Saturday, 06 January 2024 21:30

“ሰውዬው! (ጃዋር መሀመድ)”

Written by  ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ካሳ ገ/ማርያም
Rate this item
(2 votes)

 ጃዋር መሀመድ ከትንታጉ ጋዜጠኛ ደረጄ ኃይሌ ጋር ያደረገውን ቃለ ምልልስ፣ እንደሌሎች ቃለ ምልልሶች አንዴ ብቻ አይቼ አላለፍኩትም። በዩቲዩብ ደግሜ ደጋግሜ ሰልሼ አይቸዋለሁ።
1ኛ- ጃዋር መሀመድ ላይ ከፍተኛ የአካልም የአመለካከትም ለውጥ ነው ያየሁበት።
የአካል ለውጥ:-  ወደ እስር ቤት ከመግባቱ አስቀድሞ ይህን ያህል የጸጉር መሸበት አልነበረውም። መልኩ ላይም ጥርት ያለ ውበት ይታይ ነበር። አሁን ግን ልክ እንደብዙዎቹ ታስረው የተፈቱ  የሀገራችን ፖለቲከኞች ሁሉ፣ ጃዋር ፊት ላይ ማድያትና ጉስቁልና በግልጽ ይስተዋላል።
ግርማ ሞገሱም በሚያስደነግጥ ሁኔታ ጠፍቷል። ፊቱ ላይም ቀድሞ ይታይ የነበረው በራስ የመተማመን ስሜት  የለም። በሰጠው ቃለ ምልልስ ላይ፤ “ረጅም ሰዓት እተኛ ነበር። ምግብም ከእንቅልፌ ቀስቅሰው  ብላ ተብዬ ነበር የምበላው፣ … ጠዋት ላይም ተቀስቅሼ ነበር ወደ መጸዳጃ ክፍል ደርሰህ ና የምባለው።” ብሏል። ችግሩ ግን በሰአቱ ያለመመገብ  ብቻ ሳይሆን እንደ ቀድሞው የተመጣጠነና የተመረጠ  ምግብ ያለማግኘትም  ሊሆንም እንደሚችልም እገምታለሁ።
በዚያ ላይ እስር ቤት በተፈጥሮው ምቾት ሳይሆን ስጋትና ጭንቀት የሚፈጥር ነው።
የአመለካከት  ለውጥ:- ልክ እንደሰውነቱ ሁሉ ከፍተኛ የሆነ የአመለካከት  (የአስተሳሰብ) ለውጥ አይቼበታለሁ። ቀደም ብሎ የሚያራምደው የብሄር ፖለቲካና የበላይነትን እንነበር። አመጽ ቀስቃሽ፣ አትርሱኝ ባይም ግለሰብ ነበር፡፡ አሁን ግን በየንግግሮቹ መሀል ”ሀገሪቱ፣ ሀገራችን፣ ህዝቦቿ ህዝባችን ወ.ዘ.ተ . . .” የሚሉ አንድነትን የሚያንጸባርቁ ቃላትን ሲጠቀም ተሰምቷል።
2ኛ:- የጃዋር ለውጥ የመጣው እንደኔ እሳቤ በእስሩ ወቅት ከገጠመው ያልጠበቀው ሁኔታ ነው።
ጠብቆት የነበረው:- ጃዋር በመንግስት ወታደሮች በቁጥጥር ስር በዋለበት (በታሰረበት ወቅት) ቄሮ በኃይል ሊያስፈታው እንደሚችል ትልቅ ግምት የነበረው ይመስለኛል። ግን አልሆነም። ይህን ሃሳቤን የሚያጠናክርልኝን አንድ እውነታ ላቅርብ። በአንድ ወቅት “ተከበብኩ” ብሎ በፌስቡክ ገጹ ፖስት ባደረገ ጊዜ በከተማው ተፈጥሮ የነበረውን ግርግር እናውቀዋለን። በማህጸን ውስጥ አዲስ እንደተረገዘ ጽንስ ባልረጋው የለውጡ መንግስት ላይም ትልቅ ስጋትን ደቅኖ ነበር። መንግስትም ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የጃዋር እንቅስቃሴ የምንጊዜም ስጋቱ እንደሆነ በማወቁ እንቅስቃሴውን በዓይነ ቁራኛ ለመከታተል ተገዷል።
ሰውየው እስከ ታሰረበት ዕለት ድረስ በጫካ ካሉ ታጣቂዎች ወይም ወደ ደደቢት ከተሰባሰቡት የህወሃት ባለስልጣናትና ባለሀብቶች የበለጠ ለብልጽግና መንግስትና ለአገር ስጋት ሆኖ መዝለቁ ይገርለታል። ሁለተኛውና እርሱም በቃለ ምልልሱ የገለጸው፣ እጁ ላይ የፖሊስ ካቴትና ከገባበት ሰአት አንስቶ በሀገሪቱም ሆነ በዋና ከተማዋ አዲስ አበባ ስላሉ እንቅስቃሴዎች ምንም ዓይነት መረጃ ስላልነበረው ምን ማድረግ እንዳለበት ፍጹም የማያውቅበት ደረጃ ላይ እንዲሆንና አደብ እንዲገዛ የተገደደ ይመስላል፡፡ሌላው ጃዋር ላይ ለውጥ ያመጣው በጥሞና ጊዜው (ወህኒ ቤት) በርካታ መጻህፍትን ማንበቡ፣ ለራሱ ጊዜ በመስጠቱ፣ ከማንም  በላይ ነኝ ብሎ ሲያስብ የቆየው የቀድሞው ፖለቲከኛ፤  ከርሱ የሚበልጥ ሀይል እንዳለ በስተመጨረሻ በመገንዘቡን እንደሚሆን አስባለሁ።
3ኛ- ጃዋር ከፖለቲካ መውጣቱ እንደ ሀገር መጠነኛ ጉዳት ይኖረዋል። ምክንያቱም ኢትዮጵያን ጨምሮ አብዛኛዎቹ የአፍሪካ መሪዎችም ሆኑ ፖለቲከኞች በልምድ ወይም በንባብ ወይም ሳያስቡት ለአለቆቻቸው ታዛዥ በመሆናቸው ብቻ ወደ ፖለቲካ ውስጥ ገቡ እንጂ ስለፖለቲካ የጠለቀ እውቀት ኖሯቸው አይደለም። በሀገራችን ያሉ ጥልቅ የፖለቲካ ዕውቀት ያላቸውና በስልጣን ላይ ያሉት ከአንድ የእጅ ጣት ቁጥር የሚበልጡ አይደሉም።
ለሰውዬው (ጃዋር) አንድ የምመሰክርለት ነገር ቢኖር፣ ፖለቲካን ጠንቅቆ ስለማወቁ ነው። ደግሞም ተምሮ ተመራምሮ ያገኘው እንጂ በልምድ ወይም የሌሎች ፖለቲከኞች መናጆ በመሆን ያመጣው አይደለም።
የሰውዬው ትልቁ ችግር ፖለቲካውን ከስሜታዊነት ጋር፣ ከሆይሆይታ ጋር መቀላቀሉ ብቻ ነው። ለአንድ ታዳጊ ሃገር አንድ ፖለቲከኛ ማጣት ልክ የተማረ የህክምና ዶክተር ሊቆጠር ይገባል ባይ ነኝ። ለራሱ ለጃዋርም ጉዳት ነው። ምክንያቱም እሱ ፖለቲከኛ የሆነው ወዶ፣ ፈቅዶ፣ አንብቦና ተመራምሮ እንጂ እንደ ሁለተኛና ሶስተኛ ምርጫው አድርጎ የገባበት ህይወት አይደለም። ከፖለቲካ መራቁ ለራሱም የውስጥ ህመም የሚፈጥርበት ይመስለኛል። የኢትዮጵያ ፖለቲካ ለጃዋር ትኩስ ድንች ዓይነት ይሆንበታል። እንዳይውጠው ያቃጥለዋል፣ እንዳይተወው እርቦታል። መሳተፍም ያለመሳተፍም በውስጡ ያለ ነበልባል ስሜት ነው።
4ኛ- ከተናገረው የተዋጠልኝ:- ከዚህ በፊት በእርሱ ምክንያት የደረሱት ጥፋቶች በስሜታዊነትና በእልህ ከነበረው የርሱ እንቅስቃሴ ጋር የተያያዘ ስለመሆኑ የተናገረበት፣ እንዲሁም በኢትዮጵያ ፖለቲካ ዙሪያ የርሱን ሚና በተመለከተ መጽሀፍ ጽፎ እያዘጋጀ መሆኑን መናገሩ አንዱ ነው።
ያልተዋጠልኝ:- ከፖለቲካ ርቆ ለመኖር ማሰቡ፣ በሀጫሉ ግድያ ወቅት በሀገሪቱ ለደረሱት ጥፋቶችና ግጭቶች ከደሙ ንፁህ ነኝ ብሎ መናገሩ።5ኛ- ሌሎች ፖለቲከኞች ከጃዋር መማር ያለባቸው:- የመርህ ሰው መሆን፣ ለቆሙለት ዓላማ ማታገልን፣ ስለፖለቲካዊ ሳይንስ ጥልቅ ዕውቀት መኖር፣ አንባቢ መሆን፣ የአዲስ ሀሳብ የአዲስ አስተሳሰብ ባለቤት መሆን፣ ነገሮችን አስቀድሞ መተንበይና ትንበያውን  ፖለቲካዊና ሳይንሳዊ ማድረግ፣ አንደበተ ርቱዕ መሆንን፣ ለመንግስት አቅጣጫ መስጠትን ተጽዕኖ ፈጣሪነትን ማዳበር ይጠቀሳሉ።መማር የሌለባቸው:- የብሄር ፅንፈኝነት አቀንቃኝ አለመሆን፣ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል አይነት እሳቤን የማንጸባረቅ ጉዳይ፣ ለሀገር ለአንድነት ስላለው አመለካት የርሱን እሳቤ ባይጋሩ፣ በአቋም በአነጋገር እሱን ለመምሰል ባይጥሩ . . .
ስለ ጋዜጠኛ ደረጄ:- ደረጄ ደርዝ ያለው ጋዜጠኛ ነው ስለሚ ጠይቀው ሰው ማንነት በደንብ የሚያውቅ፣ በቂ ዝግጅት አድርጎ የሚገኝ፣ ማንን ባቀርብ ህዝብ ሊወደው ይችላል? ምን ያህልስ ወቅታዊ ነው? ብሎ ከእንግዳው በላይ ተዘጋጅቶ የሚቀርብ ሞያውን ጠንቅቆ የሚያውቅ ባለሞያ ነው። ሌሎች ጋዜጠኞች እኔን ጨምሮ ከእርሱ ልንማር ይገባል ባይ ነኝ።

Read 1523 times