Administrator

Administrator

ሁለት ዕውቅ ሽማግሌዎች ወዳጃቸው ለሆነ አንድ ሽማግሌ፤ “ሴት ልጅህን ለልጄ ስጠኝ” እያሉ በተራ በተራ መልዕክተኛ ላኩበት። ያም ሽማግሌ መልክተኞቹን በተራ በተራ አስተናገዳቸው። ለመጀመሪያው መልዕክተኛ፡- “መልካም፤ ልጄን ለልጅህ እሰጥሃለሁ ግን ቤትህን አሰናዳ ብለህ ንገረው” ብሎ ይልክበታል።
ለሁለተኛው መልዕክተኛም፤ “ና ቅረብ ወዳጄ። ለጌታህ ስትለው፤ ደግ ነው ልጄን ለልጅህ ልድራት ዝግጁ ነኝ፤ ሆኖም አስቀድመህ ቤትህን አሰናዳ” አለው። መልዕክተኞቹም-እርስ በእርሳቸው የተባሉትን ሳይነጋገሩ ወደ ጌቶቻቸው ሄዱ።
አንደኛው መልዕክተኛ ወደ ጌታው ሄዶ፤ “ጌታዬ ጥያቄውን አቅርቤ ነበር። ነገር ግን የ3 ወር ጊዜ ሰጥቼሃለው፤ ቤትህን አሰናዳ በለው” አሉ።
በመጀመሪያ መልሱን የሰማው ሽማግሌ ለልጁ፤ “በል ወዳጄ ሦስት ወር ቅርብ ጊዜ ነው፤ በያለበት መሬት እየገዛህ እልፍኝና አዳራሽ ሥራ፡፡ ለሚስትህና ላንተ መቀመጫ ይደላሃል” አለው፡፡
በሁለተኛ ደረጃ መልሱን የሰማው ሽማግሌ ግን፤ “ያጅሬን ብልሃት እኔ አውቃለሁ። በል ልጄ ተነስተህ ገንዘብ ይዘህ ሄደህ ወዳጅ አብዛ። እስካሁን የምታውቀው ሰው በቂ አይደለም። ቤትህን አሰናዳ ማለቱ ትርጉሙ ይሄ ነው።”
የተባለው ቀን ሲደርስ አባት ደግሶ ይጠባበቅ ኖሯል። ሁለቱ አባቶች በሰዓቱ ከች አሉ። ከተጋበዙ በኋላም አንደኛው፤ “መሬት ገዝቼ ለልጄ ሰጥቼዋለሁ።” ሲል ተናገረ።
የሠርጉ ባለቤትም፤ “የምድር ብዛት ከቁም-ነገር አይውልም። ባንድ ስተት ቀሪ ነው። እልፍኝና አዳራሹንም አውሎ ነፋስ ይጠርገዋል። የእሳት እራትና ምሳ ነው። ውሃ ሙላት ያጠፋዋል። ጠንቅ አያጣም” አለው።
ቀጥሎም ሁለተኛው አባት፤ “ገንዘብ ይዘህ ሂድ፤ ወዳጅ አብዛ” ብዬዋለሁ አለና አስረዳ። የሠርገኛው አባትም፤ “ሌላ ሀብት ሁሉ ጠፊ ረጋፊ ነው። ብዙ ወዳጅ ግን በየቦታው ቢፈራ ሀብት ነው። ጥቅምም ካንዱ ቢጠፋ ካንዱ ይገኛል፤ አንዲት ልጄን ለዚህ ልጅ መርቄ ሰጥቼዋለሁ” አለ።
* * *
ህዘብ የሚወደው መሪ ማግኘት ታላቅ ጸጋ ነው። ወዳጅ ለማፍራት የሚችል መሪ ማግኘት መታደል ነው። ለራሱ ማረፊያ እልፍኝ - ከአዳራሽ የሚሰራ መሪ ማግኘት ከቁምነገር የሚጻፍ አይደለም። ባንድ ስተት ቀሪ-ነው፤ አውሎ ንፋስ ይጠርገዋል። ህዝብ የክብሩ ምልክት የሚሆንለት መሪ ይፈልጋል። ተናግሮ የሚያጠግበው መሪ ይፈልጋል። እምነቱን የሚጥልበት፣ ለሾመው የሥልጣን ዘመን የሚበቃ ጥንካሬ ያለው ርዕሰ-ብሔር እንዲኖረው ይመኛል። በእርግጥም ህዝብ ሆደ-ሰፊ፣ እንደ ወጣት የማይቸኩል፣ በረዥምና በበሳል አካሄድ እንጂ በቆረጣ የማይመካ፣ ብልጥ ሳይሆን ብልህ የሆነ፣ የዕውቀት-የልምድና የዕድሜ ባለፀጋ የሆነ እንደራሴ ይፈልጋል።
የሀገር መሪ ሲመረጥ እንደ ቴአትር ገፀ-ባህሪ ለአንድ ወንበር (ሚና) ሁለት ሰው የሚሰለጥንበት (Double-cast እንደሚባለው) የመጠባበቂያ ሂደትም ሆነ መለዋወጫ የለውምና፣ አካላዊና አዕምሮአዊ ይዞታውና ብቃቱ በቅጡ መጤን ይኖርበታል።
የሕዝብ ስነ-ልቦናን የሚያሸንፍ መሪ የህዝብን ተስፋ ያለመልማል። መሪው ተስፋ የማይጣልበት ከሆነ፣ ተመሪውንም ይዞት ወደ ጨለምተኛ አቅጣጫ ያመራል። ዣን ፖል ሮችተር እንዳለው፤ “የእርጅና አሳዛኙ ነገር፤ ደስታችን ማለቁ ሳይሆን፤ ተስፋችን ጨርሶ መሟጠጡ ነው”። ተስፋ ያለው መሪ፤ የሆነ እንደሆነ ለነገ መቅረዝ ያበራል። ልምዱን፣ እውቀቱን፣ ደርዙን እንደ ሻማ እያቀጣጠለ የመጪውን ቀን ተስፋ የማያሳይ መሪ፣ አለቃ ወይም ሹም ከሆነ ግን ጭል-ጭል ትል የነበረችውን ነግ- ተነግ- ወዲያ ራዕይ ይጋርዳል። እርጅና ፀፀት የሚያመጣው ያልተዘጋጁበትን ቦታ እንደማታ-ሲሳይ፣ እንደማታ-እንጀራ ቆጥረው ሲቀመጡ ነው። “ምነው እዚህ እንደምደርስ ባወቅሁ፣ ራሴን በተሻለ ጠብቄ እቆይ ነበር” እንዲል ኡቢ ብሌክ፤ በስተርጅና የሚገኝ ሥልጣን ከትፍስህቱ ጭንቀቱ፣ ከተስፋው ፀፀቱ ይብሳል፡፡ እንደ ኖስትራ ዳሙስ The man who saw tomorrow ማለታችን ይቀርና The Man who’ll see Yesterday የሚል ዓይነት፤ ምስቅልቅል ውስጥ ሊከተንም ይችላል። (ራዕያችን ነገን አስቀድሞ ማየት መሆኑ ይቀርና፤ ትላንትን ነገ ለማየት መቋመጥ ይሆናል እንደማለት ነው።)
“የአንበሳ መንጋ መሪ በግ ከሚሆን ይልቅ፣ የበግ መንጋ መሪ አንበሳ ቢሆን ይሻላል” ሲል የፃፈልን ዳንኤል ዴፎ፤ የአገርን ምልክት፣ የአገርን መኩሪያ፣ የአገርን ወኪል፣ የኢገርን እንደራሴ ጉልህ ገጽታ አበክሮ ሲገልጽልን ነው። አንድም “ምነው ወጣቱ ባወቀ፣ ምነው ሽማግሌው መሥራት በቻለ” የሚለው የፈረንሳዮች አባባል፣ የዕውቀትንና የሥራን ኅብራዊ አስፈላጊነት ሲያሳየን ነው።
የነፃነትን፣ የፍትሕን፣ የመብት መከበርን ፍቱን አስፈላጊነት ከመቼውም በበለጠ እያየች፣ በላቀ ሁኔታም እየተገነዘበች፣ በመጣችው ሀገራችን ውስጥ ለዚህ እውን መሆን ብርቱ ጥረት የሚያደርጉ ብቁ ዜጎችን እንሻለን። ፈረንጆቹ እንደሚሉት፤ The Young man knows the rules the old man knows the exceptions (ወጣቱ በህግ የሚፈቀደውን ያውቃል፤ ሽማግሌው በሕግ የሚከለከለውን ያውቃል) ብለን እንዳናልፍ የሀገር ክብር፣ የመንበሩ ልዕልናና የታሪክ አደራ እንቅልፍ ይነሱናል።
ለአንድ የኃላፊነት ቦታ የብቃት መመዘኛ የዚህ ወይም የዚያ ብሔር-ብሔረሰብ መሆኑ እንዳይደለ መቼም ከመቼውም ጊዜ ይልቅ ዛሬ ሳንረዳው አይቀርም፡፡ በተግባር መከወኑ ላይ ባይሳካልንም፡፡
የአእምሮ መትባት፣ የአንጎል ብስለት፣ የእውቀት ደረጃና የሙያ ክህሎትና ሥነ-ምግባር እጅግ ወሳኝ የመሆኑን ያህል፤ የእነዚህ ሁሉ ማቀፊያ የሆነው አካላዊ ውሃ-ልክና ጤነኛነት፣ እንዲሁም የእድሜ ልከኛነት የዚያኑ ያህል ወሳኝ ነው። ይህ ባልተሟላበት ሁኔታ ኃላፊነትና ሥልጣን አካላዊ ሸክም ሲሆን፤ ውሎ አድሮም አዕምሮአዊ ጭንቀት ወደመሆን እንዳይሄድ መስጋት ተገቢ ነው። “አይቶ ነው ገምቶ ነው…” እንዲሉ ዕድሜንም አቅምንም አገናዝቦ ኃላፊነትን መቀበል ደግ ነው። አለበለዚያ እድሜ እየገፋ ሲሄድ፤ ህዝብንም “ማንስ ቢወክልህ ምን ቸገረህ?” ብሎ እንደመናቅ ያለ ክፉ ደዌ የለም። ሌላ “ጥገኛ ዝቅጠት” መጋበዝም ይሆናል ዞሮ ዞሮ። ደግሞምም የሁሉም ኃላፊነት ነው- የአጪም፣ የታጪም፣ የ”እሰይ-አበጀህ የእኛ ሎጋ!” ባይ ታዳሚም። አለበለዚያ፤
“ሰማንያውን ነህ
ዘጠናውን ነህ
ወገቤን የያዝከኝ ገላጋይ መስለህ!”
ማለት ይመጣል። ኃላፊነቱም አጠያያቂ ይሆናል። ሁሉም ጥንቃቄ ያሻዋል።

 

Saturday, 18 January 2025 22:02

መልካም የጥምቀት በዓል

ከአገራዊ የምክክር ሂደቱ ራሱን ማግለሉን ያስታወቀው የሲዳማ ፌደራሊስት ፓርቲ፤ “አገራዊ የምክክር ሂደቱ መደበኛ ሕዝባዊ ውይይት እየመሰለ ሂዷል” ሲል ተቸ።
ባለፈው ረቡዕ ጥር 7 ቀን 2017 ዓ.ም. ፓርቲው ለኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን በጻፈው ደብዳቤ ላይ እንደገለፀው፤ “አካታች” እና “ገለልተኛ” ምክክር የሚካሄድበት ዕድል ስለሌለ ራሱን ከምክክር ሂደቱ አግልሏል። አክሎም፣ የምክክር ኮሚሽኑ “ከገዢው ፓርቲ ተጽዕኖ” ውጪ መሆን አለመቻሉን ጠቅሷል።
የምክክር ሂደቱ የሃሳብ ልዩነት ያላቸውንና “የግጭቶቹ ተዋናይ የሆኑትን አካላት ያላሳተፈ”፣ “ጦርነቶች እንዲቆሙ በማድረግ አስቻይ ሁኔታን ያልፈጠረ” መሆኑን ፓርቲው አመልክቷል። ይህም ሁኔታ ከአጀንዳ ልየታ ሂደት ጀምሮ ሲስተዋል መቆየቱን ጠቁሟል።
ምክክሩ “መደበኛ ሕዝባዊ ውይይት እየመሰለ ሄዷል” ያለው ፓርቲው፣ አሁን ኮሚሽኑ እየተከተለ ባለው መንገድ “የተወሳሰቡ” ያላቸው የአገሪቱ ችግሮች እንደማይፈቱ በጽኑ እንደሚያምንም ነው ያስረዳው። ፓርቲው ከኮሚሽኑ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ከተፈራረመ ወዲህ፣ በመንግስት አካላት በተለይም የክልሉ መንግስት ከዚያ በፊት ከነበረው “በከፋ ሁኔታ” ዕመቃ እንደተፈጸመበት አብራርቷል።
በዚህ ምክክር መሳተፍ ችግሮችን የሚፈታ ውጤት ያመጣል ብሎ እንደማይጠብቅም ፓርቲው አመልክቷል። የምክክር ሂደቱ አሁን ባለው ቁመና “ከገዢው ፓርቲ ፍላጎት ውጪ ለሌሎች አስቻይ ሁኔታ መፍጠር የማይችል፣ አካታችና ሃቀኛ አገራዊ ምክክር በማድረግ ውስብስብ ችግሮቻችን በምክክር ለመፍታት የሚያስችል አቅምና ቁርጠኝነት የሌለው መሆኑን” እንዳረጋገጠ በደብዳቤው ላይ ጨምሮ አትቷል።
ኮሚሽኑ በነሃሴ ወር 2016 ዓ.ም. ባካሄደው የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት፣ ከፓርቲው ከታገዱ ግለሰቦች ጋር በመተባበር የፓርቲው ተወካዮች ከመድረኩ ተገድደው እንዲወጡ “አድርጓል” በማለትም ፓርቲው ከስሷል። አያይዞም፣ ፓርቲው “ይህም የተደረገው በዲሲፕሊን ከተሰናበቱ የፓርቲውን ሰዎች ቀድሞውኑ በማስገባትና ከእነርሱ ጋር በማበር ነው” ያለ ሲሆን፣ ቦርዱ ችግሩን ለማስተካከል ከፓርቲው አመራር ጋር ተወያይቶ ከስምምነት ላይ የደረሰ ቢሆንም፣ በተስማማው መሰረት ምንም ዓይነት እርምጃ አለመውሰዱን ነው የጠቀሰው።

የፌደራል መንግስት ለፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ተገዢ እንዲሆን ተጠይቋል። ለሁለት የተሰነጠቁት የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር እና ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) አመራሮች ሃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡም ጥሪ ቀርቧል።
ከባለፈው ሰኞ ጥር 5 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ ሁለት ቀናት በትግራይ ክልል፣ መቐለ ከተማ፣ ሮማናት አደባባይ የተካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ የተገኙ ተፈናቃዮች ተቃውሟቸውን ማሰማታቸው ተገልጿል። በዚሁ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ ከተነሱ ጥያቄዎች መካከል፣ “ይበቃል፣ ወደ ቀድሞ ቀያችን መልሱን!” የሚለው መፈክር በዋናነት ሲስተጋባ እንደነበር ተጠቅሷል።
የተቃውሞ ሰልፉ ከቀን በተጨማሪ በምሽትም ሲካሄድ የቆየ ሲሆን፣ ከተፈናቃዮች ባሻገር በተለያዩ የሞያ ዘርፎች የተሰማሩ የመቐለ ከተማ ነዋሪዎች እንደተሳተፉበት ለማወቅ ተችሏል። በርካታ የከተማዋ ጎዳናዎች ተዘግተው መታየታቸውን እንቅስቃሴውን በቅርበት የተከታተሉ ወገኖች ለአዲስ አድማስ እንደጠቆሙት፣ በርካታ የክልሉ የፖሊስ ሃይል አባላትም በጎዳናዎቹ ላይ ተሰማርተው ነበር።
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የተቃውሞ ሰልፉ በተጀመረበት ዕለት ባወጣው መግለጫ፣ የተፈናቃዮችን ጥያቄ እንደሚደግፍ አስታውቋል። አስተዳደሩ፣ “’ይበቃል፣ ወደ ቀያችን መልሱን’ በሚል መሪ ቃል በተፈናቃዮች አማካይነት የተጠራው ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ቀናና የሚደገፍ ነው” ብሏል።
“ተፈናቃዮቹ እየደረሰባቸው ላለው መከራ ተገቢ ምላሽ እየተሰጠ አይደለም” በማለት መግለጫውን የቀጠለው ጊዜያዊ አስተዳደሩ፣ “የፌደራል መንግስት የገባውን ውልና ቃል በመተግበር ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው መመለስ አለበት” ሲል አሳስቧል። “አሁንም በፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት መሰረት ከአገር መከላከያ ሰራዊት ውጪ ያሉ ታጣቂ ሃይሎች ከትግራይ ክልል ይውጡ፤ በሕገ መንግስቱ አማካይነት፣ የትግራይ ክልል ግዛታዊ አንድነት ተከብሮ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው መመለስ አለባቸው” ሲልም በመግለጫው አፅንኦት ሰጥቷል።
ከዚህ በተጓዳኝ፣ የአፍሪካ ሕብረት፣ አሜሪካ፣ የአውሮጳ ሕብረትና የዓለምአቀፉ ማሕበረሰብ የትግራይ ሕዝብን ድምጽ በማዳመጥ የፕሪቶሪያ ውል በአግባቡ ተግባራዊ እንዲሆን ጫናቸው እንዲያሳድሩ ጥሪ አቅርቧል፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ።
“ጽላል ሲቪክ ማሕበር ማሕበረሰብ ምዕራብ ትግራይ” በተሰኘ ድርጅት አስተባባሪነት ሲደረግ የቆየው የተቃውሞ ሰልፍ፣ ባለፈው ረቡዕ ጥር 7 ቀን 2017 ዓ.ም ሲደመደም፣ ተፈናቃዮች በበኩላቸው የአቋም መግለጫ አውጥተዋል። በዚህ የአቋም መግለጫ የፌደራል መንግስት ለፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት ታማኝና ተገዢ በመሆን ስምምነቱን በሙሉነት እንዲያስፈፅም ጥሪ አቅርበዋል።
የዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ የፕሪቶሪያ የሰላም ውል እንዲፈረም ያሳየው ቁርጠኝነት ገቢራዊ እንዲሆን ሚናውን ማጉላት እንዳለበት ያነሱት ተፈናቃዮቹ፣ የትግራይ ክልል በሕገ መንግስቱ መሰረት ወደ “ቀድሞ ይዞታው” እስከሚመለስ ድረስ ሰላማዊ ተቃውሞ ማሰማታቸውን እንደሚቀጥሉ በአቋም መግለጫቸው ገልጸዋል። በተጨማሪም፣ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደርና የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ከፍተኛ አመራሮች ለስልጣን ሲሯሯጡ የተፈናቃዮችን ስቃይ “ዘንግተዋል” ሲሉ ምሬታቸውን ያሰሙት እነዚሁ ሰልፈኞች፣ “ያለፈው ይበቃል፣ አሁን የተጣለባችሁን ሃላፊነት በአስቸኳይ ተወጡ!” በማለት ጥሪ አቅርበዋል።
የተቃውሞ ሰልፉ ተሳታፊዎች ለትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ ለህወሓት ሊቀ መንበር ዶክተር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል፣ እንዲሁም ለተባበሩት መንግስታት ድርጅትና፣ በክልሉ ለሚገኙ የዕርዳታ ድርጅቶች የአቋም መግለጫቸውን ማድረሳቸውን ለማወቅ ተችሏል።

 

• በሰላም ስም የሚደረጉ ሸፍጦች ይቁሙ ተባለ

በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል፣ መተከል ዞን፣ ግልገል በለስ ከተማ የሚገኝ አንድ ኬላ ለዜጎች ሞት ምክንያት መሆኑ ተገለፀ። ከግድያ በተጨማሪ፣ በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች የዕገታ ተግባር እንደሚፈጽሙ ተነግሯል።
ከግልገል በለስ ከተማ በቅርብ ርቀት በሚገኘውና “ቻይና ካምፕ” ተብሎ በሚጠራው ኬላ ላይ በርካታ ዜጎች በማንነታቸው እየተለዩ መገደላቸውን እናት ፓርቲ ባለፈው ሰኞ ጥር 5 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። የአካባቢው ነዋሪዎች በተደጋጋሚ “የኬላው መኖር ምክንያታዊ ያልሆነና አላስፈላጊ ነው” የሚል ቅሬታ ሲያቀርቡ ቢቆዩም፣ ሰሚ ሊያገኙ አለመቻላቸውን ፓርቲው በመግለጫው ላይ አመልክቷል።
ኬላው ላይ ተሽከርካሪዎችን በማስቆም ታጣቂዎቹ ተሳፋሪዎችን በማንነት እየለዩ እንደሚሰውሩ፣ እንዲሁም በአሰቃቂ ሁኔታ እንደሚገድሉ ነዋሪዎች መናገራቸውን ፓርቲው የጠቀሰ ሲሆን፣ ነዋሪዎች “በአጠቃላይ የግልገል በለሱ “ቻይና ካምፕ” ኬላ የዜጎች ድብቅ ግድያ ‘ማመቻቻ ነው’ ብሎ መደምደም ይቻላል” ማለታቸውንም አክሎ አትቷል።
ታህሳስ 24 ቀን 2017 ዓ.ም. ከቀኑ ስድስት ሰዓት አካባቢ ወደ ግልገል በለስ ከተማ ይገባ የነበረውን የሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪ ቻይና ካምፕ ኬላ ላይ ታጣቂዎቹ አስቁመው ለስራ ይጓዝ የነበረን አንድ ወጣት “የዓይንህ ቀለም አላማረንም” በሚል ምክንያት ከቆመው ተሽከርካሪ አስወርደው “በአሰቃቂ ሁኔታ” መግደላችውን እናት ፓርቲ ገልጿል። የተፈጸመውን ግድያ የተመለከቱ ተሳፋሪዎች በከተማው ውስጥ ለሚገኘው መከላከያ ሰራዊት ስለሁኔታው ቢያስታውቁም፣ “ትዕዛዝ አልተሰጠንም” በሚል እርምጃ ከመውሰድ መታቀባቸውን የጠቆመው ፓርቲው፣ “’ቻይና ካምፕ’ እና ‘ኪዳነምሕረት ሰፈር’ በተባሉ አካባቢዎች ተገቢ ማጣራት ቢደረግ፣ ሌሎች የግድያ መረጃዎች ይገኛሉ። ነገር ግን መሰል ድርጊቶች እንዳይጋለጡ ከፍተኛ ርብርብና ማድበስበስ አለ” በማለት አስረድቷል።
ይህንን የግድያ ድርጊት “ፈጽመዋል” የተባሉት ታጣቂዎች ከዚህ ቀደም ጫካ ውስጥ ሲንቀሳቀሱ እንደ ነበሩና ከክልሉ መንግስት ጋር ዕርቅ ማውረዳቸውን እናት ፓርቲ ጠቅሶ፣ እነዚሁ ታጣቂዎች ከ”ቻይና ካምፕ” ኬላ አካባቢ ወታደራዊ ካምፕ ተሰጥቷቸው ሰፍረው እንደሚገኙ አብራርቷል። በተጨማሪም ፓርቲው “በሰላም ስም ቡድኖችን እየቀለቡ ማንነት ተኮር ጭፍጨፋና እገታ ይፈጽማሉ” በማለት በክልሉ መንግስት አካላት ላይ ነቀፌታውን አሰምቷል።
“በሰላም ስም የሚደረጉ ሸፍጦች ይቁሙ” ሲል ጥሪ ያቀረበው እናት ፓርቲ፣ የድርጊቱ ፈፃሚዎች ለሕግ እንዲቀርቡ ጠይቋል። ፓርቲው አያይዞም፣ የግልገል በለስ ከተማ ነዋሪዎችን “ለከባድ ሰቆቃ እየዳረገ ነው” ሲል የጠቀሰውን ቻይና ካምፕ ኬላ “ሕዝቡን በማወያየት” በአስቸኳይ እንዲነሳ ተማጽኗል።
ተጨማሪ ድብቅ መቃብሮች “አሉባቸው” ተብለው በአካባቢው ነዋሪዎች የሚጠረጠሩ እንደ ”ቻይና ካምፕ” እና “ኪዳነምሕረት ሰፈር” ዓይነት ስፍራዎች በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንና መሰል ተቋማት ምርመራ ተደርጎባቸው ውጤቱ ለሕዝብ ይፋ እንዲሆን እናት ፓርቲ አሳስቧል። እንዲሁም “አንዳንድ የመንግስት ባለስልጣናት ያላቸው ሚና የምርመራው አካል እንዲሆን እንጠይቃለን።” ብሏል፣ ፓርቲው በመግለጫው።

 

Saturday, 18 January 2025 21:57

መልዕክቶቻችሁ

ከአዲስ አድማስ ጋር እንዴት ተዋወቅን?

አዲስ አድማስን ከ13 አመታት በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ ደብረ ማርቆስ ተማሪ በነበርኩበት ወቅት ነው የተዋወቋት። ጋዜጣዋ ቅዳሜ ከሰዓት አንዳንዴ ደግሞ እሁድ ጠዋት ትደርስ ነበር፡፡ በወቅቱ እሸት አማተር የጋዜጠኞች ክበብ አባላት በተራ እየገዛን በፍቅር የምናነባት ተወዳጅ ጋዜጣ ነበረች። ለጋዜጣው አዘጋጆች ፣ አምደኞችና በትጋት ለምታነቡ የአዲስ አድማስ ወዳጆች በሙሉ እንኳን 25ኛ አመት የምስረታ በዓል አደረሳችሁ አደረሰን!
ጌትነት ተመስገን (ጌች ሐበሻ)
***
አዲስ አድማስን ማንበብ የጀመርኩት ገና ታትማ መውጣት ከጀመረችበት ጊዜ አንስቶ ነው። በወቅቱ Yellow journalism የተስፋፋበትና ጋዜጣ ከbroadsheet ወደ tabloid የተሸጋገረበት ጊዜ ነበር። ይልቁንም tabliod ጋዜጦች በነባር ጋዜጠኞች አሉታዊ አስተሳሰብ ሥር ነበሩ። አዲስ አድማስ ግን በ100 ከሚቆጠሩ ታብሎይድ ጋዜጦች ነጥራ ወጥታለች። ሆኖም የስፖንሰር አለመኖርና የወረቀት ዋጋ መጨመር እንዲሁም ወደፊት በሚመጣው የግብር ጫና ትቀጥል ይሆን? የሚል ስጋት አለኝ። እስካሁን ያቆዩዋትን በግሌ አመሰግናለሁ።
(ተሾመ ብርሃኑ ከድር)
***
ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ የተዋወቅሁት አርሲ ነጌሌ ከተማ ሞኪያ የተባለ የመጻሕፍት መደብር ውስጥ ከብዙ መጽሔቶች ጋር ተጀቡና በተመለከትኩበት ወቅት ነው። መኮንን በተባለ በመጻሕፍት ቤቱ ባለቤት በኩል አዲስ አድማስ ጋዜጣ ለከተማችን አንባብያን የመጣችው ለአጭር ጊዜ ቢኾንም፣ በኤፍሬም እንዳለ ወጎች፣ በአሰፋ ጫቦ የትዝታ ፈለጎች፣ በነቢይ መኮንን ተረቶች የታጠኑ ርዕሰ አንቀጾች፣ በዓለማየሁ አንበሴ ወቅታዊ ዜናዎች፣ በእነ ሌሊሣ ግርማ መጣጥፎች ፍቅር ለመውደቅ ግን ከበቂ በላይ ጊዜ ነበር። ይህች የቅምሻ ተጽዕኖ፣ ጎንደር ዩኒቨርስቲ በገባሁ ወቅት የማራኪ ካምፓስ ቤተ-መጻሕፍት ውስጥ ባለው የጋዜጣ ኮርነር ጋር የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ቀበኛ እንድኾን አድርጎኛል።
እንኳን ለ25ኛ ዓመት አደረሳችሁ/ አደረሰን
(ቢንያም አቡራ)
**
ከድሮም ጀምሮ አነብ ነበር፣ ይሁንና ከዕለታት አንድ ቀን ለስራ ጉዳይ ጅማ ከተማ ሄድኩኝ፣ በከተማዋ ውስጥ ስዘዋወር ጋዜጣ የሚያዞር ልጅ አየሁኝና ጠራሁኝ፣ ከዚያ ሁለት ጋዜጣ ገዛሁኝ፣ ወደ መኖርያዬ ተመልሼ ሳነብ ግን የልበወለድ አፍቃሪ ስለነበርኩኝ በአዲስ አድማስ ተማረኩኝ፣ ከዚያ ትውውቅ ወዲህ የአዲስ አድማሰ አንባቢ ብቻ ሳይሆን ሰብሳቢ ሆንኩኝ። እዚያ ከተማ ስሄድ የሳምንቱን ብቻ ሳይሆን ያለፈውን ጭምር እየገዛሁ አስቀምጣለሁኝ።
በእርግጥ አሁን በከተማዋ ውስጥ ራስ የሚያዞር ጸሐይ እንጂ ጋዜጣ የሚያዞር የለም።
ያም ሆኖ ዕድሉ ሲገኝ በአካል ካልተገኘ በኦንላይን አነባለሁኝ። የምወደው ጥበብ የሚሰኘውን አምድ ነው፡፡ ጋዜጣውን በሙሉ ባነብም መጀመርያ ግን የኤፍሬም እንዳለን ሥራና አጭር ልበወለድ ነው የማነበው፡፡ ለመጀመርያ ጊዜ አንብቤ የማስታውሰው አጭር ልበወለድ “ጭልፊቱ” የተሰኘው ትርጉም ልበወለድ ነው፣ አቤት አፍቃሪው ፌዴሪጎ እንዴት አሳዝኖኝ ነበር፣ እንዴት አስደስቶኝ ነበር፤ ለስንት ሰውስ ተረኩት።
ይህን አጭር ልበወለድ የያዘው ህዳር 3 ቀን 2009 ዓ.ም ዕትም አሁንም ድረስ አለኝ። እና አዲስ አድማስ አንጀት የምታርስ፣ እኔን ከመሻቴ የምታደርስ ስለመሰለኝ ከተዋወቅኋት ቀን ጀምሮ እስካሁን ድረስ አነባታለሁ፡፡ እውንም በአዲስ አድማስ ተምሬአለሁኝ፣
ተዝናንቻለሁኝ፤ ተሻሽያለሁ፡፡ አሁን ደግሞ እንደ ድሮ ጅማ እየተገኘች እንደልብ አነባት ዘንድ እናፍቃለሁኝ።
(ከድር ነብሶ)
***
አዲስ አድማስን በታላቁ ወንድሜ አማካይነት ነው ማንበብ የጀመርኩት፤ አሁንም እያነበብኩ አለሁ፡፡
(ሃኒቾ ከጦር ሃይሎች)

የኮካ ኮላ መጠጦች አፍሪካ (ሲሲቢኤ)፤ በኢትዮጵያ የ2025 ከፍተኛ ቀጣሪ ኩባንያ መሆኑን “ቶፕ ኢምፕሎዮ ኢንስቲትዩት” የተሰኘ ተቋም አስታወቀ።
ተቋሙ ባካሄደው ጥናት መሰረት፤ ኩባንያው በኢትዮጵያ ውስጥ በ2025 የከፍተኛ ቀጣሪ ደረጃ እውቅና ካገኙ ስድስት ኩባንያዎች ውስጥ አንዱ ተብሏል።
በኢትዮጵያ ከፍተኛ መዋእለ ንዋይ በማፍሰስ የገበያ ተደራሽነቱን እያሰፋ ኩባንያው፤ የሰራተኛ ቅጥርንም ገበያው በሚፈልገው ልክ እያሰፋ መሆኑ ተጠቁሟል።
መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፤ ባለፉት ሁለትና ሦስት አመታት በአገሪቱ የስራ አጥነት ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ ሲሆን፤ ይሄንን ችግር ለመቅረፍም የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን ማበረታታት አስፈላጊነት ሲገለፅ ቆይቷል።
ይሁንና የኮካ ኮላ መጠጦች አፍሪካ (ሲሲቢኤ)፣ በኢትዮጵያ የፈጠረው ከፍተኛ የስራ እድልና የቅጥር አድማስ የ2025 ከፍተኛውን የዕውቅና ማእረግ ለመያዝ እንዳስቻለው ለማወቅ ተችሏል።
የኮካ ኮላ መጠጦች አፍሪካ፣ የኢትዮጵያ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ዳሪል ዊልሰን ሲናገሩ፤ “ሽልማቱ ኩባንያው ከፍተኛ አቅምና አፈጻጸም ያላቸውን ሰራተኞች ለመሳብና ለማቆየት እንዲሁም፣ በሰው ሐብት አስተዳደር እድገት ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ያለውን አቋም ያንፀባርቃል” ብለዋል።
የኮካ ኮላ መጠጦች አፍሪካ (ሲሲቢኤ)፤ በአፍሪካ ከ18 ሺህ በላይ ሰራተኞች ያሉት ሲሆን፤ በአለማቀፍ ደረጃ ከ720 ሺህ በላይ ደንበኞች እንዳሉት “ቶፕ ኢምፕሎዮ ኢንስቲትዩት” ጠቁሟል።
ኩባንያው በ15 ሀገራት ውስጥ የሚሰራ ሲሆን ስድስት ቁልፍ ገበያዎቹ ደቡብ አፍሪካ፣ ኬንያ፣ ኢትዮጵያ፣ ኡጋንዳ፣ ሞዛምቢክና ናሚቢያ ናቸው። በተጨማሪም በታንዛኒያ፣ ቦትስዋና፣ ጋና፣ ዛምቢያ፣ ኮሞሮስ፣ ኢስዋቲኒ፣ ሌሶቶና ማላዊ ከፍተኛ ገበያ እንዳለው ተገልጿል።

Saturday, 18 January 2025 21:55

ሁሌም ለመታረም ዝግጁ ነን!

ባለፈው ሳምንት ታህሳስ 3 ቀን 2017 ዓ.ም በወጣው የአዲስ አድማስ ዕትም “የአክሱም ሴት ሙስሊም ተማሪዎችን ጉዳይ ወደ ፍ/ቤት ወስጄዋለሁ” ከሚለው የፊት ገፅ ዜና ጋር የወጣው ኒቃም የለበሱ እንስቶች ምስል ስህተት መሆኑን ውድ አንባቢያን ደውለው ጠቁመውናል፡፡ ተማሪዎቹ የጠየቁት ሂጃብ እንጂ ኒቃም አይደለም ብለዋል፡፡ በዚህም መሰረት ለተፈፀመው የምስል ስህተት ታላቅ ይቅርታ እየጠየቅን፣ በመቆርቆር ስሜት፣ ስህተታችንን ላረሙን ሁሉ ልባዊ ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡ ለ25ኛ ዓመታችን የደረስነው በናንተ ፍቅርና ድጋፍ ነው ስንል፣ ይህንን ማለታችን ነው፡፡ ሁሌም ለመታረም ዝግጁ ነን፡፡

የመጀመሪያው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ታትሞ ለንባብ የበቃው ታህሳስ 29 ቀን 1992 ዓ.ም ነበር - የዛሬ 25 ዓመት በዕለተ ቅዳሜ፡፡ ከዚያን ጊዜ አንስቶ ያለ አንድ ቅዳሜ በስተቀር ጋዜጣው ያልታተመበት ጊዜ የለም፡፡ ያም ቢሆን የተከሰተው በ97 ምርጫ ማግስት በተፈጠረው ፖለቲካዊ ቀውስ ሳቢያ ነበር፡፡
የዛሬ 20 ዓመት፣ የአዲስ አድማስ ጠንሳሽ፣ መሥራችና ባለቤት አሰፋ ጎሳዬ (አሴ) በድንገተኛ ህመም ህይወቱ ባለፈበት ወቅት እንኳን ጋዜጣው ሳይታተም አልቀረም፡፡ ረቡዕ ከቀብር በኋላ ቢሮ ገብተን የቅዳሜውን ጋዜጣ ስናዘጋጅ ነበር፡፡ ከሃዘናችን ጋር እየታገልንም ቢሆን የቅዳሜውን ሳምንታዊ ጋዜጣ በጉጉት ለሚጠብቁን ውድ አንባቢያን አድርሰናል፡፡ በዚህም ኩራትና ክብር ይሰማናል፡፡ የጋዜጣው መሥራች አሰፋ ጎሳዬም ቢሆን፣ ከምንም በፊት ቅድሚያና ትኩረት የሚሰጠው ለአንባቢያን ነበርና፡፡
እነሆ አዲስ አድማስ ከዚያም በኋላ ሁለት አሰርት ዓመታትን አስቆጥራ፣ በብዙ ውጣ ውረዶችና ተግዳሮቶች አልፍ፣ እነሆ ለ25ኛ ዓመቷ በቅታለች፡፡ ኮረኮንች በበዛበት የአገራችን የግል ፕሬስ፣ ሩብ ክፍለዘመን ቀላል ዕድሜ አይደለም፡፡ ረዥም ዕድሜ ነው፡፡ ትልቅ ስኬትም ነው ማለት ያስደፍራል፡፡
ለዚህ የደረስነው ግን በውድ አንባቢያን ገንቢ አስተያየትና ድጋፍ ነው፡፡ ስለዚህም በዚህ አጋጣሚ ልባዊ ምስጋናችንን ለማቅረብ እንወዳለን፡፡ ለአዲስ አድማስ ህልውናና በስኬት መቀጠል ከእኛ ከአዘጋጆቹ እኩል የሚጨነቁና የሚጠበቡት የረዥም ጊዜ ጽሁፍ አቅራቢዎችም ሌሎቹ ትልቅ ምስጋና የምንቸራቸው ባለውለታዎች ናቸው፡፡
ማስታወቂያቸውን በጋዜጣችን ላይ የሚያወጡ የንግድ ድርጅቶችና የመንግሥት ተቋማትም ሁነኛ አጋሮቻችን ናቸውና ከልብ ልናመሰግናቸው እንወዳለን፡፡
መጪው ጊዜም ነጻ ሃሳብ በነጻነት የሚንሸራሸርበት፣ ዕውቀትና ሥልጡንነት የሚያብብበት፣ የንባብ ባህል የሚዳብርበት እንዲሆን እንመኛለን፤ ለዚያም በትጋት መሥራታችንን እንቀጥላለን፡፡
እንኳን አደረሳችሁ፤ አደረሰን!!

የኮካ ኮላ መጠጦች አፍሪካ (ሲሲቢኤ)፤ በኢትዮጵያ የ2025 ከፍተኛ ቀጣሪ ኩባንያ መሆኑን "ቶፕ ኢምፕሎዪ ኢንስቲትዩት" የተሰኘ ተቋም አስታወቀ። ተቋሙ ባካሄደው ጥናት መሰረት፤ ኩባንያው በኢትዮጵያ ውስጥ የ2025 የከፍተኛ ቀጣሪ ደረጃ እውቅና ካገኙ ስድስት ኩባንያዎች ውስጥ አንዱ ሆኗል፡፡

በኢትዮጵያ ከፍተኛ መዋእለ ንዋይ በማፍሰስ የገበያ ተደራሽነቱን እያሰፋ የሚገኘው ኩባንያው፤ የሰራተኛ ቅጥርንም ገበያው በሚፈልገው ልክ እያሳደገ መሆኑ ተጠቁሟል።

መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፤ ባለፉት ሁለትና ሦስት አመታት በአገሪቱ የስራ አጥነት ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ ሲሆን፤ ይሄንን ችግር ለመቅረፍም የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን የማበረታታት አስፈላጊነት ሲገለፅ ቆይቷል።

ይሁንና የኮካ ኮላ መጠጦች አፍሪካ (ሲሲቢኤ)፣ በኢትዮጵያ የፈጠረው ከፍተኛ የስራ እድልና የቅጥር አድማስ፣ የ2025 ከፍተኛውን የዕውቅና ማዕረግ ለመያዝ እንዳስቻለው ለማወቅ ተችሏል።

የኮካ ኮላ መጠጦች አፍሪካ፣ የኢትዮጵያ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ዳሪል ዊልሰን ሲናገሩ፤ "ሽልማቱ ኩባንያው ከፍተኛ አቅምና አፈጻጸም ያላቸውን ሰራተኞች ለመሳብና ለማቆየት እንዲሁም፣ በሰው ሐብት አስተዳደር እድገት ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ያለውን አቋም ያንፀባርቃል" ብለዋል።

የኮካ ኮላ መጠጦች አፍሪካ (ሲሲቢኤ)፤ በአፍሪካ ከ18 ሺህ በላይ ሰራተኞች ያሉት ሲሆን፤ በአለማቀፍ ደረጃ ከ720 ሺህ በላይ ደንበኞች እንዳሉት "ቶፕ ኢምፕሎዪ ኢንስቲትዩት" ጠቁሟል። ኩባንያው በ15 ሀገራት ውስጥ የሚሰራ ሲሆን፤ ስድስት ቁልፍ ገበያዎቹ ደቡብ አፍሪካ፣ ኬንያ፣ ኢትዮጵያ፣ ኡጋንዳ፣ ሞዛምቢክና ናሚቢያ ናቸው። በተጨማሪም በታንዛኒያ፣ ቦትስዋና፣ ጋና፣ ዛምቢያ፣ ኮሞሮስ፣ ኢስዋቲኒ፣ ሌሶቶና ማላዊ ከፍተኛ ገበያ እንዳለው ተገልጿል።

በተቋሙ መስፈርት መሰረት፣ ኩባንያዎች የከፍተኛ ቀጣሪነት (Top Employer) የዕውቅና ሽልማት የሚያገኙት የሥራ ከባቢያቸው፣የሠራተኞችን አቅምና ችሎታ ለማጎልበት የሚያደርጉት ጥረቶች፣ አካታችነት፣ እንዲሁም በአጠቃላይ የሰው ሃብታቸውን ለማበልጸግ ያላቸው ቁርጠኝነት ከተገመገመ በኋላ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

Page 1 of 749