Saturday, 28 June 2014 10:29

ለአልሸባብ ወደ አክራሪነት መለወጥ ኢትዮጵያ ተጠያቂ ናት መባሉን መንግስት አጣጣለ

Written by 
Rate this item
(5 votes)

አልሸባብ ፅንፈኛ ድርጅት የሆነው ኢትዮጵያ ወደ ሶማሊያ ጦር ሰራዊት በማዝመቷ ነው በማለት ኒው አፍሪካን መጽሔት የዘገበ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ የአልሸባብ ታጣቂዎች አፍጋኒስታን ሄደው ስልጠና የወሰዱት ገና ድሮ ነው በማለት ዘገባውን አጣጣለ፡፡
አልሸባብ በዩጋንዳ እና በኬኒያ በፈፀማቸው ጥቃቶች ሳቢያ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ውስጥ ስጋት መፍጠሩን በመጥቀስ ነው መጽሔቱ አልሸባብን የሚመለከት ሰፊ ዘገባ ያቀረበው፡፡
ዜጐች በሄዱበት ሁሉ በፍተሻ መከራቸውን እያዩ እንደሆነ መጽሔቱ ገልፆ፤ በኬኒያ እና በዛንዚባር የቱሪዝም ገቢ ክፉኛ አሽቆልቁሏል፤ የኬኒያ መንግስት የመከላከያ በጀቱን ለመጨመር ተገዷል፡፡
አልሸባብ ወደ አክራሪነት የተለወጠው፤ በ2006 የኢትዮጵያ መከላከያ ሀይል በአሜሪካ ድጋፍ ወደ ሶማሊያ  በመዝመቱ ነው ሲልም መጽሔቱ ኢትዮጵያን ተጠያቂ አድርጓል፡፡ በመጽሔቱ የቀረበው ውንጀላ መሰረተ ቢስ ነው ሲል ያጣጣለው የኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ፤ ኢትዮጵያ አልሸባብን አዳከመች እንጂ ወደ አክራሪነት እንዲለወጥ አላደረገችም በማለት ሰፊ ምላሽ ሰጥቷል፡፡ እንዲህ አይነቱ ውንጀላ በተደጋጋሚ የሚሰነዘር መሆኑን ሚኒስቴሩ ጠቅሶ፤ ነገር ግን ምንም አይነት ማስረጃ የማይቀርብበት መሰረተ ቢስ ውንጀላ ነው ብሏል፡፡
በሶማሊያ እየገነነ የነበረው የእስልምና ፍርድ ቤቶች ምክር ቤት በኢትዮጵያ ጦር በመመታቱ አይደለም አልሸባብ ያቆጠቆጠው፡፡ እንዲያውም የፍርድ ቤቶች ምክር ቤት ሶማሊያ ውስጥ እየተንቀሳቀሰ በነበረበት ወቅትና ከዚያ በፊት ወደ አፍጋኒስታን ለስልጠና ተልከው በነበሩ ቡድኖች ናቸው አልሸባብን የመሰረቱት ብሏል ሚኒስቴሩ፡፡
የእስልምና ፍርድ ቤቶች ህብረት ኢትዮጵያ ላይ ጦርነት አውጆ እንደነበር ሚኒስቴሩ አስታውሶ፤ ያንን ጥቃት ለመከላከል የተወሰደው ወታደራዊ እርምጃ ተገቢ ነበር ብሏል፡፡
ወታደራዊ እርምጃ የወሰድነውም፤ አለም አቀፍ ህጐችን በማይጥስ መንገድና ከሶማሊያ የሽግግር መንግስት በተደረገልን ግብዣ ነው ብሏል - ሚኒስቴሩ፡፡  የኢትዮጵያ ጦር ሶስት አመት ሶማሊያ ውስጥ በቆየበት ወቅት ምንም አይነት ድጋፍ ከአሜሪካን እንዳልተሰጠውም ጠቅሷል፡፡

Read 2796 times