Administrator

Administrator

1.ለ6 ወር የታገደው “ሕገመንግስታዊ መብት”፤ 9 ወር ሞላው - ለአገር ገፅታ ሲባል

  • ወደ አረብ አገራት ለስራ መጓዝ ከታገደ ወዲህ ወደ የመን መሰደድ ተባብሷል
  • ባለፉት ሶስት ወራት ከ18ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የመን ገብተዋል
  • አምና በተመሳሳይ ወራት ወደ የመን የተሰደዱት ኢትዮጵያውያን 14ሺ ናቸው

2.በደቡብ ኦሞ በአመት 300 “እርጉም” ሕፃናት ይገደላሉ - ለብሔረሰብ ባህል ሲባል

  • በደቡብ ኦሞ ስለ ሐመር ድንቅ ባሕላዊ አኗኗር ምሁራንና ጋዜጠኞች ይነግሩናል
  • በባሕላዊ እምነት ሳቢያ የወላድ መካን የሆኑ እናት፤ ባህላችንን እጠላዋለሁ ይላሉ
  • የደቡብ ኦሞ ሸለቆ ላይ ያተኮረው የኤንቢሲ የቪዲዮ ዘገባ “የሞት ሸለቆ” ይሰኛል

3.በዋጋ ቁጥጥር የተነሳ የዳቦ ቤቶች ቁጥር እየተመናመነ ነው - ለህዝብ ጥቅም ሲባል

  • ለምሳሌ በሙዝ ላይ የተጫነው የዋጋ ቁጥጥር ሲሰረዝ የሙዝ ዋጋ አልጨመረም
  • ዳቦ ላይ የዋጋ ተመን ሲታወጅበት፣ የዋጋ ተመን ያልወጣለት አንባሻ ይበራከታል
  • የታክሲ እጥረቱንም ተመልከቱ። የዋጋ ተመን በደርግ ጊዜ ለአገሬው አልበጀም    

      “ለስራ ወደ አረብ አገራት መጓዝ ለ6 ወር ታግዷል” የሚለውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫ የሰማን ጊዜ፤ ብዙዎቻችን በግርምት “እኮ እንዴት?” ብለን አልጠየቅንም። እንደዘበት የተነገረንን መግለጫ እንደተራ ጉዳይ አደመጥነው። ይሄውና ዘጠኝ ወር አለፈው። እንግዲህ አስቡት።  የሌላ ሰው ኑሮና ንብረት እስካልነካን ድረስ፤ በግል ሕይወታችን ውስጥ ወዲህ ወዲያ ለመንቀሳቀስ፤ መንግስትን የምናስፈቅድበት አንዳችም ምክንያት የለም። ለዚህም ነው፤ በደርግ ዘመን “የመውጫ ቪዛ” በሚል ሲደረግ የነበረው ቁጥጥር ሙሉ ለሙሉ እንዲቀር የተደረገው። በአገር ውስጥ ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስም ሆነ ከአገር ውጭ የመጓዝ መብት፤ “ተፈጥሯዊ የሰው ነፃነት” ነው። ለነገሩማ፤ በሕገመንግስት ውስጥም ከመሰረታዊ ነፃነቶች ተርታ በጥቁርና ነጭ በግልፅ ሰፍሯል።
“ማንኛውም ኢትዮጵያዊ... በፈለገው ጊዜ ከአገር የመውጣት ነፃነት አለው” ይላል - አንቀፅ 32። እንግዲህ፤ ለነፃነት ወይም ለሕገመንግስት ክብር እንሰጣለን የምትሉ ሁሉ ይህንን አስተውሉ።
በፅሁፍ ላይ የሰፈረው አንቀፅ ቀላል አይደለም። መንግስት፤ መሰረታዊ መብቶችን በይፋ ማገድ የሚችለው፤ ለፓርላማ ቀርቦ በሚፀድቅ “የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ” አማካኝነት ብቻ ነው። ለዚያውም ከፓርላማ አባላት መካከል 51 በመቶ ያህሉ ስለደገፉ ብቻ አይፀድቅም፤ ቢያንስ 67 በመቶዎቹ መደገፍ አለባቸው። ለዚያውም ከ6 ወር ላልበለጠ ጊዜ ብቻ ነው እገዳው የሚቆየው። ይህም ብቻ አይደለም። ስርዓት አልበኝነት ካልነገሰ ወይም የውጭ ወረራ ካላጋጠመ በቀር፤ አልያም አደገኛ ወረርሺኝና የተፈጥሮ አደጋ ካልተፈጠረ በቀር፤ መሰረታዊ መብቶችን ለማገድ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማውጣት አይቻልም።
ይሄ ሁሉ የተባለለት መሰረታዊ የሰዎች መብት ነው፤ በአዋጅና በፓርላማ ሳይሆን፤ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫ የታገደው። እገዳውን ለማራዘምማ፣ አዋጅ ይቅርና ብጣሽ መግለጫ ማውጣትም አላስፈለገም። ለመሆኑ፤ ተፈጥሯዊውና በሕገመንግስት የሰፈረውን “የመንቀሳቀስ ነፃነት” እንደ ተራ ነገር ያለገደብ ለመጣስ፤ ምን ምን ማመካኛዎች ቀርበዋል? ሁለት ማመካኛዎች ናቸው የቀረቡት። አንደኛ፤ “እናውቅላችኋለን” የሚል። ሁለተኛ ደግሞ፤ “የአገር ገፅታንና ክብርን እናስጠብቃለን” የሚል።  
የመጀመሪያውን ማመካኛ እንመልከት። በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ወጣት ኢትዮጵያዊያን በየአመቱ የሚሰደዱት፣ “ትክክለኛ መረጃ ስለሌላቸውና የስደትን አደጋ ስለማይገነዘቡ ነው” ሲባል እንሰማለን። ግን፤ ይሄ አባባል ሃሰት ነው። በሃረር በኩል ድንበር ለማቋረጥ ሲጓዙ ከተገኙት 700 ሰዎች መካከል ብዙዎቹ፣ ዘንድሮ ከሳዑዲ አረቢያ የተባረሩ ወጣቶች ናቸው። አደጋውን አያውቁም ልንል ነው?
በእርግጥ፤ የስደት ጉዞው ስንት ቀን እንደሚፈጅ እቅጩን አያውቁ ይሆናል። በጉዞ ላይ የሚገጥማቸው የውሃ ጥም፣ ዝርፊያ፣ እገታ... የቱን ያህል አደገኛ እንደሆነ በቁጥርና በመቶኛ አስልተው ለመግለፅ አይችሉም። ነገር ግን፤ ከሞላ ጎደል ሁሉም ስደተኞች በርካታ ፈተናዎች እንደሚገጥሟቸው ያውቃሉ። እንዲያውም ከሰማኒያ በመቶ በላይ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች፤ ገና ከመነሻው ዋና ዋናዎቹን ፈተናዎች በዝርዝር ጠንቅቀው እንደሚያውቋቸው ዘንድሮ የተካሄደ ሰፊ የጥናት ሪፖርት ይገልፃል። ዩኤንኤችሲአር፣ አይኦሜ እና ሌሎች አለማቀፍ ተቋማት ያቋቋሙት ፅ/ቤት (RMMS) ነው ጥናቱን ያካሄደው። በሰኔ ወር ይፋ የተደረገው የጥናት ሪፖርት ላይ እንደተገለፀው፤ አብዛኞቹ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በጉዞ ላይና ከዚያ በኋላ የሚያጋጥሙ ፈተናዎችን በዝርዝር ከማወቅም በተጨማሪ ህይወታቸው ለአደጋ እንደሚዳረግ ይገነዘባሉ።  
ስለዚህ፤ “አያውቁም፤ መረጃ የላቸውም” የሚለው ማመካኛ፤ መሰረት የለሽ ውሸት ነው። ደግሞስ፤ የመረጃና የእውቀት ጉድለት ካለባቸው፤ መፍትሄው መረጃ በስፋት ማቅረብና ማሳወቅ እንጂ፤ “አትጓዙም” ብሎ በግድ መከልከልና ነፃነታቸውን መጣስ ምን አመጣው?     
ከዚሁ ጋር አብሮ የሚነሳ ሌላ ማመካኛ አለ - በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ወጣት ኢትዮጵያዊያን በየአመቱ የሚሰደዱት፣ “በደላሎች ስለሚታለሉ ነው” የሚል። ይሄም፤ መሰረት የለሽ ውሸት ነው። ካልተሰደድክ ብሎ የሚያስገድድ ደላላ የለም። ደግሞም፤ አዲሱን የጥናት ሪፖርት መመልከት ትችላላችሁ። በስደት ወደ የመን ለመጓዝ የወሰኑት በደላሎች አማካኝነት እንደሆነ ከተጠየቁ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች መካከል፤ 98 በመቶ ያህሉ “አይደለም” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል። በደላሎች ውትወታና ማታለያ ለስደት የተነሳሱት ወጣቶች፤ እጅግ ጥቂት ናቸው - ሁለት ከመቶ ብቻ።
እውነታው እንዲህ በግልፅ ቢታወቅም፤ ስለ ስደት በተወራ ቁጥር፣ እንደተለመደው “ስደተኞች መረጃ የላቸውም፤ ተጠያቂዎቹ ደላሎች ናቸው” የሚል ውንጀላ ከየአቅጣጫው እንደሚዥጎደጎድ አያጠራጥርም። ለምን? ለእውነታ ብዙም ክብር የለንም። ለነፃነትም ዋጋ ስለማንሰጥ፤ በመግለጫ ብቻ “የጉዞ እገዳ” እንጥላለን - “እናውቅላችኋለን” ወይም “የአገርን ገፅታ ታበላሻላችሁ” በሚል ማመካኛ።
ነገር ግን፤ በሕጋዊ መንገድ መጓዝ ቢታገድም፣ በዘፈቀደ መሰደድ መች ይቀራል? ባለፉት ሦስት ወራት ውስጥ ከ18ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን ወደ የመን ገብተዋል። በዚህ ከቀጠለ፤ በአመት ከ90ሺ በላይ ይሆናል። አደጋውን አስቡት። ከ2000 ዓ.ም ወዲህ፣ ወደ የመን ሲጓዙ ሁለት ሺ ያህል ሰዎች መንገድ ላይ ሞተዋል።  በህጋዊ ምዝገባ ወደ አረብ አገራት የሚደረገው ጉዞ ስለታገደ፤ ያለ ቪዛ ወደ የመን የሚሰደዱ ሰዎች ሲበራከቱ በአመት ውስጥ ምን ያህሉ ሊሞቱ እንደሚችሉ አስቡት። በአማካይ ከ40 በላይ የሚሆኑት ኢትዮጵያዊያን በጉዞ ላይ እንደሚሞቱ ልብ ማለት ያስፈልጋል - በአንድ አመት ውስጥ። “አገር” ወይም “የአገር ገፅታ” ለሚባል ጣኦት መስዋእት እያደረግናቸው እንደሆነ አስቡት። በህጋዊ ቪዛ ሲጓዙ ከነበሩት ውስጥ የዚህን ያህል ሰዎች አይሞቱም ነበር።
“እናውቅላችኋለን” ከምንል ይልቅ “አናውቅላችሁም” ብንል ይሻላቸው ነበር።  ምክንያቱም፣ በሺ የሚቆጠሩት ወጣቶች ያለ ቪዛ ለመጓዝ የመረጡበትን ምክንያት ሲጠየቁ፤ ህጋዊው ጉዞ በተንዛዛ ቢሮክራሲ ሳቢያ እንቅፋት ስለበዛበት ነው ብለዋል። ዘንድሮ ደግሞ ከነጭራሹ ታግዷል። ምን ይሄ ብቻ! ጭራሽ በድንበር በኩል ከአገር ልትወጡ ስትሞክሩ ተገኝታችኋል ተብለው እዚሁ አገራቸው ውስጥ የሚታሰሩ ወጣቶችን አይተናል። ወንጀላቸው ምንድነው? የትኛውን የወንጀል አንቀፅ ጥሰዋል? ማንን ጎድተዋል? ምንም!  
በአጠቃላይ ሲታይ፤ የኛ ችግር፣ የአገራችን ችግር በአጭሩ ሊገለፅ ይችላል - ለእውነታ ዋጋ አንሰጥም። ለነፃነትስ? ለህገመንግስትስ? ለሰው ሕይወትስ? ለሰው ምርጫና ጥረትስ? ለሰብአዊ ክብርስ ዋጋ እንሰጣለን? አንሰጥም። በዚህም ምክንያት፤ “እናውቅላችኋለን” በሚል ወይም “የአገር ገፅታ” በሚሉ ሰበቦች፤ የሰዎች ተፈጥሯዊ ነፃነትና ሕይወት ላይ እንጫወታለን።
“አይ፤ ለእውነታ፣ ለነፃነትና ለሕይወት ክብር እንሰጣለን” የሚሉ ሰዎች እንደሚኖሩ ይገባኛል። “እገዳው ተገቢ ባይሆንም፣ ቢያንስ ቢያንስ በቀጥታ የሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ያነጣጠረ የመብት ረገጣ አይደለም” የሚል መከራከሪያም ያቀርቡ ይሆናል። በቀጥታ የሰው ሕይወት ላይ ያነጣጠረ ሲሆንስ ደንታ ይኖረናል?
ኢትዮጵያዊቷ የደቡብ ኦሞ ተወላጅ ቡኮ ባልጉዳ ይመስክሩ።

ሕፃናት ወደ ገደልና ወደ ወንዝ ይወረወራሉ
የ45 ዓመቷ ቡኮ ባልጉዳ የወላድ መካን ናቸው። ልጆቻቸውን በሞት የተነጠቁ እናት። የወለዱትን ህፃናት በአንዳች በሽታ ወይም በአንዳች አደጋ ማጣት ልብን ይሰብራል። በግድያ ሲሆን ግን፣ ለማሰብም ይከብዳል። እንደ ብዙዎቹ የደቡብ ኦሞ ሴቶች፣ ቡኮ ባልጉዳ ልጅ የወለዱ ጊዜ የደስታና የስጋት ስሜት ቢቀላቀልባቸው አይገርምም። የጎሳ መሪዎች መጥተው የህፃኑን አፍ ከፍተው ድዱን ያያሉ። ህፃኑ የመጀመሪያ ጥርሱን በላይኛው ድዱ ካበቀለ፤ ይዘውት ይሄዳሉ - “ሚንጊ” (እርጉም) ነው በሚል። “በጎሳችን ላይ መዓት የሚያመጣ እርጉም!” የተባለው  ሕፃን  ወደ ገደል፣ ወደ ወንዝ ይወረወራል። ይሄ ባህል ነው። ለዘመናት የዘለቀ ማይሞገት አይነኬ ባህል! “ለጎሳው” እና “ለባህሉ” ሲባል፤ ሰዎች መስዋእት ይሆናሉ።
ቡኮ ባልጉዳ የመጀመሪያ ልጅ ከተገደለባቸው በኋላ እንደገና ወልደዋል። እንደገና “ሚንጊ ነው” በሚል ተገደለ። እንዲህ ሲወልዱና ሲገደልባቸው ነው የኖሩት። በሕይወት ዘመናቸው ስምንት ወንድ ልጆችንና ሰባት ሴት ልጆችን ወልደዋል። 15ቱም ሕፃናት “ሚንጊ ናቸው” ተብለው ተገድለዋል። የወላድ መካን ያደረጋቸውን ባህል እንደሚጠሉት ይናገራሉ - ቡኮ ባልጉዳ። ዴይሊ ሜይል እንዳለው፤ 300ሺ የሕዝብ ቁጥር በያዙት የሃመር እና የባኮ ማሕበረሰብ ውስጥ በየአመቱ 300 ሕፃናት፣ “ሚንጊ ናቸው” ተብለው እንደሚገደሉ ገልፀዋል። ይሄው የሚንጊ ባህል በመላ አገሪቱ የተለመደ ቢሆን ኖሮ፣ በየአመቱ ከመቶ ሺ በላይ ሕፃናት በተገደሉ ነበር።
አሰቃቂ ነው። ግን ስለ አሰቃቂነቱ ሲነገር ሰምተናል? ተፅፎ አንብበናል?
ብዙውን ጊዜ የሚነገረንና የሚፃፍልን፤ ስለ ሐመር ወይም ስለ ደቡብ ኦሞ ድንቅ ባሕል ነው። እንዲያውም ብዙዎቹ ተናጋሪዎችና ፀሃፊዎች፤ በጋራ የተመካከሩና የተስማሙ፤ አልያም የታዘዙ ይመስል፤ ስለ ሚንጊ አይናገሩም፤ አይፅፉም። ግን የትዕዛዝ ወይም የምክክር ጉዳይ አይደለም። ለእውነታ፣ ለነፃነት፣ ለሰው ሕይወት እና ለሰብአዊ ክብር የላቀ ዋጋ ስለማንሰጥ ነው። በየአመቱ 300 ሕፃናት! ባሕልን ወይም ብሔር ብሔረሰብን በማክበር ስም ነው ይሄ ሁሉ የሚደረገው። ለዚያ ለዚያማ፤ በየአመቱ እንደ ቡኮ ባልጉዳ የመሳሰሉ የብሔረሰቡ ተወላጅ የሆኑና ልጆቻቸውን የሚነጠቁ 300 እናቶች እና 300 አባቶችስ? ምሁራን፣ ጋዜጠኞች፣ ፀሐፊዎች ... ለእውነታ፣ ለነፃነት፣ ለሰው ሕይወትና ክብር የማትቆሙ ከሆነ፣ ሥራችሁ ምንድነው? ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች ለነፃነትና ለሰው ሕይወት የማትሟገቱ ከሆነ፣ አላማችሁ ምንድነው? እርስበርስ እየተጠላለፋችሁ ስልጣን መያዝ ብቻ!

ከዳቦ ወደ አንባሻ
በ2003 ዓ.ም ከ8 ቢሊዮን ብር በላይ አዳዲስ የገንዘብ ኖቶችን በማሳተም ከፍተኛ የዋጋ ንረት የፈጠረው መንግስት፤ የዋጋ ንረቱን በነጋዴዎች ላይ በማሳበብ የዋጋ ቁጥጥርና የዋጋ ተመን እንዳወጣ ታስታውሳላችሁ።  ከመነሻው፤ የገበያ ጠቃሚነቱኮ፣ ሰዎች በፈቃደኝነት የሚያካሂዱት መሆኑ ነው። ለምንድነው መንግስት በሰዎች ንብረት ላይ አዛዥ ናዛዥ የሚሆነው? “ለህዝብ ጥቅም” ሲባል ነዋ። “ለድሃው ጥቅም” ታስቦ ነዋ። ለሰፊው ሕዝብና ለድሃው ሕብረተሰብ ይጠቅማል እስከተባለ ድረስ፤ የሰዎችን ነፃነት መጣስ ይቻላል። አያችሁ? ለነፃነት ያን ያህልም ክብር የለንም። የዋጋ ቁጥጥርና የዋጋ ተመን የታወጀ ጊዜ ተቃውሞ አሰምተናል እንዴ? ብዙዎቻችን ደግፈናል። መንግስት ከጥቂት ወራት በኋላ የዋጋ ተመኑን ለመሰረዝ የወሰነው፣ ኢኮኖሚውን ይብስ እያቃወሰ እንደሆነ በግልፅ መታየት ስለጀመረ ነው። ነገር ግን፤ ሁሉም የዋጋ ተመን አልተሰረዘም - ለምሳሌ የዳቦ።
እንግዲህ አስቡት። የዋጋ ቁጥጥርና ተመን፣ የሰዎችን ነፃነት የሚጋፋ ቢሆንም እንደግፈዋለን - ለነፃነት ዋጋ ስለማንሰጥ። የዋጋ ቁጥጥርና ተመን፣ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴን የሚያበላሽ እንደሆነ በግልፅ ቢታይም እንደግፈዋለን - ለእውነታ ዋጋ ስለማንሰጥ። ቢያንስ ቢያንስ ለእውነታ ክብር ቢኖረንኮ፣ የዋጋ ተመን እንደማያዋጣ ተገንዝበን ተመኑ እንዲሰረዝ ማድረግ እንችል ነበር። እስቲ ይታያችሁ። በመንግስት የገንዘብ ህትመት ሳቢያ የዋጋ ንረት ሲከሰት፣ እንደሌላው ሸቀጥ የስንዴ ወይም የዱቄት ዋጋም ይጨምራል። ዳቦ ጋጋሪው ግን፤ ዋጋ መጨመር አትችልም ተብሏል።
ይሄ ሊያስኬድ አይችልም። መንግስትም ይህንን ያውቃል። እናም፤ ዳቦ ቤቶች በድሮው ዋጋ የስንዴ ዱቄት እንዲያገኙ አደርጋለሁ አለ። አንደኛ ነገር፤ የመንግስት ቢሮክራት፣ “ምን አተርፋለሁ፣ ምን አገኛለሁ” ብሎ፣ በጊዜ ስንዴ ለማቅረብ ይተጋል? ከደሞዙ ውጭ ምንም አያገኝም። በጊዜ ስንዴ ባያቀርብ ኪሳራ አይደርስበትም። የወር ደሞዙ አይቀነስበትም። እናም፤ እንደምታዩት ዳቦ ቤቶች በየጊዜው የስንዴ እጥረት እየገጠማቸው ስራቸው ይስተጓጎላል። ነገር ግን፤ የስንዴ ዱቄት በፍጥነትና በድሮ ዋጋ ለዳቦ ቤቶች ቢቀርብላቸውም እንኳ ብዙም አያስኬድም። ዳቦ እያመረቱ በድሮው የዋጋ ተመን መሸጥ እንዴት ይሆናል? የቤት ኪራይ፣ የማገዶ፣ የትራንስፖርት... ብዙ ነገሮችኮ ዋጋቸው ጨምሯል። ለዚህም ነው፤ በየሰፈሩ ብቅ ብቅ ሲሉ የነበሩት ዳቦ ቤቶች እየተዳከሙና እየተዘጉ፣ ቀስ በቀስ የየከተማው የዳቦ ቤቶች ቁጥር ሲመናመን የምናየው።
በዳቦ ምትክ፤ አሁን አሁን የአንባሻ ጋጋሪዎች ቁጥር እየተበራከተ መጥቷል። አንባሻ ላይ የዋጋ ቁጥጥር አይደረግማ። ግን፣ ውድ ነው። ምክንያቱም እንደዳቦ፣ አንባሻ በብዛት ማምረት አይቻልም። ለነገሩ፤ በብዛት ማምረት ቢቻል እንኳ ዋጋ የለውም። ያኔ፣ አንባሻ ላይም የዋጋ ቁጥጥር ይጀመርና እሱም ይዳከማላ።
የዋጋ ቁጥጥር ለሰዎች ኑሮ እንደማይበጅ በተደጋጋሚ አይተነዋል። የታክሲዎች ቁጥር የተመናመነውና የትራንስፖርት እጥረት የተባባሰው ለምን ሆነና! ለነገሩማ፤ በደርግ ዘመን በስፋት ተግባራዊ የተደረገው የዋጋ ቁጥጥር፣ የአገሪቱን ኢኮኖሚ ከማቃወስና ድህነትን ከማባባስ ያለፈ ጥቅም አላስገኘም።
እንዲያም ሆኖ፤ የዋጋ ቁጥጥር ላይ ብዙም ቅሬታ የለንም። ለምን? እውነታውን ብናውቀውም፣ ነፃነትን የሚጥስ ቢሆንም፣ ኑሮን የሚረብሽ ቢሆንም፤ ለእውነታ፣ ለነፃነትና ለሕይወት ብዙም ክብር ስለሌለን የዋጋ ቁጥጥርን አንቃወምም።   

በኢትዮጵያ ታሪክ ዘመናዊና መደበኛ ሠራዊት የተመሰረተው በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመን በ1927 ዓ.ም ነው፡፡ ይህ ሠራዊት ከጦር ሜዳ ውሎ ባሻገር ፖለቲካን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ በሆኑ የአገሪቱ ጉዳዮች ላይ ወሳኝ ተሳትፎ ነበረው፡፡
የፖለቲካውን ተሳትፎ እንኳን በስሱ ብንመለከተው፣ ከ1966 እስከ 1985 በነበሩት ዓመታት የኢትዮጵያን አምስት ያገር መሪዎች አፍርቷል፡፡ አራቱ በደርግ ዘመን ርዕሰ ብሔሮች ሆነው ሲያገለግሉ፣ አንዱ ደግሞ የኢህአዴግ ፕሬዚዳንት በመሆን አገልግለዋል፡፡
በደርግ ዘመን አገሪቱን የመሩት ጀነራል አማን አንዶም፣ ጀነራል ተፈሪ በንቲ፣ ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያምና ጀነራል ተስፋዬ ገብረኪዳን ናቸው። የኢህአዴጉ ፕሬዚዳንት ደግሞ መቶ አለቃ ግርማ ወልደጊዮርጊስ ናቸው፡፡ ስለ ጦሩ አመሠራረትና ሂደት ከሚመጣው ሳምንት ጀምሮ በዝርዝር እንመለከተዋለን። ለዛሬ ግን የቆምሻ ያህል ስለ ሦስት ጀነራሎች እጣ ፈንታ እንመለከታለን፡፡
ሦስቱ ጀነራሎች ማለትም ጀነራል ሙሉጌታ ቡሊ፣ ጀነራል ከበደ ገብሬ እና ጀነራል መንግስቱ ነዋይ፤ ጦሩ ሲመሰረት በአፍላ ዕድሜያቸው ተመልምለው በመኮንነት ማዕረግ ለመመረቅ ሆለታ ከከተቱት ወጣቶች መሃል ናቸው፡፡ የጣልያን ወረራ አይቀሬነትን የተገነዘቡት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ፤ ከስዊዲን አገር አምስት የጦር መኮንኖች በማስመጣት፣ በ1927 ዓ.ም የሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤትን አቋቋሙ፡፡ ስልጠናው ሳይጠናቀቅ የፋሽት ኢጣልያ ወረራ በመጀመሩ ሰልጣኞቹ ለግዳጅ ተጠሩ፡፡
ሰልጣኞቹ እንደ አንድ የተደራጀ ጦር ሆነው መዋጋት ስለነበረባቸው በትምህርት ቤቱ ቆይታቸው ባሳዩት የቀለም ትምህርት እና ወታደራዊ ቅልጥፍና፣ የአመራር ክህሎታቸው እየታየ ሹመት ተሰጣቸው። በዚህ የተነሳም ሙሉጌታ ቡሊና ከበደ ገብሬ የሻለቃ ማዕረግ፣ መንግስቱ ነዋይ ደግሞ የመቶ አለቃ ማዕረግ ተሰጣቸው፡፡
ሦስቱም ጀነራሎች ከሌሎቹ የጦር ጓዶቻቸው ጋር በመሆን የፋሽስት ኢጣልያን ወረራ ለመመከት ዝግጁ ሆኑ። ጦሩ የተሰጠው የጦር ግዳጅ ጣርማ በር ላይ በመመሸግ ወራሪውን ኃይል መመከት ነበር፡፡ ሆኖም በታጠቀው የጦር መሳሪያ ብልጫ እና የሠራዊት ብዛት የፋሽስት ኢጣሊያ ጦር በቀላሉ ድል አደረጋቸው። ኢትዮጵያ ለጊዜውም ቢሆን በኢጣልያ ቁጥጥር ስር ዋለች፡፡ በዚህ ጊዜ ጦሩ በአንድ ላይ ሆኖ ትግሉን መቀጠል አልቻለም። ከፊሉ ጥቁር አንበሳ የሚል ድርጅት በመመስረት ትግሉን ለመቀጠል ወደ ምዕራብ ሲያቀና፣ ሌሎች በሄዱበት አካባቢ ካገኙአቸው  አርበኞች ጋር ሲቀላቀሉ፣ የተቀሩት ፋሽስት ኢጣልያ የጦሩን አባላት እያደነ መግደል ሲጀምር ወደ ስደት አቀኑ፡፡
ወደ ስደት ካቀኑት መሃል ጀነራል ሙሉጌታ ቡሊ፣ ጀነራል ከበደ ገብሬ እና ጀነራል መንግስቱ ነዋይ ይገኙበታል፡፡ ሦስቱም ጀነራሎች የተሰደዱት ወደ ጅቡቲ ነው፡፡ ጅቡቲ ውስጥ ሦስቱም ከሌሎች ስደተኛ የጦር ጓዶቻቸው ጋር በመሆን ክፉውንም ደጉንም አብረው አሳልፈዋል፡፡ በወቅቱ ከሦስቱም ጋር ጅቡቲ ከነበሩት መሃል በወቅቱ አቶ ኋላ ላይ ጀነራል ወልደሥላሴ በረካና ጀነራል ወልደዮሐንስ ሽታ ይገኙበታል፡፡ ጅቡቲ ውስጥ ካጋጠማቸው አስከፊ የስደት ኑሮ በላይ ያንገበግባቸው የነበረው በፋሽስት ኢጣልያ ለተወረረችው አገራቸው በሞያቸው ማገልገል አለመቻላቸው ነበር፡፡ አረረም መረረም የጅቡቲ የስደት ኑሮዋቸውን በአንፃራዊ ሰላም ለተወሰኑ ዓመታት ሲመሩ ቆይተው፣ ፈረንሳይ በናዚዋ ጀርመን ድል ተመታ ስትያዝ፣ ኢጣልያ የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት የሆነችውን ጅቡቲን በአየር ኃይሏ መደብደብ ጀመረች፡፡
በዚህ ወቅት ጅቡቲ ውስጥ መቆየቱ ለአደጋ መጋለጥ መሆኑን የተገነዘቡት ጀነራሎች ወደ ሌላ ቦታ መሄድ እንዳለባቸው ወሰኑ፡፡ በቅርብ ርቀት ወደምትገኘው የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት አካል ወደሆነችው በርበራ ማቅናት እንዳለባቸው ተስማሙ፡፡ በጅቡቲ የነበሩት የጦር ጓዶቻቸውን ብቻ ሳይሆን በወደቡ ይኖሩ የነበሩ ሴትና ህፃናት የሚገኙባቸው ኢትዮጵያውያንን በመያዝ ወደተባለው ቦታ በጀልባ ጉዟቸውን ጀመሩ፡፡
ጀልባዋን ከአንድ ህንዳዊ በመከራየት በህንዱ መሪነት ነው ወደ በርበራ ያቀኑት። እንቅስቃሴአቸውን ሁሉ በንቃት ሲከታተል የነበረው የኢጣልያ ስለላ መረብ በአካባቢው ለነበረው ጦሩ ስለጠቆመ፣ ከፍተኛ አደጋ ለማድረስ የሚችለውን ሁሉ አድርጐ አልተሳካለትም፡፡
ስደተኞቹ በርበራ እንደደረሱ እንደነሱው ሁሉ በርበራ ውስጥ በስደት ከሚኖሩ የጦር ጓዶቻቸው ጋር ተገናኙ፡፡ ከስደተኞቹ መሃል ጀነራል አሰፋ አየነ ኋላ ላይ የኢትዮጵያ አየር ኃይል አባት እየተባሉ ይጠሩ የነበሩት ይገኙበታል፡፡
በርበራም ከኢጣልያ ጥቃት አልተረፈችም። በዚህ ጊዜ የእንግሊዝ ጦር በባህር ኃይሉ ጭኖ ወደ የመን ዋና ከተማ ወሰዳቸው፡፡ ኤደን ለትንሽ ጊዜ ከቆዩ በኋላ ኬንያ በመሄድ፣ ከሌሎች ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ጋር በመሆን፣ ጠላታችንን መዋጋት እንፈልጋለን በማለት ለእንግሊዞቹ ማመልከቻ ስለፃፉ እንግሊዞች ወደ ኬንያ ላኩአቸው፡፡
ልብሳቸውን አወለቁ፡፡ መሬት ላይ በመተኛት በጅራፍ እንዲገረፉ በቦታው የነበረው እንግሊዛዊ ለበታቾቹ ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡ በዚህ ጊዜ ስደተኞቹ በሙሉ ልብሳቸውን በማውለቅ ከጄነራል ከበደ ጎን ተኙ። በሁኔታው የተናደዱት እንግሊዞች ጫካ እንዲመነጥሩ ያዘዙአቸው ይሄኔ ነበር፡፡ ያ ሁሉ ግፍ ተፈፅሞባቸው፣ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ አገራቸውን ከፋሽሽት ኢጣልያ ነፃ ለማውጣት ሱዳን መግባታቸው ተሰማ፡፡ ስደተኞቹ “ከንጉሠ ነገስታችን ጋር በመሆን አገራችንን ነፃ እንድናወጣ ወደ ሱዳን እንድንሄድ ፈቃድ ይሰጠን” በማለት አመለከቱ፡፡ እንግሊዞች ግን ጆሮ ዳባ ልበስ አሉ። በእንግሊዝ እርዳታ ሱዳን የገቡት ጃንሆይ፤ “ኬንያ ያሉት ስደተኞች ለማቋቁመው ጦር ስለሚስፈልጉኝ ይላኩልኝ” ብለው ስለጠየቁ፣ ኬንያ ያሉት እንግሊዞች ምንም ማድረግ አልቻሉም፡፡ ሆኖም በጀነራል ሙሉጌታ ቡሊና በጄነራል ከበደ ገብሬ ፅናትና ድፍረት የበገኑት እንግሊዞች፤ ሰበቦች በመደርደር ላለመልቀቅ ጣሩ፡፡ በዚህ የተነሳም ሌሎቹ እነሱን ትተን አንሄድም ብለው ስለቆረጡ ሁለቱንም ለመልቀቅ ተገደዱ፡፡
በኬንያ የከፋ ኑሮ ጫካ ሲመነጥሩ በነበሩበት ጉዜ በያዛቸው ወባ የተጎሳቆሉት ስደተኞች፤ ወደ ኡጋንዳ በመኪና ተጭነው ከሄዱ በኋላ በባቡር ወደ ሱዳን ተጓዙ። ሱዳን አገር ላይ ሶባ በተባለ ቦታ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ባቋቋሙት ጊዜያዊ ጦር ትምህርት ቤት በመግባት የተማሩትን የጦር ትምህርት ከለሱ፡፡
ከስልጠናው በኋላ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴን በመከተል አዲስ አበባ ገቡ፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በጃንሆይ መሪነት እንደ አዲስ ተደራጅቶ ስራውን ሲጀምር፣ ሦስቱ ጄነራሎች በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች በመመደብ አገራቸውን ማገልገል ጀመሩ። ጄነራል ሙሉጌታ ቡሊ የክብር ዘበኛ አዛዥነት ከደረሱ በኋላ በወቅቱ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግስት ውስጥ በተፈጠረው የፖለቲካ ሽኩቻ ከቦታው ተነስተው የህዝባዊ ኑሮ እድገት ሚኒስትር ሆኑ፡፡ ጄነራል ከበደ የምድር ጦር ዋና አዛዥ ሆኑ፡፡ ጄነራል መንግስቱ ደግሞ ሙሉጌታን በመተካት የክብር ዘበኛ አዛዥ ሆኑ፡፡ ለሚያውቃቸው ሁሉ የሶስቱ ጄነራሎች ጓደኝነት ጥብቅ ነበር፡፡ ጓደኝነታቸው የወንድማማችነት ያህል ስለነበር ባለቤቶቻቸውም ሆኑ ልጆቻቸው ችግር ሲገጥማቸው በቀጥታ በመሄድ ችግራቸውን የሚያካፍሉት ለነሱ ነበር።
1953 ዓ.ም ለኢትዮጵያ ሕዝብ ወሳኝ ዓመት ነበረች። ለሶስቱ ጄነራሎች ደግሞ የበለጠ፡፡ ያ ሁሉ ከልጅነት ጀምሮ በስደትና በነፃነት፣ በኋላም በነበራቸው ጥብቅ ግንኙነት የተፈጠረው ወንድማማችነት ውኃ በላው። ጄነራል መንግስቱ መንግስት ገልባጭ፣ ጄነራል ከበደ ግልበጣውን አክሻፊ፣ ጄነራል ሙሉጌታ ደግሞ ታሳሪ ሆነው አረፉት፡፡  በዚህ የተነሳም ጄነራል መንግስቱ ግልበጣው ሲከሽፍ በስቅላት ሲገደሉ፣ ጄነራል ሙሉጌታ ደግሞ በጥይት ተደብድበው ሞቱ። ለጊዜው ከሞት የተረፉት ጄነራል ከበደ ገብሬ የመጀመሪያው የተባበሩት መንግስታትን ጦር በኮንጎ የመሩ ጥቁር ጄነራል ሆኑ፡፡ በስራቸው የስዊዲን የአየር ላንድና የአንድ ጄነራሎች ገበሩ፡፡ ከዚያም የመከላከያ ሚኒስቴር በመሆን አገራቸውን አገለገሉ፡፡ በ1966 ወታደራዊው መንግስት ታላላቅ ኢትዮጵያውን የሚገኙበት ባለስልጣኖችን በግድያ ሲቀጣ፣ ጄነራል ከበደ ገብሬም በጥይት ተደብድበው ተገደሉ፡፡
ይቺ ትንሽ ታሪክ የኢትዮጵያን ምስቅልቅል ህይወት በጥቂቱም ቢሆን ታመላክታለች፡፡ የሦስቱም ጓደኛሞች ፍፃሜ ግን አይገርምም፡፡ የሳምንት ሰው ይበለን፡፡  

ባለስልጣናት ሥልጣን የማይለቁት “የስልጣን ጡር” ስለሚፈሩ ነው

        ኢህአዴግ “ረዳት መንግስት” ያስፈልገዋል ስል ሌላ የፖለቲካ ጨዋታ ውስጥ እንዳትገቡ፡፡ ያልተቀኘሁትን ቅኔም ለመፍታት እንዳትሞክሩ፡፡ እኔ ለማለት የፈለግሁት ኢህአዴግ በግራና በቀኝ በልማት ስለተጠመደ፣ ይህችን አገር በቅጡ ለመምራት “ረዳት መንግስት” ያስፈልገዋል ነው፡፡ እመኑኝ፤ በአማካሪ በምናምን ሊወጣው የሚችለው ጉዳይ አይደለም። በ“ረዳት መንግስት” ብቻ እንጂ፡፡ ያውም እኮ ቀና “ረዳት መንግስት” ከተገኘ ነው፡፡
በነገራችሁ ላይ ልማታዊው አውራ ፓርቲ፤ እዚህ ደረጃ ላይ የደረሰው በራሱ ጥፋት ነው (ለመወንጀል ሳይሆን ለመተቸት ያህል ነው!) የመንግስት ሹማምንቱን በፖለቲካ ታማኝነት ብቻ መመልመሉ ነው ለዚህ ያበቃው (የፓርቲ ፍቅር ሌላ ብቃት ሌላ!) እስቲ አስቡት… ኢህአዴግ እተማመንባቸዋለሁ ብሎ ከሾማቸው የፓርቲው ታማኝ አባላት መካከል ስንቶቹ በሙስና ተዘፍቀው ዘብጥያ እንደወረዱ! ልማታዊ ህዝብ ይፈጥራሉ የተባሉ ስንት ሹመኞች የኪራይ ሰብሳቢ ሰራዊት መልምለውና አሰልጥነው ቁጭ እንዳሉ! (“የት ይደርሳል የተባለ ዛፍ ቀበሌ ቆረጠው” አሉ!)
እኔ የምለው… ኢህአዴግ “ታማኝ” ናቸው ብሎ ከሾማቸው በኋላ ሙሰኛ ሆነው ለተገኙት አባላቱ ተጠያቂው ማነው?(እንደ ደንቡማ ኢህአዴግ ነበር!)
ይሄን ሁሉ ያመጣሁት ዝም ብዬ ለወቀሳ ብቻ አይደለም፡፡ ኢህአዴግ “ረዳት መንግስት” ያስፈልገዋል እስከመባል የደረሰው ራሱ የሾማቸው ኃላፊዎች ስራቸውን በቅጡ ስለማይሰሩ እንደሆነ ለማስረገጥም ጭምር ነው፡፡  አንድም በአቅም ማነስ፣ አንድም ደግሞ በልግመት፡፡ (የአቅም ግንባታ መ/ቤት ተዘግቷል እንዴ?)
ይሄውላችሁ…. አንዳንድ ከተጨባጩ እውነታ የተራራቁ ፖለቲከኞች (ኢህአዴግ “ፅንፈኛ ተቃዋሚዎች” የሚላቸው!) በምርጫ ዋዜማ ላይ እንደሚሉት፤ “ኢህአዴግ አብቅቶለታል፤ አንድ ሐሙስ ነው የቀረው!” ምናምን የሚል ነገር አልወጣኝም (ኧረ ወደፊትም አይወጣኝ!) “ረዳት መንግስት” የሚለው ሃሳብ ከተተገበረ እኮ ኢህአዴግ እንኳን ሊያበቃለት አዲስ ጉልበት ነው የሚያገኘው (እንደ ውለታ እንዲቆጠርልኝ ፈልጌ ግን አይደለም!)
በእርግጥ ሃሳቡ ከፀደቀ ብዙ ጥያቄዎች ሊነሱ ይችላሉ፡፡ ጉዳዩን በተመለከተ አዲስ አዋጅ ሁሉ ሊረቀቅ ይችላል፡፡ ለምን መሰላችሁ? “ረዳት መንግስት” የሚለው ትንሽ አወዛጋቢ ሊመስል ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን ሌላ ምርጫ የለም። ለነገሩ የመንግስትና የስልጣን ጉዳይ ሁሌም ስለሚያወዛግበን ነው እንጂ ቀላል ነው፡፡ ምን መሰላችሁ…ለሳይንቲስት ረዳት ሳይንቲስት፣ ለሃኪም ረዳት ሃኪም፣ ለዳኛ ረዳት ዳኛ ወዘተ… እንዳለው ሁሉ፣ ለኢህአዴግ መንግስትም “ረዳት መንግስት” እንዲኖረው ማድረግ ብቻ ነው፡፡ (ህግና ደንብ አውጥቶ ማለቴ ነው!) “ረዳት መንግስት” ከየት ይመጣል? እኔ አላውቅም፡፡ እንዴት ይደራጃል? እሱንም አላውቅም፡፡ (እኔ መፍትሔ አፍላቂ ብቻ ነኝ!)
እዚህ ጋ አንባቢ እንዲረዳልኝ የምፈልገው፣ ኢህአዴግ እንደካምቦዲያ መንግስት ከተቃዋሚዎች ጋር ስልጣን ይጋራ እያልኩ አለመሆኔን ነው፡፡ ሥልጣን ማጋራትም ሆነ መጋራት ሃጢያት ሆኖ ግን አይደለም፡፡ (ላወቀበትማ ሥልጣኔ ነበር!) የዚህ ፅሁፌ ዓላማ “የሥልጣን ማኔፌስቶ” ማዘጋጀት ባለመሆኑ ብቻ ነው፡፡ እናም ሲፈልግ ኢህአዴግ ራሱ ሊያደራጀው ወይም ደግሞ እንደ ማኔጅመንት ኩባንያ ከውጭ አገር በቅጥር ሊያስመጣው ይችላል። ዋናው ነገር ግን “ረዳት መንግስት” በአፋጣኝ እንደሚያስፈልገው ማወቁ ላይ ነው፡፡
በነገራችሁ ላይ ይሄ “ረዳት መንግስት” የሚለው ነገር በመንግስት አስተዳደር የዳበረ ልምድ አለን ከሚሉት ከየትኞቹም የዓለም አገራት ያልተቀዳ ኦሪጂናል “አገር በቀል” ሃሳብ ነው፡፡ (ከስንዴ እስከ ጸረ-ሽብር ህግ ከእነሱ ቀድተን እንችለዋለን እንዴ?) እናላችሁ… ኢህአዴግ በል ካለውና እግረ መንገድ ከመንግስት ሥልጣን ጋር እንዲለማመዱ ካሰበ… አቅም ያላቸውን ተቃዋሚዎች “ረዳት መንግስቱ” አድርጎ ሊሾማቸው ይችላል፡፡ ወይም ደግሞ ከአገሬ ተቃዋሚዎች ይልቅ ቻይናን ነው የማምነው የሚል ከሆነም (ማለቱ አይቀርም!) እንደ ኩባንያ ማኔጅመንት በኮንትራት አስመጥቶ በ “ረዳት መንግስትነት” ሊያሰራቸው ይችላል፡፡ ምርጫው የሥልጣኑ ባለቤት ነው፡፡ (የኢህአዴግ ማለቴ ነው!)
ሰሞኑን የወጣው “ብሉምበርግ” የተሰኘ የፋይናንስ መጽሔት፤ በአዲስ አበባ ተቋቁሞ ጫማ ስለሚያመርት የቻይና ኩባንያ ያወጣውን አንድ ዘገባ አነበብኩ፡፡ ኩባንያው አሁን 3ሺ500 ሰራተኞች ያሉት ሲሆን በ8 ዓመት ውስጥ የሰራተኞቹን ቁጥር 50ሺ የማድረስ ዕቅድ እንዳለው ቻይናዊው ባለቤት ለብሉምበርግ ገልጿል፡፡ እኔን ያስገረመኝ ግን የአንድ ኢትዮጵያዊ ጫማ ሰሪና የቻይና አቻው የደሞዝ ልዩነት ነው፡፡ ኢትዮጵያዊው 40 ዶላር (800 ብር ገደማ) ሲያገኝ ቻይናዊው 400 ዶላር (8ሺ ብር ገደማ) ያገኛል ብሏል - መጽሔቱ፡፡ ኢትዮጵያዊ ጫማ ሰሪ በሰዓት ስንት እንደሚከፈለው ታውቃላችሁ? 25 ሳንቲም ገደማ ነው፡፡ ወይም በቀን 2 ዶላር፡፡ በኒውዮርክ የአንድ ስኒ ቡና ዋጋም 2 ዶላር ገደማ ነው፡፡ አበሻ አገር ጉልበት እርካሽ ነው ወይስ ነፃ? (ለጠቅላላ እውቀት እኮ ነው!)
ወደ ጉዳያችን እንመለስ ---ኢህአዴግ ለ“ረዳት መንግስትነት” ቻይናዎችን ከመረጠ ጉዳዩን   ከህግ አንፃር መመርመር ሳያስፈልግ አይቀርም፡፡ (ተቃዋሚዎች እቺን ካገኙ እኮ “ለቅኝ ገዢ አገርን አሳልፎ መስጠት” በሚል መንግስትን ሊከሱት ይችላሉ!)
ይሄውላችሁ ---- አንዳንድ ካድሬዎች፤ ደርግና ንጉሱ እንኳን ያለ “ረዳት ገዝተው” የለም ወይ ብለው ሊያሳጡኝ ይሞክሩ ይሆናል፡፡ ግን እኮ ድሮና ዘንድሮ ለየቅል ናቸው፡፡ መቼም 40 ሚ. ህዝብ መምራትና 90 ሚ ህዝብ መምራት አንድ ሊሆን አይችልም፡፡ በዚያ ላይ የድሮ መንግስታት ሚናቸው የአባትነት ብቻ ነበር፡፡ ኢህአዴግ እኮ የአባትነትም፣ የእናትነትም (“የእንጀራ እናት” የሚሉትም አሉ!) የታላቅ ወንድምነትም፣ የመንግስትነትም ሚና ነው የሚጫወተው፡፡ (“ማን አስገደደው?” ለሚሉ መልስ የለኝም!) ከቅርብ ጊዜ ወዲህማ “ሥራ ብዙ” ሆኗል፡፡ በአንድ በኩል ሃዲድና አስፋልት ያነጥፋል (“የመንገድ መንግስት” ሲሉ ሰማሁ ልበል?) በሌላ በኩል ለቤት ፈላጊዎች ኮንዶሚኒየም ገንብቶ ለማስረከብ ደፋ ቀና ይላል፡፡ (በርና መስኮት የለውም ቢባልም!) እዚያ አባይ ማዶ ደግሞ ከግብጽ ጋር ስንት የተባባልንበትን የህዳሴ ግድብ ይገነባል፡፡
ይሄ ሁሉ ሳያንሰው የስኳር ፋብሪካዎችም እሱኑ ነው የሚጠብቁት፡፡ (እሱንስ ለሆላንዶች ሰጥቶ በተገላገለ!) ይሄ ብቻ ግን አይደለም፡፡ መሰረታዊ የንግድ እቃዎች ከውጭ እያስመጣ “አለ በጅምላ” በተባለው መደብር በኩል ያከፋፍላል፡፡ (ነጋዴን አላምንም ብሎ ነው አሉ!) በዚያ ላይ የፖለቲካ ሥራውም ትንፋሽ ያሳጣው ይመስላል፡፡ የምርጫ ቅስቀሳ ምናምን እኮ አይደለም፡፡ በሽብርተኝነት የጠረጠራቸውን ጋዜጠኞች፣ ጦማሪያኖች፣ ፖለቲከኞች… ከያሉበት ሰብስቦ ማሰር…ፍ/ቤት ማቅረብ፣ መክሰስ፣ ማስፈረድ፣ ለዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ነን ባዮች ኮስተር ያለ የአበሻ መልስ መስጠት… ይሄም የመንግስት ሥራ ነው፡፡ ታዲያ … በእሱስ ይፈረዳል? (ቆይ ስንት ቦታ ይሁን?!)
እውነቱን ልንገራችሁ አይደል ----- የፈረንጅ መንግስት ቢሆን ገና ድሮ “በቃኝ” ብሎ ራሱን ከስልጣን ያሰናብት ነበር፡፡ የአበሻ መንግስት ግን “ብረት” ነው፡፡ (አበሻ እጅ አይሰጥም!)  በዚያ ላይ ሹመትን የመሰለ ክቡር ስጦታ ጥለን መሄድ ባህላችን አይደለም (የስልጣን ጡር እንፈራለን!) በዚህ መሃል ነው ብዙ ውጥንቅጥ የተፈጠረው፡፡ በዚህ መሃል ነው የውሃ፣ የመብራት፣ የኢንተርኔትና የኔትዎርክ መጥፋትና መቆራረጥ እንዲሁም የትራንስፖርት ችግር መከራችንን ያበሉን፡፡ በዚህ መሃል ነው ብንጮህ ብንጮህ የሚሰማን ያጣነው። (ኢህአዴግ በብዙ የልማት ሥራዎች ተወጥሯላ!) ለዚህ ነው አይፈረድበትም የምለው፡፡ ግን መፍትሔ ያስፈልጋል፡፡ መፍትሔው ደግሞ “ረዳት መንግስት” ነው፡፡
ሰሞኑን ደግሞ ከመንግስት ሠራተኞች ደሞዝ ጭማሪ ጋር ተያይዞ ነጋዴዎች የሸቀጦችን ዋጋ በማናር ኢኮኖሚውን ለግሽበት እንዳይዳርጉት በአንድ ወገን በህገወጥ ነጋዴዎች ላይ እርምጃ እየወሰደ፣ በሌላ ወገን ሸቀጦችን በየመ/ቤቱ አከፋፍላለሁ ብሏል፡፡(ሰሞኑን በደርግ ዘመን የረሳሁትን የቀበሌ ሃሎ ሃሎ ሰማሁ ልበል!)
ወዳጆቼ… ኢህአዴግ “ረዳት መንግስት” ያስፈልገዋል ብዬ በእርግጠኝነት የምናገረው ዝም ብዬ አይደለም፡፡ ችግሩን ስላየሁለት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ኢህአዴግ ከሳጥኑ ውጪ (Out of the box እንዲሉ) የሚያስቡ መፍትሔ አፍላቂ አማካሪዎችም መቅጠር ይኖርበታል፡፡ በመንግስት ደሞዝ ሳይሆን ወፈር ባለ ደሞዝ! (የመንግስት ሠራተኞች የደሞዝ ጭማሪ ምነው ሐምሌን ተሻገረ?) እናላችሁ…ለስንት ዓመት የተወዘፈና ሊፈታ ያልቻለ የችግር ተራራ እኮ እንዲህ በቀላሉ አይናድም፡፡ (ደማሚት ሁሉ ይፈልጋል!)

Saturday, 02 August 2014 11:32

የፖለቲካ ጥግ

ፖለቲከኛ የሚናገረውን ነገር ስለማያምንበት ሌሎች ሲያምኑት ይገርመዋል፡፡
ቻርልስ ደጎል
(የቀድሞ የፈረንሳይ ፕሬዚዳንት)
ልጅ ሳለሁ ማንም የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሊሆን እንደሚችል ተነግሮን ነበር፡፡ አሁን ማመን ጀምሬአለሁ፡፡
ክላሬንስ ዳሮው
(አሜሪካዊ የህግ ባለሙያ)
ቤት የማስተዳደርን ችግር የምትረዳ ማንኛዋም ሴት አገር የማስተዳደርን ችግር ለመረዳት ቅርብ ናት፡፡
ማርጋሬት ታቸር
(የእንግሊዝ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር)
ትላንት ማታ ጨረቃዋ፣ ክዋክብቱና ፕላኔቶቹ በሙሉ በእኔ ላይ ወድቀዋል፡፡ (ሰማይ ተደፍቶብኛል እንደማለት) ወገኖቼ፤ የምትፀልዩ ከሆነ ለእኔ ፀልዩልኝ፡፡
ሃሪ ኤስ. ትሩማን
(በወቅቱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የነበሩት
የፕሬዚዳንት ፍራንክሊን ዲ. ሩስቬልትን ህልፈት አስመልክቶ ለሚዲያ የተናገሩት)
አንተ አንዲቷ ምዕራፍ ነህ፤ እኔ ሙሉው መፅሃፍ ነኝ፡፡
ፍራንሶይስ ሚቴራንድ
(የቀድሞ የፈረንሳይ ፕሬዚዳንት አማካሪያቸው የተናገሩት)
አንድ አብዮተኛ ልታስሩ ትችላላችሁ፤ አብዮቱን ግን ማሰር አትችሉም፡፡
ቦቢ ሲሌ
(አሜሪካዊ የሲቪል መብቶችተሟጋች)
አንድ ጊዜ አንድ ታላቅ ሰው፤ ጠላቶቻችሁን ውደዱ ብሎ ነበር፡፡ ይሄ መጥፎ ምክር አይደለም፡፡ ጠላቶቻችንን ልንወዳቸው እንችላለን፡፡ ይሄ ማለት ግን አንዋጋቸውም ማለት አይደለም፡፡
ኖርማን ሽዋርዝኮፕፍ
(አሜሪካዊ ጄነራል)

(ዘር ያጣን ሸረት፣ አናነ ያጣን ጉርበት፣ አባመታ ይኸን)- የጉራጊኛ ተረት

አንድ የአፍሪካ ተረት እንዲህ ይላል :-
ከዕለታት አንድ ቀን ባልና ሚስት ከፍተኛ የመኩራራት ደረጃ ላይ ይደርሳሉ፡፡
ሚስት - “በሩን ዝጋና ተኛ” ትለዋለች ባሏን፡፡
ባል - “አንቺ ምን ሥራ ይዘሽ ነው እኔ በር የምዘጋው!” ይላታል፡፡
የፉክክር በር ሳይዘጋ ያድራል ወደሚለው ተረት የሚያመራ ይሆናል፡፡
ባል በመጨረሻ አንድ ዘዴ አመጣ - ውርርድ!
“ኧረ ካሁኗ ደቂቃ ጀምሮ ቃል የተነፈሰ፤ በሩን ይዝጋ” አለ፡፡
ሚስትም ተስማማች፡፡
ዝም ዝም ሆነ ነገሩ፡፡
በመካከል አንድ ለማኝ መጣና፤
“ስለማሪያም ተዘከሩኝ” አለ፡፡ መልስ የለም፡፡
“በአምላክ እህል አቅምሱኝ” አለ፡፡
የሚሰማው የለም፡፡
ገባ ወደቤት፡፡ ከዚያ ከብረት ድስቱ ውስጥ ምን የመሰለ አጥንት አግኝቶ መጋጥ ጀመረ፡፡ ባልም እያየ ዝም፡፡ ሚስትም እያየች ዝም፡፡ አንተንፍስ ብለዋላ! በማህል ለማኝ ሃይ የሚለው ስላጣ መጋጡን ቀጠለ፡፡ ለማኙ አጥንቱን ግጦ ሲጨርስ በገመድ አስሮ ሚስቲቱ አንገት ላይ አንጠለጠለው፡፡ እሷ አሁንም ዝም አለች፡፡
ቀጥሎ አንድ ውሻ መጣ፡፡ እሚስት አንገት ላይ የተንጠለጠለውን አጥንት መላስ ጀመረ። ይሄኔ ሚስቲቱ ትዕግሥቷ አለቀና፤
“ሂድ ከዚህ!” ብላ አባረረችው፡፡
ባል - “በቃ ውርርዱን ተሸንፈሻል!” አላት፡፡
ሚስት በመሸነፏ ተናዳ ኩርፊያዋን ቀጠለች፡፡ ራት ሳይበሉ ተኙ፡፡ ባዶ ሆዳቸውን አደሩ።
ጠዋት -
ባል “አየሽ ውድ ባለቤቴ፤ ከሚበልጥሽ ሰው አትወራረጂ፡፡
ትርፉ ጦም ማደር ነው!” አላት ይባላል፡፡
                                                   *    *    *
የፉክክር ቤት ሳይዘጋ ያድራል ማለት ይሄው ነው፡፡
“እኔን አይመለከትም፤ ሌላ ሰው ጠይቅ፤ እኔ አልታገልም፤ አንተው እንዳመጣብህ ታገል…እኔ በልቻለሁ፤ ያልበላው መከራውን ይይ…” ዛሬ የሀገራችን ፈሊጥ መሆኑ ብዙ አያጠያይቅም! እንዲህ ከሆነ ደግሞ ሀገር ማደጓ ዘበት ነው፡፡ ከጠዋት እስካሁን የምናየው የሀገራችን ሁኔታ ሌላው ሞቶ፣ ሌላው ተሰውቶ፣ የሚፈራውን ፍሬ እኔ ልብላ…ሌላው በቆሰለ በታሰረበት እኔ ስሜ ይጠራ፣ እኔ ዝና ላፍራበት ማለት ባህላችን እየሆነ መምጣቱ ነው፡፡
በመሠረቱ “ሁሉ ኮርቻ ላይ ከወጣ አለንጋ ማን ሊይዝ ነው?” እንደተባለው፤ ፈረሱን የሚነዳ፣ የሚለጉምና የሚያራግፍ እንዳይጠፋ ያሰጋል፡፡ ሁሉ ፖለቲከኛ፣ ሁሉ ተናጋሪ፣ ሁሉ እኔ ነኝ የሀገር ጉዳይ የሚያገባኝ ካለ፤ ፖለቲካል ሳይንስ የተማረ ሁሉ መቅለጡ ነው በአንፃሩ “እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው” ለማለት የሚቸኩል ፖለቲከኛ የበዛበትም አገር ከፍሬው ገለባው ይበዛል፡፡
ፀጋዬ ገ/መድህን በምኒልክ አንደበት እንዲህ ይለናል፡-
“…አየህ እያሱ…ያገርህን ያበሻን ቤት አሰራር ተጨባጭ አገነባብ ባጭር ምሳሌ ላስተምርህ። ያበሻ ቤቱ፣ ያበሻ ጣራው ምሰሶ ጉልላቱ፣ ያበሻ ማዕዱ፣ ምድጃና መሶቡ፣ ያበሻ አውድማው አዳራሹና አደባባዩ እንደፀሐይ ክብ ብርሃን ጮራ እንደቀለበት የሕብር ዙሪያ እንደ ክበብ ነው…ባህልህን አስጠንቅረህ ካላወቅህ አገርህም አያውቅህ! ሕዝብህንም አታውቀው! ሕዝብህን ማወቅ ማለት የህዝብህን የባህል ብልት ጠንቅቀህ መገንዘብ ነው፡፡ ህዝብህን ማወቅ ደግሞ አገርህን ማወቅ ነው፡፡ ማንነቱን ያላጤንክለትን ሕዝብ ነገ ማስተዳደሩ ያቅትሃል እያሱ፡፡”
የሕዝብ ባህሉ እስትንፋሱ ነው፡፡ መናገሩ ነው፡፡ እንደልቡ መሆኑ ነው፡፡ ተናገር ብለህ “ቀስቅሰክ” ብለህ አትከሰውም፡፡ አለበለዚያ አገር የለውም፡፡ የህዝብ መብት ማንም እንዳሻው የሚቀለብሰው፣ እንዳሻው ዳር ድንበሩን የሚወስነው አሊያም “የአተረጓጐም ጉዳይ ነው” እያለ እንዳመቸው የሚያጣምመው አይደለም፡፡
አብዛኛው ነገረ - ሥራችን “ሲያቃጥል በማንኪያ ሲበርድ በእጅ” ዓይነት የሆነው በዚሁ ምክንያት ነው፡፡ “ከባዕድ ወስደህ ወደዘመድህ ዞረህ ጉረስ”ም ሌላው ፈሊጣችን ነው፡፡
ከጥቂት ጊዜ በፊት ሁነኛ ተቃዋሚ አጣን ይሉ የነበሩ፤ ተቃዋሚ ሲመጣ የአገር እንቅፋትና አሽክላ እንደፈጠሩ አይተናል፡፡ ተቃዋሚ ሲጠፋ በራሳቸው ማህል የተቃውሞ አውሎ - ንፋስ አስነስተው ተከፋፍለው፤ ተሰነጣጥቀው፤ እርስ በርስ ጐራ ለይተው ግራና ቀኝ ተባብለው እንደተጠፋፉም ታዝበናል፡፡ በራሳቸው ዕብጠት ወደ መፈንዳት የሄዱም እንደነበሩ ምስክር ሆነናል፡፡ ግራና ቀኝ መንገደና ተባበለው መፈረጃቸውንም ሰምተናል፣ አይተናል፡፡ ሁሉንም ጉልበተኛ እስኪውጣቸው “ዲሞክራሲ የእኛ ብቻ ናት”፤ “እንደኛ ፕሮግራም የሚጥም የትም አይገኝም!”፤ ‹እንደኛ ምርጫ “Fair” and “Free” የትም የለም› ይላሉ፡፡
ታሪክ ግን ታሪክ ሆነው እንደሚቀሩ ይዘግባል፡፡ ንድፈ - ሀሳብ ቀማሪዎቻቸውም ሆኑ አፈ - ጉባኤዎቻቸው፤ ወሬ አንጓቾቻቸውም ሆኑ ወናፎቻቸው ወይም መለከተ - ጥሩምባዎቻቸው ደሞ ለሌላ መንግሥት ማንባረቃቸውን፣ ማናፈታቸውን መቀጠላቸውንም ልብ እንላለን፡፡ ይሄ ሁሉ ሆኖ ግን ህዝቡ፣ ባለ ይዞታው፣ ባለ አገሩ፤ “ክረምት የሚያወጣውን ምግብ፣ ዳገት የሚያወጣውን ጉልበት፤ ባለቤቱ ያቀዋል” የሚለው የጉራጌ ተረት ደርዙ ይሄ መሆኑን ያቃል!!

በ11 የአፍሪካ አገራት ተሰራጭቷል

          ባለፈው ማክሰኞ ማለዳ… ሲኤን ኤን ከወደ ሴራሊዮን አንዳች አሳዛኝ ነገር ስለመከሰቱ ዘገበ፡፡ በምዕራብ አፍሪካዊቷ ሃገር በሴራሊዮን የተከሰተውን አሰቃቂ የኢቦላ ቫይረስ ወረርሽኝ ለመግታት ሌት ተቀን ደፋ ቀና ሲሉ ከነበሩት ታዋቂ ሃኪሞች አንዱ ሴራሊዮናዊ ዶ/ር ሼክ ሁማር ካሃን ሞቱ፡፡ የአገሪቱ መንግስት በህክምናው መስክ ከሚኮራባቸው ዜጎቹ የመጀመሪያው እንደሆኑ በይፋ የሚናገርላቸውና “ብሄራዊ ጀግናዬ” ብሎ የሰየማቸው ታላቅ ሰው፤ ኢቦላን በመሳሰሉ በቫይረስ የሚከሰቱ በሽታዎች ህክምና ዘርፍ በአለማችን ስማቸው ጎልቶ ከሚጠቀስ ቀዳሚ የህክምና ሊቃውንትና ባለሙያዎች አንዱ የነበሩት ሃኪም አረፉ፡፡ ከአገሪቷ መዲና ፍሪታውን 185 ማይሎች ርቃ በምትገኘው ኬኔማ የተባለች ከተማ ሆስፒታል ውስጥ የኢቦላ ህክምና የሚሰጠውን ቡድን በመምራት ከፍተኛ ስራ ተጠምደው የሰነበቱት፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ የኢቦላ ተጠቂዎችን ከሞት ለማዳን አልህ አስጨራሽ ትግል ሲያደርጉ የነበሩት ዶ/ር ካሃን፣ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ ላይ ነበር፣ ህመም ቢጤ ተሰምቷቸው እንደምንም ስራቸውን ገታ አድርገው ለማረፍ ወደ አልጋ ያመሩት፡፡

ህመሙ ግን እንዳሰቡት ቀላልና ቶሎ የሚድን አልነበረም፡፡ እያደር ባሰባቸው፡፡ ካሊሁን በምትባል ከተማ ውስጥ በሚገኝ ሆስፒታል ተኝተው፣ በድንበር የለሽ የሃኪሞች ቡድን ህክምና ሲደረግላቸው ቢቆዩም አልዳኑም፡፡ ታዋቂው ሴራሊዮናዊ የኢቦላ ሃኪም በ39 ዓመታቸው ሞቱ፤ የሞታቸው ሰበብ ደግሞ ኢቦላ መሆኑ ታወቀ - ሲታገሉት የሰነበቱት ቀሳፊ በሽታ፡፡ ይህ ድንገተኛ መርዶ፣ በኢቦላ ወረርሽኝ የተመቱ የምዕራብ አፍሪካ አገራትን ብቻም አይደለም ያስደነገጠው፡፡ ከአራት ወራት በፊት በጊኒ አሃዱ ብሎ ጀምሮ ወደ ላይቤሪያ የዘለቀው፣ ፍጥነቱን ጨምሮ ወደ ሴራሊዮን የተሻገረው ይህ ክፉኛ አሰቃይቶ ገዳይ ቫይረስ፣ ድንበር ሳያግደው መሰራጨቱን ቀጥሏልና፣ የዶ/ሩ ሞት በሌሎች አገራት ብሎም አህጉራት ለሚኖሩ ዜጎች የችግሩን መባባስ የሚመሰክር መርዶ ነበር የሆነው፡፡ አዎ!... አሁን በታሪክ እጅግ አደገኛው የተባለለት የኢቦላ ወረርሽኝ አለማችንን ጭንቀት ውስጥ ከቷታል፡፡ የዓለም የጤና ድርጅት ከአስር ቀናት በፊት ነበር፣ በምዕራብ አፍሪካ በሚገኙ አገራት ከ800 በላይ ሰዎች በኢቦላ በሽታ ተይዘው በመሰቃየት ላይ እንደሚገኙ በይፋ ያስታወቀው፡፡

ድርጅቱ በወቅቱ ይህን ይበል እንጂ፣ ሲኤንኤን ግን የታማሚዎች ቁጥር ከ 1 ሺህ 200 በላይ እንደሚሆንና ቫይረሱም ከአገራቱ አልፎ በስፋት በመሰራጨት የአህጉሪቷ ብሎም የዓለም ስጋት ሊሆን እንደሚችል ባለሙያዎች የሰጡትን አስተያየት በመጥቀስ አበክሮ ተናግሮ ነበር፡፡ እንደተባለውም ኢቦላ የዓለም ስጋት ለመሆን የፈጀበት የቀናት ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ በምዕራብ አፍሪካ የተቀሰቀሰውና እስካለፈው ሳምንት ድረስ በአካባቢው 672 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት የዳረገው የኢቦላ ወረርሽኝ፣ አሁን የመላ አለም ሰሞንኛ የጭንቀት ምንጭ ሆኗል፡፡ ዛሬ ኢቦላ የአንዲት አህጉር ሶስት አገራት ራስ ምታት ብቻም አይደለም፡፡ የቶጎው አየር መንገድ ኤስካይ፣ ቫይረሱን እንዳያሰራጭ በመስጋት ወደ ሴራሊዮንና ወደ ላይቤሪያ የሚያደርጋቸውን በረራዎች ሙሉ ለሙሉ አቋርጧል፡፡ በናይጀሪያዋ ሌጎስ የኢቦላ ሟቾች ቁጥር እያሻቀበ መምጣቱን ተከትሎ፣ በመላ አገሪቱ የወረርሽኝ ስጋት አንዣቧል፡፡ ታላቁ የአገሪቱ አየር መንገድ አሪክ ኤርም፣ ቫይረሱን ፍራቻ ወደ ላይቤሪያ ድርሽ ላለማለት ምሏል፡፡ ቫይረሱ እንደተፈራው በየአቅጣጫው በመሰራጨት የአገራትን ድንበር ተሻግሮ እየገባ እንደሆነ በርካታ የዓለማችን መገናኛ ብዙሃን እየዘገቡ ነው፡፡ ዩኤስ ቱዴይ ከትናንት በስቲያ ባሰራጨው ዘገባ እንዳለው፣ የእንግሊዝና የሆንግ ኮንግ መንግስታት ከሰሞኑ የበሽታው ምልክቶች የታዩባቸውን የአውሮፕላን መንገደኞች በፍጥነት በመያዝ በተከለለ ቦታ ውስጥ እንዲቀመጡና ቫይረሱ ወደሌሎች እንዳይዛመት ለማድረግ አፋጣኝ እርምጃ ወስደዋል፡፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በበኩሉ፣ ከትናንት በስቲያ በሰጠው መግለጫ፣ የጥንቃቄ እርምጃ መውሰድ እንደሚጀምር አስታውቋል፡፡ አየር መንገዱ ከምዕራብ አፍሪካ በሚመጡ መንገደኞች ላይ ጠበቅ ያለ የጥንቃቄ የማጣራት ስራ እንደሚጀምርና ለበረራ ሰራተኞቹ ስለ በሽታው ግንዛቤ እንዲኖራቸውና ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ የሚያስችላቸው ስልጠና መስጠቱን ገልጧል፡፡ የእንግሊዝ የጤና ሚኒስቴር ባለፈው ረቡዕ ከናይጀሪያ በመነሳት በፓሪስ አድርጎ ወደ በርሚንግሃም የገባ አንድ ግለሰብ የበሽታው ምልክቶች ታይተውበት በሃኪሞች እንዲያዝ ቢደረግም፣ ኢቦላ እንደሌለበት ተረጋግጧል፤ እስካሁንም በአገሪቱ የኢቦላ ታማሚ አልተገኘም ቢልም፣ ብዙዎች ግን መስጋታቸውን አላቋረጡም። የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ጸሃፊ ፍሊፕ ሃሞንድ፣ በዚያው ዕለት ጉዳዩ የሚመለከታቸውን ከፍተኛ ባለስልጣናትና ባለሙያዎች ያሳተፈና ኢቦላን ወደ አገሪቱ እንዳይገባ ማድረግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ የመከረ አስቸኳይ ስብሰባ ያደረጉትም ጉዳዩ ስላሰጋቸው ነው፡፡ በሩቅ ያለችው አሜሪካም ብትሆን፣ ከወደ አፍሪካ የተነሳው መቅሰፍት ዜጎቿን እንዳያገኝባት ሰግታለች፡፡ ከላይቤሪያ በመነሳት ሚኒሶታ ውስጥ በተደገሰው የልጁ ልደት ላይ ለመገኘት ጓጉቶ ወደ ሚኒሶታ ሊጓዝ የተሰናዳው ዜጋዋ ፓትሪክ ሳውየር፣ ሌጎስ ውስጥ አውሮፕላን ውስጥ እያለ በኢቦላ ለሞት መዳረጉን ስትሰማ ደግሞ ስጋቱ ጨምሮባታል፡፡ በዚህም አላበቃም፡፡ በላይቤሪያ መዲና ሞንሮቪያ የህክምና እርዳታ በማድረግ ላይ የነበሩ ሌሎች ሁለት ዜጎቿ በኢቦላ ተይዘው እንደሚሰቃዩ ተረጋገጠ፡፡

እንዲህ ያለው መጥፎ ወሬ ያስደነገጣት አሜሪካ፣ በሰው አገር ያሉ ዜጎቿ ጉዳይ ቢያሳዝናትም፣ አገር ቤት ያሉት ግን እንዳይሰጉ እየመከረች ነው፡፡ ሲዲሲ የተባለው የአሜሪካ የጤና ተቋም ባለፈው ሰኞ በሰጠው መግለጫ፣ በአገሪቱ ይህ ነው የሚባል የኢቦላ ወረርሽኝ ስጋት እንደሌለ አረጋግጧል፡፡ ይህም ሆኖ ግን በሽታው አደገኛ በመሆኑ መጠንቀቅ ይበጃል ብሏል ተቋሙ፡፡ በሽታው ከተከሰተባቸው የአፍሪካ አገራት የሚመጡ መንገደኞችን ወደ አሜሪካ አለማስገባት ሁነኛ መከላከያ መላ ነው ይላሉ- የሲዲሲ ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት ዶ/ር ማርቲ ሴትሮን፡፡ በቅርቡ ከእነዚያ አገራት የመጡና የኢቦላ ምልክቶች የተሰሟቸው ሰዎችም፣ ዛሬ ነገ ሳይሉ በአፋጣኝ ወደ ህክምና መሄድ እንደሚኖርባቸው ዶክተሩ መክረዋል፡፡ በአገራቱ የሚኖሩ ዜጎችም፣ የበሽታውን መተላለፊያ መንገዶች ጠንቅቀው በመረዳት ራሳቸውን እንዲጠብቁ ተናግረዋል፡፡ የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ጸሃፊ ፍሊፕ ሃሞንድን ጠቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ሰሞኑን እንደዘገበውም፣ በመስፋፋት ላይ የሚገኘው የኢቦላ ወረርሽኝ ለእንግሊዝም ሆነ ለሌሎች የአውሮፓ አገራት ከፍተኛ ስጋት ነው፡፡

በሬዲንግ ዩኒቨርሲቲ ታዋቂ የህክምና ባለሞያ የሆኑት ዶ/ር ቤን ኒውማን በበኩላቸው፣ ኢቦላ በአገረ እንግሊዝ የመከሰት እድሉ ከፍተኛ በመሆኑ ተገቢው ጥንቃቄ እንዲደረግ ማስጠንቀቃቸውንም አስታውሷል፡፡ ጉዳዩ ያሰጋው የአውሮፓ ህብረትም፣ ወረርሽኙ ውቅያኖስ ተሻግሮ አሰቃቂ ጥፋት ሊያደርስ የማይችልበት ዕድል የለም ብሏል፡፡ የህብረቱን ከፍተኛ ባለስልጣን ሰቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ እንዳለው፣ ከሰሞኑ ስፔን ውስጥ አንድ ዜጋ በኢቦላ ተጠርጥሮ አፋጣኝ የህክምና ክትትል ተደርጎለታል፡፡ ግለሰቡ እንደተፈራው ከቫይረሱ ነጻ መሆኑ ቢረጋገጥም፣ በሌሎች የአውሮፓ አገራት የበሽታው ምልክት የሚታዩባቸው ሰዎች ቁጥር እያደገ መምጣቱንና አገራቱ ለጉዳዩ ከፍተኛ ትኩረት መስጠት እንዳለባቸው ህብረቱ መምከሩንም ዘገባው ያሳያል፡፡ ህብረቱ አባል አገራቱን ከወረርሽኙ እንዲጠነቀቁ ከማሳሰብ አልፎ፣ ወረርሽኙን ባለበት ለመግታት ችግሩ ወደ ተከሰተባቸው የአፍሪካ አገራት ከላከው 1 ነጥብ 9 ሚሊዮን ዩሮ በተጨማሪ ሁለት ሚሊዮን ዩሮ የእርዳታ ገንዘብ እንደሚልክ፣ ሃኪሞችንም ወደ አገራቱ በብዛት እንደሚያሰማራ አስታውቋል፡፡

በሽታው ኢቦላ ነውና፣ እርግጥም የመንግስታቱ ስጋት ተገቢነት ያለው ነው፡፡ ኢቦላ ምንም አይነት ክትባት ያልተገኘለትና ይህ ነው የሚባል ህክምና የሌለው ገዳይ በሽታ ነው፡፡ ብርድ ብርድ በማለትና በማንቀጥቀጥ ጀምሮ፣ የማያቋርጥ ትውከትንና ተቅማጥን በማስከተል በአፋጣኝ ለከፍተኛ ስቃይ የሚዳርገው ይህ አሰቃቂ በሽታ፣ ለህልፈተ ህይወት ሲያበቃ ጊዜ አይፈጅበትም፡፡ በዚህ ቫይረስ ከተጠቁ ታማሚዎች፣ 90 በመቶ ያህሉ መጨረሻቸው ሞት እንደሚሆን ይነገራል፡፡ የቫይረሱን የመዛመትና ሰዎችን የማጥቃቱን ፍጥነት ከፍተኛ ያደረገው ደግሞ የሚተላለፍበት መንገድ ነው፡፡ ሽንት፣ ላብ፣ ደምና አክታን የመሳሰሉ የሰውነት ፈሳሾች አማካይነት የሚደረግ የአካል ንክኪ፣ በሽታውን ከታማሚው ወደ ጤነኛው ሰው በአፋጣኝ ያስተላልፋል፡፡ ወረርሽኙ የተቀሰቀሰባቸው የምዕራብ አፍሪካ አገራት፣ በቂ የህክምና አገልግሎትና መሰረተልማት በአግባቡ ያልተሟላላቸው መሆናቸው ችግሩን የከፋ እንደሚያደርገው እየተነገረ ነው፡፡ ሲኤንኤን እንዳለው፣ ወረርሽኙ በፍጥነት በመሰራጨት የ11 የአፍሪካ አገራትን ገፈት ቀማሽ አድርጓል፡፡ መሰራጨቱንም ቀጥሏል፡፡ ዓለምም በዚህ ቀሳፊ በሽታ ስጋት ተውጣ ሰንብታለች፡፡

         የእንግሊዝ መንግስት ያለ አሽከርካሪ በራሳቸው የሚንቀሳቀሱ መኪኖች ከመጪው ጥር ወር ጀምሮ በአገሪቱ መደበኛ መንገዶች አገልግሎት ላይ እንዲውሉ መፍቀዱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ የተሻሻለ ቴክኖሎጂ ውጤት የሆኑት እነዚህ መኪኖች፣ ተሽከርካሪዎች በሚበዙባቸው መንገዶች ላይ ያለ አሽከርካሪ ራሳቸውን ችለው መጓዝ፣ ፍጥነታቸውን መመጠን፣ አመቺ አቅጣጫዎችን መምረጥና መሰል ስራዎችን መከወን የሚችሉ ናቸው ተብሏል፡፡ የሌሎችን ተሽከርካሪዎች ሁኔታ ግምት ውስጥ ባስገባና ለአደጋ በማያጋልጥ መልኩ ራሳቸውን ችለው እንደሚንቀሳቀሱ የተነገረላቸው እነዚህ መኪኖች፣ በእያንዳንዷ ሰከንድ እንቅስቃሴያቸው አቅጣጫ ጠቋሚ ቴክኖሎጂዎችንና የሳተላይት ካርታዎችን እንደሚጠቀሙ ተገልጿል፡፡

ሾፌር አልባዎቹ መኪኖች አጠቃላይ እንቅስቃሴያቸውን የሚቆጣጠር ኮምፒውተርና በሁሉም አቅጣጫ ያለውን ሁኔታ በማሳየት አካሄዳቸውን በተገቢው መንገድ እንዲያስተካክሉ የሚያግዟቸው ካሜራዎች የተገጠሙላቸው ናቸው። መኪኖቹ አገልግሎት ላይ ከመዋላቸው በፊት ባሉት ጊዜያት የሚመለከታቸው የአገሪቱ የትራንስፖርት ተቋማት በዘርፉ ይሰራባቸው የነበሩ የመንገድ ደህንነትና የተሽከርካሪ አጠቃቀም ህጎችን እነዚህን አዳዲስ ሾፌር አልባ መኪኖች ግምት ውስጥ ባስገባ መልኩ እንዲያሻሽሉ ተጠቁሟል፡፡ የአገሪቱን ኢኮኖሚና ማህበረሰብ ወደ አዲስ ምዕራፍ የማሸጋገር ዕድል ይፈጥራል የተባለው ይህ ቴክኖሎጂ ጥቅም ላይ የሚውልበትን መንገድ በተመለከተ፣ የአገሪቱ የትራንስፖርት ዘርፍ መሃንዲሶችና የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የተሳተፉበት ጥናት ሲደረግ መቆየቱንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

እንግሊዝ ለመሰል መኪኖች ፍቃድ ብትሰጥም፣ ሌሎች አገራት ግን ጉዳዩ ስጋት ውስጥ ስለከተታቸው የሙከራ ስራ ከመስራት ባለፈ መኪኖቹ በመደበኛነት አገልግሎት ላይ እንዲውሉ አለመፍቀዳቸው ተገልጧል፡፡ ቶዮታ፣ ቢኤምደብሊው፣ መርሴድስ ቤንዝ፣ ኒሳንና ጄነራል ሞተርስን የመሳሰሉ የዓለማችን ታዋቂ የመኪና አምራች ኩባንያዎች የየራሳቸውን ሾፌር አልባ መኪኖች ዲዛይን በማድረግ ለዕይታ ማብቃት ከጀመሩ አመታት መቆጠራቸውን የጠቀሰው ዘገባው፣ ይሄም ሆኖ ግን አሜሪካን ጨምሮ የተለያዩ አገር መንግስታት ከደህንነት ስጋት ጋር በተያያዘ መኪኖቹ በብዛት ተመርተው በስራ ላይ እንዳይውሉ መከልከላቸውን አስታውሷል፡፡

         ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ በስፖርቱ ላይ አዎንታዊም አሉታዊም ሚና ይኖራቸዋል፡፡ የተሻለ ለውጥ ወይም የባሰውን ውድቀት ይፈጥራሉ፡፡ በዓለም ዙርያ በርካታ ስፖርት አፍቃሪዎች እግር ኳስ በቀላል እና ተፈጥሯዊ ባህርያቱ እንዲቀጥል ቢፈልጉም፤ የስፖርቱ ባለሙያዎች በሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መታጀቡ የእድገት መገለጫ ነው ብለው ይከራከራሉ፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ የሚሰሩ በርካታ አሰልጣኞችና የእግር ኳስ ባለሙያዎች በዘንድሮው በዓለም ዋንጫው ተግባራዊ ለሆኑ ቴክኖሎጂዎች ጠቀሜታ ድጋፋቸውን እንደገለፁ፣ የሊግ አሰልጣኞች ማህበር በቅርቡ የሰራው ጥናት አረጋግጧል፡፡ በጥናቱ እንደተገለፀው ለዳኞች ውድድር የመምራት ብቃትን ለማሳደግ ተግባራዊ የሆኑት ቴክኖሎጂዎች በ20 አገራት የሚገኙ በተለይም በአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች የሚሰሩ አሰልጣኞች በእግር ኳስ ስፖርት የቴክኖሎጂ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል 93 በመቶው ድጋፍ ሰጥተዋል፡፡

በክሪኬት፤ በራግቢ እና በሜዳ ቴኒስ የስፖርት ውድድሮች ተግባራዊ የሆኑት የዳኞችን ውሳኔ አሰጣጥ የሚደግፉ ቴክኖሎጂዎች በእግር ኳስ መስፋፋታቸው ተፈላጊ ቢሆንም፣ አንዳንዶች ሳይንስና ቴክኖሎጂ የስፖርቱን መሰረታዊ ተፈጥሮ እያደበዘዘው እንዳይቀጥል ስጋት አለን ይላሉ፡፡ ጎል ላይን፣ ውሃ እና ‹ቫኒሺንግ ስፕሬይ› ቫኒሺንግ ስፕሬይ አሁን የኢንተርኔት ቴክኖሊጂ በስፖርቱ ላይ አዎንታዊ ሚና የሚኖራቸውንና የተሻለ ለውጥ በመፍጠር ለእድገት ምክንያት የሆኑ አገልግሎቶቹን እየሰጠ ይገኛል፡፡ የስፖርቱን አሃዞች አቀናብሮ በማከማቸትና በተለያያ ስሌት መረጃ እንዲሆኑ በማስቻል የኮምፒውተር ቴክኖሎጂዎች የላቀ አስተዋፅኦ እየፈጠሩ ናቸው፡፡ እያንዳንዱን ጨዋታ በዋዜማው እና ባለቀ ማግስት ለመተንተን፤ በአሃዛዊ ቁጥሮች ለማነፃፀር፤ ለመለካትእና ለማስላት ተግባራዊ የሆኑት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂዎች ዓለም ዋንጫውን ከመቼውም የላቀ አድርገውታል፡፡ የዓለም ዋንጫው የፍፃሜ ጨዋታ 360 ዲግሪ በሚሽከረከር እና ከፍተኛ የማጉላት እና የጥራት ደረጃ ባለው አልትራ ኤችዲ ኦምኒካም ካሜራ መቀረፁ ትልቅ ስኬት ተብሏል፡፡

ይህን ዘመናዊ የካሜራ ቴክኖሎጂ ያቀረበቡት የበርሊን ዩኒቨርስቲ ሳይንቲስቶች ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ሶኒ ኩባንያ ከፊፋ ጋር በመተባበር በመላው ዓለም የሚሰራጩት ምስሎች በ4ሺ ፒክስልስ የጎላ ጥራት እንዲኖራቸው አድርጎ ተሳክቶለታል፡፡ በእያንዳንዱ የዓለም ዋንጫ በቀረፃ ላይ የሚሰማሩት 34 ግዙፍ ካሜራዎች ከ5ሺ ሰዓታት በላይ ሰርተዋል፡፡ የግብ ማረጋገጫ ቴክኖሎጂውን አስፈላጊነት ፈረንሳይ 3ለ0 ኢኳዶርን ባሸነፈችበት የ20ኛው ዓለም ዋንጫ የምድብ ጨዋታ ማጋጠሙ ይታወሳል፡፡ በዚሁ ቴክኖሎጂ አፈፃፀም ላይ መላው ዓለም የታዘበው የቴክኖሎጂውን ወሳኝ ጠቀሜታ ነበር፡፡ የጎል ላይ ቴክኖሎጂን መላው ዓለም ተቀብሎታል፡- የእግር ኳስን ተፈጥሯዊ ባህርይ ሊበርዝ ይችላል የሚል ስጋት ቢኖርም፡፡ የእግር ኳስ ደጋፊዎች ዳኞች በሚሰሯቸው ስህተቶች እና ጥፋቶች መወዛገብ ለሽንፈታቸው ምክንያት መደርደራቸውን የስፖርቱን ድባብ እና ተፈጥሯዊ ባህርይ ይገልፃል በሚል በቴክኖሎጂ እንዲቀር መደረጉን ይነቅፉታል፡፡

የጎል ላይን ቴክኖሎጂ በሚቀጥሉት ዓለም ዋንጫዎች በፍፁም ቅጣት ክልል ውስጥ በሚፈፀሙ ጥፋቶች ላይ ዳኞች ሳይታለሉ የኢሊጎሬ ውሳኔ እንዲሰጡ ለማድረግ ተግባራዊ እንዲሆን ጥሪ ያቀረቡም ነበሩ፡፡ በኳስ ግጥሚያ ላይ የቴክኖሎጂዎች ትግበራ የጨዋታውን የተሟሟቀ ሂደት፤ የፉክክር ደረጃ እና ግለት የሚያበርዱ እና የሚያስተጓጉሉ ከሆኑ ቢቀር ይሻላል በሚል የተሟገቱም አሉ፡፡ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ከባዱን ሙቀት ለመከላከል ተጨዋቾች በመሃል ግጥሚያ ላይ አቋርጠው ውሃ እንዲጠጡ የሚያስገድድ ሳይንስ ነበር፡፡ ይህ ተግባር ግን ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚያመዝን ማስረጃ በመጥቀስ የተቃወሙት ጥቂት አይደሉም፡፡ በቅጣት ምት ላይ ተጨዋቾች የሚሰሩትን የመከላከያ ግድግዳ ለማስመር ዳኞች መገልገል የጀመሩት ቫኒሺንግ ስፕሬይም ብዙም ጠቀሜታው ያልጎላ ነው፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ በሜዳ ላይ የጨዋታን ግለት የሚያበርድ ከመሆኑም በላይ በዳኛው ላይ አላግባብ ጥቃት እንዲፈፀም የሚያግዝ መሳርያ ነው በሚልም ነቅፈውታል፡፡ ይሁንና ቫኒሺንግ ስፕሬይ ቅጣት ምቶች ያለአንዳች ግርግር እንዲመቱ ሁኔታዎችን በማመቻቸቱ የሚያደንቁት አልጠፉም፡፡ ቴክኖሎጂ - ከ‹ማልያ› እስከ ‹ታኬታ› በዓለም ዋንጫው ማልያዎች፤ ሙሉ የስፖርት ትጥቆች የመጫወቻ ታኬታዎች አቅራቢ የሆኑት ሶስቱ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች አዲዳስ፣ ናይኪና ፑማ ዘንድሮ ለየብሄራዊ ቡድኖቹ ያቀረቧቸው ማልያዎች በከፍተኛ ቴክኖሎጂ የተመረቱ ናቸው፡፡

ማልያዎቹ ለከፍተኛ ደረጃ በበለፀጉ እና ሪሳይክልድ በሚሆኑ ‹‹ፖሊቲክ ፋይበርስ›› የተሰሩ፤ ተለብሰው የማያስጨንቁ፤ አየር ማስገቢያ ያላቸው፣ እንደ ቆዳ ልጥፍ ያሉ እና ቅለት ያላቸው፣ ጡንቻዎችን እንደተፈለገ ለማዘዝ የተመቹ፣ ከልክ ያለፈ ሙቀትን ለመከላከል የሚያስችሉ ናቸው፡፡ እነዚህ ብቃቶቻቸው በከፍተኛ ሳይንሳዊ ምርምርና ቴክኖሎጂ የተዘሰራላቸው ናቸው፡፡ዓለም አቀፍ የትጥቅ አቅራቢ ኩባንያዎቹ ለዓለም ዋንጫው ያቀረቧቸው ማልያዎች ርጥበት እና ላብ የሚችሉ፤ ለአተነፋፈስ የማያስቸግሩ፤ ክብደት የሌላቸው እና እንደልብ ተቀላጥፎ ለመጫወት የሚመቹ ናቸው፡፡ ናይኪ በአልባሳት የስፖርት ትጥቆቹ በርካታ የባዮ ሜካኒካል ምርምሮችን አድርጓል፡፡ አዲዳስ ደግሞ ባቀረባቸው የብሄራዊ ቡድን ማልያዎች የተጨዋቾች ስም፤ መለያቁጥር እና ልዩ ልዩ አርማዎች ከመለጠፍ ይልቅ፣ ከማልያው ጋር ተዋህደው እንዲሰሩ አድርጓል፡፡ የመጫወቻ ታኬታዎችም በቴክኖሎጂ ረቀቅ ብለው በመሰራታቸው በተለያዩ ደማቅና ሳቢ ቀለማት በጥናት እና በምክንያት ተመርተው አሽብርቀዋል፡፡ አንዳንዶቹ በክብደታቸው ቀለል ተደርገዋል፡፡

አንዳንዶቹ እንደቡትስ በቁርጭምጭሚት ላይ ሊደርስ የሚችልን ጉዳት የሚከላከል ተቀጥሎባቸዋል፡፡ በዓለም ዋንጫው በተሳተፉ 32 ብሄራዊ ቡድኖች እስከ ስምንት ትጥቅ አቅራቢዎች ቢኖሩም በቴክኖሎጂያቸው ተራቅቀው እና ገበያውን ተቆጣጥረው ያሉት ዋናዎቹ አዲዳስ እና ናይኪ ናቸው፡፡ ፑማ በቅርበት ይከተላቸዋል፡፡ ሁለቱ ኩባንያዎች ገበያውን ለመቆጣጠር የሚያደርጉት ትንቅንቅ በቴክኖሎጂ የተሻለ ሆኖ መገኘትን በማቀድ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ በእግር ኳሱ ላይ በየዓለም ዋንጫው አዳዲስ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂን በማፈራረቅ ተፅእኖ መፍጠሩ የማይቀር ይመስላል፡፡ ብራዙካ የተባለችው የአዲዳስ ኳስ ውድድሩ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ምንም አይነት ቅሬታ ስላልቀረበባትም አዲዳስን ገበያውን እንዲቆጣጠር ያስችለዋል፡፡ አዲዜሮ ኤፍ50 የተባለው የአዲዳስ ታኬታ ባደረጉ ተጨዋቾች በዓለም ዋንጫው ከገቡት 171 ጎሎች 41 በመቆጠራቸውም የምርቱን ስኬታማነት መለኪያ ሆኗል፡፡ በናይኪ ሜርኩርያል ቡት የተመዘገቡት 35 ጎሎች ናቸው፡፡ አዲዳስ ብራንድ የሆኑ ታኬታዎች 74 የናይኪ ብራንድ የሆኑ ታኬታዎች 73 ጎሎች ተቆጥሮባቸዋል፡፡ በሁለቱ ኩባንያዎች የቀረቡ ታኬታዎች በአንፀባራቂ እና ደማቅ ቀለማት መሰራታቸው ጠቃሚ ነው በሚል ኮሜንታተሮች አመስግነዋል፡፡ የታኬታዎቹ ቀለማት የተጨዋቾችን ማንነት ለመለየት ያግዛል በሚል ተደንቋል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች ታኬታዎቹ ቡትስ መምሰላቸውን ያልወደዱት ሲሆን ከቦክስ ጓንቲዎች ጋር አመሳስለዋቸዋል፡፡

         አንዳንድ ዘገባዎች በሚቀጥሉት 20 ዓመታት በዓለም እግር ኳስ ስፖርት የሮቦት ዳኞች እና የሮቦት ተጨዋቾች ማሰለፍ የሚቻልበት የስልጣኔ ደረጃ ይመጣል ይላሉ፡፡ ምናልባትም የቴክኖሎጂ ድጋፍ አስፈላጊነቱ ከታመነበት ፊፋ የተርመጠመጠበትን የሙስና ችግር የሚያጋልጥ ቴክኖሎጂ ቢፈለሰፍ ብለው የማጣጣያ ትችት ያቀረቡ መረጃዎች፤ በሚቀጥሉት ሃምሳ ዓመታት ዓለም ዋንጫ በጨረቃ ላይ ሊስተናገድ ይችላል ብለው አሹፈዋል፡፡ኤችቲቢ ኤንድ ፊልቸር ቦነስ የተባለ ተቋም የዓለማችን የእግር ኳስ ስፖርት የወደፊት አቅጣጫዎች ብሎ በሰራው ምርምር ይፋ እንዳደረገው በሚቀጥሉት 50 ዓመታት ስፖርቱ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ከፍተኛ ለውጦች ማሳየቱ የማይቀር ይመስላል፡፡ ብዙዎቹ ቴክኖሎጂዎች እስከ 2022 እ.ኤ.አ ተግባራዊ ሊሆኑ እንደሚችሉም ድምዳሜ ላይ ደርሷል፡፡

እንደተቋሙ ሪፖርት ከሆነ በሚቀጥሉት 15 ዓመታት በእግር ስፖርት በተጨዋቾች ማልያ ላይ ማንኛውንም እንቅስቃሴ ለመቅረጽ የሚችሉ በዓይን የማይታዩ ካሜራዎች ይለጠፋሉ፤ የመጫወቻ ታኬታዎች ኳስን ለመቆጣጠር መጥኖ ለመምታትና አቅጣጫ ለመገመት የሚያስችሉ ይሆናል፤ የውድድር ዳኞች ማናቸውን የጨዋታ እንቅስቃሴ ለመበታተን እንዳይገባቸው ልዩ የካሜራ ሄልሜት ሊገጠምላቸውም ይችላል፡፡ ከስምንት ዓመታት በኋላ ኳታር በምታስተናግደው 22ኛው ዓለም ዋንጫ ዙርያ ከተነሱ አከራካሪ ጉዳዮች ዋንኛው የአገሪቱ ሙቀት ለውድድሩ አይመችም የሚለው ነው፡፡ የኳታር ዓለም ዋንጫ አዘጋጆች ግን ይህ ችግር በቴክኖሎጂ የሚፈታ ነው ብለው ተከራክረዋል፡፡

እስከ 45 ዲግሪ ሴንቲግሬድ የሚደርሰው የኳታር ሙቀት በስታድዬሞች በሚገጣጠሙ እና በሚሰሩ የማቀዝቀዣ ምሰሶዎች ለእግር ኳስ ጨዋታ የተመቹ እናደርጋቸዋለን በሚል ከወዲሁ ቃል ገብተዋል፡፡ ሰሞኑንም እስከ 7.4 ሚሊዮን ዶላር የወጣበትን የማቀዝቀዣ ቴክኖሎጂን የፈተሹበት የሙከራ ተግባራትን አከናውነዋል፡፡ በርካታ ተመራማሪዎች እና ሳይንቲስቶች እግር ኳስ ከቴክኖሎጂ ጋር ተሳስሮ መቀጠሉን በመደገፍ የተለያዩ አዳዲስ ሃሳቦችን በማፍለቅ ላይ ናቸው፡፡ በሚቀጥሉት ዓለም ዋንጫዎች ተግባራዊ ቢሆኑ ተብለው ሃሳብ ከተሰጠባቸው የቴክኖሎጂ ግኝቶች የመጀመርያው ኦፍሳይድ እና ኦንሳይድ የሆኑ ኳሶችን ለመለየት እንደ ግብ ማረጋገጫ ቴክኖሎጂ አዲስ አሰራር መፈልሰፉን የጠየቁ ናቸው፡፡ ሌላው ተጨዋቾች በተጋጣሚያቸው ፋውል ሲሰራባቸው በትክክል መሰራረቱን ወይም ለማታለል መወደቁን ለማረጋገጥ የሚያስችል መሳርያም ቢኖር ተመኝተዋል፡፡ በራግቢ እና በአሜሪካን ፉትቦል ተግባራዊ የተደረገውና የሜዳ ላይ ትዕይንት በቀጥታ ተመልካች በቅርበት እየሰማ እንዲከታተል የታቀደው የቀረፃ ቴክኖሎጂም አለ፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ በተጨዋቾች ማልያዎች ላይ በሚለጠፉ ልዩ ካሜራዎች ወይንም ደግሞ በነፍሳት መልክ በሚሰሩ እና ኳስ ጨዋታውን በመካተል በሚቀርፁ ልዩ ካሜራዎች ይህን ተግባር ለማከናወን እንደሚቻልም ይገለፃል፡፡