Administrator

Administrator

ኮሪያ እስከ ሁለተኛው የአለም ጦርነት ማብቂያ ድረስ የጃፓን ቅኝ ግዛት ነበረች፡፡ የሁለተኛው የአለም ጦርነት በጃፓን ሽንፈት ተጠናቀቀ፡፡ ሽንፈቷን ተከትሎ የጃፓን አገዛዝ በኮሪያ ላይ አበቃ፡፡ አሜሪካን ቻይና እና ታላቋ ብሪታኒያ የካይሮ ስምምነት በመባል የሚታወቀውን ሰነድ አፀደቁ፡፡ የኮሪያ ሰሜኑ ክፍል በሶቪየት ህብረት፤ ደቡብ ክፍል ደግሞ በአሜሪካን የሞግዚት አስተዳደር ስር እንዲቆይ የሚያደርገው ስምምነት ተግባራዊ ሆነ፡፡ ይህ ክፍፍል ዘላቂ ይሆናል ተብሎ የታሰበ ባይሆንም፣ የሁለተኛውን የአለም ጦርነት ማብቃት ተከትሎ አሸናፊዎቹ ሀይሎች የቀዝቃዛው ጦርነት ሰለባ የማድረግ ብቃት ስለነበራቸው የተከናወነ ነበር፡፡ የቀዝ
ቃዛው ጦርነት ሁለት ተቃራኒ ጎራዎች ቀደም ብለው የኮሪያን ሰሜንና ደቡብ በመከፋፋላቸው፣ ኮሪያውያን የቀዝቃዛው ጦርነት ማሟሟቂያ ሆኑ። በ1950 ሰሜን ኮሪያ በቻይናው ማኦ ዜዱንግ እና በስታሊን አለሁ ባይነት ደቡብ ኮሪያን ወረረች። ከሶስት አመት በኋላ በተደረሰ ስምምነት ጦርነቱ አብቅቶ፣ ሰሜን እና ደቡብ  ኮሪያ የሚለው  ክፍፍል ቋሚ ሆኖ ፀና፡፡ የስምምነቱ አካል በሆነው እና የኮሪያን ጉዳይ ለማየት በሚል የተጠራው የጄኔቫ ኮንፈረንስም ምንም እንኳን ከብዙ አገሮች የአንድነት አንጀንዳ ብልጫ እንዲያገኝ ቢሞከርም የኮሪያውያኑን አንድ ማድረግ ሳይችል ተበተነ፡፡
እጣፈንታቸው በሌሎች እንዲወሰን ግድ የሆነባቸው ኮሪያዎች፤ ደቡብ እና ሰሜን ተብለው ሲለያዩ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ዝምድና ከድንበር ጋር አብሮ እንዲቆራረጥ ሆነ፡፡ ሰሜን ኮሪያ እና ደቡብ ኮሪያ የሚገኙ የአንድ ቤተሰብ አባላትን የነጠለው ውሳኔ፣ ከሀያ ሁለት አመታት በኋላ ይፋ በተደረገ ሚስጥር መፍትሄ ያገኘ መሰለ፡፡ የሁለቱ አገሮች መሪዎች በድብቅ አንዱ የአንዱን ዋና ከተማ እንደጎበኙ እና ዋና የጉብኝቱ አላማም የሁለቱ ኮሪያዎች ሰላማዊ ውህደትን በመሻት የተከናወነ መሆኑን የሁለቱ ሀገር መሪዎች ገለፁ፡፡ የሰሜንና የደቡብ ኮሪያ የጋራ ስምምነት የተባለ ሰነድ መፈራረማቸውን አወጁ። ይሁን እንጂ፤ ይህን ያስፈፅማሉ በሚል ከሁለቱ አገሮች በተውጣጡ ልዑካን የተቋቋመው ኮሚቴ ያለምንም ውጤት ከአንድ አመት በኋላ ታገደ፡፡ በ1990 የሁለቱ ኮሪያዎች ጠቅላይ ሚኒስትሮች  ሲኦል ላይ ተገናኝተው የኮሪያውያንን አንድነት በተመለከተ ውሳኔዎችን ቢያስተላልፉም፣ ከኒኩሊየር ማበልፀጊያ ፖለቲካ ጉዳይ ጋር የተያያዘ ውዝግብ በመፍጠሩ ውጤት አልባ ሆነ፡፡ ከአመት በኋላ፤ እንደገና የሰሜን እና የደቡብ ኮሪያ የጋራ ስምምነትን የሚገልፅ ሰነድ አወጡ፡፡  የሰነዱ ዋነኛ አላማም፤ የሁለቱን ኮሪያዎች ሰላማዊ ውህደት የሚመለከት እንደሆነ አወጁ፡፡
የዚህ ውህደት እርምጃ በ2000 ተጀምሮ በ2007 በሰሜን ኮሪያ መንግስት ውሳኔ እንዲቆም የተደረገው ከሀምሳ አመታት በላይ የተለያዩ ቤተሰቦችን የማገናኘቱ ስራ ሰሞኑን እንደገና አገርሽቶ የመገናኛ ብዙሀን ትኩረት ሆኗል፡፡ ቤተሰቦችን ማገናኘቱ በሚቀጥለው ወር እንደሚጀመር ከስምምነት ላይ ተደርሶ የነበረ ቢሆንም ደቡብ ኮሪያ ከአሜሪካን ጋር በምታደርገው የፖለቲካ ወንድማማችነት ምክንያት ውሳኔዬን ልሰርዝ እችላለሁ ስትል ሰሜን ኮሪያ አስጠንቅቃለች፡፡
በተለያዩ የፖለቲካ ወገንተኞች ፍላጎት እና ውሳኔ፤ እንዲሁም ፅንፈኛ አቋም በያዙ መሪዎቻቸው እሰጥአገባ ሳቢያ የተነጣጠለ የቤተሰብ አባላትን የማገናኘቱ ፕሮግራም ለኮርያዊያኖች ከጥልቅ ስሜታቸው ጋር የተያያዘ ጉዳይ ነው፡፡ ቀን በሄደ እና እድሜ በገፋ ቁጥር በሞት መለየት ሊመጣ እንደሚችል ሲያስቡት ጉጉታቸው የበለጠ ይበረታል፡፡
የደቡብ ኮሪያ የቀይመስቀል ማህበር ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በ1988 ከቤተሰባቸው ጋር ለመቀላቀል ማመልከቻ ካስገቡ 127፣400 በሰሜን ኮሪያ የሚኖሩ ዜጐች ውስጥ አርባ ሺህ ያህሉ ቤተሰቦቻቸውን መቀላቀል ሳይችሉ ህይወታቸው ማለፉን ለማወቅ ተችሏል፡፡ እስከ አሁን 16ሺ 200 ኮሪያውያን በአካል፣ 3ሺ 740 የሚሆኑት ደግሞ በቪዲዮ ከቤተሰባቸው ጋር እንዲገናኙ ለማድረግ ተችሏል፡፡ ቤተሰቦችን የማገናኘቱ ፕሮግራም ከመጀመሩ በፊት ባሉት ቀደምት አመታት፣ ኮሪያውያኑ በያሉበት ከቤተሰቦቻቸው ጋር የፖስታ የስልክም ሆነ የኢሜይል መልእክት መለዋወጥ የማይችሉ ሲሆን ያለ መንግስት ፈቃድም ድንበር ማቋረጥ ተከልክለው ቆይተዋል፡፡
የ“ሁለቱ ኮሪያዎች ውህደት” የሚለው መፈክር ለዘለቄታው ተግባራዊ አይሆንም የሚሉ ወገኖች አሉ። ለዚህ ሀሳባቸው በመከራከሪያነት የሚያቀርቧቸውን ማሳመኛዎች አንድ ሁለት ብለው ይዘረዝራሉ፡፡ አንደኛ፤ ሁለቱ ኮሪያዎች በመለያየት ባሳለፏቸው አመታት ውስጥ ብዙ የተለያዩ ማንነቶችን አብቅለዋልና ይህ ልዩነት መቼም ወደ መታረቅ ሊመጣ አይችልም፤ ይላሉ፡፡
ሁለተኛ፤ ተለያይተውም በቆዩበት ብዙ አስርት አመታት የነበራቸው ግንኙነት እጅግ የሻከረ መሆኑ ለውህደት ባይሆንም … ቢያንስ በሁለቱ መሀል ያለውን ውጥረት ለማርገብ ሊያግዝ ይችል ይሆናል። ሶስተኛው፤ ከቤተሰቦቻቸው ጋር መቀላቀል የሚፈልጉት ኮሪያውያን እድሜ ሰባ እና ከዛ በላይ በመሆኑ፤ ኮሪያን አንድ በነበረች ጊዜ የሚያውቃት ትውልድ እየከሰመ በአዲስ ትውልድ በመተካቱ ምክንያት ነው፤ ብለው ማሳመኛዎቻቸውን ይተነትናሉ፡፡ የውህደት ጥያቄውም ልክ እንደ ትውልዱ እየከሰመ ይሄዳል፤ ውህደቱ ለቀድሞው ትውልድ እንጂ ለአዲሱ ትውልድ ትርጉም የሚሰጥ ሊሆን አይችልም ይላሉ፡፡
በቀዝቃዛው ጦርነት ምክንያት ሁለት አገር የሆኑት ኮሪያውያን፤ ሰሞኑን ደግሞ ደቡብ ኮሪያ ከአሜሪካን ጋር ወግናለች በሚል ምክንያት ከሀምሳ አመታት በላይ ከተለዩዋቸው ቤተሰቦቻቸው ጋር የመገናኘት ህልማቸው ጥያቄ ላይ ወድቋል፡፡

“በሰው ስራ ታውቆ የራስን መስራት ፈተና አለው”

ከጥቂት ዓመታት በፊት በዝነኛው ድምፃዊ ሙሉቀን መለሰ ሥራዎች ከአድማጮች ጋር የተዋወቀውና ተወዳጅነትን ያተረፈው አርቲስት ብዙአየሁ ደምሴ፤ በቅርቡ “ሳላይሽ” የተሰኘ የራሱን የመጀመርያ አልበም ለጆሮ አብቅቷል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየው ገበያው አልበሙ ከወጣ ጊዜ አንስቶ ድምፃዊውን ለማግኘት ስትታትር ቆይታ ባለፈው ረቡዕ ምሽት ተሳክቶላታል፡፡ ድምፃዊውን አሁን ከሚኖርበት ካናዳ በስልክ አግኝታው በአዲሱ አልበሙና በሙያው እንዲሁም በህይወቱ ዙሪያ እንደሚከተለው አነጋግራዋለች፡፡

ደህና አደርክ ልበል፣ ደህና ዋልክ? እኛ ጋ ከቀኑ አስር ሰዓት ነው...
ደህና አደርክ ነው የሚባለው፤ እኛ ጋ ከጠዋቱ 1 ሰዓት ነው፡፡ ግን አንቺ እንዴት ዋልሽ..?
በጣም ደህና ነኝ፡፡ አንተስ እንዴት አደርክ..ለነገሩ ድምፅህም የጠዋት ድምፅ ነው…
አዎ! ከእንቅልፌ እየተነሳሁ ነው፤ ጠዋት ስለሆነ ነው ድምፄ የጎረነነብሽ…እግዚአብሄር ይመስገን በጣም ደህና ነኝ፡፡ አገር ሰላም ነው? ሁሉ አማን? እኔ ሰላም ነኝ
ቤተሰብህን ጠቅልለህ ነው እንዴ ካናዳ የገባኸው..?
ቤተሰቦቼ ኢትዮጵያ ናቸው፤ ልጆቼም ባለቤቴም፡፡
በዚያው ቀልጠህ ቀረህ እኮ! ለመሆኑ አካሄድህ ለስራ ነው ለኑሮ?
ለነገሩ አሁን ሁሉ ነገር ስላለቀ መምጣት እችላለሁ፡፡ ለተወሰኑ ጊዜያት ለስራ ነበር የሄድኩት።
አዲሱ ‹‹ሳላይሽ›› አልበምህ እንዴት ነው? ተቀባይነት አገኘ? እስካሁን ምን ያህል ቅጂዎች ተሸጡ?
በትክክል ይሄን ያህል ኮፒ ተሸጧል ማለት መረጃው የለኝም፡፡ ነገር ግን ሙዚቃዬን ካሳተመልኝ የናሆም ሪከርድስ ባለቤት ጋር በየቀኑ እንገናኛለን፡፡ እንደ አሳታሚ ሳይሆን እንደጓደኞች ነን፡፡ እናም ባለቤቱ፤ “ብዙ አልበም ሰርቻለሁ፤ በዚህ ፍጥነት የተደመጠ ብዙ አልገጠመኝም”፤ ብሎኛል፡፡ እንዲህ በመሆኑም በጣም ተደስቻለሁ፡፡ የካናዳን ነገር ደግሞ ከምነግርሽ በላይ ነው፡፡ ሙዚቃው እንዴት እንደሚደመጥ አልነግርሽም፡፡ በቃ ያስደነግጣል .. ይሄን ያህል እደመጣለሁ እንዴ? ብዬ በእጅጉ ተደንቄአለሁ፡፡ አሳታሚዬ ናሆም ሪከርድስ ደግሞ አሜሪካ ነው ያለው፡፡ እሱ እንደነገረኝ እዚያም እጅግ በጣም ጥሩ ነው፤ ኢትዮጵያ ይደመጣል የሚባለው ያህል ሳይሆን አይቀርም ከፍተኛ ተ    ቀባይነት አግኝቷል፡፡
እስከዛሬ እንግዲህ በሰው ዘፈን ነበር የምትታወቀው፡፡ ከሰው ዘፈን ወደ ራስ ሥራ የመሸጋገሩ ሁኔታስ ምን ይመስላል? መቼም ፈታኝ እንደሚሆን እገምታለሁ …
አዎ፤ ከሰው ዘፈን ወጥተሽ የራስሽን ኦርጂናል ስራ ስትሰሪ በጣም ከባድ ነው፡፡ ምክንያቱም የራስ ዘፈን ሲሆን ራስሽን ሆነሽ ነው የምርቀርቢው። በተለይ በሰው ስራ ታውቀሽ ቆይተሽ የራስሽን ስትሰሪ ትንሽ ፈተና አለው፡፡
በአዲሱ አልበምህ ላይ በድምጽህም ሆነ በአዘፋፈን ዘይቤህ የሙሉቀን መለሰ ተፅዕኖ ጎልቶ እንደሚታይብህ ይነገራል፡፡ ይህን አስተያየት ትቀበለዋለህ?
አንዳንድ ጊዜ የምትወጅው ነገር የግድ ይስብሻል። ጥሩ ነገር ማን ይጠላል ብለሽ ነው… (ሳቅ)
የመጀመሪያ አልበምህ ሙሉ በሙሉ የሙሉቀን መለሰ ነበረ፡፡ ለአንዱ ዘፈን እንደውም የቪዲዮ ክሊፕ ሁሉ ሰርተህለታል፡፡ በዚህም ከሙሉቀን ጋር ተጋጭተህ ነበር፡፡ በአዲሱ አልበምህ ደግሞ አንድ የሙሉቀን መለሰ ዘፈንን ተጫውተሃል፡፡ አሁንስ አስፈቅደኸው ነው?
አዲስ የሰራሁት አይደለም፤ ከመጀመሪያ አልበም የተረፈ ነው፡፡ እንደውም መጀመሪያ ላይ ማካተት አልፈለግሁም ነበር፡፡ በኋላ የመጣ  ሃሳብ ነው፡፡ እሱም ቢሆን ግን ለኤሌክትራ ባለቤት እንዲሁም ለግጥምና ዜማ ደራሲዎቹ  አስፈላጊው ክፍያ ተፈፅሟል፡፡ ‹‹አትከብደኝም እስዋ›› የሚለውን ነው በአዲሱ አልበም ውስጥ ያካተትኩት፡፡
በነገርሽ ላይ አሜሪካ ሳለሁ ከጋሽ ሙሉቀን ጋር በጣም እንገናኝ ነበር፤ ካናዳ ከመጣሁ ነው የተጠፋፋነው፡፡ እና ለዚህ የሙሉቀን ዘፈን ብቻ የወጣው ብር በጣም ብዙ ነው…የናሆም ሪከርድስ ባለቤት አቶ ኤልያስ ነው የከፈለው፡፡
አዲሱ አልበምህ መለቀቁን ተከትሎ ከተለያዩ አገራት የኮንሰርት ጥያቄዎች አልቀረቡልህም?
አሁን በተጨባጭ ብዙ ስራዎች፣ ብዙ ኮንሰርቶች እየመጡልኝ ነው፡፡ አልበሙ በየቤቱ ይግባ እንጂ ሥራው ችግር የለውም፤ ይመጣል፤ ሰው ውስጥ እስኪዋሃድ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ከፋሲካ በኋላ የኮንሰርት ጉዞዬን እጀምራለሁ፡፡ እስከዛ ግን ሁለት ነጠላ ዜማዎች እለቃለሁ፡፡ በተለይ አንዱ ነጠላ ዜማ በበዓል መዳረሻ ላይ ነው የሚሆነው፤ ያለቀ ስራ ነው፡፡
‹‹ሳላይሽ›› በሚለው አልበምህ ከህይወትህ ጋር የሳሰረ ዘፈን አካተሃል?
አዎ አለ፡፡ ‹‹የህልሜ ንግስት›› የሚለውን ለባለቤቴ ነው የዘፈንኩት፡፡ ከእግዚአብሄር በታች አጠገቤ ሆና ትረዳኝ የነበረች እሱዋ ነች፡፡ ‹‹ንገሪኝ›› የሚለውን ደግሞ ለእናቴ ነው የዘፈንኩት፡፡
አሁን ካናዳ ውስጥ በምን ስራ ነው የምትተዳደረው?
ሙዚቃ ነው የምሰራው፡፡ ከሙዚቃ ውጪ ምንም ነገር አልሰራም፡፡ ራሴን በሙዚቃው ዘርፍ ለማሳደግ ጥናቶች እያደረግሁ ነው፡፡ መተዳደሪያዬ ግን ሙዚቃ ነው፡፡
ለአዳዲሶቹ ዘፈኖችህ ቪዲዮ ክሊፕ ለመስራት አላሰብክም?
‹‹ሳላይሽ›› እና ‹‹ማመኔ›› ለሚሉት ዘፈኖች እዚህ ክሊፕ ሰርቼ እያለቀ ነው፡፡ በቅርቡ አድናቂዎቼ እጅ ይገባል፡፡
ቴዲ አፍሮ በስራህ እንደሚያደንቅህና ዝምድና እንዳላችሁ ሰምቻለሁ፡፡ ስለ አዲሱ አልበምህ አስተያየት ሰጠህ?
አዎ ዝምድና ነገር አለን፡፡ ዘፈኖቼን ብዙ የሰማ አልመሰለኝም፡፡ እስካሁን ምንም አይነት አስተያየት አልደረሰኝም፡፡
ካናዳ ለአርቲስቶች እንዴት ናት? ትመቻለች?
ውይ አትመችም፡፡ ከባድ ነው፤ እኔ እድለኛ ስለሆንኩ ነው፡፡ እዚህ ያለን አርቲስቶች የተወሰንን ነን፡፡ ሄኖክ አበበ፣ ፋንታሁን ሸዋንቆጨው፣ ይርዳው ጤናው፣ እና ሌሎችምሰ አሉ፡፡ ካናዳን እንደማረፊያ ነው የሚጠቀሙባት፤ የተለያዩ አገራት እየሄዱ ኮንሰርት እየሰሩ ይመጣሉ፡፡ ባለፈው ከአስቴር አወቀ ጋር ‹‹እንደ ወፍ›› በሚለው ዘፈን እየዞርኩ ኮንሰርት እንዳቀርብ አስበው ነበር፡፡ ነገር ግን ይኼንን አልበሜን ለመስራት አራት ዓመት ነው የፈጀብኝ፡፡ ትኩረቴ ሁሉ እሱላይ ነበር፡፡ አልበሜን ከዳር ሳላደርስ የትም አልንቀሳቀስም ብዬ ነው የቀረው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ኮንሰርት ለማቅረብ ሃሳብ የለህም? መቼ እንጠብቅ?
ኢትዮጵያ ላይ በቅርቡ አንድ ነገር ለማድረግ አስበናል፡፡ እስከዛው ለአድናቂዎቼ እንዲሁም ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ እጅግ እንደምወዳቸው መልዕክት አስተላልፊልኝ፡፡ እግዚአብሔር ሁሉን ነገር ስላስተካከለልኝ አመሰግናለሁ፡፡ ባለቤቴ፣ ልጆቼ፣ አባቴን ጨምሮ አብረውኝ የነበሩትን ሁሉ አመሰግናለሁ፡፡ ለዚህ አልበም በስኬት መጠናቀቅ ከመጀመሪያ እስከመጨረሻ አብረውኝ ለሰሩና ከጐኔ ላልጠፉት አማኑኤል ይልማና አቀናባሪ ወንድሜነህ ምስጋናዬ ይድረሳቸው፡፡ የናሆም ሪከርድስ ባለቤት አቶ ኤልያስንም በእጅጉ አመሰግነዋለሁ፡፡

እነሆ ወርሃ የካቲት መጣ፡፡
አበቦች አንገታቸውን ማስገግ የሚወዱበት ወቅት ነው፡፡ የሚኳኳሉበት፡፡ ከብጤዎቻቸው ይበልጥ አምረው ደምቀው ይመረጡ ዘንድ የሚዋትቱበት፡፡ “እኔን! እኔን!” የሚሉበት፡፡ አበቦች እንደዚህ ወቅት ተወዳጅ የሚሆኑበት ጊዜ ይኖር ይሆን?
የፍቅረኞች የመሽሞንሞኛ ቀን “ቫለንታይንስ ዴይ” ሰሞኑን ተከበረ አይደል! ከአንዱ ዓመት ወደ ሌላኛው እንደምን እየሰፋ፣ እየተንሰራፋ፣ እየገዘፈ እንደመጣ ለማስረገጥ ምስክር ጥራ አልባልም መቼም፡፡ ግድየለም የቢዝነስ ጋዜጦቻችን የስጦታ ገበያ ሸመታውን አስልተው፣ ከቀድመው ጊዜ ጋር አነጻጽረው ይነግሩናል፡፡ የሬዲዮ አሰናጆች ድምጻቸው አለሳልሰው፣ ሙዚቃቸውን አቀዝቅዘው የዕለቱን አዋዋል በተለይ ደግሞ አመሻሽ አትተውልናል፡፡ እኔ ግን “እባካችሁ --- የአምልኮተ- ሮማንስ ሩጫችሁን ቀንሱ!” እላለሁ፡፡
በመጀመሪያ ማጥራት ያለብን እሳቤ አለ፡፡ (አንድ ሰሞን ፈሊጥ እንደነበረው “ፍቅር አለ ወይስ የለም?” የሚል ሞኛሞኝ ክርክር ውስጥ ራሴን መዶል አልፈልግማ!) የቃላት አጠቃቀሙ በራሱ ችግር ያለበት ይመስለኛል፡፡ እርግጥ ነው አንዲት ቀዘባ እና ወዳጇ የሚጀመሩትን ፍቅር ነክ ግንኙነት ለመግለፅ love፣ relationship፣ dating  የተባሉ ቃላትን እያቀያየሩ  መጠቀም ተለምዷል፡፡ (“የከንፈር ወዳጅ” ይሏት ሀረግ ግን ትርጉሟ ተምታቷል እንጂ እንደምን ገላጭ ናት!) የኋለኞቹ ሁለት ቃላት (dating እና relationship) romance  በሚባለው ኮሮጆ ሊቋጠሩ የሚገባቸው ናቸው፡፡ እና በlove እና romance መካከል ትልቅ የትርጉም ልዩነት አለ፡፡
Love ጠሊቅ ነው፡፡ ረጅምም ነው፡፡ ጓደኝነት ነው፡፡ ንብቡነት ነው፡፡ አገልግሎት ነው፡፡ ተረት የሚመስል ስሜት አይደለም፡፡ እናት ወህኒ የወረደ ልጇን ለአፍታ እንኳ ቅያሜ ሳትይዝበት፣ለአንድም ቀን ሳታዛንፍ ተመላልሳ ስትጠይቀው እናያለን። አባት ግላዊ ምቾቱን ትቶ ከንጋት በፊት ከቤት ወጥቶ ሲፍገመገም እየዋለ፣ ማታውን ደግሞ ከልጆቹ ጋር ሲጫወት ለማምሸት ተብከንክኖ እቤቱ በጊዜ ይገባል፡፡ ባለትዳሮች ለሰላሳና አርባ አመታት ህመም እና ፈውሳቸውን ሲጋሩ እናስተውላለን፡፡ በጋሽ ስብሃት አጭር ታሪክ “ዔሊን ድንጋይ ያለበስክ” ላይ በአሮጊቷ በኩል የሚነገር ነው፡፡ (“ለምን ይለምናሉ?” ብሎ ጠየቃቸው ተራኪው አሮጊቷን። ልጃቸውን ብለው ተንከራተቱ፡፡ ልጃቸው አድጎ ሲያገባ ሚስቱ ጠላቻቸው፡፡ አሮጊቷ ልጃቸውን ፈተና ውስጥ ሊከቱት አልሻቱም፡፡ እርሱም አሁን ወልዷል፡፡ የልጁን ፍቅር ያውቁታል፡፡ ስለዚህ ሹልክ ብለው ወጡለት፡፡) ትንንሽ የሚመስሉ ትልልቅ መስዋእትነቶች ድምር ነው - love
Romance በአንፃሩ ይሄንን ሁሉ አይደለም። የሆሊውድ የእጅ ሥራ ነው (በርግጥ አንድሩ ሱሊይቫን የተባለ እና ከአስራ ምናምን ዓመታት በፊት በኒውዮርክ ታይምስ መፅሄት ላይ “The Love Bloat” የሚል ርዕስ ያለው መጣጥፍ ያሳተመ ፀሃፊ እንደሚለው፣ ሮማንስን  የፈጠረው ፈረንሳዊው ፈላስፋ ሩሶ ነው፡፡ ወደ እርሱ መመለሴ አይቀርም።) ሮማንስ ቀመር አለው፡፡ ቀመሩን አምርቶ ለዓለም ህዝብ ሁሉ የሚያስተምረው ደግሞ ሆሊውድ የተባለው ተረት አምርቶ የሚተዳደር ኢንዱስትሪ ነው፡፡ በቀመራዊ የሮማንቲክ ኮሜዲ ፊልሞች። (ሆሊውድና የአሜሪካ የሸማችነት ባህል ይሄንን አምልኮ ባይፈጥሩትም የተለጠጠ ፋይዳውን በመፍጠር ግን የድርሻቸውን ሚና እንደተጫወቱ አያጠራጥርም) አሁን ልፋቱ ሁሉ ተሳክቶለት የመላው ዓለም ወጣቶች፣በአምልኮተ ሮማንስ ተሰልበው ሲሸነጋገሉ ያመሻሉ፡፡ በሆሊውድ በተደረሰው ማኒፌስቶ መሰረት፣የሮማንስ መገለጫዎች የማያሻሙ ናቸው፡፡ አንዲትን ሴት ለdate መጠየቅ - ብዙ ጊዜ የራት ግብዣ ነው፡፡ ምርጥ ምግብ ቤት መመረጥ አለበት፡፡ በተቻለ መጠን ያንን ምሽት እንስቷ ተረት በሚመስል ስሜት ውስጥ ተንሳፋ እንድታሳልፈው እንዲያስችላት ይጠበቃል ከወንዱ። ልክ ለስራ ቅጥር የሚደረግ ፈተና የሚመስል አይነት ነገር አለበት፡፡ ከተሳካለት እና ምሽቱ በሚገባ ካለፈ ቤት ድረስ ይሸኛታል፡፡ ይስማታል፡፡ እና “ድንቅ ጊዜ ነው ያሳለፍኩት፣ አመሰግናለሁ” ይባባላሉ። ከዚያ ለጓደኞቻቸው “We are dating” ወይንም “We are seeing each other” ይላሉ፡፡ Love የምትባለውን ቃል ለረጅም ጊዜያት ምናልባትም ለወራት እና ዓመታት አይጠቀሙባትም፡፡ ወንድየው የልደት ቀኗን መርሳት የለበትም፡፡ የምትነግረውን ዝባዝንኬና እንቶ ፈንቶ ሁሉ ማዳመጥ አለበት፡፡ ደግሞ የተረት ተረቱ የመጨረሻው  ደረጃ (ጡዘት) በወርሃ የካቲት ይመጣል፡፡ የቅዱስ ቫላንታይን ቀን፡፡ አበባው ይገዛል፡፡ ወደ ምግብ ቤት ሄዶ ራት ይበላል፡፡ ስጦታም ይበረከታል፡፡ ከዚህም የተሻገረ ነገር ይኖራል፡፡ ሽርሽር ይሰናዳል፡፡ የ”አግቢኝ” ጥያቄ ይጠበቃል፡፡ ደግሞም ጥያቄው ድራማዊ መሆን አለበት፡፡ ይሄ የማይዛነፍ ቀመር የሚጠቅመው እንግዲህ የፊልም አምራቾችን፣ የምግብ ቤት ባለቤቶችን፣ የስጦታ እቃ ሻጮችን እና አበባ ነጋዴዎችን ነው፡፡ እነርሱም ለዕለቱ በሚገባ ነው የሚዘጋጁት፡፡ በዕለቱ ያለ ተጣማሪ መሆን የብቸኛነት ትርጉም ተደርጎ ይታሰባል፡፡
ልዩነቱ ግልጽ ነው፡፡ Love is authentic, Romance is counterfeit. ፍቅር ቱባ ነው። ሮማንስ ቅጂ፡፡ (ዲ.ኤች.ሎረንስ “Lady Chatterley’s Lover” ለተባለው አወዛጋቢ ልቦለዱ ማብራሪያ ይሁን ብሎ በፃፈው መጣጥፉ “Apropos of Lady Chatterley’s Lover” ላይ ይኼንን ኹኔታ አሳምሮ ገልፆታል፡፡ ሮማንስ  ውስጥ ያሉ ሰዎች “ምን ዓይነት ስሜት ሊሰማቸው እንደሚገባ ያውቁታል፣ ስለዚህም ያንን ስሜት ያድኑታል ግን እውነተኛ ስሜት አይደለም” ቃል በቃል ማስታወስ ባለመቻሌ ይቅርታ መጠየቅ ይገባኛል፡፡)
“ፍቅር ሁሉንም ነገር ይቆጣጠራል እንባላለን” ይላል- ከላይ የጠቀስኩት ጸሐፊ ሱሊይቫን ደግሞ፡፡ ነገር ግን በቫለንታይን ቀን የሚከበረው ፍቅር ምንም የሚቆጣጠረው ነገር የለም! ሩሶ የተባለው ተምኔታዊ ፈላስፋ በከበርቴው መደብ ጠባይ እና ነገረ ሥራ በመማረሩ ሰዎች ለእውነት፣ ለክብር እና ለስልጣን ያላቸውን ጥልቅ ስሜት በሌላ መተካት እንዳለበት አመነ፡፡ እና ወጣቶች በርስ በርስ ጥማት መንደዳቸው አስፈላጊ ነው ሲል ሰበከ፡፡ (በምዕራባውያን ባህል መዋደድ ለጋብቻ መሰረት መሆኑ ይለመድ የያዘው ከ19ኛው ክፍለ ዘመን በኋላ ነው፡፡ ከዚያን ጊዜ አንስቶም የፍቺ ቁጥር ጨመረ እንጂ ሲቀንስ አልታየም፡፡) ሮማንስ  ለዘመኑ ወጣቶች የሚሰጠው ብዙ ጥቅም አለ፡፡
ኢጓችንን ደባብሶ ይንከባከብልናል፡፡ በራሳችን ዙሪያ መተብተባችን ያለቅጥ እየጦዘ ነው የመጣው። ሮማንስ  ይህንን ራስ ወዳድነታችንን ያረካልናል። እንደ ወትሮው ልጅ መውለድ ዋነኛ ዓላማው ተደርጎ መታየቱ፣የቀረውን ወሲብ ልዩ ትርጓሜ የያዘ እንዲመስል ያደርገዋል፡፡ እናም ደግሞ ከመራር የህይወት ጥያቄዎች (ምን እንመን? ምንድን ነን? ወዘተ) ይገላግለናል፡፡ ይሸሽገናል፡፡
ይህ የኑሮ ፈሊጥ አሁን የእኛም ሆኗል፡፡ ችግር መሆን የሚጀምረው ግን ትክክለኛ ዋጋውን ያለአግባብ ለጥጠን የሌለውን ግዝፈት ከሰጠነው ብቻ ነው፡፡

በዓለም ላይ “የመርፊ ህግ” በመባል የሚታወቅ ህግ አለ፡፡ የምንሠራው ሥራ ሁሉ ስህተት ይሆናል ብሎ የማመን አዝማሚያ ነው፡፡ ስለዚህ ጉዳይ የሚተረክ አንድ ተረት አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሰው፤ በአንድ በጣም በራበው ጠዋት፤ ቁርስ አስቀርቦ መብላት ጀመረ፡፡ ዳቦውን ሁለት ላይ ከፈለና አንዱን ግማሽ ቅቤ ቀባው፡፡ ጥሩ አድርጐ ግማሹን ክብ ዳር እስከዳር አሳምሮ ነው በቅቤው ያዳረሰው፡፡ ከዚያ ሻዩን ለማወራረጃ ስለሚፈልገው ስኳሩን አስቀድሞ ከቶ ሻዩን ብርጭቆው ውስጥ ቀድቶ እያዘጋጀ ሳለ፤ ሳያስበው ያን የተቀባ ግማሽ ዳቦ ከጠረጴዛው ገፋና ጣለው፡፡
ዳቦው ወለሉ ላይ ወደቀ፡፡
ደንግጦ ወደ ወለሉ ሲያይ በጣም አስገራሚ ነገር ገጠመው፡፡ የዳቦው ያልተቀባው ወገን ወደመሬት፤ የተቀባው ወገን ወደላይ መሆኑን አየ፡፡ አንዳች ተዓምር እንዳየ ሆኖ ተሰማው፡፡ ተደነቀ፡፡
ወደ ጓደኛዬ ሄደና፤
“ዛሬ ጉድ ነው ያየሁት!” አለ፡፡
“ምን አየህ?”
“ብታምኑም ባታምኑም - ተዓምር ነው ያየሁት!”
“እኮ ምን አየህ? ንገረና!?”
“ቁርስ ስበላ ድንገት ግማሹ ቅቤ የቀባሁት ዳቦ መሬት ወደቀ፡፡ የሚገርመው ያልተቀባው ወገን ወደታች የተቀባው ወደላይ ሆኖ ተገኘ!”
“እረ ባክህ? ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? የተቀባ ዳቦ ሲወድቅኮ፤ ብዙ ጊዜ የተቀባው ወደ መሬት፣ ያልተቀባው ወደላይ ነው የሚሆነው፡፡ አንተ ያጋጠመህ ተዓምር ካልሆነ በስተቀር ወደላይ ሊሆን አይችልም። ምናልባት ለእኛ አልታወቀን ይሆናል እንጂ አንተ ቅዱስ ሳትሆን አትቀርም፡፡ አምላክ ምልክት ሲሰጥህ ነው” አለ
አንደኛው ጓደኛው፡፡
ከዚህ በኋላ በአንድ ጊዜ ወሬው በመንደሩ ተነዛ፡፡ ሁሉ ሰው ጆሮ ደረሰ፡፡
ሁሉ ሰው መጠያየቅ ጀመረ፡፡
“ይሄ እንዴት ሊሆን ቻለ? ማንም ሰው ያልተቀባው ወገን ወደታች ይሆናል ብሎ አይጠረጥርም፡፡ ዳቦው በተሳሳተ ወገንኮ ነው የወደቀው?” ተባለ፡፡
ማንም መልስ ሊሰጥበት ያልቻለ ትልቅ ጥያቄ ሆነ፡፡
በመጨረሻው “ለሰፈሩ ሊቅ ጥያቄውን እናቅርብለትና እሱ ይመልስልን” ተባለ፡፡
ወደመምህሩ ሊቅ ሄደው የሆነውን ተዓምር ነግረው እንዲያብራራላቸው ጠየቁት፡፡
አዋቂው፤ “በዚህ ጉዳይ ላይ፤ ለመፀለይ፣ ሃሳቡን ለማብላላትና መለኮታዊ ምጥቀት ለማግኘት፤ አንድ ማታ ያስፈልገኛል” አለ፡፡
ጊዜው ተሰጠው፡፡
በነጋታው በጉጉት ህዝቡ እየጠበቀው ሳለ መምህሩ መጥቶ፤
“ነገሩ እንኳን በጣም ቀላል ነው፡፡ ያ ዳቦ የወደቀው በትክክል መውደቅ ባለበት በኩል ነው፡፡ ቅቤው የተቀባው ግን በተሳሳተው ወገን ነው!!” አለ፡፡
                                                            *   *   *
እርግጥ በሀገራችን አንፃር ስናየው፤ ዳቦው ከሌለ ግማሹም ሆነ ሙሉው ተቀባ አልተቀባ ማለት አስቂኝ ይሆን ይሆናል፡፡ የተረቱ ምልኪ ግን፤ ስለወደቀውም ዳቦ አሉታዊ አስተሳሰብ ሊኖረን አይገባም ነው፡፡ ከዚያ ቀጥሎ ዳቦው የዳነው በተሳሳተ ወገን ስለተቀባ ነው የሚለው ሌላው አሉታዊ ምላሽ ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን። ህዝቡም መምህሩም አፍራሽ ይሆኑብናልና!
አንዳንዴ አንዳንድ ምናባዊ ፅንሰ-ሀሳብ ምድር ላይ ቢሆን ምናለበት ያሰኛል፡፡ የዳንቴ ፍልስፍና ለዚህ ይበጀናል፡፡
ሰይጣንን ከማግኘታችን በፊት የወንጀለኞች መቀጫ፤ አውቀው ኃጢአት የሰሩ የሚቃጠሉበት፤ ቦታ አንድ ህግ አለው ይባላል፡- የወሸሙና የከጀሉ፤ በዲያብሎስ ይገረፋሉ፡፡ ሸፋጮች አወናባጆች፣ አይነ ምድር ውስጥ ይደፈቃሉ አጨናባሪ አትራፊዎች እግር-ወደላይ-ራስ ወደ ታች ሆነው አዛባ ውስጥ ይዘፈቃሉ። ጠንቋዮች፣ ጠጠር ጣዮች፣ ዛጎል ወርዋሪዎች፤ አንገታቸው ወደ ጀርባ የሚዞርበት ምስል ይኖራቸዋል። አወናባጅ ፖለቲከኞች የአፈር-ውሃ ጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ ይጣላሉ፡፡ አስመሳዮች መሸከም የማይችሉት ካፖርት ይጫንባቸዋል፡፡ ሌቦች በእባብ አለንጋ ይገረፋሉ፡፡ አጭበርባሪ የፖለቲካ አማካሪዎች በእሳት ይዋጣሉ የማይሆን ወሬ የሚነዙ ፍም ውስጥ ይቀበራሉ፣ ይለናል፡፡
ከዚህ ሁሉ ይሰውረን ዘንድ መንገዱን ያብጅልን! ይሄ የገባው እራሱን ይጠብቅ፡፡
የሃገራችን ውሃ፣ የመብራት፣ የስልክ… የባንክ፣፣ የቀረጥ ወዘተ የማይነጣጠሉ ችግሮች፤ የዘንድሮ ጉዴስ እኔም ገረመኝ፡፡
አንዱን ስለው አንዱ አንዱ ባሰብኝ!
የሚለውን የዱሮ የኦርኬስትራ ኢትዮጵያን ዘፈን ያስታውሰናል፡፡ በዚያው ዘመን ስለ ሎተሪ አዟሪ በሚዘፈን ዜማ፤
“እስኪ ተመልከቱት፣ ይሄንን ፈሊጥ
እሱ እድል የሌለው፣ ዕድልን ሲሸጥ!” የሚልም ነበር፡፡ ከሁሉም ይሰውረን፡፡
ዛሬ “የባሰ አታምጣ!” ብሎ መፅናናትም አስቸጋሪ ሆኗል፡፡ እንደዕውነቱ ከሆነ የዕውቀትና የሙያ ክህሎታችን ምን ዓይነት ለውጥ ያመጣል ማለት እንጂ “ፓርቲዬ ከመደበኝ የትም ቦታ እሰራለሁ” ብቻውን መፍትሄ አያመጣም፡፡ ችግሩ የተፈጠረው በፓርቲ ምደባ ምክንያት ከሆነስ? ብሎ መጠየቅም ያባት ነው፡፡ ህዝባችን ፓርቲን እንዲያልም ሳይሆን አገር እንዲያልም ብናስብ መልካም ሳይሆን አይቀርም፡፡
የሀገራችን አካሄድ ዕውን፣ በዳቦ የተሳሳተ ወገን መቀባት? ቅቤውን አፈር አይነካውም በማለት? ዓበው እንደሚሉት ከተምኔታዊ (utopian) ገጠመኝ ይልቅ ሌላውን ግማሽ ምን እናርገው? የትኛው ይበጃል? የሚለውን በቅጡ ማጤን ዛሬም ወሳኝ ነው! በወደቀው ላይ ከመፈላሰፍ እንዴት ቀጣዩን በወጉ እንያዘው? ማለት አንገብጋቢ ጉዳይ ነው፡፡
ከቶውንም በግሎባላይዜሽን (ትርጉሙ እኳኋን በእርግጥ ባልተረጋገጠው ፅንሰ ሀሳብ ተንተርሶ) አገርን ማሰብ የተሳሳተ ድምዳሜ ላይ እንዳያደርሰን ከልብ ማውጠንጠን ይኖርብናል፡፡ ምዕራባውያን አገሮች እስከዛሬ ያልታየ የፋይናንስ ድንገተኛ አደጋ (Financial Calamity) እየገጠማቸው መሆኑን በዋዛ አንየው! ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ እየተንኮታኮተ ያለውን የኢኮኖሚ የበላይነት በተምታታ ብዥታ እንደሚመለከተው መታየት ፀሐይ የሞቀው ሀቅ ነው፡፡ ይሄን የውስጥ ድንግርግር በዓለም ዙሪያ በተለይም በአዳጊ አገሮች ላይ በመጫን የንግድ፣ የሽብርተኝነት፣ “የዲሞክራሲን አስፋፋለሁ” መርህ ምህዋር ለማስቀየር መጣጣራቸውን ከመፍራት ይልቅ ማወቅ፣ እጅ ከመስጠት ይልቅ ሉዓላዊነትን ጠንክሮ ማሰብ፤ ደግ መሆኑን የዘመኑ የፖለቲካ ጠበብት እንደሚመክሩ ልብ እንበል፡፡ ዘይት፣ ነዳጅ፣ ማዕድን… ያላቸው አገሮች የሚያስነሱትን ብጥብጥ ያስታውሷል፡፡ የራሳችንን ህዝብ ኢኮኖሚያዊ አሳር ቸል አንበል፡፡ የራሳችንን ህዝብ ፖለቲካዊ ምሬት የራሱ ጉዳይ አንበል፡፡ የራሳችንን ህዝብ አስተዳደራዊ በደል ለሌላ ለማንም ብለን ሳይሆን ለነገ የራሳችን ሰናይ ማንነት ስንል ከጉዳይ እንፃፈው፡፡ የራሳችንን ህዝብ የሞራልና የስነ-ምግባር ምንነት በትምህርት በንቃት፣ በአስተዳደጋዎ አስምህሮት ስራዬ ብለን እንደግፈው፡፡ እነዚህን ከላይ የጠቀስናቸውን ፍሬ - ጉዳዮች በቅጡ አስበንባቸው ችግሮቻችንን በየደረጃውና በወቅቱ ካልፈታን ለጎረቤት አገሮች እያሳየን ነው የምንለውን የመፍትሄ - አሽነት ሚና የለበለጠ ያስመስልብናል!  ትላንት ሩዋንዳ፣ ሱማሌ፣ ጅቡቲ ወዘተ… በሞፈር - ዘመትነት መሄዳችንን የአንገት - በላይ ያረግብናል፡፡ “የራሷ ሲያርባት የሰው ታማስላለች” እንዳይሆን እንጠንቀቅ፡፡  


“በሁሉም ማዕከላት አገልግሎቱ ያለእንከን እየተሰጠ ነው”

በአዲስ አበባ ተግባራዊ በተደረገው የቅድመ ክፍያ የመብራት አገልግሎት አሰጣጥ ደንበኞች መማረራቸውን እየገለፁ ሲሆን መብራት ሃይል በበኩሉ፤ በሁሉም ማዕከላት አገልግሎቱ ያለእንከን እየተሰጠ ነው ብሏል፡፡
ካዛንቺስ በሚገኘው የቅድመ ክፍያ አገልግሎት ማዕከል፣በክፍያ አሰባሰብ ላይ ቅሬታ ሲያቀርቡ ያገኘናቸው አንዳንድ ተገልጋዮች፤ ክፍያው የሚሰበሰበው በአንድ ሠራተኛ ብቻ በመሆኑ ወረፋ በመጠበቅ የስራ ጊዜያቸውን እያባከኑ እንደሆነ በምሬት ገልፀዋል፡፡ ረጅም ወረፋ ሲጠብቁ ቆይተው  የምሣ ሰአት አሊያም የስራ መውጫ ደርሷል እየተባሉ ወደ ቤታቸው የሚመለሱ በርካታ ደንበኞች እንዳሉ የታዘበ አንድ ወጣት የቅድመ ክፍያ አገልግሎት ደንበኛ፤ እሱም ራሱ በተመሳሳይ ምክንያት ለሶስት ተከታታይ ቀናት ወደ ማዕከሉ መመላለሱን ገልጿል።
ከሃያት አካባቢ የአገልግሎት ካርዳቸውን ለማስሞላት ካዛንቺስ ድረስ መምጣታቸውን የገለፁት አንድ ጎልማሳ በበኩላቸው፤ ድርጀቱ በከተማዋ አንድ ማዕከል ብቻ በመክፈቱ እሳቸውን ጨምሮ በርካታ ተገልጋዮች ለእንግልት መዳረጋቸውን ተናግረዋል። የአገልግሎቱ መጀመር በተለይ የመብራት አጠቃቀምን በዘመናዊ መልኩ ለመቆጣጠር ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው የሚገልፁት ደንበኞች፤ መብራት ሃይል በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የቅድመ ክፍያ አገልግሎት ማዕከላትን በስፋት በመክፈት፣ አገልግሎቱን በተደራጀ የሰው ሃይል በመስጠት ደንበኞችን ከእንግልትና ከምሬት መገላገል ይችላል  ብለዋል፡፡
የደንበኞችን ቅሬታና በአጠቃላይ አገልግሎቱን በተመለከተ ያነጋገርናቸው የኢትዮጵያ መብራት ሃይል ኮርፖሬሽን የውጭና ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ምስክር ነጋሽ፤አገልግሎቱ ከሁለት አመት በፊት እንደተጀመረና የደንበኞችን ወጪና ጊዜ ለመቆጠብ ታስቦ ተግባራዊ መደረጉን አስታውሰው፤ በከተማዋ አገልግሎቱን የሚሰጡ 29 ማዕከላት እንዳሉ፣ ሁሉም አገልግሎቱን በተቀላጠፈ መልኩ ለ174ሺ35 ደንበኞች ያህል እየሰጡ እንደሆነም ገልፀዋል፡፡ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በአዳማ ያሉት 3 ማዕከላት እና በቢሾፍቱ ያሉት 2 ማዕከላት፣ በአጠቃላይ ለ26ሺ39 ደንበኞች የተቀላጠፈ አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነም ነው ኃላፊው የተናገሩት፡፡ የቢል ህትመት ወጪን እንዲሁም የቆጣሪ አንባቢንና የገንዘብ ሰብሳቢን ድካም በማስቀረት ረገድ አዎንታዊ ሚና እንዳለው የሚነገርለት የቅድመ ክፍያ ቆጣሪ አገልግሎት ተግባራዊ በተደረጉባቸው ሶስቱ ከተሞች ለ200ሺ104 ደንበኞች አገልግሎት እየተሰጠ እንደሆነም አክለው  ገልፀዋል፡፡
በከተማዋ አንድ የአገልግሎት ማዕከል ብቻ በመኖሩ ተቸግረናል የሚለውን የደንበኞች ቅሬታ አስመልክቶ  የተጠየቁት አቶ ምስክር ሲመልሱ “ካዛንቺስና ሜክሲኮ ያሉት እንደ ዋና ማዕከል እሁድን ጨምሮ አገልግሎት የሚሰጥባቸው እንጂ ብቸኛ ማዕከላት አይደሉም፤ በከተማዋ ያሉት 29 ማዕከላት በቂ ሙያተኛ ተመድቦላቸው አገልግሎቱን በተቀላጠፈ መልኩ እየሰጡ ነው” ብለዋል፡፡ በቅርቡም የሃይል ብክነትን  ለመቆጣጠር የሚያስችሉ ሌሎች ዘመናዊ ቆጣሪዎችን ተግባራዊ ለማድረግ መስሪያ ቤቱ እቅድ መያዙን አቶ ምስክር ጠቁመዋል፡፡  

ጊዜው ቢከፋም ለጋሾች እጃቸው አልታጠፈም
50 በጎ አድራጊዎች 7.7 ቢሊዮን ዶላር ለግሰዋል
ከሴቶች ለጋሾች ይልቅ ወንድ ለጋሾች በርክተዋል

በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2013 ለተለያዩ የበጎ አድራጎት ስራዎች ገንዘባቸውን ከለገሱ አሜሪካውያን መካከል፣ የፌስቡክ መስራቹ  ማርክ ዙከርበርግና ባለቤቱ ፒሪሲላ ቻን ቀዳሚዎቹ መሆናቸውን ክሮኒክል ኦፍ ፌላንትሮፒ የተባለው ተቋም ይፋ አደረገ፡፡
ጥንዶቹ የአመቱን የወደር የለሽ የቸርነት ክብር የተጎናጸፉት፣ ሲሊከን ቫሊ ፋውንዴሽን ለተሰኘው የበጎ አድራጎት ድርጅት 990 ሚሊዮን  ዶላር ዋጋ ያለው የፌስቡክ የአክሲዮን ድርሻ በመለገሳቸው ነው፡፡ ይህ በአመቱ በአሜሪካ ምድር የተሰጠ ከፍተኛ ልግስና፣ ፋውንዴሽኑን ከአገሪቱ ታላላቅ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ተርታ ያሰልፈዋል ተብሏል፡፡
ዙከርበርግና ሚስቱ በአመቱ የአገሪቱ 50 አባ መስጠቶች ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት አሜሪካውያን በእድሜ ለጋዎቹ ሲሆኑ በሰላሳ አመት እድሜ ላይ የሚገኙት ጥንዶቹ፣ ባለፉት ሁለት አመታትም ለዚሁ የበጎ አድራጎት ድርጅት 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ የአክሲዮን ድርሻ በልግስና አበርክተዋል።
ጥንዶቹ የለገሱት ገንዘብ በትምህርትና በጤና ዘርፎች ለሚከናወኑ ስራዎች ይውላል ተብሏል፡፡
ክሮኒክል ኦፍ ፌላንትሮፒ የአመቱ ለጋስ ብሎ በሁለተኛነት ያስቀመጣቸው፣ ቴክሳስ ኢነርጂ የተባለው ኩባንያ የቀድሞ ስራ አስኪያጅ ጆርጅ ሚሼል ናቸው፡፡ ባለፈው ሃምሌ ከዚህ አለም በሞት የተለዩት እኒህ ባለጠጋ፣ቤተሰባቸው ለበጎ አድራጎት ድርጅት እንዲሰጥላቸው አደራ ብለው በሄዱት 750 ሚሊዮን  ዶላር ነው ለዚህ ክብር የበቁት፡፡
ከናይኪ ኩባንያ መስራቾች አንዱ የሆኑት ፊል ናይት እና ባለቤታቸው ፔኔሎፔም፣ ለኦሪገን ሄልዝ ኤንድ ሳይንስ ዩኒቨርሲቲ ፋውንዴሽን የካንሰር ምርምር እንዲውል መዥረጥ አድርገው በሰጡት 500 ሚሊዮን  ዶላር ከአገሪቱ የአመቱ ቀዳሚ ለጋሶች ሶስተኛ ሆነዋል፡፡ የአሜሪካን የወደር የለሽ ቸሮች ዝርዝር በቀዳሚነት ሲመሩ የቆዩት የማይክሮ ሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስና ባለቤታቸው ሚሊንዳ ጌትስ፣ በ2013 ክብራቸውን ማስጠበቅ ባይችሉም በአመቱ ከ181 ሚሊዮን  ዶላር በላይ ለግሰዋል ተብሏል፡፡ ጥንዶቹ በ2004 ለበጎ አድራጎት ተግባር ለመስጠት ቃል የገቡትን 3 ነጥብ 3 ቢሊዮን  ዶላር ቀስበቀስ መክፈል መቀጠላቸው ተነግሯል፡፡
በክሮኒክል ኦፍ ፌላንትሮፒ የ2013 ወደር የለሽ ለጋሶች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት 50 አሜሪካውያን፣ ለተለያዩ የበጎ አድራጎት ስራዎች በድምሩ 7 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ሰጥተዋል - በ2014፡፡
በአመቱ 296 ሚሊዬን ዶላር በመስጠት በለጋሾች ዝርዝር ውስጥ የአምስተኛነትን ደረጃ የያዙት ጆን አርኖልድ እና ባለቤቱ ላውራ፣ ድጋፍ የሚሹ ወገኖቻቸውን ብቻም ሳይሆን መንግስታቸውንም በመርዳት የሚታወቁ ጥንዶች ናቸው፡፡ ባልና ሚስቱ ባለፈው ጥቅምት ወር የአሜሪካ መንግስት መዘጋቱን ተከትሎ በተከሰተ የአቅም ማጣት ችግር ላይ ፈጥነው ደርሰዋል፡፡ መንግስት በወቅቱ ትምህርት ቤቶቻቸው ተዘግተው ቤት ሊውሉ የነበሩ 7ሺህ ያህል አሜሪካውያን ህጻናትን ትምህርት ማስቀጠል የቻለው፣ እነዚህ ጥንዶች ባበደሩት 10 ሚሊዮን  ዶላር ነው፡፡
በአመቱ የለጋሾች ዝርዝር ውስጥ ዙከርበርግን ጨምሮ በቴክኖሎጂው ዘርፍ የተሰማሩ ሌሎች አምስት ታዋቂ ግለሰቦችም ተካተዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል የኢቤይ መስራች ፔሪ ኦሚድያር፣ የጎግል መስራች ሰርጌይ ብሪንና ከማይክሮሶፍት መስራቾች አንዱ የሆኑት ፖል አለንና ሚስቶቻቸው ይጠቀሳሉ።
ወንዶች በሚበዙበት በዚህ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት ለጋሾች፣ የአገሪቱ ኢኮኖሚ እየተንገራገጨ ባለበት ወቅት ሳይሰስቱ በሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር ለበጎ አድራጎት ስራ መለገሳቸው ያስደንቃቸዋል ተብሏል፡፡
ለጋሾቹ በአመቱ ከሰጡት ገንዘብ አንድ ሚሊዮን ዶላር ያህሉን የወሰዱት የእርዳታ ድርጅቶች፣ ሆስፒታሎችና ኮሌጆች ሲሆኑ፤ የተቀረውም በህክምና ምርምር፣ ሰብአዊ አገልግሎቶች፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በህጻናትና ወጣቶች ወዘተ ዙሪያ ለሚሰሩ ድርጅቶችና ተቋማት እንደሚውል ተነግሯል፡፡


Monday, 10 February 2014 07:47

‘ድፍረት’ ፊልም ተሸለመ

በኢትዮጰያዊው ፊልም ባለሙያ ዘረሰናይ ብርሃኔ ተጽፎ የተዘጋጀው ድፍረት ፊልም፣ በ2014 ሰንዳንስ አለማቀፍ የፊልም ፌስቲቫል በ‘ወርልድ ሲኒማ ድራማቲክ ኦዲየንስ’ ዘርፍ ተሸላሚ ሆነ፡፡
ታዲያስ መጽሄት ከኒዮርክ እንደዘገበው፣ በእውነተኛ ታሪክ ላይ ተመስርቶ የተሰራውና የ99 ደቂቃ ርዝማኔ ያለው የዚህ ፊልም ዳይሬክተር ዘረሰናይ ብርሃኔና ፕሮዲዩሰሯ ምህረት ማንደፍሮ ባለፈው ቅዳሜ በተከናወነው የፌስቲቫሉ የመዝጊያ ስነስርዓት ላይ ተገኝተው ሽልማቱን ተቀብለዋል፡፡
በሰንዳንስ አለማቀፍ የፊልም ፌስቲቫል ላይ በመካፈል የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ፊልም የሆነውና በተለያዩ የአሜሪካ ሲኒማ ቤቶች ተዘዋውሮ ሲታይ የሰነበተው ድፍረት፣ በተመልካቾች ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነት በማግኘቱ ነው በዘርፉ ተሸላሚ ለመሆን የበቃው፡፡
ከፊልሙ ኤክስኪዩቲቭ ፕሮዲዩሰሮች አንዷ የሆነችው ታዋቂዋ የሆሊውድ የፊልም ተዋናይት አንጀሊና ጆሊ፣ ከሳምንታት በፊት ድፍረት በኢትዮጵያ የፊልምና የኪነጥበብ ዘርፍ ላይ የራሱን አሻራ ያሳረፈ ስራ ነው ስትል አድናቆቷን መግለጧ ይታወሳል፡፡

        በአፍሪካ ፖለቲካዊና የውጭ ግንኙነት ጉዳዮች ላይ በርካታ መፅሃፍትን በመፃፍ የሚታወቁት የፖለቲካ ተመራማሪው ዶ/ር ዴቪድ ሆይሌ “አለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ የአውሮፓ ጓንታናሞ ቤይ?” የተሰኘ መፅሃፍ ለንባብ አበቁ።
ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤቱ አፍሪካን ዳግም በቅኝ ግዛት ለመያዝ ታልሞ የተቋቋመ አውሮፓዊ ፍ/ቤት ነው የሚሉት ዶ/ር ዴቪድ፤ አውሮፓ ከ120 ዓመታት በኋላም በተቋሙ አማካይነት አፍሪካውያንን ለመዝረፍ እየሞከረች ነው ብለዋል።
“አውሮፓውያን፤አፍሪካንና ሌሎች ታዳጊ ሃገራትን በዘመናዊ ባርነት ለመግዛት እንዲሁም  ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ሉዓላዊነታቸውን ለማሳጣት የሚጠቀሙበት መሳሪያ ነው” በማለት መፅሃፉ ዓለም አቀፉን የወንጀለኞች ፍ/ቤት ያብጠለጥላል።
ባለፈው ሳምንት  በመዲናችን በተካሄደው 22ኛው የአፍሪካ መሪዎች ጉባዔ ላይ የተመረቀውን የዶ/ር ዴቪድ መፅሃፍ ያሳተመው የአፍሪካ የጥናትና ምርምር ማዕከል እንደሆነ ታውቋል። የመጽሐፉ ዋጋ  14.99 ዶላር  ነው፡፡ ዶ/ር ዴቪድ ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ አምስት መፅሃፍትን ያሳተሙ ሲሆን በቅርቡም የአሁኑ መፅሃፍ ተከታይ ለንባብ እንደሚበቃ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በኢትዮጵያ የኢራን ኢምባሲ የባህል ክፍል የሚዘጋጀው አመታዊው የኢራን የፊልም ፌስቲቫል ካለፈው ሰኞ ጀምሮ በብሄራዊ ትያትር ተካሄደ፡፡
የኢራንን እስላማዊ አብዮት 35ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የተከናወነው ይህ የፊልም ፌስቲቫል፣ የሁለቱን አገራት ባህላዊ ግንኙነት የማጠናከርና የኢራን የፊልም ኢንዱስትሪ የደረሰበትን ደረጃ የማስተዋወቅ አላማ እንዳለው በኢትዮጵያ የኢራን አምባሳደር አሊ ባህሪኒ በፌስቲቫሉ መክፈቻ ላይ ተናግረዋል፡፡ የኢራን ኢምባሲ የባህል ክፍል፣ በሁለቱ አገራት መካከል የተፈረመውን የባህል፣ የትምህርትና የሳይንስ ትብብር መሰረት በማድረግ የኢትዮጵያን ፊልም ለማሳደግ የሚያግዙ ስራዎችን እንደሚያከናውንም ገልጸዋል፡፡
ለሶስት ተከታታይ ቀናት በተካሄደው በዚህ የፊልም ፌስቲቫል ላይ፣ ‘ኤም ፎር ማዘር’፣ ‘ዘ ሶንግስ ኦፍ ስፓሮውስ’ እና ‘ኦን ፉት’ የተሰኙ፣ በአለማቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያገኙ ስኬታማ የኢራን ፊልሞች ለእይታ በቅተዋል፡፡

          በኢትዮጵያ እግር ኳስ የሰሞኑ አበይት መነጋገርያ አጀንዳ የ62 ዓመቱ ሰውነት ቢሻው ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት መነሳታቸው ነበር፡፡ ሰውነት ከሃላፊነታቸው ከተነሱ በኋላ ለሱፕር ስፖርት አስተያየት ሲሰጡ ለስንብታቸው በፌደሬሽን ላይ ያቀረቡት ቅሬታ የለም፡፡ በስንብታቸው ማግስት ከዋልያዎቹ በኋላ ዋንኛው ትኩረታቸው ከቤተሰባቸው ጋር ማሳለፍ እንደሆነ የተናገሩት ሰውነት ቢሻው አሰልጣኝነት የማይተውት ሙያቸው እንደሆነ በመግለፅ በአገር ውስጥ የሚወዳደሩ ክለቦችን ወይንም በአፍሪካ ደረጃ ብሄራዊ ቡድኖችን ለማሰልጠን ፍላጎት እንዳላቸው ገልፀዋል፡፡
‹‹የአሰልጣኝነት ስራ አስቸጋሪ እና ምስጋና የሚያሳጣ ነው፡፡ የምትወደደው በከፍተኛ ደረጃ ውጤታማ ስትሆን ብቻ ነው፡፡ በህይወት ውስጥ በተለያዩ  ሁኔታዎች ሊያጋጥሙ የሚችሉ ውጣውረዶችን በፀጋ መቀበል ያስፈልጋል፡፡ መባረሬ ድንገተኛ ዜና አልሆነብኝም። በደቡብ አፍሪካ ከተደረገው የቻን ውድድር ስንመለስ ከመቅፅበት ሁኔታዎች ሲቀየሩ አስተውያለሁ፡፡ ከስንብቱ በፊት ተዘጋጅቶ በነበረው የግምገማ መድረክ፤ በብሄራዊ ቡድኑ የነበሩ ችግሮችን አስረድቼ ነበር፡፡ ይሁንና ቡድኑ በቻን ተሳትፎው ለገጠመው ውጤት ማጣት እኔ ምክንያት እንደሆንኩ አስቀድሞ የተወሰነ ነበር፡፡ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በነበረኝ ሃላፊነት ባስመዘገብኳቸው ውጤቶች እኮራለሁ፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ላገኛቸው ስኬቶች 100 ፐርሰንት ብቃቴን በመስጠት አገልግያለሁ፡፡ ›› በማለት አሰልጣኝ ሰውነት ለሱፕር ስፖርት የስንብት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡
ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከተሰናበቱ በኋላ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው  የት ይሄዳሉ የሚል ጥያቄ መነሳት ጀምሯል፡፡ አሰልጣኙ በዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የደርሶ መልስ ትንቅንቅ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በናይጄርያ ከተሸነፈ በኋላ በማግስቱ ወደ ጊኒ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ሊሄዱ ነው ተብሎ ተወርቶ ነበር። በዚሁ ጊዜም አሰልጣኙ አገሬን ትቼ የትም አልሄድም፤ በብዙ ሺ ዶላሮች እንድሰራላቸው የጠየቁኝ ነበር ግን አልተቀበልኳቸውም፤ ፍላጎቴ በኢትዮጵያ መቀጠል ነው ብለው አስተባብለው ነበር፡፡ ከሳምንቱ አጋማሽ ስንብታቸው በኋላ ደግሞ ከቦትስዋና እግር ኳስ ፌደሬሽን ጋር ለአዲስ ስራ ግንኙነት ፈጥረዋል እየተባለ ነው፡፡
የዛሬ ሳምንት ቅዳሜ እለት በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ከተደረገው የግምገማና የምክክር መድረክ ከሁለት ቀናት በኋላ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ስራ አስፈፃሚ  ከቀኑ 9 ሰዓት እስከ ምሽቱ 4 ሰዓት ልዩ ስብሰባ አድርጓል። ስብሰባው በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና በረዳት አሰልጣኞቻቸው  ቀጣይ ሁኔታ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ከዚሁ የስራአስፈፃሚ ስብሰባ በኋላ በማግስቱ ረቡዕ ካሳንቺስ በሚገኘው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፅህፈት ቤት ስራ አስፈፃሚው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ ጠርቷል። ከቀኑ 10 ሰዓት የነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ በጣም በተጣበበ ጊዜ ቢጠራም በርካታ የስፖርት ጋዜጠኞች መገኘታቸውን ያደነቁት የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ መግለጫው በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኞች  ስንብት ላይ ያተኮረ መሆኑን በይፋ ገልፀዋል። ከኤሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል የግምገማ እና የምክክር መድረክ፤ ከማክሰኞው የስራ አስፈፃሚ ስብሰባ እስከ ረቡዕ ጋዜጣዊ መግለጫ የነበሩትን ሁኔታዎች ከዚህ በታች እንደቀረበው ተዳስሰዋል፡፡
ሰውነትና ዋልያዎቹ በባለድርሻ አካላት ሲገመገሙ
ከሳምንት በፊት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን በተዘጋጀው የግምገማ እና የምክክር መድረክ ላይ ከ59 በላይ የስፖርት ጋዜጠኞች መገኘታቸው ያለምክንያት አልነበረም፡፡ በእለቱ  በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና በብሄራዊ ቡድናቸው ላይ የሚደረገው ግምገማ የመጨረሻ ውጤት የሚዲያውን ትኩረት የሳበው ጉዳይ ነበር፡፡ በሙሉ ቀን በተካሄደው የግምገማ እና የምክክር መድረክ ላይ የስፖርት ኮሚሽን ተወካዮች፤ የሙያ ማህበራት ተወካዮች፤ የክለብ አመራሮች፤ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ስራ አስፈፃሚ አባላትና  ባለሙያዎችና በስፖርቱ ላይ ያገባኛል የሚሉ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ በመክፈቻ ንግግር ባስጀመሩት በዚህ ስብሰባ ላይ በጠዋት ፕሮግራም የፌደሬሽኑ ዋና ፀሃፊ የአስተዳደር ዘርፍ ካቀረቡት ሪፖርት በኋላ በቴክኒኪ ኮሚቴ ሰብሳቢው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን የነበረውን ተሳትፎ በቁጥሮች የመዘነ ግምገማ ተሰጥቷል፡፡ በመቀጠል የቀረበው ደግሞ የቻን ተሳትፎ እንዴት እንደነበር የሚያብራራ የሰውነት ቢሻው መግለጫ ነበር፡፡ በእለቱ የነበሩ ጋዜጠኞች እነዚህ መግለጫዎች ሲቀርቡ ተከታትለዋል፡፡ የአስተዳደር ዘርፉ ሪፖርት የ2 ዓመት ተኩል ስራን በአጭሩ የተነተነ ነበር፡፡ ሪፖርቱ በሰውነት ቢሻው ዘመን የነበረው  ብሄራዊ ቡድን አጠቃላይ የአስተዳደር እና የፋይናንስ ሂደት በአጭሩ መግለፁን የታዘቡ አንዳንድ ጋዜጠኞች የአሰልጣኙ መሰናበት ፍንጭ ነው ብለው ነበር፡፡ በአንፃሩ የሚዲያ ባለሙያዎች በቴክኒክ ኮሚቴው ግምገማ ብሄራዊ ቡድኑን በመዘኑ በቁጥሮች መወሳሰብ ግራ ተጋብተዋል፡፡ የቴክኒክ ኮሚቴው አሰልጣኙን ከውድድር በኋላ ከመተቸት ከውድድሩ በፊት በቂ መረጃ  በመስጠት ለምን አልሰራም በሚል ቁጭት ብዙዎች ግምገማውን አልተማረኩበትም፡፡ ከዚያ በኋላ ግን የዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው አስገራሚ ማብራርያን ሁሉም ባለድርሻ አካል በትኩረት አዳምጦታል፡፡ ሰውነት በግምገማው መድረክ ያቀቡትን መግለጫቸውን ሲጨርሱ ከብሄራዊ ቡድን ጋር በመስራት ለመቀጠል ያላቸውን ፍላጎት በመግለፅ ነበር፡፡ ለጋዜጠኞች ከአሰልጣኙ ማብራርያ ቀልባቸውን የወሰደው በብሄራዊ ቡድኑ ውጤት ማጣት ተጠያቂ ነኝ ብለው በልበሙሉነት መናገራቸው ነበር፡፡  ይሁንና ዓላማቸው የነበሩትን ልጆች በመያዝ እና አዳዲስ ተተኪዎችን በመፈለግ ብሄራዊ ቡድኑን ለቀጣዩ የሞሮኮው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማሳለፍ እንደሆነ ሲናገሩ ግን ማጉረምረም ነበር፡፡  ፌደሬሽኑ የግምገማ እና የምክክር  መድረኩን ያዘጋጀው በቅርቡ ይፋ ለሚያደርገው የ5 ዓመት መሪ ስትራቴጂክ እቅድ ግብዓት የሚሆኑ ሃሳቦችን ለማግኘት አስቦ መሆኑን በመግለፅ ሚዲያዎች በቡድን ለሚደረገው ምክክር እንዲሳተፉ ጋብዞ ነበር። ጋዜጠኞች በመድረኩ መሳተፋቸው ተገቢ አለመሆኑን አምነውበት ሳይሳተፉ ቀርተዋል፡፡
በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ዋና ፀሃፊ አቶ ይግዛው በቀረበው የአስተዳደር ዘርፍ ሪፖርት መንግስት በስፖርቱ እየተጫወተ ያለውን ወሳኝ ሚና ጎልቶ ወጥቷል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባለፉት ሁለት ዓመታት ተኩል በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ እና ዋና ውድድር፤ በዓለም ዋንጫ 3 ዙር የማጣርያ ምእራፎች፤ በሴካፋ እና በቻን ውድድሮች በነበረው ጉዞ ፌደሬሽኑ በአስተዳደራዊ ዘርፉ ካከናወናቸው ተግባራት የትጥቅ ድጋፎች እና ማበረታቻ ሽልማቶች ዋናዎቹ ነበሩ፡፡ ዋና ፀሃፊው አቶ ይግዛው ለአሰልጣኞች፤ ለተጨዋቾች፤ ለቡድን መሪዎች፤ ለልዑካኖች እና ልዩ ልዩ አስተዋፅኦ ላደረጉ ሰዎች በድምሩ 14 ሚሊዮን 875ሺ ብር ወጭ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡ ዋና ፀሃፊው አልገለፁትም እንጂ ብሄራዊ ቡድኑ በነበረው ስኬት በስፖንሰርሺፕ፤ በገቢ ማሰባሰብ እና በተለያዩ እንቅስቃሴዎች የተገኘው ብር ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ ነበር፡፡ ባለፈው ሁለት ዓመት ተኩል ብሄራዊ ቡድኑን በስፖርት ትጥቆች አቅርቦት አለመቸገሩን  የገለፁት ዋና ፀሃፊው ፤ ለብሄራዊ ቡድኑ ከፌደራል ስፖርት ከ1060 በላይ የተለያዩ ትጥቆችን፤ ከኦሎምፒክ ኮሚቴ 236 ቱታዎች መገኘቱን በመጥቀስ መንግስት በፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን በኩል   ለብሄራዊ ቡድኑ የማበረታቻ እና የምስጋና  ድጋፎችን በመስጠት የነበረው ትኩረት የሚመሰገን ነውም ብለዋል፡፡ በብሄራዊ ቡድኑ ስኬት የገቢ ምንጮቹን ያሰፋው ፌደሬሽኑ 1116 የስፖርት ቱታዎች ከ886ሺ በላይ በማውጣት ገዝቷል ፤ ብሄራዊ ቡድኑ በልምምድ ስፍራ እንዳይቸገር፤ በመኝታ እና በምግብ  ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት ሲያገኝ እንደነበርም  ዋና ፀሃፊው አቶ ይግዛው ገልፀዋል፡፡ በአስተዳደራዊ ዘርፍ የተፈጠረው ችግር የቡድን መሪዎች በየጊዜው እና በዘፈቀድ ሲቀያየሩ ከመቆየታቸው በተያያዘ እንደነበር ዋና ፀሃፊው አቶ ይግዛው በሪፖርታቸው አንስተዋል፡፡  ይሄው ዝርክርክ የፌደሬሽን አሰራር ታሪካዊ ቀውስ አስከትሏል፡፡ በዓለም ዋንጫ ማጣርያ ብሄራዊ ቡድኑ  በቢጫ ካርድ ቅጣት መሰለፍ ያልነበረበት ተጨዋች አጫውቶ በሰራው ጥፋት ለ3 ነጥብ መቀነስና ለገንዘብ ቅጣት መብቃቱ በአስተዳደር ዘርፉ የታየ የአሰራር ችግር  ነበር ብለዋል፡፡
“በቻን ውድድር ኢትዮጵያን ወክሎ የቀረበው የሰውነት ቡድን ፋውል የሚያበዛ፤ የግብ እድሉን የማይጠቀም፤ የአካል ብቃት ችግር የታየበት፤ በስነልቦና ያልጠነከረ፤ በደንብ ያልተዘጋጀ ነበር”  በማለት አሰልጣኙን በመተቸት የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ በግምገማው መድረክ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን የነበረውን ተሳትፎ በቁጥሮች ላይ በተመሰረተ ሪፖርት ፈትሸዋል ፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ በቻን ተሳትፎው በመብቃቱና በአህጉራዊ መድረክ ያለበትን ደረጃ በማሳየቱ ተጠቃሽ ውጤት መሆኑን የገለፁት ባለሙያው ለወጣቶች መነቃቃት የነበረው አስተዋፅኦ ትልቅ ጥንካሬ እንደሆነና የዜጎች መነጋጋርያ አጀንዳ መሆኑ ይደነቃል ብለዋል፡፡ የብሄራዊ ቡድኑ ድክመቶች በሁለት ነጥቦች እንደሚጠቃለሉ የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ ሲያስረዱ፤ የመጀመርያው በቻን ተሳትፎ ዋና አሰልጣኙ እና ረዳቶቻቸው ለወጣት እና ተተኪ ተጨዋቾች እድል አለመስጠታቸው በብሄራዊ ቀጣይ እድገት ተፅእኖ የሚፈጥር መሆኑን ባለመረዳት ነው ብለው፤  በሌላ በኩል የብሄራዊ ቡድኑ የተፎካካሪነት ብቃት በውጤት የታጀበ አለመሆኑ በግልፅ ከብዙ ችግሮች ጋር ታይቷል ብለዋል፡፡
የቴክኒክ ኮሚቴው ግምገማ  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን ተሳትፎው ከሊቢያ፤ ከኮንጎ እና ከጋና ጋር ባደረጋቸው ጨዋታዎች ከ3ቱ ቡድኖች በድምር የሚበልጥ ፋውል እንደሰራ፤ የግብ እድሎችን መጠቀም እንዳልቻለ፤ በኳስ ቅብብል ረገድ ውጤታማ ያልሆኑ እንቅስቃሴዎችን እንዳበዛ፤ በአጨዋወቱ ኳስ ወደ ኋላ በመመለስ መጥፎ አዝማሚያ እንዳሳየ፤ በመከላከል ላይ የጥንቃቄ ጉድለት እና ድክመት እንዳለበት፤ ኳስን በጭንቅላት መግጨት እና የተቃራኒ ቡድን ኳሶችን ከአደጋ ነፃ እንደማያወጣ፤ በመስመር ብዙም እንደማይጫወት አመልክቷል። የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ በአጠቃላይ አሰልጣኞች ለብሄራዊ ቡድን በመረጧቸው ተጨዋቾች መሄድ የሚገባቸውን እድል ነፍገው የማይገባቸውን ማሰለፋቸው ዋና ስህተት እንደነበር ሲገልፁ፤ የተጨዋቾች የአካል ብቃት  አለመሟላትና ለስነልቦና ችግሮች መጋለጥ የቡድኑን አቅም ያቃወሱ ምክንያቶችእንደነበሩም ተረድተናል ብለዋል፡፡ አሰልጣኞች ቡድኑን በብቃት እንዳላዘጋጁ፤ ለዝግጅታቸውም ከክለቦች ጋር በቅንጅት ስለማይሰራ በቡድኑ ብቃት ላይ ተፅእኖ መፍጠራቸውንም የቴክኒክ ኮሚቴው ግምገማ አብራርቷል፡፡
ለሰውነት ምስጋና ይግባቸው
የፌደሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ እንደገለፁት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና ረዳቶቻቸው ቡድኑን ተረክበው ባገለገሉበት ባለፈው ሁለት ዓመት ተኩል እግር ኳሱን ያነቃቁ በርካታ ውጤቶች እና ለውጦች ተመዝግበዋል፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ከ31 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ መብቃቱ  የመጀመርያው ድንቅ ስኬት እና አበይት የታሪክ ምእራፍ ነበር፡፡ ለ20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ እስከመጨረሻው የማጣርያ ምዕራፍ በመጓዝ ብሄራዊ ቡድኑ ከአፍሪካ 10 ምርጥ ቡድኖች ተርታ መግባቱም ይታወሳል፡፡  በአፍሪካ አገራት የእግር ኳስ ሻምፒዮንሺፕ ቻን ውድድር ኢትዮጵያ ለመጀመርያ ጊዜ መሳተፏም ተጠቃሽ ስኬት ነበር፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ባለፈው ሁለት ዓመት ከመንፈቅ ባስመዘገበው ውጤት በ2015 የአፍሪካ ዋንጫ ያለቅድመ ማጣርያ በቀጥታ ለምድብ ማጣርያ የመወዳደር እድልም አግኝቷል፡፡  
አቶ ጁነዲን ባሻ ባለፈው ሁለት ዓመት ተኩል የተገኘውን ስኬት ባጠቃለለ ንግግራቸው ‹‹ ለብዙ ዘመናት ብሄራዊ ቡድኑ ብዙ ጎል የሚገባበት፤ ተከታታይ ሽንፈቶችን የሚያስተናግድ፤ እናሸንፋለን ብለን በአዕምሯችን እንዳናስብ ያደረገን ነበር፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውና መላው ቡድናቸው ይህን የቀየረ ውጤት አስመዝግበዋል፡፡ የኢትዮጵያን ህዝብ የእግር ኳስ ስሜት አነቃቃትዋል፤ ወደ ስታድዬም  እንዲመጣ አድርገዋል፤ ኢትዮጵያ ታሸንፋለች ተብሎ መታሰብ እንዲጀምር አስችለዋል፡፡  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ማልያ ከዳር እስከዳር እንዲለበስም ምክንያት ሆነዋል፡፡›› በማለት  ምስጋና አቅርበዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በኢትዮጵያ እግር ኳስ በፈጠሩት መነቃቃት እንደ ብሄራዊ ጀግና የሚታዩ ታላቅ ሰው መሆናቸውን በድፍረት መናገር ይቻላል፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ከፍተኛውጤት አላቸው። በ50ሺህ ብር ወርሃዊ ደሞዛቸው ከፍተኛው ተከፋይ ነበሩ።
በሰውነት የስራ ዘመን በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ትልቁ ስኬት ከመመዝገቡም በላይ የአገሪቱ የእግር ኳስ ደረጃ ተሻሽሏል፤ ከዋልያዎቹ መካከል አንዳንዶቹ ወደ 6 የተለያዩ አገራት ወደ የሚገኙ ክለቦች በመሰማራት በዝውውር ገበያው ተፈላጊነታቸው ጨምሯል፡፡
የሰውነት መሰናበቻ ምክንያቶች
ስራ አስፈፃሚው በዋና አሰልጣኙ ሰውነት ቢሻው እና በረዳቶቻቸው ለተገኙ ውጤቶች ክብርና ምስጋና እንደሚገባ ቢገልፅም በብሄራዊ ቡድኑ ቀጣይ ጉዞ ላይ ባደረገው ልዩ ስብሰባ የተገኘውን ውጤት ለማስቀጠል እንቅፋት የነበሩ ድክመቶችን መርምሯል፡፡ በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የሚመራው ብሄራዊ ቡድን ከናይጄርያ ጋር ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ ባደረጋቸው ሁለት ጨዋታዎች የባከኑ እድሎች ነበሩ፡፡ ከዚያም ኬንያ ባዘጋጀችው የሴካፋ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ቡድን ለዋንጫ ተጠብቆ ከምድቡ በጊዜ የተሰናበተበት ሁኔታም ብዙ ጥያቄዎችን ፈጥሯል። በመጨረሻም  በደቡብ አፍሪካው የቻን ውድድር ቡድኑ በነበረው ተሳትፎ ደካማ አቋም ማሳየቱ እና የፉክክር ደረጃው ኋላቀር መሆኑ መረጋገጡ ሁሉንም ያሳሰበ ነበር።  ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ብሄራዊ ቡድን ዳግም ወደሽንፈት መመለሱን የፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ሲታዘብ ቆም ብሎ ማሰብ እንዳስፈለገው የተናገሩት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ የኢትዮጵያ እግር ኳስ በቀጣይ ወዴት ያመራል፤ መንግስት እና ህዝብ ከስፖርቱ ምን ለውጥ ይፈልጋሉ የሚለውን መክረንበት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና ረዳቶቻቸው በብሄራዊ ቡድኑ ያላቸው ቆይታ ማብቃት እንዳለበት ከውሳኔ ላይ ደርሰናል ብለዋል፡፡
አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ከስራ እንደተሰናበቱ የተገለፀላቸው   በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ሃላፊዎች፤ የሚዲያ ባለሙያዎች እና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት የግምገማ መድረክ ላይ በሃላፊነታቸው ስለመቀጠል ፍላጎታቸው ከተናገሩ 3 ቀናት በኋላ ነበር፡፡ አሰልጣኞቹ መሰናበታቸውን ካወቁ በኋላ ውይይት ተደርጎ በተሰራው ሁሉም መደሰቱን፤ ግንኙነታቸው እንደሚቀጥል፤ ከስፖርቱ ጎን በመሆን እንደሚቀጥሉ ቃል መግባታቸው ተነግሯል፡፡
‹‹ሰዎች ጥሩ ይሰራሉ፡፡ ጊዜዎች ይቀያየራሉ፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና ረዳቶቻቸው በዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ደርሶ መልስ ፍልሚያ ከናይጄርያ ጋር፤ በሴካፋ እና በቻን ውድድሮች ይዘው በቀረቡት  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የማሸነፍ ስሜት ቀነሰ፤ የውጤት ማጣት ተከታታለ፤ በእርግጥ ተጨዋቾችም አሰልጣኞችም በጨዋታዎቹ የተቻላቸውን ሁሉ አድርገዋል፡፡ በክለቦች መካከል ያለው ውድድር አለማደጉ፤ በታዳጊዎች ላይ የሚሰሩ ተግባራት ያልጠነከሩ መሆናቸው፤ እና የአደረጃጀት እና የአሰለጣጠን ብቃት አለማደግ ለብሄራዊ ቡድኑ ድክመት የሚጠቀሱ ምክንያቶች ናቸው፡፡ የውጤት ማጣቱ አዝማሚያ የመጣው ባለንበት ልክ እና ደረጃ ነው። እግር ኳስ ያለበትን ደረጃ ቆም ብለን ማሰብ ነበረብን ›› በማለት ለታሪካዊው ውሳኔ ያደረሱ ዝርዝር ሁኔታዎችን አቶ ጁነዲን ባሻ ገልፀዋል፡፡
 በፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ በኩል ብሄራዊ ቡድኑ በመቀጠል በ2015 በሞሮኮ ለሚዘጋጀው የአፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፍ ይፈለጋል፡፡  በታዳጊ እና ወጣት  ቡድኖች አህጉራዊ ውድድሮች ንቁ ተሳታፊ የመሆን ፍላጎትም አለ። የስፖርቱ ባለድርሻ አካላት ለለውጥ ተነሳስተው በዘላቂ ልማትና የእድገት ሂደት  እንዲሰሩ የማስተባበር እቅድም አለ፡፡ በአጠቃላይ የአሰልጣኝ ሰውነት ስንብት ስራውን ከጀመረ 4 ወራት የሆነው የፌዴሬሽን አመራር አዲስ የለውጥ ምእራፍ መክፈቱን ያበሰረበት ነበር፡፡
የአሰልጣኞቹ የኮንትራት ውል መቋረጡ ትልቅ ውሳኔ በመሆኑ በግልፅ መታወቅ አለበት ያሉት ጁነዲን ባሻ፤ አሰልጣኞች ስራቸውን ራሳቸው አልለቀቁም ወይም በክፉ ስሜት አልተሰናበቱም ብለዋል፡፡ ዋና አሰልጣኙና ረዳቶቻቸው በማንኛውም የሰራተኛ ህግ መሰረት ስንብታቸው እንደሚከናወን የገለፁት የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት በክብር እና በምስጋና ይሸኛሉ እንጂ የካሳ ክፍያ የላቸውም ብለዋል፡፡ የስራ አስፈፃሚው አሰልጣኞቹን ለመቀየር መወሰኑን በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ሲገልፅ ሌላው የፌደሬሽን ዝርክርክ አሰራርም ተጋልጧል፡፡ የአሰልጣኞቹ የቅጥር ኮንትራት ጉዳይ ነው፡፡ የአንዱ በጥቅምት፤ የሌላው በህዳር የሌላው በታህሳስ ውል የሚያበቃበት ነበር ያሉት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ የቅጥር ኮንትራት በግልፅ የሚታወቅ መሆን ቢኖርበትም አሰልጣኞቹ ኮንትራታችሁ አልቋል ብለንና ኮንትራታቸውን አቋርጠን ለማሰናበት ያልፈለግነው፤ የቡድኑን የስራ ስሜት ላለማመሳቀል እና ላለመረበሽ በመወሰናችን ነበር ብለዋል፡፡ አሁን በስልጣን ላይ ያለው ፌደሬሽን ሃላፊነቱን ከተረከበ ከ3 ቀናት በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ወደ ዓለም ዋንጫ ለማለፍ የደርሶ መልስ ማጣርያውን ከናይጄርያ ጋር በአዲስ አበባ ይጀምር ነበር። በሴካፋና በቻን ውድድሮች ከዚያ በኋላ  በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ መደረጋቸውን በማገናዘብ ይሆናል፡፡ ሆኖም ግን  በተለይ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የቅጥር ኮንትራት ውል ጥቅምት 28 አብቅቶ በይፋ ኮንትራራታቸው እንደተራዘመ ሳይገለፅ እስከ ታህሳስ 28 እየሰሩ እንዲቀጥሉ መደረጉ ፌደሬሽኑን ያስተቸዋል፡፡  
አሰልጣኞቹ እንዲሰናበቱ የተደረገው በሴካፋ እና በቻን ውድድሮች ላይ ባሳዩት ድክመት ብቻ እንዳልሆነ በመግለጫው የተናገሩት ሌላው የፌደሬሽኑ  የስራ አስፈፃሚ አባል እና ምክትል ፕሬዝዳንት የሆኑት  አቶ ተክለወይኒ ናቸው፡፡ በቻን ውድድር የኢትዮጵያ ቡድን ለዋንጫው ትልቅ ግምት ተሰጥቶት እንደነበር ከናይጄርያ እና ጋና ተርታ ይጠቀስ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ተክለወይኒ፤ ይህን በመንተራስ የፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ከአሰልጣኞቹ፤ ከረዳቶቻቸው እና ከተጨዋቾች ጋር ሲመካከር በቻን ያለው ግብ ዋንጫ ማምጣት ወይም ግማሽ ፍፃሜ መድረስ እንደሆነ ገልፆላቸዋል፡፡  የቡድኑ አባላት ይህን ግብ ለማሳካት ስንት ሽልማት ይጠብቀናል ብለው ሲደራደሩ ደህና ሽልማት ታገኛላችሁ ብለን ተማምነን ነበር ብለዋል፡፡  ከቻን ጉዞ በፊት በነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ ዋና አሰልጣኙ ዋንጫ ለማምጣት ወይም ግማሽ ፍፃሜ ለመድረስ ቃል የገቡትን ካልሆነ ተሸንፎ መመለስ የሚለውን ጨመሩበት፡፡ ተገቢ አልነበረም፡፡ ‹‹በቻን ውጤት ላይ ያደረግነው  የውስጥ ግምገማ ብሄራዊ ቡድኑ ለተሰጠው ግምት በቂ ጥረት አላደረገም ነው፡፡ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ አካላት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአፍሪካ ደረጃ በተሳተፈባቸው ውድድሮች ጥሩ መጫወቱን ገልፀውልናል፡፡ ጎንለጎን ግን የቡድኑ ደረጃ ደካማ እንደሆነና የተፎካካሪነት ብቃቱም መሻሻል እንደሚያስፈልገው መክረውናል፡፡ ስለሆነም የአሰልጣኞቹ መቀየር አስፈልጓል›› በማለት አቶ ተክለወይኒ ማብራርያ ሰጥተዋል፡፡  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በየጨዋታው ብዙ የግብ እድሎች አምልጦታል፤ ተጨዋቾቹ ጥሩ ቢጫወቱም ውጤት ግን አላገኙም፤ ለውድድሮቹ በአሰልጣኞቹ የተደረገው ዝግጅት በፕሮፌሽናል መንገድ አልነበረም። ይህ ሁሉ ዝርዝር ምክንያት የፌደሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክለወይኒ ትልቅ ክፍተት ብለውታል። ‹‹ያሉብን ክፍተቶች የማይስተካከሉ ከሆነ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚፈልገው ውጤት መቼም ሊሳካ አይችልም ስለዚህም ስርነቀል ለውጥ ያስፈልጋል በሚል ከመግባባት ላይ ደርሰናል ››ሲሉም ተጨማሪ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወቅታዊ ብቃት ላይ የፊፋ ባለሙያዎች ያደረጉትን ትንተና ለአሰልጣኞቹ መቀየር ተጨማሪ ምክንያት እንደነበር በመግለፅም  ለእግር ኳሱ ጠቅላላ ህዳሴ የሚያመጣ ስትራቴጂ እንደሚያስፈልግ ለታመነበት አቅጣጫ ውሳኔው አስፈላጊ ነበር ብለው ተናግረዋል፡፡
የሰውነት  ተተኪ ከየት? ከአገር ውስጥ ከባህር ማዶ
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ስራ አስፋፃሚ የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ቀላል ስራ አለመሆኑን ትልቅ ሃላፊነት እንደሆነ መገንዘቡን ሰሞኑን ገልጿል፡፡ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና የረዳቶቻቸውን ስንብት የወሰነው ግን በአጣብቂኝ ውስጥ ሆኖ ይመስላል፡፡ ስራ አስፈፃሚው በፕሬዝዳንቱ በኩል አሰልጣኞቹን ያሰናበትነው ሌላ አሰልጣኝ ለመቅጠር በመጓጓት ማለቱም ተስፋ ሰጪ አይመስልም፡፡ በአዲስ አሰልጣኝ ቅጥር ለኢትዮጵያ እግር ኳስ እድገት የሚመች አደረጃጀት ለመፍጠር መታሰቡን የገለፁት ፕሬዝዳንቱ ፤ ቦታውን ክፍት ማድረግ የመጀመርያው ተግባር እንደሆነ መታወቅ እንዳለበት በማስረዳት የህዝብ ጉዳይ ስለሆነ በግልፅ፤ ያለወከባ እና በጥንቃቄ ተገቢው መስፈርት ወጥቶ በሚደረግ ውድድር መሰረት የሚፈፀም እንደሚሆን ቃል ገብተዋል፡፡
የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ በአዲሱ አሰልጣኝ ቅጥር የመጀመርያ ሙከራ በአገር ውስጥ ያሉ ባለሙያዎችን ማሰስ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ከሰውነት ቢሻው ስንብት በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ጋር ስማቸው እየተያያዘ ካሉ የአገር ውስጥ አሰልጣኞች መካከል ስዩም ከበደ፤ ፀጋዬ ኪዳነማርያም እና ገብረመድህን ሃይሌ እና ሌሎችም ይጠቀሳሉ፡፡ የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት ለአሰልጣኙ ቅጥር ወደውጭ የምንወጣበት ሁኔታ ካለ የገንዘብ ምንጮቻችን በመፈተሽ የምናደርገው ይሆናል ሲሉም አስረድተዋል፡፡ የቀድሞው የጊዮርጊስ ክለብ አሰልጣኝ የነበረው፤ በሱዳኑ አልሂላል ክለብ የሰራውና በምስራቅ አፍሪካ ክለቦች ካለው ልምድ ባሻገር የሩዋንዳ እና የኡጋንዳ ብሄራዊ ቡድንን ያሰለጠነው ሰርቢያዊ ሰርዶጆቪች ሚሉቲን ሚቾ ከውጭ አሰልጣኞችቀድሞ ስሙ ተጠርቷል፡፡
በቀድሞው ፌደሬሽን የተገባላቸውቃል ሳይፈፀምላቸው ቅር ተሰኝተው የነበሩት ቤልጅማዊው ቶም ሴንትፌንትም እየተጠቀሱ ናቸው፡፡ ቶም ሴንትፌይት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ሃላፊነት ለመረከብ በይፋ ጥሪ በማክበር የመጀመርያ የውጭ አሰልጣኝ ናቸው።  ከቤልጅዬም ለሱፕር ስፖርት በሰጡት ማብራርያ ‹‹ሰውነት ቢሻው ለብሄራዊ ቡድን ባስገኘው ስኬት ምስጋና ይገባዋል። ረዳቴ ሆኖ አብረን ስንሰራ በነበረበት ወቅት እንደ አስራት መገርሳ እና ጌታነህ ከበደን የመሳሳሉ ተጨዋቾች ለቡድኑ በመምረጥ አስተዋፅኦ ነበረኝ። በእርግጥ አገሪቱን ለቅቄ የወጣሁት ከፌደሬሽኑ ጋር በተፈጠሩ አለመግባባቶች ነበር፡፡ ተመልሼ ብሄራዊ ቡድኑን የማሰልጠን እድል ባገኝ ብዙ ልሰጠው የምችለው ነገር አለ፡፡ በተለይ ዋልያዎቹ በትልልቅ ግጥሚያዎች የሚገጥማቸውን ፈተና የሚወጡበትን አቅም ማስተካከል እችላለሁ፡፡ የኢትዮጵያ ቡድን በፈጠራ እና በቴክኒክ የዳበረ ጥሩ አሰልጣኝ ካገኘ ምርጥ መሆን የሚችል ነው።›› በማለት ቶም ሴንትፌይት ለሱፕር ስፖርት ተናግረዋል፡፡
ፌደሬሽኑ የአሰልጣኙ ቅጥር በቀና መንገድ፤ አሳማኝ መመዘኛ እና መስፈርት ተዘጋጅቶ የሚከናወን እንደሆነ ሲያስታውቅ፤ ፍለጋውን በጋዜጦች ማስታወቂያዎችን በማውጣት፤ የተለያዩ ጥቆማዎችን ከባለድርሻ አካላት እና ከሙያተኞች በመቀበል፤ በብሮድካስት ሚዲያዎች በማስተዋወቅ ይሰራበታል ብሏል፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ እንደገለፁት በአሰልጣኝ አዲስ ቅጥር የማፈላለግ ተግባር ላይ  የቴክኒክ ኮሚቴ ሃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ ኮሚቴው በአንድ ሳምንት ጊዜ  ለሃላፊነቱ ብቁ የሆኑ ሰዎችን ዝርዝር እንዲያቀርብ ይጠበቃል፡፡
ቀጣዩን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ለመቅጠር ፌደሬሽኑ ያሰበው የህዝብ ፍላጎት አድጓል፤  ዓለም አቀፍ ደረጃ ይዘን ተፎካካሪ ሆነን እንቅረብ ከሚል አቅጣጫ በመነሳት ነው፡፡ ከአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው መሰናበት  በኋላ ግን ለብሄራዊ ቡድኑ የሚመጥን አሰልጣኝ ፍለጋው ፈታኝ እንደሚሆን  መገመቱ  ስጋትን የጋረጠ ሆኗል፡፡
በአገር ውስጥ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውን ተተኪ ለማግኘት አሁን ጊዜው የሚያስቸግር ይመስላል፡፡ ብቁ ናቸው የሚባሉ አሰልጣኞች በአመዛኙ  በብሄራዊ ቡድን ደረጃ ብዙም ልምድ የሌላቸው፤ የሙያ ብቃታቸው ያን ያህል የማያስመካ፤ አንዳንዶቹ በክለብ አሰልጣኝነት ሃላፊነታቸውን ለመልቀቅ የሚቸገሩ ናቸው፡፡ እነዚህ እና ሌሎችም ምክንያቶች ተተኪ አሰልጣኝ ከአገር ውስጥ የማግኘቱን እድሉን ያጠብበዋል፡፡ ከአገር ውጭ አሰልጣኝ ለመቅጠር ደግሞ ከዚህ በፊት ያሉ ተመክሮዎች የሁኔታውን አስቸጋሪነት በይበልጥ ያጎሉታል፡፡ ከአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በፊት ሁለት የውጭ አገር አሰልጣኞች ነበሩ፡፡  በትውልድ ናይጄርያዊ ሆነው ስኮትላንዳዊ ዜግነት ያላቸው አሰልጣኝ ኢፌም ኦኑራ እና ቤልጅማዊው ቶም ሴንትፌንት ናቸው፡፡
ሁለቱም አሰልጣኞች ከብሄራዊ ቡድን ጋር የነበራቸው ቆይታ አወዛግቧል፡፡ ከዚያ በፊት የነበሩትን ፈረንሳዊ አሰልጣኝ ዲያጎ ጋርዚዬቶ እና የፌደሬሽኑ እሰጥ አገባም በማስታወስ  ብዙ ልምድ መቅሰም ይቻላል፡፡ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ለማሰልጠን ብቁ ናቸው ተብለው ከውጭ የመጡ አሰልጣኞች ያለው መጥፎ አመላከት ካልተወገደ የሚያሳስብ ይሆናል፡፡ የውጭ አሰልጣኞች የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የማሰልጠን ሃላፊነቱ በምቹ ሁኔታ በነፃነት እንዲሰሩበት  የተሰጣቸው አልነበሩም፡፡ በቂ የስራ ጊዜ በኮንትራት ውላቸው አያገኙም ነበር፡፡  
ከአገር ውስጥ ባሉ አሰልጣኞች ምንም አይነት ክብር አይሰጣቸውም፤ ተባብሮ ከመስራት ይልቅ እንደውም ለውጥ አያመጡም በሚል አስተሳሰብ ዘመቻ ሲደረግባቸው አጋጥሟል፡፡ በሌላ በኩል ለአሰልጣኞቹ የሚከፈለው ደሞዝ እና ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ መጠየቁም ይፈትናል፡፡  ብዙውን ጊዜ የውጭ አገር አሰልጣኞች ቅጥር  ለማከናወንና ክፍያ በመፈፀም ፌደሬሽኑ እቅዱን  እውን የሚያደርገው ክቡር ሼህ አላሙዲ ድጋፍ ላይ በመተማመን ነበር። ክቡር ሼህ አላሙዲ ይህን አይነቱን ድጋፍ መስጠት ካቆሙ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ አስቀድመው የነበሩ ድጋፎችም በተለያዩ መንገዶች ሲመዘበሩ እና ሲባክኑ ማጋጠሙም ጥሩ ታሪክ አይደለም፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ በአሰልጣኞቹ የቅጥር ሁኔታ ላይ ፌደሬሽኑ ከየትኛው አካል ጋር ተመካክሮ እንደሚሰራ፤ በምን አይነት መስፈርት አወዳድሮ እንደሚቀጥር እና ለምን እንደቀጠረ በግልፅ ሁኔታ ያልተሰራበት ሆኖ መቆየቱን ማስታወስ ይቻላል። ሌላው ዋና አደጋ የውጭ አገር አሰልጣኞች ከተቀጠሩ በኋላ የሃላፊነት ቆይታቸው በአላስፈላጊ ጫናዎች ሲያጥር፤ በአሰለጣጠን ፍልስፍናቸው እና በቋንቋቸው ከብሄራዊ ቡድን ጋር መግባባት ሲያዳግታቸው፤ ከአገሪቱ ሚዲያዎች ጋር ተቀራርበው ለመስራት ሲቸገሩ እና ከፌደሬሽኑ አካላት ጋር መግባባት ሲሳናቸው እንደነበር ማስታወሱ ተስፋ ያስቆርጣል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአህጉራዊ እና በዓለም አቀፍ ውድደሮች በብቁ ተፎካካሪነት እንዲሳተፍ የሚያበቃውን ፕሮፌሽናል አሰልጣኝ  እንዴት ሊያገኝ ይችላል ብቻ ሳይሆን ከተገኘስ የሚጠይቀውን ውድ ክፍያ ማን ይችላል የሚሉ ጥያቄዎች ስጋት ይፈጥራሉ። የሊቢያን ብሄራዊ ቡድን በማሰልጠን በቻን ውድድር ዋንጫ ለማንሳት የቻሉት ፈረንሳዊው ሃቪዬር ክሌሜንቴ ደሞዛቸው እስከ 20 ሺ ዶላር ነው፡፡ በአጠቃላይ አንድ የውጭ አገር አሰልጣኝ ለመቅጠር በወቅቱ የገበያ ሁኔታ ኢትዮጵያ ከ15 እስከ 20 ሺ ዶላር በወር መክፈል ሊኖርባት ይችላል፡፡ ይህ ገንዘብ ታድያ ከየት ይመጣል፤ ከሼህ አላሙዲ ወይንስ ከመንግስት መልስ የሚያስፈልገው ጥያቄ ነው፡፡
ከሰውነት በኋላ ፌደሬሽኑ እና የህዳሴ ስትራቴጂው
በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል በተካሄደው የግምገማ እና የምክክር መድረክ ላይ ከፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት በመቀጠል የመክፈቻ ንግግር ያሰሙት የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ አንበሴ እንየው ነበሩ። ኮሚሽኑ እንደመንግስት የእግር ኳሱ ከፍተኛ ባለድርሻ አካል መሆኑን የጠቀሱት ምክትል ኮሚሽነሩ አቶ አንበሴ፤  እግር ኳስ አንጋፋ እና ፈርቀዳጅ ስፖርት እንደሆነ በመግለፅ የህዝብ አጀንዳና አንድ የልማት ጉዳይ ስለሆነ የግምገማ እና የምክክር መድረኩ በስፖርቱ ህዝብን የሚያስደስት እና የሚያረካ ውጤት ላይ ለሚደረስበት የለውጥ እንቅስቃሴ መነሻ መሆን አለበት ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በቀድሞው ፌደሬሽን አማካኝነት ከ2004 እሰከ 2007 በሚል የ3 ዓመት ስትራቴጂክ እቅድ ተዘጋጅቶ እንደነበር ያስታወሱት ምክትል ኮሚሽነሩ፤ በአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ውድድሮች ለመሳተፍ በሚል ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ በተወሰነ መልኩ እቅዱን ማሳካት መቻሉን አመልክተዋል፡፡ ወደፊትም በተሻለ ሁኔታ መሰራት ስላለበት  በአሁኑ ፌደሬሽንም በስትራቴጂክ እቅድ መመራት ያስፈልገዋል ብለዋል፡፡ አቶ አንበሴ እንየው እግር ኳስ የእድገታችን ልዩ መገለጫ መሆን አለበት የሚል ማሳሰቢያቸው  መንግስት ለስፖርቱ ከፍተኛ ትኩረት መስጠቱን ያረጋገጠ ነበር፡፡ በየክልሉ በርካታ ስታድዬሞች እየተገነቡ ናቸው፡፡ አካዳሚዎችም ተመስርተዋል፤ እየተሰሩም ናቸው፡፡  መንግስት በስፖርቱ ሊገኝ የሚችለውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እና የአገር መልካም ገፅታ ገብቶታል፡፡ የእግር ኳሱ ባለድርሻ አካላት በመንግስት በኩል ለስፖርቱ  የተሰጠውን ትኩረት ያህል ብዙ መስራት እንዳለባቸው መረዳት ይገባል፡፡
በእግር ኳስ ኢትዮጵያ አሸንፋ እንድትወጣ ሁሉም ይፈልጋል ያሉት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ በስፖርቱ ኢንቨስትመንት እስከዛሬ ከተደረገው የበለጠ ማሳደግ አለብን ይላሉ፡፡ እንደ ጋና አይነት አገራት በርካታ ታዳጊ ፕሮፌሽናሎችን በማፍራት በአሁኑ ጊዜ ከ354 በላይ ተጨዋቾች በላይ በመላው ዓለም በማሰማራት ከፍተኛ ተጠቃሚ መሆናቸውን ማጥናት እንደሚያስፈልግ ያስረዱት ፕሬዝዳንቱ ፤ ኢትዮጵያ ወጣት ፕሮፌሽናሎችን ለማውጣት ምን መስራት እንዳለባት፤ ስንት አካዳሚዎች ይበቁናል ስንት አካዳሚዎች አሉን እንዴት እንስራባቸው በሚል መንቀሳቀስ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
የስራ አስፈፃሚው እንደሚያስበው በኢትዮጵያ እግር ኳስ የወደፊት ጉዞ ላይ አሰልጣኝ መቀየር ብቻ ለውጥ አያመጣም፡፡ በእርግጥ የዋና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ቁልፍ ሃላፊነት ቢሆንም ጎን ለጎን በስፋት ለውጥ የሚያስፈልጋቸውም ሁኔታዎችም አሉ፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽን የማስፈፀም ብቃት እና አደረጃጀት ለውጥ እንደሚያስፈልግ ታምኖበታል፡፡ በወጣቶች አና ታዳጊዎች ላይ ባተኮረ ስትራቴጂ ከስርመሰረቱ ካልተሰራ አሰልጣኝ ተጨዋች ሊያገኝ አይችልም በሚል አስተሳሰብም ለውጥ ለመፍጠር ታስቧል፡፡ የስራ አስፈፃሚው አባላት እንደገለፁት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ላይ ስርነቀል ለውጥ ለማምጣት ለሚያስችለው ስትራቴጂክ እቅድ የባለሙያ ቡድን ተቋቁሞ ሰነዱ እየተዘጋጀ ነው፡፡  በየካቲት ወር ሰነዱ ሙሉ ተዘጋጅቶ የሚያልቀው ይህ የስትራቴጂ እቅድ በአምስት አመት መርሃ ግብር የተነደፈ መሆኑ ተገልፆ አሁን ያለው ፌደሬሽን በስልጣን ላይ በሚቆይባቸው ቀሪዎቹ 3 ዓመታት በስፋት እንደሚሰራበት፤ ለሚቀጥለው የፌደሬሽን አመራር የሚያወርሰው እንደሚሆንም ተስፋ ተደርጓል፡፡ የፌደሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክለወይኒ እንደገለፁት በዚሁ የስትራቴጂ ሰነድ ላይ ከ300 እስከ 400 የሚደርሱ ባለድርሻ አካላትን በማሰባሰብ ውይይት ለማድረግ ፍላጎት እንዳለ ጠቁመው በስትራቴጂክ እቅዱ መሰረት የብሄራዊ ቡድኑ አጠቃላይ አደረጃጀት እና መዋቅር፤ አሰራሩ፤ የሰው ሃይል አደረጃጀቱ በአጠቃላይ እንደሚገመገም እና በተገቢው  መንገድ ከተሰራበት ለውጥ መፍጠር እንደሚቻል ፅኑ እምነት አለን ብለዋል፡፡ በስትራቴጂክ እቅዱ የኢትዮጵያን እግር ኳስ ፕሮፌሽናላይዝድ ማድረግ ወሳኝ መሆኑን ስራ አስፈፃሚው ተስማምቶበታል፡፡
በዚህ የፕሮፌሽናሊዝም አቅጣጫ መሰረት የፕሪሚዬር ሊግ፤ የብሄራዊ ሊግ እና ሌሎች የወጣት እና ታዳጊ ውድድሮች ፕሮፌሽናላይዝድ ማድረግ እነደሚያስፈልግ፤ የክለቦችን አቅም እና አደረጃጀት በማሳደግ ፕሮፌሽናላይዝድ ሆነው እንዲንቀሳቀሱ ማስቻል እንደሚገባ እና የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት እንደከፍተኛ የሰው ሃይል በመጠቀም እግር ኳሱ እንደኢኮኖሚው አድጎ እንዲታይ መሰራት አለበት በሚል ነው፡፡ በወጣት እና በታዳጊ ፕሮጀክቶች፤ መንግስት፤ ክለቦች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በስፋት እንዲንቀሳቀሱም ይደረጋል፡፡
የፌደሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክለወይኒ ሃጎስ እንደሚናገሩት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ወደፊት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተፎካካሪ ሆኖ ለመቀጠል የሚችለው በእውቀት እና በስትራቴጂ እቅድ ሲሰራበት፤ የፕሮፌሽናሊዝም አቅጣጫዎችን ሲከተል ነው ፡፡ በዚህ ረገድ አሁን በስልጣን ላይ የሚገኘው የፌደሬሽን ስራ አመራር ብዙ ጥረት ማድረግ እንደሚጠበቅበትና ኢትዮጵያ ዛሬ በከፍተኛ ደረጃ የሚያፎካክረውን ስፖርት የሚመጥን ደረጃ አግኝታ እንደ ብራዚል ፤ እንደ ስፔን እና እንግሊዝ ተጠቃሚነት እንዲኖራት በመመኘት መስራት ያስፈልጋል በማለት ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡