Saturday, 08 August 2015 09:20

“የሸቀጦች ዋጋ ናረ” ማለት፣ “የመቶ ብር ኖቶች በዙ” ማለት ነው

Written by  ዮሃንስ ሰ.
Rate this item
(8 votes)

አገሪቱ ውስጥ የመቶ ብር ኖቶች መጠን
በ1999 ዓ.ም     7.7 ቢሊዮን ብር
በ2000 ዓ.ም    10 ቢሊዮን ብር
በ2001 ዓ.ም    14 ቢሊዮን ብር
በ2002 ዓ.ም    17 ቢሊዮን ብር
በ2003 ዓ.ም    23 ቢሊዮን ብር
በ2004 ዓ.ም    30 ቢሊዮን ብር
በ2005 ዓ.ም    40 ቢሊዮን ብር
በ2006 ዓ.ም    40 ቢሊዮን ብር
በ2007 ዓ.ም    53 ቢሊዮን ብር

    ከሰባት ዓመት በፊት በ99 ዓ.ም፣ በአገሪቱ የነበረው ጠቅላላ የመገበያያ ገንዘብ፣ 12 ቢሊዮን ብር ነበር። ከዚያስ? ከዚያ በኋላ ያለውማ፣ “የተዋጣለት የ‘Inflation’ ታሪክ ነው” ልንለው እንችላለን - ገንዘብ እንዴት እንደሚረክስ የሚያሳይ ታሪክ። በአዲሱ ሚሊኒዬም መግቢያ ላይ፣ 15 ቢሊዮን ብር ከደረሰ በኋላ፣ በዚያው ዓመት መጨረሻ ላይ ወደ ሃያ ቢሊዮን፣ እንደገና በቀጣዩ ዓመት አጋማሽ፣ ወደ 24 ቢሊዮን ብር ተሸጋግሯል።
በቃ፤ ሦስት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ፣ በአገሪቱ ውስጥ የሚንቀሳቀሰው የገንዘብ መጠን በእጥፍ ጨምሯል። ያው፣ ገንዘብ ሲረክስ፣ የሸቀጦች ዋጋ ይጨምራል። ሚስጥር አይደለም። ማለትም... በ2000 ዓም. እና በ2001 ዓ.ም፣ በዋጋ ንረት፣ ኢትዮጵያ የአለም አንደኛ የሆነችው አለምክንያት አይደለም።
ያኔ ነው፣ መንግስት የብር ኖት ህትመቱን ረገብ ያደረገው፣ ከ2001 ዓ.ም አጋማሽ በኋላ፣ ለአንድ ዓመት ያህል፣ ብዙም አልጨመረም። ለዚህም ነው፣ የዋጋ ንረቱ (ወደኋላ ባይመለስም)፣ ቀስ በቀስ መረጋጋት የጀመረው። ግን አልዘለቀበትም። ለምን? መንግስት እንደገና፣ የብር ሕትመቱን ተያያዘዋ።
በአገሪቱ የሚንቀሳቀሰው የብር ኖቶች መጠን፣ ከ26 ቢሊዮን ብር ወደ 39 ቢሊዮን ብር የጨመረው፣ በ18 ወራት ውስጥ ነው - እስከ 2003 ዓ.ም መጨረሻ ላይ። ይሄኛው አመትም እንዲሁ፣ “በመላው አለም ከቀዳሚዎቹ ተርታ የሚጠቀስ የዋጋ ንረት”፣ በኢትዮጵያ የተከሰተበት ወቅት እንደሆነ አስታውሱ። የብር ኖቶች መጠን፣ እንዲያ በአጭር ጊዜ ውስጥ በሃምሳ በመቶ ሲጨምር፣ ገንዘብ መርከሱና የሸቀጦች ዋጋ ሽቅብ መምጠቁ የግድ ነው።
በተቃራኒው፣ የብር ህትመት ረገብ ሲል ደግሞ፣ የዋጋ ንረቱ ይረጋጋል። ከ2003 ዓ.ም የመጨረሻ ወራት በኋላ፣ ያሉትን 18 ወራት መመልከት ይቻላል። ታተመ፣ ታተመና፤ የአገሪቱ የብር ኖቶች ወደ 46 ቢሊዮን ገደማ ደረሰ - እስከ 2005 መግቢያ ማለት ነው። በዚህ ጊዜ ውስጥ የብር ኖቶች መጠን የጨመረው፣ በ17% ገደማ ነው። ቀላል አይደለም። ግን፣ እንደ በፊቱ በሃምሳ ፐርሰንት ባለመጨመሩ፣ “ትንሽ ተሽሎታል” ልንል እንችላለን። በዚህም ምክንያት፣ በ2003 ዓ.ም ከሰላሳ በመቶ በላይ እያሻቀበ የነበረው የሸቀጦች ዋጋ፣ ቀስ በቀስ እየተረጋጋ ወደ አስር በመቶ እየበረደ መጥቷል።
ከዚያስ?
ከ2005 ዓ.ም መግቢያ አንስቶ፣ እስከ 2006 አጋማሽ ድረስ ባሉት 18 ወራት፣ ምን ተፈጠረ?
የዋጋ ንረቱም ይበልጥ ተረጋጋ። የሸቀጦች ዋጋ መጨመሩኮ አልቆመም። ግን፣ አመታዊው የዋጋ ጭማሪ፣ ወደ ስድስት ወደ ሰባት በመቶ በመውረድ፣ ቀዝቀዝ ብሏል። ለምን? የብር ህትመቱ ይበልጥ ረግቧላ። የገንዘቡ መጠን፣ 51 ቢሊዮን ብር ደርሷል። ግን፣ በ18 ወራት ውስጥ፣ በአራት ተኩል ቢሊዮን ብር (በአስር በመቶ ገደማ) ነው የጨመረው። ከቀድሞው ጋር ሲነፃፀም፣ “ደህና እየተሻለው መጥቷል” ልንል እንችላለን።
በዚሁ እርጋታው አለመቀጠሉ ነው ችግሩ። በ2006 መጨረሻ ላይ፣ የብር ህትመቱ እንደገና አገረሸበት።
ሰሞኑን ብሔራዊ ባንክ ባወጣው ሪፖርት ላይ፣ ባለፈው መጋቢት 2007 ዓም፣ በአገሪቱ ውስጥ ያለው የብር ኖቶች መጠን ምን ያህል እንደሆነ ተገልጿል። 64 ቢሊዮን ብር ደርሷል፣ ይላል ሪፖርቱ።
እውነትም አገርሽቶበታል። ያው... በአንድ አመት ተኩል ጊዜ ውስጥ፣ የብር ኖቶች መጠን፣ እንዲህ በ25 በመቶ ሲጨምር፣... የሸቀጦች ዋጋ እንደ በፊቱ ተረጋግቶ ሊቀጥል አይችልም። ሰሞኑን በማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ የወጣው መረጃም፣ ይህንን ያረጋግጣል።
ካለፈው መስከረምና ጥቅምት ወር ወዲህ፣ የሸቀጦች የዋጋ ንረት ያለማቋረጥ እያሻቀበ መጥቷል። እንዳትሳሳቱ። “የሸቀጦች ዋጋ ያለማቋረጥ እየጨመረ ነው” ማለቴ አይደለም። ጭማሪውንማ ለምደነዋል። መንግስት፣ የብር ህትመት ላይ በደንብ ፍሬን ለመያዝ ፈቃደኛ እስካልሆነ ድረስ፣ የሸቀጦች ዋጋ እየጨመረ መሄዱን አያቆምም። አስቸጋሪው ነገር፣... የጭማሪው ፍጥነት እየባሰበት መምጣቱ ነው። በአመት ውስጥ የሚከሰተው የዋጋ ጭማሪ፣ ከአስር በመቶ በላይ እየሆነ መምጣቱ ነው ፈተናው።
መስከረም ላይ፣ አመታዊው የዋጋ ጭማሪ ከስድስት በመቶ ብቻ እንደነበረ የሚገልፀው የስታትስቲክስ ኤጀንሲ መረጃ፤ ታህሳስ ላይ ሰባት መቶ፣... የካቲት ላይ ስምንት በመቶ፣... ሚያዚያ ላይ ዘጠኝ በመቶ፣... በሰኔ ወር ደግሞ ከአስር በመቶ በላይ ሆኗል። እንደ “ቀይ መስመር” ተደርጎ የሚታሰበውን ድንበር፣ ጥሶ አለፈ ማለት ነው - ወደ “ደብል ዲጂት” ተሻግሯል።
ሐሙስ እለት የተሰራጩ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ደግሞ፣ በሐምሌ ወር አመታዊው የዋጋ ንረት፣ ብሶበት 12% ደርሷል። የአለም ባንክ እንደሚለውማ፣ የዋጋ ንረቱ ከዚህም በላይ ወደ 15 በመቶ መጠጋቱ አይቀርም ነበር - በአለም ገበያ፣ የነዳጅ ዋጋ ከአምናው ባይቀንስ ኖሮ።
በእርግጥ፣ ባለፉት አመታት እንዳየነው፣ ቅጥ ባጣ የገንዘብ ህትመት ሳቢያ “የዋጋ ንረት” በተባባሰ ቁጥር፣ ጥፋቱ የሚሳበበው በነጋዴዎችና በቢዝነስ ሰዎች ላይ ነው።
ዘንድሮም፣ መንግስት፣ ጥፋቱን በነጋዴዎች ላይ ለማሳበብ መሞከሩ አይቀርም። ነገር ግን፣ ከንቱ ሙከራ ነው። ለነገሩ፣ አብዛኛው ኢትዮጵያዊም፣ ነጋዴዎችን ለማውገዝና ለመወንጀል እጅጉን ይፈጥናል። ጨርሶ፣ መረጃዎችን በወጉ ማየትና ማገናዘብ አያስፈልገውም። ደግሞ ነጋዴዎችን ለማውገዝ ምን መረጃ ያስፈልጋል? ባህላችን ነው። ግን ከንቱ ባህል ነው። አመት አመት፣ እውነታውን በመካድ፣ “አጭበርባሪና ስግብግብ ነጋዴዎች ናቸው ዋጋ የሚያስወድዱት” እያልን በጭፍን ብናወግዝ፣ ምን ትርጉም አለው? እውነታውን አይቀይረውማ። እንዲያው፣ ጭፍንነት ባህል ሆኖብን ነው እንጂ!
“የጭፍንነት አባዜ”፣ በመንግስት ላይ ብቻ ሳይሆን፣ በአብዛኛው ዜጋ፣ እንዲሁም በአብዛኞቹ ተቃዋሚዎች ዘንድ፣ ዘወትር የምንመለከተውም በሌላ ምክንያት አይደለም - ከአገሪቱ ባህል ጋር የተሳሰረ ስለሆነ ነው። አንዳንዶቹ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎችን እዩዋቸው። ስንትና ስንት መወገዝ የሚገባው፣ ተጨባጭ ጥፋት በበዛበት፣ እንደኢትዮጵያ በመሰለ አገር፣ እንዴት በጭፍን ማውገዝንና መቃወምን ይመርጣሉ? “ባቡሩ፣ አስፋልቱ፣ ግድቡ... ሕይወት የለውም” ብሎ ማወገዝና መጮህ ምን ይባላል? የጭፍንነት ባህል ካልሆነ በቀር።
በተደጋጋሚ ዘወትር የምናየው ሌላው ነገር ምን መሰላችሁ? በጭፍን ማውገዝ፣ ለተጨባጭ ችግሮች መፍትሄ አይሆንም።
ልክ እንደዚያው፣ የዋጋ ንረት ሲከሰት፣ በጭፍን፣ ነጋዴዎችን ማውገዝም፣... ቅንጣት መፍትሄ አያመጣም። ይልቅስ፣ ግራ መጋባትንና ግርግርን በመፍጠር፣ ለተጨማሪ ጉዳት ይዳርጋል። በተለይ ዛሬ ዛሬ፣ ጉዳቱ ቀላል አይደለም። በአራቱም አቅጣጫዎች መመልከት ትችላላችሁ። በአላስፈላጊ ቀውስ የሚታመሱ በርካታ አገራትን ነው የምታዩት። ምናለፋችሁ! ቀውስ የበዛበት ዘመን ላይ ነን ያለነው።
የዋጋ ንረት ከተባባሰ፣ ...ከዚያም መንግስት ጥፋቱን በሌላ ለማሳበብ፣ ነጋዴዎችን እያወገዘ፣ የዋጋ ቁጥጥር ሲያስፋፋ፣... በዚህም ተጨማሪ ግርግር እየተፈጠረ ገበያው ሲናጋ... ሄዶ ሄዶ፣ መጨረሻው ባያምርስ? አንዴ ተንሸራትተን ወደ ቀውስ ከገባን ደግሞ፣ መመለሻና መውጫ ላይገኝ ይችላል። በየጊዜው፣ ወደ ቀውስ እየገቡ፣ እዚያው የሚሰቃዩ አገራትን እንጂ፣ ከቀውስ ወጥተው የሚያገግሙ አገራትን ማየት ብርቅ ሆኗል - በዛሬው የቀውስ ዘመን።
በሌላ አነጋገር፤ ካሁን በፊት እንደተለመው፣ ዛሬም በጭፈንነት፣ ችግሮችን በሌሎች ላይ ለማሳበብ መሞከር፣ አያዋጣም። አደጋው፣ ከቁማር ጨዋታ አይተናነስም።
በአጭሩ ምን ለማለት ፈልጌ ነው? መንግስት፣ መጠንቀቅ አለበት። ደግሞም ውስብስብና አስቸጋሪ አይደለም - ጥንቃቄው።
ቅጥ ካጣ የብር ህትመት ከተቆጠበ፣ የዋጋ ንረት አይከሰትም። በቃ።

Read 4241 times