Administrator

Administrator

“ሰው ለማገልገል መፈጠር መታደል ነው”


ራስዎን ያስተዋውቁ …
ስሜ ጌታቸው ተድላ ይባላል፡፡ አሁን የምኖረው አዲስ አበባ ውስጥ ነው፡፡ ትምህርቴ በእርሻ ኢኮኖሚክስና በገጠር ልማት

ሲሆን የመጨረሻው ማዕረጌ PHD ነው፡፡ በዓለም ዙሪያ ብዙ አገሮች ላይ ሰርቻለሁ፡፡ ጡረታ ስወጣ አገሬ ላይ መጥቼ

መፃፍ የጀመርኩ ሲሆን እስካሁን  ወደ ስድስት ያህል መፃህፍትን ጽፌያለሁ፡፡
የመጽሐፍቱን ስም ቢዘረዝሩልኝ?
የመጀመሪያው መጽሀፌ የአባቴ የእርሻ ሥራ ላይ ያጠነጥናል፡፡ ሁለተኛው መጽሐፍ እኔ ሳልጽፈው ክቡር ፀሐፊ ትዕዛዝ

አክሊሉ ሃብተወልድ (በኃይለስላሴ ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩ ናቸው) እስር ቤት ሆነው የፃፉትን ህዝብ ማወቅ

አለበት በሚል በአማርኛም በእንግሊዝኛም ተረጐምኩት። በመጨረሻም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬስ “የአክሊሉ

ማስታወሻ” በሚል አውጥቶት በርካታ ቅጂዎች ተሸጠዋል፡፡ ከዚያ በኋላ በራሴ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን “የህይወት

ጉዞዬና ትዝታዎቼ” የሚል መጽሐፍ ፃፍኩኝ። ይህን ከጨረስኩ በኋላ “ተስፋ የተወጠረች ህይወት” የሚል መጽሐፍ

ፃፍኩኝ። በደርግ ጊዜ ስድስት ልጆች ከዘመቻ ጠፍተው ወደ ጅቡቲ ሰባት ቀንና ሰባት ሌሊት የተጓዙበትን ታሪክ

ያሳያል፡፡ በመጨረሻም “ከትዝታ ጓዳ” እና “እንደወጡ የቀሩት ኢትዮጵያዊ” የሚል መጽሐፍ ለመፃፍ በቅቻለሁ፡፡
በተባበሩት መንግስታት ውስጥ ለረጅም ጊዜ መስራትዎ ይታወቃል፡፡ እስኪ የት የት እንደሰሩ ይንገሩኝ…
ከ20 አመት በላይ በተባበሩት መንግስታት የምግብና እርሻ ድርጅት (FAO) ነው የሰራሁት፡፡ በልዩ ልዩ አገሮች ለምሳሌ

በሌሴቶ፣ በታንዛኒያ እና በበርካታ አገሮች ሰርቻለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ በአለም የስራ ድርጅት (ILO) ውስጥ ገባሁና

በናይጀሪያ ለአምስት አመት ሰራሁ፡፡ መጨረሻ ላይ በሰላም ማስከበር ሥራ በኢራቅ የሰሜኑ ክፍል (ኩርዶች በሚኖሩበት)

ሁለት አመት፣ ባግዳድ ደግሞ ሁለት አመት በአጠቃላይ ለአራት አመት አገልግያለሁ፡፡ ሳዳም ሁሴን በነበሩበት ዘመን

ማለት ነው።  
ጡረታ ከወጡ በኋላ ከመጽሐፍ ውጭ ምን እየሰሩ ነው?
ከመጽሐፍ ውጭ በአሁኑ ሰዓት በበጐ አድራጊ ድርጅቶች ውስጥ በበጐ ፈቃደኝነት ነው የምሰራው። በዋናነት ሜቄዶንያ

የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል ውስጥ ብዙም ባይሆን የአቅሜን ለማድረግ እየጣርኩኝ እገኛለሁ፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ በወላጅ አልባ ህፃናት፣ በሴቶች ጥቃት፣ በትምህርትና የሴቶችን አቅም በመገንባት ዙሪያ የሚንቀሳቀሱ

የበጐ አድራጐት ድርጅቶች አሉ። እርስዎ ለምን ሜቄዶንያን መረጡ?
ሜቄዶንያን የመረጥኩበት ዋናው ምክንያት የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል በመሆኑ ነው። ብዙ በጐ አድራጐት

ድርጅቶች የሚሰሩት በህፃናት፣ በጉዲፈቻ እና በመሳሰሉት ላይ ነው። ሜቄዶንያ የሚሰራው ስራ በጣም ቅዱስና የተለየ

ነው፡፡ ይህን ስልሽ የሌላው መጥፎ ነው፤ ጥቅም የለውም ለማለት አይደለም። ሜቄዶንያ በትንሽ ብር ብዙ ስራ

የሚሰራበት፣ በጐ ፈቃደኞች ያለ ክፍያና ያለ ደሞዝ፣ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ፣ ሽንትና ሰገራ የማይቆጣጠሩትን ሳይጠየፉ

እያጠቡ እያገላበጡ የሚውሉ የሚያድሩበት ድርጅት ነው፡፡ ይህ በእውነት ልብ የሚነካ በመሆኑ የመረጥኩበት ዋነኛ

ምክንያቴ ነው፡፡ መስራቹ አቶ ቢኒያም በለጠን ውሰጅ… በጣም ወጣት ነው፤ ትልቅ ሰው ነው፤ የሚሰራውም ቅዱስ ስራ

ነው፡፡ ይህን የማይሞከር ስራ ሞክሮ ለዚህ የበቃ ፅኑ ልጅ ነው፤ ይህንን ልጅ ደግሞ ማገዝ አለብኝ በሚል ነው

የመረጥኩት፡፡
እንግዲህ በጐ ፈቃደኛ ሲኮን የግድ ገንዘብ ያለው መሆን አያስፈልግም፡፡ የሜቄዶንያ መስራች  የአቶ ቢኒያም መርህ

“ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን በቂ ነው” የሚል ነው፡፡ እርስዎ በየትኛው ዘርፍ ነው እርዳታ የሚያደርጉት?   
እኔ እንግዲህ በተለያዩ ዘርፎች ነው የማገለግለው። በቻልኩት ሁሉ፡፡ ለምሳሌ በአስተዳደሩ በኩል እሰራለሁ። ከእኔ

መሰሎች ጋር ስድስት ሆነን “የአማካሪ ግሩፕ” በሚል ቡድን አቋቁመን የማማከር ስራ እንሰራለን። በገንዘብም በኩል

ቢሆን እውነት ለመናገር ያቅማችንን እያደረግን ነው፡፡ ለምሳሌ ታህሳስ 13 ቀን 2006 ዓ.ም በተደረገው የግሎባል ሆቴል

የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ላይ ለማሳተም 64ሺህ ብር ያወጣሁበትን “ከትዝታ ጓዳ” እና “እንደወጡ የቀሩት

ኢትዮጵያውያን” የተሰኙ ሁለት መፃህፍቶቼን 900 ያህል ቅጂዎች ለሽያጭ አቅርቤ ገቢ እንዲያገኙበት አድርጌያለሁ፡፡
እኔ ሁለቱን መፃህፍት በመቶ ብር እንዲሸጡ ነበር የተመንኩት፡፡ ነገር ግን እነሱ ሁለቱን በ150 ብር እንሸጣለን ብለው

በዚህ ዋጋ ሲሸጡ ነበር፡፡ ዘጠኝ መቶውም ካለቀ ወደ 135ሺህ ብር ገደማ ያገኙበታል ማለት ነው፡፡ ይህቺ የእኔ ትንሿ

አስተዋፅኦ ናት፡፡
በሜቄዶንያ ከሚገኙ 300 ያህል አረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን መካከል አይቼው በጣም ስሜቴን ነክቶታል የሚሏቸው

አሉ?
በአጠቃላይ እዛ ያሉት ሁሉ ልብ ይነካሉ፡፡ ነገር ግን እኔም ሆንኩ ባለቤቴ በጣም ልባችንን የነካው አልጋ ላይ ተኝቶ

የሚገኘው ጌዲዮን የተባለው ወጣት ነው፡፡ 24 ሰዓት እዛው እየተገላበጠ ነው የሚውል የሚያድረው። ሰውነቱ ከወገቡ

በታች ፓራላይዝድ ነው፡፡ (በነገራችን ላይ ጌዲዮን በጣም ወጣት፣ ቀይ፣ እጅግ መልከ መልካም ሲሆን መናገር ባይችልም

መስማት ግን ይችላል፡፡ አጠገቡ ያለች በጣም ወጣት አስታማሚና ተንከባካቢው ብቻ የአፉን እንቅስቃሴ አይታ

ትተረጉማለች፡፡ ከዚህ በፊት የሀብታም ቤተሰብ ልጅ ነበር ተብሏል) ይህ ወጣት በጣም ቆንጆና የሚያሳዝን ነው፡፡
አዲስ አድማስ ላይ የወጡት ኮሎኔል ታሪክም ያሳዝናል፤ ነገር ግን አሁን እርሳቸው በጥሩ ሁኔታ ላይ ነው የሚገኙት፡፡

ከሁሉም ከሁሉም ግን ማን ልቤን እንደሚነካው ታውቂያለሽ? የአዕምሮ ህሙማኑ አረጋዊያን እላያቸው ላይ ሲፀዳዱ

ተሯሩጠው የሚያፀዱትና ንፁህ የሚያደርጓቸው አስታማሚዎች ልቤን ይነኩታል። እውነቱን ልንገርሽ እኔ አላደርገውም፡፡

በዚህ መጠን ሰውን ለማገልገል መፈጠር መታደል ነው፡፡ እና እነዚህ በጐ ፈቃደኞች ዝም ብዬ ሳስባቸው ፅናታቸው

ልቤን ይነካዋል፡፡ እግዚአብሔር ይባርካቸው፡፡
ከመፃህፍቱ በተጨማሪ አንድ ስዕል ለጨረታ አቅርበው ነበር አይደል…?
አዎ! “የቴዎድሮስ የመጨረሻው የመቅደላ ጉዞ” የተሰኘ ስዕል ነበረኝ፡፡ ያወጣላቸውን ያህል ያውጣላቸው ብዬ

ሰጠኋቸው፡፡ ከ10ሺህ ተነስቶ መቶ ሺህ ብር ተሸጠ፡፡ በጣም የምወደው እና ሳሎኔ ውስጥ ሰቅዬው የነበረ ስዕል ነው፡፡

ቴዎድሮስ በፈረስ ላይ ሆነው ሰው ከቧቸው ሲጓዙ የሚያሳይ በጣም ማራኪ ስዕል ነው፡፡
ባለፈው እሁድ በግሎባል ሆቴል የተካሄደው የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም አጠቃላይ ድባብ ምን እንደሚመስል

ቢገልፁልኝ…
እውነት ለመናገር … የእሁዱ ፕሮግራም ከጠበቅነው በላይ ነበር፡፡ አንደኛ ከ3500 በላይ ሰው ተገኝቷል። በሁለተኛ ደረጃ

ሁሉም እጁን ዘርግቷል፤ በርካታ ብር ለግሷል፡፡ ለምሳሌ አንድ ስዕል ነበር፡፡ የአንዲት ሴት ስዕል ነው፡፡ ዝም ብሎ ስዕል

ነው፤ አንድ 20ሺህ ብር ቢያወጣልን ብለን ነበር የገመትነው፡፡ ነገር ግን 200ሺህ ብር ተሸጠ። ሌላ ስዕል ደግሞ 50ሺህ

ብር ቢያወጣልን ብለን አስበን 300ሺህ ተሸጠ፡፡ ብቻ ሰው የሜቄዶንያ ስራ ገብቶታል፤ መርዳት አለብን ብሎ አምኗል

ማለት ነው፡፡ ሌላው ስለሜቄዶንያ መታወቅ ያለበት በቀን አንድን ሰው ለመመገብ 20 ብር ያስፈልጋል፤ ለቁርስ፣ ምሳና

እራት ማለት ነው፡፡ አሁን ላሉት 300 ሰዎች በቀን 6ሺህ ብር እናወጣለን፡፡ በወር 180ሺህ ሲሆን በአመት 2 ሚሊዮን

አንድ መቶ ሰማኒያ ሺህ ብር ይወጣል፡፡ ይህ እንግዲህ ለምግብ ብቻ ነው። መድሀኒት፣ ልብስ፣ የንፅህና መጠበቂያ፣ እና

ሌሎችንም ሳይጨምር ነው፡፡ የዛሬ አመት ደግሞ ተረጂዎችን አንድ ሺህ የማድረግ እቅድ አለው፡፡ የሜቄዶንያ ተረጂዎቹ

አንድ ሺህ ሲደርሱ ለምግብ ብቻ ወጭው 20ሺህ ብር በቀን ይሆናል፡፡ በወር 600ሺህ ብር ይመጣል፣ በአመት ደግሞ

ወደ 5.5 ሚሊዮን ይሆናል፡፡ ይሄ ልጅ በእናትና አባቱ ቤት ነው 300ውን እየተንከባከበ ያለው፡፡
ታዲያ ተጨማሪ ቤት ሳይኖር እንዴት አንድ ሺህ ሰዎችን መርዳት ይቻላል?  
ያው መንግስት ሊሰጥ ያሰበውን 20ሺህ ሄክታር መሬት ቶሎ ቢሰጥና እዚያ ትልቅ ቤት ተሰርቶ አረጋዊያን ለብቻ፣

ሴቶችና ወንዶች ለብቻ፣ የአዕምሮ ህሙማን ለብቻ ሆነው፤ ክሊኒካቸዉ እዛው፣ ማረፊያቸውም እንዲሁ ሆኖ የተሻለ ስራ

መስራት ቢቻል ደስ ይለኛል፡፡ ቦታው ይገኝ እንጂ ግንባታው ጊዜ አይወስድም፤ ምክንያቱም ህዝብ ይገነባዋል የሚል

እምነት አለኝ፡፡
በእሁድ ዕለቱ ፕሮግራም በአጠቃላይ ምን ያህል ገቢ አገኛችሁ?
እኔ እስከማውቀው ከሶስት ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ተገኝቷል፡፡ ዲኤክስ መኪናም አግኝተናል፡፡ እግዚአብሔር ይመስገን፡፡
ከጨረታውና ከመሰል ነገሮች እንኳን ከ600ሺህ ብር በላይ ነው የተገኘው። ነገር ግን ወጪው ብዙ ነው፡፡ ያውም

ተጠንቅቀው ነው ገንዘቡን የሚያስተዳድሩት፡፡ ይገርምሻል… ሰው ማኮሮኒ ይዞ ይመጣል፣ ዱቄት ይዞ ይመጣል። በረከቱ

ነው መሰለኝ ተረጂዎቹ ጦማቸውን አድረው አያውቁም፡፡ ቢሆንም አሁንም እርዳታዎቹ ተጠናክረው መቀጠል

አለባቸው፡፡
በመጨረሻ ስለሜቄዶንያና ስለ መስራቹ አቶ ቢኒያም ምን የሚሉት ነገር አለ?
ኦ…ህ ስለ ቢኒያም ለመናገር እቸገራለሁ፡፡ እሁድ ዕለት እንኳን ንግግር ሳደርግ ስሜታዊ ሆኜ ነው ያለቀስኩት፡፡
ቢኒያም የእግዚአብሔር ሰው ነው፡፡ ለእነዚህ የአገር ባለውለታዎችና የአዕምሮ ህሙማን እግዚአብሔር የላከው ሰው ነው፡፡
በእንዲህ አይነት ጊዜ እንዲህ አይነት የተቀደሰ ስራ ለመስራት መመረጥና መታደል ያስፈልጋል። እኛ በእርሱ ዕድሜ

በነበርንበት ጊዜ ድግሪያችንን ይዘን፣ ፔኤች ዲ ይዘን፣ ንብረት አፍርተን፣ ቤት ትዳር ይዘን እያልን ነበር የምናስበው፡፡

እርሱ ግን  እንዴት ጉድጓድ ውስጥ የወደቁትን አንስቼ ያገግሙ እያለ ነው የሚጨነቀው፡፡ ይሄ በእውነት መታደል ነው።

ይህን ወጣት ማንኛውም ሰው ተሯሩጦ ማገዝ አለበት። አቶ ቢንያም እንዳለው “ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን በቂ

ነው”፡፡
አመሰግናለሁ።  

Saturday, 28 December 2013 11:10

የኢትዮ ቴሌኮም ማስተባበያ

           ጋዜጣችሁ ባለፈው ቅዳሜ ታህሳስ 12 ቀን 2006 ዓ.ም እትሙ ላይ፣ “ከዓመት በፊት ለተበላሸ ሲሚንቶ ማስቀመጫ ከ30ሺ ብር በላይ ወርሃዊ ኪራይ ይከፈላል” በሚል ርዕስ ለቀረበው ሚዛናዊ ያልሆነ ዘገባ የሚከተለውን ምላሽ አቅርበናል፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የዜና ዘገባው ሚዛናዊነት የጎደለው ከመሆኑም ባሻገር በሃቅ ላይ ያልተመሰረተ፣ አንባቢን የሚያሳስት እና የኩባንያችንን ገጽታ የሚያጎድፍ ነው፡፡ በዜና ዘገባው መነሻ “በሶማሌ ክልል በጅግጅጋ ከተማ ለቴሌ ታወሮችና የኔትወርክ ግንባታ ከጅቡቲ ተገዝቶ የገባው ሲሚንቶ ከአንድ ዓመት በፊት መበላሸቱ ቢታወቅም በየወሩ ከ30ሺ ብር በላይ ለግለሰቦች ኪራይ እየተከፈለ የህዝብና መንግስት ሀብት እየባከነ እንደሚገኝ---” ሲል የፈጠራ ሃተታውን ይጀምራል፡፡

ኢትዮ ቴሌኮም እንደ ሌሎች የሃገራችን ክልሎች ሁሉ በተለይ በኢትዮጵያ ሱማሌ ክልል በጅግጅጋ ከተማና በክልሉ ባሉ ወረዳዎች የሚያስፈልጉ ግብዓቶች እና ለሌሎች ንብረቶች ማስቀመጫ የሚያገለግል ግምጃ ቤት በከተማዋ ከሚገኝ የግል ድርጅት ተከራይቶ ሲጠቀም መቆየቱና አሁንም እየተጠቀመበት መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዘገባው ተቋሙ መጋዘን መከራየቱ የተገለፀው ትክክል ቢሆንም መጋዘኑ የሚያገለግለው ግን ለሲሚንቶ ማስቀመጫ ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም የቴሌኮም ማስፋፊያ ፕሮጀክቱ ግንባታ የሚያስፈልጉ ግብዓቶችና ቁሳቁሶች ለማስቀመጥ ጭምር ነው፡፡

ምንም እንኳን በዘገባው እንደተገለፀው፣ ከንብረቶቹ መካከል የተበላሹ ሲሚንቶዎች ቢኖሩም መጋዘኑ ግን ለፕሮጀክቶች ሥራ የሚያገለግሉ የተለያዩ ንብረቶች ማኖሪያነት እና ለሌሎች ግብዓቶች ማስቀመጫነት እያገለገለ በመሆኑ፣ በዜናው እንደተጠቆመው ያለ አገልግሎት ለመጋዘኑ በከንቱ ክፍያ እየተፈፀመ እንዳልሆነ ውድ አንባቢያን እንዲረዱልን እንፈልጋለን፡፡ ሌላው የዘገባው ስህተት ደግሞ የወርሃዊ ክፍያ መጠን ላይ ነው፡፡ በዜናው እንደተጠቀሰው፣ ለመጋዘን ኪራይ የሚከፈለው ወርሃዊ ክፍያ 30ሺ ብር ሳይሆን 12,360 ብር ነው፡፡ መጋዘኑ በአሁኑ ሰዓትም በእንቅስቃሴ ላይ ለሚገኘው ለቴሌኮም ማስፋፊያ ፕሮጀክቶችና ለሪጅኑ የኦፕሬሽን ስራ የሚሆኑ ንብረቶች የሚቀመጡበትና ለነዚህ ሥራዎች አገልግሎት እየሰጠ ያለ ሆኖ ሳለ “ጥቅም ላይ ለማይውሉ ሲሚንቶዎችና ብረቶች ያለ አግባብ ኪራይ እየተከፈለ ይገኛል” በሚል መዘገቡ ስህተት ከመሆኑም በላይ የአንድ ወገን መረጃን ብቻ በዋቢነት በመጠቀም ለአንባቢያን የቀረበ በመሆኑ የዘገባውን ሚዛናዊነት ጥያቄ ውስጥ ያስገባል፡፡ በጥቅሉ ዜናው ሲዘገብ መረጃውን ከሚመለከተው አካል ማጣራትና ሚዛናዊ ማድረግ እየተቻለ፣ፍትሃዊ ባልሆነ መልኩ የተሳሳተ መረጃ መቅረቡ አግባብ አይደለም፡፡ የኢትዮ ቴሌኮም ኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን መምሪያ

•    የልማት ሥራዎች ለብዝሐ ሕይወት አስተዋፅኦ ሊኖራቸዋል ይገባል ተብሏል
•    የተከማቸውን አገልጋይ ለማቀፍ የሚያስችል መዋቅርና አደረጃጀት ተዘርግቷል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አድባራትና ገዳማት ልማትን በማስፋፋት

ሐዋርያዊ አገልግሎትን በዘላቂነት ለማከናወን የሚያስችል ሀብትና ንብረት የሚያፈሩበት የልማት ፈንድ ሊያቋቁሙ መኾኑ

ተገለጸ፡፡ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት በሰበካ ጉባኤ ከሚሰበስቡት አስተዋፅኦ ጋራ በልማት መስኮች ለሚያገኙት ገቢ

ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አቅጣጫ መቀመጡን ለአዲስ አድማስ ያስታወቁት የሀ/ስብከቱ ምንጮች÷ ገዳማትና

አድባራት በአንድ የበጀት ዓመት መጨረሻ ለመደበኛ አገልግሎት ከሚመደበው በጀትና መጠባበቂያው ከሚተርፈው

ገንዘብ ስድሳ በመቶውን (60%) የልማት ፈንድ እንዲያቋቁሙበት የሚያስችል ጥናት መቅረቡን ገልጸዋል፡፡  

ገዳማቱና አድባራቱ በልማት ሥራዎች የሚያገኙት ገቢ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን  ያስረዱት ምንጮቹ÷ በሒሳብ

አያያዝ ፖሊሲውና ዝርዝር የአፈጻጸሙ መመሪያው መሠረት የሚመሠርቱት የልማት ፈንድ የልማት ተቋማትን

በማቋቋምና በማስፋፋት አብያተ ክርስቲያናቱን ከልመና ለማውጣት፣ የካህናትንና ሊቃውንትን የኑሮ ኹኔታ ለማሻሻልና

የገጠር አብያተ ክርስቲያናትን በዘላቂነት ከመደገፍ ጀምሮ የምግባረ ሠናይ ተግባራትን በስፋት ለማከናወን

እንደሚያገለግል ተናግረዋል፡፡

በልማት ፈንዱ የሚቋቋሙና የሚስፋፋፉ ነባርና አዲስ የልማት ሥራዎችና የምግባረ ሠናይ ተግባራት የሚመሩበት

ፖሊሲና መመሪያም ስለመረቀቁ በምንጮቹ ገለጻ ተጠቁሟል፡፡ የልማት ተቋማቱ የቤተ ክርስቲያኒቱ ዋነኛ ተልእኮ

የኾነውን ሐዋርያዊ አገልግሎትዋን በከተማና በገጠር የማፋጠንና የመደገፍ፣ የምግባረ ሠናይ ድርጅቶቿን በቋሚ የገንዘብ

ምንጭነት የማገልገል አስፈላጊነት እንዳላቸው በፖሊሲው ተዘርዝሯል፡፡
ፖሊሲው ለልማት ተቋማቱ ባስቀመጣቸው መርሖዎች መሠረት÷ በምሥረታና ማስፋፋት ወቅት ለቤተ ክርስቲያን

ምስጢራዊ አገልግሎት እንደ ግብዓት የሚያገልግሉ ዕቃዎችን ለማምረትና ለማከፋፈል ቅድሚያ መስጠት የሚጠበቅባቸው

ሲኾን ተቋማቱ የሚያመርቷቸውና የሚያከፋፍሏቸው ንዋያተ ቅድሳት፣ የኅትመት ውጤቶች፣ የምስል ወድምፅ ሥራዎችና

የመሳሰሉት ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዶግማና ሥርዐት፣ ከማኅበረሰቡ ኢትዮጵያዊ ማንነትና ትውፊት አንጻር ታሳቢ

መደረጋቸው መፈተሽና መረጋገጥ እንደሚኖርበት ተመልክቷል፡፡
ፖሊሲው የተፈቀዱ ናቸው የሚላቸው የልማት ተቋማት ለብዝኃ ሕይወት አዎንታዊ አስተዋፅኦ ሊኖራቸው እንደሚገባ፣

በዕውቀቱ የበለጸገ፣ በሥነ ምግባሩ የታነጸ ትውልድ ለማፍራት ትኩረት ሰጥተው መሥራት እንደሚያስፈልጋቸው

በመርሖው አስቀምጧል፡፡ ከተቋማቱ ዝርዝር ውስጥም ኮሌጆችና ማሠልጠኛዎች፣ ማተሚያ ቤቶች፣ የጉዞና አስጎብኚ

ድርጅት በማቋቋም የሆቴልና ቱሪዝም አገልግሎት መስጠት፣ ክሊኒኮችን፣ ሆስፒታሎችንና ፋርሚሲዎችን በማቋቋም

የሕክምና የሕክምና አገልግሎት መስጠትና መድኃኒቶችን ማከፋፈል፣ የግንባታ ቁሳቁሶችን ማቅረብ፣ ለአገልግሎትና ኪራይ

የሚውሉ ሕንጻዎችን መገንባትና ማከራየት፣ ከውጭ የሚገቡ ንዋያተ ቅድሳትን በመተካት የውጭ ምንዛሬ ማዳንና ወደ

ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሬ ማስገኘት፣ የግብርና ውጤቶችን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ ማቅረብ፣ የፋይናንስ ተቋም

አክስዮን መግዛት፣ የመንግሥት የግምጃ ቤት ሰነድና ቦንድ መግዛት ይገኙበታል፡፡
ገዳማትና አድባራት በራሳቸው አልያም በመቀናጀት ተቋማቱን መመሥረት እንደሚችሉ በመርሖው የተገለጸ ሲኾን

ቅንጅቱም አጥቢያ አብያተ ክርስቲያኒቱ ከሌሎች አጥቢያዎች ጋራ፣ አጥቢያዎች ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ጋራ እንዲሁም

ሀ/ስብከቱና አጥቢያዎቹ ከሌሎች አህጉረ ስብከትና አጥቢያዎቻቸው ጋራ ሊከናወን የሚችልበት የፕሮጀክት አጸዳደቅና

አተገባበር ሥርዐት ማካተቱ ተገልጧል፡፡
በልማት ፈንዱ የሚቋቋሙና የሚስፋፉ ተቋማት ካህናትና ሊቃውንት ከመደበኛ ተግባራቸው  በተጨማሪ

እንደየዝንባሌያቸው በተለያዩ ክሂሎቶች እየሠለጠኑ እንዲሠማሩ በማስቻል የሥራ ዕድል እንደሚፈጥሩላቸው፣

በአገልግሎታቸውም እንዲበረቱ ተገቢውን በማሟላት አስተዋፅኦ እንደሚያደርጉላቸው ታምኖባቸዋል፡፡ የልማት ተቋማቱ

ወደፊት በሀ/ስብከቱ እንደአስፈላጊነቱ ከሚተከሉት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ጋራም ተነጻጻሪ መስፋፋት

እንደሚኖራቸው ተጠቁሟል፡፡

የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት 169 በሚደርሱት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ ባሰራጨው ቅጽ እየሰበሰበው የሚገኘው

የአገልጋዮች ጠቅላላ መረጃ፣ በአሁኑ ወቅት አድባራቱና ገዳማቱ ልዩ ልዩ ክህሎትና ልምድ ያላቸው አገልጋዮች

እንዳሉባቸው የሚያመላክቱ ናቸው ያሉት ምንጮቹ÷ ይህም ለልማት ተቋማቱ ከሚፈጥረው የሰው ኃይል አቅም ባሻገር

የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርት ከዘመናዊው ሞያ ጋራ በአቻ ግመታ በማስቀመጥ በአምስቱ የአጥቢያ አብያተ ቤተ

ክርስቲያናት መዋቅርና አደረጃጀት ውስጥ በሚሠራው የሰው ኃይል ትመናና ምደባ በርካታ የአገልጋይ ቁጥር ለማስተናገድ

እንደሚያስችል ተመልክቷል፡፡

“ጋዜጠኞች ታስረዋል አልታሰሩም?”

      ከአዘጋጁ- ባለፈው ሳምንት በኒውዮርክ የሚገኘው የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት (CPJ) ባወጣው ዓመታዊ ሪፖርቱ ጋዜጠኞችን በማሰርና በማሰቃየት ኤርትራን በቀዳሚነት በማስቀመጥ ኢትዮጵያንና ግብፅን በሁለተኛነትና በሦስተኛነት ደረጃ ላይ አስቀምጧቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በተደጋጋሚ “ከጋዜጠኝነት ሙያው ጋር በተያያዘ ያሰርኩት አንድም ጋዜጠኛ የለም፤ በእስር ላይ ያሉት በሽብርተኝነት ተፈርዶባቸው የታሰሩ ናቸው” ቢልም ሲፒጄ ግን በሽብር ሽፋን ለእስር የተዳረጉ ጋዜጠኞች እንደሆኑ በሪፖርቱ ገልጿል፡፡ በአገሪቱ ያለውን የፕሬስ ነፃነት ሁኔታ አጥብቆ የሚተቸው የጋዜጠኞች መብት ተሟጋቹ ሲፒጄ፤ ከመንግስት በደረሰባቸው ማስፈራሪያና ወከባ በርካታ ጋዜጠኞች ለስደት እንደተዳረጉ ሲገልፅ ቆይቷል፡፡ ድርጅቱ ባለፈው ሳምንት ይፋ ያደረገውን ሪፖርት አስመልክቶ የመንግስት ባለሥልጣን፣ የጋዜጠኞች ማህበር አመራሮችና የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ በማነጋገር የሰጡትን አስተያየት እንደሚከተለው አጠናቅረን አቅርበነዋል፡፡

“ሲፒጄ ፖለቲካዊ አጀንዳ ያለው ነው”

(አቶ ሽመልስ ከማል፤ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ) በመጀመሪያ ሲፒጄ የኢትዮጵያ ጋዜጠኝነት እንዲያድግና እንዲስፋፋ አይፈልግም፡፡ ፖለቲካዊ አጀንዳ ያለው፣ መንግስት በኃይል ለመለወጥ ከሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች ጋር የሚንቀሳቀስ፣ በጋዜጠኝነት ታፔላ ድጋፍ የሚሰጥ ድርጅት ነው። ሥራው ከጋዜጠኝነት ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፤ ከእርሱ ጋር ከሚጠቃቀሱት አንዱ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ነው፡፡ አምነስቲ ሲፒጄን፣ ሲፒጄ አምነስቲን --- እርስ በእርስ እየተጠቃቀሱ፣ አንዳቸው ያንዳቸውን የፈጠራ ውሸት እየያዙ፣ የአገራችንን ስም ሊያበላሹ የሚጮሁ፣ ስነምግባር የሌላቸው ተቋማት ናቸው፡፡ እናውቃለን… የፖለቲካ አጀንዳ እንዳላቸው። ሁለተኛ በኢትዮጵያ የትኛው ጋዜጠኛ ነው የታሰረው? እንግዲህ እናንተም የምትኖሩባት አገር ናት፤ እናንተ መቼ ታሰራችሁ? የማታውቁት ከማርስ የመጣ የታሰረ ጋዜጠኛ አለ እንዴ ? ከቁጥሩ ብዛት ኢትዮጵያን ከአለም ሁለተኛ ሊያስብላት የሚችል---? እንዲህ ነው--- እነ ዳንኤል በቀለ እየፈተፈቱ ሲሰጧችሁ የምትቀበሉት!! የሂውማን ራይትስዎች የአፍሪካ ዴስክ ሃላፊ ዳንኤል በቀለ፣ የቅንጅት መሪ ነበረ፡፡ በ97 በሰብአዊ መብት ድርጅት ስም መንግስት ለመገልበጥ ሲሰራ ተፈርዶበት በምህረት የወጣ ነው፡፡ ይሄ ግለሰብ መንግስት ለመገልበጥ አንዴ የጋዜጠኛ ማህበር አቋቁሙ እያለ ቅስቀሳ ያደርጋል፡፡ በየትም በየትም ብሎ ይህንን መንግስት በብረትድስት ከትቶ በምድጃው ላይ መጣድ ነው የሚፈልገው፡፡ ገለልተኛነት በሌላቸውና ችግር ላይ በወደቁ ግለሰቦች የሚፃፉ አስተያየቶችን በመፃፍ የእነሱ መሳሪያ አትሁኑ፡፡ ኢትዮጵያ በጋዜጠኝነት ያሰረችው አንድም ጋዜጠኛ የለም፤ ካለ ይምጣና “እኔ በጋዜጠኝነት ስራዬ ምክንያት ታስሬአለሁ” ይበል፡፡ ግን በጋዜጠኝነት ምክንያት የታሰረ የለም።

ቆይ የሚታመነው ማነው? የኢትዮጵያ ፍርድ ቤት ነው ወይስ ሲፒጄ? የኢትዮጵያ ፍርድቤት ርዕዮት አለሙ ላይ ፅፋ ነው የፈረድኩባት አላለም፡፡ በፃፈው ተፈርዶበት የታሰረ አለ ከተባለ ዶክመንቶችን ማገላበጥ ያስፈልጋል፡፡ ማንም ደግሞ አልታሰረም። ይህ አልሆነም፡፡ ከምላሴ ላይ ፀጉር ይነቀላል፡፡ ሲፒጄ ስላጨበጨበ፣ ዳንኤል ስለጮኸ እና ብሩን ስለበተነ፣ የግንቦት ሰባት መፅሄቶች ስለጮሁ እውነቱ ተገልብጦ ይቀርባል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያላችሁ ጋዜጠኞች ታያላችሁ፣ ትሰማላችሁ፣ ታገናዝባላችሁ፣ እስኪ በፃፈው ፅሁፍ ታሰርኩ የሚል ካለ አምጡ፡፡ የሲፒጄ ቃል የሙሴ ቃል አይደለም፤ ለምን እንደ ጣኦት ታመልኩታላችሁ? በጣም እምናዝነው---- እዚህ አገር ያሉ በሳል ጋዜጦች ላይ እንዲህ አይነት ነገሮች መፃፋቸው ነው፤ የዚህ ዘመቻ ሰለባዎች መሆናቸው ያሳዝነናል፡፡ ይሄ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ነው፤ “መንግስት ከቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ህልፈት በኋላ አቋሙን ይቀይራል” ብለው ትንሽ ፋታ እንስጠው በማለት ለትንሽ ጊዜ ያቆሙት ነገር እንጂ ከዚህ በፊትም ሲያወሩት የነበረ ነው፡፡ ሲፒጄ እድሜውን ሁሉ መግለጫ ሲያወጣ፣እኛም መልስ ስንሰጥበት ነው የኖርነው፡፡ አዲስ አይደለም፡፡ ሲፒጄ መቼ ነው ስለኢትዮጵያ መልካም ነገር ተናግሮ የሚያውቀው? በፕሬስ ህጉ ላይ ሳይቀር “ኑ ና እንነጋገር” ብለናቸው ሽሽት ነው የመረጡት፡፡

ስለዚህ ሲፒጄ በኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ላይ የተሰነዘረ ስድብ ነው፡፡ እንዲህ የሚያደርገው ኢትዮጵያ ውስጥ ጋዜጠኝነት የለም ብሎ ስለሚያምን ነው፡፡ እግራቸው ሸብረክ ሲል ወንበር የሚያቀርቡላቸው በጋዜጠኝነት ስም የሚነግዱ አሉ፡፡ እነሱን ስለለመደ ሌሎቹን እንደ ባለሙያ አይቆጥርም፤ ስለዚህ ኒውዮርክ ውስጥ ቁጭ ብሎ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰቃየትና በማሰር ከአለም ሁለተኛ ነች ይላል - እናንተ አፍንጫው ስር ቁጭ ብላችሁ፡፡ ፈረንጅ የተናገረው ሁሉ ለምንድነው እንዳለ የሚወሰደው? ሁሌም አምኖ መቀበል ነው እንጂ ጉዳዩን ለማጣራት ሲሞከር አይታይም፡፡ “ሲፒጄ የወሮበሎች ቡድን ነው” (የኢብጋህ ፕሬዚዳንት፤አቶ አንተነህ አብርሃም) ሲፒጄ ኢትዮጵያን በተመለከተ ባወጣው ሪፖርት ላይ የማህበርዎም ሆነ የእርሶ አቋም ምንድነው? ሲፒጄ ያወጣው የተዛባ መረጃ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በአለም በምንም ሁለተኛ አይደለችም፡፡ የሀገራችንን ስም ለማጥፋት ስለሚፈልግ ነው፤ ምክንያቱም ድርጅቱ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ከፍተኛ የሆነ የጥቅም ችግር ያለበት ነው፡፡ የሦስት እስረኛ ጋዜጠኞችን ቁጥር ከፍ አድርጐ ማውራት ምንም አይጠቅምም፡፡ እነሱም የታሰሩት በአሸባሪነት ተጠርጥረው ነው እንጂ በጋዜጠኝነታቸው በፃፉት ፅሁፍ አይደለም፡፡ ሲፒጄ እውነተኛ ከሆነ ቱርክ ስለታሰሩት 64 ጋዜጠኞች ለምን አያወራም፡፡ ግን በማያገባው ነው የሚገባው፡፡ ሲፒጄ፤ በእስር ላይ ያሉት ጋዜጠኞች በአሸባሪነት ነው የታሰሩት የሚለውን እንደማይቀበል ይገልፃል። እርስዎ በታሰሩት ጋዜጠኞች ዙርያ አቋምዎ ምንድነው? የታሰሩ ጋዜጠኞች አሉ፤ ግን የታሰሩት በፃፉት ፅሁፍ አይደለም፡፡

ማህበራችሁ ለየትኞቹ ጋዜጠኞች መብት ነው የቆመው? እስካሁን የታሰሩ ጋዜጠኞችን ለማስፈታት ጥረት አድርጓል? እኛ የምንቆመው ከሙያ ጋር በተያያዘ ለታሰረ ጋዜጠኛ ነው፡፡ በፃፈው ፅሁፍ የተነሳ የሚታሰር ጋዜጠኛን ወዲያው እናስፈታለን፡፡ የማህበራችሁ አባላት የየትኛው ሚዲያ ጋዜጠኞች ናቸው ? ምን ያህል አባላትስ አላችሁ? የግልም የመንግስትም ጋዜጠኞች አባሎቻችን ናቸው፡፡ በአጠቃላይ 600 አባላት አሉን፡፡ ከአገር ውጪ የምስራቅ አፍሪካ ጋዜጠኞች ምክትል ፕሬዚዳንት ነን፡፡ እኛ በማውገዝ አናምንም፤ በውይይት እንጂ፡፡ በአሁኑ ሰአት የጋዜጠኞች እስር ቆሟል፤ ይህም የሆነው በኛ ጥረት ነው፡፡ የ“ኢትዮ ምህዳር” ጋዜጠኞች ከጥቂት ወራት በፊት ተከሰው አዋሳ በሄዱ ጊዜ አንደኛው ባልደረባቸው ላይ ከፍተኛ አደጋ ደርሶበታል፡፡ እነዚሁ ጋዜጠኞች ለገጣፎ ለሁለትና ለሶስት ቀናትም ታስረው ነበር፡፡ ነገር ግን የትኛውም የጋዜጠኞች ማህበር እንዳልጎበኛቸው ነግረውናል…ማህበራችሁ ለየትኞቹ ጋዜጠኞች መብት ነው የሚቆመው? መታሰራቸውንም መከሰሳቸውንም በጋዜጣቸው ላይ ሲፅፉ ነው የምንሰማው እንጂ ለኛ መጥቶ የነገረን የለም፡፡ አደጋ ደረሰበት ስላልሽው ልጅም ጓደኞቹ ወይም ቤተሰብ ከጠየቀን እንረዳለን፣ ካልጠየቀን ግን በስሙ እርዳታ አንለምንም፡፡ ማንም ጋዜጠኛ ታስሮ ወደ የትም ክልል እንዳይወሰድ ከመንግስት ባለስልጣናት ጋር ተነጋግረን መተማመን ላይ ደርሰናል፡፡ የጋዜጠኞች ማህበር እንደመሆናችሁ ከሲፒጄ ጋር ለመወያየት የሞከራችሁበት አጋጣሚ አለ? ሲፒጄ የወሮበሎች ቡድን ነው፤ የተወሰኑ ወሮበሎች ተሰብስበው ያቋቋሙት ነው፤ ጋዜጠኞችን እንወክላለን ብለው ገንዘብ ለመሰብሰብ የተቀመጡ ናቸው፡፡ ውብሸትን ለማስፈታት እንኳን እንቅፋት ሆነውብናል፡፡ ውብሸትን ለማስፈታት ሞክራችሁ ነበር ? አዎ! ይቅርታ ጠይቅ ብለነው ጠይቋል፤ በሱ ስም ግን ሲፔጂ መግለጫ እያወጣ ስራችንን አስተጓጉሎብናል፡፡ ሲፒጄ መግለጫ የሚያወጣው ለኢትዮጵያ ጋዜጠኞች አስቦ አይደለም፤ ኢትዮጵያን ለማጥቃት ነው፡፡

ብዙ በደል የሚደርስባቸውን የሌላ አገር ጋዜጠኞች ትቶ፣ ስለማያገባው ያወራል እንጂ እኛ በመወያየት ስራችንን እየሰራን ነው፡፡ የጋዜጠኞች መታሰርን አስቁመናል፤ ይህ የሆነው በኛ ጥረት ነው፡፡ “መንግስት ጋዜጠኞችን እንደሚያስር እስር ቤት ሄዶ ማየት ይቻላል” (ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ የመድረክ አመራር አባል) ለመሆኑ እዚህ አገር የጋዜጠኞች ማህበር አለ እንዴ? መንግስት ጋዜጠኞችን እንደሚያስርና እንደሚያንገላታ ለማወቅ እስር ቤት ሄዶ ማየት ይቻላል፡፡ ጋዜጠኞቹ ራሣቸው ታስረው ፍርድ ቤት ሲቀርቡ ስለነበር፣ አይኔን የበሬ ግንባር ያድርገው ካልተባለ በስተቀር ነገሩ አከራካሪ አይደለም። መንግስት እንደተለመደው የታሠረ ፖለቲከኛም ጋዜጠኛም የለም የሚለው ቀልድ ካልሆነ በቀር እነ እስክንድር፣ ውብሸትና ርዕዮትን የመሣሠሉት ታስረው እኮ ነው ያሉት፡፡ እነዚህ ሠዎች እኮ ሽጉጥ ሲሠርቁ አልታሠሩም፡፡ መንግስት፤ ጋዜጠኞቹ የታሠሩት በፃፉት አይደለም በማለት የሚናገረው ነገር መራር ቀልድ ነው፤ ዝም ብሎ “የሌባ አይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ” አይነት ነገር ነው እንጂ ሠዎቹ ጋዜጠኞች መሆናቸውና የነፃ ጋዜጣ ባለቤትና አዘጋጅም እንደነበሩ በሚገባ ይታወቃል፡፡ ከ97 ዓ.ም በኋላ እኮ መንግስት በግልፅ ጋዜጠኞች ላይ ጫና እያሣረፈባቸው ነው፡፡ ነፃ ጋዜጦች የሚኖሩት የፖለቲካ ምህዳሩ ሲሠፋ ነው፤ የፖለቲካ ምህዳሩ ደግሞ ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ የተዳፈነ ነው፡፡

“ሲፒጄ ሪፖርቱን ሲያወጣ የራሱ የሆነ ተልዕኮ አለው” (የኢነጋማ ሊቀመንበር፤ አቶ ወንደወሰን መኮንን) ባለፈው ሳምንት ሲፒጄ ባወጣው ሪፖርት፤ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰር ከአስር ሃገራት መካከል ሁለተኛ እንደሆነች ገልጿል፡፡ የጋዜጠኞችን እስር በተመለከተ የማህበራችሁ አቋም ምንድነው? ጋዜጠኞች ይታሰሩ የሚል አቋም መቼም ቢሆን ሊኖረን አይችልም፡፡ የታሰሩ ጋዜጠኞች ካሉ ጉዳያቸው ታይቶ መንግስት መፍታት አለበት የሚል አቋም ነው ያለን፡፡ ሲፒጄ ግን ይሄንን ሪፖርት ሲያወጣ የራሱ የሆነ ተልዕኮ አለው፡፡ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰር ሁለተኛ ናት ብሏል፡፡ ይሄ ከዚህ በፊትም ሆኖ የማያውቅ ግነት ነው፡፡ የታሰረ የለም። ለአፍሪካ ሚዲያ ፎረም ጉባኤ ወደ አዲስ አበባ በመጡ ጊዜ እንደ አዲስ ነው ዘመቻ የተከፈተው፡፡ በአጭሩ ግን የኢትዮጵያ መንግስት ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶት … ሁኔታውን አጢኖ የታሰሩ ጋዜጠኞችን ቢፈታ በጣም ደስተኞች ነን፡፡ ማህበርዎ ኢነጋማ ስንት አባላት አሉት? ለጋዜጠኞች መብት መከበር ያደረጋችሁት እንቅስቃሴስ ምን ይመስላል ? እኛ ከዚህ በፊትም ትግል ስናደርግ ነው የኖርነው፣ አሁንም እያደረግን ነው ያለነው፡፡ አባላት አሁን አሉ ከሚባሉትም በላይ በዚህ ሂደት ውስጥ የሚታወቅና የተለየ ስፍራ አለን ብለን ነው የምናምነው፡፡ እንደ በፊቱ የመንግስትና የግል ጋዜጠኛ የሚባል ነገር የለም፤ ያንን አንኮታኩተን ጥለነዋል፡፡ ሙያው አንድ ነው፤ ይሄንን ልዩነት የፈጠሩት እርስ በርስ ሲያባሉ የነበሩና የተለየ የፖለቲካ ተልኮ ያላቸው ሃይሎች ናቸው፡፡ እነሱ ደግሞ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከጨዋታ ውጪ ሆነዋል፡፡ ከጀርባቸው የተለየ ተልዕኮ ያላቸው ናቸው፡፡ ጋዜጠኛውን እርስ በርስ ሲያባሉ ቆይተዋል፤ አሁንም እያባሉት ይገኛሉ። ይሄንን እኔ አልቀበለውም፤ ጋዜጠኞች ሙያውን ከፖለቲካ ነፃ ሆነው መስራት አለባቸው፡፡ ጋዜጠኛው ተቀራርቦ በራሱ ጉዳይ መምከር አለበት፡፡ ጋዜጠኞች በነፃነት መስራት፣ ሃሳባቸውን መግለፅ፣ በተጨባጭ ማስረጃዎች ላይ ተመርኩዘው መተቸት አለባቸው። የሕዝብ ጥያቄ በሚመልሱበት ሰዓት በአግባቡ የመከላከል፣ የመከራከር፣ ድምፃቸውን የማሰማት መብት አላቸው፡፡

በእኛ በኩል በመንግስት፣ በግልና በኮሙዩኒኬሽን ቦታ ላይ ያሉ የሚዲያ አባላቶችን ይዘን፤ ከተወሰኑ ወራት በኋላ ጠቅላላ ጉባዔ እናደርጋለን፤ ለውጦችም ይኖራሉ፡፡ እኛ የፖለቲካ መጠቀሚያ አይደለንም፣ የትኛውንም የፖለቲካ አቋም አናስተጋባም፤ የመንግስትንም ሆነ የተቃዋሚውን። በነፃነት ሃሳባችንን በመግለፃችን ነው ውርጅብኝ ሲወርድብን የኖረው፡፡ ይሄንን ደግሞ እናውቀዋለን፡፡ ማህበራችሁ ከተቋቋመ ጊዜ አንስቶ ለመብቱ የተከራከራችሁለት ጋዜጠኛ አለ? ከተቋቋመ ጊዜ ጀምሮ ላልሽው ---- እንናገረው ብንል መፅሃፍ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ተሰሚነት የነበረው በአገር ውስጥም ሆነ በአለማቀፍ ደረጃ ኢነጋማ ነው፤ እሱ አከራካሪ አይደለም፡፡ ነገር ግን የቀድሞው አመራሮች በሚዲያው ውስጥ በነበረው የእርስ በርስ ትግል አዳክመው፣ ገለውት ነው የሄዱት። ዛሬም በአሜሪካና በአውሮፓ ሆነው “ኢነጋማ አለ” እያሉ መግለጫ እያወጡ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ ከሙያው ጋር በተያያዘ የታሰረ ጋዜጠኛ የለም። የታሰሩት በሌላ ጉዳይ ነው፤ ቢሆንም መፈታት አለባቸው ብለን እናምናለን፤ ነገር ግን መግለጫ አናወጣም፡፡ መግለጫ መስጠትም አይቻልም። ጋዜጠኛው ከሌላ አካል ከመጠበቅ ይልቅ በአንድ ላይ ሆኖ ለመብቱ መቆም አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ የሚያስፈልገው ተቀራርቦ በመነጋገር ችግሮችን መፍታት ብቻ ነው፡፡ በተለያየ ጎራ ሆኖ መተቻቸቱ ፋይዳ የለውም፡፡ በአሁኑ ጊዜ ሶስት “ነፃና ገለልተኛ ነን” የሚሉ የጋዜጠኞች ማህበራት አሉ፡፡ በቅርቡ ደግሞ አዲስ የጋዜጠኛ ማህበር ለማቋቋም እንቅስቃሴ የጀመሩ ወገኖች አሉ፡፡ አዲሱን ማህበር በተመለከተ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው? ሊቋቋሙ ይችላሉ መብታቸው ነው፡፡ ነገር ግን እነማ ናቸው የሚያቋቁሙት፣ እንዴት ነው የሚቋቋሙት፣ ከጀርባ እነማን አሉ ---- ይሄን ጠንቅቀን እናውቀዋለን፡፡ ትልቅ ጉዳይ አይደለም፤ ኖረንበታል፡፡ ለእኛ አዲስ ነገር አይደለም፡፡

ከአዲሱ ጠ/ሚኒስትር አዲስ ራዕይ እንፈልጋለን

“የራበው ሥራ ፈልጐ ማግኘት የማይችልና ልጆቹን ለማስተማር አቅም ያጣ ሰው ከባርነት ነፃ ነው ማለት አይቻልም፡፡” የሚለው የአሜሪካዊው ፕሬዚዳንት ሊንደን ቢ. ጆንሰን ንግግር እውነትነት አሁን አሁን በጆሮዬ መደወሉ ራሴን እያስገረመኝ መጥቷል፡፡ የዛሬ አምስትና ስድስት ዓመት ገደማ ደራሲና ጋዜጠኛ አለማየሁ ገላጋይ፤ ስለኑሮ ውድነት ሲጽፍ ብዙዎቻችን እያነበብን ፈገግ ከማለት በቀር ብዙ ልባችን አልተነካም ነበር፡፡ ምናልባትም በጣም አልፎ አልፎ ከምናነባቸው መጣጥፎች ይልቅ መንግስት ስለ ልማት የሚነፋው ጥሩንባ አደናቁሮን ይሆናል፡፡ አሁን አሁን የመንግሥት መዝገበ ቃላት “ልማት” የሚለው ትርጓሜ ግራ እያጋባን መጥቶ ጭራሽ ወደ ብስጭት የተመነዘረብን ብዙ ነን ብዬ አስባለሁ፡፡ መንግስት ልማት የሚለው ከእኛ አፍ “ቫት” እያለ የሚነጥቃትን ገንዘብ ሰብስቦ ለሌቦች ካጠገበ በኋላ፣ በፍርፋሪዋ የሚሠራትን መንገድና ጤና ጣቢያ ወይም ትምህርት ቤት ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ “ኮንደሚኒየም”እየተባሉ የተሠሩት ቤቶች አካባቢ ያለውን ግድየለሽነት ተመልከቱ፡፡ የውሃ መፍሰሻ ቦዮቹ ገና ተሠርተው ሳያልቁ ይፈርሣሉ። ሕንፃው ውስጥ ያሉትን የግብር ይውጣ ሥራዎች ተውአቸው፡፡ ለመሆኑ ልማትና ዕድገት ምንድነው? ወረቀት ላይ የሃሰት ሪፖርቶችን ከምሮ መቀለድ ነው። ቀልድና ውሸትስ እስከ የት ያዘልቀናል? ከወር ወደ ወር ሰዎች በልተው የማደር አቅማቸውን እያጡ፣ ልጆቻቸውን ማስተማር ተራራ መቧጠጥ እየሆነባቸው ሲመጣ --- እንዴት ስለ ዕድገት ይወራል? ጋዜጠኛ መሳይ ካድሬዎች ስለልማትና እድገት ብዙ ቢለፈልፉም ከሕዝቡ የበለጠ ጓዳውን የሚያውቅ ማንም ሊኖር አይችልም፡፡ አለ ቢባልም ከተራ ቀልድነት አያልፍም፡፡ እርግጥ ነው፤ ባለፉት ሃያ ዓመታት ጥቂት ሰዎች በኑሯቸው አድገው ይሆናል፤ ለስላሳ መጠጣት የማይችሉ ዛሬ ቤታቸው ውስኪ ደርድረው የሚመርጡበት ዕድል ደርሷቸው ይሆናል፡፡ያ ግን ዕድገት አይደለም፡፡ የማሕበረሰብ ሳይንስ ምሁራን የዕድገትና ልማትን ዓላማዎች እንዲህ ያስቀምጡታል - የሕዝቡን የገቢ መጠን በፍጥነት ማሳደግ ለዜጐች የሥራ ዕድልን መፍጠር መሠረታዊ የሆኑ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፍላጐቶችን ማርካት፤ ማህበራዊ ፍትህን ማስፈን ሥራንና የቁጠባ ባህልን በሕብረተሰቡ ማስረጽ መልካም አስተዳደርና አሣታፊ የሆነ የፖለቲካ
ምህዳር መፍጠር ከላይ የተጠቀሱትና ሌሎችም ተጨማሪ ነጥቦች የአንዲት ሀገርንና ሕዝብን ዕድገት መንገድ የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ በሀገራችን ያለው ተጨባጭ ሁኔታ ከዚህ በተቃራኒ የቆመ ይመስላል፡፡ ምናልባት የማይካድ ለውጥ አምጥቷል ብለን የምንወስደው ሕብረተሰቡ በሥራ ላይ ያለውን አመለካከት በመጠኑ መቀየር መቻሉ ነው፡፡ ቁጠባውንም በውድም ሆነ በግድ በየሰበቡ ለማስለመድ የሚደረገው ጥረት የሚናቅ አይደለም፡፡ የፖለቲካው አሣታፊነት ጉዳይ የሕፃን ልጅ ዕቃ ዕቃን የመሰለ ቀልድ ስለሆነ ጉዳዩ ለሰለቸው አንባቢ ይህን አንስቶ እንዲህና እንዲያ ማለት እንደ ደንቆሮ መቁጠር ሊመስልብኝ ይችላል፡፡ ጠቃሚ ባህሎችን ማሳደግ በሚለውም መሥመር እያንዳንዱ ብሔር ብሔረሰብና ሕዝብ (በመንግስት መሠረት) ሥነ ጽሑፉንና ባህሉን ማሳደጉን እኔ በግሌ እደግፈዋለሁ፡፡ ልክ ነው ብዬም አምናለሁ፡፡ አንዱ በባህሉ እየኮራ፣ ሌላው እያፈረ የሚደበቅባት ሀገር አሁንም እኩልነት የጐደላት ስለሆነች ያንን ሕልም ማለም ጠባብነት ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ የሚያሣዝነው ግን በዚህ በጐሣ በተከፋፈለ ከለላና አስተዳደር ምክንያት የተፈጠሩት
ጥላቻዎች ማርከሻ መድሃኒት ማጣታቸው ነው፡፡ መሪዎቻችን በወጣትነት መንፈስ በስሜታዊነት ያደረጉትን ነገር ምራቅ ሲውጡ እንኳን ለማስተካከል ያለመቅናታቸው የሚገርም ነው፡፡ ለዚህ ሃሳብ ዋቢ የሚሆነኝን አንድ ሃሳብ ወደኋላ መለስ ብዬ ሕዳር 18 ቀን፣ አንድ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ በዶክተር እሸቱ ጮሌ አዳራሽ፣ ለዶ/ር ፋሲል ናሆም (ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ) ያቀረበውን ጥያቄ ልጥቀስ፡፡ተማሪው የተወለደበትን ክልል ጠቅሶ፣ በክልሉ ዋና ከተማ የሚኖሩ የሌላ ብሔር ተወላጆች ሀገራቸው እስከማይመስላቸው ድረስ በደል እየተፈፀመባቸው እንደሆነ ገልፆ፣ መንግስት ለ “minority” ምን መፍትሔ አለው ሲል ጠይቆ ነበር፡፡ በሌላ አንፃር ደግሞ ያ ተማሪ እኖርበታለሁ ወይም ተወልጄበት ግን የዜግነት መብት አላገኘሁም የሚልበት ክልል ተወላጅ የሆነ ሌላ ተማሪ ተነስቶ፣ ችግሩ የሚታየው የቀደመው ተማሪ በጠየቀበት ክልል ብቻ ሣይሆን በሁሉም የሀገሪቱ ክልሎች መሆኑን ጠቅሶ፣ ሥራ ለመቀጠርም ሆነ ለሌላ ጉዳይ ዘር መቁጠር ግድ ስለሆነ፣ ችግሩን መፍታት ያለብን ሁላችንም ነን ብሎ ደመደመ፡፡ እኔ ግን በሁለተኛው ተማሪ ሃሳብ አልስማማም፤ ችግሩን ለመፍታት እኛ ድርሻ ቢኖረንም የአንበሳው ድርሻ ግን የመንግስት ነው፡፡ ስለዚህ መንግስት ለዚህ ነቀርሣ መፍትሔ መፈለግ አለበት፤ ሰው በገዛ ሀገሩ ባዕድ እየሆነና እየተገፋ መኖሩ የሚያመጣው ልማት ፈፅሞ ግልጽ አይደለም፡፡ ለመሆኑ መንግስት ማለትስ የሰዎች ስብስብ አይደለም እንዴ? እንዴት ይህንን ነገር ማሰብ ያቅተዋል? ባለሥልጣን ሲኮን ተከትሎ የሚመጣው አጃቢ ወታደር፣ ያበጠ ወንበር--- የነገን ጉዳይ ያዘናጋልና መሪዎቻችንም ሊያስቡበት የሚገባ ይመስለኛል። አብዛኛው ሕዝባችን ከእጅ ወደ አፍ እንኳን ኑሮ እያቃተው ከመጣ፤ የመኖር ዕድሉ እየጠበበ ከሄደ ሊፈጠር የሚችለው ነገር ምንድነው ብሎም ማሰብ ደግ ይመስለኛል፡፡ የኢሕአዴግ አማካሪዎች ምናልባት እውነት የማይናገሩ አሸርጋጆች እንዳይሆኑ እሠጋለሁ። ሕዝቡ እየተራበ

“ጠግቧል”፣ እየተማረረ “ደስተኛ ነው” እያሉ ከሆነ ፍፃሜው አያምርም። በርግጥ እኛ ሥልጣን የሌለን አስበን ምንም አናመጣም፣ ሥልጣን ያላቸው ናቸው ለችግሩ መቋጫ መፍትሄ ሊያበጁለት የሚገባቸው፡፡አዲሱም ጠቅላይ ሚኒስትር ቢሆኑ ሁልጊዜ የታላቁ መሪያችንን መዝሙር ከመዘመር ይልቅ አዲስ መዝሙርና ራዕይ ለመፍጠር መሞከር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ቶማስ ጀፈርሰን፤ ሁሉም ሰው የየራሱ ዘመን አለው፣ በሕይወት የሌለ ሰው በሕያው ሰው ዘመን ሊወስን አይችልም እንደሚል፣ አሁን ያለውን ኑሮና ሕይወት የማያዩት የቀድሞው መሪያችን ራዕይ ሊያዘልቀን ይችላል ብሎ ማመን ያስቸግራል፡፡ ርግጥ ነው ያስጀመሩትን ግድብ ማጠናቀቅ፣ የባቡሩን ሥራ መፈፀም፣ ወዘተ ጥሩ ነው። ግን በጤፍ ዋጋ፣ በስኳርና በትራንስፖርት ጉዳይ ያለውን ጣጣ ዛሬ ቢያዩ፣ እሳቸውም ደንግጠው ጭንቅላታቸውን ይይዙ ነበር፡፡ በዓመት ውስጥ ለአንድ የሆቴል ተመጋቢ ቢያንስ ሦስቴና አራቴ ዋጋ ይጨምርበታል፡፡ ታዲያ ሆዱ ባልጠገበ ሲቪል ሠራተኛ ተሠርቶ፣ ሀገርን ማሳደግ ይቻላል እንዴ? ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ አዲስ ሕልም ያልሙ እንጂ --- አዲስ ራዕይ ያምጡ! የስነ አመራር ምሁሩ

ጆን ሲ ማክስዌል እንደፃፉት፤ በየዓመቱ ዶሮዎቹን የክረምት ጐርፍ የሚወስድበት ዶሮ አርቢ፣ ሁልጊዜ በዶሮ ላይ የሙጢኝ ማለት የለበትም፤ ይልቅስ ጐርፉ ላይ ዋኝቶ አልፎ ሀብት የሚሆን ዳክዬ የማርባት ጥበብና ዘዴ ሊኖረው ይገባል። መቼም መንግስታችን ሁልጊዜ በሕይወት በሌሉት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ላይ መንጠልጠል ያለበት አይመስለኝም፤ እሳቸው በጊዜያቸው የሚሰሩትን ሰርተው አልፈዋል፡፡ አሁን ተራው የሥልጣን ወንበሩ የተሰየሙት ሰውዬ ነው፡፡ ፕሬዚዳንት ሊንደን ቢ. ጆንሰን እንዳሉት፤ ድሀና ሀብታም በጠብደል ግድግዳ ሲለይ ጥሩ አይደለም። ይልቅስ ግድግዳው የመስተዋት ነውና በኋላ የሚያመጣው መዘዝ መጥፎ ነው፡፡ ከፊሉ በሌብነት እየበለፀገ፣ ሌላው በጨዋነት እየተራበ - ለዘላለም - አይኖርምና መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ዶክተር መረራ ጉዲና እንደሚሉት፤ የራበው ሕዝብ - መሪውን ለመብላት እንዳይነሣ - ካሁኑ ማሰብ የግድ ይላል፡፡ ጆንሰን - “There are two courses open to us. We can master the problem, or we can leave it to master us” ብለዋል - የኛም ምርጫ ይኸው ነው። አዲዮስ!

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ዳንሴ የምትባል ወተት - አላቢ ሴት ራኘ ያለ ቦታ ወዳለው የላሞች በረት ሄዳ ወተቷን ታልብና በቅል ሞልታ,ኧ እንደተለመደው ጭንቅላቷ ላይ አድርጋ ወደ ቤቷ መንገድ ትጀምራለች፡፡ በመንገዷ ላይ የምታገኛቸው የሠፈሩ ሰዎች፤ “ከየት ትመጫለሽ?” ይሏታል፡፡ “ወተቴን አልቤ መመለሴ ነው” ትላለች፡፡ “ላሟ እንዴት ናት፣ ብዙ ወተት ሰጠች?” “በጣም ብዙ፡፡ ጭንቅላቴ ላይ ያሰቀመጥኩትን ቅል አታዩም፡፡ በሱ ሙሉ አልቤያለሁ” “ታድለሻል!” ይሏታል፡፡ መንገዷን ትቀጥላለች፡፡ ያገኘቻቸው ሰዎች ሁሉ አድናቆታቸውን ሲገለፁላት፣ በጣም ደስታ እየተሰማት በሀሳብ ስምጥ ትልና ለራሱዋ እንዲህ ትላለች፡- “ይሄን በቅል የሞላሁትን ወተት እንጥና፤ ቅቤ አወጣለሁ፡፡ ያንን ቅቤ ወደ ገበያ ወስጄ በደህና ዋጋ እሸጣለሁ፡፡ በዚያ ገንዘብ መዓት ዕንቁላል እገዛለሁ፡፡ ዕንቁላሉ ሲፈለፈል መዓት ጫጩት ይፈለፈሉልኛል፡፡ ጫጩቶቹ ያድጉና ብዙ ዶሮዎች ይሆኑልኛል። ከዚያ በጣም ሰፊ የዶሮ እርባታ አቋቁማለሁ፡፡ ግቢዬ ዶሮ በዶሮ ይሆናል፡፡ ከነዚያ ዶሮዎች ውስጥ በየጊዜው ጥቂቶቹን እየወሰድኩ ገበያ እቸበችባለሁ! ባለ ብዙ ብር እመቤት እሆናለሁ፡፡ ቀጥዬ በጣም ቆንጆ ቆንጆ የተባሉ ቀሚሶችና ጫማዎች እገዛለሁ፡፡ ያኔ እንግዲህ ያገሩ ሰው ሁሉ ሠርግ የሚጠራው፣ ግብዣ እሚጠራው እኔን ብቻ ይሆናል፡፡ ያገሩ ጐረምሳ ዐይንም እኔኑ ብቻ ማየት ይጀምራል፡፡ አንዱ ጐረምሣ ይመጣና “ዳንሴ እንዴት አምሮብሻል? ከእኔ ጋር ለምን አትሄጂም?” ሲለኝ፤ ደሞ ያም ሎጋ ይመጣና “ዳንሴ የኔ ቆንጆ! ዛሬ በምንም ዓይነት ከእኔ ጋር መሄድ አለብሽ” ሲለኝ፤ እኔ ግን እራሴን እየነቀነቅኩኝ፤ እየተምነቀነቅሁ ጥያቸው እሄዳለሁ!” ስትል፤ ለካ ራሷን ስትነቀነቅ ያ ጭንቅላቷ ላይ አስቀምጣው የነበረ የወተት ቅል ውሉን ስቶ ኖሮ፤ መሬት ወርዶ ተከሰከሰ፡፡ ያም ወተት ይፈስና አገር ምድሩን ይሞላዋል፡፡ በሀሳቧ የገነባችው ሀብት ንብረትና ቁንጅናም መሬት ፈስሶ ይቀራል! “ጫጩቶቹ ሳይፈለፈሉ በፊት፤ መቁጠር አትጀምር” የሚለው የፈረንጆች ተረት አመጣጥ ይሄ ነው! እኛ እናውርቸው እነሱ ያውርሱን አይታወቅም፡፡

                                                               * * *

ፈረንጆች፤ “Building a castle in the air” የሚሉት ይሄንኑ ነው፡፡ ማቀድና በባዶ ሜዳ መመኘት እጅግ የተራራቁ ጉዳዮች ናቸው፡፡ ማቀድ፤ በዝርዝር ያቀድኩትን ለመፈፀም ምን ምን አደርጋለሁ ማለትን፣ ያንንም ማስፈፀሚያ ፋይዳ ያለው ቁሳቁስንና አጋዥ የሰው ኃይልን፤ እንዴት እቀዳጀዋለሁ ማለትን፤ በመጨረሻም ቀን በቀን ሥራ ላይ ማዋልን ይጠይቃል፡፡ በዚህ ማህል ባይሳካስ ብሎ ማውጠንጠንን፣ ሁለተኛ ዘዴ መዘየድን (Plan B እንዲሉ) የግድ ማሰብን ይሻል፡፡ ካልሆነና አማራጭ ሁሉ ከተሟጠጠም በጊዜ ሀሳብን ለውጦ ወደ ሌላ ዕቅድ መሸጋገር ነው፡፡ ከዚህ ቀላልና ግልፅ መንገድ ውጪ በጉልበት ልሥራህ ቢሉት ሀብትንም ማባከን፣ የሰው ኃይልንም በአጓጉል መንገድ ሜዳ ማፍሰስ ነው፡፡ እግርህን በአልጋህ ልክ ዘርጋ፤ እንደማለት ነው፡፡ ይህን በአገር ደረጃ መንዝሮ ማየት ነው እንግዲህ አገርን ለማሳደግ መጣጣር፡፡ ከምንጨብጠው በላይ መጀመሪያ እጃችን ረዥም መሆኑን ማረጋገጥ ያስፈልጋል /a man’s reach should exceed his grasp ይላል ሮበርት ብራውኒንግ/ እጃችንን ዘርግተን የማንደርስበትን ነገር ለመጨበጥ መሞከር፤ በር ከፍተን ለዘራፊ እንደመተው ነው፡፡ የሰላም ትልቁ ጠላት ከአቅም በላይ መመኘት ነው፡፡ አሊያም የክቡር እምክቡራን ዕብደት ነው። “ከአቅም በላይ መኖር የዕድገት ፀር ነው” ይሉ ነበር ያለፈው ሥርዓት ነገረ-ሠሪዎች! ኮከብ እነካለሁ ብሎ ሠምበሌጥ ላይ መወድቅ ይከተላል፡፡ ለራስ ጥቅም ሲሉ የአገር ዕቅድ አወጣሁ ማለት መዘዙ ብዙ ነው፡፡ ድህነት ባጠጠበት፣ ችጋር በተንሠራፋበት አገር እንደ ህንድ እጉልላቱ አናት ላይ ጥቂት ባለ ፀጋ ሰዎች ብቻ ተቀምጠው፣ የበለፀገች ኢትዮጵያን መመኘት ከንቱ መገበዝ ነው፡፡ የሥራ መንፈስ ከብዙሃኑ የልብ ፍቅርና የአገር መውደድ ስሜት ጋር በፅኑ መቆራኘት አለበት፡፡ ላገር አሳቢ እየመሰለ ውስጥ ውስጡን እንደሚቦጠቡጥ ሹም ባለበት ቦታ ዕቅድ ሲታቀድ ቢውል ፍሬ-ቢስ ነው የሚሆነው። ነባር ነባር በላተኛ አባርረን ትኩስ ትኩስ፣ ልጅ-እግር በላተኛ ካመጣን፤ የበላተኞች መተካካት እንጂ የአዲስ ደም - ቅያሪ (New – Blood - Injection) አይሆንልንም፡፡ “ይህንንማ ማን ያጣዋል ይሄንን ማንም ያውቀዋል፡፡ ዝቅተኝነት’ኮ፣ የለጋ ምኞት መሰላል ነው ጠዋቱን ሥልጣን የጠማው:- ደረጃውን ሲያያዘው፣ ሽቅብ ሽቅብ ያንጋጥጣል ጫፉ ላይ ሲደርስ ግና፣ ጀርባውን ለመስጠት ይሻል ጧት የበላበትን ወጪት፣ ማታ ሰባሪ ይሆናል ቀና ብሎ ወደ ሰማይ፣ ደመናውን ብቻ ያያል እላይ ያወጣውን ታች ሰው፣ ቁልቁል ረግጦ ይሳደባል” ይላል የሺክስፒሩ ብሩተስ፡፡ ዞሮ ዞሮ ዕቅድ እንደ አቃጁ፣ ዕቅዱ እንደ ከዋኙ ነው፡፡ የሸር ዕቅድም፣ የአውቆ-አበድ ዕቅድም አለና ጠንቅቆ ማየት ይገባል፡፡ ታዋቂው ፀሀፌ-ተውኔት ፀጋዬ ገብረ መድህን በሚኒልክ ተውኔት፣ በኢልግ አፍ፣ እንዲህ ይላል፡- “ኮንቲ ኦሊኒ ግን ጭምት፣ ቀዝቃዛ፣ ነገር ለማሻከር ሆን ብሎ በዕቅድ የሚቆጣ፣ ሆን ብሎ በዕቅድ እንዳስፈላጊው ሁኔታ የሚያብድ፣ አንድ ነፃ መንግሥት ያለኔ ፈቃድ ለምን ሰንደቅ ዓላማ ተከለ ብሎ በነገረ-ቀደም አቅዶ እሚጮህ፤ … አቅዶ የሚያብድ ሥውር አደገኛ ሕሊና፣ ቁም - ነገር - አልባ ሰው ነው!” ከዚህ ይሰውረን፡፡ ዕቅዶች ይከወናሉ፡፡ ፓርቲዎች ይለመልማሉ፡፡ አገር ታድጋለች፡፡ የዕለት ጉርሥ የዓመት ልብስ ይኖረናል ማለት ያባት ነው፡፡ ሆኖም ያ እስኪሳካ ድህነት አንድያውን እንዳያደቀን ሁሉን በወግና በቅጡ ማስተካከል፣ መቆጣጠር፣ መተግበር ያስፈልጋል፡፡ አለበለዚያ “ለመብላት የጠፋ ቅቤ፣ ስሞት ባፍንጫዬ ይፈስሳል” ይላል ዶሮ፤ እንደተባለው ይሆናል!

ስለነገርየው በማጥናት መተንተን አንድ ነገር ነው፡፡ “አናሊሲስ” ይባላል፡፡
የተጠናውን እና የተተነተነውን ነገር ወስዶ በሌላ የተጠና እና የተተነተነ ነገር ላይ መደመር ደግሞ ለላ ነገር ነው፡፡ መደመሩን “ሴንቴሲስ” ይሉታል፡፡
ለምሳሌ 1 + 1 = 2 “አንድ” ቁጥር ምንን እንዳሚወክል አናውቅም፡፡ “አንድ ሰው” ማለት ሊሆን ይችላል፡፡ አንድ መንግስት---- አንድ ብርጭቆ አሊያም አንድ የሃሳብ ዘውግ ሊሆን ይችላል፡፡ ለአንድ ነገር መወከያ መጠን ገላጭ ነገር መሆኑን ብቻ ነው የምናውቀው፡፡ ምንነቱን እስካላወቅን ድረስ ከሌላ ምንነቱ ባልተተነተነ ነገር ላይ ወስደን ልንደምረው፣ ልንቀንሰው፣ ልናባዛው ወይንም ልናካፍለው እንችላለን፡፡
ነገር ግን የተተነተነ ሃሳብን ወስደን በሌላ በተተነተነ ሃሳብ ላይ የመደመሩን ፍቃድ ማነው የሰጠን? የሚለው ነው ጥያቄዬ፡፡ ወንድ ሲደመር ሴት…”ወንድ ሴት” ይፈጠራል ልንል አንችልም። የማይደመሩ ነገሮችን ከመደመር ብዙ የፅንሰ ሃሳብ መንጋደዶች ተፈጥረዋል፡፡ ለመደመር ብቁ የሚያደርጋቸው ነገር “ሎጂክ” ብቻ ሳይሆን “ምክንያታዊነትም” አንዱ  መመዘኛ መሆን አለበት፡፡
እኔም አንድን ነገር ልውሰድና…በመጠኑ በመተንተን ከሌላ ማንነቶች ጋር ለመስፋት ልሞክር፡፡ ሙከራዬ ልክ ሆኖም ይሁን ስህተት ስፌቱን የምትለብሱት እናንተ ብያኔ ትሰጣላችሁ፡፡ ለመተንተን የመረጥኩት ነገር በጣም ቀላል መሆን አለበት፡፡ ለሁላችንም ቅርብ እንዲሆን፡፡ በቀላሉ የሚገኝ…ተፈጥሮአዊ ነገር፡፡ ሁላችንንም ከተወለድን ጀምሮ ስለታደልነው እግሮቻችን ሊሆን ይችላል። ግን በተፈጥሮ ለሁላችንም የተሰጠን ነገር ከሆነ ደግሞ በተወሰኑ ሰዎች ላይ ሳይሆን ጥናት መስራት የሚያስፈልገው በብዙሐኖቹ ላይ ነው፡፡ ያ ደግሞ በጣም ብዙ ጊዜ፣ ብዙ መረጃ ያስፈልገዋል፡፡ በእኔ አስተውሎት ብቻ ሊከናወን የሚችል አይሆንም፡፡
እንደ ኪንታሮት በሽታ የመሰለ ነገርንም አይደለም መመርመር የፈለግሁት፡፡ ጤነኝነትም በሽታም ከመሰለ ነገር ቢሆን እመርጣለሁ፡፡ ምክንያቴ ወደኋላ የሚገለጽ ይሆናል፡፡
ብዙ ሩቅ መሄድ አያሻኝም ምሳሌዬን አግኝቼዋለሁ፡፡ በወንዶች እራስ ላይ የሚገኝ ነገር ነው፡፡ ነገር ግን በሁሉም ወንዶች ላይ ግን አይደለም። በአንዳንዶች እንደ ውበት፣ በሌሎች ደግሞ መልክ አጥፊ ተደርጐ ይቆጠራል፡፡ ከቁርንድድ ፀጉር ባለቤቶቹ ይልቅ ለስለስ ያለ ፀጉር ባላቸው የሰው ዝርያዎች ላይ ይኼ ክስተት ይበዛል፡፡ አንዳንዶች “የምሁርነት” ምልክት ነው ይሉታል፡፡ ከሽበት ማብቀል ባልተናነሰ ነገርዬው በማህበረሰቡ ውስጥ ያስከብራል፡፡ ተቀማጭን አሽቆጥቁጦ ከወንበር ያስነሳል፡፡ የነገርየው ባለቤቶች ቆብ በነገርየው ላይ መድፋት ያዘወትራሉ፡፡ ማዕዘናም የራስ ቅል ባላቸው ላይ በብዛት አይታይም፡፡ ወይንም በማዕዘናም ራሶች ላይ ከመውጣቱ በፊት የራስ ቅላቸውን ቅርጽ ወደ እንቁላል ክብነት ይቀይረዋል፡፡
እስካሁን ግልፅ ካልሆነላችሁ ምናልባት የነገርየው ባለቤት ስለሆናችሁ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገርየው “በራ” ተብሎ ይጠራል፡፡ “ራሰ በራ” ደግሞ የነገርየው ባለቤት ነው፡፡ የሚገርመው ግን ስለ እዚህ ነገር ያገኘሁት ትንተና ከሁለት መስመሮች የረዘመ አይደለም፡፡ በተለይ ነገርየው በጤና እክል ወይንም በአደጋ ምክንያት የመጣ ካልሆነ፡፡ በዘር የሚወረስ ምክንያቱ ግልጽ ያልሆነ የፀጉር መብቀል መቆም ነው፡፡ ልክ ሽበት ማለት የፀጉር ቀለም የሚያመርቱት የቆዳ ስር ፒግመንቶች ቀለሙን ማምረት ሲያቆሙ የሚከሰት የዕድሜ ቁልቁለት ላይ በተፈጥሮ ሂደት የሚያጋጥም ጉዳይ እንደሆነው፡፡
ይህ የተፈጥሮ ገጽታ በሽታ አለመሆኑን ካረጋገጥን በኋላ፣ ወደ ተጨማሪ አስተውሎቶቻችን እንሻገር፡፡ በተወሰኑ የወንድ ዘር ግንድን ተከትሎ የሚመጣ መሆኑን እያወቅንም…በተፈጥሮ ረገድ ሳይሆን እስካሁን ባስተዋልኩት አንፃር ድምሮቼን ለመስራት ልሞክር፡፡ ጽሑፌ ላይ ስነሳ የማይደመሩ ነገሮችን ከመደመር ነው የፅንሰ ሃሳብ መንጋደድ፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ አጉል እምነት እና አምልኮ የሚከሰቱት ብያለሁ፡፡
ምን ማለቴ እንደሆነ የበለጠ ልግለጽ፡፡ ለምሳሌ በአንድ የገጠር መንደር (ማህበረሰብ) ውስጥ የሚመለክ ዛፍ አለ እንበል፡፡ ዛፉ ትልቅ፣ ግንዶቹን ወደ ሰማይ፣ ስሮቹን ወደ አፈር ስር ሰድዶ ያጠነከረ አድባር ሊሆን ይችላል፤ በስፍራው ለሚኖሩ አምላኪዎቹ፡፡
እንግዲህ እዚህ ላይ ሁለት ነገሮች አሉ…አንድ ዛፍ አለ፡፡ ሁለት በነዋሪዎቹ አእምሮ ወይንም ነፍስ ውስጥ የፈጣሪ እውቀት እና ፍላጐት…ዛፉን የፍላጐታቸው መወከያ ወይንም የእውቀታቸው መጠቅለያ ተጠቅልሎ የሚገኝበት ቦታ ሲያደርጉት ተራው ዛፍ ወደ አድባርነት ደረጃ ከፍ ይላል። ሁለት የማይደመሩ ነገሮችን ደምረዋል የሚሉ የሎጂክ እና ምክንያታዊነት አምላኪዎች ቢኖሩም። እነሱም ከመደመር ነው እውቀታቸውን ያገኙት፡፡ እነሱም ሃሳባቸውን ከቁሳዊ እቃ ጋር ለማስተሳሰር የሚጠቀሙበት መንገድ አላቸው፡፡ የተፈጥሮን ሚስጢር ማወቂያ መንገድ ብለው ነው ይኸንን ምክንያታዊነታቸውን የሚጠሩት፡፡ ቅልብጭ ባለ ስያሜው ግን “ሳይንስ” ነው፡፡
ሳይንስ ለመባል አንድ ነገር መጀመሪያ በአስተውሎት ሊጤን ይገባል፡፡ ከማስተዋል እና ማጤኑ በኋላ…ስለነገርየው ያስተዋለው ሰው “መላ ምት” ይሰጥበታል፡፡ ከመላምቱ በኋላ ሦስተኛው እና ወሳኙ ደረጃ ይመጣል፡፡ መላ ምቱን ወደ ተጨባጭ የማይለዋወጥ እውነታ ለመቀላቀል በቤተሙከራ ተፈትኖ እውነትነቱ እና እምነትነቱ ይረጋገጣል፡፡
እኔ በመላጣ ላይ ለመምታት የሞከርኩት መላ…በመላምትነቱ ብቻ ነው የሚቀረው፡፡ ወደ ቤተሙከራ ወስዶ ለማረጋገጥ ከዚህ የበለጠ ሙያ እና አቅም ይጠይቃል፡፡ እኔ የሌለኝ ነገር ነው፡፡ መላ ምቶች ለሳይንስ ከሚቀርቡት ይልቅ ለጥበብ የቀረበ ዝምድና አላቸው፡፡ ስለ ራሰ በራ የምለውን ከጥበብ በበለጠ እርግጠኝነት ኮስተር ብሎ መቀበል ሞኝነት ነው፡፡   
 መላምቴን የትም ቦታ መጀመር እችላለሁ። ራሰ በራዎች በአብዛኛው መሪዎች ናቸው ልል እችላለሁ፡፡ ራሰ በራ ጠቅላይ ሚኒስትር እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በኢትዮጵያ የመሪነት መድረክ ላይ ዋና ተጫዋች እንደነበረ ትዝ ይለኛል?..ሌላ ማን አለ?!...አፄ ምኒልክ ራሰ በራ አልነበሩም ለማለት ብችልም….ራሳቸው ሳይሸፈን ግልጽ ፎቶአቸውን ግን አይቼ አላውቅም፡፡ የአፄ ሃይለስላሴ ፀጉር ገባ ያለ ቢሆንም እስከመጨረሻው ደረጃ አልተመለጠም፡፡
ለመሆኑ የሀገር መሪ ሆኖ የተመለጠ ሰው ካለም ሀገሩን የመራው በጭንቅላቱ ነው ወይንስ በክንዱ…ሌኒን ራሰ በራ ነበረ፡፡ ብዙ ያነብብ እና ይጽፍ የነበረ ሰው ነው፡፡ ብዙ የሚያነብና እና ብዙ የሚጽፍ መሪ ነው የሚመለጠው ማለት ነው?
መሪ ስል በጥቅሉ ነው ወይንስ በተናጠል? ለምሳሌ ቬክስፒርም በዘመኑ የስነ ጽሑፍ ዘርፉ መሪ ነበር፡፡ ራሰ በራ ነው፡፡ ግን አንዱ የአእምሮዬ ጓዳ ደግሞ አንድ የታወቀ አሉባልታ ሹክ አለብኝ፡፡ የሼክስፒርን ቅኔዎች እና ቴአትሮች የደረሰው Sir frincis ነው የሚል አሉባልታ፡፡ ሼክስፒር ተመልጦ የሚያሳይ ፖርትሬት በብዙ አጋጣሚ አይቻለሁ፡፡ ራሰ በራው ሼክስፒር ሆኖ ግን በጥበቡ ግዛት መሪ ያደረገውን ሥራዎቹን የሰራለት ባለ ሙሉ ፀጉሩ “ሰር ፍራንሲስ ቤከን” ከሆነ ---- መመመለጥ መሪ ያደርጋል የሚለውን መላ ምቴን ቅዠት ያደርገዋል፡፡
በሼክስፒር ላይ የሚወራው አሉባልታ ወደ አንድ ጥርጣሬ መራኝ፡፡ ራሰ በራ ሌባ ሊሆን ይችላል ማለት ነው? ነገር ግን በህይወት ዘመኔ  ራስ በራ የሆነ አጭበርባሪ አይቼ አላውቅም፡፡ ታክሲ ለመያዝ ስጋፋ ከጐኔ ያለው ሰው ራሰ በራ ከሆነ ለኪሴ የማደርገውን ጥንቃቄ እቀንሳለሁ፡፡ ይህ የሚያሳየው ነገር አለ፡፡ ራሰ በራ ከተሞክሮ እድሜ ልኬን እንዳየሁት የተከበሩ ሰዎች ናቸው፡፡ የረከሰ የኪስ አውላቂ ስራ አይሰሩም፡፡ ለአቅመ ራሰ በራነት ከደረሰው ይልቅ ድፍን ፀጉር ያለውን እና ወጣት የሆነውን ነው ኪሴ እንዳይገባ የምጠነቀቀው፡፡
እኔ ራሴ ፀጉረ ድፍን እና ወጣት ሆኜ ሳለሁ --- እኔን መሰል ወጣት መጠራጠሬ ምን የሚሉት ለ”መላ ምት” የማያመች ነገር ነው? “እኔ ወጣት ሆኜ ወጣቶች አልወድም/ሰይጣን ይመስሉኛል--- የዳቢሎስ ወንድም” የሚለው ይገልፀኝ ይሆን?
ለማንኛውም ራሰ በራ ኪስ አውላቂ ሊሆን አይችልም፡፡ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎችን ከሚመሩት ሰዎች ምን ያህሉ ራሰ በራ ናቸው። የተከበሩበትን ያህል ፀጉራቸው ገባ ያለ ይሆን? ፕሮፌሰር መስፍን ራሰ በራ ባለመሆናቸው ምክንያት ይሆን ብዙውን ጊዜ ፊታቸው ላይ የቁጣ ቅላፄ የሚነበበው?
ይሄንኑ የራስ በራ መላምቴን እያሰላስልኩ ጫማዬን የጠረገልኝ በፒያሳ የሚገኝ ሊስትሮ ራሰ በራ ነው፡፡ መነጽርም አድርጓል፡፡ ጫማዬን ጠርጐ፣ ክሬም ቀብቶ ያስከፈለኝ 8 ብር ነው፡፡ ነገር ግን የቀባልኝም ክሬም፣ ለመቀባት የወሰደበት ጊዜም ዘለቅ ያለ ነው፡፡ በጥራት ነው ስራውን የሰራው፡፡ በሊስትሮ ሙያ ላይ ለእኔ መሪ ነው፡፡ ገና ስራውን ከመጀመሩ በፊት እንኳን በደንብ አድርጐ ጫማዬን እንደሚያክምልኝ እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ እንደጠበቅሁት ሆነ፡፡
ቅድም የፈጠርኩት መላምቴ ትክክል ሳይሆን አልቀረም መሰለኝ፡፡ ለምሳሌ ህመም ታምሜ አንድ ክሊኒክ ብሄድ እና ከጠረጴዛው ጀርባ ተቀምጦ ስለ ህመሜ ባህሪ የሚጠይቀኝ የህክምና ዶክተር ራሰ በራ ቢሆን … እርግጠኛ ነኝ ግማሽ ህመሜ ለቀቅ እንደሚያደርገኝ፡፡ ከወጣት እና መላጣ ካልሆነው ዶክተር የበለጠ ራሰ በራው እና ምራቁን ዋጥ ያደረገው ባለሞያ መፍትሄ እንደሚሰጠኝ እርግጠኛ ነኝ፡፡
ሌላው በእይታ ካደረግሁት ጥናት የተገነዘብኩት ነገር … መለጥ ያሉ ሰዎች ወፈር ለማለትም የቀረቡ ናቸው፡፡ ወፈር ለማለት እና ቦርጭ ለማውጣት ቅርብ ናቸው፡፡
ደራሲዎችን በአይነ ህሊናዬ ደርድሬ … ይሄ በተለምዶ የሚደፉትን ቆብ በምኞት እጄ እየገለጥኩ አናታቸውን መረመርኳቸው፡፡ የሚገርመው (በተለይ በሐገራችን ላይ ያሉት) “ራስ ሙሉ” ናቸው፡፡ ከባህር ማዶ ያሉትም ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ትያትር ፀሐፊዎች እና ገጣሚዎች ግን በተገላቢጦሽ ፀጉራቸው የገባ ብዙ አገኘሁ፡፡ የህዝቡን ሀላፊነት በራሳቸው ላይ ተሸክመው በመወጣት በኩል ትልቅ ሚና የተሸከሙት ደራሲዎች ናቸው ገጣሚዎች እና ትያትር ፀሐፊዎች …፡፡
እስካሁን በራሰ በራዎች መሪነት፣ አስተዋይነት፣ ምሑርነት ላይ ማረጋገጫ ለመስጠት ስባዝን ቆይቼ አሁን እጄን ልሰጥ አልችልም! … ከደራሲ ይበልጥ ገጣሚዎች ለህዝብ ሀላፊነት ይቀርባሉ ማለት ነው-እንደኔ መላምት፡፡
ማረጋገጫዬ አስተውሎቴ ብቻ ነው፡፡ ራሰ በራ የሆኑ የአእምሮ በሽተኞችም ብዙ አይቻለሁ። ከተራው የአእምሮ በሽተኛ ላቅ ያሉ ቢሆኑ ነው የሚል መላምት አለኝ፡፡ ራሰ በራ የሆነን በሽተኛ ፀጉረ ጨብራራ ከሆነው እኩልማ ልመዝነው አልችልም፡፡ በትምህርት ብዛት ካበደው ጋር በትምህርት እጦት ምክንያት ያበደውን እኩል ቦታ ላስቀምጠውም ህሊናዬ አይፈቅድም፡፡
በዝግመተ ለውጥ እይታም ራሰ-በራነትን ልመለከተው እችላለሁ፡፡ እነ ሉሲ እና አርዲ (በስዕል ባሳዩን መሰረት) ሰውነታቸው በፀጉር የተሸፈነ ዝንጀሮ ነው የሚመስሉት፡፡ ራሰ በራ በእነሱ የጦጣ ዘመን ላይ ያለ አይመስለኝም፡፡ በዝንጀሮዎች ዘንድ ራሰ በራ የሆነ አይታችሁ ታውቃላችሁ? … እኔ አላውቅም፡፡ በሰዎች ዘንድ ግን ሰውነቱ በፀጉር የተሸፈነ ብዙ አለ፡፡ ባይሆን ዝንጀሮዎች ሲመለጡ ደረታቸው አካባቢ ነው፡፡ ጭላዳ ዝንጀሮ ደረቱ ላይ አይደለ ራሰ-በራው ያለው፡፡
ስለዚህ ፀጉሩ ገባ ገባ ካለው ይልቅ ያላለው ወደ ዝንጀሮኛ ይቀርባል እንደኔ መላምት፡፡ ግን እኔም ፀጉራቸው ገባ ካላሉት መሀል የምመደብ ነኝ። እኔ ራሴ ወደ ዝንጀሮዎቹ ጐራ ሆኜ ነው እንዴ መሰሎቼን የምነቅፈው? “… እኔ ዝንጀሮ ሆኜ ዝንጀሮ አልወድም/ሰይጣን ይመስለኛል የዳቢሎስ ወንድም”
እዚህ ላይ ላብቃ፡፡ የማይደመሩ ነገሮችን ከመደመር ምን አይነት መላ ምቶች እንደሚገኙ ለማሳየት ጥሩ ምሳሌ ይመስለኛል፡፡    

Monday, 23 December 2013 09:58

እቴጌ ጠየቁ

አዲስ ሐሳብ አፈለቁ ሳይደብቁ
        የኔ ምኒልክ ይስሙኝ
        ይህን ውብ ቦታ አገር ስጡኝ
        ቤት ልሥራ ጌታዬ ባፋጣኝ
        ይህችን አዲስ አደይ አበባ አዩልኝ
    የፍንፍኔ ውበት አይሎ
    የጣይቱስ ያገር ጥያቄ መች ተዘሎ
ሕይወት አገር አበባ
በፍል ውኃ ዳርቻ ተገነባ
ይህች አደይ አበባ
ስመ ውልደቷ በዓለም ዙሪያ አስተጋባ
የእኛይቱ ውብ አዲስ አበባ
እንሆ የኔ ውብ ጣይቱ
ቤት ሥሪና ያንቺ ትሁን አገሪቱ
በማለት
    ምኒልክ ለጣይቱ መረቋት
    በፍቅር ቃለ አንደበት ለገሷት
ይኸው የምኒልክ በረከት
የጣይቱ ልብ ምርኮ መሠረት
ሕዝብ ከቶባት ሕዝብ ገንብቷት
    የአፍሪከ አንድነት መዲና አለኝታ
    የዓለም ሰላም መድረክ መከታ
    የአገር ኤኮኖሚ የአገር ፖለቲካ ዋልታ
    እናት አዲስ አበባ ውብ አገር ውብ ስጦታ
ገ.ክ.ኃ




በተሰማሩበት መስክ ጉልህ ስራ ሰርተዋል፣ የላቀ ውጤት አስመዝግበዋል፣ ብዙዎችን ተጠቃሚ አድርገዋል፣ ሃያልነታቸውንም አስመስክረዋል ያላቸውን የአለማችን ሴቶች በየአመቱ የሚመርጠው ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፣ ዘንድሮም የ2013ን የአለማችን 100 ሃያላን ሴቶች ዝርዝር ይፋ አድርጓል፡፡
ፎርብስ በመላ አለም ከሚገኙ የተለያዩ አገራት ከመረጣቸው 100 የአመቱ ሃያላን ሴቶች መካከል፣ የቀለም ልዩነት ሳይበግራቸው ጉልህ ስራ ሰርተዋል፣ የጥቁር ሴቶች የስኬታማነት ተምሳሌት ሆነዋል ብሎ በዝርዝሩ ውስጥ ያካተታቸው ጥቁር ሴቶች አስራ አንድ ብቻ ናቸው፡፡ ከአስራ አንዱ ጥቁር ሃያላን ሴቶች መካከልም፣ ከአፍሪካ አህጉር የተመረጡት ሶስት ብቻ ናቸው፡፡
ፖለቲከኞችን፣ የኩባንያ ስራ አስኪያጆችን፣ መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ሃላፊዎችን፣ የመንግስት ባለስልጣናትንና በሌሎች መስኮች የተሰማሩ ሴቶችን የያዘው የፎርብስ የአመቱ ምርጥ ሃያላን ሴቶች ዝርዝር ከጥቁር ሴቶች መካከል በቀዳሚነት ያስቀመጠው ቀዳማዊ እመቤት ሚሼል ኦባማን ነው፡፡
ፎርብስ ሚሼል ኦባማን የመረጠው፣ በቀዳማዊ እመቤትነቷ በመጠቀም ህጻናትን ከመጠን በላይ ከሆነ ክብደት ለመታደግና ጤናማ አኗኗርና አመጋገብን ለማስፋፋት በምታደርገው ጥረት ነው፡፡ ሚሼል ከባራክ ኦባማ ጋር ሲነጻጸር በአሜሪካውያን ዘንድ የበለጠ ተወዳጅነት እንዳላቸው የገለጸው የፎርብስ መረጃ፣ ከአጠቃላዩ የአሜሪካ ህዝብ 67 በመቶ የሚሆነው ከባራክ ኦባማ ይልቅ ለሚሼል ጥሩ አመለካከት እንዳለው ያሳያል፡፡
በሃያላኑ ጥቁር ሴቶች ዝርዝር ውስጥ የተካተተችው ሌላዋ አፍሪካ አሜሪካዊት ደግሞ ኦፕራ ዊንፍሬይ ናት፡፡ ለ25 አመታት ስትመራው በነበረው ኦፕራ ሾው የተባለ ፕሮግራም አለማቀፍ ዝናን ያተረፈችው ኦፕራ፣ በሃብት መጠን ቀዳሚዋ አፍሪካ አሜሪካዊት መሆኗንም ፎርብስ ጠቅሷል፡፡ አዲስ ያቀዋቀዋመችው ዘ ኦፕራ ዊንፍሬይ ኔትዎርክ የተሰኘ የቴሌቪዥን ጣቢያ ባለፈው አመት ብቻ 83 ሚሊዮን ተመዝጋቢ ተመልካች ቤተሰቦችን ለማግኘት በቅቷል። ኦፕራ በበጎ አድራጎት ስራ ስማቸው ጎልቶ ከሚጠራ የአለማችን ለጋስ ሴቶች አንዷ ስትሆን፣ እስከ አሁን ድረስ ከ400 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር በላይ ገንዘብ ለበጎ አድራጎት ስራ አበርክታለች፡፡
የዜሮክስ ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ የሆነችው አሜሪካዊቷ ኡርሱላ በርንስ፣ ኩባንያውን ከማተሚያ መሳሪያ አምራችነት፣ ጠቅላላ አገልግሎቶችን ወደሚሰጥ ግዙፍ ኩባንያነት አሳድጋለች በሚል ነው በሃያላኑ ዝርዝር ውስጥ የተካተተችው፡፡ እ.ኤ.አ በ1980 በተለማማጅ ሰራተኛነት ዜሮክስ ኩባንያን የተቀላቀለችው ኡርሱላ በርንስ፣ በሜካኒካል ኢንጂነሪንግ ከኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ ሁለተኛ ዲግሪዋን መመረቋን ተከትሎ በቀጣዩ አመት የኩባንያው መደበኛ ሰራተኛ ሆና ተቀጥራለች። በስራዋ ውጤታማ በመሆኗ እ.ኤ.አ በ2000 የኩባንያው ምክትል ፕሬዚዳንት ተደርጋ ተሹማለች፡፡ ይህቺው ታታሪ ሰራተኛ እ.ኤ.አ በ2009 የዜሮክስ ዋና ስራ አስፈጻሚ ከሆነች በኋላም፣ የበለጠ ውጤታማ ስራ በማከናወኗና ኩባንያውን ወደተሻለ ትርፋማነት በማሸጋገሯ ነው፣ ፎርብስ ከሃያላኑ ጎራ የቀላቀላት፡፡
ሌላዋ የፎርብስ የአመቱ ሀያል ሴት አሜሪካዊቷ ድምጻዊት ቢዮንሴ ኖውልስ ናት፡፡ ፎርብስ እንዳለው፣ ቢዮንሴ በሙዚቃ ስራዎቿ ከምታገኘው በሚሊዮን የሚቆጠር ገቢ በተጨማሪ፣ ሀውስ ኦፍ ዴሪዮን በሚል ስያሜ ባቋቋመችው የአልባሳት አምራች ኩባንያዋም ከፍተኛ ትርፍ ማካበቷን ቀጥላለች፡፡
ከፔፕሲ ጋር የፈጸመችው የማስታወቂያና የኮንሰርት ስምምነት 50 ሚሊዮን ዶላር ያሳፈሳት ቢዮንሴ፣ የምንጊዜም ምርጥ ሽያጭ ካስመዘገቡ የአለማችን ታዋቂ ድምጻውያን ተርታ የምትመደብ ሲሆን 17 የግራሚ ሽልማቶችንም ተቀብላለች፡፡ ከወራት በፊት በተዘጋጀ የሱፐር ቦውል የሙዚቃ ዝግጅት ላይ ያቀረበችው የ15 ደቂቃ ሙዚቃዋን በአለም ዙሪያ የሚገኙ ከ104 ሚሊዮን በላይ ተመልካቾች እንደተመለከቱት የሚጠቅሰው የፎርብስ መረጃ፣ ድምጻዊቷ በአለም ዙሪያ ያላትን ተቀባይነት የበለጠ እያሳደገች መምጣቷ በሃያልነት እንዳስመረጣት ይናገራል፡፡
የታዋቂው ዎልማርት ኩባንያና ከአሜሪካ ታላላቅ የንግድ ኩባንያዎች አንዱ የሆነው የሳምስ ክለብ ፕሬዚዳንትና ዋና ስራ አስፈጻሚ በመሆን የሰራችው ሮዛሊንድ ብሪዌርም ሌላዋ የፎርብስ የአመቱ ሀያል ጥቁር ሴት ናት፡፡ ባለፈው አመት ጥር ወር ላይ የሳምስ መሪ ሆና የተመረጠችው ብሪዌር፣ ለኩባንያው ትርፋማነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቷ ይነገራል። እ.ኤ.አ በ2006 ዎልማርትን በመቀላቀል ዋና ስራ አስፈጻሚ ሆና ያከናወነቻቸው ስራዎቿ ኩባንያውን ማሳደግ፣ የእሷን ጥንካሬም ማስመስከር የቻሉ በመሆናቸው በሃያላኑ ዝርዝር ውስጥ መካተቷን ፎርብስ ተናግሯል፡፡
አፍሪካን የጥቁር ሃያላን ሴቶች እናት አድርገው ካስጠቀሷት ሶስት የአመቱ የፎርብስ ሃያላን ሴቶች መካከል፣ የማላዊ ፕሬዚዳንት ጆይስ ባንዳ አንዷ ናት። የአገሪቱ የመጀመሪያዋ ሴት ፕሬዚዳንት በመሆን ወደ መሪነት የመጣችው ጆይስ ባንዳ፣ የመጀመሪያዎቹን የስልጣን አመታት ከአለማቀፉ ማህበረሰብ እርዳታ በማሰባሰብና አገሪቱን ከሚፈታተናት የዋጋ ግሽበት ጋር በመታገል ነበር ያሳለፈቻቸው፡፡
ጆይስ ባንዳ ከአጠቃላይ አመታዊ ገቢዋ 40 በመቶ ያህሉን ከውጭ እርዳታ የምታገኘውን ይህቺን ድሃ አፍሪካዊት ሀገር ከገንዘብ ዕጦት ለመታደግ፣ በአለም ዙሪያ እየተንቀሳቀሰች የገንዘብ ተቋማትን በማሳመን ስራ ተጠምዳ እንደኖረች ፎርብስ ተናግሯል፡፡ ባንዳ ያለፉት መንግስታት አያደርጉ አድርገዋት የሄዷትን ማላዊ እንድታገግምና ራሷን ችላ እንድትቆም ለማስቻል እያደረገችው የምትገኘው ተጠቃሽ ጥረት የፎርብስን ሚዛን በመድፋቱ ከሃያላኑ ጎራ ተቀላቅላለች፡፡
የአፍሪካ የመጀመሪያዋ ሴት ፕሬዚዳንትና እ.ኤ.አ የ2011 የኖቬል የሰላም ተሸላሚዋ ሊይቤሪያ ፕሬዚዳንት ኤለን ጆንሰን ሰርሊፍ፣ የአፍሪካን ሴቶች ሃያልነት ያስመሰከረች ሌላኛዋ የፎርብስ ምርጥ ናት። በሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ ትምህርቷን የተከታተለችው ኤለን ጆንሰን ሰርሊፍ፣ የላይቤሪያን የእርስ በርስ ግጭት በሰላማዊ ድርድርና መግባባት ለመቋጨት ከመቻሏ በተጨማሪ፣ አለማቀፍ አበዳሪዎች የዕዳ ስረዛ እንዲያደርጉ በማግባባት ረገድ የሰራቻቸው ስራዎችም ጠንካራና ስኬታማ ሴትነቷን ያስመሰክራሉ ብሏል ፎርብስ፡፡
ፎርብስ የአመቱ ሃያል ሴት ብሎ የጠቀሳት ሌላዋ አፍሪካዊት፣ የናይጀሪያ የፋይናንስ ሚንስትርና የኢኮኖሚ አስተባባሪ ሚንስትር ንጎዚ ኦኮንጆ ኢዌላ ናት፡፡ ኢዌላ በአለም ባንክ የነበራትን የማኔጂንግ ዳይሬክተርነት ስራ ለቅቃ፣ እ.ኤ.አ ከ2011 በሚንስትርነት ከተሸመች በኋላ ተጠቃሽ ስራ መስራቷን የጠቀሰው የፎርብስ መረጃ፣ በቀጣዩ አመት የአገሪቱ ኢኮኖሚ 6.5 በመቶ እድገት እንዲያሳይ የእሷ አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን ያሳያል፡፡ እ.ኤ.አ ከ2003 እስከ 2006 በአገሯ ናይጀሪያ የኢኮኖሚ አማካሪ ሆና ትሰራ የነበረው ኢዌላ፣ አበዳሪዎች የናይጀሪያን 18 ቢሊዮን ዶላር ዕዳ እንዲሰርዙ በማስቻል ረገድ ተጠቃሽ ስራ መስራቷ ይነገራል፡፡
ከፎርብስ የአመቱ ሃያላን ጥቁር ሴቶች ዝርዝር ውስጥ የተካተተችዋ ሌላኛዋ ትጉህ ደግሞ፣ እ.ኤ.አ በ2012 የአለም የምግብ ፕሮግራም ዋና ዳይሬክተር ሆና የተመረጠችው አሜሪካዊቷ ኤርታሪን ኮሲን ናት።
ድርጅቱ በአለም ዙሪያ በሚገኙ 78 የተለያዩ አገራት ከርሃብ፣ የምግብ ዋስትናና የምግብ እጥረት ጋር  በተያያዘ የሚሰራውን ሰፊ ስራ በአግባቡ የመምራትና በስሯ የሚገኙ ከ15ሺህ በላይ ሰራተኞችን በወጉ የማስተዳደር ታላቅ ሃላፊነት የተጣለባት ኮሲን፣ ውጤታማ ስራ ማከናወኗን ፎርብስ ይመሰክራል፡፡ የመጀመሪያውን አመት በምዕራብ አፍሪካ በድርቅ፣ በሶሪያ ደግሞ በእርስበርስ ጦርነት ሳቢያ የተከሰተውን ርሃብ ለማሰወገድ ትኩረት ሰጥታ በመስራት ያሳለፈችው ኮሲን፣ በቀጣይም ከምግብ እርዳታ ወደ ራስን ማስቻል የሚደረገውን ሽግግር በመምራት ተጠቃሽ ስራ ማከናወኗን ፎርብስ ዘግቧል፡፡
በሃያላኑ ዝርዝር ውስጥ ለመቀላቀል የቻለችው ሌላዋ አሜሪካዊት፣ የኬር ዩኤስኤ ፕሬዚደንትና ዋና ስራ አስፈጻሚ ሄለን ጋይሌ ናት፡፡ እ.ኤ.አ በ2006  የኬር ዩኤስኤ ፕሬዚደንትና ዋና ስራ አስፈጻሚ ሆና የተሸመችው ሄለን፣ በ87 የአለም አገራት ድህነትን ለመዋጋት የሚከናወኑ ስራዎችን በአግባቡ መምራቷ ይነገርላታል፡፡
በቻድ፣ ኒጀር፣ ማላዊና ሌሎች የአፍሪካ አገራት ከ750 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ያደረጉ የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ፣ የምግብና የንጹህ የውሃ መጠጥ አቅርቦት ስራዎችን አከናውናለች፡፡
እ.ኤ.አ በ2003 ሮበርት ውድ ጆንሰን ፋውንዴሽን የተባለው የአሜሪካ ትልቁ የጤና ክብካቤ ተቋም ፕሬዚደንትና ዋና ስራ አስፈጻሚ ሆና የተመረጠችው ሪዛ ላቪዞ ሙርኒ፣ ሌላኛዋ የፎርብስ የአመቱ ሃያል ጥቁር ሴት ናት፡፡ ፋውንዴሽኑን ለአመታት በስኬታማነት መምራቷ የሚነገርላት ሙርኒ፣ ተቋሙን በመምራት የመጀመሪያዋ ሴት እንዲሁም የመጀመሪያዋ አፍሪካ አሜሪካዊ ናት፡፡

ምእመናን ለሚከፍሉትና ለሚሰጡት ገንዘብ ደረሰኝ የመጠየቅ ልማድ ሊኖራቸው ይገባል
ድብቅ ሙዳየ ምጽዋት ማስቀመጥ፣ በዣንጥላና በምንጣፍ ገንዘብ መለመን ይከለከላል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ገዳማት፣ አድባራትና አብያተ ክርስቲያናት የካሽ ሬጅስተር ማሽንን ለገቢ መሰብሰቢያነት ለመጠቀም  ቅድመ ዝግጅት እያደረጉ እንደሆነ ተገለጸ፡፡
ዘመኑን ያልዋጀውንና ጥራት የጎደለውን፣ ለሙስናና ብክነት የተጋለጠውን የቤተ ክርስቲያኒቱን የፋይናንስ አሠራርና ቁጥጥር ችግር፤ ግልጽነት፣ ወጥነት፣ ተቀባይነትና ተጠያቂነት ባለው የፋይናንስ አያያዝ ሥርዐት ለመቅረፍና ለማድረቅ ያስችላል፤ በሚል በቀረበው የሀገረ ስብከቱ የሒሳብ አያያዝ ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ ረቂቅ ላይ እንደተጠቀሰው÷ በማንኛውም መንገድ የተሰበሰበ ገንዘብ፣ ሕጋዊ የገቢ መሰብሰቢያ ደረሰኝ ወዲያውኑ ሊቆረጥለት የሚገባ ሲኾን ይህም በዋናነት በካሽ ሬጅስትር ማሽን እንደሚከናወን ተመልክቷል፡፡
የሀ/ስብከቱ አብያተ ክርስቲያናት የካሽ ሬጅስተር ማሽን ተጠቃሚ መኾናቸው፣ በገቢ ሒሳብ አሠራርና ቁጥጥር እያጋጠሙ ያሉ ችግሮችን ለመከላከል ያስችላል ተብሏል፡፡ በጥናቱ ላይ በመነሻነት ከተዘረዘሩት ችግሮች መካከል የዕለት ገቢዎችና ደረሰኝ አጠቃቀም ተጠቅሷል።  የቤተ ክርስቲያኒቱን የገንዘብ ገቢ ሰነዶች በሕገ ወጥ መንገድ አሳትሞ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም ለግል ገንዘብ ይሰበሰባል፤ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የተከለከለ ደረሰኝ ጥቅም ላይ የሚውልበት አጋጣሚ ታይቷል፤ ከደረሰኙ /ለከፋዩ ከሚሰጠው/ የተለየ መጠን በቀሪው ላይ መጻፍና የግል ጥቅምን ማካበት ይዘወተራል፤ ዘወትርና በክብረ በዓላት በርካታ ገንዘብ ገቢ ቢኾንም በዕለቱ ወደ ባንክ ያለማስገባት ኹኔታ አለ፤ ምእመናን ለሚከፍሉትና ለሚሰጡት ገንዘብ ደረሰኝ የመቀበል ልማድ የሌላቸው መኾኑን እንደክፍተት በመጠቀም፣ ለቤተ ክርስቲያን የመጣው ገንዘብ ‹‹በየመንገዱ እየተንጠባጠበ ወፎች የሚለቃቅሙት ይበዛል››፣ በሥራ ላይ ያልዋሉ የገንዘብ ገቢና ወጪ ሰነዶች (ሞዴላሞዴሎች ሴሪ ንምራ ቁጥር) መሠረታዊ ችግር ተጠንቶ መፍትሔ አልተሰጠም፡፡
በንግሥ፣ በወርኃዊ በዓላትና በዕለተ ሰንበት በሙዳየ ምጽዋት ሳይኾን በተዘረጋ ጨርቅ ላይ የሚሰበሰብ ገንዘብ መኖሩን የሚጠቅሰው ጥናቱ፤ በዚህ መልክ የተሰበሰበው ገንዘብ ሀ/ስብከቱ በታኅሣሥ፣ 2003 ዓ.ም. ባስተላለፈው የገንዘብ ቆጠራ፣ የንብረት አመዘጋገብና አጠባበቅ የሥራ መመሪያ መሠረት/ የምእመናንና ካህናት ሰበካ ጉባኤ ተወካዮች በሙሉ በተገኙበት ቆጠራ የማይካሄድበትና በተወሰነ መልኩም ሙሉ ገንዘቡ ገቢ የማይደረግበት ኹኔታ በመኖሩ አሠራሩ ለብኩንነት፣ ሐሜትና አሉባልታ መጋለጡን አመልክቷል፡፡ በንግሥ በዓላት ወቅት ጥላ ዘቅዝቀው የሚለምኑ ሰዎች ኹሉም ስለማይታወቁ የተኣማኒነት ችግር አለ፡፡ በስእለትና በሙዳየ ምጽዋት በውጭ ምንዛሬ የሚገቡ የውጭ ሀገር ገንዘቦች፣ በመመሪያው መሠረት በዕለቱ የባንክ ምንዛሬ ወደ ብር እየተቀየሩ በተገቢው መንገድ ገቢ አለመኾናቸው፣ በምትኩ ቅያሬው ወጥነት ያለውና ለብኩንነት የተጋለጠ እንደኾነም ተገልጿል፡፡
በቃለ ዐዋዲ ድንጋጌው የተመለከተውንና በዝርዝር የሥራ መመሪያ የተላለፈውን የገቢ አሰባሰብ በተሻለ አሠራር ያጠናክራል የተባለው በፖሊሲና መመሪያ ረቂቁ የሒሳብ ሰነዶች አያያዝ፣ ምዝገባና አወጋገድ መሠረት÷ ለሒሳብ ሥራ የሚያገለግሉ ደረሰኞችና ቫውቸሮች የዋና ተጠቃሚውን ተቋም ስም ይዘው፣ በሀገረ ስብከቱ ምስጢራዊ ኮድ ይታተማሉ፤ የማሳተም ሓላፊነቱም የሀገረ ስብከቱ የፋይናንስና በጀት ዋና ክፍል ሲኾን ይህም በዋና ሥራ አስኪያጁ ፈቃጅነት የሚከናወን ይኾናል፡፡
በማንኛውም መንገድ የተሰበሰበ ገቢ ሕጋዊ የገንዘብ መሰብሰቢያ ደረሰኝ ወዲያውኑ ሊቆረጥለት ይገባል፤ ይህም በዋናነት በካሽ ሬጅስተር ማሽን ተፈጻሚ ይኾናል፤ የገንዘብ መሰብሰቢያ ደረሰኝ ከገንዘብ ሰብሳቢ ውጭ መያዝና መጠቀም አይቻልም። ማንኛውም የገንዘብ ስጦታ በገንዘብ ያዡ በኩል መሰጠት ይኖርበታል፤ ስጦታው እንደተበረከተም ወዲያውኑ የገንዘብ መቀበያ ደረሰኝ ሊቆረጥለት ይገባል፡፡ በዐይነት የሚሰጥ ስጦታ በግዥ፣ ሽያጭና ንብረት አስተዳደር ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ መሠረት በተተመነለት ዋጋ ይመዘገባል፡፡ ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ውጭ በሙዳየ ምጽዋት ሣጥን ገንዘብ መሰብሰብ አይቻልም፤ ቋሚ ሙዳየ ምጽዋት በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን የሚቀመጥበት ቦታ ተጠንቶ፣ በሰበካ ጉባኤው መጽድቅ አለበት፤ ለቆጠራ ካልኾነ በቀር ከተቀመጠበት ማንቀሳቀስ አይቻልም፤ በትከሻና ተይዘው የሚዞሩ ሙዳየ ምጽዋት ሣጥኖች ሙሉ መረጃ ተመዝግቦ ይያዛል፡፡ የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ በሚካሄድበት ወቅት ሣጥኖቹ ከመከፈታቸው በፊት ሁሉም ቆጣሪዎች የቁልፍ ካዝናውና የቁልፍ ሣጥኖች፣ የሣጥኖቹን ብዛትና እሽጋቸው አለመከፈቱን ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል፤ የተቆጠረ ገንዘብ ሙሉ በሙሉ ወዲያውኑ ካልተቻለ ከሌላ ገንዘብ ጋራ ሳይቀላቀል በበነጋው ወደ ባንክ አካውንት መግባት አለበት፤ ዣንጥላን፣ ምንጣፍንና የመሳሰሉትን በመጠቀም ገንዘብ መሰብሰብ ፈጽሞ የተከለከለ ይኾናል፡፡ዘመናዊው የፋይናንስ አሠራር በሀገረ ስብከቱ ተቋማትና አብያተ ክርስቲያናት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ሲኾንም በተጭበረበሩ ደረሰኞችና በማይታወቁ የገንዘብ አሰባሰቦች የግል ጥቅምን ማካበት በመከላከል ለክትትልና ቁጥጥር አመች ለማድረግ እንደሚያበቃ ተመልክቷል፡፡ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት፣ በልማትና በጎ አድራጎት ተቋማቱ እንዲሁም በአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ የሚዘጋጁ የፋይናንስ ሪፖርቶች ግልጽነት፣ ወቅታዊነትና ተኣማኒነት/ተቀባይነት እንዲኖራቸው ለማድረግ፣ ሀገረ ስብከቱ በሚሰበሰበው የኻያ በመቶ ፈሰስና ከአብያተ ክርስቲያናቱ በቅጽ ተሞልቶ በሚላከው ሒሳብ መካከል በየዓመቱ የሚያጋጥመውን ልዩነት ለማስወገድ እንደሚያስችል ተገልጧል፡፡
ይህም በሒደት ከፍተኛ የሀብት ክምችት የሚገኝበት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በፋይናንስ አሠራሩና መልካም አስተዳደሩ የሁሉም አህጉረ ስብከት ሞዴል በመኾን ቤተ ክርስቲያኒቱ በመንበረ ፓትርያርክ ደረጃ ማእከላዊ የፋይናንስና በጀት አስተዳደር ይኖራት ዘንድ መሠረት ለመጣል፣ የካህናቷን ኑሮ በማሳደግና በማሻሻል ሐዋርያ ተልእኮዋን ለማጠናከር ከፍተኛ አቅም የምትፈጥርበት መሠረት ለመጣል እንደሚያስችላት ታምኖበታል፡፡