Monday, 02 March 2015 08:53

ሜድኮ ባዮ ሜዲካል ኮሌጅ ትምህርታዊ ፌስቲቫል ያካሂዳል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

*በርካታ የውጭ ዩኒቨርሲቲዎች ይሳተፉበታል

ሜድኮ ባዮ ሜዲካል ኮሌጅ የፊታችን ሰኞና ማክሰኞ ትምህርታዊ ፌስቲቫል ያካሄዳል፡፡ “የትምህርት እድልን በተቀናጀ መንገድ ከውጭ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር ተማሪዎችን ማገናኘት” በሚል መሪ ቃል በሜድኮ ባዮ ሜዲካል ኮሌጅ ውስጥ በሚካሄደው ትምህርታዊ ፌስቲቫል ላይ በርካታ የውጭ ዩኒቨርስቲዎች እንደሚሳተፉ የተገለጸ ሲሆን ከነዚህም ውስጥ የአሜሪካው ካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲና ፍራንክሊን ዩኒቨርሲቲ፣ የህንዱ አቻርያ ኢንስቲቲዩት፣የቱርኩ ኦካን ዩኒቨርሲቲ፣ የካናዳው ብሮንስቶን አካዳሚ፣ የማሌዢያው ማሌዢያ የትምህርት ማዕከል፣ የጣሊያኑ ካቶሊካ ዩኒቨርሲቲ፣ የኡጋንዳው ቪክቶሪያ ዩኒቨርሲቲ፣ የስዊዘርላንዱ ሆቴልና ቱሪዝም ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት፣ የቆጵሮሱ ግሪኒ አሜሪካን ዩኒቨርሲቲ፣ የደቡብ አፍሪካው ጆሀንስበርግ ዩኒቨርሲቲና ሌሎችም ዩኒቨርሲቲዎች እንደሚገኙበት የኮሌጁ የሚዲያ አስተባባሪ አቶ ቶፊቅ ሁሴን ገልጸዋል፡፡
በሜድኮ ባዮ ሜዲካል ኮሌጅ አስተባባሪነት ለመጀመሪያ ጊዜ የሚካሄደው ትምህርታዊ ፌስቲቫል ቀጣይነት እንደሚኖረው የተገለጸ ሲሆን የሌሎች አገራት ዩኒቨርሲቲዎችም በየተራ ፌስቲቫሉን ያዘጋጃሉ ተብሏል፡፡ የፌስቲቫሉ ዋና ዓላማ ዓለም አቀፍ ዩኒቨርሲቲዎችና ተማሪዎችን በማገናኘት ልምድ ማለዋወጥና በስኮላርሺፕ ሂደት ላይ ደላሎች የሚሰሩትን አሻጥር በማስቀረት፣ የየአገራቱ ዩኒቨርሲቲዎች በትምህርታቸው ብልጫ ላላቸው ተማሪዎች በቀጥታ የትምህርት እድል እንዲሰጡ ለማድረግ እንደሆነ አቶ ቶፊቅ ተናግረዋል፡፡  
የፊታችን ሰኞና ማክሰኞ ከጠዋቱ ሶስት ሰዓት እስከ 11 ሰዓት በሚካሄደው ፌስቲቫል፤የአገራችንም ዩኒቨርሲቲዎች የሚሳተፉ ሲሆን ፌስቲቫሉ አገራችን ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት የምታደርገውን ጥረት በማገዝ በእውቀት የበለፀገ ማህበረሰብን ለማፍራት ቁልፍ ሚና ይኖረዋል ተብሏል፡፡ በዚህ ፌስቲቫል ላይ የልምድ ልውውጦች፣ የፓናል ውይይቶችና መሰል ዝግጅቶች የሚካሄዱ ሲሆን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ መምህራንና ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት በስፍራው ተገኝተው እንዲጎበኙት ሜድኮ ባዮ ሜዲካል ኮሌጅ ጋብዟል፡፡

Read 1848 times