Administrator

Administrator

Saturday, 09 February 2013 12:41

“LIFE’S LIKE THAT” ለገበያ ቀረበ

የሥነፅሁፍ መምህር የሆኑት አቶ ገረመው ገብሬ ያዘጋጁአቸው አጫጭር የእንግሊዝኛ ልቦለዶች የተካተቱበት የምናብ ታሪኮች መድበል ሰሞኑን ለገበያ ቀረበ፡፡ LIFE’S LIKE THAT AND OTHER STORIES በሚል ርእስ ለንባብ የበቃው ባለ 44 ገፆች መፅሃፍ ለሀገር ውስጥ ገበያ በ25 ብር፣ ለውጭ ሀገራት 1.33 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡
16 ታሪኮች የተካተቱበትን መፅሐፍ ሔሪቴጅ ፕሪንቲንግ ኤንድ ትሬዲንግ ኃ.የተ.የግ.ማህበር ነው ያሳተመው፡፡ አቶ ገረመው ካሁን ቀደም የንግግር እንግሊዝኛ (Spoken English) መፅሃፍ አሳትመዋል፡፡

የግጥም በጃዝ የግጥም እና የሙዚቃ ዝግጅት የፊታችን ረቡዕ ከቀኑ 11፡30 እንደሚቀርብ አዘጋጆቹ ገለፁ፡፡ በራስ ሆቴል ትልቁ አዳራሽ የሚቀርበው 19ኛ ወርሀዊ ዝግጅት የመግቢያ  ዋጋ በሰው 50 ብር ነው፡፡አርቲስት ሜሮን ጌትነት መድረኩን በምትመራበት ዝግጅት ላይ አቶ አብዱ አሊጅራ ዲስኩር የሚያቀርቡ ሲሆን አርቲስት ጌትነት እንየው፣አበባው መላኩ፣ ዮሐንስ ገብረመድህን እና አለማየሁ ታደሰ የ”አንቲገን” ትያትርን ቅንጭብ በጃዝ ሙዚቃ ታጅበው እንደሚጫወቱ ተገልጿል፡፡

የኢራን እስላማዊ አብዮት የተካሄደበትን 34ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የኢራን ኤምባሲ‹‹የፍቅር ተዓምር›› የተሰኘ የግጥም ምሽት ትላንት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የባህል ማዕከል አቀረበ፡፡ የአምስት ታላላቅ ኢራናዊያን ገጣሚዎች ስራ በኢትዮጵያውያን ገጣሚዎች ወደ አማርኛ ተተርጉሞ የቀረበበት የግጥም ምሽት፣መታሰቢያነቱ የኢራናውያን መንፈሳዊ መሪ ለነበሩት አያቶላ ኢማም ሆሚኒ እንደነበር ታውቋል፡፡
የኢራናዊያን መንፈሳዊ መሪ አያቶላ ኢማም ሆሚኒን ግጥም ጨምሮ የኦማር ኻያም፣ የሩሚ፣ የሳዒድና የባባጥህር ግጥሞች በአማርኛ ተተርጉመው የቀረቡ ሲሆን የዛሬ 34 ዓመት በኢራን የተካሄደው እስላማዊ አብዮት በየዓመቱ በኪነጥበባዊ ዝግጅት እንደሚዘከር ታውቋል፡፡

“ውቢት እንቅልፋሟ” የሚል የልጆች ትያትር ዛሬ ከጧቱ 3 ሰዓት በኤድናሞል ሲኒማ እንደሚያስመርቅ ናታን መልቲ ሚዲያ ፕሮዳክሽን አስታወቀ፡፡ ትያትሩን ፅፎ ያዘጋጀው አብነት ጌታቸው ሲሆን በትያትሩ ምረቃ ላይ አዱኛ የዳንስ ቡድን ስራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡ ታውቋል፡፡በየትምህርት ቤቱ በመዞር የሚታየው ይኼው ትያትር፣ ከአንደኛ እስከ አራተኛ ክፍል የሚማሩ ሕፃናትን በማለም የተሰራ ነው፡፡ ትያትሩ በናታን መልቲ ሚዲያ “የተራኪ ዳንሰኛና ድራማ ክለብ” መዘጋጀቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

Saturday, 09 February 2013 12:23

የዘፈን እንቆቅልሽ

መሄድ መሄድ አይሰለቸኝ
መፈለጉ አይታክተኝ
አንዱን ጥዬ አንዱን ላንሳ
ትላንትናን ባሁን ልርሳ ከስተቴ
እማራለሁ
ከመኖሬ ብዙ አውቃለሁ
ልሩጥ ሳያልቅ ቀኔ ባክኖ
እንዳይሆን ሆኖ
ኦኦኦ በመንገዴ
ኦኦኦ በመሄዴ
ኦኦኦ እደርሳለሁ ከእቅዴ
ይሄን የዘፈን ግጥም ያቀነቀነው ማነው? የዘፈኑ ርእስ ምን የሚል ነው?
አልበሙን ያወጣው ባንድ ማን ይባላል?
መልሱን በገፅ 27 ይመልከቱ

ወደ ዋናው ጥያቄ ከመግባቴ በፊት ስለ ልብሽ ልጠይቅሽ እፈልጋለሁ፡፡ ልብሽ እንዴት ነው?
(ረጅም ሣቅ)…ልቤ ድም ድም እያለ ነው፤ በአግባቡ ይመታል፡፡
በቅርቡ ያወጣሽው አልበም “ልቤን” ስለሚል ልቧን ምን አገኘው ብዬ ነው?
“ልቤን” የዘፈንኩት ዜማና ግጥም ተሰጥቶኝ ነው፡፡ የኔ ልብ ድጋሚ ሊወሰድ አይችልም፤ ምክንያቱም አንዴ የወሰደ ወስዶታል፡፡ ሌሎቹን ልባቸው የተወሰደባቸውን ይወክላል ማለት ነው፡፡
አንቺ በጣም የታወቅሽበት ዘፈን የመጀመሪያው “ፏፏ ይላል ዶጁ” ዘፈንሽ ይመስለኛል፡፡ እውነት ነው እሱ ነው? በዛን ጊዜ ስለ ዶጁ መኪና፣ ስለ አረንቻታ መጠጥና ስለ ቸርችል ጐዳና በግጥሞችሽ ውስጥ ዘፍነሻል፡፡ ዶጁ መኪናን ደርሰሽበታል? አረንቻታ መጠጥ ምን አይነት ነበር? ቸርችል ጐዳና አንቺ ከምታውቂው ምን ያህል ተለውጧል? ምክንያቱም ያኔ ታዋቂ ጐዳና ነበርና?
ዶጅ እንግዲህ የመኪና ብራንድ ነው፡፡ አሁንም አለ፤ በጣም ፋንሲ (ቄንጠኛ) የሆነ መኪና ነው፡፡ ያኔ በእናቶቻችን ጊዜ የነበረ ስለሆነ ያኔ የማውቀው ነገር የለም፣ ዘፈኑ ሲሰጠኝ ዘፈንኩት፣ መኪናውን አላየሁትም አላገኘሁትም፡፡ ክሊፑን ስሰራ ግን ካፕቴይን አለማየሁ ይሁኑ ካፕቴይን ከበደ ስማቸውን በትክክል አላስታውስም፤ የሳቸው መኪና ነበር ይህ መኪና ዶጅ ነው ግን የመጀመሪያው ሳይሆን ተሻሽሎ የመጣ ቆንጆ መኪና ነበር፤ እሱን አይቻለሁ፣ የድሮውን አልደረስኩበትም፡፡
አረንቻታን አላውቀውም፤ በኛ ጊዜ የነበረውና አረንቻታ ተብሎ የሚሸጠው በቢራ ጠርሙስ አይነት ሆኖ እንደ አረንቻታ ይሸጣል እንጂ ራሱ አረንቻታ አይደለም ያው እሱንም አላውቀውም፤ ግን ይሄኛውም አረንቻታም ለስላሳ መጠጥ ነው፡፡ ቸርችል ጐዳና ያኔ ከነበረው ብዙ አልተለወጠም፡፡ ድሮ የነበረው አሁንም እንዳለ ነው፡፡ ይህን ጐዳና ብዙ ለውጥ አላይበትም፡፡ እኔም በዘፈኑ ብቻ ሳይሆን ካቴድራል ስማር የማውቀው ይሄንኑ ቸርችልን ነው እና ብዙ ልዩነት የለውም፡፡
“የታል ልጁ የታል” የሚለው ክሊፕሽ ላይ ሰውነትሽ ደንደን ያለ ነበር፡፡ በስተመጨረሻ “ባይ ባይ”ን ስትሰሪ በጣም ሸንቃጣ ሆንሽ፡፡ ይሄ ደግሞ የአንድ ሰሞን መነጋገሪያ ነበር፡፡ እንደውም አንድ ሰሞን ባይ ባይ ያለችው ሰውነቷን ነው እንዴ ሲባል ነበር፡፡
ትንሽ ደጋግሜዋለሁ፡፡ ይህንንም ቢሆንም ልንገርሽ ባይ ባይ ያለችው ሰውነቷን ነወይ የሚለው ሊሆን ይችላል፤ ያስኬዳልም፡፡ ሰውነቴን ልቀንስ የፈለግሁት በህመም የተነሳ ነው፡፡ ሰውነቴ ከባድ ስለነበረ ለቁመቴ አይመጥንም፤ “ፕሮፖርሽናል” አልሆነም፣ እግሬ ሰውነቴን መሸከም ስለማይችል ዶክተሮች ያለሽ አማራጭ መክሳት እንጂ ሌላ የምንሰጥሽ አማራጭ የለም ስላሉኝ በዛ ምክንያት ነው የከሣሁት፡፡
ከአኗኗር ዘይቤ መቀየር ጋር በተያያዘ በአገራችንም ብዙ ሰዎች ከልክ በላይ እየወፈሩ ነው፤ በተለይ ሴቶች በአሁን ሰዓት ውፍረት እየፈሩ ነው፡፡ መቀነስ ይፈልጉና መቀነስ ምኞት ይሆንባቸዋል፡፡ እንዴት መቀነስ እንዳለባቸው ምክር ልትለግሻቸው ትችያለሽ?
ዋናው የህክምና ባለሞያን ማማከር ነው፡፡ ዝም ብሎ መክሳትም የራሱ ችግር አለው፡፡ ምክንያቱም ሰውነት ከካሣ በኋላ በሚፈለገው መጠን በምግብ ካልተደገፈ ጥሩ አይሆንም፡፡ ስለዚህ የስነ - ምግብ ባለሙያዎችን በማማከርና በእነርሱ በመታገዝ ነው መሆን ያለበት፤ ከዚያ በኋላ ይህን ተግባራዊ ማድረግ ያንቺ ድርሻ ነው፡፡ በቀጣይ መሆን ያለበት ሌላው ዋና ነገር ለዚህ ነገር አዕምሮን ማዘጋጀት ይጠይቃል፡፡ መክሳት አለብኝ ስትይ አዕምሮሽ ዝግጁ ካልሆነና ጀምሮ ለመተው ከሆነ ይሄ አካሄድ የትም አያደርስም፡፡ እንደውም ከሁሉም የሚቀድመው ሰውነቴን እቀንሳለሁ ብለሽ ለአዕምሮሽ መንገርና መዘጋጀት፣ ከዚያም ሌሎቹን ሂደቶች መከተል ነው፤ ዋናው ከዛ በኋላ እስከ መጨረሻው ክትትሉ መሄድ አለበት፡፡ አሁን ከስቻለሁ ብለሽ ብታቆሚ ተመልሶ ይመጣል፡፡ የምንበላውንና የምንጠጣውን ነገር በአግባቡ ለሰውነት በሚስማማ ሁኔታና መጠን ማድረግ አለብሽ፡፡
ወደ አዲሱ ሥራሽ ከመምጣቴ በፊት አንድ ነገር ልጨምር፡፡ ቀደም ሲል መንፈሳዊ መዝሙር ሠርተሽ ነበር፡፡
በዚህ ወቅት በቃ ነፃነት ወደ ዘፈን አትመለስም የሚል አስተያየት ሲሰጥ ነበር፡፡ አንቺ አሁን “ልቤን” ብለሽ ወደዘፈን መጥተሻል፡፡ ከመዝሙር ወደ ዘፈን መምጣት ምን አይነት ስሜት አለው?
መዝሙርና ዘፈን ለእኔ አይለያዩም፤ አንድ ናቸው ዋናው ልዩነታቸው የምንጠቀምባቸው ቃላት ናቸው እግዚአብሔር ለእኛ ድምፃችንን መክሊት አድርጐ እስከሰጠን ድረስ እግዚአብሔርን ልናመሰግንበት ይገባል የሚል እምነት አለኝ፡፡ እግዚአብሔር ፍቅር ነው፤ አታፍቅሪ አትባይም አግብተሽ በአንድ ተወስነሽ ኑሪ ነው ትዕዛዙ፡፡
ስለዚህ የምትሰሪያቸው ነገሮች ትምህርታዊ እስከሆኑ ድረስ ከሃይማኖት ጋር የሚያጋጭ ነገር የለም፡፡ እኔም ብሆን እድገቴ በቤተ - ክርስቲያን እንደመሆኑ መጠንና ቤተ - ክርስቲያንን መርዳት ስላለብኝ የማገለግለው እግዚአብሔር በሰጠኝ ድምጽ በመሆኑ በተሰጠኝ ፀጋ እግዚአብሔርን እና ቤተ - ክርስቲያንን አገለግላለሁ፡፡ በዚህ መሠረት ሁለቱም ለእኔ ልዩነት የላቸውም፡፡
ባለፈው ገና በኢቴቪ አንቺና ኩኩ ሰብስቤ ስለወርቃማ የጓደኝነት ጊዜያችሁ እያነሳችሁ ተመልካቹን ስታዝናኑ ነበር፡፡ ስለ ጓደኝነታችሁ እስቲ ንገሪኝ…ይህን የምልሽ የአሁን ዘመን ጓደኝነት የአንድ ሰሞን ብቻ ነው ስለሚባል ነው፡፡
በእኔ እምነት ጓደኝነት እንደአያያዝሽ ነው፡፡ እኔ የምፈልጋቸው እሷም የማትፈልጋቸው ነገሮች ካሉ እነዛን አቻችለን መኖር ነው፡፡ በአጠቃላይ ተቻችለሽ መኖር ከቻልሽ ብዙ የጓደኝነት ዕድሜ ታስቆጥሪያለሽ፡፡ አሁን እኔ ከኩኩ በተጨማሪ ብዙ ጓደኞች አሉኝ፤ እሷም ብዙ ጓደኞች አሏት፡፡ እነዚህን ጓደኞችሽን ጓደኝነታቸውን ጠብቀሽ ለመቆየት መቻቻል እና አንዳንድ ነገሮች ሲኖሩ በግልጽ መነጋገር ያስፈልጋል፡፡ እነዚህ ነገሮች ሲኖሩ ጓደኝነት ይጠነክራል እድሜውም ይረዝማል፡፡ የእኔና የኩኩም ጓደኝነት በዚህ መርህ የተቃኘ እንጂ ሌላ ምስጢር የለውም፡፡
በዛው ፕሮግራም ላይ አንዳችሁ የአንዳችሁን ዘፈን ስታንጐራጉሩ ነበር፡፡ ከኩኩ ዘፈኖች የትኞቹን ታደንቂያለሽ?
እንዳልሽው በፕሮግራሙ ላይ የሷን ዘፍኛለሁ፤ ዘፈን ስጀምርም ድምፄን የገራሁት በእሷ ዘፈን ነው፡፡ ዘፈኖቿን ሁሉ እወዳቸዋለሁ፡፡
“ልቤን” በተሰኘው አልበምሽ ላይ አብይ አርካ የተባለ ወጣት አቀናባሪ ነው የመረጥሽው፡፡ በፊት በፊት ለሙዚቃ ቅንብር አንጋፋዎቹ ይመረጡ ነበር፡፡ አሁን ወጣቶቹ ትኩረት እየሳቡ ነው፡፡ አንጋፋዎቹ ጋር ወረፋ ከመጠበቅና ሥራን ከማጓተት ተብሎ ነው ወይስ ወጣቶቹን ለማበረታታት?
የኔ ምላሽ ሁለቱንም ያነሳሻቸውን ሃሳቦች የሚያስታምም ነው፡፡ ምን ማለቴ ነው በአብዛኛው ትልልቆቹ አቀናባሪዎች ብዙ ሥራ ስላላቸው የሚሰጡሽ ጊዜ በጣም ትንሽ ነው፡፡ እንደምታውቂው አሁን ያለነው ዘፋኞቹ ደግሞ እንደበፊቱ ውስን አይደለንም፤ በጣም በዝተናል፡፡ እነዛን ሁሉ አንጋፋዎቹ ማስተናገድ አይችሉም፡፡ ከታችም ያሉትን ማሳደግ አስፈላጊ ነው፡፡ በስራ እስከተግባባችሁ ጥሩ እስከመጣልሽ ድረስ እና ደስ የሚል ቅንብር ከሠራ ምንም ችግር የለውም፡፡ ወጣቱን የሚደግፍ ቤዝ ተጫዋች ትንሽ አንጋፋ የሆነ አብረሽ ታሠሪያለሽ፡፡ ይሄ ከሆነ ከወጣቶቹ ጋር የማንሰራበት ምንም ምክንያት የለም፡፡ ስራም ከሚጓተት ወጣቶችም መስራት ስለለባቸው በዚህ መልኩ ነው አብይን የመረጥኩት፡፡
በካሴት ሽፋንሽ ላይ ላቅ ያለ ምስጋና ካቀረብሽላቸው ውስጥ አቀናባሪሽ አብይ አንዱ ነው “እደግ ተመንደግ” ብለሽዋል፡፡ በስራው ያን ያህል አስደስቶሻል ማለት ነው?
አዎ ደስተኛ ነኝ፡፡ ይሄ ልጅ በጣም ልጅ ነው፣ በዛ ላይ እኛ አርቲስቶች ስንሰራ ብዙ አይነት ፀባይ አለን፡፡ ሙዚቃ ሲሰራ በርካታ ውጣ ውረዶች አሉት፡፡ ያንን ሁሉ በትዕግስት ችሎ ሲሰራ ቆይቷል፡፡ ሌላ ጊዜም እንዲህ አይነት ነገሮች ሊፈጠሩ እንደሚችሉ አስቦና ታግሶ ሲሰራ ደስ ይልሻል፡፡ ስለዚህ ማመስገንና እውቅና መስጠት አለብሽ፡፡ በዚህን ጊዜ ለሌላ ጥሩ ስራ ራሳቸውን ያዘጋጃሉ፡፡ ለዚህ ነው ወጣቱን ያመሰገንኩት፡፡
ለዚህኛው ጥያቄዬ “ልጅ ከልጅ አይበልጥም” የሚል የተለመደ መልስ አልጠብቅም፡፡
(ሣ…ቅ…)
ጥያቄውን ልስማው?
አንዳንድ አስተያየቶችን ስሰማ “ልቤን”፣ “አትደውልልኝ”፣ “ከረሜላዬ” እና “እሩቅ” በጣም እየተደመጡ ነው፡፡ አንቺ ከዚህ አልበም በጣም የወደድሽው የትኛውን ዘፈን ነው?
(ረጅም ሣቅ) ይሄንን ነገር አንቺ ካልፈለግሽው ምንም ማድረግ አልችልም፡፡ አባባሉ ግን አሁንም ትክክል ነው ልደግምልሽ እችላለሁ፡፡ ምክንያቱም አንድን ስራ ስትሰሪ ጠልተሽው የምትሠሪው ሥራ የለም፡፡ ሁሉንም መርጠሽና ወደሽ ነው የምትሠሪው፡፡ ልታበላልጭ አትችይም፡፡ አድማጭ አንዱን ዘፈን አሁን ካለበት፣ ካለፈውና በቀጣይ ካሰበው ነገር ጋር አገናኝቶ ሊወደው ይችላል፡፡ እኔ ግን እንደዘፋኝ ዘፈኖቼን አላበላልጥም፡፡ አንዱ ልነግረሽ የምፈልገው “ይላል ዶጁ”ን ብትይኝ የታወቅኩበት ዘፈን በመሆኑ በጣም እወደዋለሁ፡፡ በተረፈ ሌሎቹን ፈልጌ የሠራኋቸው በመሆናቸው ሁሉንም እወዳቸዋለሁ፡፡
በአዲሱ አልበምሽ ውስጥ “አትጠይቀኝ፣ አትደውልልኝ” የሚል ዘፈን አለ፡፡ ይሄ ዘፈን መቻቻልን አያበረታታም የሚሉ አሉ፡፡ አንቺ እንዴት አየሽው?
“አትደውልልኝ” አሉታዊ መንፈስ የለውም አትጠይቀኝ አትደውልልኝ የሚለው ሃሳቡ “አንተን ካየሁ ያገረሽብኛል” ነው፡፡ ግን ስታየው ድምፁን ስትሰማ ወደቀድሞው ስለምትመለስ፣ ካለህበት ልውደድህ፤ እኔም ኑሮዬን ልኑር፤ አትደውልልኝ አታስታውሰኝ ትላለች፡፡ ሳልፈልግ ስለሄድክብኝ አሁን ሳልፈልግ አትምጣ ነው፡፡
ወባና ፍቅር ካገረሸ ይገድላል ይባላል፡፡ እንዳትሞት ፈርታ ይሆን?
(ሣ…ቅ…) ይመስለኛል፡፡ እንደዛ አይነት ፍራቻ ሳይኖራት አይቀርም፤ ጥላቻው ግን የላትም፡፡ ነገር ግን ተመልሳ ከገባችበት የባሰ እንዳትጐዳ ብላ ነው፡፡
“ከረሜላዬ”ን ለማን ነው የዘፈንሽው? ሌላው ከረሜላዬ ትንሽ ወዝወዝ የሚያደርግና ዳንስ የሚፈልግ ነው፡፡ ለክሊፑ ዳንስ ተለማመድሽ ወይስ ቀድሞም ትችያለሽ? ወጣቶችም በፊቸሪንግ አጅበውሻል፡፡ እነማን ናቸው?
ለነገሩ ፊቸሪንግ ቶኪቻው (ዮሐንስ በቀለ) ነው የሠራው፡፡ ክሊፑ ሲሰራ ከእኔ ይልቅ የቶኪቻውን ዳንስ የበለጠ የምትመለከቱ ይመስኛል፡፡ እኔ ልሞክር እፈልጋለሁ ግን እስካሁን አልቻልኩበትም፡፡ ዘፈኑን የዘፈንኩት ለባለቤቴ ለሱራፌል በዛብህ ነው፡፡ ሌላውም እንግዲህ ከረሜላዬ ለሚለው ሊጋብዘውና ሊዘፍነው ይችላል፡፡
ባለቤትሽ አቶ ሱራፌል በአልበምሽ ላይ በግጥምና ዜማ ተሳትፏል፡፡ የሙዚቃ ባለሙያ ነው እንዴ? በስራሽስ ምን ያህል ያግዝሻል?
ባለቤቴ ከሙዚቃ ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፤ የራሱን ቢዝነስ የሚመራ ነው፡፡ ነገር ግን ለእኔ ስራ በተለይ ለዚህ አልበም በጣም ነው የደከመው፡፡ ለዚህ ሥራ ባለቤቴ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው፡፡ ከእኔ በላይ ማለት ነው፡፡ ገብቶ መዝፈን ነው የቀረው እንጂ እስከመጨረሻው ሲታገል ነበር፡፡ ዜማ ሲያስመጣ፤ ወዲህ ሲል ወዲያ ሲታገል ብዙ ረድቶኛል፡፡ በጣም ላመሰግነው እወዳለሁ፡፡ ምክንያቱም ሥራዬ እዚህ ደረጃ የደረሰው በእርሱ ብርታት ነው፡፡
ከዚህ በፊት “ፍርቱና” በተሰኘው ዜማሽ ላይ ናቲ አያሌው (ናቲማን) በፊቸሪንግ አብሮሽ ተሳትፏል፡፡ አሁን ደግሞ በ”ከረሜላዬ” ቶኪቻው ሰርቷል፡፡
የቀድሞ ዘፋኞች ከወጣት ድምፃዊያን ጋር ሲሰሩ ብዙ አይታዩም፡፡ የቀደመውን ዘፈን ከዘመኑ ጋር አቀላቅሎ መስራት አልተለመደም፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ያንቺ አስተያየት ምንድነው?
እንደሚታወቀው እኔ ከድሮ ጀምሮ ስሰራ የነበርኩት ዘመናዊ ሙዚቃዎችን ላይ ነው፡፡ እናም ድሮ ሙዚቃ በደንብ በማይታወቅበት ጊዜ የሙዚቃ አቅርቦቱ ውስን ነው፡፡ አሁን ግን ሙዚቃው በጣም ሰፊ ሆኗል፡፡ በእኛ ጊዜ ስትዘፍኚ አድማጭ ድምጽን የማድነቅና የግጥሙ መልዕክት ላይ የበለጠ የማተኮር ነገር ነበረው፡፡ አሁን ያሉት ዘመናዊ ዘፈኖች እያደጉ በመምጣታቸው፣ የእኛም አገር አድማጭ በደንብ ሞቅ ያሉና ፈጠን ያለ እንቅስቃሴ ያላቸውን የውጭ ዘፋኖች መከታተልና የዘፋኞቹ የህይወት ታሪክ ሳይቀር፤ ምን እንደበሉና እንደጠጡ የሚያውቅበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ ብዙ ወጣት የሚያዳምጠው ዘመናዊ ዘፈን በመሆኑ ራሴን ከዘመኑ ጋር በማስማማት ወጣቱም፣ በመካከለኛ ዕድሜ ላይ ያሉትም ሆነ የድሮዎቹን ባማከለ መልኩ ለመስራት ሞክሬያለሁ፡፡ ይሄ የበለጠ ጠቃሚ ነው፤ ሁሉንም ታሳቢ ማድረግ፡፡
አሁን ከካናዳ ጠቅልለሽ አንደኛሽን ነው የመጣሽው ወይስ ለአልበም ሥራሽ ብቻ ነው?
ጠቅልዬ አልመጣሁም ግን ለመምጣት በሂደት ላይ ነኝ፡፡ ጠቅልሎ ለመምጣት ዝግጅት ያስፈልጋል፡፡ በቀላሉ መጥተሽ ለመኖር አስቸጋሪ ነው፡፡ ብዙ ሊታሰብባቸው የሚገቡ ነገሮች አሉ፡፡ አስፈላጊ ነገሮችን በማመቻቸት ላይ ነኝ፡፡ ምን ልስራ፣ ልጄን የት ላስተምር የሚሉ ነገሮች ከወዲሁ እያስተካከልኩ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር በሚቀጥለው ዓመት የሚሣካ ይመስለኛል፡፡
አንድ ልጅ ብቻ ነው ያለሽ፡፡ ሌላ ልጅ መድገም አልፈለግሽም ነበር?
ልክ ነው አንድ የ10 ዓመት ልጅ ነው ያለኝ - ኢዮስያስ ሱራፎል ይባላል፡፡ እንደምታውቂው የእኛ ሥራ ትንሽ አስቸጋሪ ነው፤ እንደፈለግሽ ልጅሽን ጥለሽ የምትንቀሳቀሽበት አይደለም፡፡ አገሩ ሠራተኛ እንደልብሽ የምታገኝበት አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ እና የዛ አገር ኑሮ በፍፁም አንድ አይደለም፡፡ እና ልጅሽን አሳልፈሽ ለሌላ ሰው ጐረቤት ጠብቁልኝ ምናምን የሚባል ነገር የለም፡፡ የግድ ራስሽ መንከባከብና መጠበቅ አለብሽ፡፡ ስለዚህ አንዱን በደንብ ጠብቆና ተንከባክቦ ማሳደግ ይሻላል ከሚል ነው፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔር ይባርከው፤ እሱኑ ሺህ ያድርገው እላለሁ፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አዲካ ኤቨንትስና ኮሙኒዩኬሽን የሙዚቃ ኢንዱስትሪውን እያነቃቃ ነው ይባላል፡፡ አንቺም አብረሽው እየሰራሽ ነው፡፡ እንዴት ነው ከአዲካ ጋር ያለሽ ስምምነት?
ያው ስምምነታችን የገዢና የሻጭ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ አዲካ የኛ ስራ በቀዘቀዘበትና በሞተበት ሰዓት ተነሳሽነትን ወስዶ ለሙዚቃው ትንሣኤ በመሆኑ ሊወደስ ይገባዋል፡፡ ሙዚቀኞች በተስፋ መቁረጥ ውስጥም ሆነው ሙዚቃ ሠርተው ሲጠብቁ እየገዛና እያበረታታ ያለ ትልቅ ድርጅት ነው፡፡
የእኛ ስራ ደክመሽ የትም የመጣል ያህል ነው፡፡
የኮፒ መብት ጉዳይ ያልተረጋገጠበት አገር ውስጥ ነው ያለነው፡፡ ስለዚህ አዲካዎች መጥተው ይህን ነገር እንዋጋለን ብለው በድፍረት በመጋፈጣቸውና ለአርቲስቶች ብርታት በመሆናቸው ሊመሰገኑ ይገባል፡፡ ትልቅ ኃላፊነት ነው የወሰዱት፡፡
አዲካዎች አልበም ከገዙ በኋላ ከዘፋኙ ጋር ትልልቅ ኮንሰርቶችን የመስራት ልምድ አላቸው፡፡ ከአንቺ ጋር ኮንሰርት እንደሚኖራቸው እንጠብቅ?
አዎ ትልቅ ኮንሰርት እንደሚኖረን ተነጋግረናል፡፡ ያው የናፈቅሁትን የኢትዮጵያ ህዝብ በዛ ኮንሰርት ፊትለፊት አገኘዋለሁ የሚል ተስፋ አለኝ፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር በቀጣይ የምናየው ይሆናል፡፡
ያው እንግዲህ ኮንሰርቱ ላይ ዳንስ አልችልም ብሎ ነገር የለም መዘጋጀት አለብሸ…
(ሣ…ቅ) አዎ ግን ብዙ ጊዜ መድረክ ላይ ዳንስ ከዘፋኝ ብቻ የሚጠበቅ አይደለም፤ መድረክ ላይ የሚያጅቡኝ ዳንሰኞች ይኖራሉ፡፡ የዳንሱ ጉዳይ ብዙ የሚያሳስብ አይደለም፡፡ ለእኔም ጥሩ ነው፤ ለእነሱም የስራ ዕድል መፍጠር ይፈጥራልና መልካም ነው፡፡ እኔም እንግዲህ አቅም በፈቀደ ነቅነቅ ለማለት እዘጋጃለሁ (ሣ…ቅ)
“ልቤን” ሠባተኛ አልበምሽ ነው ልበል?
ከሌሎች ጋር በኮሌክሽን ከሠራኋቸው ጋር ልቤን ስምንተኛ አልበሜ ነው፡፡ ለነገሩ በዛን ጊዜ በኮሌክሽን ሲሰራ አንድ ታዋቂ ዘፈንሽ ነው አልበም የምትይው እንጂ እንደአሁኑ ሙሉ ካሴት ለብቻሸ አይደለም፡፡ እና በዛ ነው ስምንተኛ የምልሽ፡፡
ካናዳ ብዙ ስለቆየሽ ስለ አዲስ አበባ ጥቂት ጥያቄዎችን ልጠይቅሽ?
እኔ እኮ እዚሁ ነኝ ማለት እችላለሁ፡፡ ለምን ብትይ… በየስድስት ወሩ፣ በየአመቱ እመጣለሁኝ፡፡
ጥሩ እንግዲያውስ ወደ ጥያቄው አሁን ያለነው አዲስ አድማስ ቢሮ ነው ከዚህ ተነስተን ሸጐሌ የሚባለው ሠፈር እንሂድ ታክሲ ከየት እንያዝ?
ጉድ ፈላ! ሸጐሌ የት ነበር? (በጣም ማሰብ ጀመረች) ሸጐሌ ስሙን አውቀዋለሁ እውነት ለመናገር የት ጋ ታክሲ እንደሚያዝ፣ አቅጣጫውም የት እንደሆነ አላውቅም፡፡ (ሣ…ቅ)
ከቶታል ፒያሳ - ከፒያሣ አስኮ መድሃኒያለም ሄደሽ፣ ከዚያ ነው ሸጐሌ መንደር ሰባት የሚባል ታክሲ የምትይዢው፡፡
በፊት ብዙ ከተማ ውስጥ አትዞሪም ነበር ማለት ነው?
አዎ የመዞር “ተሰጥኦ” የለኝም፡፡ ብዙ ጊዜ ቤቴ መሆን ነው የሚያስደስተኝ፡፡
እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ የኢትዮጵያን ጉዳይ፣ ሹምሽሩን አጠቃላይ እንቅስቃሴ በሚዲያ ትከታተያለሽ ብዬ አስባለሁ?
በሚገባ! እንደ ኢትዮጵያዊነቴ ሁሉንም እከታተላለሁ፡፡
ስለዚህ አዲሱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ልትነግሪኝ ትችያለሽ ማለት ነው?
ኦ…አቶ ሃይለማሪያም ናቸዋ!
እሣቸው የኢፌድሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ናቸው፡፡ እኔ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን ነው ያልኩት…
ኦ…ስማቸው ማን ነበር? ዶክተር…እንትን የነበረው አይደለ? የጤና ጥበቃው የነበሩት እንደሆነ አውቃለሁ ዶክተር…ስማቸው ዘነጋሁት…እ…ዶክተር ቴዎድሮስ ናቸው… አለፋሽኝ፡፡
ካናዳ ምን ነበር የምትሠሪው? የምሽት ክበቦች አሉ ወይስ እንዴት ነበር?
በፊት አሜሪካ እያለሁ የምሽት ክበብ እሠራ ነበር፡፡ ካናዳ ከሄድኩ በኋላ ግን በሙዚቃ ደረጃ ሠርቼ አላውቅም፡፡
ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ አሜሪካ እየተጋበዝኩ ሾው ሠርቼ እመለሳለሁ፡፡ ካናዳ ግን ቅድም እንደነገርኩሽ የባለቤቴ ቢዝነስ አለ፤ እሱን ነው የማግዘው፡፡
ከሙዚቃው ብዙ ርቀሽ ስትመለሽ በድምጽሽ ላይ የተፈጠረ ችግር የለም ምክንያቱም አሁን የነፃነት ድምጽ ትንሽ ጐርነን ብሏል የሚሉ አድማጮች አሉ፡፡
እውነት ለመናገር በድምፄ ላይ የተፈጠረ ችግር የለም ምክንያቱም እዛ ሁሌ ቤተክርስቲያን ስለማገለግልና ተሰጥኦ ስለምቀበልና ስለምጮህ ያው ፕራክቲስ እያደረግኩ ነው ማለት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ድምጽ ሁሌም ካልሠራሽበት ክራክ እያደረገ ይመጣል፤ የታወቀ ነው፡፡ የምታንጐራጉሪና የምትዘፍኚ ከሆነ ድምጽሽ እንደተጠበቀ ይቆያል ማለት ነው፡፡ እንዳልኩሽ ቤተክርስቲያን ተሰጥኦ ስቀበል በጣም እጮሀለሁ፡፡ እዛ ማሪያም ቤተክርስቲያን አለች፤ በኢትዮጵያ ኮሙዩኒቲ የተሠራች እዛ አገለግላለሁ፤ ድምፄ በዚህ ምክንያት አላረፈም፡፡ የድምፄ ነገር ትንሽ ወፈር ብሏል ግን የተጋነነ አይደለም፡፡
አዲሱ አልበምሽ እንዴት ነው… ተቀባይነት አግኝቷል ትያለሽ?
ለነገሩ አንዳንዶቹ ትንሽ ድምጽሽ ተቀይሯል ይላሉ፡፡ በአብዛኛው ግን ጥሩ ጥሩ አስተያየቶችን ተቀብያለሁ፡፡ በስራዬ ደስተኛ መሆናቸውን ይነግሩኛል፡፡
አንድ አስቤው ያልጠየቅኩሽ ነገር አለ፡፡ ስለ “ባይ ባይ” ዘፈንሽ ብዙዎች በጣም አንጀት የሚበላ ዘፈን ነው ይላሉ፡፡ የሃሳቡ መነሻ ምንድን ነው?
የዘፈኑ ግጥምና ዜማ ደራሲ አብርሃም ወልዴ ነው፡፡
መነሻችን ከሊባኖስ ወደ ኢትዮጵያ ሲበር ሜዲትራንያን ባህር ላይ ለተከሰከሰው የኢትዮጵያ አውሮፕላንና ላለቁት ወገኖቻችን መታሰቢያ ይሆን ዘንድ ነበር፡፡ ነገር ግን ክሊፕ ለመስራት ፈልገን ወደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ ስንሄድ በፍፁም ሊተባበሩን አልቻሉም፡፡ አየር መንገድ ውስጥ አውሮፕላኖቹ አካባቢ የምንቀረፀው ነገር ነበር፡፡ ብዙ የድሮ አውሮፕላኖች አሉ፤ የሚበሩትንም አካተን መቅረጽ ፈልገን ነበር፡፡ በጣም ፈቃደኛ አልሆኑም፤ ተቸገርን፡፡
በዚህ ምክንያት “ባይ ባይ” ራሱ ለሞት ብቻ መሆን ስለሌለበት ሁሉንም እናካተው ብለን በቃ “ቻው” ለማለት ይሁን ብለን መንፈሱን ወደዚህ ቀየርነው ማለት ነው፡፡ ሰው ከአገር ሲወጣ፣ አብሮ ውሎ ሲለያይ ቻው ቻው ብሎ ነው የሚሄደው፡፡ ስለዚህ በሞትም ይሁን በጉዞ የሚለያይ ሰው ቻው ብሎ መሄዱን ይወክላል፡፡ የሆነ ሆኖ አየር መንገዱ ባይፈቅድም የሞቱት ወገኖች በዘፈኑ ተካተዋል፡፡
ያልተነሳ ነገር ካለ… ወይም ማከል የምትፈልጊው እድሉን ልስጥሽ፡፡
ሁሉም ነገር ተዳስሷል፡፡ በጣም አመሰግናለሁ፡፡

 

Saturday, 09 February 2013 12:15

ራሳችሁ ላይ አነጣጥሩ!

ብዙዎቹ መከፋቶችና መጥፎ ስሜቶች የሚመነጩት ከፉክክር ወይም ራስን ከሌሎች ጋር በማነፃፀር ነው፡፡ ሌሎች ከኛ የተሻለ ሥራ ሰርተው ስናይ ስለራሳችን መጥፎ ስሜት ይሰማናል፡፡
ትኩረታችንን ድክመቶቻችን ላይ ባደረግን ቁጥር ስለራሳችን ፈፅሞ ጥሩ ስሜት ሊሰማን አይችልም፡፡ ሌሎች ከኛ የበለጠ መልከመልካምና ቆንጆዎች በመሆናቸው ብቻ እንከፋለን፡፡ ሌሎች ከእኛ የበለጠ ገንዘብ፣ አውቶሞቢሎችና መኖርያ ቤቶች ስላላቸው በመጥፎ ስሜት እንዋጣለን፡፡
የሥራ ባልደረቦቻችን እድገት አግኝተው እኛ በማጣታችን ሆድ ይብሰናል፡፡ ሌሎች ከኛ የበለጠ ደስተኞች በመሆናቸው ብቻ ከጥሩ ስሜት እንፋታለን፡፡
አያችሁ - ራሳችሁን ከሌሎች ጋር ማነፃፀር ካልተዋችሁ በቀር ሁልጊዜም ከእናንተ የተሻለ ሰው ማግኘታችሁ አይቀርም፡፡
እናም መቼም ቢሆን ጥሩ ስሜት አይሰማችሁም ማለት ነው፡፡ ማብቂያ በሌለው የፉክክር ወጥመድ ውስጥ ከመውደቅ ይልቅ ራሳችንን ነፃ በማውጣት ህይወትን ለምን በመረጥነው መንገድ አንመራም? ሌሎች ከእኛ የሚሻሉባቸው ጉዳዮች ላይ ከማተኮርና ስለራሳችን መጥፎ ስሜት እንዲሰማን ከማድረግ ይልቅ ለምን ከሌሎች መማርና ክህሎታችንን ማሻሻል ላይ አናተኩርም?
የህይወት ቀዳሚ ግብ ማደግ እንጂ መፎካከር አለመሆኑን ማወቅ ብልህነት ነው፡፡
አትኩሮታችሁን ምንጊዜም ራስን በማሳደግና ምርጡን በማለም ላይ ልታውሉት ይገባል፡፡ ይሄ ከተሳካላችሁ የማታ ማታ ትልቁን ሽልማት መቀዳጀታችሁ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡
እ.ኤ.አ በ2004 የአቴንስ ኦሎምፒክ ላይ በወንዶች የ110 ሜትር የመሰናክል ውድድር፤ ለቻይና የመጀመርያውን ወርቅ ያስገኘላት ቻይናዊው አትሌት ሊዩ ዚያንግ ነበር፡፡ ይሄ አትሌት በኦሎምፒክ ለቻይና አዲስ ታሪክ አስመዘገበ፡፡ የአራት ጊዜ የዓለም ሻምፒዮንና በውድድሩ ተፎካካሪው የነበረው አለን ጆንሰን ከውድድሩ ቢወጣ ኖሮ ውጤትህን ይለውጠው ነበር ወይ ተብሎ የተጠየቀው ዚያንግ፤ “በፍፁም! እኔ የራሴን እቅድ ብቻ ነው የምከተለው፤እናም የላቀ ውጤት ማስመዝገቤ አይቀርም ነበር“ በማለት ነው የመለሰው፡፡ አያችሁ ይሄ አትሌት ከማን ጋር ነው የምሮጠው ብሎ እንኳ አይጨነቅም፡፡ ምርጥ ውጤት ለማምጣት ብቻ በትኩረት ይተጋል እንጂ!
ምንጭ- (The Lost Secrets of Manifestation)

Saturday, 09 February 2013 12:11

የፖለቲካ ጥግ

ነፃ ምርጫ እንድታካሂዱ ፈቅጄላችኋለሁ፤ ነገር ግን ከታማኝ አገልጋዬ ከሪቻርድ በስተቀር ማንንም እንድትመርጡ አልፈቀድኩላችሁም፡፡
ሔነሪ ሁለተኛው (የእንግሊዝ ንጉስ የነበሩት የአዲስ ቢሾፕ ምርጫን አስመልክቶ የተናገሩት)
የአሜሪካ ፕሬዚዳንትም እንኳን አንዳንዴ እርቃናቸውን መቆም አለባቸው፡፡
ቦብ ዳይላን (አሜሪካዊ ዘፋኝና የዘፈን ግጥም ደራሲ)
ለፖለቲከኞች ፍቅርም ጥላቻም የለኝም፡፡
ጆን ድራይደን (እንግሊዛዊ ገጣሚ፣ ፀሐፌ ተውኔትና ሃያሲ)
አገር ለመለወጥ ነበር ያለምነው፤ እሱን ትተን ዓለምን ለወጥን፡፡
ሮናልድ ሬጋን (የአሜሪካ ፕሬዚዳንትና አክተር የነበሩ)
ፓርላማ በለንደን ውስጥ የሚገኝ ምርጥ ክለብ ይመስለኛል፡፡
ቻርለስ ዲከንስ (እንግሊዛዊ ደራሲ)
እንግሊዝ የፓርላማዎች እናት ናት፡፡
ጆን ብራይት (እንግሊዛዊ ፖለቲከኛ)
ፓርላማ ወንዱን ወደ ሴት፤ ሴቷን ወደ ወንድ ከመቀየር በቀር ሁሉን ማድረግ ይችላል፡፡
ሔነሪ ኸርበርት ፔሞብሮክ (የእንግሊዝ መኳንንት)
ፖለቲከኛ ማለት ከሰው በቀር ሁሉ ነገር እላዩ ላይ የተቀመጠበት አህያ ነው፡፡
ኢ.ኢ ኩሚንግ (አሜሪካዊ ገጣሚና ሰዓሊ)
ም/ፕሬዚዳንት፤ የመንግስት አውቶሞቢል ትርፍ ጐማ ማለት ነው፡፡
ጆን ናንሲ ጋርነር (የአሜሪካ ምክትል ፕሬዚዳንት የነበሩ)
በተመለከተ የተናገሩት)

 

ለጠራራ ፀሐይ “ዝርፊያ” የጠራራ ፀሐይ “ዘለፋ!”
ዛሬ ወጋችንን በእንቆቅልሽ ብንጀምር ምን ይመስላችኋል? ታዲያ የፖለቲካ እንቆቅልሽ ነው፡፡ ለነገሩ ፖለቲካችን መቼ ከእንቆቅልሽ ወጥቶ ያውቃልና ነው!! (ኑሮአችንስ ቢሆን?) አሁን ለማንኛውም “እንቆቅልሽ?” ብያችኋለሁ “ምን አውቅልሽ” ካላችሁኝ ልቀጥል፡፡ “በአገራችን ብዛታቸው እንደቆጠራቸው ሰው አይነት ከፍና ዝቅ የሚሉት ምንድን ናቸው?” ምናልባት ጠጠር የሚልባችሁ ከሆነ (እንደ ጦቢያ ፖለቲካ ማለቴ ነው!) ፍንጭ ልስጣችሁ እንዴ? (ፍንጭት ግን አልወጣኝም!) ፍንጭ ከሰጠኋችሁማ ምኑን እንቆቅልሽ ሆነ! ስለዚህ በቁርጠኝነት ሙከራችሁን ቀጥሉ፡፡ ወጋችንን ወደ መቋጨቱ ገደማ ስንደርስ ታዲያ መልሱን ሹክ እላችኋለሁ (በምስጢር!)
እስቲ ፖለቲካ በፈገግታችንን ከምድረ አሜሪካ እንጀምረው፡፡ የቤቱ አዛውንት (አያት ነገር ይመስሉኛል) በድንገተኛ የልብ ህመም ራሳቸውን ይስቱና ቤተሰባቸው ተደግናጦ በብርሃን ፍጥነት ሆስፒታል ያደርሷቸዋል፡፡ እዚያም ሲደርሱ ጥብቅ የህክምና ክትትል (IC) የሚሰጥበት ክፍል እንዲገቡ ይደረጋሉ፡፡ (የፖለቲካ IC ቢኖር ጥሩ ነበር!) ከረዥም ሰዓት በኋላ የመረመራቸው ሐኪም ብቅ ይልና፤ “ሽማግሌው አዕምሮው ሞቷል፤ ልቡ ግን ይመታል” በማለት ለትልቁ ልጃቸው ይነግረዋል፡፡ (እንቆቅልሽ አይመስልም?) ልጅም፤ “እንዴ ዶ/ር፤ በቤተሰባችን ውስጥ እኮ አንድም የዲሞክራት ፓርቲ አባል ኖሮ አያውቅም!” አለው - ለዶክተሩ፡፡ (አያችሁልኝ የፈረንጅን ነገር ፍለጋ!) አዕምሮአቸው ሞቶባቸው ልባቸው የሚሰራ ዲሞክራቶች ናቸው ለማለት እኮ ነው፡፡
እስቲ ወደ ዋና አጀንዳችን ደግሞ እንግባ፡፡ እኔ የምላችሁ ግን… ኢቴቪ እዳውን ከፈለ እንዴ? (እዳችንን ማለቴ ነው!) ለምን መሰላችሁ የጠየቅኋችሁ? ኢቴቪ “አይለቀውም… አይለቀውም!” የሚል ነገር አባባሽ ቢያገኝ ኖሮ እኮ… የአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታዎችን የማስተላለፍ ባለመብት ነኝ ከሚለው ተቋም ጋር ቡጢ መግጠሙ አይቀርም ነበር ብዬ ነው፡፡ ደግነቱ አላገኘም፡፡ በነገራችሁ ላይ ኢቴቪ ክፍያ ሳይፈፅም ጨዋታውን ሲያስተላልፍ “እጅ ከፍንጅ” መያዙን እንደ ትልቅ “ሼም” መቁጠር አለብን እንዴ? (ኢቴቪ እኮ ለህዝብ ጥቅም ብሎ ነው - እንደ ኢህአዴግ!) አንድ የህትመት ሚዲያ ላይ ደግሞ “ኢቴቪ የአገር ገፅታን አበላሸ” የሚል ወቀሳ ተሰንዝሮበት አንብቤአለሁ (So what? ራሱ የገነባውን ገፅታ፤ ራሱ አፈረሰ!) እኔ ግን የቲቪ ስክሪናችን ላይ ከመጣው “ሂሳብ አልተከፈለም” የሚል “አሳጭ ፅሁፍ” ይበልጥ የገረመኝ ራሱ ኢቴቪ በራሱ ሚዲያ የሰጠው በቁጣ የታጀበ “ዘለፋ” ነው (ካፈርኩ አይመልሰኝ ይሏል ይሄ ነው!) እናላችሁ… አንድ ምሽት በ2 ሰዓት ዜና ላይ ኢቴቪ ድንገት ንዴቱን አወረደው፡፡

በጠራራ ፀሃይ ተፈፀመ ላለው “ዝርፊያ” ተመጣጣኝ ምላሽ ሰጠ፡፡ አንዳንዶችም ለጠራራ ፀሃይ “ዝርፊያ” የጠራራ ፀሃይ “ዘለፋ” ሲሉ የኢቴቪን ጀግንነትና ወኔ አደነቁ፡፡ እንደኔ እንደኔ ግን ያልተገባ አድናቆት ነው፡፡ ለነገሩ ያኛውም ወገን (ባለመብቱን ማለቴ ነው) ትንሽ ሳያበዛው የቀረ አይመስለኝም! ስንት ሺ ዩሮ ነበር የጠየቀው? (ግድብ እየገነባን መሆኑን አያውቅም እንዴ?) ካላወቀም ጥፋተኛው ራሱ ኢቴቪ ነው የሚሆነው!!
ቆይ አንድ ነገር ልንገራችሁ፡፡ ኢቴቪ ያንን የውጭ ተቋም “ክፍያ አስወደድክብኝ” በሚል ዘራፍ ያለበት ወዶ አይደለም፤ ለምዶበት ነው (ማነው ልማድ ሲሰለጥን ተፈጥሮ ይሆናል ያለው?) አሃ… የጦቢያን ነጋዴ “ለሆዱ ያደረ”፣ “ስግብግብ” ምናምን እያለ መዝለፍ ለምዶበት እኮ ነው! ይሄውላችሁ ዋጋ (ክፍያ) ተወደደብኝ ያለ ወይም ደግሞ “ስንጥቅ ሊያተርፍብኝ ነው” ብሎ የጠረጠረ ደንበኛ፤ ምን ያደርጋል መሰላችሁ? ብስጭቱን ጓዳው ትቶ ለድርድር ይተጋል (ያለ አመሉ?) እናላችሁ… ኢቴቪ “ነቄ” ቢሆን ኖሮ “ውዱን ክፍያ” አስቀንሶ ያለአንዳች ብስጭትና ዘለፋ ሥራውን ይቀጥል ነበር (Business as usual ብሎ!) ድርድሩም ባይሳካም ደግሞ ችግር የለውም (የዓለም መጨረሻ እኮ አይደለም!) መቼም ዘለፋው የተሰነዘረበት ተቋም፤ ነገሩን ሰምቶት ከሆነ እንዴት ግራ እንደሚጋባ አስቡት፡ (እንቆቅልሽ ነው የሚሆንበት!)
አያችሁ… የአፍሪካን ዋንጫ ጨዋታዎች ለኢቴቪ ለማስተላለፍ ከ1ሺ ፐርሰንት በላይ የዋጋ ጭማሪ አድርጓል የተባለው ተቋም፤ Local (ኢትዮጵያዊ ማለቴ ነው) ቢሆን ኖሮ እኮ ችግር የለውም ነበር፡፡ (ገበና ለገበና እንተዋወቃለና!) ይኸኛው ግን ዓለም አቀፍ ተቋም ነው - Strictly በነፃ ገበያ መርህ የሚመራ!! (ነፃ ገበያና ዕዝ ኢኮኖሚን ማጣቀስ አያውቅም - እንደ ኢህአዴግ!) እናም በዋጋው የተስማማ ከፍሎ አገልግሎት ያገኛል፤ ያልተስማማ ይቀርበታል፡፡ (እጅ ጥምጠዛ እኮ የለም!) አያችሁ… ኢቴቪ እዚህ አገር ነጋዴ “ዋጋ አስወደደ” በሚል ወዶ እስከሚጠላ እንደሚብጠለጠል አሳምሮ ያውቃል! (ምን ማወቅ ብቻ?) እናም በአገር ውስጥ ልማድና ደንብ ዓለም አቀፍ ቢዝነስ ለማካሄድ ዳዳው፡፡ እኔማ “እንኳንም በዚህ አለፈልን!” አልኩኝ፡፡ እንዴ… ኢቴቪ ቢነሳበት ኖሮ እኮ ወዶ እስኪጠላ በማይሰማው ቋንቋ “ያስታጥቀው” ነበር - ያውም በተረትና በምሳሌያዊ አባባል የበለፀገ! “የኒዮሊበራል ቅጥረኛ!”፣ “ፀረ-አፍሪካ!”፣ “የኢምፔሪያሊዝም ግልገል” ወዘተ…ወዘተ ሊለው ይችል ነበር እኮ፡፡ (አንድዬ አተረፈና!) ትንሽ የቆጨኝ ግን ኢቴቪ ተቋሙን “ኪራይ ሰብሳቢ!” ሳይለው መቅረቱ ነው!! ትክክለኛ የኪራይ ሰብሳቢ ምሳሌ እኮ ይሄ ተቋም ነው (መብቱ ቢሆንም!)
እኔ የምላችሁ… ፅሁፌ መግቢያ ላይ ያቀረብኩትን የእንቆቅልሽ ጥያቄ ፈታችሁት? ይሄውላችሁ… በአገራችን ብዛታቸው እንደ ቆጣሪው ከፍና ዝቅ የሚሉት ምን መሰሏችሁ? የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ናቸው!! እንቆቅልሹ ግን የእኔ ፈጠራ እንዳይመስላችሁ! (ኮፒራይቱ የአንድ ቱባ ፖለቲከኛ ነው!) ኢህአዴግ ወደ ሥልጣን ከመጣ ጀምሮ የተለያዩ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በመመስረት በሊ/መንበርነትና በፕሬዚዳንትነት ወደ ሁለት አስርት ዓመታት ገደማ የመሩት (ያውም ምክትላቸው ከነመኖራቸውም ሳይታወቁ) ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ ናቸው ባለቤቱ! በቅርቡ በአገሪቱ ውስጥ ስንት ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዳሉ ሲጠየቁ ምን አሉ መሰላችሁ? “እሱ እንደቆጣሪው ይለያያል!” (የአመቱ ምርጥ የፖለቲካ እንቆቅልሽ!)
“እውነት ግን የተቃዋሚዎች ብዛት ምን ያህል ነው?” ማነው የሚጠየቀው - ኢህአዴግ ነው ምርጫ ቦርድ? ሌላው ቢቀር እኮ መረጃው ለኢቴቪ ጥያቄና መልስ ይሆነናል፡፡ (ድንገት ከተጋበዝን ብዬ እኮ ነው!) ግን ለምንድነው በኢቴቪ የተቃዋሚዎች ጥያቄና መልስ የማይጀመረው? (ኢቴቪ የጋራ ንብረታችን ነው ብዬ እኮ ነው!)
የኢህአዴግ ፅ/ቤት ኃላፊ የተከበሩ አቶ ሬድዋን ሁሴን በቅርቡ የሰጡት መግለጫ ተቃዋሚዎችን ጭስስ እንዳደረጋቸው ታዝባችሁልኛል? 28ቱ ፓርቲዎች ባለፈው ሳምንት በሰጡት ምላሽ ኢህአዴግ ነፍሴን “አግላይ!” ብለውታል (ብርቁ ነው እንዴ ማግለል!) እሱማ ይሄኔ እግሩን ዘርግቶ Mission Accomplished ይላል፡፡ እኔን ደግሞ “ጭስስ” የሚያደርገኝ ምን መሰላችሁ? የኢትዮጵያ ፖለቲካ ማጠንጠኛው “ብሽሽቅ” መሆኑ ነው!
በነገራችሁ ላይ ፕሮፌሰር በየነ ስለተቃዋሚዎች ብዛት የሰጡትን እንቆቅልሻዊ መልስ የሚያጠናክር አባባል 28ቱ ፓርቲዎች በሰጡት መግለጫ ውስጥ አግኝቻለሁ፣ እንዲህ ይላል፡-
“ኢህአዴግ ለራሱ ፖለቲካዊ ጥቅም የሚበጀው ሲሆን 75 የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዳሉ ይናገራል” የሚለው መግለጫው፤ ሲያሻው ደግሞ ተቃዋሚዎች ውስጣቸው መፈተሽ አለበት በማለት የምርጫ ቦርድን ሥልጣን ይወስዳል ሲል ኢህአዴግን ይኮንናል፡፡ (አቤት የእንቆቅልሻችን አበዛዝ!)

Saturday, 09 February 2013 11:55

እንጨዋወት

‘ሲስተም ፌይለር’…

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
የካቲት ተጋመሰሳ! (“ገንዘብ መቁጠር ሲያቅትህ ወር ቁጠር…” ያልከኝ ወዳጄ…አሁን፣ አሁን እየገባኝ ነው!)
ስሙኝማ…ግራ እየገባን ያለ ነገር አለ፡፡ ይሄ ቴክኖሎጂ ምናምን የሚሉት ነገር..አለ አይደል ጥቅሙ ሥራን ማቅለልና መልክ ማስያዝ፣ የእኛንም መጉላላት ለማስቀረት አይደል እንዴ! ዓለም ስንት ሥራ እየሠራ ባለበት ሰዓት እኛ ሚጢጢዋ ነገር ሁሉ አቃተችን ማለት ነው!
የምር እኮ…ግራ እያጋባን ነው፡፡ “አገልግሎታችን ሁሉ ኮምፒዩተራይዝድ ሆኗል፣ ከእንግዲህ መጉላላት የለም…” ምናምን ተብሎ ደስ ሲለን ለአገልግሎት ስንሄድ ምን ይባላል መሰላችሁ…“ኮምፒዩተሩ አልሠራ አለ!” (ስሙኝማ…ይቺ አባባል ምን ትመስላለች መሰላችሁ…በቃ ልክ እርስ በእርስ ጣት መጠቋቆም እንደምንወደው ሁሉ ኮምፒዩተሩ ላይም ‘ጣታችንን የምንጠቁም’ ነው የሚመስለው፡፡ አልሠራ ያለው ኮምፒዩተሩ ነው እንጂ ኮምፒዩተሩን የሚያንቀሳቅሰው ወይም ሰው አይደለም፡ አሪፍ አይደል!)
እናላችሁ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይሄ ‘ሲስተም’ የሚሉት ነገር ልክ የሆነ ወርድና ስፋት ያለው እየመሰለን መጥቷል፡፡ አሁን፣ አሁን “ሲስተሙ አልሠራ አለ” የሚሉት ነገር ከአንዳንድ ለምድር ለሰማይ ከከበዱ መሥሪያ ቤቶች ስንሰማ…ግር የሚል ነገር አለ፡፡ መጀመሪያ ‘ሲስተሙ’ ሥራ ላይ ከመዋሉ በፊት በቂ ሙከራ አልተደረገበትም ማለት ነው! ልክ ነዋ…ነገሮች “ባገኝ ባጣ…” አይነት ነገር እየሆኑብን ነዋ! በ“ባገኝ ባጣ…” አለ አይደል… ከሆነ ይሆናል ካልሆነ አይሆንም…‘ፉል ስቶፕ’!
‘ሲስተም’ ምናምን የሚባሉ ነገሮች ግን የራሳቸው የቀረጻ፣ የሙከራ፣ የማረጋጋጫ ምናምን ነገሮች አሏቸው አይደል እንዴ! እና አንድ ነገር ገና ከመጀመሩ “ሲስተም አልሠራ አለ…” ምናመን ነገር ሲባል…ቴክኖሎጂ ላይ እምነት እንድናጣ ነው የሚያደርገን፡፡ የመዘመናችን ነገር ከ‘ፌስ ቡክ’ አላልፍ ብሎ ግራ የገባን ነው የሚመስለው፡፡ (ስሙኝማ…እንዴት ነው አሪፍ የሆነው ነገር ሁሉ ወደ እኛ ሲመጣ የሆነ ጭራና ቀንድ የሚያበቅለው! አሁን ለምሳሌ ‘ፌስቡክ’ የሚሉትን ነገር…ካወቅንበት የሚገኝበት ዕውቀትና መረጃ በምንም ሊለካ የማይችል ነው፡፡ ሆኖም በ‘የፌስቡክ’ ገጽ የሚለጠፉትን ምስሎች፣ የሚጻፉትን መልእክቶች ምናምን ስታዩ የምር አስቸጋሪ ነው፡፡ አለ አይደል…“‘ደመ መራራነታችን’ ይሄን ያህል ጠልቆ በፌስቡክም ገባ እንዴ!” ምናምን የሚያሰኝ ነው፡፡) እናላችሁ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…‘ሲስተም’ የሚባለውን ነገር “ሀይ!” የሚልልን ይጥፋ! ልክ ነዋ… “እሰይ ስለቴ ሰመረ፣ ኑሮዬ ዘመነ” ምናምን ብለን ለመዝፈን ሲቃጣን ምን ይሆናል መሰላችሁ…‘ሲስተም ፌለር’ ይገጥማል! ስሙኝማ…አንዳንድ ጊዜ “‘ሲስተሙ’ም እንደ እኛ ክፉ፣ እንደ እኛ ‘ምቁ’ ሆነ እንዴ ምናምን ያሰኛል፡፡ የምር…ካነሳነው አይቀር… እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ምን መሰላችሁ፣ ‘ደመ መራራነት’ በዛ፡፡ በዛው ልክ ክፋት በዛ፣ ምቁነት በዛ ጥላቻ በዛ!
ኮሚክ ነገር እኮ ነው…የእኛ የግለሰቦቹ ክፋት ‘ፍሬኑ ተበጥሶ’ ሲንደረደር...አንዳንዴ ክፋት የግለሰቦች ጉዳይ ብቻ መሆኑ ቀርቶ…አለ አይደል…የሆነ ‘ኦርጋናይዜሽናል ቻርት’ የተሠራለት ነው የሚመስለው፡፡ ክፋት፣ ምቀኝነት፣ ጥላቻ ምናምን የተባሉ ነገሮች…የሆነ በስርአት የተዋቀረ አይነት መልክ ያላቸው ሲመስል አስቸጋሪ ነው፡፡
ሀሳብ አለን…‘ኒኦ ክፋቲዝም ምናምን የሚባል የ‘ቦተሊካ’ ስርአት ተፈልስፎ በመጽሐፍ መልክ ይውጣልንማ! አሀ… የራሳችን ‘ዳስ ካፒታል’ የሚኖረን ደረጃ ላይ ደርሰናላ! (በነገራችን ላይ ‘ኒኦ—ክፋቲዝም’ የእኛንና የወዳጅ አገር ‘አፎች’ን በማገናኘት የተፈጠረ ነው፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…ያው በምግብ ‘ሚስቶ’ የምንለው አይነት መሆኑ ነው፡፡ ‘ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች’ አይነት ሚስቶ እንትኖች ኦፊሴላዊ እውቅና አላቸው አይደል፡፡) እናማ… ክፋት ይህን ያህል እየተዋሀደን መምጣቱ ካልቀረ አርማ ወጥቶለት፣ ‘ሲንግል’ ተለቆለት፣ የኮሚዩኒኬሽን ባለሙያ ተመድቦለት (ቂ…ቂ…ቂ…) ‘መልክ’ ይውጣለትማ!
ደግሞ ሌላ እየበዛ የመጣ ነገር አለላችሁ…ስስት! የምር… በአጥር ተንጠልጥሎ “እከሊት፣ ከእራት የተረፈች ትንሽ ሹሮ ቢጤ አለችኝ፣ ነይ አባይኝማ…” ምናምን ማለት በአርኪዮሎጂስቶች ዋሻ ውስጥ በ‘አራሚክ’ ቋንቋ ተጽፎ ይገኝ እንደሁ እንጂ…እንኳን ልንሰማው “እንዲህ ይባል የነበረበትም ዘመን ነበር እንዴ!” የምንልበት ዘመን ደርሰናል፡፡ ልጄ…ዘንድሮ እንኳን “ሹሮ አባይኝ” ሊባል ቀርቶ…አለ አይደል…የሌላ ሰው ሹሮ ላይ ሁላችንም የይገባኛል ጥያቄ ያለን ነው የሚመስለው፡፡ ‘መስጠት’ የሚለው ቃል ሙሉ ለሙሉ ‘መውሰድ’ በሚለው ስለተተካ…ከ“እራት የተረፈች ሹሮ…” መጋበዝ “ሲያምርሽ ይቅር” የሚባል ነገር ሆኗል፡፡
እናላችሁ…ነገርዬው ሁሉ…አለ አይደል…“እንካ” ማለት እየቀረ “አምጣ” ማለት ብቻ እየገነነ የመጣ ይመስላል፡፡ የእኛ የግለሰቦቹን እንኳን ተዉትና…አንዳንዴ ከተለያዩ ክፍሎች የሚወጡ መመሪያዎች፣ ደንቦች ምናምን ላይ እንኳን ከጀርባቸው የሆነ “አምጣ” የሚል ጩኸት የገደል ማሚቶ ትሰማላችሁ፡፡ እናማ…“ይቺ ያው እንደተለመደው ለገንዘብ የወጣች ነች…” እያልን ማማታችን ከቁጥር ይግባልንማ!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ጅብ ሆዬ እሜቲት አህያ የሆነ ነገር ተሸክማ ስትሄድ አይቶ ምን አላት አሉ መሰላችሁ…“አንቺም ሲሳይ፣ የተጫንሽው ሲሳይ…” ብሎ አረፈላችሁ፡፡ እናማ…አንዳንድ ጊዜ ጫና ሲበዛብን የተጫንነው ነገር ይኑርም አይኑርም…“አንቺም ሲሳይ፣ የተጫንሽው ሲሳይ…” የምንባል ይመስለናል፡፡
እናላችሁ…አሁን፣ አሁን አንዳንድ መሥሪያ ቤቶች ያለው የተገልጋይ ሰልፍ የካምቦሎጆውን የጊዮርጊስና ቡና ግጥሚያ ‘አርማጌዶን’ ሊያስንቅ እየተጠጋ ነው፡፡ እናማ…የከምፒዩተርም ይሁን የግለሰብ…‘ሲስተም’ የሚባለው ነገር “ሀይ” ይባልልንማ! ብዙ ነገሮች እየናፈቁን ነው፡፡ የምር…ዘወር እያልን ከጀርባችን የማናይበት ጊዜ እየናፈቀን ነው፡፡ የመሸበት መንገደኛ እግሩ ታጥቦ እንዲያድር የሚደረግበት አይነት መተማማን…አለ አይደል… ‘የድንጋይ ላይ ጽሁፍ’ እየሆነ በመጣበት ጊዜ የምናምነውና የሚያምነን ሰው እየናፈቀን ነው፡፡ “እንዲህ ያለ ዘመን ዘመነ ግርምቢጥ…” ምናምን እንደሚባለው ሁሉ…አይደለም ጓደኛ ጎረቤት ምናምን፣ የሥጋ ዘመድ ተሁኖ እንኳን መተማማን እየጠፋ ነው፡፡ እምነታችንን ጥለን “ይቺን ገንዘብ በአደራ አስቀምጭልኝ…” “ገበያ ደርሼ እስክመጣ ልጆቹን ጠብቅልኝ…” ምናምን የምንልበት ዘመን እየናፈቀን ነው፡፡
በፊት ጊዜ ገድገድ ሲያደርጋችሁ፣ ሲያደናቅፋችሁ “እኔን ይድፋኝ!” ምናምን የሚል የማታውቁት ሰው መአት ነበር፡፡ አዎ “ብታምኑም፣ ባታምኑም” እንደሚባለው……እንዲህ የሚባልበት ጊዜ ነበር! (ከዚህ በፊት እንዳወራነው…አለ አይደለ… “ነበር” የሚለው ቃል እየበዛ ሲሄድ አሪፍ ምልክት አይደለም፡፡) አሁን፣ አሁን ግን አይደለም የማታውቁት ሰው፣ የምታውቁት ‘ሹሮ ተበዳዳሪ’ እና ‘ቡና አጣጪ’ እንኳን ሲያደናቅፋችሁ… “ምን ያወላክፈዋል፣ እያየ አይሄድም!” ምናምን ነው የሚላችሁ፡፡ እናማ… እንደው ገድገድ ሲያደርገን እጁን ሰደድ አድርጎ “እኔን!” የሚል ህብረተሰብ ናፈቀን፡፡
ጓደኛሞች ናቸው፡፡ አንደኛው የሆነ ዕቃ ጓድኝየው ጋር በአደራ ለማስቀመጥና ላለማስቀመጥ ሲያመነታ ጓደኝየው ምን ይለዋል…“እመነኝ ሀሳብ አይግባህ፣ ዕቃውን በሚገባ እጠብቅልለሁ” ሲለው ያኛው ደግሞ “አይደለም አንተን የገዛ ወንድሜንም አላምንም…” ይለዋል፡፡ ጓደኝየው ምን ቢል ጥሩ ነው …“ልክ ነህ፣ እኔም የአንተን ወንድም አላምነውም፡፡” ከማይታመንና አደራ ከማይጣልበት ዘመድና ወዳጅ ይሰውረንማ!
በየመሥሪያ ቤቱ በር ላይ ፈገግ የሚሉ የጥበቃ ሠራተኞች ማየት ናፈቀንማ፡፡ “አቤት ጌታዬ ምን ልርዳዎት…” ማለት ቀርቶ ዱላውን እየወዘወዘ “ወዴት ነው፣ መግባት አይቻልም” የሚል የጥበቃ ሠራተኛ በዝቷል፡፡
ስሙኝማ…እንደ እኛና ቢጤዎቻችን ግራ የገባው ምስኪን ምን አለ አሉ መሰላችሁ…
ግንብ ላይ ብሠራ እባቡ መከራ፣
በዛፍ ላይ ብሠራ አሞራው መከራ፣
በምድር ላይ ብሠራ እረኛው መከራ፣
የት ውዬ የት አድር ብዬ፡፡
እናላችሁ…ብዙ ነገር እየተበላሸ ‘ሲስተም ፌይለር’ የሚሉት ነገር እግር ተወርች እያሠረን ስለሆነ “ሀይ!” ይባልልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!