፍም ግትርነት አለበት፡፡ “አባካኝነት ለድህነት ይዳርጋል፡፡ ድህነት፤ ዕውነተኛ ድህነት፣ ሞት ነው” (የኦዞ ዘፈን) የሚለውንም ልብ ይሏል፡፡ በሀገራችን ጉዳይ ግልፅ በግልፅ እንነጋገር ሲባል በፍፁም እምቢኝ ብሎ ድርቅ ማለትም ግትርነት ነው፡፡
በአንድ ወቅት በብሾፍቱ “ገፅ ለገፅ” የሚባል የብሾፍቱን የውሃና ትምህርት ችግር የሚያይ ፕሮግራም ላይ፤ ባንድ በኩል ህዝብ፣ በሌላ በኩል ከንቲባውን ጨምሮ የከተማይቱ ባለስልጣናት የታደሙበት፤ አስገራሚ ስብሰባ ተካሂዶ፤ ከንቲባው የሚገርም ግልፅ ንግግር አድርገው ነበር፡- “መንግስት ባላችሁዋቸው ችግሮች አንጻር የበኩሉን ድርሻ ይወስዳል፡፡ ህዝቡስ? ለመሆኑ ውሃ ሲፈስ ብታዩ የምትጠቁሙ እነማን ናችሁ? አለቃ ሲሰርቅ እምቢ አይደረግም (No!) የምትሉ እነማናችሁ? የሚሰረቀው ’ኮ የራሳችሁ ሀብት ነው! እንደዛ ከቀጠለኮ ብሾፍቱ የጥቂት ሰዎች ብቻ ናት ማለት ነው! ከህዝብ የማያስፈልገን ሰው የለም! አቅም ትሆኑናላችሁ! እንደምታውቁት፤ ያደግንበት አካባቢ ለዕድገት አመቺ አልነበረም። አይፈቅድም ነበር፡፡ መለወጥ አለበት፡፡ አንዱ አንዱን አይርገም! ዛሬ ማይክሮ -ሰከንድ ሚሊዮን ያሳጣል፡፡ እንፍጠን፡፡…” ብለዋል፡፡
እርስ በርስ የመረጋገም ልክፍትም ግትርነት ነው ፡፡ ፊት ለፊት በመወያየት የጋራ መፍትሄ ማምጣት ያዋጣናል፡፡ የሆነውን ለመሸፋፈን ከመሞከር በግልፅ ማፈንዳት ወደፍሬ ያደርሰናል!
ለግልፅነትም፣ ለተጠያቂነትም፣ የሁሉ እናት - ክፍል ለሆነው ዲሞክራሲም፤ ዞሮ ዞሮ መጠቅለያው ጊዜ ነው፡፡ ለጊዜ በመገዛት ጊዜን መግዛት ነው ጥበቡ፡፡ ጊዜን ካወቁ (The right timing) እንዲሉ ስኬት ቅርብ ነው፡፡ መቼ ማፈግፈግ እንዳለብህ ዕወቅ - ጊዜው አልበሰለምና። መቼ አጥብቀህ መምታት እንዳለብህ ዕወቅ - ካረፈድክ ትጠቃለህና፤ ይላሉ ፀሀፍት፡፡ የመጨረሻዋን ሶስት ደቂቃ ተጠቅምባት (Last three minutes እንዲል የቅርጫት ኳስ ህግ)፡፡ እንደጥንታዊው የግብፅ ፍርድ ‹ውሃ ውስጥ ልትጣል ትችላለህ - ከሰመጥክ ንፁህ ልትባል፤ ካልሰመጥክ ጠንቋይ ነው ተብለህ ልትቀጠቀጥ!!› ጊዜን አለማወቅ ቅጣቱ ብዙ ነው። ይህን ጉዳይ፤ መረርና ከረር ያለው አገርኛ ተረት በወጉ ይደመድመዋል፡-
“ቀን ሲሰጥ የውሻ ደም ትበቀላለህ፤
ቀን ሲከለክል ያባትህን ደም ትተዋለህ!”

የአልባሳት፣ የጨርቃጨርቅ እና የእግር ሹራብ አምራቾችንና ነጋዴዎችን በአንድነት ያሰባስባል የተባለ የንግድ ሣምንት ከነሐሴ 11-14 2006 ዓ.ም በአሜሪካን ላስቬጋስ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ ገለፁ፡፡
አለማቀፍ የፋሽን ድርጅቶች ይሳተፉበታል የተባለው የንግድ ሣምንት አለማቀፍ የፋሽን ማህበረሰቡን በማቀራረብ ሰፊ ግብይት ይፈፀምበታል ተብሎ እንደሚጠበቅ የዝግጅት አስተባባሪ የ251 ኮሚኒኬሽንና ማርኬቲንግ ማኔጅንግ ዳይሬክተር አቶ አዲስ አለማየሁ ገልፀዋል፡፡
አክለውም በዝግጅቱ ላይ የኢትዮጵያ አልባሣት፣ ጨርቃጨርቅ እና ጫማ አምራቾች እንደሚሳተፉና ከ100 ሃገራት ከተውጣጡት የንግድ ሳምንቱ ተሳታፊ ኩባንያዎች ጋር የረዥም ጊዜ ግንኙነት ይፈጥራሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል፡፡
የንግድ ትርኢቱ ከ6 ሺህ በላይ የሚሆኑ የምርት አይነቶች የሚቀርቡበት መሆኑ የተገለፀ ሲሆን፤ የ251 ኮሚኑኬሽን ተባባሪ የሆነው ማጂክ ኢንተርናሽናል የአለማቀፍ ቢዚነስ ኃላፊ ቦብ በርግ በበኩላቸው በዘርፉ የተሰማሩ የኢትዮጵያ ፋብሪካዎች ከንግድ ትርኢቱ ተጠቃሚ ይሆናሉ ብለዋል፡፡
በንግድ ትርኢቱ ላይ ይሳተፋሉ ተብለው ለሚጠበቁ የኢትዮጵያ የቆዳ ኢንዱስትሪ ማህበር፣ ለኢትዮጵያ ጨርቃ ጨርቅ አምራች ማህበራት እና ለUSAID እንዲሁም ለአሜሪካ ኤምባሲ የፕሮግራም አዘጋጆች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡  

በሶሻል ሚዲያ ላይ ስላንቺ የተፃፉ ነገሮች አሉ፡፡ ምንድነው ነገሩ?
በ”ቃል ኪዳን” መጽሔት ላይ የወጣውን መረጃ አይተሽ ይሆናል፡፡ መጽሔቱ ይዞት የወጣውን መረጃ ተመርኩዞ ነው ሶሻል ሚዲያውም የስም ማጥፋት ውንጀላውን የቀጠለው፡፡ አስገራሚው ነገር መጽሔቱ ከእኔ ጋር ያደረገው ቃለ መጠይቅም ሆነ የተለዋወጥነው መረጃ የለም፡፡ ዘገባው ሲወጣ፣ እኔ ከነአካቴው አዲስ አበባ አልነበርኩም፤ ለስራ አዳማ ሄጄ ነበር፡፡ የፋሲካን በዓል እንኳን ከቤተሰብ ጋር አላሳለፍኩም፡፡
በአሜሪካና በእስራኤል ኮንሰርት ለማቅረብ ከፕሮሞተሮች ጋር ጨርሼ፣ ኤምባሲ ለመግባት በዝግጅት ላይ ነበርኩ፡፡ የአዳማ ስራዬን ጨርሼ፤ ፕሮሞተሬ ጋር ስደውል አስደንጋጭ መልስ ሰጠኝ፡፡
ምን አለሽ?
መፅሄቱ ያወጣውን ዘገባ ነው የነገረኝ፡፡ የአዕምሮ ጤንነቴ እንደታወከና ሰሜን ሆቴል አካባቢ የሚገኘውን ቤቴን ለቅቄ፣ ኦሎምፒያና ላፓሪዚያን አካባቢ እንደምውል ፅፎ ከእነፎቶዬ አውጥቶታል፡፡ ከአንድ ወር ስራ በኋላ ተመልሼ አዲስ አበባ ስመጣ፣ ጉዳዩን ለብሮድካስት ኤጄንሲ አመለከትኩ፡፡ ብሮድካስት ኤጀንሲም መፅሄቱ ማስተባበያ እንዲያወጣ ነገረው። ማስተባበያው ግን አልተሰራም፡፡ ይሄንንም አሳወቅሁኝ፡፡ ወሬው ቤተሰቤን ሁሉ ግራ አጋብቶ ነበር፡፡ እናቴ አሁንም ድረስ ታማ ተኝታለች። እኔ ቤተሰብ የማስተዳድር ሰው ነኝ፣ ሌሊት ሰርቼ ቀኑን ሙሉ የምተኛ ሰው አይደለሁም፡፡ ይሄው መጽሔት ድምፃዊ ጎሳዬ ተስፋዬ ላይም የስም ማጥፋት ውንጀላ ፈጽሞበታል፡፡ ለጎሳዬ እንደውም ማስተባበያ ሰርተውለታል፤ ያውም ከእኔ በኋላ ነው ለማንኛውም በመፅሄቱ ላይ ክስ ለመመስረት ሂደቱን ጀምሬአለሁ፡፡
የውጭ አገር ኮንሰርቱ ምን ደረሰ?
የተናፈሰው ወሬ ሀገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን ውጭ አገርም ደርሷል፡፡ አንድ ፕሮሞተር ደግሞ ለኮንሰርት ሰው ሲወስድ፣ ታሪኩን በደንብ አጥንቶ ነው እንጂ ዝም ብሎ ከፍተኛ ብር አውጥቶ ሪስክ አይወስድም፡፡ ፕሮሞተሬ ኤምባሲ ለቪዛ ከመግባቴ በፊት ማድረግ ያለብኝን ነገር እንደሚነግረኝ ገልፆልኝ ነበር፡፡ በኋላ ግን ከእኔ ጋር ያሰበውን ኮንሰርት ሰርዞ፣ ከሌላ ድምፃዊ ጋር መዋዋሉን ነገረኝ፡፡ ምክንያቱን እንዲነግረኝ ጠይቄው ነበረ፡፡ ለጊዜው ትቼዋለሁ ብቻ ነው ያለኝ፡፡
ከዚህ ቀደም የውጭ አገር ኮንሰርቶች ሰርተሻል?
አረብ አገራት በሙሉ የቀረኝ የለም፡፡ አሜሪካና እስራኤል ግን የመጀመሪያዬ ጊዜ ነበር።
እስካሁን ስንት አልበሞችን ሰርተሻል?
“ሀቢቢ” የሚለውን ሙሉ አልበሜን ከሰራሁ በኋላ፤ አሁን ሁለተኛ ስራዬን ማስተሩን ጨርሻለሁ፣ እነ ይልማ ገብረአብ፣ መሰለ ጌታሁን፣ ሱራፌል አበበ፣ አዱኛ ቦጋለ የተሳተፉበት ሙሉ ስራ አልቆ ተቀምጧል፡፡ ምክንያቱም አሁን ሙዚቃ ቤቶች የኮፒራይት ጉዳይ ስለሚያሳስባቸው ስራዎችን አይቀበሉም።
አሁን ምን እየሰራሽ ነው ታዲያ?
አንድ የሱዳን ካምፓኒ ከሱዳን አገር መጥቶ፣ ሙሉ የሱዳንኛ ዘፈን ከፍሎ አሰርቶኛል፡፡
ምን ያህል ተከፈለሽ?
ለአስራ አንድ ዘፈኖች፤ አስራ ሶስት ሺህ ብር ነው የከፈሉኝ፡፡  ከእነ ባንዳቸው መጥተው እዛ አገር የሚወደዱ ሱዳንኛ ዘፈኖችን አሰርተውኛል።  
ከሙዚቃ ስራ ውጪ በምን ትተዳደሪያለሽ?
እኔ የስምንት ቤተሰብ አስተዳዳሪ ነኝ፤ የምኖረው ከእናቴ ጋር ነው፡፡ “ሀቢቢ ባንድ” የሚባል የራሴ የሙዚቃ ባንድ አለኝ፡፡ አሁን ለጊዜው ስራው ስለቆመ ንግድ ጀምሬያለሁ። ኮስሞቲክሶችና ሌሎች የመዋቢያ ቁሳቁሶችን ይዤ ባዛር ላይ እሳተፋለሁ፡፡ አሁን ሙዚቃ ብዙም አዋጪ ስላልሆነ፣ ባለኝ አቅምና ችሎታ ወደ ንግዱ እየገባሁ ነው፡፡ በቅርቡ “ጥራኝ አዳማ” የሚል ነጠላ ዜማ ለቅቄያለሁ። ለመኖርም ለመስራትም የማስበው አዳማ ነው፡፡ አሁን ጥሩ ስሜት ላይ ስላልሆንኩ ትንሽ እረፍት እፈልጋለሁ፡፡ ቤተሰቤን ይዤ። በተሰራው ስራ በጣም ነው የከፋኝ፡፡ ስሜን ያጠፉት ኢትዮጵያዊነት የማይሰማቸው ግለሰቦች ናቸው። እኔ ፍፁም ጤነኛና የስራ ሰው መሆኔን ማንም ኢትዮጵያዊና አድናቂዎቼ በዚህ አጋጣሚ እንዲያውቁልኝ እፈልጋለሁ፡፡