ከርቀት ስትታዘበው - 
ተከዜ ወንዝ የሚመስል - በከርሱ ውሃ 
የያዘ፤
ተሻግረኽ ስትጠጣው ግን - 
ከባሩድ በላይ የሚገድል - በሄምሎክ 
የተመረዘ፤
ሸለቆው ማዶ ቁጭ ብለህ - 
ባሻገር ያለውን ጋራ - አድማሱን 
ስታስተውለው፤
አልፈኸው እስክትሄድ ድረስ - 
ሐኖሱ ድባቡ ሁላ - እናት ኢትዮጵያን 
መሳይ ነው፤
‹‹ይሄ አገር ማን ነው›› የምትል - 
ወንዙን ስትሻገረው፣ መርዙን 
ስትጎነጨው፤
ጉድ ነው!
አገሬ ልንገርሽማ፥ ምን ምን እንዳጋጠመኝ- 
ስሚማ በመይሳው ሞት
ሕይወቴ ያንቺ ሆኖ ሳለ - ስሜቱን 
ከሥሙ ጋር - ለእኔ የሰጠ ድርጅት
ከሴት ደፋሪ መድቦኝ- ሥሜን እንደ ጥጥ 
ሲያባዝት
ያንን የሰሜን አርበኛ - 
ከአንበጣ ተርታ መድቦ - ጨፍጭፎ ያደረ 
ባንዳ፤
ከዝንጀሮ ጋር ሸምቆ- 
ሌባ ዘራፊ እያለ- ሲነዛ ፕሮፓጋንዳ፤
ቄስሽ መስቀሉን ጥሎ- ቦንብ ታቅፎ   
ሲንጋጋ 
በምሞትለት ስጠቃ- በምዋጋለት ስወጋ፤
ደፍረውኝ እንደ ደፋሪ- ሰልበውኝ እንደ 
ሰላቢ
ክደውኝ እንደ ከሃዲ - ወግተውኝ እንደ 
ደብዳቢ
ሶሪያ እንደተገኘ-
በባዕድ ስሜት ተውጬ- ስልልሽ ‹‹ያላህ 
ያረቢ››
አክሱም ጽዮንን አጥፍቶ- ለደብረ ጽዮን 
የሚሰግድ፤
የሚረዳኝ ብቸኛ ጌታ - 
ጌታቸው ረዳ ነው ብሎ - እግዜር አላሁን 
የሚክድ፤
ሲገድል ጀጋኑ የሚባል - ሲሞት ንጹሕ 
የሚሆን፤
ከተኩሶ ክሱ በርትቶ - ሲለቀልቀኝ 
እድፉን፤
ታጣቂ ካላየ በቀር- 
መባረቅ የማያሰኘው - መተኮስ 
የማይችል ክላሽ፤
መያዜን ያወቀ ውርጋጥ - 
ተኩሶ ከሸሼ ወዲያ - እኔን ሲያደርገኝ 
ተከሳሽ፤
እናም እናታለሜ- 
እንደ አምናው ሁሉ ዘንድሮም - ነፍሴን 
ልሰጥሽ ወጥቼ
ጠላትሽን ከመታሁ ወዲያ - 
እያነባሁ ነው የወጣሁ - ምድሩ ላይ 
አንቺን አጥቼ፡፡
				
		
			Sunday, 11 July 2021 18:48		
		
	  	  
	  
  
  
  
  
	  
	
		
	
	
  ከአንድ ወታደር የተላከ
Written by አሳዬ ደርቤ
			Published in
			 ከፌስቡክ ገጾች በጨረፍታ
		
		
	  
	  
		
  
