Administrator

Administrator

87 በመቶ የማሊ ሴቶች ድብደባ ተገቢ ነው ይላሉ
የጊኒና የኢትዮጵያ ሴቶችም ድብደባ ተገቢ ነው ብለው ያስባሉ


የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የተለያዩ ተቋማት በቤት ውስጥ ጥቃት ዙሪያ ያወጧቸውን ሪፖርቶች መነሻ በማድረግ በቅርቡ በ37 የአፍሪካ አገራት ላይ የተሰራ አንድ ጥናት፣ ኢትዮጵያውያን ባሎች ሚስቶቻቸውን አዘውትረው በመደብድብ 3ኛ መሆናቸውን አረጋገጠ።
‘አፍሪካ ሄልዝ፣ ሂዩማን ኤንድ ሶሻል ዲቨሎፕመንት ሰርቪስ’ የተባለው አህጉራዊ ድርጅትና በሴቶች ጥቃት ዙሪያ የሚሰሩ ሌሎች ተቋማት በጋራ የሰሩት ጥናት እንደሚለው፣ ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ኢትዮጵያውያን ባሎች የትዳር አጋሮቻቸውን መደብደብ አግባብ ነው ብለው የሚያስቡና በተለያዩ ምክንያቶች ሚስቶቻቸውን የሚደበድቡ ናቸው፡፡
ጥናቱ ከተሰራባቸው የአፍሪካ አገራት የበለጠ ተደባዳቢ ባሎች ያሉባት አገር ናት ተብላ በቀዳሚነት የተቀመጠችው ኡጋንዳን ስትሆን፣ ሴራሊዮን ሁለተኛ፣ ኢትዮጵያ ደግሞ ሶስተኛ መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡
60 በመቶ ያህሉ ኡጋንዳውያን ባሎች በትዳር ውስጥ የሚከሰቱ ግጭቶችን ለመፍታት ሚስቶቻቸውን መደብደብ ሁነኛ መላ ነው ብለው እንደሚያስቡ የጠቆመው የጥናቱ ውጤት፣ ለድብደባ ምክንያት ከሚያደርጓቸው ነገሮች መካከልም፤ ‘እዚህ ሄድኩ ሳትይኝ ከቤት ወጥተሸ ሄድሽ’፣ ‘የምልሽን አትሰሚኝም’፣ ‘ከእከሌ ጋር ያለሽ ነገር ምንድን ነው?’፣ ‘ልጆቼን በወጉ አልተንከባከብሽም’ እና ሌሎች ከወሲብና ከቅናት ጋር ተያያዙ ጉዳዮች እንደሚገኙበት አመልክቷል፡፡
ጥናቱ በተሰራባቸው አገራት የሚገኙ አብዛኞቹ ባሎች የድብደባን አስፈላጊነት የሚያምኑበት ሲሆን፤ በአንዳንዶቹ አገራት የጥቃቱ ሰለባ የሆኑት ሚስቶችም ተመሳሳይ አመለካከት እንዳላቸው ተጠቁሟል፡፡ መሰል አመለካከት ከሚንጸባረቁባቸው አገራት መካከል ጥናቱ በቀዳሚነት ያስቀመጠው ማሊን ሲሆን፣ ከ15 እስከ 49 የዕድሜ ክልል ውስጥ ከሚገኙ የአገሪቱ ሴቶች 87 በመቶ ያህሉ፣ ባሎች ሰበብ አስባብ እየፈጠሩ ሚስቶቻቸውን መደብደባቸው ተገቢ ነው ብለው እንደሚያስቡ አረጋግጧል፡፡ የማሊን ሴቶች ተከትለው የጊኒና የኢትዮጵያ ሴቶችም ድብደባ ይገባል ብለው ያስባሉ ብሏል ጥናቱ፡፡
የኡጋንዳ መንግስት ቃል አቀባይ ኦፎኖ ኦፖንዶ ለ “ኒውስ ቪዥን” ጋዜጣ በሰነዘሩት አስተያየት፤ የጥናቱ ውጤት ትክክለኛ መሆኑን ገልጸው፣ በአብዛኞቹ የአገሪቱ የገጠር አካባቢዎች የቤት ውስጥ ጥቃት እንደሚፈጸምና ተገቢ ነው ተብሎ እንደሚታመን እማኝነታቸውን ሰጥተዋል፡፡
“አብዛኞቹ ባሎች የቤተሰቡ የገቢ ምንጭ በመሆናቸው በሚስቶቻቸው ላይ የፈለጋቸውን ጥቃት ቢሰነዝሩ ሃይ ባይ የለባቸውም፡፡ አንዳንዴ ደግሞ፣ ባሎች ሌላ ሚስት ወደቤታቸው ለማስገባት ሲሞክሩ ሚስቶች ነገሩን በመቃወም ከቤታቸው ለመውጣት ይሞክሩና በባሎቻቸው ድብደባና ግርፋት ይደርስባቸዋል፡፡” ብለዋል ቃል አቀባዩ፡፡

በአምስት ወራት ውስጥ ተጨማሪ 2 አውሮፕላኖች ያስገባል

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደተለያዩ አለማቀፍ መዳረሻዎች የሚያደርገውን በረራ የበለጠ አጠናክሮ ለመቀጠል የሚያስችለውን 8ኛውን ቦይንግ 787 ድሪምላይነር አውሮፕላን መረከቡን ገለጸ፡፡
የዘመናዊ ቴክኖሎጂ ውጤት የሆነውን ቦይንግ 787 ድሪምላይነር አውሮፕላን በመጠቀም ከጃፓን ቀጥሎ በአለማችን ሁለተኛው መሆኑን የገለጸው አየር መንገዱ፣ 8ኛውን ቦይንግ 787 ድሪምላይነር አውሮፕላን ባለፈው ሳምንት መረከቡንና እስከ መጪው ታህሳስ ወር መጨረሻም ሌሎች ሁለት ተጨማሪ አውሮፕላኖችን እንደሚያስገባ ከትናንት በስቲያ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡የመጀመሪያውን ቦይንግ 787 ድሪምላይነር አውሮፕላን በነሃሴ ወር 2012 ማስገባቱን ያስታወሱት የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ መድህን፣ አውሮፕላኑ ለተሳፋሪዎች ምቾት በመስጠትና በአጠቃላይ ይዞታው በዘርፉ አቻ የማይገኝለት መሆኑን ጠቁመው፣ አየር መንገዱ ለወደፊትም የደንበኞቹን ፍላጎት ለማሟላት የአዳዲስ  ቴክኖሎጂ ውጤቶች የሆኑ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በማስመጣት አገልግሎቱን የበለጠ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
ይህን ዘመናዊ አውሮፕላን በመጠቀምና አገልግሎት በመስጠት ከአፍሪካ ትልቁ አየር መንገድ መሆኑን የገለጸው የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ በዚህ አውሮፕላን ወደተለያዩ የአፍሪካና የአውሮፓ ሃገራት፣ ብራዚል፣ አሜሪካ፣ ካናዳና ቻይና በረራ እያደረገ እንደሚገኝ ጠቁሟል፡፡
አየር መንገዱ ቦይንግ 777፣ ቦይንግ 787ና ቦይንግ 737ን ጨምሮ 68 ያህል እጅግ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በመጠቀም፣ በአምስት አህጉሮች ወደሚገኙ 82 አለማቀፍ መዳረሻዎች በረራ እያደረገ የሚገኝ አለማቀፍ ዝናን ያተረፈ ተቋም መሆኑንም አስታውቋል፡፡  የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአሁኑ ሰዓት ቪዥን 2025 የተባለውንና ስምንት የንግድ ማዕከላት ያሉት የአፍሪካ መሪ የአቪየሽን ግሩፕ ለመሆን የሚያስችለውን የ15 አመታት ስትራቴጂክ ዕቅድ ቀርጾ በመተግበር ላይ እንደሚገኝና ባለፉት ሰባት አመታት በአማካይ 25 በመቶ አመታዊ ዕድገት ማስመዝገቡንም አክሎ ገልጿል፡፡

*የአካባቢውን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለመቅረፍ እስከ ግማሽ ቢሊዮን ብር ያስፈልጋል



በዋግ ኸመራ ዞንና አካባቢው ነዋሪዎች ዘንድ ተወዳጅ የሆነውን የሻዳይ በዓል፣ ከወትሮው በተለየ መልኩ በድምቀት ለማክበር እየተዘጋጀ መሆኑን የገለፀው የዋግ ልማት ማኅበር ዋልማ)፤የአካባቢውን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለመቅረፍ እስከ ግማሽ ቢሊዮን ብር እንደሚያስፈልግ አስታወቀ፡፡
የዋልማ ሊቀመንበር አቶ ምትኩ በየነ ከማኅበሩ ሥራ አስፈፃሚ አባላት ጋር በሰጡት መግለጫ፣ ሻዳይ፣ ከጥንት ጀምሮ በአካበቢው ሕዝብ ዘንድ በድምቀት የሚከበር ሃይማኖታዊና ባህላዊ በዓል ቢሆንም ተቀዛቅዞ እንደነበር ጠቅሰው፤ ከ7 ዓመት ወዲህ ግን ክልሉና የዞኑ አስተዳደር በዓሉ ሃይማኖታዊና ጥንታዊ ይዘቱን እንደጠበቀ ለትውልድ እንዲተላለፍና የቱሪስት መስህብ እንዲሆን ትኩረት ይሰጠው ዘንድ ባሳሰቡት  መሰረት፣ ህልውናው ታድሶ እየተከበረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በየዓመቱ ከነሐሴ 16 እስከ 18 የሚከበረው የሻዳይ በዓል፣ ማኅበሩ ከተቋቋመ ከ2002 ወዲህ ለሦስት ዓመት ከልማት ጋር ተቀናጅቶ እየተከበረ መሆኑን ጠቅሰው፣ ማኅበሩ ዘንድሮም ለየት ባለ መልኩ፣ “ኅብረት ለዋግ ልማት” በሚል መሪ ቃል፣ ከፍተኛ አገር አቀፍ ልማታዊ ኅብረት ለመፍጠር እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ዘንድሮ በርካታ እንግዶች ተሳታፊ ይሆናሉ ያሉት አቶ ምትኩ፤ በዓሉን የሚያከብሩት የዋግ ዞን ልጃገረዶች ብቻ ሳይሆኑ በዓሉን ‹አሸንዳ› በማለት ከሚያከብሩት አጎራባች አካባቢዎች- ትግራይ፣ ላሊበላና ቆቢ የተውጣጡ ልጃገረዶችም እንዲሳተፉ ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡
በአሉን ከልማት ጋር ለማስተሳሰር የተፈለገው አካባቢው በርካታ ዘርፈ ብዙ የልማት፣ የትምህርትና  የጤና ችግሮች ስላሉበት ነው ያሉት ሊቀመንበሩ፤ አገሪቷ እነዚህ ችግሮች እያሉባት የምዕተ አመቱን ግቦች ማሳካት ያዳግታታል ሲሉ ተናግረዋል፡፡
“አካባቢው በተራራ ስለተሸፈነ ለማልማት አስቸጋሪ ነው፣ እስካሁን በአገሪቷ የተከሰቱ የድርቅ አደጋዎችም አካባቢውን አልፈው ሲያጠቁ ቆይተዋል፣ በአካባቢው ተራራ የሚፈሰው ውሃ ህዳሴው ግድብ ውስጥ የሚገባ ስለሆነ ተራራው ደን ከለበሰ ከተራራው እየታጠበ የሚሄደው ደለል ግድቡን በመሙላት ዕድሜውን ያሳጥረዋል፣ በአስተዳደሩ ውስጥ ካሉ 232 ት/ቤቶች ውስጥ 217ቱ ደረጃ አንድና ሁለት ቢሆኑም ከ106 ት/ቤቶች 514 የመማሪያ ክፍሎች የዳስ ወይም የዛፍ ጥላ መማሪያ ናቸው፡፡ ከ125 ቀበሌዎች ውስጥ 23ቱ ምንም ዓይነት ቁሳቁስ የላቸውም፡፡ በዞኑ የዓይን ህክምና የሚስፈልጋቸው ዜጎች ቁጥር ከፍተኛ ቢሆንም  ህክምናውን  የሚሰጥ ተቋም ባለመኖሩ 6,342 ወገኖች አደጋ ላይ ናቸው” ሲሉ ችግሮቹን በዝርዝር ተናግረዋል፡፡
“ለልማታዊ ኅብረቱ በሚገኝ ገቢ በተመረጡ ቀበሌዎች መዋዕለ ሕፃናት በመክፈት፣የትምህርት መርጃ መሳሪያዎችንና የውስጥ ቁሳቁስ በማሟላት፣ የጤና ተቋማት በመገንባት እንዲሁም  የዓይን ህክምና ተቋም በመክፈት ዋና ዋና ችግሮች የተባሉትን ለመቅረፍ አስበናል” ያሉት ሊቀመንበሩ፤ሁሉም የበዓሉ ታዳሚ እንዲሆንና የልማት ዕቅዳቸውን እንዲደግፍ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡    

አስራ አራት አንጋፋና አማተር ሰዓሊያን የሚሳተፉበት “ጅማሬ” የተሰኘ የስዕል አውደርዕይ ዛሬ በ11 ሰዓት 30 ሽሮሜዳ ኪዳነምህረት ቤ/ክርስቲያን መንገድ ላይ ታቦት ማደሪያው ፊትለፊት በሚገኘው ሚራጅ ኮፊ ሮስተር ይከፈታል፡፡
የአውደርዕዩ አዘጋጅ አቶ ዮሐንስ አክሊሉ እንደገለፁት፤ አውደርዕዩ እስከ ሐምሌ 5 ቀን 2006 ዓ.ም ለ15 ቀናት ለተመልካች ክፍት ሆኖ የሚቆይ ሲሆን  በየሦስት ወሩ የሚዘጋጅ ፕሮግራም እንደሆነም ታውቋል፡፡

በደርግ ዘመን ጠ/ሚኒስትር የነበሩት ፍቅረሥላሴ ወግደረስ “እኛ እና አብዮቱ” በሚል ርዕስ በፃፉት መፅሃፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተ-መፃህፍትና ቤተ-መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ውይይት እንደሚካሄድ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ አስታወቀ።
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ፅሑፍ ባለሙያ የሆኑት አቶ ሰለሞን ተሰማ ለውይይቱ መነሻ ሃሳብ እንደሚያቀርቡ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጠቁሞ፤ የሥነ-ፅሁፍ ቤተሰቦች በውይይቱ ላይ እንዲገኙ ጋብዟል፡፡

በመርሲ ዲኮር ዲዛይንና ሞዴሊንግ ማሰልጠኛ ተቋም ለሁለተኛ ጊዜ የተዘጋጀ “Visual Art Meets Fashion” የተሰኘ የስዕልና ቅርፃ ቅርፅ አውደ ርዕይ ትላንት ከምሽቱ 11 ሰዓት ላይ ቦሌ መድኃኒዓለም አካባቢ በሚገኘው ካሌብ ሆቴል የተከፈተ ሲሆን መታሰቢያነቱ ለአርቲስት አለ ፈለገሰላም እና እጅግ ለተከበሩ ለዓለም ሎሬት ዶ/ር ሜድ ጥበቡ የማነብርሃን እንደሆነ ታውቋል፡፡ ትላንት በመክፈቻው ዕለት በዲዛይነር ምህረት ምትኩ የተሰናዳ የፋሽን ትርኢት የቀረበ ሲሆን የ57 ሰዓሊያንና የ6 ቀራፂያን ሥራዎች አውደርዕይ ተከፍቷል፡፡ አውደርዕዩ እስከፊታችን ሰኞ ምሽት ድረስ ለተመልካች ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ አዘጋጆቹ አስታውቀዋል፡፡ ማሰልጠኛ ተቋሙ ባለፈው ዓመት ለተከበሩ የዓለም ሎሬት ሜትር አርቲስት አፈወርቅ ተክሌ መታሰቢያነት ተመሳሳይ አውደርዕይ አዘጋጅቶ እንደነበር በላከው መግለጫ አስታውሷል፡፡

ታጋዮች የህዝብ ጫማ ናቸው፤ ታጋዮች የግል ጥቅምና ምቾታቸውን በሰፊው ህዝብ ጥቅምና ምቾት የቀየሩ የህዝብ መድህኖች ናቸው፤ ታጋዮች ለህዝባቸው ምቾትና ድሎት ሲሉ ከፍተኛ መስዋዕትነት የሚከፍሉ የህዝብ ቤዛዎች ናቸው፡፡…
እነዚህን የመሳሰሉ የአብዮታውያን የፕሮፓጋንዳ ርግረጋዎች የኢትዮጵያ አብዮት በግብታዊነት ፈነዳ ከተባለበት ከየካቲት 1966 ዓ.ም ጀምሮ አብዮታዊና ተራማጅ ነን ከሚሉ ሃይሎች ዘንድ ስንሰማው የኖርነውና ዛሬም እየሰማነው ያለነው ጉዳይ ስለሆነ ምንም አስደናቂ ነገር የለውም፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ግን ይህ የአብዮታውያኑ መሀላ፣ የታጋዮቹን ሰውነትና የሰውን ልጅ ባህርይ በወጉ ከግምት ውስጥ ያስገባ አይደለም፡፡ እናም ነገሩ አብዛኛውን ጊዜ የሚባለውን ያህል ትክክል ወይም እውነት ሆኖ አይገኝም፡፡ ይህን ለማረጋገጥ ደግሞ ማስረጃ ፍለጋ የአለም አብዮተኞችን የታሪክ መዝገብ ማገላበጥ ጨርሶ አያስፈልገንም፡፡ የሀገራችን አብዮተኞች ታሪክ ከበቂ በላይ ነው፡፡
የጊዜያዊ ወታደራዊ መንግስት መሪዎች በስልጣን ላይ በቆዩበት አስራ ሰባት አመታት ሰፊውን የኢትዮጵያ ህዝብ ከአስከፊ ድህነት ለማላቀቅ ሲሉ አንድም ቀን እንኳ ሳይደላቸውና ሳይስቁ ከፍተኛ መስዋዕትነት ይከፍሉ እንደነበር በተደጋጋሚ ይናገሩ ነበር፡፡ እነዚህ አብዮታውያን ወታደራዊ መሪዎች በተግባር ያደረጉት ግን ካለፈው እጅግ የከፋ ድህነትን ለሰፊው ህዝብ እኩል በማካፈል፣ ራሳቸውንና የራሳቸውን ወገን ከድህነት ማላቀቅ ነው፡፡
“አብዮታዊውን” ወታደራዊ መንግስት ለአስራ ሰባት አመታት በዘለቀ የትጥቅ ትግል የዛሬ 23 አመት አሸንፎ ስልጣን የተቆጣጠረው ኢህአዴግ፣ ተራራ ያንቀጠቀጡት ታጋዮቹ በግል ጥቅምና ምቾት የማይንበረከኩ፣ የህዝብ ጥቅም፣ ምቾትና ብልጽግና የመጀመሪያም የመጨረሻም የትግል ግባቸው እንደሆነና ለዚህም ግብ መሳካት የህይወት መስዋዕትነት እንደከፈሉ በተደጋጋሚ ሊያስረዳን ሞክሯል፡፡
ጥረቱ ያላቋረጠና ከባድ መሆኑ ሲታይ ደግሞ ኢህአዴግም እንደሌሎቹ አብዮታዊ ድርጅቶች ሁሉ የታጋዮቹን ሰውነት ጨርሶ የረሳ አስመስሎት ነበር፡፡ የማታ ማታ በተግባር የታየው ግን በቃል ከተወራው በእጅጉ የተለየ ነበር፡፡ የራሳቸውን ጥቅምና ብልጽግና ከምንም ሳይቆጥሩ ለህዝባቸው ጥቅም፣ ምቾትና ብልጽግና እውን መሆን የህይወት መስዋዕትነት ለመክፈል ለአፍታም እንኳ አያመነቱም ተብለው ብዙ እጅግ ብዙ የተነገረላቸው “አብዮታውያን” ታጋዮች “የከተማ ስኳር ፈታቸው፤ የድል ማግስት ህይወት ጽኑ የትግል መንፈስና ስሜታቸውን ሰልቦ ከማይወጣው የትግል አላማቸው አሳታቸው” ተብሎ በራሳቸው ድርጅት አንደበት ተነገረባቸው፡፡
ይህንን በይፋ የተናገረው ድርጅታቸው ኢህአዴግ፤ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡ በማግስቱ እንደ ከፍተኛ የድርጀቱና የሀገር መሪነታቸው ለሌሎች አርአያ መሆን ሲገባቸው፣ በከተማው ስኳር ተታለው ከህዝብ ጥቅምና ብልጽግና ይልቅ ለራሳቸው ጥቅም፣ ምቾትና ብልጽግና ሌት ተቀን ሲጥሩና ህገወጥ ድርጊቶችን ሲፈጽሙ አግኝቻቸዋለሁ ያላቸውን ከፍተኛ የኢህአዴግና የመንግስት ባለስልጣናት እንደ እጅ ስራቸው መጠን ህግ ያውጣቸው ብሎ ዘብጥያ አወረዳቸው፡፡
የአብዮታዊቷ ኩባ ታሪክም ከኢትዮጵያም ሆነ ከሌሎቹ አብዮተኛ ሀገራት የተለየ አይደለም፡፡ እንደ አውሮፓውያን ዘመን አቆጣጠር በ1959 ዓ.ም የባቲስታን መንግስት በትጥቅ ትግል አስወግደው ስልጣን ስለተቆጣጠሩት የኩባ አብዮታዊ ታጋዮች ያልተባለና፣ ያልተነገረ ገድል አለ ለማለት ያስቸግራል፡፡ በተለይ ደግሞ የኩባ አብዮት ግንባር ቀደም መሪና የኩባ ጭቁን ህዝብ አባት ስለሚባሉት ስለ ጓድ ፊደል ካስትሮ በቃል ያልተነገረ፣ በጽሑፍ ያልተፃፈ፣ በፊልምም ያልቀረበ… እራስን ለህዝብ ጥቅም አሳልፎ ስለመስጠት ገድል.. ለሞት መድሃኒት እንኳ ፈልጐ ማግኘት አይቻልም፡፡
ራሳቸውን ለሰፊው ጭቁን የኩባ ህዝብ ፍፁም አሳልፈው የሰጡና ከወታደር ካኪ ሌላ የረባ ልብስ እንኳ የላቸውም እየተባለ ነጋ ጠባ የሚወደሱት ጓድ ፊደል ካስትሮ ግን እንደሚወራላቸው አይነት ሰው ሳይሆኑ ይልቁንም ልክ እንደ አንድ ታላቅ ንጉስ እጅግ በተንደላቀቀ ሁኔታ በምቾት የኖሩ ሰው እንደሆኑ ከተለያዩ ወገኖች በሹክሹክታ ሲወራ ቢከርምም ማረጋገጥ ሳይቻል ቆይቶአል፡፡
ሁዋን ሮናልዶ ሳንቸዝ የተባለ የ65 አመት ጐልማሳ ኩባዊ ግን ይህንን የሚያረጋግጥ ማስረጃ በቅርቡ ይፋ አድርጓል፡፡ ከ1977 እስከ 1994 ዓ.ም የፕሬዚዳንት ካስትሮ የቅርብ አማካሪና ከታናሽ ወንድማቸው ከራውል ካስትሮ ቀጥሎ እጅግ ጥብቅ ሚስጥረኛቸው የነበረው ሁዋን ሮናልዶ ሳንቸዝ፣ በቅርቡ ባሳተመው መጽሐፍ፤ ፕሬዚዳንት ጓድ ፊደል ካስትሮ 20ትላልቅ የቅንጦት መኖሪያ ቤቶች፣ የግል ደሴትና የመዝናኛ ጀልባ አሏቸው፡፡
የኩባው አብዮተኛ ጀግና ጓድ ፊደል ካስትሮ፤ በተጠቀሰው አመት ውስጥ በከፍተኛ ሚስጥር ይካሄድ በነበረ የእፅ ዝውውር ንግድ ውስጥ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ሀቫና ከተማ አቅራቢያ ባቋቋሙት የወታደራዊ ማሰልጠኛ ካምፕ ውስጥም እንደ አይ አር ኤ የመሳሰሉ ታጣቂ የሽብር ቡድኖችን ያሰለጥኑ ነበር፡፡     

የታዋቂው ድምጻዊ ቦብ ዳይላን አንድ የዘፈን ግጥም፣ ሰሞኑን ሱዝቤይ በተባለው አለማቀፍ አጫራች ኩባንያ አማካይነት ለጨረታ ቀርቦ 2 ሚሊዮን ዶላር በመሸጥ ክብረወሰን ማስመዝገቡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ከቦብ ዳይላን ታዋቂ ስራዎች አንዱ የሆነው ‘ላይክ ኤ ሮሊንግ ስቶን’ የተባለው ዘፈን ግጥም፣ በራሱ በድምጻዊው የተጻፈ ሲሆን፣ በአራት ነጠላ ወረቀቶች ላይ በእርሳስ የተጻፈው የግጥሙ ኦሪጅናል ኮፒ ነው በጨረታው የተሸጠው፡፡
ቦብ ዳይላን የከፍተኛ መደብ አባላት በሚኖሩበት ማህበረሰብ ውስጥ የብቸኝነት ኑሮን በምትገፋ አንዲት ባይተዋር ሴት ዙሪያ የሚያጠነጥነውን ይህን የዘፈን ግጥም፣ የ24 ዓመት ወጣት ሳለ ነበር እ.ኤ.አ በ1965ዓ.ም የጻፈው፡፡
የአጫራቹ ኩባንያ ባልደረባ የሆኑት ሪቻርድ ኦስቲን እንዳሉት፣ የቦብ ዳይላን ሥራዎች በዘመናዊው ሙዚቃ ጉዞ ላይ የራሳቸውን አስተዋጽኦ ያበረከቱና አቅጣጫ የቀየሩ ናቸው፡፡
ግጥሙን ለአጫራቹ ኩባንያ ያቀረበው ግለሰብ ማንነት ባይገለጽም፣ የድምጻዊው የረጅም ጊዜ አድናቂ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ከዚህ በፊት ለጨረታ ቀርቦ በከፍተኛ ዋጋ በመሸጥ ክብረወሰኑን ይዞ የነበረው፣ እ.ኤ.አ በ1967 በታተመው ‘ሎንሊ ሃርትስ’ የተሰኘ አልበም ውስጥ የተካተተው የታዋቂው ድምጻዊ ጆን ሌነን ሙዚቃ፣ ‘ፎር ኤ ዴይ ኢን ዘ ላይፍ’ የተሰኘ ግጥም ነበር፡፡ ግጥሙ ከሶስት አመታት በፊት ለጨረታ ቀርቦ በ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዶላር መሸጡን ቢቢሲ አስታውሷል፡፡  

Saturday, 28 June 2014 11:49

የጸሐፍት ጥግ

(ስለ ሂስና ሃያስያን)
ሃያሲ ማለት መንገዱን የሚያውቅ ነገር ግን መኪና ማሽከርከር የማይችል ሰው ነው፡፡
ኬኔዝ ቲናን
(እንግሊዛዊ የትያትር ሃያሲ)
ፊልሞቼን የምሰራው ለህዝቡ እንጂ ለሃያስያን አይደለም፡፡
ሴሲል ቢ.ዲ.ሚሌ
(አሜሪካዊ የፊልም ፕሮዲዩሰርና ዳይሬክተር)
ነፍሳት የሚነክሱን ለመኖር ብለው እንጂ ሊጎዱን አስበው አይደለም፡፡ ሃያስያንም እንደዚያው ናቸው፤ ደማችንን እንጂ ስቃያችንን አይሹም፡፡
ፍሬድሪክ ዊልሄልም ኒቼ
(ጀርመናዊ ፈላስፋና ገጣሚ)
ሃያስያን ለሚሉት ነገር ትኩረት አትስጡ፡፡ ለሃያሲ ሃውልት ቆሞለት አያውቅም፡፡
ዣን ሲቤሊዩስ
(ፊንላንዳዊ የሙዚቃ ቀማሪ)
ሰዎች ሂስ እንድትሰጣቸው ይጠይቁሃል፤ የሚፈልጉት ግን ሙገሳ ብቻ ነው፡፡
ሶመርሴት ሟም
(እንግሊዛዊ ደራሲ)
ሃያሲ ህግ ሳይሆን አስተላላፊ፣ ድልድይ መሆን አለበት፡፡
ቶኒ ሞሪሶን
(አሜሪካዊ ደራሲ)
ጌታዬ፤ ዝንብ ትልቁን ፈረስ ልትነክሰውና ዓይኑን ልታርገበግበው ትችላለች፡፡ ይሄ ግን አንደኛቸው ነፍሳት፣ ሌላኛቸው ፈረስ መሆናቸውን አይለውጠውም፡፡
ሳሙኤል ጆንሰን
(ስለሃያስያን የተናገረው)
ሃያስያን እነማን እንደሆኑ ታውቃላችሁ? በሥነጽሑፍና በሥነጥበብ ዘርፍ ያልተሳካላቸው ሰዎች ናቸው፡፡
ቤንጃሚን ዲስራሊ
(የእንግሊዝ ጠ/ሚኒስትርና ፀሐፊ የነበሩ)
ሃያስያን የሚሉትን ብሰማቸው ኖሮ፣ በስካር ናውዤ የውሃ አሸንዳ ስር እሞት ነበር፡፡
አንቶን ቼኾቭ
(ሩሲያዊ ደራሲ)
ሽልማት የሚያሸንፉ ትያትሮች የሚፃፉት ለሃያስያን ብቻ ነው፡፡
ሊው ግሬድ
(ዩክሬን ተወላጅ እንግሊዛዊ
የፊልምና ቴሌቪዥን ፕሮዲዩሰር)