
Administrator
”አዲስ ገና 2017 ኤክስፖ“ የፊታችን አርብ ይከፈታል
• ኤክስፖው በኤግዚቢሽን ማዕከልና በመስቀል አደባባይ ይካሄዳል
• አዘጋጁ ጨረታውን ያሸነፈው በ80ሚ.600ሺ ብር ነው
• መኖሪያ ቤት የሚያሸልም የሎተሪ ዕጣ ተዘጋጅቷል
ሮበስት ቢዝነስ ግሩፕና ሠላሳ መልቲ ሚዲያ ከንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ”አዲስ ገና 2017 ኤክስፖ“፤ የፊታችን አርብ ታሕሳስ 4 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከልና በመስቀል አደባባይ ይከፈታል፡፡
የገና ኤክስፖን በተመለከተ አዘጋጆቹ በዛሬው ዕለት ረፋዱ ላይ በስካይላይት ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
በመግለጫው ላይ እንደተነገረው፤ የዘንድሮው የገና ኤክስፖ ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከልና በመስቀል አደባባይ በጥምረት ይካሄዳል፡፡
በገና ኤክስፖው ላይ ከ500 በላይ የሚሆኑ የአገር ውስጥ አምራች ፋብሪካዎች፣ የኢንዱስትሪ መንደሮች፣ ትላልቅ አስመጪዎች፣ ማህበራትና ዩኒዬኖች፣ የሪል እስቴት አልሚዎች፣ የፋይናንስ ተቋማት፣ የኤሌክትሪክ መኪና አቅራቢዎችና ከስምንት የተለያዩ አገራት የተውጣጡ የውጭ ኩባንያዎች ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡
የበዓል ኤግዚቢሽኖች የሚዘጋጁበት አንዱ ዓላማ ገበያውን ለማረጋገት እንደሆነ ያስረዱት አዘጋጆቹ፤ በአንድ የ20 ሊትር ዘይት ላይ እስከ 400 ብር ቅናሽ ተደርጎ ለሸማቹ እንደሚቀርብ ጠቁመዋል፡፡ ሌሎች የዕለት ተዕለት ፍጆታዎችም በፋብሪካ ዋጋ ለሽያጭ እንደሚቀርቡ ተነግሯል፡፡
እስከ ታሕሳስ 28 ቀን 2017 ዓ.ም ለ25 ቀናት ክፍት ሆኖ በሚዘልቀው የገና ኤክስፖ የተለያዩ መዝናኛዎች እንደሚኖሩ የተገለጸ ሲሆን፤ 100 ተወዳጅ ድምጻውያን ከአምስት የሙዚቃ ባንዶች ጋር ታዳሚዎችን እንደሚያዝናኑ ታውቋል፡፡
የተለያዩ የህጻናት መጫዎቻዎችን ያካተተ “የህጻናት ዓለም” መዘጋጀቱም በመግለጫው ላይ ተጠቁሟል፡፡ ለልጆች በተዘጋጀው የጌም ዞን፤ የዳይኖሰሮች ትርኢት፣ የግመልና ፈረስ ሽርሽር፣ የገና ጨዋታና የህጻናት የገና ስጦታዎች እንደሚኖሩም ታውቋል፡፡
በዚህ ኤክስፖ ላይ የፌስቲቫል ድባብ ለመፍጠር የተለያዩ ጥረቶች መደረጋቸውንም አዘጋጆቹ አብራርተዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አንዱ ትልቁ የገና ዛፍ ሲሆን፤ ሌላው 2017 ስኒዎችን የሚይዝ ትልቅ ረከቦት ነው ተብሏል፡፡
”አዲስ ገና 2017 ኤክስፖ“ን ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ህዝብ ይጎበኘዋል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፤ የመግቢያው ዋጋ 100 ብር እና 200 ብር መሆኑን አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡
በዘንድሮው የገና ኤክስፖ ከብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር ጋር በመተባበር የመኖሪያ ቤት የሚያሸልም የሎተሪ ዕጣ መዘጋጀቱም ታውቋል፡፡
ሮበስት ቢዝነስ ግሩፕ የአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ለገና በዓል ያወጣውን ጨረታ ያሸነፈው በ80 ሚሊዮን 600 ሺ ብር ሲሆን፤ ይህም በማዕከሉ ታሪክ ከፍተኛው የጨረታ ዋጋ መሆኑ ታውቋል፡፡
የአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ሃላፊዎች በመግለጫው ላይ በሰጡት ማብራሪያ፤ ማዕከሉ ለገና በዓል ባወጣው ግልጽ ጨረታ ከ5 በላይ ተወዳዳሪዎች የተሳተፉ ሲሆን፤ በመጨረሻም ሮበስት ቢዝነስ ግሩፕ ጨረታውን በከፍተኛ ዋጋ አሸንፏል፡፡
“አንድም ከቀበሮ፤ አንድም ከአንበሳ ተማር” አንበሳ ከወጥመድ ለማምለጥ አይችልም። ቀበሮ ደግሞ ከተኩላ ለማምለጥ አትችልም። ወጥመዱን ለማየት ቀበሮ ሁን። ተኩላ እንዳይጠጋህ አንበሳ ሁን።
ማኪያቬሊ (ጣሊያናዊ የታሪክ ባለሙያ፣ የሀገር መሪ፣ እና የፖለቲካ ፍልስፍና አዋቂ)
አንድ ጊዜ እንዲህ ሆነ።
የዱር አራዊት ንጉሥ አንበሳ ታሞ አልጋ ላይ ዋለ። ጠያቂና አስታማሚ አጣ። ከህመሙም በላይ ጠያቂ ማጣቱ በጠናበት ጊዜ፣ ለአሣማና ለዶሮ በደብዳቤ መልዕክት ላከ። እንዲህ ብሎ፡-
“ውድ አሳማ!
ውዲት ዶሮ!
እነሆ ካመመኝና አልጋ ከዋልኩ አያሌ ወራት ሆኑኝ። እህል ከቀመስኩ ደግሞ ሣምንት አለፈኝ። ዞር ዞር ብዬ የሚበላ ፈልጌ እንኳ አፌ እንዳላረግ ህመምተኛ ሆንኩ። አቅሜም ደከመ። የሰው ልጆች አንበሳ ሲያረጅ የዝምብ መጫወቻ ይሆናል፤ የሚሉት የዋዛ አነጋገር አይደለም። ዱሮ የሚሰግዱልኝ፣ የሚሽቆጠቆጡልኝና ከሥሬም የማይጠፉ ብዙ አውሬዎች ዛሬ አንዳቸውም አጠገቤ ያሉ አይመስሉም። አንዳንዱ ያለወትሮው ዝምተኛ ሆኗል። በአንፃሩ አንዳንዱ፣ ምንም ፍሬ ጠብ አይለውም እንጂ፤ አፍ ለቆበታል። አንዳንዱ እኔ ካልኖርኩ የማይኖር ይመስል በፍርሃት ተውጦ ተደብቆ ይተኛል። ሌላ ቀርቶ፣ አይምሬውን ክርኔን የቀመሱት፣ ሳገሣ ድራሻቸው ይጠፋ የነበሩት እነ አያ ጅቦ፣ እነ አያ ከርከሮ፣ እነ ብልጢት ጦጣ፣ ዛሬ አልጋዬ ድረስ መጥተው እንኳ ለመጠየቅ ንቀት አደረባቸው። እንዲያውም “አንበሳ ከታመመ፣ የልብ ወዳጅ ከጠመመ፣ መመለሻ የለውም” እያሉ እየረገጡ አላገጡብኝ አሉ። በዙሪያዬ የነበሩት ሁሉ “አምላክ አንተንም እኛንም እኩል ነው የፈጠረን” ማለት ጀምረዋል። ይሄ ቀን የማያልፍና፣ ከታመምኩት በሽታ ድኜ፣ ካልጋ ቀና የማልል መስሏቸው ነው። እንግዲህ የቀራችሁኝ ውድ ወዳጆች እናንተና ይህን ደብዳቤ ይዞላችሁ የመጣው ዝንጀሮ ብቻ ናችሁ። ስለዚህ አደራ ሳልሞትባችሁ ድረሱልኝ።”
ፊርማ የማይነበብ
የናንተው አንበሳ፣
የጥንቱ የጠዋቱ የዱር አራዊት ንጉሥ
አሳማና ዶሮ ደብዳቤው እንደደረሳቸው በጣም አዘኑ።
“ምን ብናደርግለት ይሻላል?” አለ አሳማ።
ዶሮም፤ “መቼም ነግ በእኔ ማለት ደግ ነው። አንድ ነገር ማድረግ አለብን”
አሳማ፤ “ግን አያ አንበሶን እንዲህ እስኪማረር ድረስ ያደረሱት እነማን ይሆኑ?”
ዶሮ፤ “ዛሬ ማን ይታመናል ብለህ ነው አሳምዬ? የልብ ወዳጅ የታለና? ያው እሱ ራሱ የጠቃቀሳቸው በጣም ቅርብ ቅርብ ያሉ ባለሟሎች እነ አያ ጅቦ፣ እነ እመት አህያ፣ እነ አቶ በቀቀን፣ እነ ጆሮ-ትላልቄ ይሆናሏ።”
አሳማ፤ “አትይኝም? ጆሮ.. ትላልቄም ጨከነበት?”
ዶሮ፤ “እየነገርኩህ! ባለንበት ዘመን፣ የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ማንም አይተኛም”
አሣማ፤ “ዕውነትሽን ነው። በይ እኛም ሳይረፍድ የምንይዘውን ይዘን ሄደን እንጠይቀውና ይውጣልን”
ዶሮ፤ “እንዲህ እናድርግ። እኔ እንቁላል ላዋጣ። አንተ ደግሞ ስጋ አዋጣና ሃምበርገር ይዘንለት እንሂድ”
አሣማ፤ “በጣም ድንቅ ሃሳብ አመጣሽ። በቃ ሀምበርገር እንውሰድለት”
በዚሁ ተግባቡና ጠዋት ወደ አንበሳው ሊሄዱ ተስማምተው ተለያዩ።
ጥቂት እልፍ እንዳሉ ግን፤ አሣማ አንድ ነገር ትዝ አለውና ዶሮዋን ጠራት። ከዚያም “ስሚ አንቺ ዶሮ፤ አሁን እናዋጣ የተባባልነው፤ ሚዛናዊ መዋጮ አይደለም። እኔ ተበድያለሁ!”
ዶሮም ነገሩ ስላልገባት፤ “ለምን? እንዴት ነው ሚዛናዊ ያልሆነው?”
አሳማም፤ “አየሽ፤ አንቺ ዕንቁላሉን የምታዋጪው ወልደሽው ነው። እኔ ግን ሥጋ እምሰጠው ከገዛ አካሌ ቆርጬ ነው። ያንቺ ተሳትፎ ብቻ ነው (Participation እንዲሉ)። የእኔ ግን ጉዳዩ ውስጥ በአካል መግባት ነው (Involvment እንዲሉ)” አላት።
***
ህመም፣ ችግርና ሣንካ ሲያጋጥመን ወዳጅ አይክዳ። እንደ አረጀ አንበሳም የዝምብ መጫወቻ ከመሆን ይሰውረን። ከፍሬ-ቢስ ልፈፋ ያውጣን። በእኩልነት የማያምን “ዲሞክራት መሪ” አያጋጥመን።
በአገራችን ውስጥ ያሉ የፖለቲካ ሰዎች ሚና፣ ጉዳዩ ውስጥ የመግባት እንጂ ዕንቁላል የመጣል ተሳትፎ ብቻ እንዳይሆን የሁሉም ወገን ጥረትና ትግል ሊኖርበት ይገባል። በሀገራችን የፖለቲካ ውጣ - ውረድ ውስጥ አያሌ አንበሶች ታይተዋል። ሆኖም የአንበሳነታቸው መጠንም ሆነ አንበሳዊ ባህሪያቸው፤ የተለያየ ሆኖ እናገኘዋለን። አንዳንዱ በጭራሽ ሌላ ፍጡር አያስጠጋም። ንፁህ ነው እንኳ ቢባል። ዲ.ኤች.ሎረንስ እንዳለው ነው፡- “አንበሳን ማንም ኃይል፤ ከበግ ግልገል ጋር ሊያስተኛው አይችልም። ግልገሏ ሆዱ ውስጥ ካልገባች በስተቀር።” አንዳንዱ ደግሞ ቀን ሲጨልምበት ወይም እክል ገጥሞት ከአልጋ ሲውል በቀላሉ የሚደፈር ይሆናል። ሆራስ የተባለው የዜማና ምፀታዊ ግጥም ፀሀፊና ታዋቂ ሮማዊ (ከክርስቶስ ልደት በፊት በ65-ዓመት)፤
ታሞ ልትጠይቀው፣ ሄዳ ወደ አንበሳ
ቀን- አይታ ቀበሮ፣ ነገር ልታነሳ
እንደዚህ አለችው፣ በሰላ ወቀሳ
“ጌታው አቶ አንበሶ፤
የእግር-ጥፍር አሻራህ፣ ያስፈራኛል በጣም፤
ግን ምስሉ ይገርማል፤ መሬት ላይ ሲታተም
ወደ ራስህ ዞሮ፣ አንተኑ ሲጠቁም።
ከያዘው አቅጣጫ እንደማይመለስ፣ አሳምሬ ባቅም
የእግር- ጥፍር አሻራህ፣ ያስፈራኛል በጣም።
ከሄደበት መንገድ፣ ወደኔ ባይመጣም።”
ብሎ እንደፃፈው ነው።
አንዳንዶቹ፤ በ19ኛው ክ/ዘመን አጋማሽ የነበሩት የአርጀንቲናው ፕሬዚዳንት በአንድ ወቅት “በአሁኑ ሰዓት ሰላማዊ አብዮተኛ (Pacifist Revolutionary ማለት) አትክልት-በል አንበሳ Vegetarian Lion ማለት ነው” ብለው እንደገለጹት ዓይነት ናቸው።
በአገሬው ዐይን ሌላ፣ በአለም አቀፍ ማህበረሰብ ዐይን ሌላ፣ የሆኑም አሉ። ሩሲያዊው ደራሲ ሶልዘንስቲን እንደሚለው፤ “ለእኛ ሩሲያ ውስጥ ላለነው፤ ኮሙኒዝም የሞተ ውሻ እንደማለት ነው። ለብዙ ምዕራባውያን ግን በህይወት ያለ አንበሳ ይመስላቸዋል” ማለት መሆኑ ነው።
ሌሎች አንበሶች ደግሞ፤ ዊንስተን ቸርችል 80ኛውን የልደት በዓላቸውን ሲያከብሩ ለሁለቱም ምክር ቤቶች እንደተናገሩት፤ “አገሬ የአንበሳ ልብ አላት። እኔ ደግሞ እንደዳልጋ አንበሳ መጮህን ታድያለሁ”፤ የሚሉ ናቸው።
በኢትዮጵያ የፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ውስጥ ሁሉ ያየናቸው የፖለቲካ ፓርቲም ሆነ የብዙኃን ንቅናቄ መሪዎች አንድ የጋራ ጠባይ አላቸው። ይህንን ፀባይ አፍሪካዊው የስዋሂሊኛ ተረት በደንብ ይገልጠዋል፡- “የተቆለመመ ጥፍር ያላቸው ሁሉ አንበሳ አይደሉም”።
ትላንት በተካሄደውም ሆነ ዛሬ በአገራችን እየተካሄደ ባለው ፖለቲካዊ ሂደት ውስጥ የሚጓዙ ኃይሎች ሁሉ መማርና ማወቅ ያለባቸው አንድ ቁም ነገር አለ፡-
“አንድም ከቀበሮ፤ አንድ ከአንበሳ ተማር”
አንበሳ ከወጥመድ ለማምለጥ አይችልም።
ቀበሮ ደግሞ ከተኩላ ለማምለጥ አትችልም።
ወጥመዱን ለማየት ቀበሮ ሁን።
ተኩላ እንዳይጠጋህ አንበሳ ሁን።
ኢህአፓ የገዢው ፓርቲ የ5 ዓመት ጉዞ ኪሳራ ነው አለ
ባለፉት አምስት ዓመታት ገዢው ፓርቲ ተገምግሞ ከስሯል ሲሉ የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ተቀዳሚ ምክትል ሊቀ መንበር መጋቢ ብሉይ አብርሃም ሃይማኖት ተናገሩ።
መጋቢ ብሉይ አብርሃም ሃይማኖት ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ የብልጽግና ፓርቲ የአምስት ዓመታት ጉዞ ሲገመገም፣ የህግ የበላይነትን በማስከበርና ኢኮኖሚውን በማሳደግ በኩል ድክመት ማሳየቱን ገልፀዋል። “ከኮሪደር ልማትና ከሚያብለጨልጩ ነገሮች ውጪ ለሕዝባችን ጠብ የሚል አዲስ የኢኮኖሚ ለውጥ አልታየም” ሲሉም ተችተዋል።
በከፍተኛ የዋጋ ንረት ሳቢያ፣ ዜጎች የዕለት ጉርሳቸውን ማግኘት አለመቻላቸውን የሚገልፁት የኢህአፓ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር፤ በጥቅሉ አሁን ላይ ያለው ወጣት ተስፋ መቁረጡን ይናገራሉ።
የጸጥታና ሰላም ጉዳይን በተመለከተ የሕግ የበላይነት አለመከበሩን የጠቆሙት መጋቢ ብሉይ፤ “ሕገ መንግስታዊ መብቶች ጭምር እየተናዱ ነው።” ብለዋል። በመንግስትነት የሚያስተዳድረው ብልጽግና ፓርቲ፤ ሕገ መንግስቱን አክብሮ ማስከበር ሲገባው፣ እሱም አላከበረውም፤ ማስከበርም አልቻለም” ሲሉም ነቅፈዋል።” በተጨማሪም፣ ፓርቲው አገራዊ ችግሮችን ለመቅረፍ የሚጠቀመው ብቸኛ አማራጭ ጦርነት ብቻ ነው። ሲሉም ትችታቸውን ሰንዝረዋል።
“ብልጽግና ፓርቲ በጉልበት እንጂ በፖለቲካዊ ውይይትና ንግግሮች መፍትሔ ለማምጣት ሲንቀሳቀስ አልታየም። ከብዙ ዕልቂት በኋላ፣ የተወሰነ ነገር ይጀምርና በሁሉም ቦታ ላይ ተግባራዊ ስለማይሆን በአንድ ቦታ ግጭት ጋብ ሲል፣ በሌላ ቦታ እንደገና ያገረሻል።” ይላሉ፣ መጋቢ ብሉይ አብርሃም።
ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ ገዢው ፓርቲ ተገምግሞ ከስሯል ያሉት የኢሕአፓ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀ መንበር፤ ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ባለፈው ቅዳሜ፣ በዓድዋ መታሰቢያ ሙዚየም በተካሄደው የብልጽግና ፓርቲ አምስተኛ ዓመት የምስረታ በዓል የማጠቃለያ ፕሮግራም ላይ ለተፋላሚዎቻቸው “ሺህ ዓመት ቢታገሉንም አያሸንፉንም” ሲሉ መናገራቸው ጦርነት እንደሚፈልጉና በተቃራኒ ጎራ የሚገኙ ለሺህ ዓመት ትግል እንዲያካሂዱ ምክረ ሃሳብ እንደሰጡ የሚያስቆጥርባቸው ነው ብለዋል።
“ከአንድ አገር የሚመራ ፓርቲ ይህ ንግግር አይጠበቅም። ጉልበትና አቅሙ ቢኖረውም እንኳ፣ ችግሮችን በሰላም እንዲፈቱ ነው ማድረግ ያለበት፤ ምክንያቱም የአገር ውስጥ ችግሮች ተባብሰው ውስጣዊ አንድነት ከሌለ፣ ለጠላት በሮች ክፍት ይሆናሉ። አገርም ለከፍተኛ አደጋ ትጋለጣለች።” ብለዋል፣ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀ መንበሩ። “ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፖለቲካዊ ጥያቄዎች በውይይትና ድርድር መፈታት እንደሚችሉ ነው መናገር የነበረባቸው” ብለዋል።
በሚቀጥለው ዓመት ብሔራዊ ምርጫ የሚደረግ ቢሆንም፣ በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎች ግጭቶች በመከሰታቸው ሳቢያ የፓርቲያቸው እንቅስቃሴ መገደቡን የተናገሩት መጋቢ ብሉይ አብርሃም፤ በተለይ፣ በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች ማደራጀትና እንቅስቃሴ ማድረግ እንዳልተቻለ ገልፀዋል።
በአዲስ አበባ ከተማም ፓርቲያቸው በመንግስት በሚደርስበት ጫና ሳቢያ ጠቅላላ ጉባዔውን ለማድረግ አለመቻሉን የጠቆሙት መጋቢ ብሉይ አብርሃም፤ የፖለቲካው ምህዳር መጥበቡን የሚያሳዩ ከበቂ በላይ አብነቶች መጥቀስ ይቻላል ብለዋል።
ገዢው ፓርቲ ያለፉትን አምስት ዓመታት በጥልቀት ገምግሞ ከስሕተቶቹ በመማር ከቻለ አሁን የሚታየውን ችግር እንዲቀርፍ ያሳሰቡት ፖለቲከኛው፤ ሁሉንም ችግር በጉልበት ለመፍታት ከማሰብ ይልቅ በፖለቲካዊ መፍትሔዎች ላይ ማተኮር እንደሚያስፈልግ መክረዋል። “ለሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ምቹ ምህዳር መፍጠርና ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን ማስፋት ብልጽግና ፓርቲ የሚሰጠን ልዩ ስጦታ አይደለም፤ መብታችን ነው” የሚሉት ተቀዳሚ ምክትል ሊቀ መንበሩ፣ “ኢትዮጵያ አሁን እየሄደችበት ባለው መንገድ ከቀጠለች፣ የመፍረስ አደጋ ይጋረጥባታል” ብለዋል።
“በአሁኑ ወቅት በስቃይና በመከራ ላይ የሚገኘው ሕዝብ ብሶቱን ሲያቀርብ አለመናቅና ዝቅ ብሎ ማዳመጥ እንጂ በተለያየ መንገድ ለመሸወድ መሞከር ጥሩ ውጤት አያመጣም። “ያሉት የኢህአፓ አመራሩ፤” ችግሩ በፍጥነት መፍትሄ ካልተበጀለት እየሰፋ ሄዶ ብልጽግና ፓርቲንም ጭምር ሰለባ የሚያደርግ ቀውስ ሊፈጠር ይችላል”ሲሉ አሳስበዋል።
የመምህራን ማሕበሩ በማህበራዊ ሚዲያ የሥራ ማቆም አድማ መጠራቱን አላወቅም አለ
“በሥራ ማቆም አድማው የሚጎዳው አገርና ትውልድ ነው”
በተለያዩ የማህበራዊ ትስስር ገጾች በመላ አገሪቱ የሚገኙ መምህራን ከታሕሳስ 1 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ የስራ ማቆም አድማ እንዲያደርጉ የተሰራጨውን ጥሪ እንደማያውቅ የኢትዮጵያ መምሕራን ማሕበር አስታወቀ። “ወቅቱን ያገናዘበ የደመወዝ ጭማሪ ይከፈለን” በሚል የሥራ ማቆም አድማው በማህበራዊ ሚዲያ መጠራቱን ለማወቅ ተችሏል።
የኢትዮጵያ መምህራን ማሕበር ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አበበ ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ፤ ከሰሞኑ ብቻ ሳይሆን በየጊዜው የሥራ ማቆም አድማ እንዲደረግ የተለያዩ ጥሪዎች እንደሚቀርቡ ጠቁመው፣ አሁን የተጠራውን የስራ ማቆም አድማ ግን ማህበራቸው እንደማያውቀው ገልፀዋል።
የደመወዝ አለመከፈል፣ የደሞዝ መቆረጥ፣ የመምህራን እስርና የመሳሰሉት ችግሮችን ዕልባት ለመስጠት ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር እየተነጋገሩ መሆኑን የገለጹት የማህበሩ መሪ፤ ባለፈው ጥቅምት ወር በአዳማ ከተማ የማህበሩ ምክር ቤት ባካሄደው ስብሰባ ላይ የመንግሥት አካላት ተገኝተው፣ በመምህራን የሚቀርቡ ቅሬታዎችን እንዲያውቁ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ፣በዚሁ ስብሰባ ላይ በጉልህ የተነሱ ሃሳቦችን በውሳኔ ሃሳብና በአቋም መግለጫ መልክ በማጠናቀር፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤትን ጨምሮ ወደ 11 ገደማ ለሚሆኑ የፌደራል መስሪያ ቤቶች እንዲሁም መላኩንም ጠቁመዋል፡፡
አያይዘውም ፤የደረጃ ዕድገትና የትምሕርት ማሻሻያ፣ ውዝፍ ክፍያዎችን፣ እንዲሁም የሁለትና ሦስት ወር ደመወዝ ያልከፈሉ አካባቢዎች የትኞቹ እንደሆኑ ለማጣራት የመረጃ ማሰባሰብ ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ ምክትል ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል። በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የደመወዝ አከፋፈል ላይ ችግሮች እንደሚስተዋሉ የጠቆሙት ምክትል ፕሬዚዳንቱ፤በተለያዩ ምክንያቶች የመምህራን ደመወዝ እንደሚቆረጥም ገልፀዋል።
“ለመምህራኑ ደመወዝ መቆረጥ እንደ ምክንያት የሚቀርበው ደግሞ ‘ለልማት’ የሚል ነው” ያሉት አቶ ሽመልስ፤ በዚያ ላይ መምህራን ደመወዛቸው እንዲቆረጥ ፈቃደኛ መሆናቸው አይጠየቅም” ብለዋል። “የደመወዛቸውን መቆረጥ ተከትሎ የመማር ማስተማር ሂደቱ ይስተጓጎላል። ምክንያቱም መምህራኑ መብታቸውን ለማስከበር የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን ያደርጋሉ” ሲሉ አስረድተዋል። እነዚህን እንቅስቃሴዎች በማረጋጋት፣ መምህራን ስራቸውን እንዲሰሩ ከማስቻል ባሻገር፣ ማሕበሩ የመንግስት አካላት፣ ያለመምህራን ፈቃደኝነት ደመወዝ ከመቁረጥ እንዲታቀቡ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ለአብነት ያህል በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ ኮሬ ዞን፣ ሳርማሎ ወረዳ ከመምህራን ደመወዝ 25 በመቶ መቆረጡን ተከትሎ የወረዳው ባለስልጣናት ጥያቄ ያነሱ 66 መምህራንን በጸጥታ ሃይሎች አማካይነት ሕዳር 11 እና 12 ቀን 2017 ዓ.ም. በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ማድረጋቸውን አቶ ሽመልስ ያወሳሉ። ማህበሩ የእነዚህ መምህራን ጉዳይ መረጃው እንደደረሰው፣ ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ጋር በመነጋገር፣ እንዲሁም የማሕበሩ ተወካዮችና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች ቦታው ድረስ በመገኘት የታሰሩት መምህራን ከእስር እንዲፈቱ ለማድረግ መቻሉን ተናግረዋል።
በሌላ በኩል፣ የዩኒቨርስቲ መምህራን “የፌደራል ተቋም ሰራተኞች ናችሁ” ተብለው የቤት መስሪያ ቦታ በሚሰጥበት የመኖሪያ ቤት ፓኬጅ ተጠቃሚ አለመሆናቸውን ያነሱት ምክትል ፕሬዚዳንቱ፤ ማሕበራቸው አገልግሎቱ ለዩኒቨርስቲ መምህራኑ መሰጠት እንዳለበት በማሳሰብ፣ ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ደብዳቤ እንደጻፈ ገልጸዋል። ከትርፍ ሰዓት ሥራ ጋር በተገናኘም ጥያቄዎች እንደሚነሱ አቶ ሽመልስ ጠቅሰዋል፡፡
“የዩኒቨርስቲ መምህራን ‘ደብል ታክሴሽን (Double Taxation) እየተተገበረብን ነው’ ይላሉ። በመጀመሪያ መደበኛ ደመወዛቸው ታክስ ይደረጋል። የትርፍ ሰዓት ስራ ሲሰሩ ደግሞ፣ በዚያው ስራ ያገኙት ክፍያ ታስቦ በተጨማሪነት ታክስ ይደረግባቸዋል። በዚህም ምክንያት ደመወዛቸው ተቆራርጦ ለመምህራኑ የሚደርሳቸው ገቢ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም። አብዛኛው ለታክስ የሚውል ነው።” በማለት ያስረዳሉ፤ አቶ ሽመልስ። ማሕበራቸው ይህ የታክስ አሰራር ትክክል አለመሆኑን ተገንዝቦ አቋም እንደወሰደበትም ጠቁመዋል።
“ከመምህራን እኩል እየወጣን እየወረድን ችግሮችን ለመፍታት በመንቀሳቀስ ላይ ነን” ያሉት የማሕበሩ ምክትል ፕሬዚዳንት፤ “በማሕበራዊ ሚዲያ ላይ እየተላለፈ ባለው የስራ ማቆም አድማ ጥሪ የሚጎዳው አገርና ትውልድ ነው።” ብለዋል። “መምህራን ሥራ አቁመው ወደዚህ ያልተገባ ተግባር ይገባሉ ብዬ አላስብም” ሲሉም ግምታቸውን ገልፀዋል።
ከሰሞኑ በማሕበራዊ ትስስር ገጾች ላይ የተጠራውን የመምህራን የሥራ ማቆም አድማ ማሕበራቸው እንደማያውቀውም አቶ ሽመልስ አክለው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
በትግራይ የግሪሳ ወፍ መንጋ በብዛት መከሰቱ ተገለጸ
ብዛታቸው ከ4-5 ሚሊዮን ይደርሳሉ ተብሏል
በትግራይ ክልል የግሪሳ ወፍ መንጋ በብዛት መከሰቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ የገለጸ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት ብዛታቸው ከ4-5 ሚሊዮን እንደሚደርሱ አመልክቷል፡፡ የቢሮው የሕዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ሚኪኤለ ምሩጽ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ ግሪሳ ወፍ በአጎራባች ክልሎች እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን፣ የግብርና ሚኒስቴር የመከላከል ስራዎችን እንደሚሰራ ስለሚገመት በትግራይ ከፍተኛ ችግር ይፈጥራል የሚል ግምት አልነበረም ብለዋል። ይሁንና ባለፈው ሳምንት የግሪሳ ወፍ መንጋ በድንገት ወደ ትግራይ ክልል መግባቱን ሃላፊው ገልፀዋል።
“የግሪሳ ወፍ መንጋው መጀመሪያ የገባው በራያ ጨርጨር ወረዳ በኩል ነው” ያሉት አቶ ሚኪኤለ፤ በወረዳው ባጌ ደልቦ በሚባል አካባቢ በሚገኙ የሳቫና እና የአል አሙዲ የግል እርሻዎች ላይ የመጀመሪያ ጉዳት ማድረሱን ጠቁመዋል፡፡ እንደ ክልል የተወሰኑ የመከላከል ቅድመ ዝግጅቶች መደረጋቸውን የገለጹት ሃላፊው፣ አርሶአደሩን የማንቃት ስራ መሰራቱንና በየወረዳው የመከላከል ግብረ ሃይል መቋቋሙን ተናግረዋል።
“የግሪሳ ወፍ መንጋ ወደ ትግራይ ክልል ገና ሲገባ፣ የቢሮው ባለሞያዎች ወደ ስፍራው ተልከው የዳሰሳና ሕዝቡን የማንቀሳቀስ ስራ ሲሰራ ቆይቷል።
የግሪሳ ወፍ መንጋ ብዛቱ መጀመሪያ ላይ አንድ ሚሊዮን እንደሚደረስ ተገምቶ ነበር። አሁን ላይ ግን የግሪሳ ወፍ መንጋው ብዛት ከአራት እስከ አምስት ሚሊዮን ይደርሳል” ብለዋል፣ ሃላፊው፡፡
የግሪሳ ወፍ መንጋው የመራቢያ አካባቢ አፋር ክልል፣ አዋሽ መሆኑን የሚናገሩት አቶ ሚኪኤለ፤ ነገር ግን የወፍ መንጋው ወደ ትግራይ የገባው ከአማራ ክልል ኮምቦልቻና ሸዋሮቢት አካባቢዎች ተነስቶ ነው ይላሉ፡፡ ግሪሳውን ለማባረር በአምቡላንስ የሳይረን ድምጾች ጭምር ታግዞ ከፍተኛ ድምጽ በማሰማት የመከላከል ስራ ሲሰራ መቆየቱን የሚገልጹት የሕዝብ ግንኙነት ሃላፊው፤ ከግብርና ሚኒስቴር በሁለት ቡድኖች የተዋቀሩ ባለሞያዎች ወደ ትግራይ ክልል መምጣታቸውንና ከክልሉ ባለሞያዎች ጋር በመናበብ አብረው እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም፣ ከግብርና ሚኒስቴር የተላኩ አራት መኪናዎች ከእነ ኬሚካል መርጫ መሳሪያዎቻቸው፣ ኬሚካሎችና ባለሞያዎቻቸው ጭምር ወደ ትግራይ ክልል መምጣታቸውንም አስታውቀዋል።
የኬሚካል ርጭት ለማካሄድ ከፍተኛ ዝግጅት ተደርጎ ለአይሮፕላን ማረፊያ የሚሆን ቦታ በመቐለ አካባቢ ለማዘጋጀት ወደ ስራ መገባቱን የገለፁት አቶ ሚኪኤለ፣ በህዳር 21፣ 23 እና 25 ሦስት ጊዜ የኬሚካል ርጭት መካሄዱን ተናግረዋል። “የተካሄደው ርጭት ውጤታማ ነው። ነገር ግን የግሪሳ ወፎቹ ብዛት ከፍተኛ ስለሆነ፣ በቶሎ ሊረግብ አልቻለም። አሁንም ሕብረተሰቡ በመከላከል ስራ ላይ ይገኛል።“ ብለዋል።
ሃላፊው አክለውም፤ የግሪሳ ወፍ መንጋው ከራያ ጨርጨር ተሻግረው ወደ አላማጣ አካባቢ እየገቡ መሆኑንና በግብርና ቢሮ በኩል ወደ አንድ ሺሕ ሄክታር መሬት አሰሳ ተደርጎ፣ 500 ሄክታር መሬት በግሪሳ ወፍ መንጋ ጉዳት እንደደረሰበት መረጋገጡን ጠቁመዋል። ሆኖም ግን በተለያዩ ጉዳዩ በሚመለከታቸው የተለያዩ ተቋማት ጥልቅ ምርመራ ከተደረገበት በኋላ፣ ስለደረሰው ጉዳት ሙሉ መረጃ እንደሚገኝና ይፋ እንደ ሚደረግ አቶ ሚኪኤላ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል።
ዋልታ እና ፋና ተዋህደው ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ተመሰረተ
“የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን መመስረት የመደመር እሳቤ ውጤት ነው”
ሁለቱ በመንግሥት የሚተዳደሩት ዋልታ ሚዲያና ኮሙዩኒኬሽን ኮርፖሬት እና ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት አ.ማ ሰሞኑን በይፋ ተዋህደው ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን አ.ማ ተመሥርቷል፡፡ የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን የማብሰሪያና ሥራ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ህዳር 25 ቀን 2017 ዓ.ም በግራንድ ኤሊያና ሆቴል ተካሂዷል፡፡
ለተመሳሳይ ዓላማ የተቋቋሙት የሚዲያ ተቋማት ውህደት፣ አንድ ግዙፍና ተደራሽ ሚዲያ ለመመስረት ያለመ ነው ተብሏል፡፡ ውህደቱ የፋይናንስ፣ የሰው ሃይል፣ የቴክኖሎጂና የመሰረተ ልማት አቅምን በማቀናጀት የሃብት ብክነትን ማስቀረት እንደሚያስችል የተጠቆመ ሲሆን፤ ከዚህም ባሻገር የተቋማቱ ውህደት ትርፋማነትንና ውጤታማነትን ለማሳደግ እንደሚያግዝ ተገልጿል። የውህደቱ ሒደት አስፈላጊውን ሕግና ሥርዓት ተከትሎ መፈጸሙም ተነግሯል፡፡
የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን የማብሰሪያና ሥራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ ንግግር ያደረጉት በምክትል ጠ/ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ፤ መንግስት ከለውጡ ወዲህ የሚዲያን ጥቅም በመረዳት ሰፋፊ ስራዎች በመስራት ላይ እንደሚገኝ አመልክተዋል፡፡ ሁለቱ ተቋማት የመንግስት ግልጸኝነት እንዲታይ ሰፋፊ ሥራዎችን እንደሰሩ ጠቁመው፤ መንግሥትም ለሚዲያው ትኩረት በመስጠት ተቋማቱ የለውጡ ተጠቃሚ እንዲሆኑ አድርጓል ብለዋል። የመረጃ ተደራሽነት ከፍ እንዲል ማድረግ፣ ብሄራዊ ትርክት ላይ መስራትና ኢትዮጵያ በዓለም ተጽእኖ ፈጣሪ እንድትሆን ማድረግ ከአዲሱ ተቋም እንደሚጠበቅም አደም ፋራህ ገልጸዋል፡፡
የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዶ/ር ለገሰ ቱሉ በበኩላቸው፣ አዲስ የተመሰረተው ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን፣ የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም የሚያስከብር ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ አክለውም፤ ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን በገለልተኝነትና በብቁ የጋዜጠኝነት ሥነ ምግባር፣ ትውልድን በብሔራዊ ማዕቀፍ የሚገነባ፣ የተለየ ተግባር ያለው ትልቅ ሚዲያ ነው ብለዋል።
የጠ/ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር እና የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ቦርድ ሰብሳቢ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ባደረጉት ንግግር፤ ዋልታ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን ኮርፖሬት እና ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተዋህደው የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን መመስረት የመደመር እሳቤ ውጤት ነው ብለዋል፡፡ “በኢትዮጵያ ልክ ኢትዮጵያን መግለጥ ለመቻል በማሰብ ተነጣጥለው ሲንቀሳቀሱ የነበሩት ሁለቱ ሚዲያዎች ተዋህደው አንድ ሆነዋል” ሲሉም አክለዋል፡፡
በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የቀድሞው የዋልታ ሚዲያና ኮሙዩኒኬሽን ኮርፖሬት ዋና ሥራ አስፈጻሚ፣ አቶ መሐመድ ሀሰን፣ በተቋሙ ቆይታቸው ላበረከቱት አስተዋጽኦ የእውቅና ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
በዚህ መርሃ ግብር ላይ በምክትል ጠ/ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ፣ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ለገሰ ቱሉ፣ የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ፣ የሚዲያው አመራሮች፣ የድርጅቱ ሰራተኞች፣ ተባባሪ አዘጋጆች፣ የሚዲያው አጋሮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን አ.ማ፤ ሁለት የቴሌቪዥን ቻናሎችና ሦስት ሬዲዮ ጣቢያዎች እንደሚኖሩት ታውቋል፡፡
የፓስታ ፌስቲቫል ዛሬ በሚሊኒየም አዳራሽ ይካሄዳል
በኢትዮጵያ ሲዘጋጅ ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑ የተነገረለት የፓስታ ፌስቲቫል፤ በዛሬው ዕለት ከረፋዱ 5፡30 ጀምሮ በሚሊኒየም አዳራሽ ይከናወናል፡፡
በካልቸር ክለብ በተዘጋጀው የጣልያን ምግብ ፌስቲቫል ላይ ከ5ሺ እስከ 7ሺ እንግዶች እንደሚታደሙ ይጠበቃል፡፡ በፌስቲቫሉ ላይ ከ23 በላይ የፓስታ ምግብ ሻጮች የተለያዩ ዓይነት የፓስታ ምግቦች፣ ሱጎዎችና ጣፋጮችን እንደሚያቀርቡ ታውቋል፡፡
የመግቢያው ዋጋ 250 ብር ሲሆን፤ትኬቶችን በቴሌብር መግዛት ወይም መግቢያው በር ላይ ማግኘት ይቻላል፡፡
በዚህ ፌስቲቫል ላይ ከግሩም የፓስታ ምግቦች ባሻገር፣ ሙዚቃና ከምግብ ማብሰል ጋር የተያያዙ አዝናኝ ትርኢቶች ይኖራሉ ተብሏል፡፡
“ሚለርስ ፎር ኒውትሪሽን” በኢትዮጵያ ሥራ ጀመረ
ኩባንያው የተመጣጠነ ምግብ እጥረትን ለመቅረፍ እንደሚሰራ ተገልጿል
“ሚለርስ ፎር ኒውትሪሽን” የተሰኘው የውጪ ኩባንያ በኢትዮጵያ የተመጣጠነ የምግብ እጥረትን ለመቅረፍ ስራ መጀመሩን አስታወቀ። ኩባንያው ይህን ያስታወቀው ባሳለፍነው ሳምንት መጀመሪያ ላይ በሃያት ሬጀንሲ ሆቴል ለመገናኛ ብዙኃን በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫና አጠቃላይ ዕቅድና ግቡን ለባለድርሻ አካላት ባስተዋወቀበት የግማሽ ቀን መርሃ ግብር ላይ ነው።
ሚለርስ ፎር ኒውስትሬሽን በተለይ “ሰርቭ” ከተሰኘ የበጎ አድራጎት ማህበር ጋር በመተባበር በኢትዮጵያ የሚታየውን የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ለመቅረፍ ስራ የጀመረ ሲሆን፤ ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ ለ140 ፋብሪካዎች የቴክኒክ ድጋፍ እንዲሁም ለ40 ፋብሪካዎች ደግሞ ስልጠና መስጠት መቻሉን የኩባንያው ሀላፊ ተናግረዋል። የሚለርስ ፎር ኒውትሬሽን የኢትዮጵያ ፕሮግራም ሀላፊ አቶ እያቄም አምሳሉ ጨምረው እንደገለፁት፤ የተመጣጠነ የምግብ እጥረት በሀገር አቀፍ ደረጃ አሳሳቢ መሆኑን አስታውሰው፤ በዚሁ ምክንያት በኢትዮጵያ የሚገኙና እድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች የሆኑ ህፃናት 22 ከመቶዎቹ ከክብደት በታች እንደሚገኙ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት፣ የምግብና የመጠጥ ኢንዱስትሪ ምርምር ልማት ማእከል በቅርቡ ያወጣውን መረጃ በዋናነት አቅርበዋል።
ከላይ የተቀመጠው አሀዝ በኢትዮጵያ ያለውን የምግብ እጥረት በመቅረፍ፣ ጤናማና አምራች ዜጋን ለመፍጠር፣ ሁሉም ባለ ድርሻ አካላት የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባ የሚያሳይ ነው ተብሏል።
ከዚህ አኳያ ሚለር ፎር ኒውትሬሽን፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የተመጣጠነ ምግብ እጥረት በከፍተኛ ሁኔታ ይቀርፋል የተባለ ሲሆን፤ በተለይም የስንዴ ዱቄት አምራችና የምግብ ዘይት ፋብሪካዎችን በቫይታሚን በማበልፀግ እጥረቱን ለመቀነስ እንደሚሰረራ ተናግሯል።
ሚለርስ ፎር ኒውትሪሽን በአፍሪካና በእሲያ እንደሚሰራ የተገለፀ ሲሆንበኢትዮጵያ፣ በኬንያ፣ ናጄሪያ፣ ፓኪስታን፣ ባንግላዲሽን ጨምሮ በጥቅሉ በስምንት ሀገራት እየሰራ ይገኛል።
ባለፈው ሳምንት በተከናወነው የፕሮጀክት ማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የኢትዮጵያ ምግብና መድሃኒት ባለስልጣን ሃላፊዎችን ጨምሮ ሌሎች ባለድርሻ አካላትም ታድመዋል።
ወጣቱ ባለሃብት ከ2 ሚ. ብር በላይ ድጋፍ አደረገ
ባቡል ኬይር በቀን ከ4 ሺ በላይ ወገኖችን ይመግባል
በተለያዩ የበጎ አድራጎትሥራዎች ላይ ገንዘቡንና ጊዜውን በመሥጠት በንቃት የሚሳተፈው ወጣቱ ባለጸጋ ምህረትአብ ሙሉጌታ፤ በዛሬው ዕለት አበበ በቂላ ስቴዲየም አካባቢ ባለው ባቡልኬይር በመገኘት ከ1 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ የ4ሺ ሰው የምሳ ወጪ ሸፍኗል፡፡
ከዚህም ባሻገር፣ ድርጅቱ እየሰራ ያለውን የበጎ አድራጎት ለማገዝ የ1 ሚሊየን ብር ድጋፍ አድርጓል።
ስጦታውን የተረከቡት የድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ ሀናን ማህሙድ ምህረት አብ፣"ዛሬ ሰርፕራይዝ ነው ያደረግኸን፤ ይሄን ያህል መጠን ያለው ድጋፍ ሲደረግልን የመጀመሪያው ነው።" ሲሉ ለባለሃብቱ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
በሀገራችን በራስ ተነሳሽነት በደጋግ ኢትዮጵያውያኖች ከተመሠረቱ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች መካከል ባቡል ኬይር የበጎ አድራጎት ድርጅት አንዱ ሲሆን፤ድርጅቱ ከተመሠረተበት ጊዜ አንስቶ በርካታ አስታዋሽ ያጡ ኢትዮጵያውያንን በመርዳት ላይ ይገኛሉ፡፡ ባቡል ኬይር በቀን ከ4 ሺ በላይ ወገኖችን ይመግባል፡፡
በኢትዮጵያ የሚኖሩትን የውጭ አገር ሰዎችን ያዋረደ ፣ የማይገባም ቃል የተናገረ እንደ ሕጉ በብርቱ ቅጣት ይቀጣል !!!
"የአዲስ አበባ ከተማ ማዘጋጃ ቤት ለሕዝብ ማስታወቂያ"
ከዚህ ቀድሞ በመስከረም 11 ቀን 1928 ዓ.ም በተነገረው አዋጅ እንደሰማችሁት የኢጣልያ መንግሥት በኢትዮጵያ ላይ የአጥቂነት ሥራ በመሥራቱ ኢትዮጵያዊ የሆነ ሁሉ ከተነሣበት ጠላት እንዲከላከል ምንም ቢታዘዝ ጠላት የተባሉት ወሰን አልፈው መሣሪያ ይዘው የወገኖቻችንን የኢትዮጵያን ሰዎች ደም ለማፍሰስ የሚመጡ ኢጣልያኖች ናቸው እንጂ በአዲስ አበባ ከተማም ቢሆን ከከተማ ውጭም ቢሆን በኢትዮጵያ የሰላማዊነት ሥራ እየሠሩ ለመኖር የመጡት አይደሉምና የኢትዮጵያ ሕዝብ በእንግዳ ተቀባይነቱና በአክባሪነቱ ከውጭ አገር ሰዎች ጋራ ተስማምቶ በሳላም በመኖሩ በዓለም የተመሰገነ ስለሆነ ይህ መልካም ስማችን ሳይጠፋ ተከብሮ እንዲኖር ገፍቶ የመጣውን ጠላታችንን ወደድንበራችን ሒደን ለመመለስ ከማሰብ በቀር በመካከላችን እኛን ዘመድ አድርገው በሚኖሩ የውጭ አገር ሰዎች ላይ ማናቸውንም የጠላትነት አሳብ የሚገልጥ ነገር እንዳታደርጉ እናስታውቃለን። አሁን ከኢጣልያን ጋራ በተነሣው ጠብ ምክንያት በማስፈራራት በመጋፋት ወይም የማይገባ ቃል በመናገር ይህን በመሰለ አደራረግ ሁሉ በኢትዮጵያ የሚኖሩትን የውጭ አገር ሰዎች ያዋረደ፥ የማይገባም ቃል የተናገረ እንደ ሕጉ በብርቱ ቅጣት ይቀጣል።
መስከረም 14 ቀን 1928 ዓ.ም
የአዲስ አበባ ከንቲባ
ምንጭ:- ብርሃንና ሰላም ጋዜጣ