Monday, 30 October 2023 09:59

የውጭ ሀገር ገንዘቦችን በማተምና ማዕድኖችን በመያዝ ወንጀል የተከሰሱት የፀሐይ ሪል ስቴት ጀነራልማናጀርን ጨምሮ 9 የውጭ ሀገር ዜጎች የዋስትና ጥያቄ ውድቅ ተደረገ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

የውጭ ሀገር ገንዘቦችን በማተም እና የተለያዩ ማዕድኖችን በመያዝ ወንጀል የተከሰሱት የፀሐይ ሪል ስቴት ጀነራል ማናጀርን ጨምሮ 9 የውጭ ሀገር ዜጎች ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄ ውድቅ ተደረገ።

ፍርድ ቤቱ የተከሳሾቹን የዋስትና ጥያቄና የዐቃቤ ሕግ የመቃወሚያ ክርክሮችን መርምሮ የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ ያደረገው።

የዋስትና ጥያቄያቸውን ውድቅ ያደረገው የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ልደታ ምድብ 8ኛ የገቢዎችና ጉሙሩክ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ነው።

በቀረበባቸው ተደራራቢ ክስ ላይ የዋስትና ጥያቄያቸው ውድቅ ከተደረገባቸው ተከሳሾች መካከል የፀሐይ የሪል ስቴት መስራች፣ ባለድርሻ እና ስራ አስኪያጅ ቺያን ኩዊን ጨምሮ ዘጠኝ የውጭ ሀገር ዜጋ የሆኑ ተከሳሾች ናቸው።

የፍትህ ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዐቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ ላይ የወንጀል ተሳትፎ ጠቅሶ ተደራራቢ ሰባት ክሶችን በየድርሻቸው አቅርቦባቸው ነበር።

በተለይም ባቀረበው በ1ኛ ክስ ላይ ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ተከሳሾች ላይ ብቻ በቀረበው ክስ ላይ እንደተመላከተው የወንጀል ህግ አንቀፅ 32 ንዑስ ቁጥር 1/ሀ እና አንቀጽ 356 ላይ የተደነገገውን በመተላለፍ ተከሳሾቹ ፀሀይ ሪል ስቴት ኃ/የተ/የግ/ማህበር ውስጥ 11ኛ ፎቅ ላይ በሚገኘው ቤት ውስጥ ከነሃሴ 24 ቀን 2015 ዓ. ም እስከ ጳጉሜ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ ሀሰተኛ ገንዘብ ለመስራት የሚያገለግሉ መሳሪያዎች፣ የተለያዩ ኬሚካሎች እና ወረቀቶች በመጠቀም ሀሰተኛ የአሜሪካ ዶላር፣ ዩሮ፣ የእንግሊዝ ፓውንድ፣ የቻይና ይዋን እና የሌሎች የተለያዩ ሀገራት ገንዘቦችን አመሳስለው በማተም ላይ እያሉ እጅ ከፍንጅ ተይዘዋል የሚል ክስ ቀርቧል።

በሁለተኛው ክስ ደግሞ የወንጀል ህጉ አንቀፅ 32/ንዑስ ቁጥር 1/ሀ እናአንቀጽ 371 ንዑስ ቁጥር 2 ላይ የተደነገገውን በመተላለፍ፣ በሚኖሩበት ቤት ውስጥ ገንዘቦች ለመስራት የሚያገለግሉ፣ 2 የብር ማተሚያ ማሽን እና የተለያዩ ኬሚካሎች ማለትም በጀሪካን፣ በጠርሙስ፣ በብልቃጥ እና በበርሜል ባለ 500 ኖት ሀሰተኛ ዩሮ ለመስራት የተዘጋጀ 60 ሚሊየን 750 ሺህ ብር የሚገመት ነጭ ወረቀት ብዛት በነጠላ 121 ሺህ 500 ዩሮ እና 42 ሚሊየን 400 ሺህ ዶላር የሚገመት ሀሰተኛ ዶላር ለመስራት የተዘጋጀ ባለ 100 ኖት 424 ሺህ አረንጓዴ ወረቀት የተገኘባቸው መሆኑን ዐቃቤ ህግ ጠቅሷል።

በተጨማሪም 16 ሚሊየን 150 ሺህ የሚገመት ነጭ የዶላር ወረቀት፣ የተለያየ ነጭ ዱቄት፣ አንዱ እሽግ በውስጡ 500 ወረቀት የያዘ 32 እሽግ በብር ቅርፅ የተቆራረጡ ወረቀቶች፣ በአልሙንየም የተጠቀለለ በገንዘብ ቅርፅ የተቆረጠ ጥቁር ቀለም ያለው ወረቀት፣ 28 እሽግ አንዱ 500 የያዘ የገንዘብ መስሪያ ወረቀት፣ እንዲሁም ገንዘብ ለመስራት የሚያገለግሉ መስሪያና መሳርያዎች ይዘው በፀጥታ አካላት በተደረገ ክትትል ይዘውት የተገኙ መሆኑን ዐቃቤ ሕግ ጠቅሶ ሀሰተኛ ነገሮችን ለመስራት የሚያገለግሉ መስሪያ እና መሳሪያዎች መያዝ ወንጀል ክስ አቅርቦባቸዋል።

3ኛ ክስ ደግሞ በ1ኛ ተከሳሸ ላይ ብቻ የቀረበ ሲሆን÷ በዚህም የወንጀል ህግ አንቀፅ 359 ስር የተደነገገውን በመተላለፍ በጳጉሜን 1 ቀን 2015 ዓ.ም በተደረገው ፍተሻ ሀሰተኛ የሆኑ ባለ 100 የገንዘብ ብዛቱ 297 ሺህ 400 የአሜሪካ ዶላር፣ ባለ 50 የገንዘብ ብዛቱ 36 ሺህ 250 የእንግሊዝ ፓውንድ፣ ባለ 500 ዩሮ 62 ሺህ የሆነ፣ እና ባለ 200፣ 650 ሺህ 600 ዩሮ፣ እንዲሁም ባለ 1 ሺህ 567 የቻይና ዩዋን ይዞ የተገኘ መሆኑ ተጠቅሶ ተከሳሹ ላይ ሀሰተኛ ገንዘብ ይዞ መገኘት ወንጀል ክስ ቀርቧል።

በሌላ በኩል በአንደኛ ተከሳሽ ላይ በሌላኛው በቀረበበት 5ኛ ክስ ላይ ደግሞ ተከሳሹ ማዕድን የመያዝ ፍቃድ ሳይኖረው ክብደቱ 108 ነጥብ 43 እና 51 ነጥብ 88 ግራም የሚመዝን ኦፓል የተፈጥሮ ማዕድን እና 4 ነጥብ 99 ግራም የሚመዝን ኳርትዝ እንዲሁም 77 ነጥብ 71 ግራም የሚመዝን አጌት የተፈጠሮ ማዕድን እና 104 ነጥብ 59 ግራም የሚመዝን ማግኔታይት የተፈጥሮ ማዕድን ይዞ የተገኘ መሆኑ በክሱ ተጠቅሶ ፍቃድ ሳይኖረው የተፈጥሮ ማዕድን መያዝ እና የአዋጁን ድንጋጌዎች መተላለፍ ወንጀል ክስ መቅረቡ ይታወሳል።

በተለይም አንደኛ ተከሳሽ በኮንትሮባንድ ወንጀል ክስ የቀረበበት ሲሆን÷ ሌሎቹ ማለትም ከ2ኛ እስከ 9ኛ ተራ ቁጥር የተጠቀሱት ተከሳሾች ላይ ደግሞ የፀና የመኖሪያ ፍቃድ ሳይኖር በሀገር ውስጥ መኖር ወንጀል ክስ ቀርቧል።፡

በአጠቃላይ ተከሳሾቹ ላይ የቀረበባቸው ተደራራቢ የወንጀል ክስን በችሎት እንዲደርሳቸው ተደርጓል ማንነታቸውም ተረጋግጧል።

ከ1 እስከ 6 ኛተራ ቁጥር የተጠቀሱ ተከሳሽ ጠበቆች የአንደኛ ተከሳሽ የልብ ህመምተኛ መሆናቸውንና ቋሚ አድራሻ እንዳላቸው ጠቅሰው የዋስትና መብት እንዲፈቀድ ጠይቀዋል ነበር።

በተጨማሪም ከ2 እስከ 6ኛ ተራ ቁጥር የተጠቀሱት ደንበኞቻቸውን በሚመለከት የቀረበባቸው ክስ ከ7 ዓመት በላይ የማያስቀጣ የወንጀል ድንጋጌ መከሰሳቸውን ጠቅሰው የዋስትና መብት ጥያቄ አንስተዋል።

በዐቃቤ ሕግ በኩል ደግሞ ተከሳሾቹ ከተከሰሱበት ተደራራቢ ክስ የቀረበባቸው እና ቋሚ አድራሻ የሌላቸው ከመሆኑ አንጻር ቢወጡ የዋስትና ግዴታቸውን አክብረው ሊቀርቡ አይችሉም ሲል በመቃወም ተከራክሯል።

የሰበር ሰሚ ችሎት ተደራራቢ ክሶችን በሚመለከት በልዩነት ዋስትናን ሊያስከለክል ስለሚችል ድንጋጌዎች በማብራራት በመከራከር ተጠርጣሪዎቹ ማረሚያ ቤት እንዲወርዱ ጠይቋል።

ሌሎቹ ከ7ኛ እስከ9ኛ ተራ ቁጥር የተከሰሱ በኤሌክትሪክ ባለሙያ እና ሁለት እግር ኳስ ተጫዋች ነን ያሉ የላይቤሪያና የጊኒ ዜግነት ያላቸው ተከሳሾችን በሚመለከት በችሎት የተገኙ ጠበቃ ድጋፍ ለማድረግ በማስፈቀድ ተከሳሹ በቱሪስት ቪዛ ሀገር ውስጥ በገቡ በሁለት ሳምንታቸው በፀሐይ ሪል ስቴት በሄዱበት መያዛቸውን ጠቅሶ ቪዛና ፓስፖርት ያላቸው መሆናቸውን በማመላከት ከሀገር እንዳይወጡ እግድ ተጥሎ የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጥያቄ ቀርቦ ክርክር ተደርጎበት ነበር።

የግራ ቀኙን ክርክር የመረመረው ችሎቱ ተከሳሾቹ ላይ የቀረበው ተደራራቢ ከባድ ወንጀል መሆኑን ተከትሎ ቢወጡ ተመሳሳይ ድርጊት ላይ ሊሳተፉና ቋሚ አድራሻ ስለሌላቸው የዋስትና ግዴታቸውን አክብረው ላይቀርቡ ይችላሉ የሚለውን ግምት በመያዝና እንዲሁም ዋስትና ሊገደብ የሚችሉባቸው የሰበር ሰሚ ችሎት ያስቀመጣቸው የድንጋጌ ነጥቦች በምክንያትነት በመጥቀስ የተከሳሾቹን ዋስትና ጥያቄ አለመቀበሉን አብራርቷል።

የዋስትና ጥያቄያቸው ውድቅ የተደረገባቸው ተከሳሾች ጉዳያቸውን በማረሚያ ቤት ሆነው እንዲከታተሉ በማለት ከቀጠሮ በፊት የሚቀርብ የክስ መቃወሚያ አስተያየትና የዐቃቤ ሕግ መልስን መርምሮ ብይን ለመስጠት ለህዳር 4 ቀን 2016 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

ኤፍ ቢ ሲ

Read 715 times