Saturday, 19 January 2013 14:31

ለምን ይዋሻል? በስመ-ልደቱ

Written by  በዶ/ር ፍቃዱ አየለ
Rate this item
(2 votes)

ነገር ዜሮ፣ እንደ ተለመደው በዓለ-ገናው ሰበብ ሆነልኝና ርቄያት ወደ ከረምኩት ዋናይቱ ከተማ አዲስ አበባ ከተፍ አልኩኝ (ከስራ አድራሻዬ ከተራራማይቱ ገጠራማ ቀበሌ ከየተቦን) እንዲህ ከረም እያልኩ ብቅ ስል መዲናይቱም የግንባታ ብቅል አበቃቅላ ታስገርመኛለች፡፡ እደጊ ሸገር እደጊ፡፡ ‹‹እደጊ ግን ደግሞ ሰውም በመልካም የሚያድግብሽ ከተማ ያድርግሽ›› ማለቴም የተለመደ ነው፡፡ታዲያ መዲናይቱን የተራራቅኳትን ያህል አዲስ አድማስ ጋዜጣንም እንዲሁ ተራርቂያት መክረሜ ገራሚ የሚሆን አይመስለኝም፡፡

ታዲያ አውደ-ገናው ግድ ብሎኝ ወደ መዲናይቱ አዲስ አበባ ብቅ ስል፣ቀነ- ቅዳሜ በሆነ አዚምኛ ሰበብ ስልብ ብላ ከእጄ ካላፈተለከች በቀር፣‹‹የቅዳሜ ውበት›› የምትመስለኝ አዲስ አድማስ ጋዜጣ እንድታመልጠኝ አልሻም፡፡ እናም በዚህ ሳምንት ‹‹ተወዳጅ ናት›› የምላት ጋዜጣ በእጄ ገባች፡፡ ገና አንድ ገፅ ስገልጥ ‹‹ታህሳስ የበርካታ ዓማልክት የልደት ቀን›› በሚል የገደፈ ርዕስ፣ ግድፈታምነቱ የጠነነ የገናውን በዓል ተተግኖ የተዘለጎሰ መጣጥፍ ገጠመኝ፡፡ ርዕሱ የታህሳስን ‹‹ወር››ነት ዘንግቶ ‹‹ቀን›› እያለ መጮሁ ሲደንቀኝ፣ የ‹‹ቅጥፈቱንም›› የ‹‹ልኩንም›› አማልክት መደበላላቁ መፈናፈኛ ያሳጣኝን የጊዜ ጉልበት ተገዳድሬ ብዕር እወድር ዘንድ ግድ አለኝ፡፡ ይሄ መጣጥፍ እውነተኛውን ‹‹ባለ ልደት›› ከሃሰተኞቹ ልደተኞች ጋር ቀያይጦ ከማላቆጡ ብዛት፣ለየዋህ ታዳሚ መነሾ እሳቤው ስለ ዓመት በዓለተኞቹ አማልክት ለመዘከር የተጣጣረ ሊመስል ይችል ይሆናል፡፡ ጠጋ ብሎ ላተኮረበት ግን ዋናው ኢላማ ‹‹ታህሳስ ልደቴ የሚሉ ዓማልክትን የምታመልኪ ሁሉ የምታመልኪው አፈ ታሪክ መሆኑን ልንገርሽ›› ለማለት መሆኑ ብዙም አያመራምር፡፡ ስለሆነም ምላሽ ቀርቅቦ በአዲስ አድማስ በኩል ብቅ የማለቱ አስፈላጊነት ታየኝ፣እናም ብቅ አልኩ፡፡

የተለቋቆጠው ጭብጥ ሰፊነት በአንዲት መጣጥፍ የመጠናቀቁ ጉዳይ ቢያጠራጥረኝም እንደሚኖረኝ ጊዜ መጠን ጉዳዩን ማብራራት ተገቢ ነው ብዬ ብዕር ወረቀቴን ሸክፌአለሁ፡፡ የታመንኩበት ቅዱስ አምላክ የእናንተንም የእኔንም ጊዜ ይባርክልና፡፡ እንግዲህ የእርግጠኝነቴ ፍርጣሜ ሰበቡ በእምነት የተገለጠልኝ እውነት ህያውነት ቢሆንም፣በእምነት አልባነት ድንዳኔ በገነገነ ብዕር መንፈሳዊውን ሃቅ በ‹‹ዓለማዊ›› ሽሙጥ ለጎሰመ ፀሃፊ፣ከዛው ከሰፈሩ የተመዠረጠን ትክክለኛ ምንጭ ማሳየት እና ለጋዜጣይቱ ታዳሚ ደግሞ የቅብጥርጥሮሹን አስመሳይነት በእውነተኛው ታሪክ መገላለጥ ወደድኩኝ፡፡ ለእኔ እምነት በቂዬ ቢሆንም ከእምነት ወዲያ ማዶ ያሉት በተበራረዘ ታሪክ ሰበብ በእምነት በሚገኝ ህይወት ላይ እንዳይዘብቱ እውነተኛውን የታሪክ ምንጭ መምዘዝ የውዴታ ግዴታዬ አደረኩት፡፡‹‹እንዴት? እንዴት?›› ለሚል ‹‹እንደተለመደው›› ነው መልሴ፡፡ ነገር አንድ ፣ ደረቅ ምንጭ የታህሳስ ሃያ ሰባቱ ስም-አልባ ፀሃፊ ‹‹በየአገሩ እና በየዘመኑ ከድንግል የተወለዱ፣ የአምላክ ልጅ አምላክ ተብለው የሚመለኩ ቸር ጌቶች፣ ስማቸው ቢለያይም ታሪካቸው በጣም ተመሳሳይ ነው፡፡ በተለይ የሆረስና የኢየሱስ፣ የሚትራና የኢየሱስ ተመሳሳይነት በጣም ሰፊ በመሆኑ ለበርካታ ምዕተ አመታት ሲያወዛግብ ቆይቷል›› ብለዋል፡፡ ከዚህ አባባላቸው ልብ ሊባል የሚገባው ሃቅ ኢየሱስ ላይ መተኮሩ ነው፡፡ ሆረስም፣ ሚትራም ከደረቅ ምንጭ በመነጨ የለበጣ እይታ የተገናዘቡት ከኢየሱስ ጋር ነው፣ ምክንያቱ ደግሞ በስመ ልደቱ ተመካኝቶ ኢየሱስን ‹‹የተኮረጀ አምላክ›› ለማድረግና ታሪኩን ለመደፍጠጥ መሆኑ አይጠረጠርም፡፡ ሆኖም ሚትራም ይሁን ሆረስ ከኢየሱስ ጋር ያላቸው ተመሳሳይነት በጣም ሰፊ ሳይሆን እጅግ መንማና ነው፡፡ የኢየሱስን እውነተኛ አምላክነት ላለመቀበል በፀሃፊው እይታ በ ‹‹ዚጊየስት ሙቪ›› ለስክሪፕትነት ከዛም ከዚህም ቦጨቅ ቦጨቅ ተደርጎ በተለጣጠፈ የታሪክ ቡቱቶ ላይ መመስረት ለጊዜው እንቅልፍ ሊሰጥ ቢችልም ዘላቂ መልስነቱ ግን የከቸረረ ነው፡፡

አካሪያ፣ ጀራልድ ማሲ፣ ቶማስደን፣ ጀምስ ፍሬዘር፣ ፍሬክ እና ጋንዲ የፃፏቸው መፅሃፍት የታህሳስ ሃያ ሰባቱ ፀሃፊ ‹‹እንደተጠቀሙት›› ለጠረጠርኩት የዚጊየስት (zeitgeist) ትዕይንተ ትሪት ስክሪፕት ዋና ምንጮች ናቸው፡፡ እነዚህም ጊዜ የተፋቸው ብቻ ሳይሆን በ ‹‹ይሆን ይሆናል›› ላይ ተደላድለው ሲያበቁ ብዙ ታሪካዊ ማመሳከሪያዎችን እነሱ ሊሉ የፈለጉትን ስላላሉላቸው ወዲያ አሽቀንጥረው ጥለው ከደረቅ ምንጭ ያነቀሩ ረጋ-ሰራሽ ስራዎች ናቸው፡፡ እነሱም ቢሆኑ በዋቢነት በታህሳስ 27 ፀሃፊ ሊጠቀሱ እምነት ያልተጣለባቸው በመሆኑ ፀሃፊው ‹‹ለምን ይዋሻል?›› ይባሉ ዘንድ ሰበብ ሆኗል፡፡ ታሪኩን በራሳቸው ስልጣን እንዳሻቸው አርከፍክፈውታልና ‹‹ለምን ይዋሻል?›› ማለታችን አግባብነቱ ያስማማን ይመስለኛል፡፡ ጽሁፉ ጭርቅ ጭርቅ የሚል ስለሆነ ከደረቅ ምንጭ መቧጠጡን ገና ሳይጠየቅ ያትታል፣ መጠየቁ ባይቀርም፡፡ ታዲያ በጭርቅርቅታው መነሻ ላይ ‹‹የሆረስ ታሪክ በአጭሩ ይሄን ይመስላል›› ብለው ያስቀመጧት ቁምጥምጥ ያለች ‹‹ታሪክ››፣ የሆረስን አፈታሪክ አትመስልም፡፡ አትመስልም ብቻ ሳይሆን ‹‹ሆረስ›› ስሙን ብቻ ይዞ ጥልቅ ያለባት የአንቀፅ ኩሬ መስላኛለች፡፡ እንግዲህ የአህዛብ አፈታሪካዊ አማልክት የሆኑትን ሆረስ፣አቲስ፣ክሪሽና፣ ደዮኒስስ፣ ሚትራና ሌሎችም በታህሳስ ሃያ ሰባቱ ፀሃፊ የተጠቀሱና ያልተጠቀሱ አማልክት ጸሃፊው የተመኙትን ያህል ከክርስቶስ ኢየሱስ አምላክነት ጋር ሊሸረቡና የክርስቶስን እውነተኛ አምላክነት ሊሸፍኑ የማይችሉ መሆናቸውን ከየምንጫቸው እያጣቀስኩ ማብራራቴን ጊዜ ቀይ እስኪያበራብኝ ድረስ በብዕር ሩጫዬ እፋለመዋለሁ፡፡ በመጀመሪያ ሖረስ(ሆረስ)፡፡

ነገር ሁለት ፣ ነገረ ሆረስ (ከምንጩ) የሆረስ አፈታሪክ ሁለት ምንጮች አሉት፡፡ የዚህ ሆረስ የተባለው የግብፅ አፈታሪካዊ አምላክ ምንጮች ራሳቸው ግብፃውያንና ለጥቆም ደግሞ ግሪካዊያን ናቸው፡፡ ታዲያ የታህሳስ ሃያ ሰባት ስም አልባው ፀሃፊ የሁለቱንም የማይመስል ኩስምን ያለች ታሪክ ሲወረውሩልን፣ መነሻ ሃሳባቸው ተመሳሳይ የልደት ‹‹ቀነ- ወር›› ሊነግሩን ብቻ አልመሰለኝም፡፡ ነገር ግን አማልክቱ የልደት ‹‹ቀነ-ወር›› ብቻ ሳይሆን ታሪክም የሚኮራረጁ፣ አንዱ ከሌላው የማይሻል ‹‹አፈ ታሪኮች›› ናቸው እና ‹‹በአፈ ታሪክ አልሸወድም ወይም አልተሸወድኩም›› ነው ነገሩ፣ አዬዬዬ! የነገረ ሆረስ እውነታ ግን ከዚህ እንደሚከተለው ታትቷል፡፡ ዋና የሚባሉት ምንጮች፣አንዱ ግብፆቹ ራሳቸው በየ‹‹ድግምቶቻቸው›› እና በየ‹‹ጥንተ- ስዕሎቻቸው›› ላይ ቸክችከው እና ፈቅፍቀው ካስቀሯቸው መካነ ቅርሶቻቸው የሚቀዳ ሲሆን ዝክረ ፒራሚድ (pyramid texts) ልንለው እንችላለን፡፡ ሌላው ደግሞ በግሪኮቹ የታሪክ ጥራዝ ተዘክረው በብዛት ወደ ላቲን ተተርጉመው የአፈታሪክ መዓት የሚቀፈቀፍባቸው መፅሃፍት ናቸው፡፡ በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን የተጻፈው የፕሉታርክ De Iside et Osiride (Plutarch On Osiris & Isisi) ዋንኛው ነው፡፡ እነዚህ መጻህፍትና ቅርሳ ቅርስ ስለአፈ ታሪኮቹ ‹‹ስልጣን ያለን ማመሳከሪያ ነን›› ቢሉ እድሜያቸው ምክንያታቸው ነው፡፡ ከእነዚህ ምንጮች ያልቀዳ በአፈታሪክ ስም ያሻውን የቀባጠረ መሆኑ አያጨቃጭቅም፡፡ ሆረስ የግብፆች አምላከ-ጭልፊት (falcon-god) ሲሆን የሰማያት-ጌታም "lord of sky" ይባላል፤ የአምላካዊ ንጉስነትም ምስል ነው፡፡ በግብፅኛ ስሙ "ሃር" ተብሎ የሚጠራ ሲሆን ትርጓሜውም " ከ ፍ ተ ኛ ው " ፣ " የ ማ ይ ደ ረ ስ በ ት " ፣ "የትየለሌው" እንደማለት ይቆጠራል፡፡ ደግሞም "ህራይ" ከሚለው የግብፅ ቃል ጋርም ሊዛመድ ይችላል፣ፍችውም "ከፍ ብሎ ያለ፣ከላይ የሚገኝ" ማለት ነው፡፡ ይህ ስም በግብፃውያን ምስለ-ፅሁፎች (hieroglyph) ላይ በነገስታት ማዕረግ ከክርስቶስ ልደት 3000 ዓመት አካባቢ ጀምሮ ይከሰት የነበረ ታሪከኛ አፈ-ታሪክ ነው፡፡

አፈ-ታሪክ (myth)!! የኦሲሪስ አፈ ታሪክ እንዳይፈረካከስ ገና ከጥንት ሙሉ በሙሉ ጥበቃ ባይደረግለትም የአፈ ታሪኩ አንኳር ትረካዎች በግሪካዊው Plutarch (ፕሉታርክ) On Isis & Osiris ለታሪክ እንዲበቃ ተደርጓል፡፡ የፕሉታርክ ትረካዎች ከግሪክ ወደ ላቲን ተመልሰው De Iside e osiride በሚል ስም በአፈ- ታሪክ ምንጭነት እያገለገሉ ነው፡፡ ይህ ላቲነኛው ትርጉም ዋንኛ የሆረሶች ታሪክ ምንጭ ነው፡፡ ስለሆነም በሆረስ ዙሪያ ለሚነገሩ አዲስና አሮጌ ትረካዎች ዋና ከሚባሉት ማጣቀሻዎች ግንባር ቀደሙ በመሆኑ ለዚህም ጽሁፍ የማጣቀሻ ማጣቀሻዎች ምንጭ እሱ ነው፡፡ ይኸው ከግብፆች አማልክት ዋንኛ የሚባለው ሆረስ በብዙ ማዕረጎችና ቅፅል ስሞች የተንበሸበሸ ሲሆን ጭልፊት፣ ጭልፊት-ራስ ሰውዬ፣ ክንፋም እንጎቻ (winged disk) ወዘተ ተብሎ ይጠራል፡፡ ስለሆነም ጥናተ-ግብፃውያን (Egyptologists) ስለተለያዩ አይነት ሆረሶችና አምላከ ሆረሶች መተረክ የውዴታ ግዴታቸው ሆኖ ቀርቷል፡፡ ለማንኛውም በጥንታዊ ግብፃውያን ከተተረኩ መንጋ ሆረሶች መካከል ዝነኛው የ"ኦሲሪስ (Osiris) እና የኢሲስ (Isis) ልጅ የሆነው በግብፅ ንጉስነት የሚታወቀው ሆረስ ነው፡፡ የሆረስ አባት ኦሲሪስ "ስብዕናን የተላበሰ መሬት" ተብሎ ከሚታወቀው (Geb) (ገብ) እና የ‹‹አማልክት እናት›› ደግሞም የሰማይዋ (የጠፈሯ) እመቤት ("mother of gods" and ''goddess of the sky'') ከምትባለው Nout/Nut (ኑት/ነት) የተወለደ ሲሆን ሚስቱ ደግሞ ኢሲስ ትባላለች፡፡ ይህቺ ኢሲስ ታዲያ በፈርኦኖቹ ዘመን እጅግ ገናናዋ ባለ አፈታሪክ እና እጅግ የተስፋፋ የኑፋቄ ምንጭ ነበረች፣ ነችም፡፡ ሆረስ በህያው የምድር ንጉስነቱ ተለይቶ የሚወሳ ሲሆን አባቱ ኦሲሪስ ደግሞ በሙት (በሙትቻ) ነገስትነቱ ይታወቃል፡፡ ሆረስ የአባቱ አልጋ ወራሽና ምትክ ነበረ፡፡ Heliopolitan Ennead (ሄሊዮፖሊቲን ኤንያድ) በተሰኘ የእነሆረስ አፈታሪካዊ የዘር ግንድ መዘርዝር ውስጥ የGeb (ገብ) እና Nut (ነት) ልጅ የሆነ የኦሲሪስ ወንድም አለ፡፡ ስሙ ደግሞ ሴት/ሴዝ (Seth) ይባላል፡፡

ይህ ትልቅየው ሆረስ [Horus the Elder (Haroeris)] ተብሎ የሚታወቀው ሴዝ (Seth)አንዳንዴ የዋነኛው ሆረስ አጎት ወይም ወንድም እየተባለ ቢጠቀስም አጎትነቱ ከወንድምነቱ ይልቅ በሚበዙት ማጣቀሻዎች ላይ ይጎላል፡፡ እንግዲህ ሆረስ የግብፅን ንግስና ለመጎናፀፍ ለ80 አመታት ያህል ከአጎቱ ከ Seth (ሴዝ) ጋር ተፋልሟል ታዲያ በዚህ ጦርነት ሆረስ አንድ አይኑን አጥቷል፡፡ የሚደንቀው ግን ያልጠፋችው የሆረስ አይን ዝናዋ ከሆረስ ከራሱ አለመተናነሱ ነው፡፡ በየዶላሩ ላይ በትኩረት ስትመለከቱ በፒራሚዱ አናት ላይ ተድቦልቡላ የምታፈጥባችሁ እሷ የሆረስ ዓይን ትሆን እንዴ@ ከሆነች ይኸው እስከዛሬ እያሾለቀች ነው - በብርም በመጣጥፍም ላይ፡፡ አይ ሆረስ!ነገር ሦስት፣ ውልደተ ሆረስ (የድንግል ጭልፊት ልጅ)ኦሲሪስ የግብፅን ምድር ያስተዳድር ነበር፡፡ ነገር ግን ቀናተኛ በሆነው በገዛ ወንድሙ ተታሎ ለህልፈት በቃ፡፡ ቲፎን "Typhone" እየተባለም የሚጠራው የኦሲሪስ ወንድም ''ሴዝ'' ወይም "ሴት" በኦሲሪስ ልክ የሆነ ሬሳ ሳጥን አዘጋጀ፡፡ ከእለታት አንድ ቀን አንድ ታላቅ ግብዣ ላይ 72 ከሚጠጉ ሴረኞች ጋር በማበር የሬሳ ሳጥኑ ልኩ ለሚሆን ቃልኪዳን አፀደቁ፡፡ እናም እያንዳንዱ እንግዳ ከሬሳ ሳጥኑ ውስጥ እየተጋደመ በመለካት ተጠመደ፡፡ በመለካት ከተጠመዱት ሁሉ ሬሳ ሳጥኑ ለኦሲሪስ ልክክ አለለት፡፡ ነገር ግን ኦሲሪስ ከሳጥኑ ከመውጣቱ በፊት ሴትና ሌሎቹ ሴረኞች ሳጥኑን በኦሲሪስ ላይ ጠረቀሙት፡፡ ከዛም በምስማር ከርችመው፣ በመዳብ አሽገው ወደ አባይ ወንዝ ወረወሩት፡፡ የሬሳ ሳጥኑም ከጊዜ በኋላ Byblos (ቢብሎስ) ከተሰኘ ቦታ በደረቅ መሬት ላይ ተገኘ፡፡

የኦሲሪስ ሚስት ኢሲስ ያለመታከት ባሏን ስታፈላልግ ከርማ በመጨረሻ የሬሳ ሳጥኑ ያለበትን ስፍራ ደረሰችበት፡፡ ኢሲስ ሬሳውን ወደ ግብጽ እንዲመለስ ብታደርግም Seth (ሴዝ) ሬሳውን አገኘና ብዙ ቦታ ቆራርጦ ቦጫጭቆ በምድሪቱ ሁሉ ላይ በተነው፡፡ የኦሲሪስ ባለቤት ኢሲስ ራሷን ወደ ጭልፊትነት ቀይራ ከእህቷ Nephthys (ነፍዚስ) ጋር በምድሪቱ ሁሉ እየበረረች ቁርጥራጮቹንና ቡጭቅጫቂዎቹን ሁሉ አሰባስበለች - አንድ ነገር ብቻ ሲቀር፡፡ እሱም የባለቤቷ ብልት፡፡ ቁርጥራጮቹን ሁሉ መልሳ ገጣጠመችና ኦሲሪስ ወደ ዘላለማዊ ጥበቃው ከመግባቱ በፊት ህይወት ዘርታበት ስታበቃ፣አስመስላ በሰራችው የወንድ ብልት አማካኝነት ተገናኝታው ሆረስን ፀነሰች፡፡ (እዚህች ጋ ቆም ብሎ ኢሲስ ባል እንደነበራት፣ባል ካላት ደግሞ ድንግልና መደንገሉ ማብቃቱን መጠርጠር ይገባል፣ ባል ያላት ድንግል በአፈ-ታሪክ ይቻል ይሆንን@) ተጨማሪ እንዲሆነን ፕሉታርክ በ Molaria V የሚለውን አብረን ብናነብ መልካም ነው ብዬ አሰብኩ፡፡ "…of the parts of Osiris' body the only one which Isis didn't find was the male member for the reason that this had been at once tossed into the river, & the lepidotous, the sea-bream and the pike had fed upon it. But Isis made a replica of the member to take its place, and consecrated the phallus, in honor of which the Egyptians even at the present day celebrate festival…'' በነገራችን ላይ ኢሲስ የባሏ የኦሲሪስ ሚስት ብቻ ሳትሆን እህቱም እንደነበረች በአፈ-ታሪኩ ቅብጥርጥሮሽ ውስጥ መተረቱን በፕሉታርክም በዝክረ ፒራሚድ (pyramid texts) ውስጥም ተሰንቅሮ ይገኛል፡፡ እና ኢሲስ እህት-ሚስት ነች ይባላል፡፡ ከላይ በፕሉተርክ እንደተገለፀው ደግሞም በሌላኛው ግሪካዊ የታሪክ ሰው Diodorus እንደፀናው ‹‹የኦሲሪስ ክፍለ አካላት በወንድሙ በሴዝ ተቆራርጦና ተቦጫጭቆ በአባይ ውሃ ላይ ሲወረወር በአሳ ከተዋጠው በትረ ወንዳወንድነቱ (male member) በቀር ሌላ አካሉ በ"እህት-ሚስቱ" በኢሲስ ተሰብስቦ በአስማቷ ህይወት ለብሶ ከምን እንደሰራችው ባልተገለፀ ነገር (አንዳንድ ማጣቀሻዎች ከወርቅ ይላሉ) በእራሷ የተበጀውን በትረ-ወንድነት አካሉ ላይ ገጥማ ትፀንስ ዘንድ ተቻላት፡፡›› ይላል አፈ ታሪኩ፡፡ እንግዲህ ልብ በሉ ሆረስ በዚህ መልኩ ነው የተፀነሰው፡፡ስለሆረስ አፀናነስ ጥቂት ምንጮችን አከል አከል ባደርግ ነገሬን ማፈርጠሙ አይጠረጠርም፡፡ ትክክለኛ ምንጭ እስካልተጠቀሰ ድረስ "ለምን ይዋሻል?" ማስባሉ አይቀሬ ነውና፡፡ የአሁኑ ምንጮቼ ነው የተፀነሰው፡፡ስለሆረስ አፀናነስ ጥቂት ምንጮችን አከል አከል ባደርግ ነገሬን ማፈርጠሙ አይጠረጠርም፡፡ ትክክለኛ ምንጭ እስካልተጠቀሰ ድረስ "ለምን ይዋሻል?" ማስባሉ አይቀሬ ነውና፡፡ የአሁኑ ምንጮቼ ደግሞ የጥናተ ግብፃውያን ሊቃናት ናቸው፡፡ሌስኮ (Lesko)በ ‹‹Great Goddesses of Egypt›› ላይ “Drawings on contemporary funerary papyri shows her as a kite hovering above Osiris, who is revived enough to have an erection & impregnate his wife” ብሎ ፅፏል፡፡

ባጭሩ‹‹ጭልፊት ነገር ሆና ወንድነቱ እስኪነሳ ተንሳፈፈችበት …›› ለማለት ነው፡፡ አፈ ታሪኮቹ እፍረት አያቁም፤ሁሉ ነገር በቁሙ ነው፡፡ እንደኛ እንደዱሮው፡፡
በ”Gods & men in Egypt” ዱናንድ እና ዚኮች “after having sexual intercourse in the form of a bird, with the dead god she restored to life, she gave birth to a posthumous son, Horus.” ብለው ከትበዋል፡፡ ‹‹ ወፍ ነገር ሆና ከሞተው አምላክ ጋር ግንኙነት ከፈጸመች በኋላ … የሙት ልጅ የሆነውን ሆረስን ወለደች›› ለማለት ይመስላል፡፡
Richard Wilknson ደግሞ በ “complete gods and goddess of Ancient Egypt’’ በተባለ መጽሃፉ “through her magic Isis revivified the sexual member of Osiris and become pregnant by him, eventually giving birth to their child, Horus” ብሎ መስክሯል፡፡
እንግዲህ ከላይ በጥቂቱ ዳሰስ ዳሰስ ያደረኩት በታሪክነትና በስነ-ፅሁፍ ቅርስነት ዋጋ ሊኖረው ይችላል ተብሎ የሚታሰበው ግብፃዊው አፈታሪካዊ ቅብጥርጥሮሽ ለተነሳሁበት ጭብጥ መረጃ ቢሆን ብዬ እንጂ ጣፋጭነትና ተወዳጅነት የሌለበት ከንቱነቱ አስደምሞኝ አይደለም፡፡
ነገር ግን ይህ ‹‹የኦሲሪስ-ኢሲስ-ሆረስ›› አምላከ-ግብጽ ‹‹ከድንግል የተወለደ አምላክ ነው›› ብለው በእውነተኛው አምላክ ልደትና በዚያ ድንቅ ታሪክ ላይ የኩረጃና የአፈታሪክነት ቅብ ለመቀባባት በአሽሙር ብዕር ቀለም ለረጩ ማጣፊያነት ቢበዛ እንጂ አያንስም፡፡ ከላይ በማስረጃ እንዳያችሁት የሆረስ እናት ኢሲስ የተቦጫጨቀ አስክሬን ቀጣጥላ ያውም ለመፀነስ ዋና የተባለውን በትረ ወንድነት እራሷ ‹‹በትራ›› ሆረስን ለመፀነስ አንዴ ጭልፊት፣ አንዴ ወፍ ፣ አንዴ ሌላ አይነት በራሪ ነገር እየሆነች ስትርመሰመስ ሁሉም ምንጮች ቁልጭ አድርገው አሳይተዋል፡፡ በየትኛውም ተቀባይነት ባለው የሆረስ ታሪካዊ ትውፊት ላይ ኢሲስ ከሞተው ‹‹ባል-ወንድሟ›› ጋር ስትገናኝ ‹‹ድንግል ነበረች›› ተብሎ አልተፃፈም፡፡ ታዲያ ‹‹ለምን ይዋሻል?›› ከሆነችም ‹‹ድንግል ጭልፊት›› ወይም ‹‹ድንግል ወፈ-በራሪ›› ትሆን እንደሆነ እንጃ፡፡ እኔ ‹‹ድንግል ጭልፊት›› ብያታለሁ፣ ምክንያቱም በፀነሰች ጊዜ ጭልፊት ሆና ነበርና፡፡ የልጃገረድ ሳይሆን የጭልፊትነቷ ‹‹ድንግልና›› ነው የተፃፈላት፡፡
አቤት አለመመሳሰል፡፡ የሚገርመው የኢሲስ አፈ-ታሪካዊ ታሪኳ ሳይሆን ታሪክንና አፈታሪክን በአንድ ማነቆ ለማቆራኘት ከዚህ እዚያ የተንሳፈፉት የታህሳስ ሃያ ሰባቱ የአዲስ አድማስ ፀሃፊ ናቸው ፡፡ እንግዲህ የአፈ ታሪክ ገድለኛው ሆረስ ከድንግል አለመወለዱን ልብ በሉልኝ፡፡
የሆረስ ውልጃ ‹‹ድንግለ ውልደት›› ሳይሆን ‹‹ምትሃተ ውልደት›› ነው፡፡ የእንዲህ አይነት ታሪኮችና ውልደቶች ምንጭ ሰፈሩ ከየት እንደሆነ እውነተኛውን ድንግለ-ውልደት ለተቀበሉ ብዙም አምታች አይደለም፡፡ ነገር ግን ተአምራት ሁሉ ምትሃት ሆኖ ለቀሰፈው፣‹‹ደምረህ፤አባዝትህ ቁጭ አድርግልኝ›› ብሎ ለገረረ፣ የሆረስ አይነት ታሪኮች ድንቅ መሸሸጊያ ዋሻዎች ናቸው፡፡

ብርቱ ምሽግ ለመሆን ቢከጅላቸውም ‹‹ከፍ ያለውን በእግዚአብሄርም እውቀት ላይ የሚነሳውን ነገር›› ማፍረስ የሚችል እውነት የሚባል መዶሻ መኖሩ መረሳት የለበትም፡፡ ያ መዶሻ ደግሞ የማይሻረው ቃል ነው፣ እሱም ‹‹የጦር እቃችን ስጋዊ አይደለምና ምሽግን ለመስበር ግን በእግዚአብሄር ፊት ብርቱ ነው›› ይላል፡፡
ታዲያ እንዴት እንዴት ተደርጎ በዚያም በዚህም ይዋሻል; ‹‹ሃይልህ ብዙ ሲሆን…ዋሹብህ›› የሚለው የመፅሃፉ ቃል ተተገበረን?እንግዲህ ሆረስ ስለተባሉ አማልክት ስለ ክንፋቸው፣ስለ ፀሃይ እና ጨረቃ አይኖቻቸው ወዘተ በዝርዝር መተረኩ አላስፈላጊ አይደለም፡፡ የታህሳስ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ፀሃፊ ‹‹ወደተናቀ ወደ መጀመሪያ ትምህርት›› ትዝታ የግድ ስበውናልና መልስ መስጠት ተገቢ ስለነበር ነው ከላይ ያለውን ከጥንተ መዛግብት ብቻ ሳይሆን ከ‹‹ጥንተ›› ንባቤ ጨለፍ አድርጌ እንካችሁ ማለቴ፡፡ ጊዜና ስፍራ ለዛሬ ከዚህ አስቁመውኛልና የቀረውን ለሳምንት አሻግሬ ‹‹ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን›› እያልኩ ልሰናበት፡፡

Read 2173 times