Administrator

Administrator

 ርዕስ ፦የዱር አበባ
                                ዘውግ ፦ ግጥም
                             የህትመት ዘመን ፦ 2017
                             ገጣሚ፦ ቴዎድሮስ ካሳ
                                       ሲራክ ወንድሙ

        ሁለት ሥጋ’ና ደሞች
ሁለት የሥጋ እስረኞች
ገላን ጥለው እሳት ሆነው
አዎ ... እሳት ሁነው !
 ፍም ነበልባል ፤ ...
ሕይወት አፈር እንዳትባል
 ሕይወት ውኃ እንዳትባል
ሕይወት እሳት ብቻ ሁና !

ሕይወት የዱር አበባ !
ሥነ ግጥም፤ የአፍላነት ወዝ ጠፈጠፍ ነው ከተባለ የሚገለፀው፣ በሌሪክ የግጥም ዘውግ ሆኖ እናገኘዋለን። ሌሪክ፤ ግጥሞች ግላዊ ስሜቶችን ፣ ሀሳቦችንና  ምናኔ ጠቀስ የሆኑ ጥልቅ ስሜቶችን ሙዚቃዊ ቃናና ምት በማላበስ የሚቀርብበት ዘውግ ነው።
በስሜት በተሞሉ ቃላት እንደመልካ ብናኝ የመርጠባቸውና ከውስብስብ ደረቅ ሴራ ይልቅ አንድ አፍታ ወስደው ግላዊ ስሜታቸውን መተንፈስ መቻላቸው እንዲሁም በቅሬታ ውስጥ እንደተገኘ አፍለኛ ሙዚቃ፣ ዜማ ለበስ ቃናን መቸራቸው ከባህሪ ተቆጥሮ የሚለዩበት ድንበር ነው።
 ትንሽ ቁስል
 እድሜ ሙሉ ትዝ የምትል!
የአንቺ ፍቅር
ስር የሚሰድ ከጅማት ስር  
(ገፅ 33 )
ሌሪክ ግጥሞች እንደ ሁሉን ወዳጅ ትንሽዬ ህፃን ናቸው። ያየ አያልፋቸውም፤ ወደ ደረቱ አስጠግቶ ይስማቸዋል። ከልብ፣ ከነፍስና ከስሜት የሚወለዱ ናቸውና ከጠራቸው ጋር በቀላሉ ስምምነት ይፈጥራሉ። ተግባቢ ናቸው፡፡ «ይሄ ልጅ ከሁሉ ነዋሪ ነው» እንደሚባለው አይነት መልከኛ...!
የቴዎድሮስ ግጥሞችም እንዲሁ ናቸው። ስዕላዊ መገለጫቸው ረቀቅ ጠበቅ ያለ ውልን እንደ ዝናር በወገቡ ሸብ ያደረገ ነው።
ከሌሪካዊ የግጥም ዘውግ ባህሪ የሆነው አንዱ፣ የተፈጥሮና የፍቅር ጭብጥ በዚህም መድበል ውስጥ ነፍስ ዘርቶ እንዲንቀሳቀስ የተዳው ይመስለኛል፡፡  
ተፈጥሮን ስል
ተፈጥሮዬ
ቀዝቃዛ አካል ውስጥ እንደሚዋኝ
ቁስል እንደበዛበት ፍቅር ነው
ረጅም ስሞሽ ያደክመኛል
ዝም ያለ ሰው ይገድለኛል።
(ገፅ 20 )
ፍቅርን ስል
የተጎነጨሁት ወይኑ አልደረቀም
ገና
ጆሮዬ ስር
ስሰማ ያመሸሁት ሙዚቃ አልበረደም።
(ገፅ 27)
ስዕልን ስል
 የህይዎት ጣዕም
የህይዎት ውበት
ቀዝቃዛ ሻይ
እጅሽ መሃል የበረደ፤
ግማሽ እድሜ
አንቺን ሲያስብ የነጎደ ፤
ጅምር ሀሳብ  
ጅምር ግጥም  
          ጠርቶ ያመጣው፤
ውብ ወዘና
ጎረምሳ ሌት የሚጠጣው።  »
(ገፅ 32-33 )
ገጣሚው የሌሊት ፍቅርና ምሰጣ እያዘገመ በስንኞቹ ውስጥ እንዲያደባ የፈቀደ ይመስላል። የውብ ሰመመናዊ የትዝታው ጫፎች፣ የተቋጠሩት በሌሊቱ የዝምዝማት ሸማ ውስጥ ነው። ዘውትር ማኅሌታይ እንዲባሉ በሌት የተወለዱም ጭምር..!!
ደሳስ የሚሉ ወቅት የወለዳቸው የህይወት የሞቅታ እቅፍ ያባባቸው ስንኞች ልክ እንደልብ ምት በረገጡት አፈር ላይ ሲዘሉ፣ ብርሃን እቅፍ ውስጥ ተወልደው ጊዜን ለመገዘት ሀሳብ ያላቸው፤ ምሽት ያላቸው ፤ ምኞት ያላቸው አይነት ናቸው። የተቃኑበት ለጋ ሰመመናዊ የወቅት ትንፋሽ፣ በፀዓዳማው የሳቅ ወንዝ እያሳሳቀ እንደሚወስዳቸው ወጣት ውበቶች ናቸው።
ለዚህም ይመስለኛል በግጥም ላይ የሚስማሙ በርካታ ምሁራን፤ አንባቢና ግጥም አድናቂያን ለግጥም የተመረጠ የሚሏት ወቅት ወጣትነትን ነው። ወጣትነት ለግጥም ገና የፈካ አበባ እንደማለት ነው። የእንቡጥነት ዘመኗን ባጅታ ብቅ ባለች አበባ ላይ ዓይን ይራኮታል። ጓጊና ቀጣፊ መዳፎች የእጆቻቸው መንገድ አበባና አበባዋ ጋር ብቻ ይሆናል።
Catharsis የሚባለው ጥንታዊው የግሪክ ፅንሰ ሀሳብ ውስጥ ስለ ግጥምና ስሜታዊ መግለጫን በተመለከተ እንዲህ የሚለው ማብራሪያ ትዝ አለኝ፡- Poetry provides a means for young people to articulate complex emotions that they may struggle to express verbally. Writing or reading poetry can serve as a cathartic release, helping them process feelings related to identity, relationships, and life transitions.
እኔም ለዚሁ አንድምታ እቀርባለሁ።
ለጋነት ለየትኛውም ኪነ ጥበባዊ ውልደቶች (በተለይም ለግጥም) መልከኛው ሰሞን ነው።
ምርጥ ግጥም ማለት
ቃላት ያልነካው ነው፤
ምርጥ ግጥም ማለት
 በሁለት ፍቅሮች መኃል፤
ያለ ዝምታ ነው
(ገፅ 88 )
ወጣትነት የለጋነት ቤት ከመሆን ባለፈ የስስነት ቋቱ ነው። ከዚያ በላይ ያለው እድሜ የተግሳፅና የምክር እጀታዎች የሚበዙበት ሲሆን፤ ከዚህ በታች ያለው ደግሞ ልክ በSigmund Freud  early childhood experience theory መሰረት፣ ደስታዎቻችንን በአፋችን የምናስስበት ሰሞን ነች። ይህም ከቆዳ መገልበጥ በፊትና በኋላ ብለን ልንጠራው እንችላለን። ከመገልበጡ በፊት ያለው ጊዜ መነካት ወደ ስሜትና ትርጉም የሚቀርብበት ለጋ ወቅት ነው።
ምሁራኑ ለስነ ጥበብ የተመቸ የሚሉትም ይህቺኑ ዕድሜ ነው። ገጣሚነትና ሁሉን አቀፍ ሚናነትም እዚሁ ጋ በስፋት የሚነሳ ዓብይ ጉዳይ ነው። መሳሳቱና ህመሙን ያወጀበት ታዛ ላቅ ሲል የብዙ ግፉዓን ነፍሶች ማፅናኛ ድንኳን ይሆናል። ይህን ጉዳይ በተመለከተ ገጣሚው ራሱም በገፅ 97 ላይ ይህንኑ ፈርጅ እንዲህ ይዳስሰዋል፡-
 እሳት!
እሳት!
 እሳት!
በእያንዳንዱ ሰው ነፍስ ፤ የምትፈላውን
 የውበት ወርቅ ሐርር ፤ ጎንጉኖ ሲለብሳት
 እጅግ ያሳዝናል
እንዲህ ያለው ወዳጅ ፤
በቁሙ ‘ሚቃጠል
ገጣሚ ይባላል።
(ገፅ 91 )
ቴዎድሮስ ካሳ በውስጡ ሺህ ዓመት ህይወትን የታዘበ፣ ያየ ያስተዋለ በሚመስል ልክ ብዕሩ የበረታች ወጣት ነው። ቀድሞ ከዘመን መንቃት ዕድሜን ማስከተል፣ የአሪፍ ትውልድ መገለጫ ነውና ቴዲ ከነብስ የሚወለዱ ግጥሞች ባለቤት ነው። ስንኞቹን ለጋነት አይጎበኛቸውም። ለዘብ ብለው የሚተፉት ስሜት ልብ ውስጥ የሚቀሩ ናቸው። የሚቀሩም ብቻ ሳይሆን አንባቢን መያዝ የሚችሉ በሳሎች ናቸው። የታደለ ዘመን እንዲህ ያሉ ብሩህ ወጣቶችን በወቅት አፈሩ ላይ ያጎነቁላል።
“የዱር አበባ”ን በተመለከተ የቴዎድሮስ ካሳ mystical ማጫወቻዎቹ ውስጥ እሳትን ... ናፍቆትን እና ዝምታን እንድንመለከት እፈልጋለሁ።
እሳት
ከግሪክ አፈታሪካዊ ትርክቶች በመነሳትና እሳት ሰርቆ አሰቃቂ የቅጣትን ፅዋ ከተጎነጫት ፕሮማቲየስ በመነሳትና እሳት የመጀመሪያውና ትልቁ የሰው ልጅ የግኝት ውጤት መሆኑን በመጠቅለል በፊደል ተሰርተው እሳት ከሚረጩ ስንኞች ጋር እናዘግማለን።
ተመልከችው እርሱን
 ፍቅር አጠውልጎት ፤
 ናፍቆት ፍም አድርጎት
 ፍም እሳት ነበልባል ፤
 በአካሉ አለሁ ቢልም
የለም እንዳይባል!
(ገፅ 89)
ግጥሞቹ በባህሪያቸው እሳታዊ ውበት፣ እሳታዊ ናፍቆታዊ ምስሎችንና መሰል ድምፆችን ያዘሉ ሲሆኑ፤ የአንባቢው ልብ ላይ ያለውን ተመሳሳይ ስሜታዊ ሻማ ለመለኮስ ያለመ ይመስላል። በሚስቲሲዝሙ አለም እሳት ብዙውን ጊዜ እንደተለዋዋጭ ኃይል ይታያል። የመንፃትን ሂደት ቆሻሻዎችን (ያደፉ የሀላፊ ጊዜ ማንነታዊ ጥላዎችን ) በማቃጠል እና እንደገና ማደስ እንዲሁም ዳግመ ውልደት መፈከሪያ አንዱ መንገድ ነው።
(ፊኒክስ በእሳት ወላፈኑ እርር ብላ ራሷን ዳግመኛ እንደምትወልደውም እንደማለት..! )
እሳት ነፍስን ለማንፃት በአምልኮ ስርዓቶች ውስጥ በስፋት ጥቅም ላይ ይውላል።
ሕይወት ድጋሚ
በዓይኖችሽ ውስጥ እንድትወልደኝ
 እፈልጋለሁ።
 አፍ አፉን ቢስሙት የማይጠግቡት ፍቅር
ሆኜ
መወለድ እፈልጋለሁ።
(ገፅ 99 )
እሳት የመለኮት መገኘት አንዱ መንገድ ሆኖም ይቀርባል፤ ለምሳሌ ያህል፡- በክርስትናው አውድ  በሙሴ ታሪክ ውስጥ የሚቃጠለው ቁጥቋጦ፣ የእግዚአብሔርን መገኘት ሲያመለክት፣ በሂንዱ የእምነት ዳራ  ደግሞ የእሳት አምላክ በሰዎችና በመለኮታዊው አካል መካከል አስታራቂ ተደርጎ ይቆጠራል።
 ከዚህም ባሻገር እሳት የእውቀትና የመገለጥ ምልክት ፣ የጥፋትና የትርምስ ፣ የመንፈሳዊ መነቃቃት ተምሳሌትና በግለሰብ አውድ ውስጥ እንደ ፍቅር ፣ ከፍተኛ ፍላጎትና ኃይለኛ ስሜቶችን ሊወክል ይችላል። እሳት በብዙ መተርጎም መተንተን ከሚችሉ ግዙፍ ጉዳዮች ውስጥ አንዱ ነው። ለዚህ ይሆን ቴዎድሮስ በአንድ ግጥሙ እንዲህ የሚለን፡-
ወደ እሳት ሲጠሩህ ክንፎችህን ዘርጋ
ልቦናህን ከፍተህ  አይኖችህን ዝጋ ፥           
ቅለበዉ ጠጠሩን ፥
የወንጭፉን ሩሕ ፥       
“እንሂድ” በላቸዉ ፥ ለስቃይ ሲጠሩህ ፥                            
ታገለዉ ወጀቡን ፥          
ግፋዉ ማዕበሉን ፥             
 ዝለቀዉ አፀዱን ፥                                          
 ተቀበለዉ ስሙን ፥      
 [ የሰዉ ልጅነቱን ]                                            
 ዉደደዉ ሙላቱን ፥                                          
 ዉደደዉ ጉድለቱን ፥                                        
 አፍቅረዉ ጥመቱን ፥     
 አፍቅረዉ ቅናቱን  ፥      
 የአካል እንግልቱን    
     [የሰዉ ልጅነቱን]                
(ተናገር ለሁሉም  ሰው ከልብሱ በታች ፍም እሳት መኾኑን! )
(ከገፅ 76-77 )
ናፍቆት
“Nostalgia is a form of suffering.”
Milan Kundera:
ሩህሩህነት አምጦ የወለዳቸው የአሁንም ሆኑ የሀላፊ ጊዜ የህይወት ውልብታዎች በናፍቆት ስም የቆሙበት በራፍ መፅሐፉን እፁብ ለማድረግ ምስጠት ከሰጡ ነገሮች ውስጥ አንዱ ነው። ናፍቆት በስስ ዝማሬ የተደረሰባቸው ንዝረታዊ እሳታዊ መታመቆች ስለናፍቆት መጮህ ብቻም ሳይሆን በእምባ መሬት ላይ አስቁመው ህመምን የሚያስናፍቁ ናቸው። መሻታቸው ተፈጥሮ ፣ ስክነት ፣ ዝምታና ሌላም ሌላም ነገር ቢሆን፣ የታሰሩበት ገመድ ግን ናፍቆት ነው። ስጥም ያለ ደስ የሚሉ ልጃገረድ ስንኞች ውስጥ ፈገግ ያለ ህይወት....
ዛሬ ሌሊት
 ሕልም አየሁ፡፡
የሚጣፍጥ ወይነ-ጠጅ አፌን ሲሞላው፤
 ከአፌ ወይነ-ጠጅ ሲፈልቅ
 የወይን ፍሬ ሁኜ ፤
በቀጭን አረንጓዴ ሐረግ ላይ ተንጠልጥዬ ፤
ቀረፋ የተሞላ ንፋስ ሲያወዛውዘኝ
መብሰል ቆዳዬን አሳብጦት
ልፈነዳ ... ቅብትት ብዬ ... ቀልቼ ፤
(ገፅ 95)
ዝምታ
ዝምታ አንዳንድ ግጥሞቹ በዝምታ እንደሚፈስሱ ፀባየኛ ወንዞች ይመስላሉ። ጉልበታቸው እርጋታ ሆኖ አገኛቸዋለሁ። ልስላሴ ውስጥ እንደተገኘ ኩልል ያለ መፍሰስ አንዱ የዚህ መፅሐፍ ባህሪ ነው። ከባህሪነቱም ባሻገር በህይወቲቱ ሌማት ላይ ተንጠራርቶ ከሚዘግናት እፍኞቹ ወይም በመኖሩ ከሚገደው ነገሮቹ መሀል የዝምታ ባንዲራ አንዱና ዋነኛው ነው።
በሚወዳቸው ትዝታማ ሌቶቹ ውስጥ የሚወለዱ አጋጣሚዎቹ ዝም ያሉ ይምሰሉ እንጂ እሱ ተውሶ የሚሰጠን የትርጓሜ አሀድ ከመርቀቅ አይዛነፍም። ግጥሞቹም ሆነ ስንኞቹ ውስጥ ያደረው ሰው (ገጣሚው) ዝምታ ወዳድነቱ ከስክነታዊ አፍታዎች ጋር አዛምዶታል የሚል መደምደሚያ አለኝ። ያም የጥሩ framework ስራን በመፅሐፉ ውስጥ እናገኛለን።
ሌላው የተሰበሩ ዜማዎች ወጀብ መፅሐፉን ከስሜት ቅለት አንፃር ሊያደክሙት እንደሚችሉ ባምንም፣ የዚያን ያህል ጨለማ የጎላባቸው እንዳልሆኑ ግን መስክር ቢሉኝ ዓይኔን አላሽም። መሳጭነቱ ላይ የተዘሩት እነዚያ ፊደላት እሳታማ ናቸው። በውሃ የሚጠፉ ሳይሆኑ በእምባ ተግ የሚሉ አይነት ወደረኞች...! ሰመመን ያጫራቸው ግልፍተኛ ቁጭቶችም በጊዜ በዘመንና በህይወቲቱ ላይ ጥርሳቸውን ነክሰው ከእንግዲህ አልወድቅም የሚሉበት ታዛ በራሱ የጥንካሬ መንፈስን ናፋቂነትና ቅናት የሚያሳድሩ ናቸው። በዚህም ገጣሚው የተመስጥኦ ፍጆታዎቹ ብዬ ከብዙ በጥቂቱ ከለቀምኳቸው ጉዳዮቹ ውስጥ ዝምታ  አንደኛው ሲሆን፤ ለኪነ ጥበብም ሆነ ለመኖር ብስለት በርግጥም በዝምታ ውስጥ የታሸች መንደር ህይወት ናት።
ማኅሌታዊነት
“የዱር አበባ” ጥዑማዊ የሌት ትዝታዎች ፣ የሌት ዝማሬዎች የአበባ ገላቸውን የበተኑበት አይነት ሜዳ ነች። ማህሌታዊ አቋቋሟ ልጅነት ነው። ውበት ነው። ስስነት ነው። «ጠበሏ አፋፍ በጨረቃ.. » እንዳለው ፀጋዬ፣ የዱር አበባንም በሌት አምባ የሚያስወጣት ብዙ መዝሙሮች ፣ ብዙ መናፈቆች ፣ ብዙ ትዝታዎች አሏት።
ናፍቆት የወለደው ትኩስና ገር ፍቅር፣ በርጋታ የታሸው ከበቢ ውስጥ እየተትጎለጎለ የሚወጣው የዝምታ እጣን ፣ ካሸለቡ ግዑዝ ተፈጥሮ ጋር በነፃነት በደስታ መስከርና ሌላም ሌላም የሌት ማኅሌቶቹ ውስጥ የሚታዩ ድምፀቶች ናቸው።
ከርዕሶቹ ጀምሮ ብንነሳ
- የሌሊት ሹክሹክታ
- የሌት ወራጅ ሀሳብ 1 , 2 , 3
- የአንድ ምሽት ሀሳብ
የሚሉ እና ብዛት ያላቸው ሌሊት አወዳሽ ስንኞች በመፅሐፉ ውስጥ በብዛት ይታያሉ።
በዚህም ግጥሞቹ ማኅሌት የቆሙ ኮከቦች ይመስላሉ። መቋሚያ ፅናፅሉ ናፍቆት ሲሆን እሳት እሳት የሚሉ አበባማ ስንኞች ውስጥ ወዙን እንደ ሉባንጃ እየበተነ ማሂጠንቱን ይቋጥራል።
እንደከርቤ ውብ ጉም
እንደሎሚ ሽታ
አበባ እንዳየ ንብ
እኔ እወድሻለሁ...
(ገ/ክርስቶስ ደስታ )
እንደመውጫ፡- አበባን ከስነ ዓለማዊ አተያይ (cosmological outlook) በመነሳት እንመልከትና ላብቃ፦
ልክ እንደ እሳት ሁሉ አበባ በ cosmological point of view (የስነ ዓለም አተያይና ትርጓሜ )  ውስጥ በርካታ ፍቺዎችን ያዘለ ነው። ስነ ህይወታዊ ዝግመተ ለውጥን በተመለከተ አበቦች ( የአበባ ተክሎች ) የመራቢያ አወቃቀሮች ሲሆኑ፤ በዝግመተ ለውጥ ሂደት ውስጥ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወቱ ይነገራል። የመራቢያና የጄኔቲክ ልዩነትን በማመቻቸት የአበባ ብናኞችን ይስባሉ። ይህ የህይወት ትስስርንና በአፅናፈ ሰማይ ውስጥ ያለውን የዝግመተ ለውጥ እንዲሁም የመላመድ ሂደቶችን ሊያመለክት ይችላል።ይህንንም ተከትሎ የህይወት ኡደት እና ሽግግር ሌላኛው ምልከታ ሲሆን፤ በዚህ ውስጥ አበቦች ብዙ ጊዜ ለአጭር ጊዜ የሚቆዩ ናቸው። (ምናልባትም ይሄን ይሆን ህይወት የዱር አበባ ያለን? )
 ይህ በአፅናፈ ሰማይ ውስጥ ላለው ጊዜያዊ ተፈጥሮ ተምሳሌታዊ አሀድ ሆኖ ሊያገለግል ይችላል።
በዚህም የልደት ፣ የእድገት ፣ የመበስበስ እና የመታደስ ጭብጦችን ያሳያል።
 እኒያን የልጅነት ወቅት አበቦች
 የጣዕም ወራት ጣዕሞች ፤
እኒያን ፣... ትናንሽ ክንፎች
 ትናንሽ ለስላሽ ላባዎች ፤
እኒያን ፣...
 ደማም ከንፈሮች
 ስኳር ስኳር ፤ የሚሉ ልቦች ፤
እኒያን ፣...
የፀዳል ሳቆች
 አንፀባራቂ ራቁቶች ፤
ማደግ ... ወዴት ወሰዳቸው!?
(ገፅ 56)
 ከዚህም ባሻገር አበባ በሰው ልጅ የባህል ታሪክ ውስጥ የተለያዩ ትርጉሞችን ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ለአብነት ያህል እንደ ውበት፣ ፍቅር እና መንፈሳዊነት ያሉ ጥልቅ ፅንሰ ሀሳቦች በአበባ ይወከላሉ። በስነ ዓለማት ዳራ መሰረት፤ ትርጉምንና ትስስርን ለማግኘት የሚደረጉ ሙከራዎችን ያንፀባርቃል።
የዓይኔን ልቦናዬን ፤
ቅንድቤን
 ከንፈሬን
 ልቤን
 ኩላሊቴን
 :
ተመልከተኝ እኔን
ገላው የረገፈ አበባ መሆኔን!
(ገፅ 80)
በአበባነት መፈከሪያ ተደርገው የሚቆጠሩት እነኚህ የህይወት ዘለላዎች በመድብሉ ውስጥ ከፍተኛ ቦታ ተሰጥቷቸው በአጀብ ሰፍረው ይታያሉ። ገጣሚው ህይወትን በአበባ ቅንጣት ይመስላታል። ቀጥሎም እሳትን ያስከትለዋል።
በግሌ ቴዎድሮስ ካሳ በዚህ መድበሉም ሆነ ባልታተሙ ግጥሞቹ ከሎሬት ፀጋዬ ገብረ መድህን ጋር ህይወትን ፣ ፍጥረትን ፣ ጊዜን ፣ ሰውነትንና መሰል ጉዳዮችን የሚያይበት መንገድ ተቀራራቢነቱ የዘውድና የጎፈር አይነት የመገላበጥ የእድሜ ልዩነት ይመስለኛል።
በርግጥ ፀጋዬ እሳት ሲል ከላይ በፈከርነው መሰረት ውድመትና ጥፋትን (አብዮት) አይነት የሞት ጥላዎችን ሲሸሽ፣ ቴዎድሮስ በበኩሉ፣ ልክ እንደ ወፊቱ (ፊኒክስ ) በመቃጠል መሻገርን (ዳግመ ውልደትን) ናፋቂ ሆኖ እናገኘዋለን።
መፅሐፊቱም ለገበያ የዋለችው በመጨረሻዋ የህዳር ቅዳሜ በመሆኑ ከህዳር መታጠን ጋር ተቃጥሎ በመጪዎቹ ወራት ውስጥ ለመታደስ ይሆናል ብለን እንጠርጥር ! ካልጠረጠርን ምኑን ሀበሻ ሆንን!?
ይሁኔ በላይ «ገላጋይ» በሚለው የበዕውቀቱ ስዩምን ግጥም ተውሶ በዘፈነው አንድ ዘፈን «በአንድ ዱር ይበቅላል ብትርና አበባ» የምትል ስንኝ አለች። ሰውን ከዱር አበባነት ከመሰልነው ዘንድ ከአበባው ይልቅ በትሩ ባሳደደን የቁጭት ድምፅ ውስጥ ፤ ሳይቀጠፉ መርገፍን በህይወት ላይ መተከዝ ሆኖ አግኝቼዋለሁ።
«ኧረ ወይኔ ህይወት! »
በተለይ ይህን መድበል በማነብበት ወቅት (በ1985 ይመስለኛል) ታትሞ ለአንባቢ የቀረበው የአንጋፋው ደራሲ አዳም ረታ መፅሐፍ ከሆነው ማህሌት ውስጥ «የአበቦች ታሪክ» የሚለውን አጭር ፅሁፍ እያስታወስኩ መቃበዜን አንባቢ ተረድቶ በሽግግር እንዲጋበዝልኝ ስል በውል ባልጠይቅም እሺ ለሚለኝ ግን አልሽኮረመምም።



  አንድ ባለፀጋ ሊሞት ሲል ኑዛዜ ማድረግ ፈለገና፣ ሦስቱንም ልጆቹን ጠርቶ ከመናዘዙ በፊት አንድ ጥያቄ አቀረበላቸው።
“ለመሆኑ ወፍ ለመሆን የምትችሉ ቢሆን ኖሮ፣ የትኛዋን ዓይነት ወፍ ለመሆን ትፈልጋላችሁ?” በመጀመሪያ የመለሰው ታላቅየው ልጅ ነበር። እሱም፤ “እኔ ሁልጊዜ እየቀማችና እየዘረፈች የምትኖረውን ጩልሌ መሆን ነው የምፈልገው” አለ።
ሁለተኛው ልጅ- “እኔ ሸመላ የምትባለውን የወፍ ዓይነት ለመሆን ነው የምፈልገው። ሸመላ ከባልንጀሮቿ ጋር በማህበር በአንድነት ሆና ትበርራለች። እኔም እንደዚህ ማድረግ እወዳለሁ” አለ።
ሦስተኛው ልጅ- “እኔ ዝዬ ለመሆን ነው የምፈልገው። ይህቺ ወፍ ረዥም አንገት ያላት ናት። አንዳች ነገር ለመናገር ባሰብኩኝ ጊዜ ከልቤ እስከማወጣው፣ ይህን ረዥሙን አንገት እስኪያልፍ ድረስ ብዙ ጊዜያት አገኛለሁ” አለ።
አባትዬው ሁሉንም መልስ ካዳመጠ በኋላ፣ ጩልሌ ለመሆን ለተመኘው ልጅ፤ “ሰላምና የሀቀኝነት ሥራ ባለበት አገር ያለኝን ርስቴን በሙሉ አውርሼሃለሁ። በሸፍጥ ለመቀመጥ አይመችህምና።”
ሸመላ ለመሆን ለተመኘውና በማህበራት ለመኖር ላሻው ልጁ፤ “ስምምነት የሌለበትና የጦርነት አገር በሆነው የአገራችን ክፍል ያለኝን ርስቴን ሁሉ አውርሼሃለሁ። በዚህ የሚኖሩ አውሬዎችና ቂማቸውን በእኛ ላይ ሊወጡ የሚፈልጉ ክፉዎች ሲመጡ ታበርድልናለህና።”
ለሦስተኛው ልጅ እንዲህ አለው፤ “አንተ ብልህና ጥንቁቅ በመሆንህ ውርስ አያሻህም። የሚበቃህንና የሚያስፈልግህን በጥበብህና በበሳል ተግባርህ ልታገኘው ትችላለህ”
ውሎ አድሮ ይህ ሦስተኛ ልጅ የአገር መሪ ሆነ።
***
ብልህ መሪ ማግኘት መታደል ነው። ቀማኛና ጩልሌ መሪ ማግኘት መረገም ነው። ብልህ መሪ ሸፍጥ አያጠቃውም። ብልህ መሪ በአስተዋይነቱ ለመምራት እንጂ በብልጥነቱ አታሎ እንደ መንጋ ለመንዳት አይሻም። ብልህ መሪ፤ አውሬዎችንና ቂማቸውን በእኛ ላይ ሊወጡ የሚፈልጉ ክፉ ሰዎችን ሁሉ እንደየአመጣጣቸው ይመልሳቸዋል- እንደየብልህነታቸው ድል ይመታቸዋል። ብልህ መሪ አስቦ ይናገራል። እንደ ዝዬ አንገተ- ረዥም ስለሆነ የልቡን ለመናገር ጊዜ ይወስዳል። አመዛዝኖ እንጂ በግልፍተኝነት፣ አጢኖና አርቆ- አስቦ እንጂ ከአፍንጫው ባልራቀ መንገድ ጊዜያዊ ድልን ለመጎናጸፍ ብሎ የችኩል መልስ አይሰጥም። በራሱም ጥበብና ዕውቀት ይተማመናል እንጂ በቡድኑና በወገኑ ግፊት ዘራፍ አይልም። እንዲህ ያለ በሳል መሪ ያገኘ ህዝብ፣ የፖለቲካ ፓርቲ፣ ተቋም ወይም ድርጅት በለስ የቀናው ነው! እጁን ታጥቦ የሠራው እንዲሉ። ሁሌ በትላንት መመካትና በትላንት መታበይ አያዋጣንም።” በጠቅል ጊዜ ያልተማረ
 ማዘኑ አይቀርም እያደረ” ማለት ዕውነትነት ቢኖረውም እንኳ፣ በዚያ ተገልግለን ፍሬ ካላፈራን፣ የዛሬን ትምህርት ከመቆርቆዝ አናድነውም። ያኔ ያኔ ነበር። ዛሬ ዛሬ ነው። ከያኔዎቹ በከፊልም ለዛሬ መቆርቆዝ አዋጥተዋል። ያባት ዕዳ ለልጅ ነውና!
የታሪክ የመጨረሻ ክፋቱ፤ በተደገመ ቁጥር የበለጠ ዋጋ ማስከፈሉ ነው- ይላሉ። በሀገራችን መንግሥታት በተቀያየሩና ነባሩ ፈርሶ፣ መጪው ተወልዶ አንገቱ እስኪጠና ድረስ ምንጊዜም አንድ ጠባብ የመንሸራሸሪያ ኮሪደር ሳይፈጠር ቀርቶ አያውቅም። ይህ ኮሪደር በሁለት የታፈኑ ክፍሎች መካከል እንዳለ የመተንፈሻ ቦታ ያለ ነው። ይህ የመተንፈሻ ቦታ ትክክለኛ ሳንባ ያላቸው ብቻ አየር የሚወስዱበትና አረፍ፣ ሰከን ብለው የሚተነፍሱና የሚያስቡበት ነው። ይህ የመተንፈሻ ቦታ ከአብዮት ወይም ከአንዳች ዓይነት መንግስታዊ ለውጥ በኋላ “ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ” “የሽግግር መንግስት” (Interim)፣ “መረጋጊያ ኮሚሽን”፤ “የዕውቀትና የእርቅ ኮሚሽን” (Truth and Reconciliation Commission) እንደማለት ነው። ይህ ኮሪደር ከጦርነት በኋላ ፋታና እፎይታ ሲገኝ የቆሰለውን ለማከም፣ የፈረሰውን ለመገንባት፣ የሞተውን ለመተካት፣ የባሰበትን ለመገላገል፣ ካሣ ፈላጊው ገድሉን ለመደርደር፣ ተሿሚው  ቢሮውን ለማጠን፣ ነጋሲው ዘውድ  ለማማረጥ የሚያገኘው የመተንፈሻ ቦታና ጊዜ እንደማለትም ነው። ፓርቲዎች ተፈረካክሰው፣ ድርጊቶች አብጠው ፈንድተው እንደገና መልካቸውን ለማበጀት፣ ራሳቸውን ደግመው ለመሥራት ሲሞክሩ፣ የተሳሳተው ሲያቀረቅር፣ ያልተሳሳተ የመሰለው “ያለ እኔ ማን አለ!” በማለት ቀና ቀና ሊል ሲቃጣው፣ አይሞቀኝ አይበርደኝ ባዩ ደግሞ አንዴ ከረባት ሊያስር፣ አንዴ ቁልፉን ሊፈታ ሲያኮበኩብ፣ በመካከል የሚገኝ የአየር ጊዜ፣ የመተንፈሻ ሰዓት ነው። ይህ ወቅት “ምን ይቀጥል ይሆን?” በሚልና አብዛኛው ሰው በግምት ይህ ይሆናል፣ ያ ይፈርሳል፣ ያ ይሾማል፣ ያ ይወርዳል፣ ያ ባለበት ይረግጣል የሚልበት ጊዜ ነው። በቦታውና በሰዓቱ ፈጦ እስኪመጣ ድረስ፣ ዕውነቱ ግን መካከል ተቀምጦ የሚስቅበት ሁኔታ ይፈጠራል።
(We all dance around and guess
The truth, sits in the middle, and laughs.
እንዲል ሮበርት ፍሮስት።)
በሀገራችን የፋታ ጊዜ ወይም የመተንፈሻ ኮሪደርን በአግባቡ የተጠቀምንበት ወቅት ነበር ለማለት አያስደፍርም። በገጠመን የመተንፈሻ ጊዜ ሁሉ ለአሸናፊው በማጨብጨብ፣ አሊያም ከተሸናፊው ጋር ሙሾ በማውረድ የምናጠፋው ዕድል ቁጥር-ስፍር የለውም። “በጣም አንጣላ፤ ከታረቅን እንዳይቆጨን” የሚለውም፤ “ከመታህ ድርግም፣ ከዋሸህ ሽምጥጥ!” የሚለውም “አምሳም ታለበ መቶ ያው በገሌ” የሚለውም፣ “አፌ ዝም ብሎ እጄን ይጎራረሱበታል” የሚለውም… ሁሉም የየራሱን ዘፈን በማዳመጥ ጊዜውን ያሳልፍና ኋላ ብልጡ ሲብለጠለጥበት ፀጉሩን ይነጫል። አምባገነኑ “ለምሳ ያሰቡንን ለቁርስ አረግናቸው” ሲለው “ዋ ነዶ!” እያለ ማድቤት የተሰቀለ ጭስ የጠጣ ጠመንጃ እንደነበረው ይተርካል። የጀግና አገር እንደነበረው በቁጭት ያወሳል። ሁሉም ካለፈ በኋላ! ራሱን እስኪነካው ድረስ ሌላው ተሸወደ ብሎ በኩራት ይስቃል። “የኔ ድንግል ሲጠፋ ሰው አልሰማም። የሷ ግን የባሰ ነው፤ አደባባይ ወጣ!” አለች፤ እንደተባለችው ልጃገረድ፤ አሟሟትንና አወዳደቅን በማወዳደር መገበዝ እንደ ገድል ተቆጥሮ የነበረበት ጊዜም ጥቂት አይደለም።
በጊዜያዊና ዘላቂ መንግሥት መካከል፣ በጊዜያዊና ዘላቂ ዓላማ መካከል፣ በጊዜያዊና ዘላቂ ሰው መካከል የመተንፈሻ ቦታ፣ የመሸጋገሪያ ኮሪደር አለ፣ ነበረ፣ ይኖራል። አገር የሚገነባው ይህን ዐይነቱን ሥፍራ ልብ በማለትና ትኩረት በመስጠት ነው። ብልጥ መሪ ሄዶ ብልህ መሪ እስኪገኝ፣ አፍአዊ አለቃ ተወግዶ ልባም አለቃ እስክናፈራ፣ ለቋሳ ፓርቲ ፈርሶ ጠንካራ ፓርቲ እስኪተባ፣ ጊዜው የደረሰ ተሰናብቶ ጊዜው ያልደረሰ እስኪተካ፣ ስግብግብ ምሁራዊ አመለካከት እስኪከስምና ጥልቀት ያለው ደግ አስተሳሰብ እስኪናኝ፣ ረጋና ሰከን ብሎ አገርንና ህዝብን የሚያስብ ዜጋ መኖር ይኖርበታል። ከአድልዎና ከሙስና ከዘፈቀደ አመራር የሚወጣው፣ ከተንሸዋረረም፣ አንደኛውን ዳፍንተኛ (Obscurant) ከሆነም አተያይ ለመዳን የሚቻለው በመማር፣ በማስተዋልና በቅንነት በማሰብ ነው። ለሀገር የሚበጅ ረብ- ያለው ዕውቀትና ሙያ ሳይጨብጡና ስለ ነገ አንዳችም ራዕይ ሳይዙ፣ በግምገማ ኃይል ብቻ ሌላውን እያወረዱና እያዋረዱ መጓዝ ሁሌ አይመችም። ሁሉን ለምዕራብ አማልክት ትቶም ብሔራዊ ህልውና አይገኝም። ለኃያላን ተስያለሁ፤ ከእገሌ ተዋውያለሁ፣ ከእገሌ ተማምያለሁ፣ በእገሌ መጀን ብያለሁ፣ ቢሉ የራስ አገራዊ የሰው ኃይል በተቀናጀ ንጣፍ ላይ ካልተገነባ፣ የራስን አቅም በአግባቡ ለመጠቀም ካልተቻለና የራስን መተማመን ካልፈጠሩ፣ የውጪው ትርፍ ነው። ዋናውን ይዞ ይሄዳል እንጂ ዋና አይሆንም። ደካማ አገር፣ ከደካማ አገር፣ ውሽልሽልን ከውሽልሽል አቆራኝቶ ለማቆም ምንም ዓይነት ማሰሪያ ገመድ አይገኝም። አብሮ ለመውደቅ ያግዝ እንደሁ እንጂ እውነተኛ ህብረት አይፈጥርም። ቴሌዎች “የኬብል ብልሽት” የሚሉት ዓይነት ሳይሆን አይቀርም።
ከወፍ ወፍ ይለያልና ጭልፊቱን፣ ሽመላውንና ዘዬውን ያልለየ ህዝብ ምኔም ከችግር አይወጣ። ሁሌም ከአደጋ አያመልጥም። ብስለትና ብልህነት እጅግ ወሳኝ ነው። ብልጥ መሪ በዕለት በዕለቱ ጉዳይ ዐይንን ያውራል። ሞኝ መሪ በጭፍንና በእልህ ገደል ይከታል። በብልጥ አትሞኝ፣ በሞኝ አትመራ የሚባለው እንግዲህ ለዚህ ነው!

 መንግሥት በጃል ሰኚ ነጋሳ ከሚመራው የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ጋር የተፈራረመውን ስምምነት ለሕዝብ ግልጽ እንዲያደርግ ፓርቲዎች ጠየቁ፡፡ ፓርቲዎቹ በጋራ ባወጡት መግለጫ፤ “በአዲስ አበባ የተለያዩ አካባቢዎች የዘለቀው ተኩስ በሰላም ስምምነት የመጣ ሳይሆን፤ ሆን ተብሎ የሕዝብን ሥነ ልቡና ለመስለብና ለማስፈራራት የተደረገ ነው” ብለዋል።
መኢአድ፣ ኢሕአፓ፣ አማራ ግዮናዊ ንቅናቄ እና እናት ፓርቲ በጋራ  መግለጫቸው ላይ በሰጡት ማብራሪያ ከዚህ ቀደም   የመንግስት ከፍተኛ አመራሮችና ኦነግ በፈጸሙት ግልጽነት የጎደለው ስምምነት ሳቢያ፣ ከመንግስት በኩል ቃል የተገባለት እንዳልተፈጸመ የገለጸው የኦነግ አንደኛው ክንፍ፣ ተመልሶ ጫካ መግባቱን አውስተዋል። ይህን ተከትሎም፣ በአገር ላይ በተለይም  በኦሮሚያ ክልል አለመረጋጋት ሰፍኖ ለዓመታት መዝለቁን አመልክተዋል።
ከሰሞኑ መንግስት “ኦነግ ሸኔ” በማለት ከሚጠራው እና በጃል ሰኚ ነጋሳ የኦሮሞ ነጻነት ጦር አንደኛው ወገን ጋር የሰላም ስምምነት መፈረሙን ያስታወቁት ፓርቲዎቹ፣ ስምምነቱን “መጥፎ ሰላም የለም” በማለት መቀበላቸውን በመግለጫቸው ላይ አትተዋል። ስምምነቱን ተከትሎ  በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢዎች ለሦስት ቀናት የዘለቀ ተኩስ ሲሰማ መቆየቱን በመግለጽ፤ “በተኩሱም እስከ አሁን አንዲት እናት በጥይት ተመትተው ሕይወታቸው ማለፉን አረጋግጠናል።” ብለዋል።
የሰላም ስምምነቱ ጥርጣሬ እንዳጫረባቸው የጠቆሙት ፓርቲዎቹ፤“ጥርጣሬያችን የሚነሳው ከስምምነቱ ግልጸኝነት ማጣት ብቻ ሳይሆን፤ ከእንዲህ ዓይነት ክስተቶች ጭምር ነው።” ብለዋል። “ስምምነቱ መሳሪያ ማውረድን አይጨምርም ወይ?” ሲሉ የሚጠይቁት ፓርቲዎቹ፤ በሂደቱ ዙሪያ የግልጽነት አለመኖርና የሰላሙ ዘላቂነት በእጅጉ እንደሚያሳስባቸው ተናግረዋል፡፡
የሰላም ስምምነቱ ሂደትና ዝርዝር ነጥቦች ለሕዝብ ይፋ እንዲደረጉ የጠየቁት አራቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ “በአዲስ አበባ የተለያዩ አካባቢዎች የዘለቀው ተኩስ በሰላም ስምምነት የመጣ ሳይሆን ሆን ተብሎ የሕዝብን ስነ ልቡና ለመስለብና ለማስፈራራት የተደረገ ነው” በማለት አስረድተዋል። በተኩሱ ምክንያት መገናኛ አካባቢ ለተገደሉት እናት መንግስት “ሃላፊነት ወስዶ” ቢያንስ ቤተሰባቸውን ይፋዊ ይቅርታ እንዲጠይቅና ተገቢውን ካሳ እንዲከፍል ጠይቀዋል።
በተያያዘ ዜና፣ ኢዜማ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ከታጠቁ ሃይሎች ጋር የደረሰበትን የሰላም ስምምነት ቅርጽና ይዘት ለሕዝብ ግልጽ እንዲያደርግ ኢዜማ ባለፈው ሰኞ ህዳር 30 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ጠይቋል። “ታጣቂዎቹ ወደ ከተማ ሲገቡ በተለያዩ ቦታዎች  ተኩስ ማሰማታቸው በንጹሃን ዜጎች ላይ ከፍተኛ ስጋትና የስነ ልቦና ጫና የሚያሳድር፣ አግባብነት የሌለው ተግባር ነው“ ሲል ፓርቲው ኮንኖታል።
በሁሉም ቦታዎች ተኩስ እንዲቆምና መንግስት ክስተቱን አጣርቶ ለሕዝብ እንዲያሳውቅ የጠየቀው ኢዜማ፤ወደ ከተማም ሆነ ወደ ተሃድሶ ስልጠና የሚገቡ ታጣቂዎች ትጥቃቸውን ለጸጥታ አካላት አስረክበው ሊሆን ይገባል” ብሏል፤ በመግለጫው፡፡


በርካታ ኤርትራውያን ስደተኞች የኮንትሮባንድ ንግድን ጨምሮ በሌሎች ሕገ ወጥ ተግባራት መሰማራታቸው ተነግሯል። የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት እንደገለጸው፣ ስደተኞችን ወደ ሕጋዊ መንገድ ለማስገባትና ለመመዝገብ በተደጋጋሚ ጥሪ ቢያደርግም፣ ተመዝግበው ወደ ህጋዊ ስርዓቱ የገቡ ግን በጣም ጥቂት ናቸው ብሏል።
አገልግሎቱ ትናንት ታህሳስ 4 ቀን 2017 ዓ.ም. በሰጠው ማብራሪያ፣ ከኤርትራ ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡ ኤርትራዊያን ለ9ዐ ቀናት ያለቪዛ ክፍያ በቀን ማህተም ገብተው እንዲቆዩ ማድረጉን አውስቶ፣ “በሁለቱም ህዝቦች ያለው ግንኙነትና ወንድማማችነት ለማጠናከር ምን ያህል ቁርጠኛ አቋም እንዳለው ለመገንዘብ ይቻላል” ብሏል። አያይዞም፣ በርካታ ኤርትራውያን በሕገ ወጥ መንገድ ወደ አገር ውስጥ በመግባትና በሕጋዊ መንገድ ገብተው ከተፈቀደላቸው የጊዜ ገደብ በላይ በመቆየት በሕገ ወጥ መንገድ እየተንቀሳቀሱ እንደሚገኙ አመልክቷል።
ተቋሙ ኤርትራውያኑን ወደ ሕጋዊ መንገድ ለማስገባትና ለመመዝገብ በተደጋጋሚ ጥሪ ቢያደርግም፣ ተመዝግበው ወደ ህጋዊ ስርዓቱ የገቡ ግን “በጣም ጥቂት ናቸው” ብሏል። “በርካታ የኤርትራዊ ዜግነት ያላቸው ዘመድ ለመጠየቅ በማስመስል ከዱባይ፣ ከኤርትራና ከኡጋንዳ በመመላለስ የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦች በሻንጣ በማስገባትና በማስወጣት የኮንትሮባንድና ሌሎች ህገወጥ ተግባራት ሲያከናውኑ ተገኝቷል” ሲልም አብራርቷል።
ኤርትራውያኑ በተለያዩ አገራት ከሚገኙ ሌሎች ሕገ ወጥ ደላሎች ጋር በመተሳሰር በርካታ ስደተኞችን በሕገ ወጥ መንገድ ሲያዘዋውሩ መገኘታቸውን ተቋሙ አስታውቋል። ለተለያዩ ሕገ ወጥ ተግባራት የሚያገለገሉ ሐሰተኛና የተጭበረበሩ የጉዞና የይለፍ ሰነዶች፣ ማህተሞች፣ የባንክ ሂሳብ ደብተሮች በማዘጋጀትና በመጠቀም ህገ-ወጥ ተግባራት ሲፈጽሙ፣ የተለያዩ ሐሰተኛ ሰነድና ማንነት በመጠቀም ህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር ሲያከናውኑ እና ከህግ ውጭ ሰነዶችን ሲጠቀሙ መገኘታቸውንም ተቋሙ በማብራሪያው ላይ ገልጿል።
በመሆኑም ማንኛውም የውጭ አገር ዜጋ የአገሪቱን ሕግ ተላልፎ ከተገኘ በሕግ ተጠያቂ እንደሚሆን የጠቀሰው የኢሚግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት፣ በተለያዩ መገናኛ ብዙሃን አማካይነት በኤርትራውያን ስደተኞች ላይ ያለአግባብ ክፍያ እንደሚጠየቁና ዲፖርቴሸን እንደሚፈጸምባቸው ተደርጎ መዘገቡ ከእውነት የራቀ መሆኑን ነው ያመለከተው።

• ለአዲስ የትብብር ምዕራፍ ትልቅ እርምጃ ነው ተብሏል

ኢትዮጵያና ሶማሊያ በቱርኩ ፕሬዚዳንት ሬሴፕ ጣይብ ኤርዶጋን አደራዳሪነት፣ ከስምምነት ላይ መድረሳቸው ተገለጸ፡፡ ሁለቱ አገራት በትላንትናው ዕለት በአንካራ ለሦስተኛ ጊዜ ባደረጉት ድርድር ለአንድ ዓመት የዘለቀ ዲፕሎማሲያዊ ፍጥጫቸውን በስምምነት ፈትተዋል ነው የተባለው፡፡

ትላንት ረቡዕ ታህሳስ 2 ቀን 2017 ዓ.ም፣ ከ8 ሰዓታት ውይይት በኋላ የተደረሰው ስምምነት፤ በሁለቱ የአፍሪካ ቀንድ ሀገራት መካከል ዳግም ሰላምና ትብብር እንዲሰፍን መንገድ እንደሚከፈት ይጠበቃል።

ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድና የሶማሊያው ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ ማሃሙድ በቱርክ አደራዳሪነት ለሚደረገው የሦስተኛው ዙር ድርድር አንካራ የገቡ ሲሆን፤ ባለፈው ሀምሌና ጥቅምት ወር የተደረጉ የድርድር ጥረቶች ውጤት አለማምጣታቸው ይታወቃል፡፡

የቱርኩ ፕሬዚዳንት ሬሴፕ ጣይብ ኤርዶጋን ከድርድሩ በኋላ በጋራ በሰጡት መግለጫ፤ ስምምነቱን ለአዲስ የትብብር ምዕራፍ ትልቅ እርምጃ ነው ብለውታል፡፡

"ይህ ስምምነት በጋራ መግባባትና በጋራ ግቦች ላይ የተመሰረተ አዲስ ዘመን መጀመሩን ያመለክታል" ያሉት ኤርዶጋን፤ ስምምነቱ የሶማሊያን ሉዓላዊነት በማክበር፣ የኢትዮጵያን አሳሳቢ የባህር በር ፍላጎት እንደሚፈታ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።

በጋዜጣዊ መግለጫው ወቅት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፣ ኢትዮጵያ እርግጠኛና አስተማማኝ የባህር በር እንደምትፈልግ አፅንኦት የሰጡ ሲሆን፤ ስምምነቱን፣ የውጥረት ዓመት ወደ አዲስ አጋርነት የተቀየረበት ነው ሲሉ ገልጸውታል።

"ይህ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለጎረቤቶቻችንና በአጠቃላይ ለአካባቢው ሁሉ የሚጠቅም ነው" ሲሉም ጠ/ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

ፕሬዚዳንት መሀሙድ በበኩላቸው፤ ስምምነቱ ለልዩነቶቻቸው መፍትሔ የሰጠ ሲሉ በማወደስ፣ የሶማሊያን የትብብር ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል፡፡ “ወደፊት የጋራ ብልጽግናን ለመገንባት ከኢትዮጵያ አመራርና ህዝብ ጋር ለመስራት ዝግጁ ነን” ብለዋል፤ፕሬዚዳንቱ፡፡

ለዚህ ታሪካዊ ስምምነት የቱርክ የሽምግልና ሚና ወሳኝ ነበር ተብሏል፡፡ ኤርዶጋን በግል የሦስቱንም ዙር ድርድሮች ተከታትለዋል፡፡ የእርሳቸው ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች በአፍሪካ ቀንድ ውስጥ እያደገ የመጣውን የቱርክን ተፅእኖ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፤ አገሪቱ በአካባቢው መረጋጋትን በማስፈን ረገድ ቁልፍ ሚና እየተጫወተች ነው፡፡

• 7ሺ የሚደርሱ የዩኒቨርሲቲና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ጎብኝተውታል


የአውሮፓ ህብረት ከኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የ2017 ዓ.ም የአውሮፓ የከፍተኛ ትምህርት ኤግዚቢሽን፣ ባለፈው ሰኞ ህዳር 30 እና ታህሳስ 1 ቀን 2017 ዓ.ም በኮተቤ ዩኒቨርሲቲ የተካሄሰ ሲሆን፤ 7ሺ የሚደርሱ የሁለተኛ ደረጃና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንደጎበኙት አዘጋጆቹ ገለጹ፡፡

በኤግዚቢሽኑ መክፈቻ ላይ የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ አምባሳደር ሶፊ ፉሮም ኤምስበርገር፣ የኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ብርሃነ መስቀል ጠና፣ የአውሮፓ ህብረት አምባሳደሮችና ከፍተኛ የመንግሥት ሃላፊዎች ተገኝተው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡

ለሁለት ቀናት በተካሄደው የከፍተኛ ትምህርት ኤግዚቢሽን፤ ቤልጂየም፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ሀንጋሪ፣ስፔይንና ፖርቹጋልን ጨምሮ አስር የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራትና ሦስት የአውሮፓ የትምህርትና ሥልጠና ተቋማት የሚሰጧቸን የከፍተኛ ትምህርት ዕድሎች ለጎብኚዎች አስተዋውቋል፡፡

የትምህርት ኤግዚቢሽኑ ዓላማ የአውሮፓ አባል አገራትና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማቶቻቸው ለኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ያዘጋጇቸውንና የሚሰጧቸውን የነጻ ትምህርት ዕድሎች (ስኮላርሺፕ) ማስተዋወቅና ግንዛቤ መስጠት ነው ተብሏል፡፡ በዚህም ረገድ የዘንድሮ ኤግዚቢሽን የታለመለትን ግብ መምቱን አዘጋጆቹ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

የአውሮፓ የከፍተኛ ትምህርት በአውሮፓ ህብረት በአዲስ አበባ ሲዘጋጅ የዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን፤የመጀመሪያው ኤግዚቢሽን የዛሬ 5 ዓመት፣ በ2012 ዓ.ም በስካይላይት ሆቴል ነበር የተካሄደው፡፡

የአውሮፓ ህብረት፤ የኢትዮጵያን ትምህርት ከሚደግፉ የልማት አጋሮች ግንባር ቀደሙ ሲሆን፤በያዝነው የ2017 ዓ.ም ለ57 ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ሙሉ የማስተርስ ዲግሪ የኤራስመብ ሙንደስ ነጻ የትምህርት ዕድል መስጠቱ ይታወቃል፡

የቀድሞው ታዋቂ አክቲቪስትና ፖለቲከኛ ጃዋር መሃመድ የጻፈው፣ “አልጸጸትም” የተሰኘ ግለ ታሪክ (Memoir) መጽሐፍ በመጪው ሳምንት ሐሙስ ታህሳስ 10 ቀን 2017 ዓ.ም፣ በኬንያ ናይሮቢ ይመረቃል፡፡ መጽሐፉ በአማርኛና ኦሮሚፋ ቋንቋዎች ነው የተዘጋጀው፡፡

ጃዋር ሞሃመድ የታዋቂው የኦሮምኛ አቀንቃኝ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያን ተከትሎ፣ ለእስር መዳረጉ የሚታወስ ሲሆን፤ ከእስር በተፈታ ማግስት ኢትዮጵያን ለቅቆ በመውጣት፣ መኖርያውን በኬንያ ናይሮቢ ማድረጉ ይታወቃል፡፡

በአጭር ጊዜ ውስጥ በሥራዎቿ ተወዳጅነትን ባተረፈችው ደራሲ ህይወት ተፈራ የተፃፈው “ተድባብ” የተሰኘ ታሪካዊ ልብ ወለድ መፅሐፍ ከሰሞኑ ለገበያ ቀረበ። በዋልያ መፃሕፍት የታተመው ይህ ታሪካዊ ልብ-ወለድ፤ ጭብጡን በአድዋ ጦርነትና ድል ዙሪያ ያደረገ ነው፡፡
ደራሲዋ ከአንባቢያን ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ የተዋወቀችው “ማማ በሰማይ” በሚል ወደ አማርኛ በተተረጎመው “Tower in the sky” በተሰኘ የበኩር መጽሐፏ ነው፡፡ ለጥቃም “ሃሰሳ” በሚል የተተረጎመ “Mine twin” እና “ምንትዋብ” የተሰኙ ታሪካዊ ልብወለዶችን ለአንባቢያን አድርሳለች፡፡ ከሰሞኑ ለንባብ የበቃው “ተድባብ” ታሪካዊ ልብ ወለድ  ለደራሲዋ አራተኛ ሥራዋ መሆኑ ነው።
“ተድባብ” ለደራሲ ህይወት ተፈራ አራተኛ ሥራዋ ነው

ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳንና ታንዛኒያ የኤሌክትሪክ ኃይል ለመሸጥ በዝግጅት ላይ መሆኗን  የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር አቶ ሀብታሙ ኢተፋ ትናንት ማምሻውን አስታውቀዋል።

ኢትዮጵያ ላለፉት ዓመታት ለሱዳን፣ኬንያና ጅቡቲ የኤሌክትሪክ ኃይል ስትሸጥ የቆየች ሲሆን፤ አሁን ደግሞ ለደቡብ ሱዳንና ታንዛኒያ ለመሸጥ በዝግጅት ላይ መሆኗ ተነግሯል፡፡

ኢትዮጵያ፣ ኬንያንና ታንዛኒያን የሚያገናኘውን 400 ኪሎ ዋት የኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ መስመር በቅርቡ ባጠናቀቀችው  ኬንያ በኩል፣ ኢትዮጵያ ለታንዛኒያ የኤሌክትሪክ ኃይል እንደምታቀርብ ይጠበቃል፡፡

የምስራቅ አፍሪካ ፓወር ፑል  (ኢኤፒፒ) ስብሰባ ከትናንት ጀምሮ በኬንያ ሞምባሳ  እየተካሄደ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ ተወካይ የኃይል አቅርቦቱን ስምምነት  ለማጠናቀቅ ከታንዛኒያና ኬንያ አቻዎቻቸው ጋር እየተወያዩ መሆኑ ታውቋል፡፡

 ኢኤፒፒ በምስራቅ አፍሪካ በሚገኙ 11 ሀገራት የኤሌክትሪክ ሃይሎቻቸውን ለማገናኘት የተቋቋመ ሲሆን፤ ብሩንዲ፣ የኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ፣ ግብፅ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ሱዳን፣ ታንዛኒያ፣ ሊቢያ፣ ጅቡቲና ኡጋንዳ የኢኤፒፒ አባል ናቸው።

አማራ ባንክ  የባለ አክስዮኖች 3ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን በዛሬው ዕለት በሚሊኒየም አዳራሽ ያካሄደ ሲሆን፤ የባንኩ  አጠቃላይ ሀብት 35.2 ቢሊዮን ብር መድረሱን አስታውቋል፡፡

አማራ ባንክ ባለፉት ዓመታት ተግዳሮቶች ቢገጥሙትም፣ ዘንድሮ  669 ሚሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን ይፋ አድርጓል፡፡  

ባንኩ ለደንበኞቹ  የሚሰጠውን የብድር መጠን 33 በመቶ በማሳደግ  20 ቢሊዮን ብር ገደማ ማድረሱን ያስታወቀ ሲሆን፤ አጠቃላይ የተቀማጭ ገንዘብ መጠኑ  26 በመቶ አድጓል፡፡  የመደበኛና ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት በድምሩ 25 ቢሊዮን ብር መድረሱንም  አመልክቷል፡፡

በተጨማሪም የባንኩ ዓመታዊ ገቢ 146 በመቶ ዕድገት በማሳየት፣ 4.4 ቢሊዮን ብር ገቢ አስመዝግቧል።

ከ1.8 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችና ወደ 600 ሺ የሚጠጉ የሞባይል ባንኪንግ ተጠቃሚዎች ያሉት  አማራ ባንክ፤ የደንበኞቹ  ብዛት እያደገ መምጣቱን አስታውቋል።

በተደራሽነት ረገድም በበጀት አመቱ 143 አዳዲስ ቅርንጫፎችን በመላ አገሪቱ በመክፈት አመርቂ እድገት ያስመዘገበ ሲሆን፤  አጠቃላይ የቅርንጫፎቹን ቁጥርም 310 አድርሷል፡፡

Page 11 of 752