Monday, 09 March 2015 11:42

“ጋዜጣው ፈር ቀዳጅ ነው”

Written by 
Rate this item
(8 votes)

አቶ ሙሼ ሰሙ
(የቀድሞ የኢዴፓ ሊቀመንበር)

    አዲስ አድማስን በሶስት መሠረታዊ አቅጣጫዎች የማየው፡፡ አንደኛ ፈር ቀዳጅ ጋዜጣ ነው፡፡ በተለያዩ አምዶቹ የተለያዩ አጀንዳዎችን፡- ማህበራዊ፣ ስፖርት፣ ጤና፣ ኪነጥበብ፣ ፖለቲካና የመሳሰሉት ጉዳዮችን አካትቶ የሚወጣ ጋዜጣ ነው፡፡ በዚህ ደረጃ የተሟላ ገጽታ ይዘው መውጣት ከጀመሩ ጋዜጦች ቀዳሚው ነው፡፡ ብዙዎቹ ሲጀምሩ ዋነኛ ጉዳያቸው ፖለቲካ ብቻ ነበር፡፡ ቋሚ አምደኛ የሚባለው ነገርም ብዙ ጊዜ ከአዲስ አድማስ ጋር የመጣ ባህል ነው። ቋሚ አምደኛን ለረጅም ጊዜ ማሳተፍ በሌሎች ሀገሮች የተለመደ ነው፡፡ በ97 ዓ.ም ከተፈጠረው መንገራገጭ ውጪ አብዛኛውን ጊዜ ጋዜጣው በተቻለው መጠን ሚዛናዊና ምክንያታዊ ለመሆን ጥረት ሲያደርግ አያለሁ።
ሁለተኛው ፈር ቀዳጅ ነው የሚያስብለኝ በሌሎች ጋዜጦች ላይ የሚደርሰው ፈተና ሁሉ በዚህ ጋዜጣ ላይ አይደርስም የሚል እምነት የለኝም፡፡
የተለያዩ ተግዳሮቶች አሉበት፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያ ውስጥ ተግዳሮት የሚያጋጥመው ከመንግስት ብቻ አይደለም፡፡ በመንግስት ውስጥ የተቀመጡ ባለስልጣኖችም የተግዳሮት ምንጭ ናቸው። ያንን ሁሉ ተቋቁሞ ላለፉት 15 አመታት ሣይቋረጥና ሣያጓድል መውጣቱ በጣም ትልቅ ፈር ቀዳጅነት ነው ብዬ አምናለሁ።
ይሄ ደግሞ የምክንያታዊነት ውጤት ነው። ሽያጩ ጨመረ ቀነሰ ሳይባል የፖለቲካው ትኩሳትና መቀዛቀዝን ሳይከተል ወጥነትን ይዞ መሄዱ አንዱ ፈርቀዳጅነት ነው፡፡
ሌላው በህዝቡ ዘንድ ባለው ተቀባይነት በጣም ወጥቶ ወይም ወርዶ ያየሁበት ሁኔታም አልነበረም፡፡ ይሄ እንግዲህ ለአንድ ጋዜጣ በጣም ወሳኝ ነገር ነው፡፡ በቋሚነት አንባቢ ያለው፣ በትክክል ስነልቦናውን ተረድቶ መልዕክቱን ማስተላለፍ የቻለ ጋዜጣ ነው ብዬም አስባለሁ፡፡ ከነዚህ አኳያ አዲስ አድማስ ፈር ቀዳጅ ነው፡፡ የራሱን ደንበኞች መፍጠር የቻለም ጋዜጣ ነው፡፡
ወደፊት፣ ይሄን ተቀባይነቱን ተጠቅሞና አድማሱን አስፍቶ፣ ሌላውን ማህበረሰብ መድረስ የሚያስችል ውጥን ያስፈልገዋል ብዬ አስባለሁ፡፡ በፖለቲካ ጉዳይ ላይ ሠፋፊ ሃተታ የመፃፍ ጉዳይ ብዙም አይታይም፤ ለዚህ ትኩረት መስጠት አለበት፡፡ ሠፋ ያሉና ጥልቀት ያላቸው ፅሁፎች የሚያስተናግድበት ሁኔታ ሊታሰብ ይገባል፡፡ እንደ ተቋም፤ በእነዚህ 15 አመታት ግዙፍና ሠፊ መሆን መቻል ነበረበት፡፡ ያንን መፍጠር ያስፈልጋል። በቂ አቅም ሲፈጥር ተፅዕኖ መቋቋምና ስራውን በነፃነት መስራት ይችላል፡፡

Read 2159 times