Administrator

Administrator

በፖላንዷ ከተማ ባይድጎስዝ ነገ በሚደረገው 40ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያ ጠንካራ ቡድን በማሳተፍ ለተቃናቃኝ አገሮች ፈተና እንደምትሆን ተገለፀ፡፡ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናው ከ56 አገራት የተውጣጡ ከ432 በላይ አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች ለአዋቂ እና ለወጣት በተዘጋጁ አራት የውድድር መደቦች ይሳተፋሉ፡፡ በአዋቂ አትሌቶች ውድድሮች የኢትዮጵያ የቅርብ ተቀናቃኝ እንደምትሆን የተጠበቀችው ኬንያ ብትሆንም ባለፉት የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮናዎች ለሜዳልያ ፉክክር የበቁት ኤርትራ እና ኡጋንዳም ጠንካራ አትሌቶች ያሳትፋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በዓለም የአገር አቋራጭ ሻምፒዮና ታሪክ ከ1980 ወዲህ በተደረጉ የአዋቂ አትሌቶች ውድድሮች በወንዶች 13 የወርቅ ሜዳልያ በመውሰድ ኬንያ ስትመራ ኢትዮጵያ 11 በማስመዝገብ ሁለተኛ ነች፡፡

በሴቶች ደግሞ 9 የወርቅ ሜዳልያ ያስመዘገበችው ኢትዮጵያ የምትመራ ሲሆን ኬንያ በ4 የወርቅ ሜዳልያዎች ትከተላለች፡፡ ለሻምፒዮናው አይኤኤኤፍ ለሽልማት ያዘጋጀው 280ሺ ዶላር ሲሆን በዋናዎቹ የወንዶች 12 ኪሎ ሜትር እና የሴቶች ስምንት ኪሎሜትር ውድድሮች በግልና በቡድን እስከ ስድስት በሚመዘገበው ደረጃ መሰረት ገንዘቡን ያከፋፍላል፡፡ ለግል አሸናፊዎች ለወርቅ ሜዳልያ 30ሺ ዶላር ለቡድን አሸናፊ ደግሞ 20ሺ ዶላር ተመድቧል፡፡ በ40ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ የኢትዮጵያ ቡድን ከሁለት አመት በፊት በስፔን ፑንታ ኡምቡራ የገጠመውን የውጤት መቀዛቀዝ እንደሚያሽል ተስፋ ተደርጓል፡፡

በአዋቂ ወንዶች ከተያዙት አትሌቶች ከ2 አመት በፊት በስፔን ፑንታ አምብራ በተካሄደው 39ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በ12 ኪሎሜትር የወርቅ ሜዳልያ ለኢትዮጵያ ያስገኘው የ24 አመቱ ኢማና መርጋ እና በለንደን ኦሎምፒክ በ10ሺ የነሐስ ሜዳልያ ያገኘውና ከፍተኛ ልምድ ያለው ታሪኩ በቀለ በሜዳልያ ተቀናቃኝነት ትኩረት አግኝተዋል፡፡ በሴቶች ደግሞ በአገር አቋራጭ ሩጫ ለአራት ጊዜያት የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃችው ጥሩነሽ ዲባባ እና ለሁለት ጊዜያት በታዳጊዎች ውድድር ያሸነፈችው ታናሽ እህቷን ገንዘቤ ዲባባ ውጤታማ እንደሚሆኑ ተዘግቧል፡፡ ኢማና መርጋ የዓለም አገር አቋራጭ የሻምፒዮናነት ክብሩን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ዝግጅት ማድረጉን የገለፀው የአይኤኤኤፍ ዘገባ ጥሩነሽ ዲባባ በበኩሏ በአዋቂ ሴቶች የስምንት ኪሎሜትር ውድድር በኢትዮጵያዊ አትሌት ለመጨረሻ ጊዜ ከ5 ዓመት በፊት የተገኘውን የወርቅ ሜዳልያ ክብር ወደ ኢትዮጵያ ልትመልስ ትችላለች ብሏል፡፡

በባይድጎስዝ 40ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ በአዋቂ ሴቶች ህይወት አያሌው፤ ገነት ያለው ፤መሰለች መልካሙና በላይነሽ ኦልጅራ ተሳታፊ ሲሆኑ በወንዶች ደግሞ ከኢማና መርጋ ሌላ ማራቶኒስቱ እና የዘንድሮው የጃንሜዳ አገር አቋራጭ አሸናፊ ፈይሳ ሌሊሳ ፤ ሞሰነት ገረመው፤ አበራ ጫኔ፤ ታሪኩ በቀለ እና መካሻው እሸቴ ተወዳዳሪ ናቸው፡፡ በወጣት አትሌት ውድድሮች ኢትዮጵያ በሁለቱም ፆታዎች አዳዲስ አትሌቶችን በብዛት የምታሳትፍ ይሆናል፡፡ በወጣት ወንዶች የ8 ኪሎሜትር ውድድር የ18 አመቱ ሃጎስ ገብረህይወት የሚጠበቅ ነው፡፡ ባለፈው ወር በቦስተን አሜሪካ በቤት ውስጥ የ3ሺ ሜትር ውድድር አዲስ ሪከርድ ያስመዘገበው ሃጎስ ዘንድሮ በጃንሜዳ የአገር አቋራጭ ሻምፒዮና በወጣቶች ውድድር አሸናፊ ነበር፡፡ ባለፈው አመት በዓለም የታዳጊዎች ሻምፒዮና በ5ሺ ሜትር ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ሙክታር ኢድሪስም ለውጤታማነቱ ግምት ያገኘ ሲሆን አትሌቱ ከሁለት ወራት በፊት በጣሊያን የተደረጉ ሶስት ዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸውን የአገር አቋራጭ ውድድሮች በማሸነፍ ጥሩ ብቃት መያዙ ተመስክሮለታል፡፡

በወጣት ሴቶች የ6 ኪሎ ሜትር ውድድር ላይ ኢትዮጵያ አዳዲስ አትሌቶችን እንደምታሳትፍ ተገልጿል፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት በስፔን ፑንታ ኡምብራ ተደርጎ በነበረው 39ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን በውጤቱ በኬንያ በጣም ተበልጦ ነበር፡፡ በወቅቱ በአትሌቶችና በቡድን ደረጃ ለሽልማት ከቀረቡት 8 የወርቅ ሜዳልያዎች የኬንያ ቡድን 6ቱን ሲወስድ የኢትዮጵያ ቡድን 2 የወርቅ ሜዳሊያዎችን ብቻ አግኝቷል፡፡ በአጠቃላይ የኬንያ ቡድን በሻምፒዮናው ከቀረቡ 24 ሜዳልያዎች 11 ሲወስድ በኢትዮጵያ የተመዘገበው 5 ሜዳልያዎች ብቻ ነበር፡፡ በሻምፒዮናው ለሽልማት ከቀረበው ገንዘብ የኬንያ ቡድን 127ሺ ዶላር በመረከብ ከፍተኛ የበላይነት ሲያሳይ ለኢትዮጵያ የደረሰው 72ሺ ዶላር ብቻ እንደነበርም ይታወሳል፡፡

የሴኔጋል ተወላጅ የሆነው የአር ኤንድ ቢ እና የሂፖፕ ምርጥ ዘፋኝ ኤኮን፣ በአፍሪካ የማደርጋቸውን አስተዋፅኦዎችን እቀጥላለሁ ሲል ለሲኤንኤን ተናገረ፡፡ በሙሉ ስሙ አሌያሙኒ ዳማላ ባዲራ ተብሎ የሚጠራው ኤኮን ‹ስታድዬም› በሚል ስያሜ አራተኛ የአልበም ስራውን ለገበያ እንደሚያበቃ ታውቋል፡፡ ከእነ ማይክል ጃክሰን፤ ሌዲ ጋጋ፤ ስኑፕ ዶግ እና ኤሚነም ተጣምሮ በመስራት የሚታወቀው ኤኮን በአዲሱ አልበሙ ከፍተኛ ስኬት ሊያገኝ እንደሚችል ያምናል፡፡

ከአፍሪካ የፈለቀና በዓለም የሙዚቃ ኢንዱስትሪ ከፍተኛ ስኬት የተቀዳጀ አርቲስት መሆኑን የገለፀው ኤኮን፤ በኪነጥበብ እና በበጎ አድራጎት ስራዎች ለአህጉሪቱ በአርዓያነት የሚታዩ ስራዎችን መስራት የምንጊዜም ፍላጎቴ ነው ብሏል፡፡ ከ10 አመት በፊት የመጀመርያ አልበሙን ለገበያ ያበቃው ኤኮን፤ አስቀድሞ በ3 አልበሞቹ በመላው አለም ከ10 ሚሊዮን በላይ ቅጂዎችን ሸጧል፡፡ ሙዚቃ የሚያሳትምና የሚያከፋፍል “ኮንቪክት” የተሰኘ ኩባንያ እንዲሁም ልብስና የፋሽን ቢዝነስ እያንቀሳቀሰ የሚገኘው ኤኮን፤ በሴኔጋል ‹ኮንፊደንስ› በተባለ ፋውንዴሽኑ ለትምህርት ቤት እና ለጤና ጣቢያ ግንባታ የበጎ አድራጎት እንቅስቃሴ ያካሄዳል፡፡

‹‹ኦዝ ፡ ዘ ግሬት ኤንድ ፓወርፉል›› የተሰኘው ፊልም በፈረንጆቹ አዲስ ዓመት 2013 ከፍተኛውን ገቢ ለማግኘት የበቃ ፊልም መሆኑን ሎስአንጀለስ ታይምስ አስታወቀ፡፡ በዋልት ዲዝኒ፣ በ215 ሚሊዮን ዶላር የተሰራው ፊልም ከሁለት ሳምንት በኋላ በመላው ዓለም ከ288 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ አግኝቷል፡፡ ፊልሙ ለእይታ በበቃባቸው የመጀመርያዎቹ ሶስት ቀናት በዓለም ዙርያ ከ150 ሚሊዮን ዶላር በላይ ማስገኘቱ፣ የፊልሙ ቀጣይ ክፍሎችን የመስራት ሃሳቦችን አነሳስቷል፡፡

በጥንቆላ አፈታሪክ ዙርያ የሚጠነጥነው “አድቬንቸር ፋንታሲ” ፊልም፣ ጄምስ ፍራንኮ በመሪ ተዋናይነት ሰርቶበታል፡፡ ሚላ ኩኒስ፤ ራቼል ዊሴዝ እና ሜሸል ዊልያምም ተውነውበታል፡፡ ‹ኦዝ፡ ዘ ግሬት ኤንድ ፓወርፉል›፣ ከ74 አመታት በፊት ‹ዘ ዎንደርፉል ዊዛርድ ኦፍ ኦዝ› በተባለው ዘመን ያልሻረው መፅሃፍ ላይ በመመስረት በ3ዲ የተሰራ ነው፡፡ የፊልሙ ዲያሬክተር በስፓይደርማን ሶስት ፊልሞች ከፍተኛ አድናቆት ያተረፈው ሳሚ ራይሚ ነው፡፡

እንግሊዛዊቷ ድምፃዊት አዴሌ በጥቂት አመታት ውስጥ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ ሽልማቶችን ሁሉ በመሰብሰብ ስኬታማ እንደሆነች ቢዝነስ ኢንሳይደር ገለፀ፡፡ አዴሌ ከ3 ሳምንታት በፊት በ85ኛው የኦስካር ምሽት ላይ ለጀምስ ቦንድ ፊልም በሰራችው ሙዚቃ በምርጥ ኦርጅናል ዜማ ዘርፍ የኦስካር ሽልማት ወስዳለች፡፡ የ24 አመቷ አዴሌ አዲስ አልበም ለመስራት እንደማትቻኮል ወኪሏ ሰሞኑን ያሳወቀ ሲሆን፣ የመስራት ፍላጎት ቢኖራት እንኳን ዘንድሮ ጋብቻ ለመመስረት ማቀዷ ዝግጅቷን ያስተጓጉለዋል የሚሉ ዘገባዎች ወጥተዋል፡፡

አዴሌ በትልልቆቹ የኪነጥበቡ ኢንዱስትሪ ሽልማቶች ተሸላሚ የሆነችበት እድሜ በጣም የሚያስገርም ነው ያለው ዘ ቢዝነስ ኢንሳይደር፣ 9 የግራሚ፤ 4 የአሜሪካን ሚውዚክ አዋርድ፤ 12 የቢልቦርድ ሚውዚክ አዋርድ እና 4 የብሪት አዋርድ ሽልማቶችን በመሰብሰብ ወደር የለሽ ሆናለች፡፡ ‹21› የተሰኘው የአዴሌ ሁለተኛ አልበም በ2011 እና 2012 የዓለምን ገበያ ለመምራት የበቃ ሲሆን በአለም ዙርያ 12.5 ሚሊዮን ቅጂ ተሸጧል፡፡ አዴሌ ‹‹19›› በሚል ርእስ የመጀመርያ አልበሟን በመልቀቅ የዓለም የሙዚቃ ኢንዱስትሪን የተቀላቀለችው ከ4 ዓመታት በፊት ነበር፡፡

የሆሊውድ ፊልም ሰሪዎች፣ የቻይና መንግስት በሚፈፅምባቸው ሳንሱር ቢማረሩም፣ የአገሪቱ ገበያ ተመችቷቸዋል፡፡ በሌላ በኩል በቻይና የተሰሩ ፊልሞች በዓለም አቀፍ ገበያ እንዳልተሳካላቸው ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡ ለሆሊውድ ፊልሞች፣ ትልቋ ገበያቸው አሁንም አሜሪካ ነች፡፡ በመቀጠልም ጃፓን፡፡ ነገር ግን በቻይና የሆሊውድ ፊልሞች ገበያ በየአመቱ በ30% እያደገ መጥቷል፡፡ እናም በ2012 ቻይና ለሆሊውድ ፊልሞች ሦስተኛ ገበያ ሆናላቸው 2.71 ቢሊዮን ዶላር ገቢ አግኝተውባታል፡፡ በከፍተኛ ወጪ ተሰርተው ከፍተኛ ገቢ ያስገኙ ፊልሞች (ለምሳሌ ስካይ ፎል እና ዘ ዳርክ ናይት ራይዝስ) በቻይና ገበያ ደርቶላቸዋል፡፡

‹ኩንጉፋ ፓንዳ 3› የተባለውን ፊልም፣ ድሪም ዎርክስ ከቻይና ኩባንያ ጋር በመተባበር እንደሚሰራ የጠቀሰው ኒውዮርክ ታይምስ፣ ዋልት ዲዝኒ ደግሞ‹አይረን ማን 3› በከፊል በቻይና ምድር መቅረፁን ገልጿል፡፡ በ2002 እኤአ በቻይና የነበረው የሲኒማ ቤቶቸ ብዛት ከ10 አመታት በኋላ በ10 እጥፍ በማደግ 13ሺ ደርሷል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በቻይንኛ ቋንቋ የተሰሩ የቻይና ፊልሞች፣ በአለም ገበያ ያገኙት ተቀባይነት እጅግ የቀዘቀዘ መሆኑን ያመለከተው የሲኤንኤን ዘገባ ነው፡፡ በቻይና ቋንቋ የተሰሩት ፊልሞች በአገር ውስጥ ያላቸው ገበያ የተሟሟቀ ቢሆንም ከአገር ውጭ ግን ብዙም አልተሳካላቸውም፡፡ “ሎስት ኢን ታይላንድ” የተባለ ፊልም በቻይና እስከ 202 ሚሊዮን ዶላር ቢያስገባም፤ በሰሜን አሜሪካ ያስገባው ከ70ሺ ዶላር አይበልጥም፡፡

የሹሩባ ማውጫዎችን የሚያሳይና በአመት ሁለት ጊዜ የሚታተም መፅሔት ማዘጋጀት መጀመሩን “መኪያ ሹሩባ ሥራ” አስታወቀ፡፡ የመፅሔቱ ዋና አዘጋጅ ወይዘሪት መኪያ ሁሴን፣ መፅሄቱ ረዣዥም ፅሁፎች የሌሉት በእንግሊዝኛ ብቻ የሚታተም ነው ብላለች፡፡ Ethiobraids የተሰኘው መፅሔት 64 ገፆች ያሉት ሲሆን በ100 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

በአባይ ጉዳይ ላይ ከተፃፉት አዳዲስ መፃህፍት መካከል አንዱ፤ የኒውዮርክ ከተማ ነዋሪ በሆኑት አቶ ገብረፃድቅ ደገፋ የተዘጋጀ ሲሆን፣ “ናይል ታሪካዊ፣ ሕጋዊና ልማታዊ ገጽታዎች - ለ21ኛው ክፍለ ዘመን ማስጠንቀቂያ” በሚል ርእስ ተተርጉሟል፡፡ በአቶ ወርቁ ሻረው ተተርጉሞ በ406 ገፆች የቀረበው መፅሐፍ፤ በ60 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

የአምስት ወር ነፍሰጡር የነበረችውን ባለቤቱን ሆዷ ላይ ስድስት ቦታ በጩቤ ወጋግቶ የገደለው ተጠርጣሪ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ዋለ፡፡ ባልና ሚስቱ ለአራት ዓመታት በጋብቻ ተሳስረው ሲኖሩ የሁለት ዓመት ልጅ አፍርተዋል፡፡ በምዕራብ ጐጃም ቡሬ ከተማ ውስጥ በተፈፀመው በዚህ ወንጀል ከሟች ሌላ የሟች ወ/ሮ ተናኜ ገረም ወላጅ እናትና አባት በጩቤ የመወጋት ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ የቡሬ ወረዳ ፖሊስ ፅ/ቤት መርማሪ የሆኑት ዋና ሳጅና አልማው ደሴ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት ባለፈው ወር መጨረሻ በባልና ሚስት መካከል በተፈፀመ ያለ መግባባት ሚስት ወደ ወላጆቿ ቤት ሄዳ ነበር፡፡

ባል እዚያ ሄዶ ግድያውን መፈፀሙን ተናግረዋል፡፡ ተጠርጣሪው በትዳር አጋሩ ላይ ይህን ወንጀል በፈፀሙ የአካባቢው ህብረተሰብ ቁጣ ተቀስቅሷል፡፡ ተጠርጣሪው በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሎ ምርመራ መካሄዱን የጠቆሙት ዋና ሳጅን አልማው የምርመራ መዝገቡ ለዐቃቤ ሕግ ተላልፎ ክስ መመስረቱንም ጠቁመዋል፡፡ በተጠርጣሪው በጩቤ የተወጉት የሟች ወላጅ እናትና አባት በአሁኑ ወቅት በህክምና ላይ እንደሚገኙም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በመንፈሳዊ ኮሌጁ ትምህርት ተቋርጧል፤ ተማሪዎቹም ምግብ መመገብ አቁመዋል

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርት÷ ለትምህርት ጥራት መሻሻልና ለደቀ መዛሙርቱ መብት መከበር ከመቆም ይልቅ ገንዘብ ለመሰብሰብና የግል ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ ቅድሚያ ይሰጣሉ ያሏቸው ሁለት የአስተዳደር ሓላፊዎች ከሥልጣን እንዲወገዱ ያቀረቡት ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ ባለማግኘቱ ትምህርት ማቆማቸውንና ምግብ ከመብላት መከልከላቸውን አስታወቁ፡፡ በጥያቄያቸው ያመለከቷቸው በርካታ የኮሌጁ ችግሮች ላለፉት ዐሥራ አራት ዓመታት ሲንከባለሉ የቆዩ መኾናቸውን የገለጹት ደቀ መዛሙርቱ÷ የመምህራኑ አቅም ማነስና የትምህርት ጥራት መውደቅ፣ የምግብ መበከልና የአስተዳደሩ በጥቅም ትስስርና በሙስና መዘፈቅ ሊታገሡት ከሚችሉት በላይ በመኾኑ ፓትርያሪኩና የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤቱ አፋጣኝ መፍትሔ እንዲሰጧቸው መጠየቃቸውን ገልጸዋል፡፡

ይኹንና ፓትርያሪኩን በአካል አግኝቶ ለማነጋገር አልያም የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ሓላፊዎችን ለማግኘት በተደጋጋሚ ያደረጉት ጥረት ከኮሌጁ ሓላፊዎች ጋራ በጥቅም ተሳስረዋል ያሏቸው አካላት እንደፈጠሩት በሚያምኑት መሰናክል አለመሳካቱን አስታውቀዋል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ከኮሌጁ አስተዳደር ጋራ የገቡበት ውዝግብ ከተቀሰቀሰ ሁለተኛ ሳምንቱን የያዘ ሲኾን ትምህርት መቋረጡም ተዘግቧል፡፡ ለደቀ መዛሙርቱ ጥያቄ ደረጃ በደረጃ ምላሽ እንደሚሰጥ የገለጸው አስተዳደሩ÷ ደቀ መዛሙርቱ ካለፈው ሳምንት አጋማሽ ጀምሮ ያቋረጡትን ትምህርት እስከ ረቡዕ ቀትር ድረስ በአስቸኳይ እንዲቀጥሉ አሳስቧል፡፡ ደቀ መዛሙርት ወደ ትምህርታቸው የማይመለሱ ከኾነ ደግሞ በዚያው ዕለት ንብረትና መታወቂያ እያስረከቡ ኮሌጁን ለቀው እንዲወጡ አስተዳደሩ አስጠንቅቋል፡፡

‹‹ለሁለት ሰዎች ሲባል ሁለት መቶ ተማሪ አይባረርም፤ ብቃት የሌላቸውና ኮሌጁን እንደ ርስት በዘመድ ይዘው የጥቅም ማግበስበሻ ያደረጉት አካዳሚክ ዲኑና የቀን መርሐ ግብር አስተባባሪው ከሓላፊነታቸው ይነሡልን፤›› የሚሉት ደቀ መዛሙርቱ በበኩላቸው÷ ችግሮቻቸው በመሠረቱ ደረጃ በደረጃ መፈታት እንደሚገባቸው ቢቀበሉም ወደ ትምህርት ገበታቸው የሚመለሱት ግን የኮሌጁ ምክትል አካዳሚክ ዲንና የቀን መርሐ ግብር አስተባባሪው ከሓላፊነታቸው ሲነሡ ብቻ ነው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ እንደሚያስረዱት÷ በተጠቀሱት የኮሌጁ አስተዳደር ሓላፊዎች ደረጃ ብቻ ሳይሆን በቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተዳደር መዋቅሮች ውስጥ ምእመኑ ‹‹የገንዘብ ምንጭ ብቻ ኾኗል፤ አገልጋይ ጠፍቷል፡፡›› ደቀ መዛሙርቱ÷ ኮሌጁን እንደ ግለሰብ ቤትና እንደ ዘመድ ርስት ይቆጥራሉ በሚሏቸው ጥቂት ሓላፊዎች መካከል አለ የሚሉት የጥቅም ትስስር በትምህርት ጥራትና በመብታቸው ላይ የፈጠረውን ተጽዕኖ የሚገልጹት ‹‹ኮሌጁ የትምህርት ሳይሆን የንግድ ማእከል ኾኗል፤›› በሚል ነው፡፡

ለአዲስ አድማስ አስተያየታቸውን የሰጡ የደቀ መዛሙርቱ መማክርት አባላት እንዳስረዱት÷ የተለያዩ ገባሬ ሠናይ ድርጅቶች ለኮሌጁ የገንዘብ ድጋፍ ያደርጋሉ፤ ከእነርሱም በላይ በዋናነት ሁሉም አህጉረ ስብከት ከጠቅላላ ገቢያቸው አምስት ከመቶ ፈሰስ ያደርጋሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ኮሌጁ ሕንጻውን በማከራየትና የመማሪያ ክፍሎቹን ለተለያዩ ኮሌጆች በመፍቀድ ከፍተኛ ገቢ ይሰበስባል፡፡ ይኹንና ደቀ መዛሙርቱ በሜዳ ላይ የሚማሩበት አጋጣሚ አለ፡፡ በየመርሐ ግብሩ ከተዘረጉት ኮርሶች ብዛት ጋራ የሚመጣጠኑ መምህራንን መቅጠር እየተቻለ የመምህራን ምደባው አራትና አምስት ኮርሶችን በሚይዙ ጥቂት መምህራን መካከል የተወሰነ ነው፡፡ የመምህራኑ ዕውቀት ‹‹ሙሉዕ በኩለሄ›› እስካልኾነና መምህራኑ ከተጨማሪ ሓላፊነቶች ጋራ ከሚያጋጥማቸው የዝግጅት ማነስ የተነሣ ምደባው የትምህርት ጥራቱን የሚጎዳው ይኾናል፡፡ ይህም በትምህርት አሰጣጡና በምዘናው ላይ በሚያስከትለው አሉታዊ ተጽዕኖ የተነሣ አቤቱታ የሚያቀርቡ ደቀ መዛሙርትን የሚያሸማቅቁ፣ ከዚህም አልፎ በመማሪያ ክፍሎችና በቤተ መጻሕፍት ውስጥ ሳይቀር የሚደበድቡ መምህራን መኖራቸውን ነው ደቀ መዛሙርቱ ለአዲስ አድማስ የተናገሩት፡፡

በተማሪዎች አቀባበል ወቅት ኮሌጁ የሙሉ ጤንነት ምርመራ እንደሚያደርግላቸው የገለጹት ደቀ መዛሙርቱ በሂደት ግን በካፊቴሪያው ጥንቃቄ የጎደለው የምግብ ዝግጅት የተነሣ ጤንነታቸው የተጎዳና በቂ ሕክምና የማያገኙ ደቀ መዛሙርት ቁጥር ጥቂት እንዳልኾነ ደቀ መዛሙርቱ ለዝግጅት ክፍሉ ገልጸዋል፡፡ በቤተ መጻሕፍት አገልግሎትና በመረጃ ቴክኖሎጂ ረገድ የሚሰጠው አገልግሎትም አንፋውን ኮሌጅ የሚመጠን እንዳልኾነ ነው ደቀ መዛሙርቱ የሚናገሩት፡፡ ‹‹የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ከተቀሩት ሁለት የቤተ ክርስቲያኒቱ ኮሌጆች ጋራ ሲነጻጸር አንጋፋ ቢኾንም ዛሬ ከአስተዳደሩ ድክመት የተነሣ የሚገኝበት ደረጃ ከዘመናዊነት የራቀ ነው፤›› ይላሉ ደቀ መዛሙርቱ፡፡ ይህ የኮሌጁ ኹኔታ የሚያሳስባቸውና በጉዳዩ ላይ ከደቀ መዛሙርቱ ጋራ የሚመክሩ መምህራን ማስጠንቀቂያ እንደሚሰጣቸውና ስለላ እንደሚካሄድባው ተመልክቷል፡፡

በኮሌጁ ሰፍኗል የሚሉትን ሙስናና የአሠራር ብልሽት የሚቃወሙት የአገርንና የሕዝብን ሀብት ከማዳን አንጻርም በመኾኑ መንግሥትም ሊያግዘን ይገባል፤ ‹‹ችግራችንን የማይፈቱልን ከኾነ ችግር ባይፈጥሩብን›› በማለትም በግል እየጠሩ ያስፈራሩናል፤ ይዝቱብናል ያሏቸውን የፖሊስ አባላት ይጠይቃሉ ደቀ መዛሙርቱ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ በአድራሻ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የጻፉትን ጥያቄዎቻቸውን ለጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ ለሰብአዊ መብት ኮሚሽንና ለፌዴራል ፖሊስ በግልባጭ ማሳወቃቸውን የገለጹ ሲኾን ለጥያቄዎቻቸው በቂ ምላሽ እስኪያስገኙ ድረስ ውርጩን፣ ረኀቡንና እንግልቱን ተቋቁመው ለመቆየት መወሰናቸውን ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡ በደቀ መዛሙርቱ ጥያቄዎችና ተቃውሞዎች ላይ የኮሌጁን ሓላፊዎች አስተያየትና ምላሽ ለማግኘት የኮሌጁ ምክትል አካዳሚክ ዲንን በስልክ ለማነጋገር የሞከረን ቢኾንም ዲኑ በአካል ካልቀረባችኹ በስልክ ምላሽ አልሰጥም ብለውናል፡፡ የዝግጅት ክፍሉ በነበረበት የጊዜ እጥረት ዲኑን በአካል አግኝቶ ሊያነጋግራቸው አልቻለም፡፡