Saturday, 04 July 2015 09:32

የአለም ባንክ የኢትዮጵያ የነፍስ ወከፍ ገቢ 550 ዶላር ነው አለ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

ኢትዮጵያ በነፍስ ወከፍ ገቢ ከ213 አገራት 203ኛ ሆናለች
- መንግስት የነፍስ ወከፍ ገቢያችን ከ550-700 ዶላር ደርሷል ይላል
- ሞናኮ በ100 ሺህ ዶላር ስትመራ፣ ማላዊ በ250 ዶላር መጨረሻ ላይ ትገኛለች
           በየአመቱ ሃምሌ ወር መጀመሪያ ላይ የዓለማችንን አገራት ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ ይፋ የሚያደርገው የአለም ባንክ፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት የኢትዮጵያ አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ 550 ዶላር እንደነበር ገለፀ፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት በበኩሉ፤ አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢያችን ከ550-700 ዶላር ደርሷል ማለቱ ይታወቃል፡፡የዓለም ባንክ ከትናንት በስቲያ ያወጣው የአለማችን አገራት የኢኮኖሚ ሁኔታ መረጃ እንደሚያሳየው፣ ኢትዮጵያ በአመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ ከዓለማችን 213 አገራት 203ኛ ደረጃን ይዛለች፡፡
የባንኩ ያለፈው ዓመት የአገራት አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ መረጃ እንደሚያሳየው፤ 10 የአለማችን አገራት፣ በ2013 ከነበራቸው የነፍስ ወከፍ ገቢ ጭማሪ ያሳዩ ሲሆን፣ ካላደጉ የአለማችን አገራት መካከል ባንግላዴሽ፣ ኬንያ፣ ማያንማር እና ታጂኪስታን የነፍስ ወከፍ ገቢያቸውን በማሻሻል ወደ አነስተኛ መካከለኛ ገቢ አገራት ሲቀላቀሉ፣ ደቡብ ሱዳን በበኩሏ፤ የነፍስ ወከፍ ገቢዋ በመቀነሱ ከዝቅተኛ ገቢ አገራት ጋር ተቀላቅላለች ብሏል የአለም ባንክ፡፡ሞንጎሊያና ፓራጓይ በ2013 ከነበሩበት አነስተኛ መካከለኛ ገቢ፣ ዘንድሮ ወደ ከፍተኛ መካከለኛ ገቢ አገራት ተርታ መቀላቀላቸውን የገለጸው የአለም ባንክ፤ አርጀንቲና፣ ሃንጋሪ፣ ሲሸልስና ቬንዙዌላ በበኩላቸው ደረጃቸውን በማሻሻል አምና ከነበሩበት ከፍተኛ መካከለኛ ገቢ ወደ ከፍተኛ ገቢ አገራት ሸጋግረዋል ብሏል፡፡በአመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ ከአለማችን አገራት ዝቅተኛውን ደረጃ የያዘችው ማላዊ ናት ያለው የአለም ባንክ፤ በ2014 የነፍስ ወከፍ ገቢዋ 250 ዶላር ብቻ የሆነው ማላዊ፣ ባለፉት 24 አመታት
የነፍስ ወከፍ ገቢዋ የጨመረው በ70 ዶላር ብቻ ነው ብሏል፡፡ በአንጻሩ በአመቱ ከፍተኛውን የአለማችን አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ ያገኘችው የፈረንሳዩዋ ከተማ ሞናኮ ስትሆን፣ የነፍስ ወከፍ ገቢው ከ100 ሺህ ዶላር በላይ ነው ተብሏል፡፡በአለም ባንክ መስፈርት መሰረት፤ አመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢያቸው ከ12ሺህ ዶላር በላይ የሆኑ፣ ከፍተኛ ገቢ፤ ከ12 ሺ 735 እስከ 4ሺህ 126 ዶላር የሆኑ፣ ከፍተኛ መካከለኛ ገቢ፣ ከ4ሺህ 125
እስከ 1ሺህ 46 ዶላር የሆኑ፣ ዝቅተኛ መካከለኛ ገቢ፤ ከ1ሺህ 45 ዶላር በታች የሆኑ፣ ዝቅተኛ ገቢ
ያላቸው አገራት ተብለው ይመደባሉ፡፡

Read 7125 times