Administrator

Administrator

አቶ ሀይለማርያም ወልዱ በቅርቡ “ህልፈተ አንጃ ወ ክሊክ ዘ ኢህአፓ” የሚል መፅሀፍ ለንባብ አብቅተዋል፡፡ ከመፅሀፉ ጋር በተያያዘ  የኢሕአሠ ቤዝ የነበረውን የኢሮብ ህዝብ አስመልክቶ ከአዲስ አድማስ ጋር ቃለምልልስ አድርገዋል፡፡



ኢህአፓ አለሁ ነው የሚለው፤ አንተ በመጽሐፍህ “ህልፈት አንጃ ወ ክሊክ ዘ ኢሕአፓ” በማለት ሞቷል ትላለህ፡፡
ይህ የብዙዎች ጥያቄ ነው፡፡ አለሁ የሚለው ወገን መኖሩን ማሳየት መቻል አለበት፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ (ኢትዮጵያ ውስጥ ነው ያለሁት) ኢትዮጵያ ውስጥ ኢህአፓ እንደ ድርጅት የለም ፣አመለካከቱ ራዕዩ አለ፡፡ የኢህአፓ ልጆች የታገሉለት ነገሮች በህገመንግስቱ ተረጋግጧል። አተገባበር ላይ “እንዴት ነው” ብትይኝ ሌላ ነገር ነው፡፡ በዚህ አይን ከታየ ኢህአፓ አለ፡፡ ከዚያ ውጪ ኢትዮጵያ ውስጥ ኢህአፓ እንደ ድርጅት የለም። ሜዳው ኢትዮጵያ ውስጥ ነው፤ ዳያስፖራ አለሁ ማለት የትም አያስኬድም፡፡
የበረሃ ስም እስኪለምዱት አይከብድም?
ምንም አይከብድም ግዴታ ነው፡፡ እኔን፤ ብርሃነመስቀል በዛብህ ነህ አለኝ፡፡ ተቀበልኩት። እሱን ክርስቲያን አካባቢ ሰለሞን፤ ሙስሊሞች አካባቢ ሱሌይማን እንለው ነበር፡፡
ከኢህአፓ ሠራዊት ከኢህአሠ የምታደንቀው የጦር መሪ ማን ነበር?
እኔ ጦርነት ላይ የመሳተፍ ዕድል አልነበረኝም፡፡ ሮባ ጥሩ ተዋጊ ነው ሲሉ ግን እሠማለሁ፡፡ ሠራዊቱ የምሁር ሠራዊት ነበር፡፡ ምሁር ሁለት ልብ ነው፤ ለጦርነት ምቹ አይደለም፡፡ እኔም ያው ነበርኩ፡፡
እስቲ ወልዱ ስለ ራስህ ንገረኝ
ትውልዴ ኢሮብ ነው፡፡ የተወለድኩት አሊቴና ነው፡፡  እስከ አስራ ሁለተኛ ክፍል የተማርኩት አዲግራት ነው፡፡ አዲስ አበባ በቀዳማዊ ሀይለስላሴ ዩኒቨርሲቲ ለሁለት አመት ተምሬያለሁ፡፡ በደርግ ዘመን ወደ ትግል ገባሁ፡፡ የመጀመሪያዎቹ የትግል አመታት ጥሩ አልነበሩም፡፡
ለምን የመጀመሪያዎቹ የትግል አመቶች ጥሩ አልነበሩም?
በአጭር ጊዜ ውስጥ ነው ደርግ እጅ ላይ የወደቅሁት፡፡ የድርጅቴን ስም አጋልጦ ላለመስጠት ራሴን ጀብሀ ነኝ አልኩ፡፡  የታሠርኩት አስመራ ውስጥ ስንበል የሚባል ቦታ ነበር፡፡ የተለመደው የደርግ ምርመራ ከተደረገብኝ በኋላ፣ ጉዳዬ ወደ ጦር ፍርድ ቤት ተላለፈ፡፡ በጦር  ፍርድ ቤት በመታየት ላይ እያለ  ወህኒ ቤት ሆኜ ጥሩ ነገሮችን አግኝቻለሁ።
ምን ጥሩ ነገር አገኙ?
በአጋጣሚ ከአዲስ አበባ የወህኒ ቤት አስተዳዳሪዎች ወደዚያ ሲመጡ የጠየቅሁት የመብት ጥያቄ (ት/ቤትና ላይብረሪ እንዲከፈት) ምላሽ በማግኘቱ፣ በእስረኞቹ ዘንድ ተቀባይነት እንዳገኝ አደረገኝ፡፡ ለእኔ የመጀመሪያ ሹመት ማለት ይቻላል። የእስረኞቹ ፀሐፊ ሆንኩ፡፡ ቋንቋ ተማርኩ፣ ብዙ መፃሕፍት አነበብኩ፡፡
ከመታሰሬ በፊት የነበረኝ የማርክሲዝም ዕውቀት ውሱን ነበር፡፡ ከታሠርኩ በኋላ ማርክሲዝም ሌኒኒዝም፣ ማኦይዝም ከዚያም አልፎ ስለ ፎኮይዝም፤ በደንብ በማንበቤ የቲዮሪ ትጥቅ አገኘሁ፡፡  ስለ ህቡዕ የፖለቲካ ድርጅት አሠራር በተግባር የተማርኩትም ወህኒ ቤት ነው፡፡ ከሁሉም ጋር በነበረኝ ግንኙነት የህዝባዊ ግንባር አይን ውስጥ ገባሁ፡፡ በተማርኩት መሠረትም የቤት ስራ ተሰጥቶኝ በብቃት ተወጥቻለሁ፡፡
የቤት ስራው ምን ነበር?
እስረኞችን ማስፈታት ነበር፡፡ ይሄን ያደረግሁት ከተራ ወታደር እስከ ሃላፊዎች ድረስ በድርጅት እንዲታቀፉ በማድረግ ነው፡፡ ኤርትራዊያኑን በኤርትራ ድርጅት ኢትዮጵያውያኑን በኢትዮጵያ ድርጅት፣ እንዲደራጁ በህዋስ ማዋቀር ነበር፡፡
ማን ነበር የመለመለህ?
አንዲት አዜብ የምትባል ልጅ ናት፡፡ አዲስ አበባ እንደምታውቀኝ ነግራኝ የመለመለችኝ፡፡ በኋላ ላይ ግን እሷን ያሠማራት ሰው አስመራ ውስጥ የታወቀ (ከ1966 እስከ 1983 ድረስ የፌዳይን መሪ የነበረ) ልጅ መሆኑን አወቅሁኝ፡፡ የበረሃ ስሙ ቫይናክ ይባላል፡፡
ቫይናክ በቅርብ በመኪና አደጋ ከሞቱት የኤርትራ ጀነራሎች አንዱ ነው አይደል?  ቫይናክ የተባለው ለምንድን ነው?
አዎ በቅርቡ ነው የሞተው፡፡ ቫይናክ ማለት የመድሃኒት ስም ነው፡፡ የራስ ምታት መድሃኒቶች ካፌኖል፣ ቫይናክ፣ አስፕሪን ናቸው፡፡ ቫይናክ እንግዲህ “አስቸጋሪውን የሚያስታግስ” ለማለት የወጣ ይመስለኛል፡፡
ኢሮብ የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ሠራዊት (የኢህአፓ ወታደራዊ ክንፍ) ይንቀሳቀስበት የነበረ ቦታ ነው፡፡ እስቲ ስለአካባቢውና ስለህዝቡ ንገረኝ…
ስለ ህዝቡ ማንነት የተለያዩ አፈታሪኮች አሉ። በአብዛኛው ተቀባይነት ያገኘው፣ አሁን ያለው የኢሮብ ህዝብ ከደጋ አካባቢ  ከውቅሮ በስደት መጥቶ ነው የሚለው ነው፡፡  በኔ እይታ ግን  እዚያ የቆየ ነው የሚሉትን እጋራለሁ፡፡ ምክንያቱም ቋንቋው ከኩሽ ቋንቋዎች የሚመደበው ሳሆ ነው፡፡ ይህ ቋንቋ ከአፋርኛ ጋር ከቀበሌኛ ልዩነት በስተቀር ይግባባል። በምስራቋ አፍሪካ የህዝቦች እንቅስቃሴ ነበር፡፡ በዚህ ውስጥ ግን የሚንቀሳቀሰው ወገን እምነቱንም ሆነ ቋንቋውን አይለቅም፡፡ እኔ ራሴን እንደሳሆ ነው የምቆጥረው፡፡ በሀይማኖት እስከ አስራ ስምንተኛው ክፍለ ዘመን ድረስ ሶስት ቤተክርስትያኖች ነበሩ፣ ህዝቡም ክርስትናን ተቀብሎ ነበር ይባላል፡፡ ነገር ግን የባህላዊ እምነት ተከታዮች ነበሩ፡፡ በየቦታው መስዋዕት የሚያደርጉባቸው ቦታዎች ነበሩ፡፡ ዝናብ ከጠፋ ላም ወይም  በሬ ስጋውን ትልቅ አምራ መጥቶ ሲወስደው መንፈስ ወሰደው ይህን የሚያሳይ እስከአሁን አሁንም ድረስ ህብረተሰቡ በዘፈኑ ላይ የሚያስገባው ሀረግ አለ፡፡ “አኸዬ ጉማይቶ” (“አሞራው ናና ውሰደው” ማለት ነው፡፡) ከዚያ ዝናብ ይመጣልናል ብለውም ያምናሉ፡፡
ቤተክርስቲያኖች አሉ ይባል እንጂ ቄሶች የሚመጡት ከጉንደጉንደ ነበር፡፡ ጉንዳጉንዲ ደቀ እስጢፋኖስ በመባል በሚታወቅ በ13ኛውና 14ኛው ክፍለዘመን አካባቢ በስራዬ የተጀመረ እንቅስቃሴ ውስጥ የነበሩ መነኮሳቶች የነበሩበት ነው፡፡ እንቅስቃሴው በመሪዎች ተወገዘና ተከታዮቹ ተገደሉ፡፡ ከሠራዬ ታቦታቸውን ይዘው ወደ ሽሬ መጡ፣ ወደ ጐንደር ሄዱ፤ ከዚያ ወደ ጐጃም፣ ወደ ሰሜን ሸዋ መጡ፡፡ ሰሜን ሸዋ ደብረብርሃን ላይ እንዲቃጠሉ ተደረጉ፡፡
ከዚያ ያመለጡት በወሎ አድርገው ትግራይ ገብተው ያረፉት ጉንደጉንደ ላይ ነው፡፡ ከደጋ ወደ ኢሮብ ተሰደደ የሚባለው ህዝብ ከዚህ ታቦት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ኢሮብ የሚለው ቃልም ከዚያ ጋር ይያዛል፡፡
እንዴት?
ቆላ ላይ አንድ እንግዳ ሲመጣ “እንደምን ዋላችሁ” ወይ “አመሻችሁ” ካለ፣ አባወራው አይወጣም። እዛው ሆኖ ግቡ ነው የሚለው፡፡ በሳሆ ኦሮባ ይባላል፡፡ ግቡ ማለት ነው፡፡ እኔ ያገኘሁት መረጃ እንደሚያሳየው፤ ታቦት ይዘው የመጡት ጉንዳጉንዳ እንደደረሱ ሰዎች ያገኙና “እዚህ ቤት” ሲሉ ኢሮባ አሏቸው፡፡ ለቀሩት ተከታዮቻቸው በፃፉት ደብዳቤ፤ “እኛን የተቀበሉን ህዝቦች አግኝተናል፤ ህዝቡም ኢሮብ ይባላል” ብለው ፃፉ የሚል ነው፡፡
ኢሕአሠን  እንዴት ነው የኢሮብ ህዝብ  ኦሮባ ያለው?
አንደኛው ከኢህአፓ መስራቾች አንዱ የሆነው ተስፋዬ ደበሳይ የአካባቢው ተወላጅ ነው፡፡ ተስፋዬን    ጨምሮ ብዙ የአካባቢው ተወላጆች አውሮፓ በተለይ ቫቲካን ነበሩ፡፡ ምክንያቱም ከኢሮብ ጐሳዎች አንዱ የሆነው ቡክናይተአረ የሚባለው  የካቶሊክ እምነት ተከታይ ስለሆነ የትምህርት እድል ይሰጣቸው ነበር።
የኢሕአሠን ትግል  ጐጃም  ለማድረግ ታስቦ ነበር፡፡ ነገር ግን ሱዳን በዚያን ወቅት አስተማማኝ ሀይል አልነበረም፡፡ ባሌም ታስቦ ነበር፡፡ ሶማሌያም አስተማማኝ አልነበረም፡፡ ሌላው ደግሞ አወሮፓ የነበሩ የኢሮብ ተወላጆች የተወሰኑት የኢህአፓ አባል ስለነበሩ ከህዝቡ ተቀባይነት ማግኘት ከባድ አይሆንም በሚል ይመስላል፡፡ ቦታው ለቀይ ባህርም ቅርብ ነው፡፡ አዱሊስ ቅርብ ነው፡፡ አሲምባ ተራራ ጫፍ ላይ የየመን ዋና ከተማ ትታያለች፡፡ ስንቅ ለማጓጓዝም አመቺነቱን በማየት፣ ጂኦግራፊውም ስትራቴጂካዊ ቦታ ላይ ስለሆነ ነው፡፡  
ህዝቡስ?
የኢሮብ ህዝብ አንድን ነገር ቶሎ አይቀበልም። ከተቀበለ ደግሞ ጽኑ ነው፡፡ እንዲቀበል ደግሞ የራሱን ሰው ይፈልጋል፡፡
የኢሮብ ህዝብ ዛሬ ላይ የኢሕአሠን ሠራዊት እንዴት ያስታውሰዋል?
የልጆቻችን ወንድሞች እና ጓደኞች እንደሆናችሁ ሰምተናል፡፡ እንደ ልጆቻችን እንቀበላችኋለን፡፡ ግን ከድታችሁን ለጠላት አጋልጣችሁን እንዳትሄዱ” ነበር ያሏቸው፡፡ አሁን ህዝቡን እንዴት ያዩታል ላልሽኝ፤ ኢሕአሠን በደንብ ነበር የተቀበሉት፡፡ ወደኋላ ግን በኔ እይታ  በጣም አዝነውበት ነበር፡፡
ለምን
ካዘኑባቸው ምክንያቶችም አንዱ፣ አንጃ ተብለው በተገደሉ ሰዎች ምክንያት ነው፡፡ አንጃ በሚል ተይዘው የነበሩትን ሰዎች አስመልክቶ የኢሮብ ህዝብ ሽማግሌ ልኳል፡፡ እነዚህን ልጆች እንዳትገድሉ ብሏል፡፡ በወቅቱ የፖሊት ቢሮ አባል የነበረው ዘርዑ ክህሸንም አይገደሉም ብሎ ቃል ገብቶላቸው ነበር። ግን ተገደሉ፡፡ ጨካኞች ናቸው አሉ፡፡ ሌላው ባልጠበቁት ሁኔታ ሲሸነፍ አዩት፡፡ ሀይል ነበረው ፣መሳሪያ ነበረው፡፡ ሠራዊት ነበረው ግን ተሸነፈ። አላማውን ሲያነሱ ግን እስከአሁን “ያ ሠራዊት” ይላሉ፡፡ ከሁሉም የኢትዮጵያ ክፍል የተውጣጣ በመሆኑ ልዩ ነው፡፡ ስሜቱ የተዘበራረቀ ነው፡፡
መጽሐፍህ ላይ “ገበሬ የሀይል ሚዛን ወደሄደበት ፊቱን ያዞራል” ብለሀል፡፡ የኢሮብ ህዝብን ከዚህ አባባል ጋር በማገናኘት  አስረዳኝ?…
ይህ በሁሉም ገበሬ የሚታይ ነው፡፡  ኢሮብ አንደኛ ገበሬ አልነበረም፡፡ አርብቶ አደር ነበር። የጐሳ ትስስር ነው የነበረው፡፡ የኔ ወገን የሆነው ለኔ ሲል ለኔ ያደላል፤ ወደኋላ ግን ትክክለኛ የገበሬ ጥቅመኝነት አይቼበታለሁ፡፡ ሠራዊቱ አካባቢውን ለቆ ከወጣ በኋላ እኔ እዚያ ቆይቻለሁ፡፡ አጋፍጠው ሊሰጡኝ ባይፈልጉም ስጋት ግን አለባቸው፡፡ ብሄድላቸው ደስታቸው ነው፡፡ የገዛ ዘመዶቼ ከዚያ አካባቢ ብጠፋላቸው ደስ ይላቸው እንደነበር አውቃለሁ፡፡
ስለአባትህ ንገረኝ…
አባቴ በወቅቱ ዘመናዊ ትምህርት ከወሰዱት ውስጥ ነው፡፡
አባትህ ሽፍታ ነበሩ ይባላል ዕውነት ነው?
አዎን
የአካባቢው ዳኛም፣ አስተዳዳሪም፣ ፖሊስም ሁሉንም ነው፡፡ አባቴ በአካባቢው ተወዳጅ ነበር፡፡ በለቅሶም ሆነ በሠርግ ስሙ ይነሳል፡፡ ተስፋዬ ደበሳይ በእረፍት ጊዜው የሚውለው ከአባቴ ጋር ነበር፡፡ ብዙ የህግ እውቀት ከአባቴ እንዳገኘ ነግሮኛል፡፡ የትግል ሜዳ ላይ ከብርሃነመስቀል ጋር ሲያስተዋውቀኝ፣ አባቱ በህይወት ቢኖሩ ከኛ ጋር ይሠለፉ ነበር ብሎታል፡፡
በድንበር ኮሚሽኑ ውሳኔ መሠረት ለኤርትራ እንዲሰጡ የተወሰኑ የኢሮብ አካባቢዎችን አንተ እንዴት ነው የምታያቸው?
አባቴ በሀላፊነት ላይ በነበረ ጊዜ ትልቁ ራስምታቱ እሱ ነበር፡፡ በተለይ አይጋ የውጥረት ቦታ ነው፡፡ በደንብ ሳይካለል የቀረ ቦታ ነው፡፡
ኢሮብ በትግራይ በኩልና ኢሮብ በኤርትራ መሠረታቸው አንድ ነው?
አዎ አንድ ነው፡፡ የሶስት ወንድማማቾች ልጆች ናቸው፣ ኢሮቦች፡፡ ሀሳበላ፣ ቡክናይተአረ  እና ጋዳ ይባላሉ፡፡ ጋዳ በሰሜን በኩል ነው ወደ ኤርትራ የሚጠጋው፤ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ ናቸው። የነሱ ግንኙነት ከኤርትራ ጋር ነው - በጣም ተቀላቅለዋል፡፡ ቋንቋው ትግርኛ እና ሳሆ ነው፡፡ መሀል ያለው ቡክናይታ ካቶሊክ ነው፤ ከነሱ  ወደ ሰሜን ስትሄጂ መነኩሲቶ የሚባል የኤርትራ ቦታ አ። እነሱም ካቶሊኮች ናቸው፡፡ የጋብቻ ግንኙነታቸው ከካቶሊኮቹ ጋር ነው፡፡ ብቻውን የሚቀረው ሃሰበላ ነው፤ ከአጋመ ጋር ይዋሰናል፤ ኦርቶዶክስ ነው፡፡ በዘር የተሳሰሩ ናቸው፤ በኮሚሽኑ ውሳኔ መሠረት፤ ብክናይተአረና ጋዳ ለኤርትራ  ተወስነው ሀሰበላ ነው ለኢትዮጵያ የቀረው፡፡ ቦታዎቹን ሳውቃቸው በኢትዮጵያ ግዛት ስር የነበሩ ናቸው፡፡
የታሪክ ተማሪ ነህ ድንበር ማስመር ላይ ስህተት እንዳለ ነግረኸኛል፡፡ እሰቲ ስለእሱ አብራልኝ …  
ከአድዋ ጦርነት በኋላ በማካለል ላይ የተደረገ ስህተት ነው፡፡ መረብ፣ በላሳ፣ ሙና የሚለው ነው። በካርታው ላይና መሬት ወርዶ ያለው ላይ ማለት ነው፡፡ በጣሊያን ጊዜ ራሱ ቦታው የአርበኞች ቦታ ነበር፡፡ ከኤርትራም ሆነ ከትግራይ በኩል ጣሊያንን የተዋጉ አርበኞች የተሸሸጉት ኢሮብ ነው፡፡ ኢሮብ ኢትዮጵያዊ ነው፡፡
መጽሐፉን ለማዘጋጀት ያነሳሳህ ምንድንነው?
መጽሐፉን ለመፃፍ ካሰብኩ ቆይቻለሁ፡፡ ግን የጽሑፍ ችሎታ የለኝም፡፡ ብዙ መፃሕፍቶች እየወጡ ነው፤ አንብቤያለሁ፡፡ አንድ ሳይነኩዋት የሚያልፉዋት ቦታ አለ፤ ሁሌም ይከነክነኛል፡፡ ይህ ድርጅት በአንድ ወቅት በጣም ገንኖ የወጣ፣ ተቀባይነት ያገኘ ነበር፡፡ የተቀጨው ግን በአጭሩ ነው፡፡  
ለውድቀቱ መፍጠን አስተዋጽኦ ያደረጉት ምንድን ናቸው? ውስጣዊ ችግሩ ወይስ ውጫዊው? የሚለውን ለማሳየት በክፍፍሉ ላይ አተኮርኩ፡፡ የተወሰኑ ዶክመንቶች፣ ግለሰቦችና የራሴን ተመክሮ አካትቼ አስቀመጥኩ፡፡ የቀረውን ሌላው ሊሞላው ይችላል ብዬ ነው፡፡
መጽሐፉ ከዚህ በፊት በሌሎች መፃሕፍቶች ወይም ሰነዶች ላይ ያሉ መረጃዎችን ነው የገለበጠው የሚል አስተያየት ይሰነዘራል፡፡
አዎ ትክክል ነው፡፡ የማውቃቸውም ያነበብኳቸውም  የማምንባቸውም ስለሆኑ ነው የተጠቀምኩባቸው፡፡
ከኢሕአሠ ሸፍተህ ነበር፡፡ ከደርግም ሸፍተሃል ይሄ ነገር እንዴት ነው?
አዎ ሸፈትኩ ድርጅትህን ከድተህ መሳሪያ ይዘህ መጥፋት ከባድ ወንጀል ነበር፡፡ እኔ እርምጃ አልተወሰደብኝም፡፡ የሸፈትኩት እስር ቤት አያለሁ ለሠራዊቱ የነበረኝ ግምትና ስሄድ ያገኘሁት  በጣም የተለያየ ስለነበረ ነው፡፡ መጽሐፌ ላይ የአሊቴናን ካርታ ያስገባሁት ያለምክንያት አይደለም፡፡
አሊቴና በጣም ስትራቴጂክ ናት፣ ሁለት በር አላት፡፡ ያንን ጥሶ የህወሓት ሠራዊት ሲገባ ኢሕአሠ እንዳለቀለት ገባኝ፡፡ ከዛ ደግሞ ማጋለጥ ውስጥ ተገባ፡፡ ተጠርቼ ነበር አልሄድኩም፡፡ ሠራዊት ሆኖ መቀጠል አይችልም፡፡ ለውጥ ያስፈልገዋል ብዬ አሰብኩ፡፡ እና መጀመር አለብኝ ብዬ ከጓደኛዬ ጋር ተመካከርኩና እንገንጠል አልን፡፡ ለውጥ እናድርግ ወይ ለውጥ አድርገው ይቀላቅሉን አልን፡፡ ጓደኛዬ የትጥቅ እና ስንቅ ሃላፊ ነበረ፡፡ የተቀበሩ መሳሪያዎች ያሉበትን ቦታ ያውቃል፤ ችግር እንደማይገጥመን ደምደመን፤ ሄድን፡፡ ከዚያ ብዙ ሽማግሌዎች ተላኩብን በኋላ ግን ሃሳቤን የሚያስቀይር ሚስጥር አገኘንና ለመመለስ ወሰንኩ ፡፡ ህወሓት ለጦርነት እንደተዘጋጀ ሰማን፡፡ በዛ ሰአት ጥሎ መሄድ ስላልታየኝ ተመለስኩና ያገኘሁትን መረጃ ሰጠሁ፡፡ በዚህ ምክንያት ይመስለኛል ያልታሠርኩት፡፡
የመጨረሻዎቹ የኢሕአሠ ቀኖች  በትግል ሜዳ ላይ ምን ይመስሉ ነበር?
በጣም አስቀያሚ፡፡  ጦርነት እየገፋ መጣና ኢሮብ አካባቢ ደረሰ፡፡ ለመውጣት በኤርትራ በኩል  መንገድ መከፈት ነበረበት፡፡  ጀብሀ፤ አይሀ በምትባል ቦታ ብቻ ነው ማለፍ የሚቻለው ብሎ ቢስማማም  አንድ ጋንታ በሌላ መንገድ ለመግባት ስትሞክር ትያዛለች፡፡ ስንደርስ ትጥቅ አስፈትተዋቸው አናስገባም ይሉናል፡፡ ከዚያ መሳሪያቸውን ተረክበን ከሚሊሺያዎቹ ጋር አንድ ኮረብታ ላይ ቁጭ ብለን ሸመዛና በሚባል ሜዳማ ቦታ ላይ የኛ ሠራዊት ይተማል (ለቅሶ)፡፡
አንተ እዚያ ቀረህ?
ለአንድ አመት ኢሮብ ቆየሁ፡፡ መቆየቴ ጥሩ ነበር። ደርግ አዲስ አበባ ውስጥ ያደርግ የነበረውን ሰቆቃ ለማምለጥ የሚመጡትን እየተቀበልን እናሳልፍ ነበር፡፡ ማህተም ያለው ሰነድ እጃችን ላይ ነበር፡፡
በኋላስ አንተ ምን ሆንክ?
እዚ መቆየት ከባድ ነበር፡፡ የቀረሁት ከገበሬዎች ጋር ነው፡፡ ቀድሞ ያነሳነው የገበሬ ባህርይ እየገፋ ሲመጣ፣ መቆየት የሚፈልጉት እዚያው ቀሩ፡፡ ህወሓትን የሚቀላቀሉ፡፡ ተቀላቀሉ እኔ አዲስ አበባ ት/ቤት ገባሁ፡፡
ቀጣዮቹ አመታትስ?
አስተማሪ  ነው የምትሆነው፣ ተብዬ ጐጃም ተመደብኩ፡፡ ጐጃም ሳለሁ እስከ 1983 ድረስ ስለነበሩት ጓዶች እንዴት እንደነበሩ አውቃለሁ፡፡
እንዴት ነበሩ?
ቻግኒ  እና ዳንግላ እነሱን ለመፈለግ ሄጃለሁ።  ግን እኔ የማውቀው የኢሕአሠን አይነት ሆኖ አላየሁትም፡፡ በሽፍትነት ደረጃ እንደነበሩ ነው የሰማሁት፡፡
ከዚያስ
ወደ መጨረሻ አካባቢ (ከሁለት አመት በኋላ) የኢህድን ወሬ እሠማ ስለነበር “እነሱ ይሆኑ እንዴ እውነተኞቹ ኢህአፓዎች?” በሚል ማፈላለግ ጀመርኩ፡፡ 79 እና 80 አካባቢ ከማን ጋር እንደሆነ በትክክል ባላውቅም (ኢህዴን፣ ህወሓት፣ ሻዕቢያ) አዲስ አበባ ውስጥ በትክክል የፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ ነበርኩ፡፡
ደርግ እንዲወድቅ እንቅስቃሴ ከሚያደርጉት ከማናቸውም ጋር በህቡዕ እሠራ ነበር፡፡ ደርግ ሲወድቅ ቀጥታ ያገኘኋቸው ኢህዴኖችን ነው፡፡ ፎረም 84 የሚመራው በነሱ ነበር፡፡  ከአመራሮቹ አንዱ ሆንኩ፡፡ እራሴን እንደ ኢህዴን ቆጠርኩ፡፡ የክልል 14 ፀሐፊ ነበርኩ፡፡
ኢህዴንን ለምን መረጥክ?
አንደኛ ከኢሕአሠ የማውቃቸው ስለነበሩ፡፡ ሲሆን ቀጥሎ ህብረ - ብሔራዊ ስለነበር ነው፡፡
ለምን ከሃላፊነትህ ለቀቅህ?
ኢህዴን ወደ ብአዴን ሲቀየር ወደ የብሔር ድርጅት የሚል ነገር  ሲመጣ ስላልተስማማኝ ነው፡፡ ሌላው ደግሞ ያነበብኳቸው መፃሕፍቶች በዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት ላይ ያሳደሩብኝ ተጽእኖዎች ሊያስቀጥለኝ ስላልቻለ! አልቻለም፡፡ በ1989 ዓ.ም በፈቃዴ ለቀቅኩ፡፡

ሌሊት አጎበር ስላለ ትንኟ የንክሻ ሰዓቷን ወደ ቀን አዘዋውራለች
(አቶ ገዛኢ አምባዬ፤ የባዝኦፍ አምራች ኩባንያ መስራችና ዳይሬክተር)
በሙያቸው አካውንታንት የሆኑት አቶ ገዛኢ አምባዬ፤ በ1964 ዓ.ም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ውስጥ ተቀጥረው በሙያቸው መስራት እንደጀመሩ ይናገራሉ፡፡ በውሃና ፍሳሽ፣ በኢትዮጵያ ውሃ ስራዎች ድርጅትና በብረታ ብረት ኮርፖሬሽን በከፍተኛ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ ያገለገሉ ሲሆን በ1981 ዓ.ም ወደ ኬኒያ በማምራት የኢምፖርት ኤክስፖርት ስራ ላይ ከመሰማራታቸውም በተጨማሪ ባርና ሬስቶራንት በመክፈት ለረጅም አመታት መስራታቸውን ገልፀዋል፡፡ አንበሳ ባንክና ኢንሹራንስን ከመሰረቱት ሰዎች አንዱ የሆኑት አቶ ገዛኢ፤ ከ10 ዓመት በፊት ከውጭ ተመልሰው በአገራቸው መኖር ሲጀምሩ፣ ወባ በአገሪቱ ላይ እያደረሰ ያለውን ጥፋት መመልከታቸውን ያስታውሳሉ፡፡ ወባ በአፍሪካ እያደረሰ ያለውን ጥፋት በተመለከተ ጥናት ሰርተውም ለአሜሪካው ግዙፍ ኩባንያ IFF በመስጠት ተቀባይነት በማግኘታቸው፣ በለገጣፎ አካባቢ “ባዝኦፍ” የተሰኘ የወባ ትንኝ ማባረሪያ መድኀኒት በማምረት ላይ ይገኛሉ፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ በመድኀኒቱና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ከአቶ ገዛኢ አምባዬ ጋር ተከታዩን ቃለ-ምልልስ አድርጋለች፡፡


“ባዝኦፍ” የተባለውን የወባ ማባረሪያ ቅባት እንዴት ሊያመርቱ ተነሱ?
እኔ በ1981 ጀምሮ ወደ ጎረቤት አገር ኬኒያ ሄጄ ነበር፡፡ ከኢትዮጵያ ወይንና አምቦ ውሃ እየወሰድኩ ለኬኒያ፣ ለሩዋንዳ ለኡጋንዳና ብሩንዲ አከፋፍል ነበር። ኬኒያም ውስጥ “ግሪን” የተባለ ባርና ሬስቶራንት ነበረኝ፡፡ እዚያ እየሰራሁ እያለ IFF (International Flavors and Fragrance) የተባለ የአሜሪካኖች ትልቅ ኩባንያ ነበር፡፡ ይህ ኩባንያ ማጣፈጫዎችንና መዓዛማ ዘይቶችን ያመርታል፡፡ እነ ኮካ ኮላ፣ ለነ ፔፕሲና ሌሎችም ትልልቅ ኩባንዎች የሚያከፋፍል ነው፡፡ ከ10 ዓመት በፊት የዚህ ትልቅ ኩባንያ ወኪል ሆኜ ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጣሁት። ሁኔታዎችን በማመቻቸት ስመላለስና እዚህ ቢሮ ስከፍት ግን 15 ዓመት ሆኖኛል፡፡ እናም እነሱ ጋር  በነበረኝ ግንኙነት ቸኮሌት፣ ከረሜላና መሰል ጣፋጮችን የሚያመርት ኩባንያ ለራሴ መክፈት አስቤ ስንቀሳቀስ፣ በወቅቱ ወባ በተለይ በአማራና በሌሎች ክልሎች የአገሪቱ ፈተና ሆኖ አየሁት፡፡ መነሻዬ ይሄ ነው፡፡
ከዚያ ምን አደረጉ?
በወቅቱ ወባ ህዝቡን እየፈጀች መሆኑን ከተለያዩ ሚዲያዎች አንብቤ ነው በጣም ያዘንኩት፡፡ ምን ይሻላል ምንስ ቢደረግ ህዝቡን መታደግ ይቻላል በሚል ራሴ በራሴ ትግል ውስጥ ገባሁ፡፡ አንድ ጥናት አጠናሁና “IFF” ላልኩሽ ኩባንያ አቀረብኩኝ፡፡ አፍሪካ የኮስሞቲክስም የሽቶም ችግር እንደሌለባት፣ በአሁኑ ጊዜ ሕዝቧ በወባ እያለቀ ስለመሆኑ፣ አምራች ኃይሉ በወባ ጥቃት እያለቀ እንደሆነ የሚያሳይ ነው ጥናቱ። ጥናቱን ተቀብለው ካዩት በኋላ “ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ፍሎሪዳ” አገሩም ወባማ ስለሆነ ቀድመው አጥንተው ነበር፡፡ ጥናቱን ያጠኑበትን ዋና መነሻ ሲነግሩኝም፤ “The Boston Tea Revolution” በነበረ ጊዜ የአሜሪካ ሰራዊት ያለቀው በወባ ነው፡፡ ያኔ ግን ወባ ነው ተብሎ በሽታው ተለይቶ አልታወቀም ነበር። የሆነ ሆኖ ጥናቱን ተቀበሉት፡፡ ከዚያ “ኢሴንሻል ኦይሉን” እንዲልኩልኝ አደረግሁኝ።
ኦይሉ ከተላከ በኋላ መጀመሪያ ጥናቱን የትኛው የአፍሪካ አገር አደረጉ?
መጀመሪያ ጥናቱ እንዲጠና የወሰንኩት ኬኒያ ነው፡፡ ምክንያቱም ኬኒያ ውስጥ “ኢሲፕ” የተባለ የዓለም ሳይንቲስቶች በሙሉ ስለ “ትሮፒካል ዲዚዝ” ጥናት የሚያደርጉበት ማዕከል ስላለ ነው። ከእነሱ ጋር ስምምነት በማድረግ፣ ከአሜሪካ የተላከው “ኢሴንሻል ኦይል” ከፔትሮሊየም ጄሊ (በተለምዶ ባዝሊን የምንለው) ጋር ተቀላቅሎ ቢሰራ በእርግጥ የወባ ትንኝን ያባርራል ወይ? የሚለውን እንዲያረጋግጡልኝ ነው ያደረግሁት። ብዙ ዶላር ካስከፈሉኝ በኋላ ጥናቱን ሰሩልኝ። ብዙ ዶላር የከፈልኩት ጥናቱ ሰፊ ስለሆነ ነው። አንደኛ የላብራቶሪ ሙከራ ያደርጋሉ፣ ሁለተኛ ወባ በተነሳ ጊዜ ገጠር ገብተው ካምፕ ሰርተው፣ ህዝብን አስተባብረው፣ ደም ምርመራ ያደርጋሉ። ምክንያቱም ጥናቱን የሚያካሂዱት በዓለም የጤና ድርጅት (WHO) መስፈርት መሰረት ስለሆነ ነው። ጥናቱ ወደ ሁለት ዓመት ገደማ ወስዶ፣ በመጨረሻ ምርምሩን አድርገን፣ሰ ቅባቱ “ባዝኦፍ” ከ 8 ሰዓት በላይ የወባ ትንኝ ያባርራል ሲሉ የምስክር ወረቀት ሰጥተውኛል፡፡ ይህ ከሆነ ወደ ስምንት ዓመት ገደማ ይሆነዋል፡፡
መድኀኒቱ በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር እውቅና አግኝቷል?
በሚገባ! እኔ ሰርተፍኬቱ ከተሰጠኝ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ ሳመጣው፣ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ኃላፊዎች በጣም ተደስተው ነበር፡፡ እኔ ባዝኦፍን ወደ ኢትዮጵያ ባስገባሁበት ወቅት ሰዎች የሚጠቀሙት አጎበር በኬሚካል ያልተነከረ ስለነበር ብዙም ውጤታማ አልነበረም፡፡ ስለዚህ ጤና ጥበቃችሁ “ይህ መድኀኒት አማራጭ ስለሚሆነን አገር ውስጥ ያሉ የምርምር ተቋማት ለምን ጥናት አያደርጉበትም? ፓስተር ወይም አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቢመራመሩበት ጥሩ ነው” አሉኝ፡፡
ምርምሩ ተካሄደ?
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲዎች እንዲያጠኑት እንደገና ስምምነት አደረግን፡፡ “አክሊሉ ለማ የምርምር ማዕከል” የትሮፒካል ዲዚዝና የወባ ምርምር ማዕከል ነው፡፡ በዚህ መሰረት የላብራቶሪ ሙከራ ተደረገበት። ቆቃ አካባቢ ወባ ተነስቶ ስለነበር ዶክተሮቹ እዚያ ድረስ ሄደው ምርምርና ጥናት አድርገው፣ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ውጤቱ አመርቂ ነው በሚል ማረጋገጫ ሰጡኝ፡፡
ባዝ ኦፍ የሚመረትበት ፋብሪካ የት አካባቢ ይገኛል? በዓመት ምን ያህል ያመርታል?
ፋብሪካው ለገጣፎ ይገኛል፡፡ በጥሩ ሁኔታ እያመረትን ነው፡፡ አንደኛ ለፋርማሲዎች እናከፋፍላለን፤ ዋና የባዝኦፍ ተጠቃሚ ግን መከላከያ ሰራዊታችን ነው፡፡ ሰራዊቱ በፊት ከውጭ እያስመጣ ይጠቀም ነበር፡፡ እኛ ማምረት ከጀመርን በኋላ ከውጭ ማስገባታቸውን አቁመዋል፡፡ የተሻለ ጠቀሜታ አግኝተንበታል በማለት፣ በጀታቸው ውስጥ አስገብተው በየአመቱ ይወስዳሉ፡፡ ፌደራል ፖሊስም እንዲሁ እየወሰደ ነው፡፡ ሌሎች ተቋማትም መውሰድ ጀምረዋል፡፡ መንግስትም ይህንን በማየት ከወርልድ ባንክ ባገኘው ድጋፍ፣ በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር በኩል ወደ 103 ሺህ ዶላር ገደማ ድጋፍ አድርጎልናል፡፡ ይህ እርዳታ የተሻለ ምርምርና ጥናት ለማካሄድ እንዲሁም ኤክስፖርት ለማድረግ እንቅስቃሴ የሚውል ነው፡፡
እስካሁን ወደ ውጭ መላክ አልጀመራችሁም?
ጀምረናል፤ ወደ ናይጄሪያ፣ ኡጋንዳ፣ ሱዳን ሱማሌላንድና ሞቃድሾ ልከናል፡፡ሰ በአሁኑ ሰዓት ሌሎች የወባ ችግር ያለባቸው አገሮችም ምርቱን ለመውሰድ ጥያቄ እያቀረቡ ነው፡፡
“ኢሴንሻል ኦይሉ” ከአሜሪካ IFF እያስመጣችሁ ነው የምትጠቀሙት? ሌላስ ማቴሪያል ምንድን ነው የሚያስፈልጋችሁ?
ቤዙ እንዳልኩሽ ባዝሊን ነው፡፡ ባዝሊን ከውጭ ይመጣል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ከአንዳንድ ሳይንቲስቶች ጋር “ኢሴንሻል ኦይሉ”ን እዚሁ ለማምረት በምክክር ላይ ነን፡፡ አገራችን በርካታ ለመድኀኒትነት የሚያገለግሉ ሁሉም አይነት ዕፅዋት ስላላት ምቹ ናት፡፡ መድኀኒቱ ከእፅዋት ነው የሚሰራው፡፡ እነሱ የሰሩት ፎርሙላ ስላለን “ኢሴንሻል ኦይሉ”ን እዚሁ ለማምረት ዶክተሮቹን አጋር አድርገን ፋብሪካውን በማቋቋም ላይ ነን፡፡
ከረሜላና ቸኮሌት የሚያመርት ኩባንያም እንዳለዎት ሰምቻለሁ፡፡ ከባዝኦፍ ማምረቻው ጋር አንድ ላይ ነው ያሉት?
ቅርብ ለቅርብ ነበሩ፡፡ አሁን መለያየት ስላለባቸው እየለየናቸው ነው፡፡ በሁለቱም ኩባንያዎች ውስጥ አንድ የእንግሊዝ ኩባንያ በሽርክና ለመስራት መጥቷል፡፡ አሁን ከፍተኛ እንቅስቃሴ አለ፡፡ “ባዝኦፍን” ስናመርት በዚያውም ሽቶና መሰል መዓዛ ያላቸውን ምርቶችም እዚህ ለማምረት እያስመዘገብን ነው፡፡ አላማችን ከውጭ የሚመጡ የቼኮሌት፣ ከረሜላ፣ የወባ መድኅኒቶችና ሌሎችንም አስቀርተን አገር ውስጥ እንዲመረቱ ማድረግ ነው። እዚህ አምርተንና እሴት ጨምረን ኤክስፖርት ማድረግ ከኢኮኖሚም አኳያ አገሪቱን ይጠቅማታል፡፡
ባዝኦፍ ከስምንት ሰዓት በላይ የወባ ትንኝን እንደሚያባርር ተገልጿል፡፡ የመከላከል አቅሙ በመቶኛ ሲሰላ ምን ያህል ነው?
የዓለም የጤና ድርጅት አንድ መድኀኒት ከ60 እስከ 68 በመቶ መከላከል ከቻለ ውጤታማ ነው ይላል፡፡ ባዝኦፍ ግን 90 በመቶ አመርቂ ነው፡፡ ከስምንት ሰዓት በላይ እስከ 11 ሰዓት ድረስ ይሰራል። እየቆየ ኃይሉ እየደከመ እየደከመ ስለሚሄድ ግን በአማካኝ ከስምንት ሰዓት በላይ ይሰራል፤ በሚል እውቅና ተሰጥቶታል፡፡
አሁን አሁን በወባማ አካባቢ የሚገኙ ነዋሪዎች በኬሚካል የተነከረ አጎበር እየተጠቀሙ ነው፡፡ የባዝኦፍ ተጨማሪ ነው ወይስ እንዴት ነው?
አሁን ጥሩ ጥያቄ አመጣሽ፡፡ ሁሉም የተነከረ አጎበር ስለሚጠቀም፣ ሌሊት ትንኟ የሰዎችን ደም ማግኘት አልቻለችም፡፡ ስለዚህ የምትናከስበትን ሰዓት ቀይራለች፡፡ ለመኖርና እድሜዋን ለማራዘም ንክሻዋን ወደ ቀን አዘዋውራለች፡፡ የአሜሪካ ሳይንቲስቶችም ጥናት የሚያሳየው ይህንኑ ነው። ይህን በተመለከተ ሳይንቲስቶች በ6300 ሰዎች ላይ ጥናት ሲያደርጉ ለመጀመሪያው ቡድን አጎበር ብቻ ሰጡ፣ ለሁለተኛው ደግሞ መከላከያ ቅባቱንም አጎበሩንም ሰጡ፡፡ ውጤቱ ምን ሆነ መሰለሽ? አጎበሩንም መከላከያ ቅባቱንም የተጠቀሙ ሙሉ በሙሉ ከወባ በሽታ ነፃ ሲሆኑ አጎበሩን ብቻ ከተጠቀሙት መካከልብዙዎቹ በቀን እየተነከሱ የወባ ተጠቂ መሆናቸውን ያሳያል፡፡
አሁን ባዝኦፍን ተፈላጊ ያደረገው አንዱም ጉዳይ የወባ ትንኟ የንክሻ ሰዓቷን ወደ ቀን ማዛወሯ ነው፡፡ ቀን ቀን አጎበር ተሸክመሽ አትንቀሳቀሺም፤ ስለዚህ የግድ በወባማ አካባቢና በወባ ነሻ ወቅት ቀንም ባዝኦፍ መቀባት ግድ ነው፡፡
አሁን ክረምት እንደመሆኑ እስከ ህዳር ባለው ጊዜ ወባ በከፍተኛ ሁኔታ የሚቀሰቀስበት ወቅት ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት የምርታችሁ ተፈላጊነት ምን ይመስላል?
እንደነገርኩሽ በቋሚነት የሚወስዱ እንደ መከላከያ ሰራዊት ያሉ ተቋማት አሉ፡፡ ምርቱ በጣም ተፈላጊ ነው፡፡ አሁን ሁለቱም ፋብሪካዎች በ6500 ካ.ሜ ላይ ነው ያሉት፡፡ 15 ሺህ ካሬ ለባዝኦፍ ማስፋፊያ ጠይቀን እየጠበቅን ነው፡፡ ጉዳዩ አንገብጋቢና መንግስትን የሚያግዝ በመሆኑ ማስፋፊያው ሲፈቀድ፣ በስፋትና በጥራት ለማምረት ዝግጁ ሆነናል፡፡ አጋሮቻችን ብሩን ልከዋል፤ የገበያውን አዋጭነት፣ ላለፉት ዓመታት ሁለቱም ኩባንያዎቻችን የነበራቸውን ጉዳዮች መሰል ታሪኮች አስጠንተው ካመኑበት በኋላ ነው ገንዘቡን የላኩት፡፡
በመጨረሻ የሚሉኝ ካለ?
ያው ባዝኦፍ በዚህ መልኩ እየተመረተ ነው፡፡ ለወባ በሽታ በአማራጭነት በመቅረቡ መንግስትም ደስተኛ ነው፡፡ኤክስፖርት እየተደረገ የውጭ ምንዛሬም እያመጣ ነው፡፡ መከላከያው ትልቅ ፋይዳ ያለው ስለሆነ፣ ወደፊት የወባን በሽታ ሙሉ ለሙሉ ለመቅረፍ በምንችልበት አቅም ላይ እንድንደርስ በምርምሩም ሆነ በሁሉም ረገድ በርትተን እንሰራለን፡፡

የ95 ዓመት አባት አርበኛ ናቸው፡፡ ያልዘመቱበት የጦር አውድማ የለም። በዚህ ዕድሜያቸው ከ70 ዓመት በፊት የተደረጉ ጦርነቶችን ከእነ ዓመተምህረታቸው ያስታውሳሉ፡፡
ባለፈው ሳምንት በኢኮኖሚና ንግድ አምድ ላይ ቃለምልልስ የተደረገላቸው “የባላገሩ አስጐብኚ ድርጅት” ባለቤት፣ አባት አርበኞችን ወደ ታላቁ ህዳሴ ግድብ ወስዶ የማስጐብኘት ሃሳብ የመጣላቸው በእኚህ አዛውንት ጥያቄ መሆኑን ገልፀውልናል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛዋ ናፍቆት ዮሴፍ ከእኚህ የዕድሜ ባለፀጋ አባት ጋር ማራኪና አዝናኝ ቃለምልልስ አድርጋለች። እነሆ:-



ስምዎትን ያስተዋውቁኝ አባት…
ሃምሳ አለቃ ደምሴ ፀጋዬ እባላለሁ፡፡ ትውልድና እድገቴ ወሎና ጎንደር ነው፡፡ በአንድ ጎን ደባት ገብርኤል ነኝ፡፡ በሌላ ጎኔ ደግሞ ወሎ ውስጥ የጁ እና ላስታ ነው እድገቴ፡፡ ጠቅለል ስታደርጊው ዘር ሃረጌ ከወሎ እና ከጎንደር ይመዘዛል ማለት ነው፡፡
እስቲ ስለልጅነት ያጫውቱኝ?
እንዴ! የአስተዳደጌ ሁኔታማ ምን ይወራል። የተወለድኩት በ1911 ዓ.ም ታህሳስ 3 ቀን ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምረሽ እድሜዬን ማስላት ትችያለሽ፡፡ ጠላታችን ጣሊያን መጥቶ አባቶቻችን ሲዘምቱ የ18 ዓመት አፍላ ጎረምሳ ነበርኩኝ፤ በ1928 ዓ.ም ማለት ነው፡፡ አባቴ በውጊያው ቆስሎ ነበር ከዘመቻው የተመለሰው፡፡
የት ቦታ አባትዎ እንደቆሰሉ አልነገሩዎትም?
ነግሮኛል! ማይጨው ላይ ነው የተመታው፡፡ የዘመተው ከደጃዝማች አድማሱ ብሩ ጋር መሆኑንም አጫውቶኛል፡፡ ደጃዝማቹ እዚያው በውጊያው ሲሞቱ፣ አባቴ ግን ቆስሎ መጣ፡፡ የማስታውሰው እኔ የ19 ዓመት ወጣት ስለነበርኩ፣ አባቴ ውጊያ ሲሄድ የእርሻውን ስራ እኔ እሸፍን ነበር፡፡ አባቴ ከውጊያ የመጣ ቀንም ሞፈርና ቀንበሬን አነባብሬ እርሻ ወርጄ ማሽላ ስዘራ ነበር የዋልኩት፡፡ እነሱ ሲመጡ ጥይቱ እንደ ማሽላ ቆሎ… ጣ  ጣ   ጣ  ጣ ይላል፡፡ ምንድን ነው ነገሩ ብዬ ስጠይቅ፤ “አባትሽ መጣ” አሉኝ፤ አንቺ ነበር የሚሉኝ፡፡
ለምንድነው አንቺ የሚልዎት?
ምክንያቱ በግልፅ አይገባኝም፡፡ ስገምት ግን ስራመድ ከእግሬ እንደ ሴት ፈጠን እላለሁ፡፡ ለዚያ ይመስለኛል፡፡
ከዚያስ?
ከዚያማ ማሽላውን ዘርቼ ጨርሼ፣ ሞፈርና ቀንበሩን እዚያው ትቼ፣ መዋጆውን ይዤ በሬዎቼን እየነዳሁ ነበር፤ ወደ ቤት ለመግባት፡፡ በኋላ አባትሽ መጣ ሲሉኝ፣ መዋጆውንም በሬውንም ትቼ በሩጫ ወደ ቤት መጣሁ፤ ስደርስ አባቴን አገኘሁት፡፡
በጣም ተጎድተው ነበር?
በጣም እንጂ! ሚያዚያ ወር ላይ ነበር የመጣው፡፡ ከዚያ ግንቦት፣ ሰኔ፣ ሐምሌ እና ነሐሴን አስታመምነው፡፡ ከተሻለው በኋላ አሁንም የጠላት ጦር እያየለ ሲመጣ፣ “አገሬ ተወርራ አልቀመጥም” ብሎ ታላቅ ወንድሙን፣ የመጀመሪያ ልጁን (ታላቄን)፣ እኔን አስከትሎ ከአንድ ቤት አራት ሆነን ዘመትን!! ታች ጋይንት አርብ ገበያ ላይ በተደረገው ጦርነት ህዝብ አለቀ፡፡ ከላይ በአውሮፕላን እንደበደባለን፣ በመሬት ይህ ነው ብዬ በቁጥር የማልጠቅሰው እስከ አፍንጫው የታጠቀ የጣሊያን ወታደር አለ፡፡ ምን አለፋሽ… ምድር ቃጤ ሆነች፡፡ እኔ ነጭ ቃታ ቤልጂግ ይዣለሁ፣ አባቴ ረጅም ለበን የሚባል መሳሪያ ይዟል። አባቴ ጥይት ሲያልቅበት አፈሙዙን ድንጋጥ ሰብሮ መሃል ገባ፡፡ ይህን ነጫጭባ ሁላ አንጀት አንጀቱን ዘክዝኮ ዘክዝኮ ከጣለ በኋላ፣ እሱም ወንድሙም፣ የመጀመሪያ ልጁም እዚያው አለቁ (ሲያወሩኝ ስሜታቸው እየጋለ ነው)
እርስዎም በምን ተዓምር ተረፉ ታዲያ?
እኔ አብሬ መሞት ፈልጌ ነበር፡፡ ሰዎች “አንተ እንኳን ትረፍ” በሚል ወደ ኋላ ጎተቱኝና ከእነሱ ጋር አፈገፈግን፡፡ ከዚያ ተርፌ አምስቱን አመት ጣሊያን ከአገራችን እስኪወጣ ተዋግቼ ይኸው እዚህ ደረስኩኝ፡፡
ኮሪያ ዘምተዋል እንዴ?
እንዴታ! ኮሪያና የኤርትራ ዘመቻ አንድ ቀን ነው የዘመትነው፡፡ በወቅቱ ኤርትራ በፌዴሬሽን ነበር የምትተዳደረው፡፡
ራስ ገዝ ነበረች አይደል?
አዎ! ከዚያ በኋላ ከእኛ ጋር ተቀላቀለች፡፡ ይህ እንግዲህ በ1973 ነው፡፡ ከዚያ በኋላ “ወርቋ ኤርትራ ከእናቷ ኢትዮጵያ ጋር በሰላም ተቀላቀለች” ተባለ። ወታደሮቹና ኤርትራዊያኑ አምስት ቀን ሙሉ አብረውን ሲበሉና ሲጠጡ ቆይተው ጃንሆይ ወደ አዲስ አበባ ሲመለሱ፣ እኛ ወደ ምፅዋ ልንወርድ ስንል መንገድ ላይ ጠብቀው አይጠምዱንም መሰለሽ! አስቢው… ሁለት ሻምበል ጦር ወደፊት ሄዷል፡፡ የመሳሪያ ግምጃ ቤቱንና ጠቅላይ ሰፈሩን ሰዎች ከሁለት ቆርጠው ተኩስ ከፈቱብን፡፡
ከኢትዮጵያ ጋር ተቀላቀለች ከተባለ በኋላ ነው?
ታዲያስ! አብረውን በልተው ጠጥተው… የሻዕቢያ ነገር ተመልከቺ! ከዚያ እኔም በሁለት ጥይት ተመትቼ ወደቅኩኝ፡፡
ተጐድተው ነበር?
ታፋዬን ነው የተመታሁት፡፡ ከዚያ በኋላ የሆነውን የተደረገውን አላውቅም፤ ራሴን ስቼ ነበር፡፡ በኋላ ስነቃ አብረውኝ የነበሩት በመትረየስ ጭንቅላታቸውን ተመትተው እኔ ላይ ወድቀዋል። ሬሳ ሲነሳ እኔ ከእነ ነፍሴ ተገኘሁ፡፡ የሚያውቁኝ ሰዎች “አሞራዋ በነፍስ አለች” ብለው እኔን ጨምሮ ሰባት ቁስለኛ በሄሊኮፕተር ተጭነን፣ አዲስ አበባ ምኒልክ ሆስፒታል ገባን፡፡ ሁለቱ ጓዶቻችን ሆስፒታል እንደደረሱ ሞቱ፡፡ አምስታችን ተረፍን፡፡
ሆስፒታል ምን ያህል ጊዜ ለህክምና ቆያችሁ?
አንድ አመት ከዘጠኝ ወር ያህል ሆስፒታል ቆይተናል፡፡ ከዚያ በየቦታው አንድ አንድ ጋሻ መሬት ተሰጠን፡፡ ለእኔ ጉራጌ ዞን ጨወና ወረዳ፣ አመያ የተባለ ቦታ ደረሰኝ፡፡ ያንን መሬት ስቃበጥበት ኖርኩኝ፡፡
የትዳር ህይወትዎ ምን ይመስላል? ልጆችስ ወልደዋል?
ልጆች ወልደዋል ወይ ነው ያልሽው? ያውም በቁና ሙሉ ነዋ! ትዳር ይዤ መውለድ የጀመርኩት በ1937 ዓ.ም ነው፡፡ 19 ልጆች ወልጃለሁ፡፡
ሁሉም በህይወት አሉ?
19 ልጆች ወልጄ አሳድጌ ነበር፡፡ አምስቱ ሞቱብኝ፡፡ አሁን 14 ልጆች፣ 18 የልጅ ልጆች፣ ብዙ የልጅ ልጅ ልጆች አሉኝ፡፡ ከቅድመ አያትም እስከ ምንጅላትነት ደርሻለሁ፡፡
እንደ እርስዎ አርበኛ የሆነ የሆነ ልጅ አለዎት?
አይይይ…….የለኝም፡፡ ወደፊት አርበኛ ይሆኑ እንደሆነ እንጂ እስካሁን የለኝም፡፡
ሶማሊያ ኢትዮጵያን ስትወርር ዘምተዋል?
እንዴ ምን ነካሽ… በደንብ እንጂ! በኦጋዴን ዘጠነኛ ማካናይዝድ ጦር ውስጥ ነበርኩኝ፡፡ ይህ ሁሉ አልፎ መጨረሻ አካባቢ ጡረታ ልወጣ ስል አዲስ አበባ መጣሁ፡፡ በመከላከያ ሚኒስቴር በደሞዝና መዝገብ ቤት ተቀጥሬ ስሰራ ቆይቻለሁ፡፡ በሂሳብ አስተዳደርና በመዝገብ አያያዝ ባለሙያ ሆኜ ነው የሰራሁት፡፡
ተምረዋል ማለት ነው?
እስከ ስድስተኛ ክፍል ተምሬ ሚኒስትሪ ወስጃለሁ፡፡ በየነ መርዕድ ት/ቤት ነው የተማርኩት። እዚሁ አዲስ አበባ ውስጥ ከዚያ በኋላ በርካታ መስሪያ ቤቶች ሰርቻለሁ… ይገርምሻል!
አሁን በጥንታዊት ኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር ውስጥ ተሳትፎም ምንድነው?
በፊት በሌላ ኮሚቴ ውስጥ እሰራ ነበር፡፡ አሁን የመቃብር ኮሚቴ ነኝ፡፡
በጡረታ ደሞዝ ነው የሚተዳደሩት?
ጡረታም አለኝ ግን ብዙ ልጆቼ ከውጭ በየአቅጣጫው ብር ይልካሉ፤ የብር ችግር የለብኝም። ከባለቤቴ ጋር ዘና ብዬ ተደስቼ ነው የምኖረው፡፡
እድሜዎ 95 ዓመት እንደሆነ ነግረውኛል፡፡ ግን ሙሉ ጥርስ፣ ሙሉ ጤና አለዎት፡፡ አመጋገብዎ እንዴት ነው?
የተገኘውን እበላለሁ፤ መጠጥ ድሮም አሁንም በአፌ አይዞርም፤ ውሃ ብቻ ነው የምጠጣው፡፡ ጥሬ ስጋ ድሮ እበላ ነበር፤ አሁን ለጤና ጥሩ አይደለም ስለሚባል ትቻለሁ፡፡
የታላቁን የህዳሴ ግድብ ለመጎብኘት ከፍተኛ ጉጉት እንዳለዎት ሰምቻለሁ…?
ወይ ልጄ ሁሉም በየጊዜው በየትውልዱ ታሪክ ይሰራል፡፡ በእኛ ትውልድ ያለ በቂ መሳሪያ በጦርና በጎራዴ ዘመናዊ መሳሪያ የታጠቀውን ጣሊያንን አሳፍረናል፡፡ አክሱምን፣ ላሊበላን፣ ጎንደርን ገንብተው ያለፉ ትውልዶች አሉ፡፡ ይሄ ትውልድ ደግሞ ለም አፈር አዝሎ ሲጓዝ፣ ሌላ አገር ሲያለማ የነበረውን አባይን ሲገድብ እድሜ ሰጥቶኝ ከደረስኩ እንዴት አልጓጓ? ግድቡን ጠዋት ጎብኝቼ ማታ ብሞት ደስታውን አልችለውም፡፡
ከዚህ በኋላ ስንት ዓመት መኖር ይፈልጋሉ?
እየውልሽማ… እግዚያብሔር ለአብርሃም 500 ዓመት ሲሰጠው፣ ለዚህች አጭር እድሜ ብዬ ቤት አልሰራም ብሎ በድንኳን ኖረ፡፡ እኔ አሁን ወደ 95 ዓመት እየሄድኩ ነው፡፡ ለእኔስ 150 ዓመት ቢሰጠኝ ምን ይለዋል? (ረጅም …..ሳቅ)

ሰሞኑን በእጅጉ ማርኮኝ የተመለከትኩት “Trance” የተሰኘ ፊልም ላይ፣ ዋና ገፀ-ባህሪው ሳይመን ሳያውቀው የገባበት የቁማር ጨዋታ (gambling) የለየለት ሱሰኛ ያደርገውና የዕዳ አረንቋ ውስጥ ይዘፈቃል፡፡ ከቁማር ሱሰኝነቱ ለመላቀቅ የዘየደው መላ ወደ ቴራፒስት ዘንድ መሄድ ነው፡፡ በሂፕኖቴራፒ ከቁማርተኝነቱ ለመፈወስ፡፡ ሂፕኖሲስ የህክምናው (ቴራፒው) ሂደት ሲሆን ባለሙያው ወይም ባለሙያዋ ሂፕኖቲስት ይባላሉ፡፡ ቴራፒውን የወሰደው ሰው ደግሞ “ሂፕኖታይዝድ” ሆኗል ይባላል፡፡
በነገራችሁ ላይ ሂፕኖሲስ ታካሚውን በሰመመን ስሜት ውስጥ በማስገባት፣ ሃሳቡንና ትኩረቱን በአንድ የሆነ ጉዳይ ላይ እንዲያነጣጥር፣ የተወሰኑ ቃላትን ወይም ዓ.ነገሮችን በመደጋገም አሊያም የአዕምሮ ምስል በመፍጠር… የሚሰጥ ህክምና (ቴራፒ) ነው፡፡ ሂፕኖሲስ ያልተፈለገ ባህሪን (ድርጊትን) ለማስወገድ ወይም ለመቆ›ጣጠር በቁጥጥር ሥር ለማዋል ጥቅም ላይ ሊውል ይችላል፡፡ ከሲጋራ ሱሰኝነት ለመላቀቅ፣ ከእንቅልፍ እጦት (Insomnia) ለመገላገል፣ ከመጠን በላይ የመብላት ፍላጐትን ለማስወገድ …ወዘተ ሊያግዝ እንደሚችል ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
ወደ ፊልሙ ልመልሳችሁ፡፡ በቁማር ሱሰኝነት ኑሮው የተቃወሰው ሳይመን፤ ኤልዛቤት ላምብ የተባለች ቴራፒስት ዘንድ በመሄድ ችግሩን ተናግሮ ቴራፒውን ይጀምራል፡፡ የቁማር ሱሰኝነቱ ስር የሰደደ በመሆኑ ብዙ ጊዜ እንደሚወስድበት ይገለጽለትና ህክምናውን ይቀጥላል፡፡ በዚህ ሂደትም ከኤልዛቤት ጋር እየተቀራረበ ይመጣል፡፡ የጦፈ የፍቅር ግንኙነትም ይጀምራል፡፡
ቴራፒስቷ ከደንበኞቿ ጋር እንዲህ ያለ ግንኙነት ውስጥ መግባት እንደሌለባት ታውቃለች፡፡ ግን አንዴ ሆነ፡፡ እናም “የፈሰሰ ውሃ አይታፈስም” ብላ ገፋችበት። ከጥቂት ጊዜ በኋላ የሳይመን ፍቅር ወደ ጥርጣሬና ቅናት እየተቀየረ መጣ፡፡ የት ገባሽ፣ የት ወጣሽ ማለት አበዛ፡፡ ፍቅረኛውን የሚያጣት፣ እየመሰለው ይጨነቅ ጀመር፡፡ ቅናቱ እየተባባሰ እንደ እብደት አደረገው፡፡ መላ ህይወቱን እሷ ላይ ጣለ፡፡ ከእሷ ከተለየ የሚሞት ሁሉ መሰለው፡፡ በዚህ የተነሳም ያፈቀራትን ያህል ጠላት፡፡ አንድ ቀን ሬስቶራንት ውስጥ ተቀምጠው ሳለ “ወንድ አየሽ” ብሎ በጥፊ አጠናገራት፡፡ ይሄን ጊዜ ነው ኤልዛቤት ከዚህ ጨዋታ መውጣት እንዳለባት የወሰነችው፡፡ ግን በየት በኩል? ሳይመን አለቅም ብሎ ሙጭጭ አለባት፡፡ ረዥም የይቅርታ ደብዳቤ ፃፈላት። እየደወለ ነዘነዛት፡፡ እያለቀሰ ተማፀናት፡፡ ኤልዛቤት ግን የዚህ መጨረሻ ምን እንደሚሆን አላጣችውም፡፡ ነገርዬው በዚህ ከቀጠለ የማታ ማታ እንደሚገድላት ቅንጣት አልተጠራጠረችም፡፡
ጉዳዩን ለፖሊስ ብታመለክትም ነገሬ ሳይሏት ቀሩ፡፡ ጠበቆች፤ ስሟን ቀይራ አገር ጥላ እንድትወጣ መከሯት፡፡ እሷ ደግሞ ይሄን ለማድረግ ፈቃደኛ አልነበረችም፡፡ ሁለት ጊዜ ተጎጂ መሆንን አልፈቀደችም፡፡ እናም ጉዳዩን በቁጥጥሯ ሥር ለማዋል መረጠች፡፡
ሳይመንን ከቁማር ሱሰኝነት ለመገላገል ወይም ቁማር ለማስረሳት ስትጠቀምበት የቆየችውን ቴራፒ ለዚህ ዓላማ አዋለችው፡፡ “መርሳት የምትፈልገው ቁማሩን ሳይሆን እኔን ነው” በማለት እርሷን እንዲረሳት ተከታታይ ቴራፒ ሰጠችው፡፡ ቀስ በቀስም እሷን እየረሳ መጣ፡፡ እሷን ብቻ ሳይሆን የፍቅር ግንኙነታቸውንም ጭምር ረሳው፡፡ ሁሉ ነገር ከአዕምሮ ትውስታው እልም ብሎ ጠፋ፡፡ የቁማር ሱሱን ሊረሳ ሄዶ ፍቅሩን ረስቶ ተመለሰ፡፡
አንዳንድ በፀብና በቅናት የተሞሉ አደገኛ የፍቅር ግንኙነቶች እንዲህ “ዲሊት” እየተደረጉ ከትውስታ ማህደር ቢጠፉ ብዙ ጥንዶችን ከከፋ ችግር ሊታደጉ ይችላሉ፡፡ በእርግጥ ወደ ፊልሙ መጨረሻ አካባቢ የሳይመን ትውስታ ይመለሳል፡፡ “ለምን እንድረሳ አደረግሽኝ?” ብሎ የቀድሞ ፍቅረኛውን ይጠይቃታል፡፡ ኤልዛቤትም “ትውስታህ በሰረገላ ቁልፍ ተከረቸመ እንጂ ከጥቅም ውጭ አልሆነም” ስትል ትመልስለታለች፡፡
ኤልዛቤት በሂፕኖቴራፒ ክህሎቷ ራሷን ከሞት፣ የቀድሞ ፍቅረኛዋን ደግሞ ከዕድሜ ልክ እስርና ፀፀት ለማትረፍ ችላለች፡፡ ይሄን ፊልም ተመልክቼ ስጨርስ ወደ አዕምሮዬ የመጣው፣ በሃይልና በዱላ የታጀበው የአገራችን የፍቅር ግንኙነት ነው፡፡ በበዛ ቅናት እየተሰቃየ ሚስቱን ለሚደበድብ ባል፤ ይሄ ቴራፒ ግሩም ይመስለኛል፡፡ ፍቅረኛውን ከእነ ትዝታዋ በማስረሳት አዲስ ህይወት እንዲመራ ለማድረግ ይረዳል፡፡
በሂፕኖቴራፒ ሰዎች እንዲረሱ ብቻ ሳይሆን የረሱትንም እንዲያስታውሱ (ትውስታቸው እንዲመለስ) ማድረግ ይቻላል፡፡ ሳይመን ጭንቅላቱ ላይ ጉዳት ከደረሰበት በኋላ ያስቀመጠበት የጠፋበትን የመኪና ቁልፍ በሂፕኖሲስ እንዲያስታውስ አድርጋዋለች - ቴራፒስቷ ኤልዛቤት፡፡ ዓምና ለእይታ የበቃውን “Trance” የተሰኘ ፊልም ፈልጋችሁ ተመልከቱት፡፡ ድንቅ ፊልም ነው!! (በነገራችሁ ላይ እኔ የተረኩት ከሙሉ ፊልሙ እጅግ ጥቂቱን ብቻ ነው)

ከ“አነስተኛና ጥቃቅን” ተነስቶ፤ ዛሬ የአለማችን ባለ ሃብት ሆኗል!
እንደ ቻይና ወጣቶች በቢል ጌትስ የቢዝነስ አርአያነት ለብልጽግና እንጥራለን?
ወይስ እንደ ለማኝ በቢል ጌትስ ምጽዋት ተማምነን እጅ እንስማለን?

“የአገሬ ሰውና የአገሬ መንግስት ይመሳሰላሉ፤ ራሳቸውን ጠልፈው መጣል ይቀናቸዋል” በሚል ርዕስ ባለፈው ሳምንት በአዲስ አድማስ የወጣው ጽሑፍ፤ በአንድ ሃሳብ ላይ የሚያጠነጥን ነበር። ስለ እድገትና ብልጽግና እናወራለን፡፡ ጥሩ ነገር መመኘት በጐ ነው፡፡ ነገር ግን ምኞታችንን እውን እንዳናደርግ፤ ራሳችንን ጠልፈን እንጥላለን ይላል ጽሑፉ፡፡ እንዴት?
ብልጽግናን፣ ቢዝነስን፣ ስኬታማንና ትርፋማነትን ከማክበር ይልቅ “የዚህ አለምን ህይወት” እየናቅን፤ መመነንን፣ ችግር መካፈልን፣ ምጽዋትን፣ ምስኪንነትንና መስዋዕትነትን እናመልካለን፡፡
በአንድ በኩል ብልጽግናን ብንመኝም፤ በሌላ በኩል ሁለመናችንን በፀረ ብልጽግና ሃሳቦችና ባህሎች ተብትበን አስረነዋል፡፡ እንዲህ ራሳችንን ጠልፈን የመጣል አባዜ እንደተጠናወተን የሚገልፀው ጽሑፍ፤ በርካታ ሰሞነኛ ዜናዎችን በማስረጃነት ያቀርባል፡፡ ይህ የምዕተ ዓመታት “በሽታ” ምንኛ ስር የሰደደና በሰፊው የተንሰራፋ እንደሆነም በዝርዝር ያስረዳል፡፡ እውነትም የባህል እና የአስተሳሰብ “በሽታ” ተጠናውቶናል፡፡ ሃሙስ እለት በቢል ጌትስ “የክብር ዶክትሬት” ሽልማት ላይም በግላጭ አየሁት - “የቢዝነስ ስኬትህን ሳይሆን የምጽዋት እጅህን እናደንቃለን” ብለን ሸለምነው፡፡
ይሄ ነው ዋናው በሽታችን - ለኋላቀርነትና ለድህነት የዳረገን ነባር በሽታ! በእርግጥ አንዳንድ ሰዎች በሽልማቱ ዙሪያ ሌላ ሌላ ቅሬታ ሲያነሱ ሰምቻለሁ፡፡ ለምሳሌ፤ የስራ ባልደረባው በማኔጅመንት መስክ ትምህርቱን ተከታትሎና ጥናት አካሂዶ በዶክትሬት ዲግሪ እንደሚመረቅ የገለፀልኝ አንድ ባለሙያ፤ የዚህኛው ዶክትሬት “የክብር ዶክትሬት” አይደለም ወይ? ሲል ጠይቋል። በእርግጥም የትምህርት ተቋም ውስጥ ገብቶ፤ በዶክትሬት ዲግሪ መመረቅ…ማለትም በማንኛውም መስክ የእውቀትና የክህሎት፣ የአቅምና የብቃት ባለቤት ወይም ጌታ መሆን፣ ትልቅ “ክብር” ነው፡፡
በዚያው መጠን፤ ከትምህርት ተቋም ውጭም፤ ብቃቱን ተጠቅሞ የስኬትና የሃብት ባለቤት (ጌታ) ለመሆን የቻለም፤ ክብር ይገባዋል፡፡ ደግሞስ ሌላ ምን የክብር ምንጭ አለ? የአንዳች ጠቃሚ ነገር ባለቤት፣ ጌታ ከመሆን ውጭ ሌላ የክብር ምንጭ የለም፡፡ ከሺ ዓመታት በፊት በስልጣኔ ጐዳና ሲራመዱ የነበሩት ኢትዮጵያውያን፣ ይህ እውነት ገብቷቸው ነበር፡፡ “ባለ” ወይም “በዓለ” የሚሉ ቃላት በመጠቀም ነበር አክብሮትና አድናቆታቸውን የሚገልፁት - ዛሬ “ባለ ሀብት” እንደምንለው፡፡
“ባለ” ወይም “በዓለ”… የአንዳች ነገር ባለቤት ወይም ጌታ መሆንን - ያስገነዝባል፡፡ ከዚህም ጋር ክብርና አድናቆትን ይገልፃል፡፡ በዓል ማለት ጌትነትና ባለቤት ነው፤ ክብር እና ሞገስም ነው፡፡ ለአማልክት እና ለጀግኖች፤ “በዓል” የሚል የማዕረግ መጠሪያ ይጠቀሙ ነበር፡፡ ባለነበል (ነበል -ባል)፤ የእሳት ጌታ ነው እንደማለት፡፡ ባለሀብት፣ ባለአገር፣ ባለአምባ ወዘተ… ብቃትና ባለቤትነትን፣ ከጀግንነትና ከክብር ጋር አጣምረው ነበር የሚያስቡት፡፡ ቅዱስ ሲሉ ጀግና ማለታቸው ነበር፡፡
ከጊዜ በኋላ የስልጣኔ አስተሳሰብ ሲጠፋ የስልጣኔ ጉዞውም ተረሳ፡፡ “የዚህ አለም ነገር” ሁሉ ከንቱ ነው ተባለ፡፡ የእውቀትም ሆነ የብቃት፣ የስኬትም ሆነ የሃብት ባለቤትነት ተናቀ፡፡ ክብርም አጣ፡፡ በዚያው መጠን ድንቁርናና ምስኪንነት፣ ውድቀትና ድህነት የሚወደስበት ኋላቀር ባህል ወረስን፡፡ እናም፤ ስልጣኔንና ብልጽግናን የምንፈልግ ከሆነ፤ በትምህርት ተቋምም ሆነ በሌላው የህይወት አለም የብቃትና የስኬት ባለቤትነትን ማክበር ይገባል፡፡ ለቢል ጌትስ የተዘጋጀው “የክብር ዶክትሬት” በዓይነቱ በአፍሪካ የመጀመሪያው ነው መባሉ ያልተዋጠላቸው ሰዎች በበኩላቸው፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ብቻ ሳይሆን መንግስት ጭምር የገባበት ጉዳይ መሆኑ እንደ ትልቅ ነገር መቆጠር የለበትም ብለዋል፡፡
ለተራ ነገርና ለቁም ነገር፣ ለትንሹም ለትልቁም… እንዲያው በዘፈቀደ “በአፍሪካ የመጀመሪያው…” እየተባለ ሲነገር መስማት ሊያስጠላ ይችላል፡፡ የአዲስ አበባ አስተዳደር፤ የጐዳና ቆሻሻ የሚያፀዱ መኪኖችን እንደሚገዛ የገለፀ ሰሞን፤ “በአፍሪካ ደረጃ በሁለተኝነት የሚጠቀስ” ማለቱን ታስታውሱ ይሆናል፡፡
እንግዲህ ነገሩን ስታስቡት፤ “በአፍሪካ የመጀመርያው፣ በአፍሪካ ሁለተኛው…” የሚያስብል ጉዳይ አይደለም፡፡ በዚያ ላይ ደግሞ መረጃው እውነት ነው፡፡ ከ20 ዓመታት በፊት እዚሁ አገራችን ውስጥ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የጐዳና ማጽጃ መኪና ይጠቀም ነበር፡፡ በበርካታ የአፍሪካ አገራትም እንዲሁ ከአመታት በፊት ተጀምሯል፡፡ ይህንን መረጃ ለማግኘት፤ በኢንተርኔት አንድ ሁለት ደቂቃ ድረገፆችን ገለጥለጥ ማድረግ ይበቃል፡፡ ዛሬ‘ኮ …ክብር ለነ ቢል ጌትስ ይድረሳቸውና፤ ጀግኖቹ የቴክኖሎጂና የቢዝነስ ሰዎች በየበኩላቸው በተቀዳጁት የጥረት ስኬት አማካኝነት፤ እንደ “ተዓምር” በሚያስደንቅ ሁኔታ በቀላሉ ብዙ ብዙ መረጃ ማግኘት የምንችል ሰዎች ሆነናል፡፡ የብቃት ባለቤት አድርገውናል - የብቃት ባለቤት የሆኑ ጀግኖች፡፡
ለማንኛውም ለቢል ጌትስ የተሰጠ የክብር ዶክትሬት…”በዩኒቨርስቲ ብቻ ሳይሆን በመንግስትም ጭምር የተዘጋጀ ስለሆነ ከአፍሪካ የመጀመሪያው ነው” መባሉ ብዙም ትርጉም የለውም፡፡ “ከአፍሪካ የመጀመሪያው” የሚል ተቀጥላ ሳያስፈልገው፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ መንግስት ለቢል ጌትስ ክብር እና አድናቆቱን ገለፀ ቢባል በቂ ነው፡፡ እንዲያውም “ትልቅ ቁም ነገር” ሊሆን ይችል ነበር፡፡ ለምን በሉ፡፡
ብዙዎቻችን ብልጽግናን እየተመኘን የስኬትን ወሬ ማዘውተር ጀምረን የለ? በጐ ጅምር ነው። መንግስትም እንዲሁ ስለ እድገትና ብልጽግና እየደጋገመ ማውራቱ መልካም ነው፡፡ “ዋናው ጠላታችን ድህነት ነው” በሚል አባባል የሚታጀበው የመንግስት ንግግር፤ የአገሪቱ የወደፊት ተስፋ ያለው “ሃብት ፈጣሪ የኢንዱስትሪ ቢዝነስ” ላይ እንደሆነ ይገልፃል፡፡
ሃብት ፈጣሪ የኢንዱስትሪ ቢዝነስ የሚስፋፋው እንዴት ነው? ብላችሁ ጠይቁት፡፡ ምላሽ ይሰጣችኋል፡፡ የመንግስት የኢኮኖሚ ፖሊሲ፣ የኢንዱስትሪ ፖሊሲ፣ የአምስት አመት የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ፣ አመታዊ የኢኮኖሚ ሪፖርት…እና ሌሎች ሰነዶችን ስትመለከቱ፤ ተመሳሳይ ምላሽ ታገኛላችሁ፡፡
ከድህነት በመላቀቅ ብልጽግናን እውን የምናደርገው፤ ሃብት ፈጣሪ የቢዝነስ ሰዎች ሲበራከቱ ብቻ እንደሆነ የሚገልፀው መንግስት፤ የተማሩ ወጣቶች በሥራ ፈጣሪነት በአነስተኛና ጥቃቅን የቢዝነስ መስክ እየተሰማሩ ስኬታማ ሲሆኑ፤ ትልልቅ የኢንዱስትሪ ቢዝነስ እንደሚስፋፋ ያስረዳል፡፡ በዚህም ምክንያት “የኢንተርፕርነርሺፕ አስተሳሰብ፣ እውቀትና ክህሎት” ቀዳሚ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል” ሲልም በሰነዶቹ ይገልፃል - ለአገሪቱ የብልጽግና ተስፋ ቁልፍ ጉዳይ መሆኑን በመጥቀስ፡፡ በአጭሩ፤ ከችጋር ሳንላቀቅ በህይወት ለመቆየት ብቻ የምንፈልግ ከሆነ እርዳታና ምጽዋት ላይ ማተኮር እንችላለን፡፡ ድህነትን ወዲያ አሽቀንጥረን ወደ ብልጽግና ለመንደርደር ከፈለግን ግን፤ በአነስተኛና ጥቃቅን ቢዝነስ ላይ ተሰማርተው ለብልጽግና የሚጣጣሩ ሚሊዮን ወጣቶች፣ ስኬታማ ሃብት ፈጣሪዎች፣ ትርፋማ የቢዝነስ ሰዎች ያስፈልጉናል ይላል መንግስት፡፡
ታዲያ ሃብት ፈጣሪ ይሆናሉ ተብለው ለሚጠበቁ ለእነዚህ ወጣቶች፣ ከእነቢል ጌትስ የበለጠ አርአያና ጀግና ከወዴት ይገኛል? እንደ አብዛኛው አነስተኛና ጥቃቅን ተቋም፤ ቢል ጌትስ ከቤተሰቦቹ መኖሪያ ቤት ስር፣ ጠባብ ምድር ቤት ውስጥ ነው ቢዝነሱን የጀመረው፡፡ በአካባቢው ለሚገኙ ትናንሽ ድርጅቶች አነስተኛ አገልግሎቶችንና የቴክኖሎጂ መፍትሔዎችን በመስጠት የተጀመረው የቢል ጌትስ ቢዝነስ፤ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣው፤ ቀን ከሌት በየእለቱ ለ16 ሰዓታት ያህል ተግቶ ስለጣረ ነው፡፡
በሰፈርና በከተማ ታጥሮ አልቀረም፡፡ በአገር ደረጃ ብቻ ሳይሆን በአለም ዙሪያ፤ የሰው ልጆችን ሕይወት የሚያሻሽሉ ቴክኖሎጂዎችን በመፍጠር የአለማችን ቁንጮ ሃብታም ለመሆን በቅቷል። በስኬታማነቱና በጀግንነቱ የተነቃቁ እልፍ ወጣቶችም፤ በየራሳቸው መስክ ተዓምር የሚያሰኝ የሃብት መጠን እንዲፈጥሩ አርአያ ሆኗቸዋል- በአሜሪካ ብቻ አይደለም፡፡ በቻይናም ጭምር እንጂ፡፡ ሃብትን እንደ ኩነኔ፣ በሚቆጥር ጥንታዊ ባህልና ባለሀብትነትን እንደ ወንጀል በሚቆጥር የሶሻሊዝም አስተሳሰብ ለድህነትና ለረሃብ ተዳርጋ የነበረችው ቻይና፤ “ባለሀብትነት ቅዱስነት ነው” በሚል ሃሳብ ነው የብልጽግና ጉዞ የጀመረችው፡፡ በእርግጥም ባለፉት 20 ዓመታት የቻይና ወጣቶች በአድናቆት ከሚጠቅሷቸው ጀግኖች መካከል፣ ቢል ጌትስ ተጠቃሽ መሆኑ አይገርምም፡፡ እኛም ብልጽግናን ከምር የምናከብር ከሆነ የቢዝነስ ስኬታማነቱ ትልቅ ቁምነገር መሆኑን በመገንዘብ፣ አክብሮትና አድናቆታችንን ለመግለጽ፣ የክብር ዶክትሬት ብንሰጠው መልካም ነበር፡፡ በእርግጥ ቢል ጌትስ ለኢትዮጵያ ብዙ የገንዘብ እርዳታ ሰጥቷል፡፡ ማመስገን ይገባል፡፡
ነገር ግን እርዳታና ምጽዋት፤ ለጊዜው ድህነትን ለመቋቋም ይጠቅም እንደሆነ እንጂ ለብልጽግና አያበቃም፡፡ የላቀ ክብር እና አድናቆት መስጠት ያለብን ለቢዝነስ ስኬታማነትና ለሃብት ፈጣሪነት ነው - ብልጽግናን የምናከብር ከሆነ፡፡ አሳዛኙ ነገር፤ ከእርዳታና ከተመጽዋችነት በተቃራኒ፣ የቢዝነስ ስኬትና ሃብት ፈጠራ ዋና የአገሪቱ የብልጽግና ተስፋዎች ናቸው የሚል መንግስት፤ ለቢል ጌትስ የክብር ዶክትሬት የምንሰጠው በሃብት ፈጣሪነቱና በቢዝነስ ስኬታማነቱ ሳይሆን በእርዳታ ለጋሽነቱ ነው ማለቱ ነው፡፡ ቢያንስ ቢያንስ፤ “ባለ ሃብትነቱንና ስኬታማነቱን እናከብራለን፤ እናደንቃለን፡፡ የዛሬው ሽልማት ግን ለሰጠን እርዳታ ምስጋናችንን የምንገልጽበት ነው” ብሎ መናገር ይቻል ነበር፡፡ ይሄም ይቅር፡፡ ግን፤ እርዳታ ለመስጠት የቻለው‘ኮ፤ በቢዝነስ ስኬታማነቱ ሃብት የፈጠረ ጀግና ስለሆነ ነው፡፡ ሃብት መፍጠር እንጂ ሃብት መስጠትማ ቀላል ነው፡፡ አርአያ አያስፈልገውም፡፡  

ባለፈው ሳምንት በጎንደር የቅማንቶች መብት ተሟጋች ከሆኑት ከአቶ ነጋ ጌጤ ጋር ባደረግነው ቃለ-ምልልስ “ጎንደር የቅማንቶች ናት” በማለት ሰፊ ማብራሪያ መስጠታቸው ይታወሳል፡፡ ዛሬ ደግሞ የታሪክ ተመራማሪው አቶ ሲሳይ ሳህሌ በጎንደር ታሪክና ሥልጣኔ ዙሪያ የሰጡንን ማብራሪያ እናቀርባለን፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ ቃለ-ምልልስ ያደረገላቸው የታሪክ ተመራማሪ፣ የፈረንሳይ ከተማ “ቬንሰንት - ጎንደር ያልተማከለ የትብብር ስምምነት የራስ ግንብ ሙዚየም ፕሮጀክት አስተባባሪም ናቸው፡፡

 ጎንደር እንዴት ተመሰረተች?
በ1623 ሰኔ ወር ላይ አፄ ሱንስዮስ ለልጃቸው ለአፄ ፋሲል በህይወት እያሉ ስልጣናቸውን ያስተላልፋሉ፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት ሜንዴዝ የሚባል የካቶሊክ ሚሽነሪ መጥቶ ነበር፡፡ አዘዞ (አሁን አፄ ቴዎድሮስ ኤርፖርት ያለበት ቦታ)፣ ጎርጎራ እና ደንቀዝ የሚባሉ ቦታዎች ሶስት የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያኖች ተሰርተው ነበር፡፡ ደንቀዝ ላይ ያለው እንደ ቤተመንግስትም ያገለግል ነበር፡፡ አፄ ሱስንዮስ ስልጣናቸውን አስተላልፈው ያረፉትም በዚሁ የካቶሊክ ደብር ውስጥ ሆነው ነው፡፡ ከዚያ በኋላ አፄ ፋሲለደስ የህዝቡን ፍቃድ ለማሟላት ኢየሱሳውያኑን ከሃገር አባረሩ፡፡ ስልጣናቸውን ተቀብለው አፄ ከተባሉ ከ4 ዓመታት በኋላ አሁን ቤተመንግስታቸው ከሚገኝበት ቦታ መጥተው የዛሬዋን ጎንደር ሊመሰርቱ ችለዋል፡፡
ለምን ወደ ጎንደር መምጣት አስፈለጋቸው? እዚያው አባታቸው የነበሩበት ቦታ ላይ መንግስታቸውን መመስረት አይችሉም ነበር?
በሶስት ምክንያቶች ነው እንደዚያ ያደረጉት። አንደኛው ከእምነት አንፃር፣ ጎርጎራ ካቶሊካውያኑ የነበሩበት ቦታ ስለነበር የረከሰ ነው ተብሎ ታመነ። ስለዚህ አዲስ ቦታ መቀየር አስፈለጋቸው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት፣ ጎርጎራ ወባማ አካባቢ ስለነበር ሰራዊታቸውን ፈጀባቸው፡፡ እናም ከጤና አኳያ የአሁኑ ጎንደር ተመራጭ ሆነ፡፡ ሦስተኛው ምክንያት፣ ጎንደር ወይና ደጋ አየር ንብረትና ከ40 በላይ ምንጮች ያላት ነበረች፡፡ በወንዞችም የተከበበች በመሆኗም የሰራዊቱን የውሃ ፍላጎት ታሟላ ነበር፡፡
አሁን ቤተ መንግስቱ ያለበት ቦታ 2200 ሜትር ከባህር ጠለል በላይ ከፍታ አለው፡፡ ዙሪያውን ደግሞ እስከ 3 ሺህ ሜትር ከፍታ ያላቸው ተራራዎች አሉ። እነዚህ ተራራዎች የአየር ወለድ በሽታ ቢመጣ ወደ ከተማዋ አያስገቡም/አያሳልፉም ተብሎ ይታሰባል፡፡ ከጦር ስትራቴጂ አንፃርም በተራራ መከበቧ ጠላት በቀላሉ እንዳይገባ ይከላከላል፡፡ ተራራዎቹ በትልልቅ ዛፎች የተጠቀጠቁ መሆናቸውም የማገዶ ፍጆታን ያሟላሉ፡፡ በእነዚህና በሌሎች ምክንቶች ጎንደር በ1628 ዓ.ም ተመሰረተች፡፡
አፄ ፋሲለደስ በ1660 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ፣ የጎንደር ህዝብ ብዛት 27 ሺህ ደርሶ ነበር። ይሄ የሚያሳየው ከተማዋ በወቅቱ እጅግ ሰፊ መሆኗን ነው፡፡ በእነ እቴጌ ምን ትዋብ ዘመን ደግሞ የህዝብ ብዛቱ እስከ 100 ሺህ ደርሶ ነበር፡፡
ከብሄር፣ ከሃይማኖት አንፃር ምን አይነት ማህበረሰብ ነበር የሚኖርባት?
እንደውም ጎንደርን በወቅቱ ከነበሩት የሃገሪቱ አካባቢዎች ለየት የሚያደርጋት ቤተ እስራኤሎች፣ ባህላዊ እምነት ተከታዮች፣ ሙስሊሞች፣ የውጭ ዝርያ ያላቸው ቱርኮች… ሁሉም አንድ ላይ እንደልባቸው ተስማምተው የሚኖሩባት መሆኑ ነበር፡፡ በተለያዩ ሥራዎች ላይ የተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎችም ይኖሩባት ነበር፡፡ አናፂዎች፣ ግንበኞቹ፣ ሸማ ሰሪዎች፣ የብረታ ብረትና የወርቅ ስራ የሚሰሩ እንዲሁም ነጋዴዎች ሁሉ አንድ ላይ ይኖሩባት ነበር፡፡ በጊዜው ንግዱን በሚገባ ያውቁታል ተብሎ ስለሚታመን ነጋድራሶች ከሙስሊሞች ነበር የሚመረጡት፡፡
አፄ ፋሲለደስ ቤተ-መንግስታቸውን ካሳነፁ በኋላ በዙሪያው ሰባት ቤተ-ክርስቲያኖችን አሰርተዋል፡፡ በየጊዜው ነገስታቱ እየተተኩ ለ120 ዓመታት እጅግ የረቀቀ የህንፃ ግንባታ ጥበብን ሰርተው አልፈዋል፡፡ የጎንደር ስልጣኔ የመጨረሻዋ ንግስት የነበሩት እቴጌ ምንትዋብም የራሳቸውን ቤተ-መንግስትና ቤተ-ክርስቲያን አሳንፀዋል ቁስቋም ትባላለች፡፡
አፄ ፋሲል ለምን 7 ቤተ-ክርስቲያናትን በዙሪያቸው አሰሩ?
በወቅቱ እንደሚታወቀው ነገስታቱ በእምነታቸው ጠንካሮች ነበሩ፡፡ የጊዮርጊስ ታቦት ዘማች ታቦት ነው፤ ተዋጊ ነው፡፡ በአድዋ ጦርነት ጊዜም ቢሆን አፄ ምኒልክ ይዘው ዘምተዋል። የድንግል ማርያም ደግሞ ከንግስቲቱ ማረፊያ ቤት አጠገብ እንድትተከል ተደርጓል፡፡ ከትውፊቱ ከተቀበልነው ታሪክ እንደምንረዳው፣ አፄ ፋሲል ቤተ መንግስታቸውን ሲገነቡ አውሬ ሲያስቸግራቸው ባህታውያን የአቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስን ታቦትን ትከል ብለው ሲመክሯቸው ያንን አደረጉ፡፡ መብረቅ ሲያስቸግራቸው የቅዱስ ሚካኤልን ታቦት፣ በሽታ ሲያስቸግራቸው የዓለም መድኀኒት የሆነውን የመድኀኒዓለም ታቦት እንዲተክሉ ተመከሩ፡፡ በዚህ ሂደት ነው ደብራቱን በዙሪያቸው የተከሉት ተብሎ ይነገራል፡፡ በሌላ በኩል በወቅቱ ካቶሊኮች ተባረው “ፋሲል ይንገስ ሃይማኖት ይመለስ” ተብሎ ሲታወጅ፣ አፄው ለሃይማኖታቸው ያላቸውን ፅናት ለማሳየት በርካታ ቤተ-ክርስቲያናትን እንደተከሉ ይታመናል፡፡
በዚያን ጊዜ የቤተ-መንግስቱ የአኗኗር ስርአት ምን ይመስል ነበር?
በአጠቃላይ የቤተ መንግስቱ ቅጥር ግቢ 70 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ነው ያረፈው፡፡ 12 በሮችም አሉት፡፡ ወደ ቅፅሩ የሚገባው እንደየደረጃውና ማዕረጉ በሚፈቅድለት በር ብቻ ነው፡፡ ራስች በር - ራሶች ብቻ የሚገቡበት ነው፣ የንጉሱ በር (ጃንተከል በር) ንጉሱ ብቻ የሚገቡበት ነው፡፡ ግምጃ ቤት በር የሚባል አለ - የግምጃ ቤት አስተናባሪዎች የሚገቡበት ነው፡፡ ቀጭን አሸዋ በር የሚባል አለ ይህ የግንባታ እቃዎች የሚገቡበት በር ብቻ ነው፡፡ እርግብ በር የሚባለው ደግሞ የደናግላን እና የመነኮሳት በር ነው፡፡ እንቢልታ ነፊዎች ብቻ የሚገቡበት ደግሞ እንቢልታ በር ይባላል፡፡ በሃዘን ጊዜ ሃዘንተኞች የሚገቡበት በር ተዝካሮ በር ይባላል፡፡ ተዝካሮ በር ፊት ከቤተመንግስቱ በስተደቡብ ባለው አነስተኛ ሜዳ ላይ አስከሬን ተቀምጦ ይለቀሳል፡፡ በጥንቱ የጎንደር ባህል ቦታው ሰዎች ሲሞቱ አስከሬናቸው ተቀምጦ ረዘም ላለ ሰአት ለቅሶና የሽኝት ስነ ስርዓት የሚከወንበት ነው፡፡ ባልደራስ በር የሚባለው ደግሞ ፈረሰኞችና የፈረሰኛ አዛዥ በር ነው፡፡ የንጉሱ ፕሮቶኮሎች የሚገቡበት በር ደግሞ “ኳሊ” በር ይባላል፡፡ በዚህ በኩል ባለጉዳዮችም ሆኑ የንጉሱ የቅርብ አጋዞች ይስተናገዱ ነበር፡፡
ንጉሡ በወቅቱ የከተማውን ህዝብ ግብር ያበሉ ነበር?
እንግዲህ በኢትዮጵያ ታሪክ ንጉሱ ግብር ካላበላ ምኑን ንጉስ ሆነው ይባል ነበር፡፡ ግብር ማስገበርም አለበት፡፡ ግብር በወርቅ፣ በብር፣ በከብት፣ በአሞሌ፣ በጥይት በመሳሰሉት መልክ ከነዋሪው ይሰበሰባል። ንጉሱ ደግሞ በምትኩ ለታችኛው የህብረተሰብ ክፍል ግብር ሰብስቦ በየጊዜው ያበላል፡፡ ራሶችና መኳንንቶችም በየአውራጃቸው ላለ ህዝብ ግብር ማብላት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ግብር ሲበላ ሰው እንደማዕረጉ ነው የሚቀመጠው፡፡ መጀመሪያ ንጉሱ ይቀመጣሉ፤ ከዚያ ንግስቲቷ ይቀጥላሉ፣ እጨጌውና የአክሱም ንቡረ ዕድ ይከተላሉ፡፡ እንዲህ እንዲያ እያለ መኳንንቱ በየደረጃቸው ይቀመጣሉ፡፡ ብዙውን ጊዜ ከፋሲካ በኋላ ነው ግብር የሚበላው፤ በበአላትም እንደአስፈላጊነቱ ንጉሱ ደግሶ ህዝቡን ያበላል፡፡  
ዳኝነት እና ፍርድስ እንዴት ነበር የሚከናወነው?
ዳኝነት እሚሰጠው እምነትን መሰረት በማድረግ ነበር፡፡ የእምነት ወይም ከፍተኛ ሃገራዊ ጉዳይ ከሆነና በመኳንንቱ መወሰን የማይችል ከሆነም ዙፋን ችሎት ላይ ይቀርባል፡፡ በእምነት ጉዳይ ክርክር ስለመካሄዱ ሁሌም በምሳሌነት የሚጠቀሰው የአልፈንዞ ሜንዴዝ እና የእጨጌ ጊዮርጊስ ክርክር ነው፡፡ በወቅቱ አልፈንዞ ሜንዴስ ከእጨጌው የሚቀርብለትን መከራከሪያ መመለስ አቅቶት ነበርና አንድ ጥያቄ ጠየቃቸው። “ስላሴዎች ሁል ጊዜ ፀጉራቸውን የማይላጩት ለምንድን ነው?” በማለት እሳቸውም “አንተ ቅንድብህን ትላጨዋለህን?” ሲሉ ጥያቄውን በጥያቄ መለሱለት፡፡ ቀጥሎም “የአብ ፊቱ ወዴት ነው?” ሲል ጠየቀ፡፡ እሳቸውም ጧፍ አበሩና “የዚህ መብራት ፊቱ ወዴት ነው?” አሉት፡፡ መልስ ሊሰጣቸው አልቻለም፡፡ በዚህም የእግዚአብሔር ፊት በሁሉም አቅጣጫ ነው ብለው ክርክሩን ረቱት ይባላል፡፡
ከፋሲል በኋላ አፄ (ፃድቁ) ዮሐንስ ነበሩ፡፡ እሳቸው የእንስሳትን መብት እስከማስጠበቅ የደረሱ ሰው ናቸው፡፡ ከደግነታቸው ብዛት ትልቅ ደውል በውጨ በኩል አስተክለው ነበር፡፡ ዳኝነት ጎደለብኝ ተበደልኩ የሚል ሰው መጥቶ ይደውላል፡፡ ከዚያም ይገባና ከንጉሱ ዘንድ ፍርድ አግኝቶ ይሄዳል፡፡ አንድ ጊዜ ምን ሆነ፡- ዝናብ እየዘነበ ነበር፡፡ ደውሉ ይደወላል፡፡ በዚህ ዝናብ ማን ፍርድ የጎደለበት ይሆን የመጣው ብለው እልፍኝ አስከልካያቸውን ይልኩታል፡፡ “ኧረ ጃንሆይ  አህያ ነው እንጂ ሰውስ የለም” ይላቸዋል፡፡ አህያውን አስገባው አሉት፡፡ አህያው ሲታይ ጀርባው ተጋግጧል፡፡ ባለቤቱ ተፈልጎ ይቅረብ ተባለና መጣ፡፡ “ለምን እንዲህ አደረክ፣ እድሜ ልኩን ያገለገለህን አህያህን ለምን ጣልከው?” ሲሉ ሰውየውን ገስጸው ቀጥተው ላኩት፡፡ አህያው ደግሞ በቤተ መንግስት ውስጥ ገብስና ባቄላ እየበላ እንዲኖርና ከቁስሉ እንዲያገግም ተደረገ፡፡ በዚያውም “የተገጠበ አህያ ጭነት እንዳይጫን” የሚለው አዋጅ ታወጀ፤ ጭኖ የተገኘም ይቀጣ ነበር፡፡ ያኔ ነው የእንስሳት መብት የታወጀው፡፡
ጎንደር የ44 ታቦታት መገኛ ሲባል ምን ማለት ነው?
ጎንደር ከመመስረቷ በፊት በአካባቢው አራት ደብሮች ነበሩ፡፡ አንደኛው አርባዕቱ እንስሣ ይባላል፡፡ በሌላ አቅጣጫ ቃአ ኢየሱስ የሚባል አለ፡፡ ጊዮርጊስ በሌላ አቅጣጫ አለ፤ አበራ ጊዮርጊስ የሚባልም አለ። ከዚያ በኋላ አፄ ፋሲል 7 ተከሉ፡፡ ፃድቁ ዮሐንስ 2 ተከሉ፣ አድያም ሰገድ ኢያሱ ደብረ ብርሃን ስላሴ ጨምሮ 2 ተከሉ፡፡ እንዲህ እንዲያ እያሉ ነገስታቱ በተፈራረቁ ቁጥር አዳዲስ ደብሮችን ሲተክሉ ኖሩ። በዚህ ሂደት በእነዚህ ነገስታት 30 ተተከሉ። 14 ያህሉ ደግሞ ቀድሞም የነበሩ ናቸው፡፡ እነዚህ ተደምረው ጎንደር የ44 ታቦት መገኛ ሃገር ተባለች፡፡ ኋላ ላይ በደርቡሽ ጦርነት 4 ያህሉ ተቃጥለው ነበር፡፡ ሃገሬው የተቃጠሉትን እንደገና ሰርቷቸው ነበር፡፡ አሁን ሁለቱ እየተሰሩ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ሌሎች ደብሮች በብዛት የተተከሉ ቢሆንም የጥንቱን የጎንደር ስልጣኔ ለማስታወስ 44ቱ ታቦታት የጎላ ቦታ አላቸው፡፡
ጎንደር የሚለው ስያሜስ ከየት የመጣ ነው?
ብዙ አፈታሪኮች አሉ፣ ነገር ግን ዋናው ማየት ያለብን የታሪክ ጥራዞችን ነው፡፡ የአፄ አምደፅዮን ዜና መዋዕል ላይ “ጎንደር” የሚለው ስም ሰፍሯል። ጎንደር ከመመስረቷ ከ300 ዓመት በፊት መሆኑ ነው፡፡ ወደ አፈታሪኩ ስንመለስ ቃሉ የማን እንደሆነ ባይታወቅም ጉንዳ ሃገር ወይም ትልቅ ሃገር ማለት ነው፡፡ አንዳንዶቹ ጓንግ እና ዳራ ከሚሉ ሁለት ቃላት የመጣ ሲሆን በአንገረብ እና ቃሃ ወንዝ መካከል ስላለች ነው ይህ ስም የተሰጣት ይላሉ፡፡ ግን የተጨበጠ ነገር የለውም፡፡
ነገስታቱ ይህን የቤተመንግስቱን ቦታ ከመያዛቸው በፊት ቦታው ላይ ምን ነበር?
እንደ አፈታሪክ እዚህ ቦታ ላይ (አሁን ቤተመንግስቱ ያለበት) ውሃ ነበር ይባላል፡፡ ውሃውን አድርቀው ቤተ መንግስታቸውን ሰሩ፤ አንዳንድ ታሪክ ደግሞ ቦታው የባላባቶች/የእርሻ ቦታ ነበር ይላሉ። ሌሎች አፈታሪኮች አፄ ፋሲል አደን ወጥተው አንዳንዶች ጎሽ ይላሉ ሌላው አንበሳ ይላል እያባረሩ መጥተው እዚህ ቦታ ሲደርሱ ተሰወረባቸው፤ ባህታዊ ተገልጦ ቤተ መንግስትህን የምትሰራበት ቦታ ይሄ ነው ብሎ ነገራቸው ይባላል፡፡ ከዚያ በፊት መላዕኩ ራጉኤል “ጎ” የሚባል ቦታ ላይ ትነግሳለህ ብሎ በራዕይ ይነግራቸው እንደነበር ይነገራል፡፡ “ጎ” ሲላቸው ቦታውን ፍለጋ ጎዛራ፣ ጎጃም፣ ጎርጎራ ሄደው በመጨረሻ ጎንደር ፀንቶላቸዋል ነው የሚባለው። ነገር ግን በዚህ አካባቢ አድባራት በፊትም መኖራቸውን ስናይ ሰዎች ይኖሩበት እንደነበር ያመላክተናል፡፡
የኖህ መቃብር ነው የሚል ታሪክም ይነገራል?
ሰዎች የራሳቸውን ታሪክ ይዘው ሊነሱ ይችላሉ። እኔም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ይሄን ነገር ሰእየሰማሁ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በ1960ዎቹ የተፃፈ አንድ ታሪክ የሚያሳየው፤ ፋሲል ቤተመንግስቱን እንደ ኖህ መርከብ አድርጎ እንደሰራው ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው ታሪክ የመጣው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ነው፤ ግን ሰፊና ጥልቀት ያለው ጥናት ይፈልጋል፡፡
በ150 ዓመታቱ የጎንደር ስልጣኔ ከታዩ ዘመናዊ ነገሮች ጥቂቶቹን ቢጠቅሱልን…
የቤተ መንግስቱ የህንፃ ጥበብ ዋናው ነው፡፡ አንዳንዶች የውጭ ሰዎች እጅ አለበት ይላሉ፤ ነገር ግን አሰራሩ በፊትም በአክሱም ዘመነ መንግስት የነበረ ነው፡፡ ህንዳውያንም ሆነ ፓርቹጋሎች ከመምጣታቸው በፊት እንደነበር ይናገራል፡፡ እ.ኤ.አ ከ1563-97 ዓ.ም የነገሱት አፄ ሰርፀድንግል ቤተ መንግስታቸው እንፈራዜ የምትባል ቦታ (ከጎንደር ወደ ባህርዳር ሲሄድ 60 ከሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ቦታ) ላይ የሚገኝ ቤተ መንግስት ላይ ይህ ቴክኖሎጂ ተሰርቶበታል፡፡ ስለዚህ የውጭ ኃይሎች እጅ አለበት የተባለው አያሳምንም፡፡
ሌላው ግዙፍ የሆኑ የንግድ መስመሮች - እስከ አውሮፓ፣ ኤሽያ የሚዘልቁ ተፈጥረው ነበር፡፡ የቤተ መንግስቱን አኗኗር ካየን ደግሞ ዘመናዊ ነበር፡፡ ዛሬ ፋሽን የምንለው… በዚያን ጊዜ ቀጭን ፈታዮች በሚባሉ ባለሙያዎች ለቤተ መንግስቱ ወይዛዝርት በየአይነቱ አልባሳት እየተሰሩ ያንን ፋሽን ይከተሉ ነበር፡፡ ዛሬ “ስቲም” የምንለው ያኔ “ወሸባ” ይባል ነበር፡፡ የፀጉር፣ የንቅሳት አይነት እንደፋሽን ይታይ ነበር፡፡ ዛሬ ዶሮ አስራ ሁለት ብልት አላት እንላለን። ያ መለኪያ የወጣው በወ/ሮ ምንትዋብ ጊዜ ነው። የዓሣ አሰራርና የተለያዩ የምግብ አሰራሮች ያኔ የመጡ ናቸው፡፡ ይህ ስርአት እንግዲህ ወደ ከተማው ተስፋፍቷል፡፡ እኛ ዛሬ የተጣራ ውሃ እያልን የታሸገ ውሃ እንጠጣለን፡፡ ይሄ በዚያን ጊዜም ይደረግ ነበር። የፈረስ ማቆሚያ (ፓርኪንግ) አገልግሎት ይሰጥ ነበር፡፡ ዛሬ የመኪና ፓርኪንግ እንደምንለው በአፄ በከፋ ዘመን ባለ ዘጠኝ በር ዘመናዊ የፈረስ ማቆሚያ /ፓርኪንግ/ ተሰርቶ ነበር፡፡ እንግዶች ፈረሶቻቸውን እዚያ ነበር የሚያቆሙት፡፡
በ5 ዓመት የጣሊያን ወረራ ቤተ መንግስቱ ለጣሊያን ገዢዎች መቀመጫነት አገልግሏል ይባላል?   
በሚገባ አገልግሏል፡፡ እንዲያውም ጣሊያን ከተማዋን ለሁለት ከፍሎ ነበር የሚያስተዳድረው። ከጃን ተከል በታች ያለው የሃገሬው ወይም የሃበሻ መንደር ነበር፡፡ አሁን ፒያሳ የምንለው ደግሞ የጣሊያኖች ነበር፡፡ ያኔ ሃበሾች ወደ ነጮች መንደር መዝለቅ አይፈቀድላቸውም፡፡ በቤተ መንግስቱ ውስጥም ለግብር በሚቀመጡበት ወቅት ነጮቹ በተመረጠ ቦታ ሃገሬው በሌላ ቦታ ሳይቀላቀሉ እንዲቀመጡ ይደረጋል፡፡ ምግብ ሲቀርብም ነጮቹ በስርአቱ ይመገባሉ፡፡ ሃበሾቹ ተሻምተው እንዲመገቡ ይደረግ ነበር፡፡ ጣሊያን ቤተ መንግስታቱ በጥቁሮች መሰራታቸውን አምኖ ላለመቀበል “የፖርቹጋል ግንቦች” ይላቸው ነበር፡፡ የከተማዋን ስያሜዎችም በብዛት ቀይሮ ነበር፡፡
ጃንተከል ዋርካ ዝነኛ ነው፤ ስለሱ ታሪክ ይንገሩን…
ጃንተከል እንግዲህ አፄ ፋሲል ተከሉት ተብሎ ይታመናል፡፡ ለዚያም ነው ጃንሆይ የተከሉት ለማለት ጃን ተከል የተባለው፡፡ በወቅቱ የሃገር ሽማግሌዎች በስሩ ተቀምጠው ይወያዩ ነበር፡፡ ስቅላትን የመሳሰሉ ፍርዶችም ይፈፀሙበት እንደነበር በስፋት ይነገራል።

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
“ወራሪም ፈጣሪን ላያቅ
የጣለውን በስሏል እንጂ፣ ወድቋል ብሎ ግፉ ላያልቅ…”
ይላል ሎሬት ጸጋዬ፡፡ እኛም ዘንድሮ የጣልነውን “ወድቋል” ሳይሆን “በስሏል” የምንልበት ዘመን ይመስላል፡፡ በየዓለም ጥጉ ሁሉ የምታዩት ነገር “ወድቋል” ማለት ቀርቶ “በስሏል” ማለቱ የሰውን ልጅ የሚያግባባ ብቸኛው ቃል የሆነ ይመስላል፡፡
የምር ግን…ዓለማችን ችግሯ በዛሳ! አንዱ የቸገረው ምን አለ መሰላችሁ…“ምናልባት ይቺ ምድራችን የሌላ ዓለም ገሀነም ልትሆን ትችላለች፡፡”አሪፍ አባባል አይደል! አሁን፣ አሁን የምንሰማውና የምናየው ነገር ሁሉ…አለ አይደል…“የሰው ልጅ ወደ ድንጋይ ተመለሰ እንዴ!” ያስብላል፡፡
የምር እኮ… እንዴት ነው እውቀት እየበዛ ሄደ በሚባልበት ዘመን ይሄን ሁሉ ጭካኔ የምናየው! እናላችሁ…ምድራችን በአንዱ ሲብስባት በሌላው እንኳን እንዳንጽናና ‘የተካበ’ የሚመስለው ሁሉ እየተሰነጣጠቀ ግራ ገብቶናል። ሸሽተን የምንሸሸግባቸው የውጪ ‘ቻነሎች’ የሚያሳዩን ነገሮች ሁሉ “ይሄ ስምንተኛው ሺህ ሚሌኒየሙን አልፎ… አዘናግቶ መጣብን እንዴ!” ያሰኛሉ። (በነገራችን ላይ…አሁን ያለንበትን ዘመን ከኃይማኖታዊ አስተምህሮቶችና ትንቢቶች ጋር እያጣቀሱ ‘ጊዜው መድረሱን’ የሚናገሩ እየበዙ ነው።)
ቦምብ ከሚንዳት ምድር አላቆ አበባ የሚያብባት ምድር ያድርግልንማ! እናማ…የባሩድ ሽታ በጽጌረዳ መአዛ የተተካባት ምድር ያድርግልንማ!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይቺን ካወራናት እንድገማትማ…ሰውየው የገጠር ሰው ነው፡፡ እናላችሁ…የሰው ነፍስ ያጠፋና ፍርድ ቤት ይቀርባል፡፡ ታዲያ ‘ለማተቡ፣ ለክሩ’ የሚቆም ስለሆነ መግደሉን እንደሚያምን ለዘመዶቹ ይነግራቸዋል፡፡ ስለ ህጉ ብዙም ዝርዝር ስለማያውቅ የሚወሰንበትን ግን አላሰበውም። ታዲያማ፣ ችሎት ቀርቦ የእምነት ክሀደት ቃል ሊጠየቅ ሲል አጎቱ ማስጠንቀቂያ ሹክ ሊለው ጠጋ ይለዋል፡፡ ይሄን ጊዜ ዳኛው ያዩትና “እዛ’ጋ፣ ተጠርጣሪውን ምንም ነገር ማናገር ክልክል ነው!” ብለው ይቆጣሉ፡፡ ይሄኔ አጎትየው ወደኋላ ያፈገፍግና ምን ቢል ጥሩ ነው…
“ጌታዬ፣ ቢያምን እንደሚሞት፣ ቢክድ እንደሚተርፍ እሱ መች አጥቶት ነው እኔ የምነግረው!” ብሎ አረፈው፡፡
ዘንድሮ ያልሆነው ሆነ፣ የሆነው አልሆነም እየተባልን በአጠቃላይ “…እኛ መች አጥተነው ነው የሚነግሩን…” የሚያስብሉ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ በዓይናችን በብረቱ አጥርተን የምናየው፣ በጆሯችን አጥርተን የምንሰማው ነገር ተመልሶ ሲነገረን፡፡
እናላችሁ…አንዳንዴ ስለተለያዩ ነገሮች ሲወራ እኛ ያለንባት ራሷ ጦቢያ መሆኑን ረስተን… “እስቲ ይቺን የምታወሩላትን አገር አሳዩን… ልንል ምንም አይቀረን፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ስለ መግባባት ካወራን ይቺን ስሙኝማ… ሰውየው ክፍል ውስጥ አማርኛ እያስተማረ ነው፡፡ ደግሞላችሁ…ተማሪዎቹ ገና ጀማሪዎች በመሆናቸው ስለ ስዋስው ምናምን ብዙም የሚያውቁት ነገር አልነበረም፡፡
እናላችሁ…በሚገባ ሳያስረዳቸው ምን ብሎ ይጠይቃቸዋል፣ “‘አበበ ከበደን በዱላ መታው’ የሚለው አረፍተ ነገር ውስጥ ግሱ የምን ግስ ነው?” ብሎ ይጠይቃል፡፡
አንደኛው ተማሪ ምን ብሎ መለሰ መሰላችሁ…“የወንጀል ክስ ነው፡፡” ልክ ነዋ…በዱላ መምታት ወንጀል ነዋ! “በዱላ መታው” ካሉ በኋላ ወላ ‘ገቢር ግስ’፣ ወላ ‘ተገብሮ ግስ’ ብሎ ነገር የለማ! ቂ…ቂ…ቂ… (አስተማሪው ያቀረበው የምሳሌ ዓረፍተ ነገር “አበበ ከበደችን በከንፈሮቹ ሳማት…” ቢሆን ኖሮ ግሱ ‘ተሻጋሪ’ ግስ ይሆን ነበር! ሳይገባኝስ!)
እናማ…ችግሩ የመላሹ ሳይሆን የአስተማሪው ነው፡፡ ዘንድሮም አብዛኛው ችግር የእኛ ‘የመረጃ’ ተቀባዮች ሳይሆን የእነሱ ‘የመረጃ’ ሰጪዎቹ ነው። የእውነት መረጃ የሚሰጡን ሳይሆን እኛ ጥቁር ያልነውን እነሱ “ቀይ ነው ብያለሁ ቀይ ነው…” አይነት ነገር ይሆናል፡፡ ይሄኔ ታዲያ እኛ ደግሞ…ጮክ ብለን ባንናገር እንኳን በሆዳችን “…እኛ መች አጥተነው ነው የሚነግሩን…” እንላለን፡፡
(ያን ሰሞን የድራፍት ዙሪያ ‘ሀሜታ’ ላይ “እንኳን ጮክ ብለን ጠንከር አድርገን ስንተነፍስም ዓይን በዝቶብናል…” ያልከው ወዳጄ ‘አድናቂህ’ ነኝ።) በነገራችን ላይ…እግረ መንገዴን የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ…በአንድ ተጠባባቂ ተጫዋች ብቻ የነጥብ ዓለም አቀፍ ጨዋታ በመጫወት ከዓለም ስንተኛ ነን! አይ ጦቢያ! እኔ የምለው… ‘እሱ ሰፈር’ በዛ ሰሞን “ተሽሎታል…” ምናምን ሲባል አልነበረም እንዴ! ኮሚክ ነገር እኮ ነው…ፓስፖርት ላይ የተጻፈ ዓመተ ምህረት አይቶ ‘ለመደመርም’ ካሽ ሬጂስተር ማሺን ምናምን ሊያስፈልገን ነው ማለት ነው!
ደግሞላችሁ የኳስ ነገር ካነሳን አይቀር… ኳስ ጨዋታዎች በቲቪ ላይቭ ሲተላለፍ ‘ኮሜንተሪ’ የሚያሰሙት…ሁሉም እንቅስቃሴ ‘ሙሉ አረፍተ ነገር’ መሆን አለበት እንዴ! “የእንትን በረኛ ለመሀል ተከላካዩ…” እንዳቀበለው በመግለጽ የተጀመረው ዓረፍተ ነገር እስኪጠናቀቅ ኳሷ በሰባት በስምንት እግሮች ተነክታ ትመለሳለች። እንዴ… ጨዋታውን እኛም እያየነው እንደሆነ ልብ ይባልልና! አለበለዛ “ስምንት ቁጥሩ አንጋጋው አናጌ ከባላጋራ ተጫዋቾች መሀል ከፍ ብሎ ዘሎ ኳሷን በጭንቅላቱ ገጫት…” አይነት ነገር ግስ፣ ስም፣ ተውላጠ ስም፣ ተሳቢ፣ ቦዝ አንቀጽ ምናምን አሥራ ስምንት የንግግር ክፍል ያለበት ይመስላል፡፡ ዓረፍተ ነገሩ ሲጀመር ምጥ የጀመራት ሲያልቅ ልትወልድ ትችላለች እኮ! (ቂ…ቂ…ቂ… እኛም የማጋነን ዕድል ይድረሰና!)
የምር ግን ላይቭ ኮሜንታሮቻችን ዘዴያቸውን መፈተሽ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡  ደግሞ የተጫዋቹ ቁጥር እየቀረ ስም ከእነ አባቱ ሳይቀር ሁሉም መባል የለበትም፡፡ አንጋጋው አናጌ በአንድ ጨዋታ ላይ ሙሉ ስሙ የተጠቀሰውን ብዛት ከቄስ ትምህርት ቤተ ጀምሮ መዝገቦች ላይ የተጻፈው ተደምሮ አይደርስበትም፡፡ (‘ማጋነን’ ለመደብኝ ማለት ነው!)
ከተጨዋወትን አይቀር ይቺን ስሙኝማ…‘በኮሚዋ’ ሩስያ ዘመን የኮሚኒስት ፓርቲው የምስረታ በዓል እየተከበረ ነበር፡፡ እናላችሁ…በአንድ የሀገሪቱ አውራጃ በዓሉን ምክንያት በማድረግ ልዩ ዝግጅት ነበር፡፡ በዝግጅቱም ላይ የአካባቢው የፓርቲ ሊቀመንበር ንግግር ያደርጋል።
“የተወደዳችሁ ጓዶች!” ከአብዮቱ በኋላ ፓርቲያችን ያስመዘገባቸውን ስኬቶች ልብ በሉ። ለምሳሌ እዚህ አጠገቤ ያለችውን ማሪያን ተመልከቱ፡ ከአብዮቱ በፊት ምን ነበረች? ማንበብ መጻፍ የማትችል መሀይም አርሶ አደር፡፡ የነበራት አንዲት ቀሚስ ብቻ ነበረች፣ ጫማም ስላልነበራት በባዶ እግሯ ነበር የምትሄደው፡፡ አሁንስ? አሁን በአካባቢያችን ቤት ለቤት በመዞር ወተት በመሸጥ ትታወቃለች፡፡ ወይንም ኢቫን አንድሪቭን ተመልከቱት፡፡
በሰፈራችን የነጣ ድሀ ነበር፡፡ ፈረስ የለው፣ ላም የለው፣ መጥረቢያ እንኳን የለውም ነበር። አሁንስ? አሁን ትራክተር አሽከርካሪ ነው። ደግሞም ሁለት ጫማ አለው፡፡ ዕድሜ ለአብዮቱ ሁለት ጫማ! ወይ ደግሞ ትሮፊም ሴሜኖቪች አሌክሲቭን ተመልከቱት፡፡ የለየለት ወሮበላ፣ ሰካራምና መቼም የማይጸዳ ነበር፡፡ ያገኘውን ምንም ነገር ከመስረቅ ስለማይመለስ ማንም ሰው አያምነውም ነበር። አሁን ግን ዕድሜ ለአብዮቱ የፓርቲ ኮሚቴው ጸሀፊ ሆኗል።”
እኔ የምለው…እኛ ዘንድ ተመሳሳይ ‘ስኬቶች’ ካሉ ይገለጹልንማ!
እናላችሁ… በዚህ የቴክኖሎጂ ዘመን፣ በእነፌስቡክ ዘመን፣ በትዊተር ዘመን፣ በዩ ቲዩብ ምናምን ዘመን “…እኛ መች አጥተነው ነው የሚነግሩን…” ባንባባል አሪፍ ነው፡፡ አሥር ወር ገበያ ላይ ቆይቶ መውጣቱን እንኳን ሰው ነገሬ ያላላውን አልበም “በከፍተኛ ደረጃ እየተሸጠ ነው…” አይነት ነገር ስንባል፤…ሰው ሳይበዛ ገብተን እንደ ቲያትር ቤት መዳፋችን የዝንጀሮ እንትን እስኪመስል ድረስ ካላጨበጨብን አስተናጋጆች ብቅ የማይሉበትን ሬስቱራንት “በዚህ ሬስቱራንት ደንበኛ ንጉሥ ነው…” ምናምን ስንባል፤ ሀሳብ የሚሰጥ ጠፍቶ ሰብሳቢዎቹ… አለ አይደል… የስብሰባው መሪዎችም፣ የስብሰባው ንቁ ተሳታፊዎችም እነሱ ብቻ በሆኑበት “ከፍተኛ የሀሳብ ልውውጥ የተደረገበት ስብሰባ…” ሲሉን…በቃ ቀሺም ነገር ነው፡፡
በትንሹም በትልቁም “…እኛ መች አጥተነው ነው የሚነግገሩን…” የማንባባልበትን ዘመን ያምጣልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

አንድ የአፍጋኒስታኖች ተረት እንዲህ ይላል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሰው ሚስቱ ድርስ-እርጉዝ ሆና ስለነበር ለሚወለደው ወይም ለምትወለደው ልጅ አልጋ ሊያሰራ፤ ወደ አልጋ ሰሪ ሄደ፡፡  ያ አልጋ ሰሪ አናጢ፤
“ምን ፈልገህ ወደኔ መጣህ?” ሲል ይጠይቃል፡፡
“ለልጄ አልጋ ላሰራ ፈልጌ ነው” ይላል አባት፡፡
“መልካም፡፡የህፃን ልጅ አልጋ ግምቱ የታወቀ ስለሆነ አሳምሬ እሰራልሃለሁ” አለው፡፡
አባት፤ በጉዳዩ ተስማምቶ፤
“በል እንካ ቃብድህን፡፡ አደራ ደህና አድርገህ ስራልኝ” ብሎ ገንዘቡን ሰጠው፡፡
አባት የልጁ መወለድ እየቀረበ ስለመጣ ወደ አናጢው እየሄደ፤
“እህስ፤ ምን አደረስክልኝ?” ይለዋል፡፡
“ቆይ ትንሽ ጠብቅ” ይላል አናጢ፡፡
አባት ሌላም ቀን ይመጣል፡፡
የአናጢው መልስ፤
“ቆይ ትንሽ ጠብቀኝ” ሆነ፡፡
በዚህ ማህል ልጁ ተወለደ፡፡ አደገ፡፡
ጎረመሰ፡፡ ጎለመሰና ሚስት አገባ፡፡ ሚስቱ ፀነሰች፡፡ አረገዘች፡፡
ልጁ እንግዲህ አባት ነውና፤ ኃላፊነት አለበትና፤ ወደ አባቱ ሄዶ፤
“አባቴ ሆይ! መቼም አንተ ልምድ አለህና ለሚወለደው ልጄ አልጋ ከየት እንደምገዛለት ንገረኝ?” አለው፡፡
አባትየውም፤
“የውልህ ልጄ! የዛሬ ሃያ ዓመት፤ ለአንድ አናጢ አንተ ስትወለድ የምትተኛበት አልጋ ላሰራ ቀብድ ሰጥቼው ነበር፡፡ ሂድና አልጋው አልቆ ከሆነ፤ ቀሪውን ከፍለህ አልጋውን አምጣና ልጅህ ይተኛበታል!” አለው፡፡
ልጅየውም ተደስቶ ወደ አናጢው ሄደና፤
“ጌታው፤ ከዚህ ቀደም አባቴ አልጋ ሊያሰራ ገንዘብ ከፍሎህ ነበር፡፡ እሱን ለመውሰድ ነበር የመጣሁት”
አናጢውም፤
“እናንተ ሰዎች አልጋ በጥድፊያ አይሰራም፡፡ አትጨቅጭቁኝ፡፡ አታጣድፉኝ፡፡ እኔ የጥድፍ ጥድፍ ስራ አልወድም፡፡ ካልፈለጋችሁ ገንዘባችሁን ልመልስላችሁ እችላለሁ!” አለ፡፡
                                               *            *              *
ለልጅ አልጋ ማሰራተን የመሰለ ቁምነገር የለም፡፡ ትውልድን እንደመታደግ ነው፡፡
ከሃያ ዓመት በኋላ “አታጣድፉኝ!” ከሚል ይሠውረን!
የአልጋ ነገር ሁሌም አሳሳቢ ነው፡፡ አዲስ ህፃንም ይተኛበት የቆየ፤ ችግር አያጣውም፡፡ አልጋ ሲሰራ ጥድፊያ አይወድም፡፡ ሃያ ዓመት ቢፈጅም ጥድፊያ አይወድም፡፡ ሰሪውም በቀላሉ አይለቅም! “የጥድፊያው ጥቅም ለሠሪው ነው ለአሠሪው?” ነው ጥያቄው፡፡ ማስተዋልን የመሰለ ነገር የለም ዞሮ ዞሮ፡፡
ምንም ሆነ ምን ድህነትን ማሸነፍ ግዳችን ነው! “ነጭ ደሀ ነጭ ብር ይወልዳል” ቢሉም አበሳውን ማስታወስ ተጨምሮ መሆን አለበት፡፡ ቢያንስ እንደ ፀሐፌ-ተውኔት “ስደተኛ ዘላን ሶማሌ በሄደበት ሣር ወይም አሣር ይጠብቀዋል” የሚል የአምሣ ባምሳ ግምት (Probability) ፈጥሮ ስለአገር ማሰብ ብልህነት ነው፡፡ ምሁሩም፣ መሀይሙም፣ ጠቢቡም፣ ግብዙም ስለአገር ጨለምተኛ (Pessimist) ሆኖ የትም አንደርስም!!
እንደሌላው ዓለም ሁሉ፤ ያለጥርጥር ልማት በኢትዮጵያ፤ ሂደት እንጂ ግብ ብቻ አይደለም፡፡
የጥንቱን የጠዋቱን የሀገራችንንና የውጪውን አገር ልማታዊ መንፈስ እንድናይ ይረዳን ዘንድ ጸጋዬ ገ/መድህን በምኒልክ አንደበት የሚከተለውን ይለናል፡-
“አውሮጳውያን የእጅ-ሥራ ዕድገታቸው፣ የዘመናዊ ሥልጣኔያቸው፣ የቱን ያህል ይደንቃል፡፡ እቴ ጣይቱ፡፡ መሣሪያ፣ መኪና፣ ፋብሪካ፣ የባህር መልህቅ፣ የመሬት መንኮራኩር ሥራቸው የቱን ያህል ይመጥቃል፡፡ የመንገድ ድልድያቸው፣ ወፍጮአቸው፣ ትምህርታቸው፣ እርሻቸው፣ ባንክ የሚሉት የገንዘብ ብልፅግና ዘዴአቸው፣ አውራ ጎዳኖቻቸው፣ ውሃ በቧንቧና ቃል በሽቦ እሚስብ፣ ነፋስ መላላኪያቸው፣ ብርሃን በክር እሚጠልፍ የሌት ሻማቸው፣ ሰፊ ከተማ ሙሉ ከፋሲል ግንብ የሚበልጡ ህንፃዎቻቸው፣ እቴ ጣይቱ አባ ማስያስና ኢንጂነር ኢልግ አጫውተውሽ የለ?! ብቻ ወደኛ የሚልኩብን ጦራቸውን ብቻ ነው፡፡”
ከላይ የተጠቀሰውን ስንመረምር፤
ዕደ ጥበብ ከዚያ ተነስቶ ዛሬ የት ደረሰ? ፋብሪካ የት ደረሰ? ባህርና ትራንዚት ምን ያህል ተራቀቀ? ትራንስፖርትና መገናኛ ምን ያህል አዘገመ ወይም ፈጥኖ ሄደ? የመንገድ፣ የድልድይ ሥራ ምን ያህል ረቀቀ? እርሻ ምን ያህል ሜካናይዝድ ሆነ? (በደርግ ዘመን ከፊል-ካፒታሊዝሙ ይስፋፋ መስሏቸው ትራክተሮች አስመጥተው “በሶሻሊዝም ተወረሰብኝ!” የሚሉ (ኮማንድ - ኢኮኖሚ ነብሱን ይማረውና) አንድ ባለሀብት፤ “ከጓድ ሊቀመንበር ጋር ወደፊት!” እና “ሶሻሊዝም ይለምልም” የሚል መፈክር ባዩ ቁጥር፤ እጃቸውን በጭብጨባ እያጣፉ “አጀብ!... ትራክተር!” ይሉ ነበር አሉ፡፡
የዛሬ ኢንቬስተር ይሄን አይልም ብለን ተስፋ እናደርጋለን! የባንክ ሥርዓታችንስ የት ደረሰ? ባንክ ውስጥ ካለን ገንዘብና በየሰዉ ትራስ ስር ካለው ገንዘብ የቱ ይበዛል? ሁለቱንም ነብሳቸውን ይማርና የቀድሞው መሪ ለባንኮች፤ “ከእናንተ አየለ (አይ.ኤም.ኤፍ) ይሻላል፡፡ ገንዘቡ በአጁ  አለ፡፡ ያንቀሳቅሰዋል!” ብለው ነበር አሉ፡፡ “ነፋስ መላላኪያችን” የት ደረሰ ማለት ያባት ነው (3G እና 4G እንዲሉ!) ብርሃን በክር የሚጠልፍልን መብራት ኃይልስ? ብሎ መጠየቅም ያባት ነው፡፡ ግንባታና ህንፃዎቻችንስ? ሰው ሰው ይሸታሉን? ለኢኮኖሚያዊ ዕድገታችን ያላቸው አስተዋፅኦ የሚተነትንልን የቱ ኢኮኖሚስት፣ የቱስ ባለሥልጣን ነው? ማንም ይሁን ምን፣ ገዢም ይሁን ተገዢ፣ ባለሃይማኖትም ሆነ ኢሃይማኖታዊ፣ የተማረም ሆነ ያልተማረ፣ አገር ውስጥ ያለም ሆነ ዲያስፖራ፣ ሀሳባዊም ሆነ ቁስ-አካላዊ፣ የእኛም ይሁን የውጪ ኃይል… ምኒልክ እንዳሉት… “ወደኛ የሚልኩት ጦራቸውን ብቻ” የሚለውን ነዋሪው ዜጋ እንደምን ያየዋል? መባባል አለብን፡፡ ሁሉ ነገር መጨረሻው ፀብ መሆኑን እንደምን እንየው? መቼ ነው ስለ አዎንታዊ ማንነታችን ደርዝ ያለው ግንዛቤ እምንጨብጠው?
እነዚህን ጥያቄዎች እያሰላሰልን ከገዢም ያልሆኑ ከተገዢም ያልሆኑ “የአየር ባየር ነጋዴዎች” እንዲሉ፤ “የአየር ባየር ፖለቲከኞች” ኋላ የአገር ውስጥ ገቢ መስሪያቤት (ፖለቲካ ሲገባው) የማይምራቸው እንደማለት፤ ፍፃሜያቸው መሬት የሆነ፤
“ጠላትማ ምን ጊዜም ጠላት ነው
አስቀድሞ መግደል አሾክሿኪውን ነው”  
እንደሚባሉ ያሉ አያሌ ናቸው፡፡ “መንገድ ሲበላሽ ትራፊክ ይበዛል፡፡ አገር ሲበላሽ ጃርት ያፈራል” የሚባለውን የጥንት አባባል ዛሬም ልንደግመው ተገደናል፡፡ ይህን ጉዳይ በትግሪኛ ተረት ብናስቀምጠው፤ “ጫማ ምን ክብር ቢኖረው፤ ሁል ጊዜም እግር ሥር ነው” ይሆናል!!  


የጸረ ሽብርተኝነት ህጉ ይሻሻል ብለዋል
ከዚህ በፊት በሽብርተኝነት የተፈረደባቸው እንዲፈቱ ጠይቀዋል
41 የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች፣ የፕሬስ ነጻነት አቀንቃኞች፣ አለማቀፍና ክልላዊ የሲቪል ማህበረሰብ ተቋማትና የሙያ ማህበራት መንግስት በቅርቡ የሽብርተኝነት ክስ የመሰረተባቸውን ጋዜጠኞችና የዞን 9 ጦማርያን በአፋጣኝ እንዲፈታ ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ከትናንት በስቲያ በላኩት ደብዳቤ መጠየቃቸውን ብሉምበርግ ኒውስ ዘገበ፡፡
ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ አርቲክል 19 ምስራቅ አፍሪካ፣ ሲቪል ራይትስ ዲፌንደርስ፣ ወርልድ አሊያንስ ፎር ሲቲዝን ፓርቲሲፔሽን፣ ፔን አሜሪካና የመሳሰሉት አለማቀፍ ድርጅቶች በጋራ በጻፉት ደብዳቤ፣ መንግስት ጋዜጠኞችንና ጦማርያንን በሽብርተኝነት እየከሰሰ ለእስር መዳረጉን መቀጠሉ ያሳስበናል፣ እየተወሰደ ያለው እርምጃ ተገቢነት የሌለው በመሆኑ መገታት ይኖርበታል ብለዋል፡፡
ሶስቱ ጋዜጠኞችና ስድስቱ ጦማርያን ሶስት ወራት ለሚሆን ጊዜ ይህ ነው የሚባል ክስ ሳይመሰረትባቸው ያለአግባብ በእስር ላይ መቆየታቸውንና አንዳንዶቹም በምርመራ ወቅት እንግልት እንደደረሰባቸው መናገራቸውን የጠቀሰው ደብዳቤው፣ ይህም አግባብ አለመሆኑን ገልጿል፡፡
ጋዜጠኞቹና ጦማርያኑ በተመሰረተባቸው የሽብርተኝነት ክስ በረጅም አመታት እስር ብሎም በሞት ሊቀጡ እንደሚችሉ ስጋታቸውን የገለጹት ድርጅቶቹ፤ ይህም አለማቀፍ ህጎችን የሚጥስና በቀጠናው የተረጋጋ ሰላምና ደህንነት ለመፍጠር የሚደረገውን አለማቀፍ ጥረት ዋጋ የሚያሳጣ እርምጃ ይሆናል ብለዋል፡፡
መንግስት አግባብነት በሌለው የጸረ ሽብርተኝነት ህግ በቁጥጥር ውስጥ አውሎ ክስ የመሰረተባቸውን ጋዜጠኞችና ጦማርያን በአፋጣኝ ከእስር እንዲለቅ አስፈላጊውን ሁኔታ እንዲያመቻቹ ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ጥያቄ ያቀረቡት እነዚህ ድርጅቶች፤ ከዚህ በፊት በተመሳሳይ ሁኔታ በጸረ ሽብር ህጉ ተከሰው የተፈረደባቸው ዜጎች ጉዳይ አግባብ አለመሆኑን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሳይቀር እንዳመነበትና እንዳወገዘው አስታውሰዋል፡፡
ከጋዜጠኞቹና ከጦማርያኑ በተጨማሪም፣ ከዚህ በፊት በሽብርተኝነት ተከሰውና ተፈርዶባቸው ያለአግባብ በእስር ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን በሙሉ መንግስት በአፋጣኝ እንዲፈታና የጸረ ሽብርተኝነት ህጉንም አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች መስፈርቶችን በሚያሟላ መልኩ እንደገና አሻሽሎ እንዲያጸድቅ ጠይቀዋል፡፡ኢትዮጵያ የአለማቀፉ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ስምምነትና የአፍሪካን የሰብዓዊና የህዝብ መብቶች ኮንቬንሽን ፈርማ የተቀበለች ሃገር እንደመሆኗ፣  መንግስት አለማቀፍ ህጎች የጣሉበትን ግዴታ በማክበር መሰረታዊ መብቶቻቸው ተጥሰው ለእስር የተዳረጉ ዜጎችን በሙሉ ከእስር እንዲለቅ ጠይቀዋል፡፡
ደብዳቤውን የጻፉት ድርጅቶች የሚከተሉት ናቸው፡፡
1. Amnesty International 
2. ARTICLE 19 Eastern Africa 
3. Central Africa Human Rights Defenders Network (REDHAC), Central Africa 
4. CIVICUS: World Alliance for Citizen Participation 
5. Civil Rights Defenders, Sweden 
6. Coalition pour le Développement et la Réhabilitation Sociale (CODR UBUNTU), Burundi 
7. Committee to Protect Journalists 
8. Community Empowerment for Progress Organization (CEPO), South Sudan 
9. Conscience International (CI), The Gambia 
10. East and Horn of Africa Human Rights Defenders Project 
11. Egyptian Democratic Association, Egypt 
12. Electronic Frontier Foundation 
13. Ethiopian Human Rights Project (EHRP) 
14. Elma7rosa Network, Egypt  15. English PEN 
16. Freedom Now 
17. Front Line Defenders, Dublin  18. Human Rights Watch 
19. International Women’s Media Foundation (IWMF) 
20. Ligue des Droits de la personne dans la region des Grands Lacs (LDGL), Great Lakes 
21. Ligue Iteka, Burundi 
22. Maranatha Hope, Nigeria 
23. Media Legal Defence Initiative
24. National Civic Forum, Sudan 
25. National Coalition of Human Rights Defenders, Kenya 
26. Niger Delta Women’s movement for Peace and Development, Nigeria 
27. Nigeria Network of NGOs, Nigeria  
28. Paradigm Initiative Nigeria, Nigeria  
29. PEN American Center  30. PEN International  
31. Réseau africain des journalistes sur la sécurité humaine et la paix (Rajosep), Togo  
32. Sexual Minorities Uganda (SMUG), Uganda  
33. South Sudan Human Rights Defenders Network (SSHRDN), South Sudan 
34. South Sudan Law Society, South Sudan  
35. Tanzania Human Rights Defenders Coalition, Tanzania 
36. Twerwaneho Listeners Club (TLC), Uganda 
37. Union de Jeunes pour la Paix et le Développement, Burundi  
38. WAN-IFRA (The World Association of Newspapers and News Publishers)  
39. West African Human Rights Defenders Network (ROADDH/ WAHRDN), West Africa
40. Zambia Council for Social Development (ZCSD), Zambia
41. Zimbabwe Human Rights NGO Forum, Zimbabwe

     የኢትዮጵያ የጤና መድህን ኤጀንሲ ከ “ጤና ለሁሉም ዘመቻ” ጋር በመተባበር ባዘጋጀው “የጤና መድህንን ለህዝብ የማስተዋወቅ ዘመቻ” አገር አቀፍ የዘገባ ውድድር ያሸነፉ ጋዜጠኞችን ከትናንት በስቲያ በኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ባከናወነው ስነስርዓት ሸለመ፡፡
የህትመት፣ የቴሌቪዥን፣ የሬዲዮና የድረ-ገጽ በሚሉ አራት ምድቦች በተከፋፈለውና ጋዜጠኞች የማህበራዊ ጤና መድህንን በተመለከተ ለአንባቢ፣ ለተመልካችና ለአድማጭ ያቀረቧቸውን ዘገባዎች ለውድድር ባቀረቡበት በዚህ ውድድር ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ የወጡ አሸናፊዎች ከኤጀንሲው ተጠባባቂ ዋና ዳይሬክተር ከዶ/ር መንግስቱ በቀለ እጅ የላፕቶፕ፣ የዘመናዊ ሞባይል ቀፎ፣ የፎቶግራፍ ካሜራና የሰርተፍኬት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
ዶ/ር መንግስቱ ሽልማቱን ለአሸናፊዎች ከሰጡ በኋላ ባደረጉት ንግግር፤ ጋዜጠኞች፣ የድረ-ገጽ ጸሃፊያንና መገናኛ ብዙሃን ጉዳዩን በተመለከተ በህብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤ በመፍጠር  ኤጀንሲው ለያዘው ዕቅድ መሳካት ትልቅ ሚና እንደሚጫወቱ ጠቅሰው፣ ኤጀንሲው በቀጣይም መሰል ስራዎችን በቅንጅት መስራቱን እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የ “ጤና ለሁሉም ዘመቻ” ዳይሬክተር ወ/ሮ ህይወት እምሻው በበኩላቸው፣ የጤና መድህን በገንዘብ እጦት ምክንያት ተገቢውን የህክምና አገልግሎት ለማግኘት ተቸግረው በህመም ለሚሰቃዩና ለሞት ለሚዳረጉ ዜጎች ትልቅ መፍትሄ እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡
የጤና መድህን ስርዓትን በተመለከተ በህብረተሰቡ ውስጥ በቂ ግንዛቤ በመፍጠር ረገድ ብዙ ስራ መሰራት እንዳለበት ጠቁመው፣ በዕለቱ ለሽልማት የበቁትም ሆኑ ሌሎች ጋዜጠኞች ስርዓቱን ለመዘርጋት በሚደረገው ቀጣይ እንቅስቃሴ ውስጥም የራሳቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ከመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳይ ቢሮና ከብሮድካስት ባለስልጣን የተውጣጡ የውድድሩ ዳኞች ባካሄዱት ግምገማ፤ በህትመት ዘርፍ መላኩ ብርሃኑ ከአዲስ ጉዳይ መጽሄት፣ ምህረት አስቻለው ከሪፖርተር ጋዜጣ፣ ስመኝ ግዛው ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ በመውጣት ተሸልመዋል፡፡
በድረ-ገጽ ዘርፍ ጋዜጠኛ አንተነህ ይግዛው፣ ጋዜጠኛ ደመቀ ከበደ፣ ጋዜጠኛ ኢዮብ ካሣ ሲያሸንፉ፤ በሬዲዮ ዘርፍ ጋዜጠኛ ገዛኸኝ ተስፋዬ እና ጋዜጠኛ ገናናው ለማ ከደቡብ ክልል መገናኛ ብዙሃን፣ ጋዜጠኛ ገመቺስ ምህረቴ ከፋና ብሮድካስት ኮርፖሬት እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ በመውጣት፤ በቴሌቪዥን ዘርፍ ደግሞ ጋዜጠኛ ሰለሞን ገዳ በብቸኝነት አሸናፊ ሆኗል፡፡