
Administrator
ሁለት የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ታገዱ
የሲቪክ ተቋማት በነፃነት የሚሰሩበት ምህዳር እንዲፈጠር ተጠይቋል
በለውጡ ማግስት የሲቪክ ተቋማት በነፃነት እንዳይንቀሳቀሱ የሚያግዱና የሚያፍኑ ህጎች መሻሻላቸውን ተከትሎ፤ ምህዳሩ የበለጠ ምቹና ነፃ እንደሚሆን ብዙዎች ጠብቀው ነበር፡፡ በእርግጥም ላለፉት 4 እና 5 ዓመታት በአንፃራዊነት የተሻለ እንቅስቃሴ ታይቶ ነበር፡፡ በርካታ ሲቪል ተቋማት ተመስርተዋ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን ሁኔታዎች ፈፅሞ ተለይተዋል ይላሉ - የሰብአዊ መብ ተሟጋቾች፡፡
ከሰሞኑ አንጋፋው የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) እና የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት አዳዲስ ተሟጋቾች ማዕከል ባወጡት መግለጫ፤ በሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶ ባለስልጣን መታገዳቸውን አስታውቀዋል፡፡ ድርጅቶቹ የታገዱት “ከተቋቋሙበት ዓላማ ውጪ ሲንቀሳቀሱ ተገኝተዋል” በሚል ምክንያት መሆኑን ጠቁመዋል።
ኢሰመጉ ከትላንት በስቲያ ታሕሳስ 17 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ እንዳመለከተው፣ በተሻሻለው የሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ዓዋጅ መሰረት ተመዝግቦ ሲንቀሳቀስ ቢቆይም፣ ታሕሳስ 14 ቀን 2017 ዓ.ም. ከሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን በተጻፈ ደብዳቤ መታገዱን አመልክቷል። ድርጅቱ ለዕግድ የበቃበትን ምክንያት ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ሲገልጽ፣ ከተቋቋመለት ዓላማ ውጪ እየተንቀሳቀሰ መሆኑንና፣ ገለልተኛ እንዳልሆነ ጠቁሞ፣ እ.ኤ.አ. በ2023 የበጀት ዓመት የአስተዳደር ወጪ ገደብ ጠብቆ እንዳልሰራና ሃላፊነት በጎደለው መልኩ እንደተንቀሳቀሰ በደብዳቤው ላይ ጠቅሷል።
በአሁኑ ሰዓት ዕግዱ በሚነሳበት ሁኔታ ላይ ከባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ጋር በመነጋገር ላይ እንደሚገኝ የገለፀው ኢሰመጉ፣ “የገጠመንን ተግዳሮት በንግግር በመፍታት አሁንም ቢሆን ለሰብዓዊ መብት መከበር፣ ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታና ለሕግ የበላይነት የአገራችንን ሕግና ስርዓትን በመከተልና የድርጅታችን ሕገደንብ በሚፈቅድልን መሰረት እንደ ሁልጊዜው በገለልተኝነትና በሃላፊነት መንፈስ ስራችንን በትጋት ለመወጣት እንጥራለን” ብሏል፣ በመግለጫው።
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ማዕከል በበኩሉ፣ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ታሕሳስ 17 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፤ ታህሳስ 16 በደረሰው ደብዳቤ፣ ድርጅታቸው ከማንኛውም እንቅስቃሴዎች እገዳ እንደተጣለበት ማወቁን ጠቁሟል። አያይዞም፣ ከባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የተላከለት ደብዳቤ የተጻፈው ታሕሳስ 14 መሆኑን ገልጾ፣ እንደ ኢሰመጉ ሁሉ ማዕከሉ የታገደው “ድርጅቱ ከተቋቋመበት ዓላማ ውጭ በመንቀሳቀሱና ገለልተኛ ባለመሆኑ” በሚሉ ምክንያቶችና “ግልጽ የሆነ የአደረጃጀት መዋቅር የሌለው ነው” በሚል ክስ እንደሆነ ተጠቅሷል።
በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ በባለስልጣን መ/ቤቱ በተጻፈው ደብዳቤ ማዕከሉ፤ “ሃላፊነት በጎደለው መልኩ የተንቀሳቀሰ መሆኑ በተደረገ ክትትልና ግምገማ ለማረጋገጥ ተችሏል” ብሏል። ይሁንና በባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የቀረቡበትን ክሶች ያጣጣለው ማዕከሉ፣ “ድርጅታችን ከተመሰረተበት ጊዜ አንስቶ ከተቋቋመበት አላማ ውጭ በየትኛውም ያልተገባ ወይም ከህግ የሚጻረር እንቅስቃሴ ላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ተሳትፎ የማያውቅ መሆኑን ገልጷል” ሲል አትቷል።
ድርጅቱ አክሎም፣ በማያውቀው መልኩ ሃሳቡ በሕግ አግባብ ባልተጠየቀበት ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ክትትልና ግምገማ ያካሄደ መሆኑን በመግለጽ፣ ያስተላለፈው ዕገዳ “አግባብነት ያለውና ሕግን የተከተለ ነው” ብሎ እንደማያምን በመግለጫው ጠቅሷል። በዕግዱ ዙሪያ “በቂ ማብራሪያ” እንዲሰጠው የሚጠይቅ ደብዳቤ ለባለስልጣኑ ማስገባቱንም ማዕከሉ አመልክቷል።
ባለስልጣኑ ይህንን ደብዳቤ ተመልክቶ ውሳኔ እስኪሰጥ ድረስም ድርጅቱ ከየትኛውም ሥራዎቹ መታገዱንና ጽሕፈት ቤቱም መዘጋቱን ድርጅቱ በመግለጫው አመልክቷል፡፡
ባለፈው ሕዳር ወር ውስጥ በጥቂት ቀናት ልዩነት የመብቶችና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል (ካርድ)፣ የሕግ ባለሞያዎች ለሰብዓዊ መብቶች ስብስብ ለሰብዓዊ መብቶች በኢትዮጵያ በባለስልጣኑ መ/ቤት የታገደ ሲሆን፤ ከቀናት በኋላ በድርጅቶቹ ላይ የተጣለው ዕግድ ቢነሳም፤ ካርድና የሕግ ባለሞያዎች ለሰብዓዊ መብቶች በድጋሚ መታገዳቸው ይታወሳል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ላይ እየተጣለ ያለው ዕገዳ አሳሳቢ መሆኑን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ማዕከል አስታውቋል፡፡
በተመሳሳይ፣ “የኢትዮጵያ መንግስት፣ የሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩ የሚሰሩ ድርጅቶችን ማዋከብና፣ ማገድ ሊያቆም ይገባል” በማለት ዓለማቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ሂዩማን ራይት ሰዎች ህዳር 27 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አሳስቦ ነበር። ተቋሙ አክሎም፤ በአገሪቱ የሲቪክ ተቋማት በነጻነት ሊሰሩበት የሚያስችል ምህዳር እንዲፈጠር ጠይቋል።
ይህ ዜና ማተሚያ ቤት እስከገባበት ሰዓት ድረስ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን የሰጠው መግለጫም ሆነ ማብራሪያ የለም።
ኤልያስ መልካ የቅንብር አሻራውን ያሳረፈበት አልበም ሊወጣ ነው
አንጋፋው የሙዚቃ ባለሙያ ኤልያስ መልካ የቅንብር አሻራውን ያሳረፈበት የድምጻዊ አብርሃም በላይነህ (አብርሃም ሻላዬ) “ቀን በቀን” የተሰኘ አልበም ሊወጣ መሆኑ ተነግሯል። በአልበሙ ወጣትና አንጋፋ ባለሞያዎች እንደተጣመሩበት ተጠቅሷል።
የፊታችን ታኅሳስ 22 ቀን 2017 ዓ.ም. በድምፃዊው የዩቱዩብ ቻናል ለአድማጭ በሚደርሰው በዚሁ አልበም ላይ፣ የዚህ ትውልድ ቀለም የሆኑት ኤልያስ መልካና ሚካኤል ሃይሉ (ሚኪ ጃኖ) በላቀ ደረጃ በሙዚቃ ቅንብር የተጣመሩበት ሲሆን፤ ወንደወሰን ይሁብ፣ መሰለ ጌታሁን፣ ናትናኤል ግርማቸውና አንተነህ ወራሽን የመሳሰሉ የግጥምና ዜማ ሞያተኞች በአልበሙ ላይ ተሳትፈዋል።
“ቀን በቀን” አልበምን ሰርቶ ለማጠናቀቅ 9 ዓመታትን እንደፈጀ ተነግሯል።
ከአስራ ሦስት ዓመታት በፊት ለሙዚቃ አድማጮች ባደረሰው “ሻላዬ” የተሰኘ ባሕላዊ ነጠላ ዜማው ከፍተኛ ተወዳጅነትና ዕውቅናን ያተረፈው አብርሃም በላይነህ (አብርሃም ሻላዬ)፤ ለዓመታት በለቀቃቸው ነጠላ ዜማዎቹ በሙዚቃ አፍቃሪያን ዘንድ ከፍ ያለ ዝናን ከማትረፉም በላይ፣ “እቴ ዓባይ” በተሰኘ ስራውም በ“All African Music Award" አሸናፊ መሆኑ ይታወሳል፡
የግጥም መድበል እየተሸጠ ነው - ይዘዙን!
በዘውዴ አለልኝ የተጻፈው ‹‹ጊዜን መሸከም›› የተሰኘ የግጥም መድበል ለንባብ በቃ። መድበሉ 54 ግጥሞችን የያዘ ሲሆን በ162 ገጾች የተቀነበበ ነው፡፡
የመጽሐፉ ቅርጽ በዋሽንት አውታረ ቅኝት የተሠራ ሆኖ በጥቁር፣ ሰማያዊ፣ ሐምራዊና ነጭ ቀለማት የተከፋፈለ ነው። ቀለማቱ ከኢትዮጵያ ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያዎች ዋሽንት፣ ክራር፣ ነጋሪትና ሞረሽ ከምትባል ወፍ ጋር የተቀነባበረ ነው። እያንዳንዱ ክፍል ቀለማዊና ሙዚቃዊ ፍካሬ መግቢያ አለው።
የግጥም መድበሉ ታትሞ ለሽያጭ ተዘጋጅቷል፡፡ መጽሐፉን ለመግዛት የምትፈልጉ በኦንላይን ይዘዙን፡፡ ዋጋው ለአገር ውስጥ 350 ብር ሲሆን፣ ለውጭ ሀገር በ20 ዶላር ተተምኗል።
የባንክ ሂሳብ ቁጥር...
አቢሲኒያ ባንክ ( bank of abyssinia) 200869327 ዘውዱ አለልኝ አራገው ( zewdu alelgn aragaw)
ዳሽን ባንክ (Dashen bank) 5472769396011 ዘውዱ አለልኝ አራጋው ( zewdu alelgn aragaw)
ንግድ ባንክ (CBE ) 1000298476936 (Daniel abreha) ዳንኤል አብርሃ
ቴሌ ብር / tellebirr፦ 0913240885 zewdu alelgn
እባክዎ ክፍያ የፈጸሙበትን የባንክ ደረሰኝ Screenshot አድርገው፣ ወይም ፎቶ አንስተው በዚህ የቴሌግራም ሊንክ @Gizienmeshekem2424 ይላኩልን፡፡
አርቲስት መስከረም አበራ የኢቭ የሕጻናት ዳይፐር የብራንድ አምባሳደር ሆነች
በተለያዩ የፊልምና የመድረክ ተውኔቶች የምትታወቀው አርቲስት መስከረም አበራ፤ የኢቭ የሕጻናት ዳይፐር የብራንድ አምባሳደር ሆና ተመርጣለች። አርቲስት መስከረም ለብራንድ አምባሳደርነቱ የተከፈላትን ክፍያ በይፋ ከመግለጽ ተቆጥባለች።
ዛሬ ታህሳስ 19 ቀን 2017 ዓ.ም. በስካይላይት ሆቴል በተካሄደ መርሃግብር፣ ስለ አርቲስት መስከረም አበራ ሞያዊ አበርክቶና ስነ ምግባር፣ በደራሲና ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ተ/አረጋይና በተውኔት ደራሲና አዘጋጅ ዳግማዊ “አመለወርቅ” ፈይሳ አማካይነት የቀረበ ሲሆን፤ ኢቭ ሞዴስ እና የሕጻናት ዳይፐር፣ አርቲስት መስከረምን ለብራንድ አምባሳደርነት መምረጡ ተገቢ መሆኑን ተናግረዋል።
አርቲስት መስከረም በበኩሏ፤ ከኢቭ ሞዴስ ጋር የነበራትን ቀደም ያለ መስተጋብር በማውሳት፣ “ከራሴ ሴትነት ጋር በተገናኘ የ’ኢቭ’ን ምርት አውቀዋለሁ” ብላለች። አያይዛም፣ “ልጅ የለኝም፤ ነገር ግን ልጅ ለወለዱ ወዳጆቼ በመስጠት ምርቱን እንዲጠቀሙ አደርጋለሁ” ስትል ቃል ገብታለች።
የብራንድ አምባሳደርነቱ ለአንድ ዓመት የሚቆይ ሲሆን፣ የቢልቦርድ፤ የቴሌቪዥንና የራዲዮ ማስታወቂያዎችን መስራት የሚያስችላት መሆኑ ተነግሯል። አርቲስቷ ከአምራች ድርጅቱ ስለተከፈላት የገንዘብ መጠን በይፋ ከመግለጽ ተቆጥባለች።
“የእኔ ደስታ በሞያዬ መቆየት ነው፤ ፍላጎቴም የሕዝቡን ስሜት መረዳት ነው። የኢቭ ዳይፐር የብራንድ አምባሳደርነት የመጀመሪያ ስራዬ ይሆናል። ወደፊት ሌሎች ስራዎች ይኖራሉ” ብላለች፤ አርቲስት መስከረም አበራ፡፡
ኢቭ ሞዴስ እና ዳይፐርን የሚያመርተው ጊዮፒዮን የንጽህና መጠበቂያ ግብዓቶች አቅራቢ ድርጅት፣ በኢትዮጵያ ስራውን ከጀመረ 16 ዓመታት ያስቆጠረ ሲሆን፤ የተለያዩ የጥራት ሽልማቶችን እንዳሸነፈ ለማወቅ ተችሏል።
ዳሸን ባንክ የሴቶችን የመሪነት ሚና ለማሳደግ የሚያስችል መርሃ ግብር አስጀመረ
ዳሸን ባንክ የሴቶችን የመሪነት ሚና ተሳትፎ ለማሳደግ የሚያስችል መርሃ ግብር አስጀምሯል፡፡ መርሃ ግብሩ የሴት ሰራተኞቹን አቅም ይበልጥ ለማጎልበት ያስችላል ተብሏል።
በመርሃ-ግብሩ ማስጀመሪያ ላይ ንግግር ያደረጉት የባንኩ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አፋው ዓለሙ፤ “ዛሬ የምንኮራባቸው የአገራችን ታሪካዊ ድሎችን እንድንጎናፀፍ ሴቶች ከፍተኛ አስተዋፅዎ አበርክተዋል” ብለዋል፡፡
ከታላላቅ አገራዊና ተቋማዊ ስኬቶች ጀርባ የሴቶች ሚና የጎላ መሆኑን የገለጹት አቶ አስፋው፤ ሴቶች ተገቢው ዕውቅና ሊሰጣቸው እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
ዳሸን ባንክ ይህን ክፍተት በአግባቡ ተገንዝቦ የሚሰራ በመሆኑ ከምስረታው ጀምሮ ሴቶችን በከፍተኛ የአመራር እርከኖች ላይ በመሾም ወደፊት በማምጣት ላይ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡
ባንኩ ሴቶችን በአግባቡ ያካተተ አሰራር በመፍጠር አዳዲስ ፈጠራዎችንና ውጤታማነትን እንደሚያጎለብት ተመላክቷል፡፡
መርሃ-ግብሩ ባንኩ ሁሉም ሰራተኞች ዕኩል ዕድል የማግኘትና የማደግ አጋጣሚ እንዲያገኙ ለማድረግ ካለው ራዕይ ጋር አብሮ የሚሄድ እንደሆነም ተጠቁሟል፡፡
በዳሸን ባንክ የሰው ሐብት ዋና መኮንን ወ/ሮ ህይወቴ ከፈለኝ በበኩላቸው፤ “ፕሮግራሙ በባንካችን ወደፊት ከፍተኛ አመራር መሆን የሚችሉ ሴቶችን ከወዲሁ ለመለየትና ለማብቃት የተነደፈ ነው” ብለዋል፡፡
በተጨማሪም፣ የተሻለ ልምድ ያላቸውን ሴቶች ድጋፍ ከሚሹ ሴቶች ጋር በማገናኘት ጠቃሚ የሙያ ዕድገት እንዲያገኙ የሚያስችሉ ድጋፎችን ለመስጠት ያለመ እንደሆነም አብራርተዋል፡፡
በመድረኩ ላይ ሐሳባቸውን ያጋሩት የ'ሴታዊት ንቅናቄ' መስራች ዶ/ር ስህን ተፈራ፤ ዳሸን ባንክ ሴቶችን በሁሉም መስክ ብቁ ለማድረግ እየሰራ ያለው ሥራ ለሌሎች ተቋማት ምሳሌ የሚሆን ነው ብለዋል።
አዲሱ “ማይክሽን መከለሻ” ቅመም በይፋ ተዋወቀ
ባለፈው መስከረም ወር ላይ ገበያውን እንደተቀላቀለ የተነገረለት አዲሱ “ማይክሽን መከለሻ” ቅመም በዛሬው ዕለት በሸራተን አዲስ ሆቴል በይፋ ተዋወቀ፡፡
“ማይክሽን መከለሻ” የተለያዩ ሃገራዊ ቅመሞችን እንዲሁም በብዙዎች ዘንድ ተወዳጅነት ያተረፈውን የሸኖ ለጋ ቃናን በውስጡ የያዘ ነው ተብሏል፡፡
ዛሬ ታህሳስ 19 ቀን 2017 ዓ.ም፣ ረፋዱ ላይ አዲሱን ምርት በይፋ የማስተዋወቅ መርህ ግብር በሸራተን አዲስ የተከናወነ ሲሆን፤የአምራች ድርጅቱ ሎንግሪቨር አግሮ ኢንዱስትሪ መሥራችና ባለቤት ከአጋሮቻቸው ጋር ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
ለተለያዩ የምግብ ዓይነቶች ከተፈጥሮአዊ ግብአቶች ተቀምሞ የተሰናዳው “ማይክሽን መከለሻ”፤ ሃገራዊ ቅመሞችን ያካተተ ሲሆን፣ ከእነዚህም ውስጥ ቅርንፉድ፣ ከሙን፣ ቀረፋ፣ የካርዌል ዘርና ሌሎች የተለያዩ ቅመሞችን በአንድ ላይ የያዘ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ሎንግሪቨር አግሮ ኢንዱስትሪ ባወጣው መግለጫ፤ ”ለዘመናዊም ሆነ ለባህላዊ ምግቦች እንዲሁም በፍስክ ወቅት ጭምር ተስማሚ ነው ነው” ብሏል፡፡
በማናቸውም ሱቆችና ሱፐርማርኬቶች ለገበያ እንደቀረበ የተነገረለት “ማይክሽን መከለሻ”፤ አንዱ በ25 ብር እንደሚሸጥ ተጠቁሟል፡፡
የ“ማይክሽን መከለሻ” አምራች የሆነው ሎንግሪቨር አግሮ ኢንዱስትሪ እ.ኤ.አ በ2022 ዓ.ም በኢትዮጵያ የተቋቋመ ድርጅት ሲሆን፤ የተለያዩ የምግብ ምርቶችን ለማምረት የተቋቋመ የውጭ ኢንቨስትመንት ኩባንያ ነው፡፡ ድርጅቱ በዱባይ በዓለማቀፍ ደረጃ ዕውቅናን ያተረፈው የዩኒግሎካል ኢንተርትሬድ አካል ነው፡፡
አሚጎስ ከ101 ሚሊዮን ብር በላይ የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ
• የማህበሩ ጠቅላላ ሃብት ከ1 ቢ.ብር በላይ ደርሷል
አሚጎስ የገንዘብ ቁጠባና ብድር የህብረት ሥራ ማህበር፣ በ2016 በጀት ዓመት በአጠቃላይ 145 ሚሊዮን ብር ማትረፉንና ከ101 ሚሊዮን ብር በላይ የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ፡፡
የማህበሩ አባላት የትርፍ ክፍፍል ድርሻ 53 በመቶ ነው ተብሏል፡፡
የህብረት ሥራ ማህበሩ ይህን ያስታወቀው ዛሬ ታሕሳስ 19 ቀን 2017 ዓ.ም፣ 11ኛ የባለአክስዮኖች ዓመታዊ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን በኢንተር ላግዠሪ ሆቴል ባካሄደበት ወቅት ነው፡፡
የማህበሩ አባላት በተገኙበት ለግማሽ ቀን በተካሄደው በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የ2016 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻፀም ሪፖርት የቀረበ ሲሆን፤ በዚህ ወቅትም የአሚጎስ ጠቅላላ ሃብት ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ መድረሱ ተነግሯል፡፡
አሚጎስ በዛሬው ጉባኤው የኅብረት ስራ ማህበሩን ጠቅላላ ጉባኤ ተወካዮች የመረጠ ሲሆን፤ በቀጣይ ያቀዳቸው ሰፋፊ ስራዎችም ቀርበዋል።
የዛሬ 12 ዓመት በሦስት ዓይን ገላጭ መሥራቾች ተጀምሮ ዛሬ ወደ 10ሺ የሚጠጉ አባላትን ያፈራው የህብረት ሥራ ማህበሩ፤ ወደ 3 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ አጠቃላይ ካፒታል ያለው ሲሆን፤ ከ120 በላይ ሰራተኞች ይዞ በተለያዩ የክልል ከተሞች ቅርንጫፎቹን በማብዛት ተደራሽነቱን እያሰፋ እንደሚገኝ ከማህበሩ የተገኘ መረጃ ይጠቁማል፡፡
አትሌት ስለሺ ስህን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ሆነው ተመረጡ
በ28ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ለቀጣይ አራት አመት ፌዴሬሽኑን በፕሬዝዳንት ለመምራት ምርጫ እየተከናወነ ይገኛል፡፡ በዚህም ከኦሮሚያ ክልል የተወከሉት አትሌት ስለሺ ስህን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ሆነው ተመርጠዋል፡፡
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ምርጫ እየተከናወነ ነው
“ትልቅ አርቲስ መሆን እፈልጋለሁ”
ባለፈው ሳምንት ዕትም የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ ከወጣቱ
ድምፃዊ ልዑል ሲሳይ ጋር ያደረገችው ቃለ ምልልስ የመጀመሪያ ክፍል ለንባብ
በቅቶ ነበር፡፡ ቀሪውና የመጨረሻው ክፍል እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡
“
” አንብቡት፡፡
ከዚህ በኋላ ነው “ልዑል” የተሰኘው ሙሉ አልበምህ የተለቀቀው?
አዎ በትክክል!
ብዙ ጊዜ አልበም ሲሰራ የአልበሙ መጠሪያ የሚሆነው ከትራኮቹ ላቅ ያለው ስራ ነው፡ አንተ አልበምህን በስምህ የሰየምክበት የተለየ ምክንያት አለህ?
አልበሙን በስሜ የሰየምኩበት ሁለት ምክንያቶች አሉኝ። አንደኛው የብራንዲንግ ጉዳይ ነው። እኔ ገና ጀማሪና አዲስ እንደመሆኔ ስሜን እንዴት አድርጌ በቀላሉ ከሰዎች አዕምሮ ውስጥ ማስረጽ እችላለሁ ከሚል መነሻ ነው። ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የአልበሙ ግጥምና ዜማዎች የእኔ አይደሉም። ነገር ግን አንዱን አንስቼ የአልበሙ መጠሪያ እንዳላደርግ ሁሉም ግጥምና ዜማዎች አሪፍ ስለሆኑ ማበላለጥ አልቻልኩም። ስለዚህ እነዚህ በአልበሙ ውስጥ የተካተቱት ስራዎች፣ የኔ ልዑል ጣዕሞችና ልዑል የሚወዳቸው ሥራዎች ናቸው ለማለት አልበሙን “ልዑል” አልነው። ጠቅለል ሲል አንድ የብራንዲንግ ጉዳይ፣ ሁለትም ስራዎቼ የራሴ የምወዳቸው ጣዕሞች ስላሉት ነው ስያሜው ልዑል የተሰኘው። 14ቱም ትራኮች አምኜባቸው ወድጃቸው፣ የሰራኋቸው የልዑል ጣዕሞች ናቸው ለማለት ነው።
“ልዑል” አልበም በአጠቃላይ ምን መልክ አለው? የህዝቡ ምላሽ ምን ይመስላል? እኔ በብዛት ከአልበምህ ሲደመጡ የምሰማቸው “የእኔ ዓመል” እና “መልኬ በቃኝ” የተሰኙትን ነው…..
አልበሙ ከወጣ ባለፈው ህዳር 26 አንድ አመት ሞላው። ተሰርቶ ለመጠናቀቅ ስድስት ዓመታትን ወስዷል። የህዝቡ ምላሽ እጅግ የሚገርምና ከጠበቅኩት በላይ ነው። እንደ ጀማሪነቴም በራሴ ዩቲዩብ ቻናል ነው የለቀቅኩት።
አዲስ አልበም ሆኖ አንተም አዲስ ድምፃዊ ሆነህ---ብዙ የተደከመበትን ስራ በአዲስና በራስህ ዩቲዩብ መልቀቅህ ስጋት አላሳደረብህም?
እርግጥ ይህ ጉዳይ የብዙዎችም ጥያቄና ስጋት ነበር። ነገር ግን ፈጣሪ ይመስገን ከጠበቅኩት በላይ ውጤታማ ሆኗል። በአሁኑ ወቅት አርቲስቶች በራሳቸው ስራዎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያደርጉ የተለያዩ ፕላትፎርሞች ተፈጥረዋል። እድሜ ለቴክኖሎጂ። የአንድ አርቲስት ንብረቶቹ ዘፈኖቹ ናቸው። ከቅጂ መብትም አንፃር፣ ከተጠቃሚነቱም አንፃር አርቲስቶች ስራዎቻቸውን በራሳቸው ዩቲዩብ መልቀቅ መቻላቸው ትልቅ እድል ነው። እነዚህ ስራዎች ለልጅ ልጅም የምናወርሳቸው፣ ተጠብቀው የሚቆዩትም በራሳችን ብንለቃቸው ነው በሚል ድፍረት ነው፤ ልዑል ዩቲዩብ ቻናል ላይ የጫንኳቸው፤ ውጤቱም አሪፍ ነው። እግዚአብሔር ይመስገን። ከገቢ አንፃር ካየነው ቀስ በቀስ ነው የሚመጣው። ነገር ግን እኔ እንደ ትልቅ ስኬት ያየሁት፣ በአዲስ ዩቲዩብ ቻናል ለቅቄውም ከጠበቅኩት በላይ መታየቱና መደመጡ ነው። እኔ አርብ ቀን ጭኜው ቅዳሜና እሁድ በዩቲዩቡ ብዙ ሰው አይቶታል፡፡ በቲክቶክና በተለያዩ ፕላትፎርሞች ዘፈኖቼን በደንብ አገኘኋቸው። እኔ ሰርፕራይዝ የሆንኩበት ነው። አሁን በዩቲዩብም ገቢ እየመጣ ለስራው ያወጣሁትን እየመለሰ ነው። በጣም የሚገርምሽ በዚህ አንድ ዓመት ውስጥ 26 እና 27 አልበሞች ወጥተዋል። ከግማሽ በላይ ያህሉ በራሳቸው ዩቲዩብ ነው የጫኑት፤ አዳዲስ ቲዩብ እየከፈቱ። ይህ ጥሩ ጅማሬ ነው። ከቅጂ መብትም አንፃር የቴክኖሎጂውን መራቀቅ ተከትሎ፣ ነገሮችን በቀላሉ ማግኘት ይቻላል። ስለዚህ ከዚህ ለመዳን በራስ ዩቲዩብ መጫን ትልቅ አጋጣሚ ነው። እኔ ደግሞ የቴክሎጂውንና የሶሻል ሚዲያውን ጉዳይ ወንድሜ መላኩ ሲሳይ ያግዘኛል እናም እድለኛ ነኝ። በሌላ በኩል በዩቲዩብ ጭኛለሁ ብዬ ዝም አላልኩም፤ ያልተቋረጠ የሬዲዮ ማስታወቂያም ሰርቼ ነበር፡፡ የማስታወቂያ ጉዳይ ሊዘነጋ የማይገባው ጉዳይ ነው። ምንም ስራ ጥሩ ቢሆን ማስተዋወቅ ግን ወሳኝ ነው። እኔ አልበሜን ለማስተዋወቅ ያልገባሁበት ቀዳዳ የለም። አንድም ስኬታማ ያደረገውና ዩቲዩብ ቻናሌንም እንዲታይ ያደረገው የፕሮሞሽኑም ጉዳይ ነው። ለምሳሌ “የኔ አመል” የተሰኘው ቪዲዮ ያለው ስራዬ ከ11 ሚሊዮን በላይ ተመልካች አግኝቷል። ሌሎችም በሚሊዮን የሚቆጠር፣ 900 ሺህ፣ 800 ሺህ፣ 600 ሺህ እይታ ያላቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተደመጡ እያደጉ ነው ያሉት።
ይህንን ቃለ ምልልስ የምናደርገው አልበምህ በወጣ በአንድ አመቱ ነው። ሰሞኑን እጅህ ከምን?
ባለፈው አመት በ2016 ዓ.ም በአልበም የመጀመሪያው በኮንሰርትም የመጀመሪያው ነበር - “ልዑል” አልበም። የእኔ አልበም ከተለቀቀ በኋላ ደከም ብሎ የነበረው የሙዚቃው ዘርፍ መነቃቃት ሲጀምር ነው ሌሎችም በድፍረት መልቀቅ የጀመሩት። እኔም አልበሜን እንዳወጣሁ በሦስት ወይም በአራት ወሩ “ልዑል” የተሰኘ ኮንሰርት በሚሊኒየም አዳራሽ በስኬት መስራት ችያለሁ። ቅድም እንዳልሽው እኔ እድለኛ ነኝ። ሰኔ 1 ቀን 2016 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ ሰው በጠበቅነው ልክ ግጥም ብሎ ጥሩ ኮንሰርት መስራታችንም አልበሙን የበለጠ ተወዳጅና ተደማጭ እንዲሆን አነቃቅቶታል። የኮንሰርቱ ቪዲዮም ላልታደሙት እንዲደርስና እንዲታይ በዩቲዩብ ቻናሌ ለቅቄዋለሁ።
እጅህ ከምን ላልሽኝ …. በቅርቡ ከእስራኤል ሀገር የሚጀምር የሙዚቃ ሾው ይኖረኛል። ቀኑም በፈረንጆች አዲስ አመት ዋዜማ ሊሆን ይችላል፡፡ በእርግጥ ቀኑን ቁርጥ አላደረጉም፤ ግን በነገርኩሽ ቀናት አካባቢ ይሆናል። ከእስራኤል በፊት እዚሁ አዲስ አበባ አንድ ሾው ይኖረኛል። ወይ ከፍ ብሎ በኮንሰርት ደረጃ ካልሆነም ሚኒ ኮንሰርት ሆኖ በሆቴል ውስጥ ሊሆን ይችላል፡፡ እሱን ጊዜው ሲደርስ የምናየው ይሆናል። በአውሮፓም ደረጃ በንግግር ላይ ያሉ የሾው ሂደቶች አሉ። ስምምነቶቹና ንግግሮቹ እያለቁ ሲሄዱ በጊዜው ይፋ እያደረግናቸው እንሄዳለን ማለት ነው። በቅርቡ የሚወጣ አንድ ነጠላ ዜማም በማጠናቀቅ ላይ ነኝ። ርዕሱ “አልቻልኩም” ይሰኛል።
ከሙዚቃ ጉዞዎችህ ምን ትጠብቃለህ?
የውጪ ሾውን በተመለከተ ለእኔ አዲስና ሞክሬው የማላውቀው ነው። ጥሩ የሆነ ታዳሚ ይመጣል ብዬ ነው የምጠብቀው። እኔ በበኩሌ በከፍተኛ ሁኔታ እየተዘጋጀሁ ነው። ዝግጅቴ ከራሴ ስራዎች በተጨማሪ የሌሎች የምወዳቸውን ድምፃውያን ስራዎች ያካተተ ነው።
ለምሳሌ የማን የማን ዘፈኖች ላይ እየተዘጋጀህ ነው… ከራስህ ስራዎች በተጨማሪ?
የቴዎድሮስ ታደሰ፣ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)፣ የንዋይ ደበበን፣ የጋሽ ማህሙድ አህመድና የጋሽ ጥላሁን ገሰሰ፡፡ እነዚህ አምስት አርቲስቶች ሥራዎች ላይ ትኩረት አድርጌ እየተዘጋጀሁ ነው።
የእነዚህን አንጋፋ አርስቶች ሥራ ክለብ ውስጥም ትጫወታቸው ነበር?
አዎ በደንብ።
አሁን ክለብ መጫወት አቆምክ?
አዎ ካቆምኩ ቆየሁ። አልበሙ ከመውጣቱ አራት ወይም አምስት ወር በፊት ነው ቀድሜ ያቆምኩት።
ክለብ ውስጥ ምን ያህል ጊዜ ሰራህ?
ወደ ስድስት ዓመት ሰርቻለሁ። ያው የምሽት ክበብ ራስን በኢኮኖሚ ከመደገፍ ባለፈ ሙያ ለማሳደግ የሚረዳ መድረክ ነው። አንዳንድ አርቲስት ራሱን በኢኮኖሚ ለመደገፍ ሙሉ ትኩረቱን ክለብ ላይ ያደርጋል። አንዳንዱ ደግሞ በሳምንት አንድ ጊዜ ክብብ እየሰራ ጎን ለጎን አልበም እየሰራ ይቀጥላል። እኔም በ6 አመት ውስጥ ለአንድ ዓመት ክለብ ያልሰራሁበት፣ በሳምንት አንድ ቀን ብቻ እየሰራሁ አልበሙ ላይ ትኩረት አድርጌ ነበር ቆየሁት። ለምሳሌ ለሦስት ዓመት ያህል ሸራተን አዲስ “ኦፊስ ባር” ነበር ሀሙስና ቅዳሜ የሰራሁት። በኦፊስ ባር ያለማቋረጥ ለሦስት ዓመት ሰርቻለሁ፡፡ ከእነሱ ጋር ሳቆም ደግሞ ሁለት ዓመት ከምናምኑን የተለያዩ ክለቦች በሳምንት አንድ ቀን አልፎ አልፎ ሁለት ቀንም እየሰራሁ የማገኘውን ገንዘብ እየቆጠብኩ፣ እንደ ወጣትነቴ ብዙ ነገሮች ቢያምሩኝም ከእነዚያ ነገሮች እራሴን እየገታሁ፣ ከወንድሜ ጋር በመተጋገዝ ነው፣ የአልበሙን ስራ ከዳር ያደረስኩት። የአልበሙን ወጪ የሸፈንነው እኛው ነን። ወንድሜ ከገንዘብም ባሻገር በብዙ ነገር ነው የሚደግፈኝ፡፡ ከኢቨንት ከአርቲስት ማኔጀርነት ባሻገር ጎበዝ ደራሲም ነው። “ማህረቤ” የተሰኘ በጊዜው ውጤታማ የሆነ ፊልም ደርሶ ፕሮዲውስ በማድረግ ለእይታ አብቅቷል። ቃልኪዳን ጥበቡና ኤልያስ አማን ተውነውበታል።
በተለያየ ዘርፍ ኪነጥበቡን እየተጠበባችሁበት ነዋ?
አዎ በሚገባ። በብዙ ድጋፍ ውስጥ ነው የመጣሁት፡፡ ነገር ግን አንድ ጀማሪ አርቲስት ምን ችሎታና አቅም ቢኖረው፣ በገንዘብም በሙያም ደጋፊ ከሌለው በጣም ይቸገራል። ከዚህም አልፎ የሙያ ስነምግባርና መልካም ባህሪ ከሌለው ያለውንም ነገር ያጣል። ምክንያቱም ያለውንም ነገር በአግባቡ መጠቀም አይችልም። ስለዚህ ለአንድ አርቲስት ብቻ አይደለም ለማንኛውም ሰው የሙያ ዲሲፕሊንና መልካም ባህሪ ያስፈልገዋል። ይሄ ከሌለ ውጤታማ የመሆኑ ጉዳይ ጥያቄ ምልክት ውስጥ ይገባል ማለት ነው። እኔን የጠቀመኝ ሜሪጆይ በምሰራበት ጊዜ ቅዳሜና እሁድ ኮርስ እንወስድ ነበር ብዬሽ አልነበር? እነዚህ ኮርሶች ለእኔ ትልቅ የጉዞ ስንቅ ሆነውኛል። አሁን ታዳጊ ወጣቶች በኪነጥበቡ በተለያዩ ውድድሮች ላይ ብቅ ብቅ የሚሉ ልጆች ላይ በግሌ የማስተውላቸው ችግሮች ስላሉ ነው። ነገሮች አልጋ በአልጋ ሆነው የሚጠብቋቸው የሚመስላቸው አሉ። ይህ አስተሳሰብ ልክ አይደለም። እኔ ይሄ የምነግርሽ ነገር ለነዚህ ታዳጊዎች ትምህርት የሚሆን ከሆነ፣ እኔ የመጣሁት ከደሀ ቤተሰብ ነው። ነገር ግን ክለብ በምሰራበት ጊዜ እኔም ወንድሜም ከምናገኘው ነገር በአግባቡ ነበር የምንጠቀመው። እንደነገርኩሽ እንደወጣትነታችን ብዙ ነገር ቢያምረንም፣ ጫማም ሆነ ልብስ አያጓጓንም ነበር። ከዚያ ቆጥበን ለአላማችንና ለኪነ-ጥበቡ ስራ ነበር የምናውለው። ከዚህ በተጨማሪ ዲሲፕሊን አለን። ትልልቅ አርቲስቶችን ስናገኝ ሥነ-ስርዓት ባለው መልኩ አናግረን አክብረን ነው የምንሸኘው። ሰውን የሚያቆየው ባህሪው ነው…. አይደለ?
ልክ “መልኬ በቃኝ” እንደተሰኘው ስራህ ማለት ነው?
ትክክል! የሙያ ዲስፕሊን ያለኝ መሆኑ፣ በትህትናና በስነ-ምግባር ሰዎችን መቅረቤ፣ ከግጥምና ዜማ ደራሲዎችም ሆነ አቀናባሪዎች ቀና የሆነ ምላሽ እንዳገኝ ስለረዳኝ ውጤታማ ስራ መስራት ችያለሁ። በአጠቃላይ ሰው ጥሩ ስነምግባርና የሙያ ዲስፕሊን ከሌለው ተሰጥኦ ብቻውን ዋጋ የለውም።
እኔ የምልህ ….. አልበምህ የወጣ ሰሞን ሰይፉ ፋንታሁን ከነፒጃማው እቤትህ መጥቶ በተኛህበት ሰርፕራይዝ ያደረገህ የእውነት ነው ወይስ ድራማ ነው?
በጭራሽ ድራማ አይደለም፤ የእውነት ነው፡፡ ከወንድሜ ጋር ተማክረው ያደረጉት ነው፡፡ ያ አጋጣሚ ደግሞ ብዙ ሰው ጋር ተደራሽ ሆኖ ሳላስበው ለአልበሜ ትልቅ ፕሮሞሽን ነበር የሆነኝ፡፡ እንደዚህ አይነት ነገር በውጪው የመዝናኛ ዘርፍ ላይ የተለመደ ነገር ቢሆንም፣ ለእኛ አገር ትንሽ እንግዳ ነገር ነውና የሰውን ቀልብ ስቦ ነበር፡፡ በዚሁ አጋጣሚ ሰይፉን በጣም አመሰግናለሁ፡፡ ሰይፍሽ ከዚያ በኋላ በሬዲዮም በማስታወቂያም ብዙ ረድቶኛል፡፡ ከሰይፉ ሾው በኋላ ብዙ ነገሮች ቀና ሆነውልኛል፡፡
ልዑል በሙዚቃ ራሱን ምን ደረጃ ላይ ማግኘት ነው ህልሙ?
እኔ እንደ አንድ ድምፃዊ ትልቅ አርቲስት የመሆን ህልም ነው ያለኝ፡፡ በእርግጥ ኢትዮጵያ እንደ እነ ጥላሁን ገሰሰ፣ አስቴር አወቀ፣ ማህሙድ አህመድ፣ ሙሉቀን መለሰና፣ ንዋይ ደበበ ያሉትን ያፈራች ሀገር ናት፡፡ ወደ ዘመናችን ስንመጣ ቴዲ አፍሮን፣ ጎሳዬ ተስፋዬን፣ እነ ጂጂን መጥቀስ እንችላለን፡፡ እነሱ ደግሞ ተተኪ ይፈልጋሉ፡፡ እኔም እነሱ ደረጃ ላይ ከመድረስ የተለየ አይደለም ህልሜ፡፡ እነሱ ደረጃ ለመድረስ ካለምሽ እንደነሱ ጥረት ድካምና የሙያ ፍቅር ብሎም የሙያ ዲሲፕሊን ያስፈልጋል፡፡ እኔም እነዚህ ሀብቶች አሉኝ ብዬ ነው የማስበው፡፡ በአጠቃላይ ትልቅ አርቲስት መሆን እፈልጋለሁ፡፡