Saturday, 26 October 2013 13:35

በኬንያና በዚምባብዌ የታሠሩ ኢትዮጵያውያን ይከሰሳሉ ተባለ

Written by  ማህሌት ፋሲል
Rate this item
(22 votes)

በህገወጥ መንገድ ወደ ኬንያና ወደ ዚምባብዌ ድንበር ሲያቋርጡ ተይዘው የታሰሩ መቶ ያህል ኢትዮጵያውያን ክስ ይጠብቃቸዋል ተባለ፡፡
ሰሞኑን ወደ ናይሮቢ ሊገቡ ሲሉ በፖሊስ የተያዙት ሀምሳ ሶስት ወጣት ኢትዮጵያውያን ህጋዊ ፓስፖርት እንደሌላቸውና ከአማርኛ ውጪ በእንግሊዝኛ መግባባት እንደማይችሉ የሳምራ ፖሊስ ኮማንደር ኤል ሙታሚያ ተናግረዋል፡፡ ከስደተኞቹ ጋር፣ ህገወጥ የሰዎች ዝውውር የሚያካሂዱ ደላሎች ናቸው የተባሉ ኬንያዊያንም ታስረዋል፡፡
በሌላ በኩል የዚምባቡዌን ድንበር አቋርጠው ወደ ደቡብ አፍሪካ ሊሄዱ የነበሩ ሰላሳ ስምንት ኢትዮጵያውያን በሃገሪቱ ፖሊስ ተይዘዋል፡፡ ወጣት ስደተኞቹ ወደ ዙምባብዌ የገቡት በህገወጥ መንገድ ስለሆነ ክስ ይመሰረትባቸዋል ሲል ፖሊስ ገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ፣ በኬንያና በዙምባቡዌ ለታሰሩ ስደተኞች ከመንግስት እገዛ ይደረግላቸው እንደሆነ ከአዲስ አድማስ ተጠይቀው፣ “መንግስት ሁልጊዜም ዜጐቹን የመርዳት ፍላጐት አለው፤ በየአገሩ ያሉ ኤምባሲዎቻችንም በዚህ ፖሊሲ መሰረት እየሰሩ ነው” ብለዋል፡፡
በቅርቡ የወጣው የአለም አቀፍ የስደተኞች ድርጅት መረጃ እንደሚለው በየአመቱ ከሀያሺ በላይ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያንና ሶማሊያዊያን በኬንያ በኩል ደቡብ አፍሪካ ይገባሉ፡፡

Read 2661 times