Administrator

Administrator

ሰሞኑን በእጅጉ ማርኮኝ የተመለከትኩት “Trance” የተሰኘ ፊልም ላይ፣ ዋና ገፀ-ባህሪው ሳይመን ሳያውቀው የገባበት የቁማር ጨዋታ (gambling) የለየለት ሱሰኛ ያደርገውና የዕዳ አረንቋ ውስጥ ይዘፈቃል፡፡ ከቁማር ሱሰኝነቱ ለመላቀቅ የዘየደው መላ ወደ ቴራፒስት ዘንድ መሄድ ነው፡፡ በሂፕኖቴራፒ ከቁማርተኝነቱ ለመፈወስ፡፡ ሂፕኖሲስ የህክምናው (ቴራፒው) ሂደት ሲሆን ባለሙያው ወይም ባለሙያዋ ሂፕኖቲስት ይባላሉ፡፡ ቴራፒውን የወሰደው ሰው ደግሞ “ሂፕኖታይዝድ” ሆኗል ይባላል፡፡
በነገራችሁ ላይ ሂፕኖሲስ ታካሚውን በሰመመን ስሜት ውስጥ በማስገባት፣ ሃሳቡንና ትኩረቱን በአንድ የሆነ ጉዳይ ላይ እንዲያነጣጥር፣ የተወሰኑ ቃላትን ወይም ዓ.ነገሮችን በመደጋገም አሊያም የአዕምሮ ምስል በመፍጠር… የሚሰጥ ህክምና (ቴራፒ) ነው፡፡ ሂፕኖሲስ ያልተፈለገ ባህሪን (ድርጊትን) ለማስወገድ ወይም ለመቆ›ጣጠር በቁጥጥር ሥር ለማዋል ጥቅም ላይ ሊውል ይችላል፡፡ ከሲጋራ ሱሰኝነት ለመላቀቅ፣ ከእንቅልፍ እጦት (Insomnia) ለመገላገል፣ ከመጠን በላይ የመብላት ፍላጐትን ለማስወገድ …ወዘተ ሊያግዝ እንደሚችል ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
ወደ ፊልሙ ልመልሳችሁ፡፡ በቁማር ሱሰኝነት ኑሮው የተቃወሰው ሳይመን፤ ኤልዛቤት ላምብ የተባለች ቴራፒስት ዘንድ በመሄድ ችግሩን ተናግሮ ቴራፒውን ይጀምራል፡፡ የቁማር ሱሰኝነቱ ስር የሰደደ በመሆኑ ብዙ ጊዜ እንደሚወስድበት ይገለጽለትና ህክምናውን ይቀጥላል፡፡ በዚህ ሂደትም ከኤልዛቤት ጋር እየተቀራረበ ይመጣል፡፡ የጦፈ የፍቅር ግንኙነትም ይጀምራል፡፡
ቴራፒስቷ ከደንበኞቿ ጋር እንዲህ ያለ ግንኙነት ውስጥ መግባት እንደሌለባት ታውቃለች፡፡ ግን አንዴ ሆነ፡፡ እናም “የፈሰሰ ውሃ አይታፈስም” ብላ ገፋችበት። ከጥቂት ጊዜ በኋላ የሳይመን ፍቅር ወደ ጥርጣሬና ቅናት እየተቀየረ መጣ፡፡ የት ገባሽ፣ የት ወጣሽ ማለት አበዛ፡፡ ፍቅረኛውን የሚያጣት፣ እየመሰለው ይጨነቅ ጀመር፡፡ ቅናቱ እየተባባሰ እንደ እብደት አደረገው፡፡ መላ ህይወቱን እሷ ላይ ጣለ፡፡ ከእሷ ከተለየ የሚሞት ሁሉ መሰለው፡፡ በዚህ የተነሳም ያፈቀራትን ያህል ጠላት፡፡ አንድ ቀን ሬስቶራንት ውስጥ ተቀምጠው ሳለ “ወንድ አየሽ” ብሎ በጥፊ አጠናገራት፡፡ ይሄን ጊዜ ነው ኤልዛቤት ከዚህ ጨዋታ መውጣት እንዳለባት የወሰነችው፡፡ ግን በየት በኩል? ሳይመን አለቅም ብሎ ሙጭጭ አለባት፡፡ ረዥም የይቅርታ ደብዳቤ ፃፈላት። እየደወለ ነዘነዛት፡፡ እያለቀሰ ተማፀናት፡፡ ኤልዛቤት ግን የዚህ መጨረሻ ምን እንደሚሆን አላጣችውም፡፡ ነገርዬው በዚህ ከቀጠለ የማታ ማታ እንደሚገድላት ቅንጣት አልተጠራጠረችም፡፡
ጉዳዩን ለፖሊስ ብታመለክትም ነገሬ ሳይሏት ቀሩ፡፡ ጠበቆች፤ ስሟን ቀይራ አገር ጥላ እንድትወጣ መከሯት፡፡ እሷ ደግሞ ይሄን ለማድረግ ፈቃደኛ አልነበረችም፡፡ ሁለት ጊዜ ተጎጂ መሆንን አልፈቀደችም፡፡ እናም ጉዳዩን በቁጥጥሯ ሥር ለማዋል መረጠች፡፡
ሳይመንን ከቁማር ሱሰኝነት ለመገላገል ወይም ቁማር ለማስረሳት ስትጠቀምበት የቆየችውን ቴራፒ ለዚህ ዓላማ አዋለችው፡፡ “መርሳት የምትፈልገው ቁማሩን ሳይሆን እኔን ነው” በማለት እርሷን እንዲረሳት ተከታታይ ቴራፒ ሰጠችው፡፡ ቀስ በቀስም እሷን እየረሳ መጣ፡፡ እሷን ብቻ ሳይሆን የፍቅር ግንኙነታቸውንም ጭምር ረሳው፡፡ ሁሉ ነገር ከአዕምሮ ትውስታው እልም ብሎ ጠፋ፡፡ የቁማር ሱሱን ሊረሳ ሄዶ ፍቅሩን ረስቶ ተመለሰ፡፡
አንዳንድ በፀብና በቅናት የተሞሉ አደገኛ የፍቅር ግንኙነቶች እንዲህ “ዲሊት” እየተደረጉ ከትውስታ ማህደር ቢጠፉ ብዙ ጥንዶችን ከከፋ ችግር ሊታደጉ ይችላሉ፡፡ በእርግጥ ወደ ፊልሙ መጨረሻ አካባቢ የሳይመን ትውስታ ይመለሳል፡፡ “ለምን እንድረሳ አደረግሽኝ?” ብሎ የቀድሞ ፍቅረኛውን ይጠይቃታል፡፡ ኤልዛቤትም “ትውስታህ በሰረገላ ቁልፍ ተከረቸመ እንጂ ከጥቅም ውጭ አልሆነም” ስትል ትመልስለታለች፡፡
ኤልዛቤት በሂፕኖቴራፒ ክህሎቷ ራሷን ከሞት፣ የቀድሞ ፍቅረኛዋን ደግሞ ከዕድሜ ልክ እስርና ፀፀት ለማትረፍ ችላለች፡፡ ይሄን ፊልም ተመልክቼ ስጨርስ ወደ አዕምሮዬ የመጣው፣ በሃይልና በዱላ የታጀበው የአገራችን የፍቅር ግንኙነት ነው፡፡ በበዛ ቅናት እየተሰቃየ ሚስቱን ለሚደበድብ ባል፤ ይሄ ቴራፒ ግሩም ይመስለኛል፡፡ ፍቅረኛውን ከእነ ትዝታዋ በማስረሳት አዲስ ህይወት እንዲመራ ለማድረግ ይረዳል፡፡
በሂፕኖቴራፒ ሰዎች እንዲረሱ ብቻ ሳይሆን የረሱትንም እንዲያስታውሱ (ትውስታቸው እንዲመለስ) ማድረግ ይቻላል፡፡ ሳይመን ጭንቅላቱ ላይ ጉዳት ከደረሰበት በኋላ ያስቀመጠበት የጠፋበትን የመኪና ቁልፍ በሂፕኖሲስ እንዲያስታውስ አድርጋዋለች - ቴራፒስቷ ኤልዛቤት፡፡ ዓምና ለእይታ የበቃውን “Trance” የተሰኘ ፊልም ፈልጋችሁ ተመልከቱት፡፡ ድንቅ ፊልም ነው!! (በነገራችሁ ላይ እኔ የተረኩት ከሙሉ ፊልሙ እጅግ ጥቂቱን ብቻ ነው)

ከ“አነስተኛና ጥቃቅን” ተነስቶ፤ ዛሬ የአለማችን ባለ ሃብት ሆኗል!
እንደ ቻይና ወጣቶች በቢል ጌትስ የቢዝነስ አርአያነት ለብልጽግና እንጥራለን?
ወይስ እንደ ለማኝ በቢል ጌትስ ምጽዋት ተማምነን እጅ እንስማለን?

“የአገሬ ሰውና የአገሬ መንግስት ይመሳሰላሉ፤ ራሳቸውን ጠልፈው መጣል ይቀናቸዋል” በሚል ርዕስ ባለፈው ሳምንት በአዲስ አድማስ የወጣው ጽሑፍ፤ በአንድ ሃሳብ ላይ የሚያጠነጥን ነበር። ስለ እድገትና ብልጽግና እናወራለን፡፡ ጥሩ ነገር መመኘት በጐ ነው፡፡ ነገር ግን ምኞታችንን እውን እንዳናደርግ፤ ራሳችንን ጠልፈን እንጥላለን ይላል ጽሑፉ፡፡ እንዴት?
ብልጽግናን፣ ቢዝነስን፣ ስኬታማንና ትርፋማነትን ከማክበር ይልቅ “የዚህ አለምን ህይወት” እየናቅን፤ መመነንን፣ ችግር መካፈልን፣ ምጽዋትን፣ ምስኪንነትንና መስዋዕትነትን እናመልካለን፡፡
በአንድ በኩል ብልጽግናን ብንመኝም፤ በሌላ በኩል ሁለመናችንን በፀረ ብልጽግና ሃሳቦችና ባህሎች ተብትበን አስረነዋል፡፡ እንዲህ ራሳችንን ጠልፈን የመጣል አባዜ እንደተጠናወተን የሚገልፀው ጽሑፍ፤ በርካታ ሰሞነኛ ዜናዎችን በማስረጃነት ያቀርባል፡፡ ይህ የምዕተ ዓመታት “በሽታ” ምንኛ ስር የሰደደና በሰፊው የተንሰራፋ እንደሆነም በዝርዝር ያስረዳል፡፡ እውነትም የባህል እና የአስተሳሰብ “በሽታ” ተጠናውቶናል፡፡ ሃሙስ እለት በቢል ጌትስ “የክብር ዶክትሬት” ሽልማት ላይም በግላጭ አየሁት - “የቢዝነስ ስኬትህን ሳይሆን የምጽዋት እጅህን እናደንቃለን” ብለን ሸለምነው፡፡
ይሄ ነው ዋናው በሽታችን - ለኋላቀርነትና ለድህነት የዳረገን ነባር በሽታ! በእርግጥ አንዳንድ ሰዎች በሽልማቱ ዙሪያ ሌላ ሌላ ቅሬታ ሲያነሱ ሰምቻለሁ፡፡ ለምሳሌ፤ የስራ ባልደረባው በማኔጅመንት መስክ ትምህርቱን ተከታትሎና ጥናት አካሂዶ በዶክትሬት ዲግሪ እንደሚመረቅ የገለፀልኝ አንድ ባለሙያ፤ የዚህኛው ዶክትሬት “የክብር ዶክትሬት” አይደለም ወይ? ሲል ጠይቋል። በእርግጥም የትምህርት ተቋም ውስጥ ገብቶ፤ በዶክትሬት ዲግሪ መመረቅ…ማለትም በማንኛውም መስክ የእውቀትና የክህሎት፣ የአቅምና የብቃት ባለቤት ወይም ጌታ መሆን፣ ትልቅ “ክብር” ነው፡፡
በዚያው መጠን፤ ከትምህርት ተቋም ውጭም፤ ብቃቱን ተጠቅሞ የስኬትና የሃብት ባለቤት (ጌታ) ለመሆን የቻለም፤ ክብር ይገባዋል፡፡ ደግሞስ ሌላ ምን የክብር ምንጭ አለ? የአንዳች ጠቃሚ ነገር ባለቤት፣ ጌታ ከመሆን ውጭ ሌላ የክብር ምንጭ የለም፡፡ ከሺ ዓመታት በፊት በስልጣኔ ጐዳና ሲራመዱ የነበሩት ኢትዮጵያውያን፣ ይህ እውነት ገብቷቸው ነበር፡፡ “ባለ” ወይም “በዓለ” የሚሉ ቃላት በመጠቀም ነበር አክብሮትና አድናቆታቸውን የሚገልፁት - ዛሬ “ባለ ሀብት” እንደምንለው፡፡
“ባለ” ወይም “በዓለ”… የአንዳች ነገር ባለቤት ወይም ጌታ መሆንን - ያስገነዝባል፡፡ ከዚህም ጋር ክብርና አድናቆትን ይገልፃል፡፡ በዓል ማለት ጌትነትና ባለቤት ነው፤ ክብር እና ሞገስም ነው፡፡ ለአማልክት እና ለጀግኖች፤ “በዓል” የሚል የማዕረግ መጠሪያ ይጠቀሙ ነበር፡፡ ባለነበል (ነበል -ባል)፤ የእሳት ጌታ ነው እንደማለት፡፡ ባለሀብት፣ ባለአገር፣ ባለአምባ ወዘተ… ብቃትና ባለቤትነትን፣ ከጀግንነትና ከክብር ጋር አጣምረው ነበር የሚያስቡት፡፡ ቅዱስ ሲሉ ጀግና ማለታቸው ነበር፡፡
ከጊዜ በኋላ የስልጣኔ አስተሳሰብ ሲጠፋ የስልጣኔ ጉዞውም ተረሳ፡፡ “የዚህ አለም ነገር” ሁሉ ከንቱ ነው ተባለ፡፡ የእውቀትም ሆነ የብቃት፣ የስኬትም ሆነ የሃብት ባለቤትነት ተናቀ፡፡ ክብርም አጣ፡፡ በዚያው መጠን ድንቁርናና ምስኪንነት፣ ውድቀትና ድህነት የሚወደስበት ኋላቀር ባህል ወረስን፡፡ እናም፤ ስልጣኔንና ብልጽግናን የምንፈልግ ከሆነ፤ በትምህርት ተቋምም ሆነ በሌላው የህይወት አለም የብቃትና የስኬት ባለቤትነትን ማክበር ይገባል፡፡ ለቢል ጌትስ የተዘጋጀው “የክብር ዶክትሬት” በዓይነቱ በአፍሪካ የመጀመሪያው ነው መባሉ ያልተዋጠላቸው ሰዎች በበኩላቸው፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ብቻ ሳይሆን መንግስት ጭምር የገባበት ጉዳይ መሆኑ እንደ ትልቅ ነገር መቆጠር የለበትም ብለዋል፡፡
ለተራ ነገርና ለቁም ነገር፣ ለትንሹም ለትልቁም… እንዲያው በዘፈቀደ “በአፍሪካ የመጀመሪያው…” እየተባለ ሲነገር መስማት ሊያስጠላ ይችላል፡፡ የአዲስ አበባ አስተዳደር፤ የጐዳና ቆሻሻ የሚያፀዱ መኪኖችን እንደሚገዛ የገለፀ ሰሞን፤ “በአፍሪካ ደረጃ በሁለተኝነት የሚጠቀስ” ማለቱን ታስታውሱ ይሆናል፡፡
እንግዲህ ነገሩን ስታስቡት፤ “በአፍሪካ የመጀመርያው፣ በአፍሪካ ሁለተኛው…” የሚያስብል ጉዳይ አይደለም፡፡ በዚያ ላይ ደግሞ መረጃው እውነት ነው፡፡ ከ20 ዓመታት በፊት እዚሁ አገራችን ውስጥ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የጐዳና ማጽጃ መኪና ይጠቀም ነበር፡፡ በበርካታ የአፍሪካ አገራትም እንዲሁ ከአመታት በፊት ተጀምሯል፡፡ ይህንን መረጃ ለማግኘት፤ በኢንተርኔት አንድ ሁለት ደቂቃ ድረገፆችን ገለጥለጥ ማድረግ ይበቃል፡፡ ዛሬ‘ኮ …ክብር ለነ ቢል ጌትስ ይድረሳቸውና፤ ጀግኖቹ የቴክኖሎጂና የቢዝነስ ሰዎች በየበኩላቸው በተቀዳጁት የጥረት ስኬት አማካኝነት፤ እንደ “ተዓምር” በሚያስደንቅ ሁኔታ በቀላሉ ብዙ ብዙ መረጃ ማግኘት የምንችል ሰዎች ሆነናል፡፡ የብቃት ባለቤት አድርገውናል - የብቃት ባለቤት የሆኑ ጀግኖች፡፡
ለማንኛውም ለቢል ጌትስ የተሰጠ የክብር ዶክትሬት…”በዩኒቨርስቲ ብቻ ሳይሆን በመንግስትም ጭምር የተዘጋጀ ስለሆነ ከአፍሪካ የመጀመሪያው ነው” መባሉ ብዙም ትርጉም የለውም፡፡ “ከአፍሪካ የመጀመሪያው” የሚል ተቀጥላ ሳያስፈልገው፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ መንግስት ለቢል ጌትስ ክብር እና አድናቆቱን ገለፀ ቢባል በቂ ነው፡፡ እንዲያውም “ትልቅ ቁም ነገር” ሊሆን ይችል ነበር፡፡ ለምን በሉ፡፡
ብዙዎቻችን ብልጽግናን እየተመኘን የስኬትን ወሬ ማዘውተር ጀምረን የለ? በጐ ጅምር ነው። መንግስትም እንዲሁ ስለ እድገትና ብልጽግና እየደጋገመ ማውራቱ መልካም ነው፡፡ “ዋናው ጠላታችን ድህነት ነው” በሚል አባባል የሚታጀበው የመንግስት ንግግር፤ የአገሪቱ የወደፊት ተስፋ ያለው “ሃብት ፈጣሪ የኢንዱስትሪ ቢዝነስ” ላይ እንደሆነ ይገልፃል፡፡
ሃብት ፈጣሪ የኢንዱስትሪ ቢዝነስ የሚስፋፋው እንዴት ነው? ብላችሁ ጠይቁት፡፡ ምላሽ ይሰጣችኋል፡፡ የመንግስት የኢኮኖሚ ፖሊሲ፣ የኢንዱስትሪ ፖሊሲ፣ የአምስት አመት የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ፣ አመታዊ የኢኮኖሚ ሪፖርት…እና ሌሎች ሰነዶችን ስትመለከቱ፤ ተመሳሳይ ምላሽ ታገኛላችሁ፡፡
ከድህነት በመላቀቅ ብልጽግናን እውን የምናደርገው፤ ሃብት ፈጣሪ የቢዝነስ ሰዎች ሲበራከቱ ብቻ እንደሆነ የሚገልፀው መንግስት፤ የተማሩ ወጣቶች በሥራ ፈጣሪነት በአነስተኛና ጥቃቅን የቢዝነስ መስክ እየተሰማሩ ስኬታማ ሲሆኑ፤ ትልልቅ የኢንዱስትሪ ቢዝነስ እንደሚስፋፋ ያስረዳል፡፡ በዚህም ምክንያት “የኢንተርፕርነርሺፕ አስተሳሰብ፣ እውቀትና ክህሎት” ቀዳሚ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል” ሲልም በሰነዶቹ ይገልፃል - ለአገሪቱ የብልጽግና ተስፋ ቁልፍ ጉዳይ መሆኑን በመጥቀስ፡፡ በአጭሩ፤ ከችጋር ሳንላቀቅ በህይወት ለመቆየት ብቻ የምንፈልግ ከሆነ እርዳታና ምጽዋት ላይ ማተኮር እንችላለን፡፡ ድህነትን ወዲያ አሽቀንጥረን ወደ ብልጽግና ለመንደርደር ከፈለግን ግን፤ በአነስተኛና ጥቃቅን ቢዝነስ ላይ ተሰማርተው ለብልጽግና የሚጣጣሩ ሚሊዮን ወጣቶች፣ ስኬታማ ሃብት ፈጣሪዎች፣ ትርፋማ የቢዝነስ ሰዎች ያስፈልጉናል ይላል መንግስት፡፡
ታዲያ ሃብት ፈጣሪ ይሆናሉ ተብለው ለሚጠበቁ ለእነዚህ ወጣቶች፣ ከእነቢል ጌትስ የበለጠ አርአያና ጀግና ከወዴት ይገኛል? እንደ አብዛኛው አነስተኛና ጥቃቅን ተቋም፤ ቢል ጌትስ ከቤተሰቦቹ መኖሪያ ቤት ስር፣ ጠባብ ምድር ቤት ውስጥ ነው ቢዝነሱን የጀመረው፡፡ በአካባቢው ለሚገኙ ትናንሽ ድርጅቶች አነስተኛ አገልግሎቶችንና የቴክኖሎጂ መፍትሔዎችን በመስጠት የተጀመረው የቢል ጌትስ ቢዝነስ፤ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣው፤ ቀን ከሌት በየእለቱ ለ16 ሰዓታት ያህል ተግቶ ስለጣረ ነው፡፡
በሰፈርና በከተማ ታጥሮ አልቀረም፡፡ በአገር ደረጃ ብቻ ሳይሆን በአለም ዙሪያ፤ የሰው ልጆችን ሕይወት የሚያሻሽሉ ቴክኖሎጂዎችን በመፍጠር የአለማችን ቁንጮ ሃብታም ለመሆን በቅቷል። በስኬታማነቱና በጀግንነቱ የተነቃቁ እልፍ ወጣቶችም፤ በየራሳቸው መስክ ተዓምር የሚያሰኝ የሃብት መጠን እንዲፈጥሩ አርአያ ሆኗቸዋል- በአሜሪካ ብቻ አይደለም፡፡ በቻይናም ጭምር እንጂ፡፡ ሃብትን እንደ ኩነኔ፣ በሚቆጥር ጥንታዊ ባህልና ባለሀብትነትን እንደ ወንጀል በሚቆጥር የሶሻሊዝም አስተሳሰብ ለድህነትና ለረሃብ ተዳርጋ የነበረችው ቻይና፤ “ባለሀብትነት ቅዱስነት ነው” በሚል ሃሳብ ነው የብልጽግና ጉዞ የጀመረችው፡፡ በእርግጥም ባለፉት 20 ዓመታት የቻይና ወጣቶች በአድናቆት ከሚጠቅሷቸው ጀግኖች መካከል፣ ቢል ጌትስ ተጠቃሽ መሆኑ አይገርምም፡፡ እኛም ብልጽግናን ከምር የምናከብር ከሆነ የቢዝነስ ስኬታማነቱ ትልቅ ቁምነገር መሆኑን በመገንዘብ፣ አክብሮትና አድናቆታችንን ለመግለጽ፣ የክብር ዶክትሬት ብንሰጠው መልካም ነበር፡፡ በእርግጥ ቢል ጌትስ ለኢትዮጵያ ብዙ የገንዘብ እርዳታ ሰጥቷል፡፡ ማመስገን ይገባል፡፡
ነገር ግን እርዳታና ምጽዋት፤ ለጊዜው ድህነትን ለመቋቋም ይጠቅም እንደሆነ እንጂ ለብልጽግና አያበቃም፡፡ የላቀ ክብር እና አድናቆት መስጠት ያለብን ለቢዝነስ ስኬታማነትና ለሃብት ፈጣሪነት ነው - ብልጽግናን የምናከብር ከሆነ፡፡ አሳዛኙ ነገር፤ ከእርዳታና ከተመጽዋችነት በተቃራኒ፣ የቢዝነስ ስኬትና ሃብት ፈጠራ ዋና የአገሪቱ የብልጽግና ተስፋዎች ናቸው የሚል መንግስት፤ ለቢል ጌትስ የክብር ዶክትሬት የምንሰጠው በሃብት ፈጣሪነቱና በቢዝነስ ስኬታማነቱ ሳይሆን በእርዳታ ለጋሽነቱ ነው ማለቱ ነው፡፡ ቢያንስ ቢያንስ፤ “ባለ ሃብትነቱንና ስኬታማነቱን እናከብራለን፤ እናደንቃለን፡፡ የዛሬው ሽልማት ግን ለሰጠን እርዳታ ምስጋናችንን የምንገልጽበት ነው” ብሎ መናገር ይቻል ነበር፡፡ ይሄም ይቅር፡፡ ግን፤ እርዳታ ለመስጠት የቻለው‘ኮ፤ በቢዝነስ ስኬታማነቱ ሃብት የፈጠረ ጀግና ስለሆነ ነው፡፡ ሃብት መፍጠር እንጂ ሃብት መስጠትማ ቀላል ነው፡፡ አርአያ አያስፈልገውም፡፡  

ባለፈው ሳምንት በጎንደር የቅማንቶች መብት ተሟጋች ከሆኑት ከአቶ ነጋ ጌጤ ጋር ባደረግነው ቃለ-ምልልስ “ጎንደር የቅማንቶች ናት” በማለት ሰፊ ማብራሪያ መስጠታቸው ይታወሳል፡፡ ዛሬ ደግሞ የታሪክ ተመራማሪው አቶ ሲሳይ ሳህሌ በጎንደር ታሪክና ሥልጣኔ ዙሪያ የሰጡንን ማብራሪያ እናቀርባለን፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ ቃለ-ምልልስ ያደረገላቸው የታሪክ ተመራማሪ፣ የፈረንሳይ ከተማ “ቬንሰንት - ጎንደር ያልተማከለ የትብብር ስምምነት የራስ ግንብ ሙዚየም ፕሮጀክት አስተባባሪም ናቸው፡፡

 ጎንደር እንዴት ተመሰረተች?
በ1623 ሰኔ ወር ላይ አፄ ሱንስዮስ ለልጃቸው ለአፄ ፋሲል በህይወት እያሉ ስልጣናቸውን ያስተላልፋሉ፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት ሜንዴዝ የሚባል የካቶሊክ ሚሽነሪ መጥቶ ነበር፡፡ አዘዞ (አሁን አፄ ቴዎድሮስ ኤርፖርት ያለበት ቦታ)፣ ጎርጎራ እና ደንቀዝ የሚባሉ ቦታዎች ሶስት የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያኖች ተሰርተው ነበር፡፡ ደንቀዝ ላይ ያለው እንደ ቤተመንግስትም ያገለግል ነበር፡፡ አፄ ሱስንዮስ ስልጣናቸውን አስተላልፈው ያረፉትም በዚሁ የካቶሊክ ደብር ውስጥ ሆነው ነው፡፡ ከዚያ በኋላ አፄ ፋሲለደስ የህዝቡን ፍቃድ ለማሟላት ኢየሱሳውያኑን ከሃገር አባረሩ፡፡ ስልጣናቸውን ተቀብለው አፄ ከተባሉ ከ4 ዓመታት በኋላ አሁን ቤተመንግስታቸው ከሚገኝበት ቦታ መጥተው የዛሬዋን ጎንደር ሊመሰርቱ ችለዋል፡፡
ለምን ወደ ጎንደር መምጣት አስፈለጋቸው? እዚያው አባታቸው የነበሩበት ቦታ ላይ መንግስታቸውን መመስረት አይችሉም ነበር?
በሶስት ምክንያቶች ነው እንደዚያ ያደረጉት። አንደኛው ከእምነት አንፃር፣ ጎርጎራ ካቶሊካውያኑ የነበሩበት ቦታ ስለነበር የረከሰ ነው ተብሎ ታመነ። ስለዚህ አዲስ ቦታ መቀየር አስፈለጋቸው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት፣ ጎርጎራ ወባማ አካባቢ ስለነበር ሰራዊታቸውን ፈጀባቸው፡፡ እናም ከጤና አኳያ የአሁኑ ጎንደር ተመራጭ ሆነ፡፡ ሦስተኛው ምክንያት፣ ጎንደር ወይና ደጋ አየር ንብረትና ከ40 በላይ ምንጮች ያላት ነበረች፡፡ በወንዞችም የተከበበች በመሆኗም የሰራዊቱን የውሃ ፍላጎት ታሟላ ነበር፡፡
አሁን ቤተ መንግስቱ ያለበት ቦታ 2200 ሜትር ከባህር ጠለል በላይ ከፍታ አለው፡፡ ዙሪያውን ደግሞ እስከ 3 ሺህ ሜትር ከፍታ ያላቸው ተራራዎች አሉ። እነዚህ ተራራዎች የአየር ወለድ በሽታ ቢመጣ ወደ ከተማዋ አያስገቡም/አያሳልፉም ተብሎ ይታሰባል፡፡ ከጦር ስትራቴጂ አንፃርም በተራራ መከበቧ ጠላት በቀላሉ እንዳይገባ ይከላከላል፡፡ ተራራዎቹ በትልልቅ ዛፎች የተጠቀጠቁ መሆናቸውም የማገዶ ፍጆታን ያሟላሉ፡፡ በእነዚህና በሌሎች ምክንቶች ጎንደር በ1628 ዓ.ም ተመሰረተች፡፡
አፄ ፋሲለደስ በ1660 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ፣ የጎንደር ህዝብ ብዛት 27 ሺህ ደርሶ ነበር። ይሄ የሚያሳየው ከተማዋ በወቅቱ እጅግ ሰፊ መሆኗን ነው፡፡ በእነ እቴጌ ምን ትዋብ ዘመን ደግሞ የህዝብ ብዛቱ እስከ 100 ሺህ ደርሶ ነበር፡፡
ከብሄር፣ ከሃይማኖት አንፃር ምን አይነት ማህበረሰብ ነበር የሚኖርባት?
እንደውም ጎንደርን በወቅቱ ከነበሩት የሃገሪቱ አካባቢዎች ለየት የሚያደርጋት ቤተ እስራኤሎች፣ ባህላዊ እምነት ተከታዮች፣ ሙስሊሞች፣ የውጭ ዝርያ ያላቸው ቱርኮች… ሁሉም አንድ ላይ እንደልባቸው ተስማምተው የሚኖሩባት መሆኑ ነበር፡፡ በተለያዩ ሥራዎች ላይ የተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎችም ይኖሩባት ነበር፡፡ አናፂዎች፣ ግንበኞቹ፣ ሸማ ሰሪዎች፣ የብረታ ብረትና የወርቅ ስራ የሚሰሩ እንዲሁም ነጋዴዎች ሁሉ አንድ ላይ ይኖሩባት ነበር፡፡ በጊዜው ንግዱን በሚገባ ያውቁታል ተብሎ ስለሚታመን ነጋድራሶች ከሙስሊሞች ነበር የሚመረጡት፡፡
አፄ ፋሲለደስ ቤተ-መንግስታቸውን ካሳነፁ በኋላ በዙሪያው ሰባት ቤተ-ክርስቲያኖችን አሰርተዋል፡፡ በየጊዜው ነገስታቱ እየተተኩ ለ120 ዓመታት እጅግ የረቀቀ የህንፃ ግንባታ ጥበብን ሰርተው አልፈዋል፡፡ የጎንደር ስልጣኔ የመጨረሻዋ ንግስት የነበሩት እቴጌ ምንትዋብም የራሳቸውን ቤተ-መንግስትና ቤተ-ክርስቲያን አሳንፀዋል ቁስቋም ትባላለች፡፡
አፄ ፋሲል ለምን 7 ቤተ-ክርስቲያናትን በዙሪያቸው አሰሩ?
በወቅቱ እንደሚታወቀው ነገስታቱ በእምነታቸው ጠንካሮች ነበሩ፡፡ የጊዮርጊስ ታቦት ዘማች ታቦት ነው፤ ተዋጊ ነው፡፡ በአድዋ ጦርነት ጊዜም ቢሆን አፄ ምኒልክ ይዘው ዘምተዋል። የድንግል ማርያም ደግሞ ከንግስቲቱ ማረፊያ ቤት አጠገብ እንድትተከል ተደርጓል፡፡ ከትውፊቱ ከተቀበልነው ታሪክ እንደምንረዳው፣ አፄ ፋሲል ቤተ መንግስታቸውን ሲገነቡ አውሬ ሲያስቸግራቸው ባህታውያን የአቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስን ታቦትን ትከል ብለው ሲመክሯቸው ያንን አደረጉ፡፡ መብረቅ ሲያስቸግራቸው የቅዱስ ሚካኤልን ታቦት፣ በሽታ ሲያስቸግራቸው የዓለም መድኀኒት የሆነውን የመድኀኒዓለም ታቦት እንዲተክሉ ተመከሩ፡፡ በዚህ ሂደት ነው ደብራቱን በዙሪያቸው የተከሉት ተብሎ ይነገራል፡፡ በሌላ በኩል በወቅቱ ካቶሊኮች ተባረው “ፋሲል ይንገስ ሃይማኖት ይመለስ” ተብሎ ሲታወጅ፣ አፄው ለሃይማኖታቸው ያላቸውን ፅናት ለማሳየት በርካታ ቤተ-ክርስቲያናትን እንደተከሉ ይታመናል፡፡
በዚያን ጊዜ የቤተ-መንግስቱ የአኗኗር ስርአት ምን ይመስል ነበር?
በአጠቃላይ የቤተ መንግስቱ ቅጥር ግቢ 70 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ነው ያረፈው፡፡ 12 በሮችም አሉት፡፡ ወደ ቅፅሩ የሚገባው እንደየደረጃውና ማዕረጉ በሚፈቅድለት በር ብቻ ነው፡፡ ራስች በር - ራሶች ብቻ የሚገቡበት ነው፣ የንጉሱ በር (ጃንተከል በር) ንጉሱ ብቻ የሚገቡበት ነው፡፡ ግምጃ ቤት በር የሚባል አለ - የግምጃ ቤት አስተናባሪዎች የሚገቡበት ነው፡፡ ቀጭን አሸዋ በር የሚባል አለ ይህ የግንባታ እቃዎች የሚገቡበት በር ብቻ ነው፡፡ እርግብ በር የሚባለው ደግሞ የደናግላን እና የመነኮሳት በር ነው፡፡ እንቢልታ ነፊዎች ብቻ የሚገቡበት ደግሞ እንቢልታ በር ይባላል፡፡ በሃዘን ጊዜ ሃዘንተኞች የሚገቡበት በር ተዝካሮ በር ይባላል፡፡ ተዝካሮ በር ፊት ከቤተመንግስቱ በስተደቡብ ባለው አነስተኛ ሜዳ ላይ አስከሬን ተቀምጦ ይለቀሳል፡፡ በጥንቱ የጎንደር ባህል ቦታው ሰዎች ሲሞቱ አስከሬናቸው ተቀምጦ ረዘም ላለ ሰአት ለቅሶና የሽኝት ስነ ስርዓት የሚከወንበት ነው፡፡ ባልደራስ በር የሚባለው ደግሞ ፈረሰኞችና የፈረሰኛ አዛዥ በር ነው፡፡ የንጉሱ ፕሮቶኮሎች የሚገቡበት በር ደግሞ “ኳሊ” በር ይባላል፡፡ በዚህ በኩል ባለጉዳዮችም ሆኑ የንጉሱ የቅርብ አጋዞች ይስተናገዱ ነበር፡፡
ንጉሡ በወቅቱ የከተማውን ህዝብ ግብር ያበሉ ነበር?
እንግዲህ በኢትዮጵያ ታሪክ ንጉሱ ግብር ካላበላ ምኑን ንጉስ ሆነው ይባል ነበር፡፡ ግብር ማስገበርም አለበት፡፡ ግብር በወርቅ፣ በብር፣ በከብት፣ በአሞሌ፣ በጥይት በመሳሰሉት መልክ ከነዋሪው ይሰበሰባል። ንጉሱ ደግሞ በምትኩ ለታችኛው የህብረተሰብ ክፍል ግብር ሰብስቦ በየጊዜው ያበላል፡፡ ራሶችና መኳንንቶችም በየአውራጃቸው ላለ ህዝብ ግብር ማብላት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ግብር ሲበላ ሰው እንደማዕረጉ ነው የሚቀመጠው፡፡ መጀመሪያ ንጉሱ ይቀመጣሉ፤ ከዚያ ንግስቲቷ ይቀጥላሉ፣ እጨጌውና የአክሱም ንቡረ ዕድ ይከተላሉ፡፡ እንዲህ እንዲያ እያለ መኳንንቱ በየደረጃቸው ይቀመጣሉ፡፡ ብዙውን ጊዜ ከፋሲካ በኋላ ነው ግብር የሚበላው፤ በበአላትም እንደአስፈላጊነቱ ንጉሱ ደግሶ ህዝቡን ያበላል፡፡  
ዳኝነት እና ፍርድስ እንዴት ነበር የሚከናወነው?
ዳኝነት እሚሰጠው እምነትን መሰረት በማድረግ ነበር፡፡ የእምነት ወይም ከፍተኛ ሃገራዊ ጉዳይ ከሆነና በመኳንንቱ መወሰን የማይችል ከሆነም ዙፋን ችሎት ላይ ይቀርባል፡፡ በእምነት ጉዳይ ክርክር ስለመካሄዱ ሁሌም በምሳሌነት የሚጠቀሰው የአልፈንዞ ሜንዴዝ እና የእጨጌ ጊዮርጊስ ክርክር ነው፡፡ በወቅቱ አልፈንዞ ሜንዴስ ከእጨጌው የሚቀርብለትን መከራከሪያ መመለስ አቅቶት ነበርና አንድ ጥያቄ ጠየቃቸው። “ስላሴዎች ሁል ጊዜ ፀጉራቸውን የማይላጩት ለምንድን ነው?” በማለት እሳቸውም “አንተ ቅንድብህን ትላጨዋለህን?” ሲሉ ጥያቄውን በጥያቄ መለሱለት፡፡ ቀጥሎም “የአብ ፊቱ ወዴት ነው?” ሲል ጠየቀ፡፡ እሳቸውም ጧፍ አበሩና “የዚህ መብራት ፊቱ ወዴት ነው?” አሉት፡፡ መልስ ሊሰጣቸው አልቻለም፡፡ በዚህም የእግዚአብሔር ፊት በሁሉም አቅጣጫ ነው ብለው ክርክሩን ረቱት ይባላል፡፡
ከፋሲል በኋላ አፄ (ፃድቁ) ዮሐንስ ነበሩ፡፡ እሳቸው የእንስሳትን መብት እስከማስጠበቅ የደረሱ ሰው ናቸው፡፡ ከደግነታቸው ብዛት ትልቅ ደውል በውጨ በኩል አስተክለው ነበር፡፡ ዳኝነት ጎደለብኝ ተበደልኩ የሚል ሰው መጥቶ ይደውላል፡፡ ከዚያም ይገባና ከንጉሱ ዘንድ ፍርድ አግኝቶ ይሄዳል፡፡ አንድ ጊዜ ምን ሆነ፡- ዝናብ እየዘነበ ነበር፡፡ ደውሉ ይደወላል፡፡ በዚህ ዝናብ ማን ፍርድ የጎደለበት ይሆን የመጣው ብለው እልፍኝ አስከልካያቸውን ይልኩታል፡፡ “ኧረ ጃንሆይ  አህያ ነው እንጂ ሰውስ የለም” ይላቸዋል፡፡ አህያውን አስገባው አሉት፡፡ አህያው ሲታይ ጀርባው ተጋግጧል፡፡ ባለቤቱ ተፈልጎ ይቅረብ ተባለና መጣ፡፡ “ለምን እንዲህ አደረክ፣ እድሜ ልኩን ያገለገለህን አህያህን ለምን ጣልከው?” ሲሉ ሰውየውን ገስጸው ቀጥተው ላኩት፡፡ አህያው ደግሞ በቤተ መንግስት ውስጥ ገብስና ባቄላ እየበላ እንዲኖርና ከቁስሉ እንዲያገግም ተደረገ፡፡ በዚያውም “የተገጠበ አህያ ጭነት እንዳይጫን” የሚለው አዋጅ ታወጀ፤ ጭኖ የተገኘም ይቀጣ ነበር፡፡ ያኔ ነው የእንስሳት መብት የታወጀው፡፡
ጎንደር የ44 ታቦታት መገኛ ሲባል ምን ማለት ነው?
ጎንደር ከመመስረቷ በፊት በአካባቢው አራት ደብሮች ነበሩ፡፡ አንደኛው አርባዕቱ እንስሣ ይባላል፡፡ በሌላ አቅጣጫ ቃአ ኢየሱስ የሚባል አለ፡፡ ጊዮርጊስ በሌላ አቅጣጫ አለ፤ አበራ ጊዮርጊስ የሚባልም አለ። ከዚያ በኋላ አፄ ፋሲል 7 ተከሉ፡፡ ፃድቁ ዮሐንስ 2 ተከሉ፣ አድያም ሰገድ ኢያሱ ደብረ ብርሃን ስላሴ ጨምሮ 2 ተከሉ፡፡ እንዲህ እንዲያ እያሉ ነገስታቱ በተፈራረቁ ቁጥር አዳዲስ ደብሮችን ሲተክሉ ኖሩ። በዚህ ሂደት በእነዚህ ነገስታት 30 ተተከሉ። 14 ያህሉ ደግሞ ቀድሞም የነበሩ ናቸው፡፡ እነዚህ ተደምረው ጎንደር የ44 ታቦት መገኛ ሃገር ተባለች፡፡ ኋላ ላይ በደርቡሽ ጦርነት 4 ያህሉ ተቃጥለው ነበር፡፡ ሃገሬው የተቃጠሉትን እንደገና ሰርቷቸው ነበር፡፡ አሁን ሁለቱ እየተሰሩ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ሌሎች ደብሮች በብዛት የተተከሉ ቢሆንም የጥንቱን የጎንደር ስልጣኔ ለማስታወስ 44ቱ ታቦታት የጎላ ቦታ አላቸው፡፡
ጎንደር የሚለው ስያሜስ ከየት የመጣ ነው?
ብዙ አፈታሪኮች አሉ፣ ነገር ግን ዋናው ማየት ያለብን የታሪክ ጥራዞችን ነው፡፡ የአፄ አምደፅዮን ዜና መዋዕል ላይ “ጎንደር” የሚለው ስም ሰፍሯል። ጎንደር ከመመስረቷ ከ300 ዓመት በፊት መሆኑ ነው፡፡ ወደ አፈታሪኩ ስንመለስ ቃሉ የማን እንደሆነ ባይታወቅም ጉንዳ ሃገር ወይም ትልቅ ሃገር ማለት ነው፡፡ አንዳንዶቹ ጓንግ እና ዳራ ከሚሉ ሁለት ቃላት የመጣ ሲሆን በአንገረብ እና ቃሃ ወንዝ መካከል ስላለች ነው ይህ ስም የተሰጣት ይላሉ፡፡ ግን የተጨበጠ ነገር የለውም፡፡
ነገስታቱ ይህን የቤተመንግስቱን ቦታ ከመያዛቸው በፊት ቦታው ላይ ምን ነበር?
እንደ አፈታሪክ እዚህ ቦታ ላይ (አሁን ቤተመንግስቱ ያለበት) ውሃ ነበር ይባላል፡፡ ውሃውን አድርቀው ቤተ መንግስታቸውን ሰሩ፤ አንዳንድ ታሪክ ደግሞ ቦታው የባላባቶች/የእርሻ ቦታ ነበር ይላሉ። ሌሎች አፈታሪኮች አፄ ፋሲል አደን ወጥተው አንዳንዶች ጎሽ ይላሉ ሌላው አንበሳ ይላል እያባረሩ መጥተው እዚህ ቦታ ሲደርሱ ተሰወረባቸው፤ ባህታዊ ተገልጦ ቤተ መንግስትህን የምትሰራበት ቦታ ይሄ ነው ብሎ ነገራቸው ይባላል፡፡ ከዚያ በፊት መላዕኩ ራጉኤል “ጎ” የሚባል ቦታ ላይ ትነግሳለህ ብሎ በራዕይ ይነግራቸው እንደነበር ይነገራል፡፡ “ጎ” ሲላቸው ቦታውን ፍለጋ ጎዛራ፣ ጎጃም፣ ጎርጎራ ሄደው በመጨረሻ ጎንደር ፀንቶላቸዋል ነው የሚባለው። ነገር ግን በዚህ አካባቢ አድባራት በፊትም መኖራቸውን ስናይ ሰዎች ይኖሩበት እንደነበር ያመላክተናል፡፡
የኖህ መቃብር ነው የሚል ታሪክም ይነገራል?
ሰዎች የራሳቸውን ታሪክ ይዘው ሊነሱ ይችላሉ። እኔም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ይሄን ነገር ሰእየሰማሁ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በ1960ዎቹ የተፃፈ አንድ ታሪክ የሚያሳየው፤ ፋሲል ቤተመንግስቱን እንደ ኖህ መርከብ አድርጎ እንደሰራው ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው ታሪክ የመጣው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ነው፤ ግን ሰፊና ጥልቀት ያለው ጥናት ይፈልጋል፡፡
በ150 ዓመታቱ የጎንደር ስልጣኔ ከታዩ ዘመናዊ ነገሮች ጥቂቶቹን ቢጠቅሱልን…
የቤተ መንግስቱ የህንፃ ጥበብ ዋናው ነው፡፡ አንዳንዶች የውጭ ሰዎች እጅ አለበት ይላሉ፤ ነገር ግን አሰራሩ በፊትም በአክሱም ዘመነ መንግስት የነበረ ነው፡፡ ህንዳውያንም ሆነ ፓርቹጋሎች ከመምጣታቸው በፊት እንደነበር ይናገራል፡፡ እ.ኤ.አ ከ1563-97 ዓ.ም የነገሱት አፄ ሰርፀድንግል ቤተ መንግስታቸው እንፈራዜ የምትባል ቦታ (ከጎንደር ወደ ባህርዳር ሲሄድ 60 ከሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ቦታ) ላይ የሚገኝ ቤተ መንግስት ላይ ይህ ቴክኖሎጂ ተሰርቶበታል፡፡ ስለዚህ የውጭ ኃይሎች እጅ አለበት የተባለው አያሳምንም፡፡
ሌላው ግዙፍ የሆኑ የንግድ መስመሮች - እስከ አውሮፓ፣ ኤሽያ የሚዘልቁ ተፈጥረው ነበር፡፡ የቤተ መንግስቱን አኗኗር ካየን ደግሞ ዘመናዊ ነበር፡፡ ዛሬ ፋሽን የምንለው… በዚያን ጊዜ ቀጭን ፈታዮች በሚባሉ ባለሙያዎች ለቤተ መንግስቱ ወይዛዝርት በየአይነቱ አልባሳት እየተሰሩ ያንን ፋሽን ይከተሉ ነበር፡፡ ዛሬ “ስቲም” የምንለው ያኔ “ወሸባ” ይባል ነበር፡፡ የፀጉር፣ የንቅሳት አይነት እንደፋሽን ይታይ ነበር፡፡ ዛሬ ዶሮ አስራ ሁለት ብልት አላት እንላለን። ያ መለኪያ የወጣው በወ/ሮ ምንትዋብ ጊዜ ነው። የዓሣ አሰራርና የተለያዩ የምግብ አሰራሮች ያኔ የመጡ ናቸው፡፡ ይህ ስርአት እንግዲህ ወደ ከተማው ተስፋፍቷል፡፡ እኛ ዛሬ የተጣራ ውሃ እያልን የታሸገ ውሃ እንጠጣለን፡፡ ይሄ በዚያን ጊዜም ይደረግ ነበር። የፈረስ ማቆሚያ (ፓርኪንግ) አገልግሎት ይሰጥ ነበር፡፡ ዛሬ የመኪና ፓርኪንግ እንደምንለው በአፄ በከፋ ዘመን ባለ ዘጠኝ በር ዘመናዊ የፈረስ ማቆሚያ /ፓርኪንግ/ ተሰርቶ ነበር፡፡ እንግዶች ፈረሶቻቸውን እዚያ ነበር የሚያቆሙት፡፡
በ5 ዓመት የጣሊያን ወረራ ቤተ መንግስቱ ለጣሊያን ገዢዎች መቀመጫነት አገልግሏል ይባላል?   
በሚገባ አገልግሏል፡፡ እንዲያውም ጣሊያን ከተማዋን ለሁለት ከፍሎ ነበር የሚያስተዳድረው። ከጃን ተከል በታች ያለው የሃገሬው ወይም የሃበሻ መንደር ነበር፡፡ አሁን ፒያሳ የምንለው ደግሞ የጣሊያኖች ነበር፡፡ ያኔ ሃበሾች ወደ ነጮች መንደር መዝለቅ አይፈቀድላቸውም፡፡ በቤተ መንግስቱ ውስጥም ለግብር በሚቀመጡበት ወቅት ነጮቹ በተመረጠ ቦታ ሃገሬው በሌላ ቦታ ሳይቀላቀሉ እንዲቀመጡ ይደረጋል፡፡ ምግብ ሲቀርብም ነጮቹ በስርአቱ ይመገባሉ፡፡ ሃበሾቹ ተሻምተው እንዲመገቡ ይደረግ ነበር፡፡ ጣሊያን ቤተ መንግስታቱ በጥቁሮች መሰራታቸውን አምኖ ላለመቀበል “የፖርቹጋል ግንቦች” ይላቸው ነበር፡፡ የከተማዋን ስያሜዎችም በብዛት ቀይሮ ነበር፡፡
ጃንተከል ዋርካ ዝነኛ ነው፤ ስለሱ ታሪክ ይንገሩን…
ጃንተከል እንግዲህ አፄ ፋሲል ተከሉት ተብሎ ይታመናል፡፡ ለዚያም ነው ጃንሆይ የተከሉት ለማለት ጃን ተከል የተባለው፡፡ በወቅቱ የሃገር ሽማግሌዎች በስሩ ተቀምጠው ይወያዩ ነበር፡፡ ስቅላትን የመሳሰሉ ፍርዶችም ይፈፀሙበት እንደነበር በስፋት ይነገራል።

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
“ወራሪም ፈጣሪን ላያቅ
የጣለውን በስሏል እንጂ፣ ወድቋል ብሎ ግፉ ላያልቅ…”
ይላል ሎሬት ጸጋዬ፡፡ እኛም ዘንድሮ የጣልነውን “ወድቋል” ሳይሆን “በስሏል” የምንልበት ዘመን ይመስላል፡፡ በየዓለም ጥጉ ሁሉ የምታዩት ነገር “ወድቋል” ማለት ቀርቶ “በስሏል” ማለቱ የሰውን ልጅ የሚያግባባ ብቸኛው ቃል የሆነ ይመስላል፡፡
የምር ግን…ዓለማችን ችግሯ በዛሳ! አንዱ የቸገረው ምን አለ መሰላችሁ…“ምናልባት ይቺ ምድራችን የሌላ ዓለም ገሀነም ልትሆን ትችላለች፡፡”አሪፍ አባባል አይደል! አሁን፣ አሁን የምንሰማውና የምናየው ነገር ሁሉ…አለ አይደል…“የሰው ልጅ ወደ ድንጋይ ተመለሰ እንዴ!” ያስብላል፡፡
የምር እኮ… እንዴት ነው እውቀት እየበዛ ሄደ በሚባልበት ዘመን ይሄን ሁሉ ጭካኔ የምናየው! እናላችሁ…ምድራችን በአንዱ ሲብስባት በሌላው እንኳን እንዳንጽናና ‘የተካበ’ የሚመስለው ሁሉ እየተሰነጣጠቀ ግራ ገብቶናል። ሸሽተን የምንሸሸግባቸው የውጪ ‘ቻነሎች’ የሚያሳዩን ነገሮች ሁሉ “ይሄ ስምንተኛው ሺህ ሚሌኒየሙን አልፎ… አዘናግቶ መጣብን እንዴ!” ያሰኛሉ። (በነገራችን ላይ…አሁን ያለንበትን ዘመን ከኃይማኖታዊ አስተምህሮቶችና ትንቢቶች ጋር እያጣቀሱ ‘ጊዜው መድረሱን’ የሚናገሩ እየበዙ ነው።)
ቦምብ ከሚንዳት ምድር አላቆ አበባ የሚያብባት ምድር ያድርግልንማ! እናማ…የባሩድ ሽታ በጽጌረዳ መአዛ የተተካባት ምድር ያድርግልንማ!
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይቺን ካወራናት እንድገማትማ…ሰውየው የገጠር ሰው ነው፡፡ እናላችሁ…የሰው ነፍስ ያጠፋና ፍርድ ቤት ይቀርባል፡፡ ታዲያ ‘ለማተቡ፣ ለክሩ’ የሚቆም ስለሆነ መግደሉን እንደሚያምን ለዘመዶቹ ይነግራቸዋል፡፡ ስለ ህጉ ብዙም ዝርዝር ስለማያውቅ የሚወሰንበትን ግን አላሰበውም። ታዲያማ፣ ችሎት ቀርቦ የእምነት ክሀደት ቃል ሊጠየቅ ሲል አጎቱ ማስጠንቀቂያ ሹክ ሊለው ጠጋ ይለዋል፡፡ ይሄን ጊዜ ዳኛው ያዩትና “እዛ’ጋ፣ ተጠርጣሪውን ምንም ነገር ማናገር ክልክል ነው!” ብለው ይቆጣሉ፡፡ ይሄኔ አጎትየው ወደኋላ ያፈገፍግና ምን ቢል ጥሩ ነው…
“ጌታዬ፣ ቢያምን እንደሚሞት፣ ቢክድ እንደሚተርፍ እሱ መች አጥቶት ነው እኔ የምነግረው!” ብሎ አረፈው፡፡
ዘንድሮ ያልሆነው ሆነ፣ የሆነው አልሆነም እየተባልን በአጠቃላይ “…እኛ መች አጥተነው ነው የሚነግሩን…” የሚያስብሉ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ በዓይናችን በብረቱ አጥርተን የምናየው፣ በጆሯችን አጥርተን የምንሰማው ነገር ተመልሶ ሲነገረን፡፡
እናላችሁ…አንዳንዴ ስለተለያዩ ነገሮች ሲወራ እኛ ያለንባት ራሷ ጦቢያ መሆኑን ረስተን… “እስቲ ይቺን የምታወሩላትን አገር አሳዩን… ልንል ምንም አይቀረን፡፡
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ስለ መግባባት ካወራን ይቺን ስሙኝማ… ሰውየው ክፍል ውስጥ አማርኛ እያስተማረ ነው፡፡ ደግሞላችሁ…ተማሪዎቹ ገና ጀማሪዎች በመሆናቸው ስለ ስዋስው ምናምን ብዙም የሚያውቁት ነገር አልነበረም፡፡
እናላችሁ…በሚገባ ሳያስረዳቸው ምን ብሎ ይጠይቃቸዋል፣ “‘አበበ ከበደን በዱላ መታው’ የሚለው አረፍተ ነገር ውስጥ ግሱ የምን ግስ ነው?” ብሎ ይጠይቃል፡፡
አንደኛው ተማሪ ምን ብሎ መለሰ መሰላችሁ…“የወንጀል ክስ ነው፡፡” ልክ ነዋ…በዱላ መምታት ወንጀል ነዋ! “በዱላ መታው” ካሉ በኋላ ወላ ‘ገቢር ግስ’፣ ወላ ‘ተገብሮ ግስ’ ብሎ ነገር የለማ! ቂ…ቂ…ቂ… (አስተማሪው ያቀረበው የምሳሌ ዓረፍተ ነገር “አበበ ከበደችን በከንፈሮቹ ሳማት…” ቢሆን ኖሮ ግሱ ‘ተሻጋሪ’ ግስ ይሆን ነበር! ሳይገባኝስ!)
እናማ…ችግሩ የመላሹ ሳይሆን የአስተማሪው ነው፡፡ ዘንድሮም አብዛኛው ችግር የእኛ ‘የመረጃ’ ተቀባዮች ሳይሆን የእነሱ ‘የመረጃ’ ሰጪዎቹ ነው። የእውነት መረጃ የሚሰጡን ሳይሆን እኛ ጥቁር ያልነውን እነሱ “ቀይ ነው ብያለሁ ቀይ ነው…” አይነት ነገር ይሆናል፡፡ ይሄኔ ታዲያ እኛ ደግሞ…ጮክ ብለን ባንናገር እንኳን በሆዳችን “…እኛ መች አጥተነው ነው የሚነግሩን…” እንላለን፡፡
(ያን ሰሞን የድራፍት ዙሪያ ‘ሀሜታ’ ላይ “እንኳን ጮክ ብለን ጠንከር አድርገን ስንተነፍስም ዓይን በዝቶብናል…” ያልከው ወዳጄ ‘አድናቂህ’ ነኝ።) በነገራችን ላይ…እግረ መንገዴን የሆነ ነገር ትዝ አለኝማ…በአንድ ተጠባባቂ ተጫዋች ብቻ የነጥብ ዓለም አቀፍ ጨዋታ በመጫወት ከዓለም ስንተኛ ነን! አይ ጦቢያ! እኔ የምለው… ‘እሱ ሰፈር’ በዛ ሰሞን “ተሽሎታል…” ምናምን ሲባል አልነበረም እንዴ! ኮሚክ ነገር እኮ ነው…ፓስፖርት ላይ የተጻፈ ዓመተ ምህረት አይቶ ‘ለመደመርም’ ካሽ ሬጂስተር ማሺን ምናምን ሊያስፈልገን ነው ማለት ነው!
ደግሞላችሁ የኳስ ነገር ካነሳን አይቀር… ኳስ ጨዋታዎች በቲቪ ላይቭ ሲተላለፍ ‘ኮሜንተሪ’ የሚያሰሙት…ሁሉም እንቅስቃሴ ‘ሙሉ አረፍተ ነገር’ መሆን አለበት እንዴ! “የእንትን በረኛ ለመሀል ተከላካዩ…” እንዳቀበለው በመግለጽ የተጀመረው ዓረፍተ ነገር እስኪጠናቀቅ ኳሷ በሰባት በስምንት እግሮች ተነክታ ትመለሳለች። እንዴ… ጨዋታውን እኛም እያየነው እንደሆነ ልብ ይባልልና! አለበለዛ “ስምንት ቁጥሩ አንጋጋው አናጌ ከባላጋራ ተጫዋቾች መሀል ከፍ ብሎ ዘሎ ኳሷን በጭንቅላቱ ገጫት…” አይነት ነገር ግስ፣ ስም፣ ተውላጠ ስም፣ ተሳቢ፣ ቦዝ አንቀጽ ምናምን አሥራ ስምንት የንግግር ክፍል ያለበት ይመስላል፡፡ ዓረፍተ ነገሩ ሲጀመር ምጥ የጀመራት ሲያልቅ ልትወልድ ትችላለች እኮ! (ቂ…ቂ…ቂ… እኛም የማጋነን ዕድል ይድረሰና!)
የምር ግን ላይቭ ኮሜንታሮቻችን ዘዴያቸውን መፈተሽ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡  ደግሞ የተጫዋቹ ቁጥር እየቀረ ስም ከእነ አባቱ ሳይቀር ሁሉም መባል የለበትም፡፡ አንጋጋው አናጌ በአንድ ጨዋታ ላይ ሙሉ ስሙ የተጠቀሰውን ብዛት ከቄስ ትምህርት ቤተ ጀምሮ መዝገቦች ላይ የተጻፈው ተደምሮ አይደርስበትም፡፡ (‘ማጋነን’ ለመደብኝ ማለት ነው!)
ከተጨዋወትን አይቀር ይቺን ስሙኝማ…‘በኮሚዋ’ ሩስያ ዘመን የኮሚኒስት ፓርቲው የምስረታ በዓል እየተከበረ ነበር፡፡ እናላችሁ…በአንድ የሀገሪቱ አውራጃ በዓሉን ምክንያት በማድረግ ልዩ ዝግጅት ነበር፡፡ በዝግጅቱም ላይ የአካባቢው የፓርቲ ሊቀመንበር ንግግር ያደርጋል።
“የተወደዳችሁ ጓዶች!” ከአብዮቱ በኋላ ፓርቲያችን ያስመዘገባቸውን ስኬቶች ልብ በሉ። ለምሳሌ እዚህ አጠገቤ ያለችውን ማሪያን ተመልከቱ፡ ከአብዮቱ በፊት ምን ነበረች? ማንበብ መጻፍ የማትችል መሀይም አርሶ አደር፡፡ የነበራት አንዲት ቀሚስ ብቻ ነበረች፣ ጫማም ስላልነበራት በባዶ እግሯ ነበር የምትሄደው፡፡ አሁንስ? አሁን በአካባቢያችን ቤት ለቤት በመዞር ወተት በመሸጥ ትታወቃለች፡፡ ወይንም ኢቫን አንድሪቭን ተመልከቱት፡፡
በሰፈራችን የነጣ ድሀ ነበር፡፡ ፈረስ የለው፣ ላም የለው፣ መጥረቢያ እንኳን የለውም ነበር። አሁንስ? አሁን ትራክተር አሽከርካሪ ነው። ደግሞም ሁለት ጫማ አለው፡፡ ዕድሜ ለአብዮቱ ሁለት ጫማ! ወይ ደግሞ ትሮፊም ሴሜኖቪች አሌክሲቭን ተመልከቱት፡፡ የለየለት ወሮበላ፣ ሰካራምና መቼም የማይጸዳ ነበር፡፡ ያገኘውን ምንም ነገር ከመስረቅ ስለማይመለስ ማንም ሰው አያምነውም ነበር። አሁን ግን ዕድሜ ለአብዮቱ የፓርቲ ኮሚቴው ጸሀፊ ሆኗል።”
እኔ የምለው…እኛ ዘንድ ተመሳሳይ ‘ስኬቶች’ ካሉ ይገለጹልንማ!
እናላችሁ… በዚህ የቴክኖሎጂ ዘመን፣ በእነፌስቡክ ዘመን፣ በትዊተር ዘመን፣ በዩ ቲዩብ ምናምን ዘመን “…እኛ መች አጥተነው ነው የሚነግሩን…” ባንባባል አሪፍ ነው፡፡ አሥር ወር ገበያ ላይ ቆይቶ መውጣቱን እንኳን ሰው ነገሬ ያላላውን አልበም “በከፍተኛ ደረጃ እየተሸጠ ነው…” አይነት ነገር ስንባል፤…ሰው ሳይበዛ ገብተን እንደ ቲያትር ቤት መዳፋችን የዝንጀሮ እንትን እስኪመስል ድረስ ካላጨበጨብን አስተናጋጆች ብቅ የማይሉበትን ሬስቱራንት “በዚህ ሬስቱራንት ደንበኛ ንጉሥ ነው…” ምናምን ስንባል፤ ሀሳብ የሚሰጥ ጠፍቶ ሰብሳቢዎቹ… አለ አይደል… የስብሰባው መሪዎችም፣ የስብሰባው ንቁ ተሳታፊዎችም እነሱ ብቻ በሆኑበት “ከፍተኛ የሀሳብ ልውውጥ የተደረገበት ስብሰባ…” ሲሉን…በቃ ቀሺም ነገር ነው፡፡
በትንሹም በትልቁም “…እኛ መች አጥተነው ነው የሚነግገሩን…” የማንባባልበትን ዘመን ያምጣልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

አንድ የአፍጋኒስታኖች ተረት እንዲህ ይላል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሰው ሚስቱ ድርስ-እርጉዝ ሆና ስለነበር ለሚወለደው ወይም ለምትወለደው ልጅ አልጋ ሊያሰራ፤ ወደ አልጋ ሰሪ ሄደ፡፡  ያ አልጋ ሰሪ አናጢ፤
“ምን ፈልገህ ወደኔ መጣህ?” ሲል ይጠይቃል፡፡
“ለልጄ አልጋ ላሰራ ፈልጌ ነው” ይላል አባት፡፡
“መልካም፡፡የህፃን ልጅ አልጋ ግምቱ የታወቀ ስለሆነ አሳምሬ እሰራልሃለሁ” አለው፡፡
አባት፤ በጉዳዩ ተስማምቶ፤
“በል እንካ ቃብድህን፡፡ አደራ ደህና አድርገህ ስራልኝ” ብሎ ገንዘቡን ሰጠው፡፡
አባት የልጁ መወለድ እየቀረበ ስለመጣ ወደ አናጢው እየሄደ፤
“እህስ፤ ምን አደረስክልኝ?” ይለዋል፡፡
“ቆይ ትንሽ ጠብቅ” ይላል አናጢ፡፡
አባት ሌላም ቀን ይመጣል፡፡
የአናጢው መልስ፤
“ቆይ ትንሽ ጠብቀኝ” ሆነ፡፡
በዚህ ማህል ልጁ ተወለደ፡፡ አደገ፡፡
ጎረመሰ፡፡ ጎለመሰና ሚስት አገባ፡፡ ሚስቱ ፀነሰች፡፡ አረገዘች፡፡
ልጁ እንግዲህ አባት ነውና፤ ኃላፊነት አለበትና፤ ወደ አባቱ ሄዶ፤
“አባቴ ሆይ! መቼም አንተ ልምድ አለህና ለሚወለደው ልጄ አልጋ ከየት እንደምገዛለት ንገረኝ?” አለው፡፡
አባትየውም፤
“የውልህ ልጄ! የዛሬ ሃያ ዓመት፤ ለአንድ አናጢ አንተ ስትወለድ የምትተኛበት አልጋ ላሰራ ቀብድ ሰጥቼው ነበር፡፡ ሂድና አልጋው አልቆ ከሆነ፤ ቀሪውን ከፍለህ አልጋውን አምጣና ልጅህ ይተኛበታል!” አለው፡፡
ልጅየውም ተደስቶ ወደ አናጢው ሄደና፤
“ጌታው፤ ከዚህ ቀደም አባቴ አልጋ ሊያሰራ ገንዘብ ከፍሎህ ነበር፡፡ እሱን ለመውሰድ ነበር የመጣሁት”
አናጢውም፤
“እናንተ ሰዎች አልጋ በጥድፊያ አይሰራም፡፡ አትጨቅጭቁኝ፡፡ አታጣድፉኝ፡፡ እኔ የጥድፍ ጥድፍ ስራ አልወድም፡፡ ካልፈለጋችሁ ገንዘባችሁን ልመልስላችሁ እችላለሁ!” አለ፡፡
                                               *            *              *
ለልጅ አልጋ ማሰራተን የመሰለ ቁምነገር የለም፡፡ ትውልድን እንደመታደግ ነው፡፡
ከሃያ ዓመት በኋላ “አታጣድፉኝ!” ከሚል ይሠውረን!
የአልጋ ነገር ሁሌም አሳሳቢ ነው፡፡ አዲስ ህፃንም ይተኛበት የቆየ፤ ችግር አያጣውም፡፡ አልጋ ሲሰራ ጥድፊያ አይወድም፡፡ ሃያ ዓመት ቢፈጅም ጥድፊያ አይወድም፡፡ ሰሪውም በቀላሉ አይለቅም! “የጥድፊያው ጥቅም ለሠሪው ነው ለአሠሪው?” ነው ጥያቄው፡፡ ማስተዋልን የመሰለ ነገር የለም ዞሮ ዞሮ፡፡
ምንም ሆነ ምን ድህነትን ማሸነፍ ግዳችን ነው! “ነጭ ደሀ ነጭ ብር ይወልዳል” ቢሉም አበሳውን ማስታወስ ተጨምሮ መሆን አለበት፡፡ ቢያንስ እንደ ፀሐፌ-ተውኔት “ስደተኛ ዘላን ሶማሌ በሄደበት ሣር ወይም አሣር ይጠብቀዋል” የሚል የአምሣ ባምሳ ግምት (Probability) ፈጥሮ ስለአገር ማሰብ ብልህነት ነው፡፡ ምሁሩም፣ መሀይሙም፣ ጠቢቡም፣ ግብዙም ስለአገር ጨለምተኛ (Pessimist) ሆኖ የትም አንደርስም!!
እንደሌላው ዓለም ሁሉ፤ ያለጥርጥር ልማት በኢትዮጵያ፤ ሂደት እንጂ ግብ ብቻ አይደለም፡፡
የጥንቱን የጠዋቱን የሀገራችንንና የውጪውን አገር ልማታዊ መንፈስ እንድናይ ይረዳን ዘንድ ጸጋዬ ገ/መድህን በምኒልክ አንደበት የሚከተለውን ይለናል፡-
“አውሮጳውያን የእጅ-ሥራ ዕድገታቸው፣ የዘመናዊ ሥልጣኔያቸው፣ የቱን ያህል ይደንቃል፡፡ እቴ ጣይቱ፡፡ መሣሪያ፣ መኪና፣ ፋብሪካ፣ የባህር መልህቅ፣ የመሬት መንኮራኩር ሥራቸው የቱን ያህል ይመጥቃል፡፡ የመንገድ ድልድያቸው፣ ወፍጮአቸው፣ ትምህርታቸው፣ እርሻቸው፣ ባንክ የሚሉት የገንዘብ ብልፅግና ዘዴአቸው፣ አውራ ጎዳኖቻቸው፣ ውሃ በቧንቧና ቃል በሽቦ እሚስብ፣ ነፋስ መላላኪያቸው፣ ብርሃን በክር እሚጠልፍ የሌት ሻማቸው፣ ሰፊ ከተማ ሙሉ ከፋሲል ግንብ የሚበልጡ ህንፃዎቻቸው፣ እቴ ጣይቱ አባ ማስያስና ኢንጂነር ኢልግ አጫውተውሽ የለ?! ብቻ ወደኛ የሚልኩብን ጦራቸውን ብቻ ነው፡፡”
ከላይ የተጠቀሰውን ስንመረምር፤
ዕደ ጥበብ ከዚያ ተነስቶ ዛሬ የት ደረሰ? ፋብሪካ የት ደረሰ? ባህርና ትራንዚት ምን ያህል ተራቀቀ? ትራንስፖርትና መገናኛ ምን ያህል አዘገመ ወይም ፈጥኖ ሄደ? የመንገድ፣ የድልድይ ሥራ ምን ያህል ረቀቀ? እርሻ ምን ያህል ሜካናይዝድ ሆነ? (በደርግ ዘመን ከፊል-ካፒታሊዝሙ ይስፋፋ መስሏቸው ትራክተሮች አስመጥተው “በሶሻሊዝም ተወረሰብኝ!” የሚሉ (ኮማንድ - ኢኮኖሚ ነብሱን ይማረውና) አንድ ባለሀብት፤ “ከጓድ ሊቀመንበር ጋር ወደፊት!” እና “ሶሻሊዝም ይለምልም” የሚል መፈክር ባዩ ቁጥር፤ እጃቸውን በጭብጨባ እያጣፉ “አጀብ!... ትራክተር!” ይሉ ነበር አሉ፡፡
የዛሬ ኢንቬስተር ይሄን አይልም ብለን ተስፋ እናደርጋለን! የባንክ ሥርዓታችንስ የት ደረሰ? ባንክ ውስጥ ካለን ገንዘብና በየሰዉ ትራስ ስር ካለው ገንዘብ የቱ ይበዛል? ሁለቱንም ነብሳቸውን ይማርና የቀድሞው መሪ ለባንኮች፤ “ከእናንተ አየለ (አይ.ኤም.ኤፍ) ይሻላል፡፡ ገንዘቡ በአጁ  አለ፡፡ ያንቀሳቅሰዋል!” ብለው ነበር አሉ፡፡ “ነፋስ መላላኪያችን” የት ደረሰ ማለት ያባት ነው (3G እና 4G እንዲሉ!) ብርሃን በክር የሚጠልፍልን መብራት ኃይልስ? ብሎ መጠየቅም ያባት ነው፡፡ ግንባታና ህንፃዎቻችንስ? ሰው ሰው ይሸታሉን? ለኢኮኖሚያዊ ዕድገታችን ያላቸው አስተዋፅኦ የሚተነትንልን የቱ ኢኮኖሚስት፣ የቱስ ባለሥልጣን ነው? ማንም ይሁን ምን፣ ገዢም ይሁን ተገዢ፣ ባለሃይማኖትም ሆነ ኢሃይማኖታዊ፣ የተማረም ሆነ ያልተማረ፣ አገር ውስጥ ያለም ሆነ ዲያስፖራ፣ ሀሳባዊም ሆነ ቁስ-አካላዊ፣ የእኛም ይሁን የውጪ ኃይል… ምኒልክ እንዳሉት… “ወደኛ የሚልኩት ጦራቸውን ብቻ” የሚለውን ነዋሪው ዜጋ እንደምን ያየዋል? መባባል አለብን፡፡ ሁሉ ነገር መጨረሻው ፀብ መሆኑን እንደምን እንየው? መቼ ነው ስለ አዎንታዊ ማንነታችን ደርዝ ያለው ግንዛቤ እምንጨብጠው?
እነዚህን ጥያቄዎች እያሰላሰልን ከገዢም ያልሆኑ ከተገዢም ያልሆኑ “የአየር ባየር ነጋዴዎች” እንዲሉ፤ “የአየር ባየር ፖለቲከኞች” ኋላ የአገር ውስጥ ገቢ መስሪያቤት (ፖለቲካ ሲገባው) የማይምራቸው እንደማለት፤ ፍፃሜያቸው መሬት የሆነ፤
“ጠላትማ ምን ጊዜም ጠላት ነው
አስቀድሞ መግደል አሾክሿኪውን ነው”  
እንደሚባሉ ያሉ አያሌ ናቸው፡፡ “መንገድ ሲበላሽ ትራፊክ ይበዛል፡፡ አገር ሲበላሽ ጃርት ያፈራል” የሚባለውን የጥንት አባባል ዛሬም ልንደግመው ተገደናል፡፡ ይህን ጉዳይ በትግሪኛ ተረት ብናስቀምጠው፤ “ጫማ ምን ክብር ቢኖረው፤ ሁል ጊዜም እግር ሥር ነው” ይሆናል!!  


የጸረ ሽብርተኝነት ህጉ ይሻሻል ብለዋል
ከዚህ በፊት በሽብርተኝነት የተፈረደባቸው እንዲፈቱ ጠይቀዋል
41 የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች፣ የፕሬስ ነጻነት አቀንቃኞች፣ አለማቀፍና ክልላዊ የሲቪል ማህበረሰብ ተቋማትና የሙያ ማህበራት መንግስት በቅርቡ የሽብርተኝነት ክስ የመሰረተባቸውን ጋዜጠኞችና የዞን 9 ጦማርያን በአፋጣኝ እንዲፈታ ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ከትናንት በስቲያ በላኩት ደብዳቤ መጠየቃቸውን ብሉምበርግ ኒውስ ዘገበ፡፡
ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ አርቲክል 19 ምስራቅ አፍሪካ፣ ሲቪል ራይትስ ዲፌንደርስ፣ ወርልድ አሊያንስ ፎር ሲቲዝን ፓርቲሲፔሽን፣ ፔን አሜሪካና የመሳሰሉት አለማቀፍ ድርጅቶች በጋራ በጻፉት ደብዳቤ፣ መንግስት ጋዜጠኞችንና ጦማርያንን በሽብርተኝነት እየከሰሰ ለእስር መዳረጉን መቀጠሉ ያሳስበናል፣ እየተወሰደ ያለው እርምጃ ተገቢነት የሌለው በመሆኑ መገታት ይኖርበታል ብለዋል፡፡
ሶስቱ ጋዜጠኞችና ስድስቱ ጦማርያን ሶስት ወራት ለሚሆን ጊዜ ይህ ነው የሚባል ክስ ሳይመሰረትባቸው ያለአግባብ በእስር ላይ መቆየታቸውንና አንዳንዶቹም በምርመራ ወቅት እንግልት እንደደረሰባቸው መናገራቸውን የጠቀሰው ደብዳቤው፣ ይህም አግባብ አለመሆኑን ገልጿል፡፡
ጋዜጠኞቹና ጦማርያኑ በተመሰረተባቸው የሽብርተኝነት ክስ በረጅም አመታት እስር ብሎም በሞት ሊቀጡ እንደሚችሉ ስጋታቸውን የገለጹት ድርጅቶቹ፤ ይህም አለማቀፍ ህጎችን የሚጥስና በቀጠናው የተረጋጋ ሰላምና ደህንነት ለመፍጠር የሚደረገውን አለማቀፍ ጥረት ዋጋ የሚያሳጣ እርምጃ ይሆናል ብለዋል፡፡
መንግስት አግባብነት በሌለው የጸረ ሽብርተኝነት ህግ በቁጥጥር ውስጥ አውሎ ክስ የመሰረተባቸውን ጋዜጠኞችና ጦማርያን በአፋጣኝ ከእስር እንዲለቅ አስፈላጊውን ሁኔታ እንዲያመቻቹ ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ጥያቄ ያቀረቡት እነዚህ ድርጅቶች፤ ከዚህ በፊት በተመሳሳይ ሁኔታ በጸረ ሽብር ህጉ ተከሰው የተፈረደባቸው ዜጎች ጉዳይ አግባብ አለመሆኑን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሳይቀር እንዳመነበትና እንዳወገዘው አስታውሰዋል፡፡
ከጋዜጠኞቹና ከጦማርያኑ በተጨማሪም፣ ከዚህ በፊት በሽብርተኝነት ተከሰውና ተፈርዶባቸው ያለአግባብ በእስር ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን በሙሉ መንግስት በአፋጣኝ እንዲፈታና የጸረ ሽብርተኝነት ህጉንም አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች መስፈርቶችን በሚያሟላ መልኩ እንደገና አሻሽሎ እንዲያጸድቅ ጠይቀዋል፡፡ኢትዮጵያ የአለማቀፉ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ስምምነትና የአፍሪካን የሰብዓዊና የህዝብ መብቶች ኮንቬንሽን ፈርማ የተቀበለች ሃገር እንደመሆኗ፣  መንግስት አለማቀፍ ህጎች የጣሉበትን ግዴታ በማክበር መሰረታዊ መብቶቻቸው ተጥሰው ለእስር የተዳረጉ ዜጎችን በሙሉ ከእስር እንዲለቅ ጠይቀዋል፡፡
ደብዳቤውን የጻፉት ድርጅቶች የሚከተሉት ናቸው፡፡
1. Amnesty International 
2. ARTICLE 19 Eastern Africa 
3. Central Africa Human Rights Defenders Network (REDHAC), Central Africa 
4. CIVICUS: World Alliance for Citizen Participation 
5. Civil Rights Defenders, Sweden 
6. Coalition pour le Développement et la Réhabilitation Sociale (CODR UBUNTU), Burundi 
7. Committee to Protect Journalists 
8. Community Empowerment for Progress Organization (CEPO), South Sudan 
9. Conscience International (CI), The Gambia 
10. East and Horn of Africa Human Rights Defenders Project 
11. Egyptian Democratic Association, Egypt 
12. Electronic Frontier Foundation 
13. Ethiopian Human Rights Project (EHRP) 
14. Elma7rosa Network, Egypt  15. English PEN 
16. Freedom Now 
17. Front Line Defenders, Dublin  18. Human Rights Watch 
19. International Women’s Media Foundation (IWMF) 
20. Ligue des Droits de la personne dans la region des Grands Lacs (LDGL), Great Lakes 
21. Ligue Iteka, Burundi 
22. Maranatha Hope, Nigeria 
23. Media Legal Defence Initiative
24. National Civic Forum, Sudan 
25. National Coalition of Human Rights Defenders, Kenya 
26. Niger Delta Women’s movement for Peace and Development, Nigeria 
27. Nigeria Network of NGOs, Nigeria  
28. Paradigm Initiative Nigeria, Nigeria  
29. PEN American Center  30. PEN International  
31. Réseau africain des journalistes sur la sécurité humaine et la paix (Rajosep), Togo  
32. Sexual Minorities Uganda (SMUG), Uganda  
33. South Sudan Human Rights Defenders Network (SSHRDN), South Sudan 
34. South Sudan Law Society, South Sudan  
35. Tanzania Human Rights Defenders Coalition, Tanzania 
36. Twerwaneho Listeners Club (TLC), Uganda 
37. Union de Jeunes pour la Paix et le Développement, Burundi  
38. WAN-IFRA (The World Association of Newspapers and News Publishers)  
39. West African Human Rights Defenders Network (ROADDH/ WAHRDN), West Africa
40. Zambia Council for Social Development (ZCSD), Zambia
41. Zimbabwe Human Rights NGO Forum, Zimbabwe

     የኢትዮጵያ የጤና መድህን ኤጀንሲ ከ “ጤና ለሁሉም ዘመቻ” ጋር በመተባበር ባዘጋጀው “የጤና መድህንን ለህዝብ የማስተዋወቅ ዘመቻ” አገር አቀፍ የዘገባ ውድድር ያሸነፉ ጋዜጠኞችን ከትናንት በስቲያ በኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ባከናወነው ስነስርዓት ሸለመ፡፡
የህትመት፣ የቴሌቪዥን፣ የሬዲዮና የድረ-ገጽ በሚሉ አራት ምድቦች በተከፋፈለውና ጋዜጠኞች የማህበራዊ ጤና መድህንን በተመለከተ ለአንባቢ፣ ለተመልካችና ለአድማጭ ያቀረቧቸውን ዘገባዎች ለውድድር ባቀረቡበት በዚህ ውድድር ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ የወጡ አሸናፊዎች ከኤጀንሲው ተጠባባቂ ዋና ዳይሬክተር ከዶ/ር መንግስቱ በቀለ እጅ የላፕቶፕ፣ የዘመናዊ ሞባይል ቀፎ፣ የፎቶግራፍ ካሜራና የሰርተፍኬት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
ዶ/ር መንግስቱ ሽልማቱን ለአሸናፊዎች ከሰጡ በኋላ ባደረጉት ንግግር፤ ጋዜጠኞች፣ የድረ-ገጽ ጸሃፊያንና መገናኛ ብዙሃን ጉዳዩን በተመለከተ በህብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤ በመፍጠር  ኤጀንሲው ለያዘው ዕቅድ መሳካት ትልቅ ሚና እንደሚጫወቱ ጠቅሰው፣ ኤጀንሲው በቀጣይም መሰል ስራዎችን በቅንጅት መስራቱን እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የ “ጤና ለሁሉም ዘመቻ” ዳይሬክተር ወ/ሮ ህይወት እምሻው በበኩላቸው፣ የጤና መድህን በገንዘብ እጦት ምክንያት ተገቢውን የህክምና አገልግሎት ለማግኘት ተቸግረው በህመም ለሚሰቃዩና ለሞት ለሚዳረጉ ዜጎች ትልቅ መፍትሄ እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡
የጤና መድህን ስርዓትን በተመለከተ በህብረተሰቡ ውስጥ በቂ ግንዛቤ በመፍጠር ረገድ ብዙ ስራ መሰራት እንዳለበት ጠቁመው፣ በዕለቱ ለሽልማት የበቁትም ሆኑ ሌሎች ጋዜጠኞች ስርዓቱን ለመዘርጋት በሚደረገው ቀጣይ እንቅስቃሴ ውስጥም የራሳቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ከመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳይ ቢሮና ከብሮድካስት ባለስልጣን የተውጣጡ የውድድሩ ዳኞች ባካሄዱት ግምገማ፤ በህትመት ዘርፍ መላኩ ብርሃኑ ከአዲስ ጉዳይ መጽሄት፣ ምህረት አስቻለው ከሪፖርተር ጋዜጣ፣ ስመኝ ግዛው ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ በመውጣት ተሸልመዋል፡፡
በድረ-ገጽ ዘርፍ ጋዜጠኛ አንተነህ ይግዛው፣ ጋዜጠኛ ደመቀ ከበደ፣ ጋዜጠኛ ኢዮብ ካሣ ሲያሸንፉ፤ በሬዲዮ ዘርፍ ጋዜጠኛ ገዛኸኝ ተስፋዬ እና ጋዜጠኛ ገናናው ለማ ከደቡብ ክልል መገናኛ ብዙሃን፣ ጋዜጠኛ ገመቺስ ምህረቴ ከፋና ብሮድካስት ኮርፖሬት እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ በመውጣት፤ በቴሌቪዥን ዘርፍ ደግሞ ጋዜጠኛ ሰለሞን ገዳ በብቸኝነት አሸናፊ ሆኗል፡፡

ተቃዋሚዎች በአተገባበሩ ላይ ብሔራዊ መግባባት መፈጠር አለበት ይላሉ
የፀረ-ሽብር ህጉ የዛሬ ስድስት ዓመት ገደማ መውጣቱን ተከትሎ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና  ጋዜጠኞች በሽብርተኝነት ተከሰው መታሰራቸው በህጉ ላይ የከረረ ተቃውሞ የሚሰነዝሩ ወገኖች እንዲበራከቱ አድርጓል፡፡ አንድነት ፓርቲ መቃወም ብቻም ሳይሆን ህጉ ከእነአካቴው እንዲሰረዝ “የሚሊዮን ድምፆች ለነፃነት” በሚል ባደረገው የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ፣ ያቀደውን ያህል ድምፅ ማግኘቱን ጠቁሞ  ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንደሚወስደው መግለፁ አይዘነጋም፡፡
የፀረ-ሽብር ህጉ አወዛጋቢነት በአገር ውስጥ ብቻ የተወሰነ አይደለም፡፡ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት፤የፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች መታሰርን በመቃወም መንግስት ህጉን፣ተቺዎቹን ለማጥቂያነት እየተጠቀመበት ነው በማለት ይኮንናሉ፡፡   
 የግንቦት 7 ዋና ፀሃፊ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ የመን ላይ ተይዘው ለኢትዮጵያ መንግስት መተላለፋቸውን ተከትሎ አራት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር አባላት ተይዘው መታሰራቸው (በሽብርተኝነት የተከሰሱትን  ጦማሪዎችና ጋዜጠኞች ጨምሮ) በብዙዎች ዘንድ ስጋትን ፈጥሯል፡፡ ፓርቲዎቹም የፖለቲከኞቹን መታሰር  በመቃወም መግለጫዎች አውጥተዋል፡፡ ለመሆኑ በሽብር ወንጀል እየተጠረጠሩ የሚታሰሩ ዜጐች መበራከት በአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ ላይ ምን አንደምታ ይኖረው ይሆን? በቀጣይስ ሀገሪቷን ወዴት ይመራታል? በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የፓርቲ አመራሮችና የህግ ባለሙያዎች የሰጡንን አስተያየት እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡


“በኢትዮጵያ ሽብርተኛ ማለት ነፃነትን መሻት፣ እውነትን መፈለግ ነው”
(ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር)

ሽብርና ሽብርተኝነት አሁን በኢትዮጵያ ባለው ግንዛቤ፤ እውነት ለሚናገሩ፣ለህብረተሰቡ መብት መከበር ለሚቆሙ፣ መንግስትን አምርረው ለሚተቹ ሰዎች የሚሰጥ ስም ነው፡፡ በየጊዜው ሽብርተኛ እየተባሉ የሚታሠሩት የማህበረሰብ መሪዎች፣ ጋዜጠኞችና የፖለቲካ መሪዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ሽብርተኛ ማለት  ነፃነትን መሻት፣ እውነትን መፈለግና  መንግስትን መተቸት ሆኗል፡፡
መንግስት ሰዎችን በብዛት ማሰሩ አቅመቢስ እየሆነ መምጣቱን ያሳያል፡፡ የህዝብ ጥያቄ እያሸነፈ መንግስት  ተቀባይነት እያጣ ሲመጣ ነው ሁሉን ነገር በጉልበት ለማድረግ የሚፈልገው፡፡ በአንፃሩ እውነትን የሚፈልጉ ሰዎች በታሰሩ ቁጥር የነፃነት ትግሉ እየተፋፋመ እንደሆነ ነው የሚያሳየው፡፡ በዚህ ረገድ እኔ ብሩህ ተስፋ ይታየኛል፡፡ ምክንያቱም ለእውነት ብለው ለመታሰር የሚደፍሩ ሰዎች (እነ አንዷለም ከታሰሩበት ጊዜ ጀምሮ) እየበዙ ነው፡፡ ለመታሰር ዝግጁ የሆኑ ሰዎች በዙ ማለት ወደ ለውጥ መቅረባችንን ያመለክተናል፡፡


አዋጁ በአግባቡ እየተተረጐመ አይደለም”
ዶ/ር ጫኔ ከበደ፤ የኢዴፓ ሊቀመንበር)


በአጠቃላይ መንግስት እየተከተለ ያለው አካሄድ ለዲሞክራሲ ግንባታው በጣም እንቅፋት እየፈጠረ ነው፡፡ በተለይ የፀረ ሽብር አዋጅን በተመለከተ የአተረጓጐም ስህተት እየተከተለ ነው የሚል ግንዛቤ አለን፡፡
የፀረ ሽብር ህግ ቢያስፈልገንም አተረጓጐሙ ግን በአግባቡ መሄድ አለበት፡፡ መንግስት የራሱን ጥቅም ለማስከበርና የገዥውን ፓርቲ እድሜ ለማራዘም ብቻ የተናገረውንም፣ ጦር ይዤ እታገላለሁ የሚለውንም፣ የሚጽፍበትንም--- በአጠቃላይ ገዥውን ፓርቲ የማይደግፈውን  ሁሉ በሽብር ስም ማሠሩ የተሳሳተ አካሄድ ነው፡፡
ይሄ አጠቃላይ የዲሞክራሲ ሂደቱን የሚያስተጓጉል ሲሆን የህብረተሰቡንም መብት የሚጫን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎቹንም አካሄድ ሊያበላሽ የሚችል፤ ወደ ኋላ እየመለሰን ያለ አካሄድ እንደሆነ ኢዴፓ ያምናል፡፡
ከዚህ አንፃር ገዥው ፓርቲ፣ ለዲሞክራሲ ግንባታ ምንም አይነት ቁርጠኝነት እያሳየ አለመሆኑን እንዲሁም  የስርአት ለውጥ በተጨባጭ ከምርጫ ሳጥን እንዳይገኝ፣ መጪውን ምርጫ ለማበላሸት እየተከተለው ያለው መንገድ ነው ብለን እናምናለን፡፡
የኛ ፓርቲ ብሔራዊ መግባባትን እንደ አንድ ትልቅ አጀንዳ ይዞ ይንቀሳቀሳል፡፡ መንግስት ብሔራዊ መግባባት መፈጠር አለበት ሲባል “የተጣላ ሰው የለም፤ማንን ከማን ለማግባባት ነው” የሚል መልስ ይሰጣል፡፡ ነገር ግን ገዥው ፓርቲ ቆም ብሎ በዚህ ጉዳይ ላይ ማሰብ አለበት፡፡ ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎችም በተለያዩ ዲፕሎማሲያዊ አካሄዶች መንግስትን ብሔራዊ መግባባት እንዲፈጠር የምንጠይቅበትን አካሄድ በጋራ መፈለግ ይገባናል። አለበለዚያ ለህዝባችን ምንም ነገር ሳንሰራ፣ የቆምንለትን አላማ ሳናሳካ እንዲሁ ዝም ብለን ጊዜ መፍጀት ይሆናል፡፡
በፀረ ሽብር ህጉም ላይ ቢሆን የጋራ ግንዛቤና መግባባት መያዝ ያስፈልጋል፡፡ ህጉ በጣም አስፈላጊ ነው፤ በአተረጓጐሙ ዙሪያ ግን የጋራ ግንዛቤ ሊኖረን ይገባል፡፡ ሲረቀቅ ጀምረን እስካሁን በአተረጓጐሙ ላይ ተቃውሟችንን ስናቀርብ ቆይተናል፡፡ በህጉ አተረጓጐም ላይ የጋራ ግንዛቤ ሊኖረን ይገባል፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ተቃራኒ ሃሳብን ለማስተናገድ ዝግጁ መሆን ይጠበቅባቸዋል፡፡ እንደውም ተቃዋሚ ፓርቲዎች በጋራ ቁጭ ብለን መግባባት ይኖርብናል፡፡


 “ሽብርተኛ ስለመሆናቸው መንግስት ተጨባጭ ማስረጃ አያቀርብም”

(አቶ ጥላሁን እንደሻው፤ የመድረክ አመራር)


በሠላማዊ ትግሉና ሠላማዊ ታጋዮች ላይ በሽብርተኝነት ስም የሚወሰዱት እርምጃዎች፣ሽብርተኝነት የሚለውን ስያሜ በአግባቡ እንዳንረዳ እያደረገን ነው ያለው፡፡ ሽብርተኝነት ሲባል በአለማቀፍ ደረጃ የታወቁ ነገሮች አሉ፡፡ አሸባሪዎች በሃይል አስፈራርተው የራሳቸውን ፖሊሲና አማራጭ ሌላው እንዲከተል በማድረግ፣ “ይሄን ባታደርግ እንዲህ አደርጋለሁ” የሚሉ ናቸው፡፡ መድረክም ይህን መሰሉን ድርጊት አጥብቆ ይቃወማል፡፡ አሁን በኛ ሀገር እነዚህ አሸባሪ ተብለው የሚወነጀሉ ሰዎች ይሄንን አድርገዋል ወይ? ማንን ነው ያስገደዱት? ማንን ነው ያስፈራሩት? በማን ላይ ነው እርምጃ የወሰዱት? በሚለው ላይ መንግስት በተጨባጭ ማስረጃ አያቀርብም፡፡ በዚህም ሳቢያ እኛም አሸባሪ ስለመሆናቸው ምንም ልንገነዘብ አልቻልንም፡፡ ጭራሽ አሸባሪ በሚለው ጉዳይ ላይ ግራ እንድንጋባ እየሆንን ነው፡፡ ሽብርተኝነት የሚለው በራሱ ግልጽነት ይጐድለዋል፡፡
መንግስት የሽብርተኝነትን ትርጓሜ ጥርት አድርጐ ባለማስቀመጡ፣ ህጉን ሠላማዊ ሰዎችን ለማስፈራሪያነት እየተጠቀመበት ነው የሚል ስጋት አለን፡፡ የሽብር ክሶችና እስራት እየተጠናከረ መቀጠሉ ምርጫው እየተቃረበ ሲመጣ፤ ለማሸማቀቅና የፍርሃት ድባብን ህዝብ ላይ ለመጫን ነው፡፡ ህዝብ በፍርሃትና በመሸማቀቅ የተሣተፈበት ምርጫ ደግሞ ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ሊሆን አይችልም። ሰው ተደፋፍሮ ከውስጡ መሸማቀቅና ፍራቻን እንዲያስወግድ ከተፈለገ፣ አሸባሪን ከሰላማዊ ትግል የሚለይ ነገር መቀመጥ አለበት፡፡ አለበለዚያ አሁን የተያዘው የሽብርተኝነት ግንዛቤ በምርጫም ሆነ በፖለቲካ ሠላማዊ ትግል ላይ አሉታዊ ተጽእኖ ያሳድራል፡፡ ግንዛቤውን ለማጥራትም ሆነ ችግሩን ለመፍታት ብሔራዊ መግባባት ያስፈልገናል። ሽብርተኝነት ምንድን ነው በሚለው ጉዳይ ላይ ብሔራዊ መግባባት ሊኖረን ይገባል፡፡ ሽብርተኝነትን እንዴት በጋራ እንታገል በሚለው ላይም በተመሳሳይ የጋራ መግባባት መፈጠር አለበት፡፡ ብሔራዊ መግባባት ካለ የሽብር አደጋዎችን ሁሉ መከላከል እንችላለን፡፡ ገዥው ፓርቲ የውይይት በሮችን ሁሉ መዝጋቱን ትቶ፣ ተቃዋሚዎችን እንደጠላት መመልከቱን አቁሞ፣ ብሔራዊ መግባባት የሚፈጠርበትን የውይይት መድረክ ሊያመቻች  ይገባዋል፡፡

===========
“አዋጁ የምርጫ 97 ውጤት ነው”
(ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው፤ የአንድነት ሊቀመንበር)

ፓርቲዬ አንድነት የፀረ - ሽብር አዋጁ፤ የዲሞክራሲ ሂደቱን የማፈን ጥረት ውጤት ነው ብሎ ያምናል፡፡ በዚህ መሠረት በ“የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት” ላይ በዋናነት የፀረ ሽብር ህጉ እንዲሰረዝ ጠይቀናል፡፡ ህጉ ከየት መጣ ብለን ከጠየቅን፣የምርጫ 97 ውጤት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ኢህአዴግ በነፃ ምርጫ ማሸነፍ እንደማይችል ሲረዳ፣ የዲሞክራሲ ተቋማትን የማፈን እንቅስቃሴ ውስጥ ነው የገባው፡፡ ሚዲያዎችን፣ ፓርቲዎችን፣ሲቪል ማህበራትን ማፈን የሚለውን እንደ አማራጭ ለመጠቀም ስለፈለገ፣ በእያንዳንዱ ጉዳይ አዋጅ አውጥቶበታል፡፡ ስለዚህ የፀረ ሽብር ህጉም የዲሞክራሲ ስርአቱን ሙሉ ለሙሉ ለማዳፈን የወጣ ነው ብለን እናምናለን፡፡
እኛ የፀረ ሽብር ህጉ መሠረዝ አለበት ስንል፣ ሽብርተኝነትን እንደግፋለን ማለት አይደለም፡፡ ከማንም በላይ ሽብር ለሃገራችን አስጊ ነው በሚል እምነት፣ ፓርቲዬም ሆነ እኔ ከመንግስት ጐን ተሠልፈን የምንዋጋው ጉዳይ ነው፡፡ ነገር ግን አሁን  ያለው አዋጅ እየተተረጐመበት ባለው አግባብ ላይ ከፍተኛ ጥያቄ አለን፡፡
ሚዲያው አካባቢ ሲኬድ በከፍተኛ ሁኔታ ራሱን በራሱ የሚገድብ (Self censorship) ሆኗል። ሲቪል ሶሳይቲውም የኢህአዴግን ቡራኬ ካላገኘ መኖር አይችልም፡፡ ይሄ ዲሞክራሲውን በእጅጉ ይጐዳል፡፡
ኢህአዴግ ኳሱ በእጁ ነው፡፡ ሁኔታዎች በዚህ መልኩ ሊቀጥሉ አይችሉም፡፡ የሆነ ቦታ መቆማቸውም አይቀርም፡፡
ስለዚህ ዲሞክራሲው እንዳይቀጭጭ፣ እንዳይጐዳ ኳሱን በእጁ የያዘው ኢህአዴግ ቆም ብሎ ማሰብ ይኖርበታል፡፡ የዲሞክራሲ ሂደቱ በሚፈቅደው መጠንም ብሔራዊ መግባባት ላይ እንዲደረስ መድረኩንም መፍጠር አለበት፡፡ እኛ በዚህ አዋጅ ላይ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ በፍትህና በዲሞክራሲያዊ ስርአቱ ላይ ከብሔራዊ መግባባት የሚያደርስ ውይይት እንዲፈጠር እንፈልጋለን፡፡ ብሔራዊ መግባባት መኖር አለበት፡፡   


“ህጉ ለኛ አስፈላጊ ነው ወይ?”

(አቶ ተማም አባቡልጉ፤ ጠበቃና የህግ አማካሪ)

ብዙ ሰው ህጉ በአግባቡ መተርጐም አለበት በሚለው ላይ ነው ጥያቄ የሚያነሳው፡፡ እኔ ደግሞ ህጉ ለኛ አስፈላጊ ነው ወይ የሚለውን ነው የምጠይቀው፡፡ ህጉ ላይ የተጠቀሱት ነገሮች እኮ በወንጀለኛ ህጉ ላይ አሉ፡፡ እንደገና በሌላ መልክ መምጣታቸው አግባብ አልነበረም፡፡ በዚህ ጉዳይ የሚከሰሱ ሰዎችን ስንመለከት ፖለቲከኞች ናቸው፡፡ ከዚህ አንጻር “ህጉ ለማጥቂያነት አልዋለምን?” የሚል ጥያቄ ያስነሳል፡፡ የሽብር አዋጅ በየትኛው ዓለም ቢሆን በአገር ላይ የሚደርስን ጥቃት  የሚከላከል እንጂ ፓርቲን፣ ጋዜጣንና ሃሳብን በነፃነት መግለጽን አይደለም መገደብ ያለበት፡፡ ለምሣሌ ሩዋንዳ በህጓ ላይ ሃሳብን የመግለጽ ነፃነትን በተመለከተ፣ ቀጥታ የጅምላ ጭፍጨፋን የሚያነሳሱ ሃሳቦችን ለይታ ነው ገደብ ያበጀችው፡፡ የኛ ግን ጥቅል ነው፡፡ ይሄን አይመለከትም ተብሎ ተለይቶ መቀመጥ አለበት። በእንግሊዝ ሀገር ህጉ ሲወጣ ፖለቲከኞች “አንዴ ስልጣን ላይ የወጣው መንግስት ስልጣን እንዳይለቅ የማድረጊያ መንገድ ሆኗል” ብለው ነው ህጉን ኋላ ላይ ያስቀሩት፡፡ ስለዚህ በኛም ሃገር ህጉ ለፖለቲካ ማጥቂያ አይውልም ተብሎ አይታሰብም፡፡

  •      መንገደኞች በአውሮፕላን መጓዝ እየፈሩ ነው፣ ባለሙያዎች አደጋ ቀንሷል እያሉ ነው
  • የኢንሹራንስ ኩባንያዎች በአመት 65 ሚ. ዶላር ይሰበስባሉ፣ በ5 ወር ብቻ 600 ሚ. ዶላር ካሳ ይከፍላሉ

            አመቱ ለአለማችን የአየር ትራንስፖርት የቸር አልሆነም - በተለይ ደግሞ ለማሌዢያ፡፡ ከወራት በፊት የማሌዢያ አየርመንገድ ቦይንግ 777 አውሮፕላን 239 ሰዎችን ይዞ ከኳላላምፑር ወደ ቤጂንግ በመብረር ላይ ሳለ፣ ድንገት ከራዳር እይታ ውጭ ሆነ፡፡ አለም ድንገት ደብዛው የጠፋውን አውሮፕላን ፍለጋ ውቅያኖስ አሰሰ፤ ከወዲያ ወዲህ ተራወጠ፤ ወደ ሰማይ አንጋጠጠ፡፡ ከዛሬ ነገ ይገኛል በሚል ተስፋ ፍለጋው ለወራት ዘለቀ - ተስፋ እንደራቀ፡፡ አንዳች እንኳን ተጨባጭ መረጃ ሳይገኝ፤ አውሮፕላኑን የበላው ጅብ ሳይጮህ፣ ነገሩ እንቆቅልሽ እንደሆነ ዘለቀ፡፡ ማሌዢያ በላይዋ ላይ የደረበችውን ማቅ ሳታወልቅ፣ ያለፈው ሃዘን ሳይወጣላት፣ በሆነው ነገር ሳትጽናና ሌላ ነገር ሆነ - ሌላ አውሮፕላኗ በአሰቃቂ ሁኔታ ተከሰከሰ፡፡ ይህ ክስተት ለማሌዢያ ብቻም ሳይሆን ለአጠቃላዩ የአቪየሽን ኢንዱስትሪና ለመላው አለም አስደንጋጭ መርዶ ነበር፡፡

የማሊዢያው አየር መንገድ አውሮፕላን ከቀናት በፊት በበረራ ቁጥር ኤም ኤች 17 ከአምስተርዳም ተነስቶ ወደ ኳላላምፑር በመጓዝ ላይ እያለ፣ ዩክሬንንና ሩስያን በሚያዋስነው ድንበር ላይ በሚሳዬል ተመትቶ መውደቁንና 298 ሰዎች መሞታቸውን ተከትሎ፣ ግጭት ባለባቸው አካባቢዎች የአየር ክልል ውስጥ መብረር ወይም አለመብረር የዓለማችን ታላላቅ አየር መንገዶች ዋነኛ ጥያቄና ጭንቀት ሆኗል፡፡ ብዙዎቹ አለማቀፍ የሲቪል አቪዬሽን ተቆጣጣሪዎች በዚህ የግጭት አካባቢ በረራ እንዳያደርጉ በአየርመንገዶች ላይ እገዳ ባለመጣላቸው ወይም ማስጠንቀቂያ ባለመስጠታቸው፤ አብዛኛዎቹ አየርመንገዶች የአየር ክልሉን በማቋረጥ ከአውሮፓ ወደ ደቡብ ምስራቅ እስያ መጓዛቸውን ቀጥለው ነበር፡፡ በአካባቢው የተቀሰቀሰው ግጭት ስጋት ያጫረባቸው ኤር በርሊን፣ ኮሪያን ኤርና ኤር ስፔስን የመሳሰሉ የተለያዩ አገራት አየር መንገዶች ግን፣ ወደዚህ አየር ክልል ድርሽ ማለት ካቆሙና ዙሪያ ጥምጥም መብረር ከጀመሩ ወራት አልፏቸዋል፡፡ “መሰል ግጭቶች ያሉባቸው አካባቢዎች ለአየር መንገዶችና ለአጠቃላዩ የአለማችን የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ስጋት ሆነዋል፡፡

እኛም ስጋት ስለገባን በተቻለን መጠን ከአካባቢዎቹ ስንርቅ ቆይተናል፡፡ ከግጭት አካባቢዎች ለመሸሽ የበረራ መስመሮችን መቀየር፣ ለተጨማሪ ወጪ መዳረጉ አይቀሬ ነው። አየር መንገዳችን ግን፣ ለደህንነት ሲል ተጨማሪ ወጪ ሲያወጣ ነው የቆየው” ብለዋል የኤዥያና አየር መንገድ ቃል አቀባይ፡፡ የማሌዢያ ትራንስፖርት ሚኒስትር ሊሎ ቲዮንግ የአገራቸው አውሮፕላን ከሰሞኑ አደጋ ላይ መውደቁን ተከትሎ ከተለያዩ አካላት ለምን በአደገኛ አየር ክልል ውስጥ በረረ በሚል የተሰነዘረበትን ትችት አልተቀበሉትም፡፡ “ይህን የአየር ክልል እያቋረጥን መጓዝ ከጀመርን አመታት ተቆጥረዋል፡፡ ምንም የገጠመን ችግር አልነበረም፡፡ ደህንነቱ የተረጋገጠ ክልል ነው፡፡ ሌሎች አየር መንገዶችም ይሄን ክልል እያቋረጡ መብረራቸውን ቀጥለዋል፡፡ ታዲያ እኛ ለምንድን ነው የምናቆመው?” ሲሉ ጠይቀዋል ቲዮንግ፡፡ የማሌዢያው አየር መንገድ አውሮፕላን አደጋ ኣለምን አሳዝኖ ሳያበቃ፣ ከቀናት በኋላም ሌላ አሳዛኝ ክስተት ተፈጠረ፡፡

በበረራ ቁጥር ጂ ኢ 222 በረራ ላይ እያለ ባጋጠመው አስቸጋሪ የአየር ጠባይ ሳቢያ፣ በታይዋኗ የፔንጉ ደሴት ለማረፍ በመሞከር ላይ የነበረውና ንብረትነቱ የትራንስ ኤዥያ አየር መንገድ የሆነው አውሮፕላን ታይዋን አካባቢ ተከሰከሰ፡፡ 47 ሰዎችም ለህልፈተ ህይወት ተዳረጉ፡፡ የአቪየሽን ዘርፉ መርዶ አላበቃም፡፡ ባለፈው ረቡዕ ደግሞ ሌላ አሳዛኝ የአቪየሽን ኢንዱስትሪ መርዶ ተሰማ፡፡ 116 ተሳፋሪዎችን ይዞ በበረራ ቁጥር ኤኤች 5017 ከቡርኪናፋሶ በመነሳት ወደ አልጀርስ በመጓዝ ላይ የነበረ ንብረትነቱ የኤር አልጀሪያ አየር መንገድ የሆነ አውሮፕላን በአሰቃቂ ሁኔታ ተከሰከሰ፡፡ ቀጠለናም የታይዋን አየርመንገድ አውሮፕላን ተከስክሶ ከ50 በላይ ሰዎች ለህልፈተ ህይወት ተዳረጉ፡፡ እነዚህ ሰሞንኛ አሰቃቂ አደጋዎች፣ ብዙዎች የአቪየሽን ኢንዱስትሪውን እንዲጠራጠሩት አድርጓል ይላል ዩ ኤስ ቱዴይ፡፡ አደጋዎቹ አንድ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ መከሰታቸውን በጥርጣሬ ያዩት እንዳሉ የጠቆመው ጋዜጣው፣ የኢንዱስትሪው ኤክስፐርቶች ግን ነገሩ ከሁኔታዎች መገጣጠም የዘለለ ትርጉም የለውም ስለማለታቸው ዘግቧል፡፡ “የማሌዢያው ተመትቶ፣ የትራንስ ኤዢያው ደግሞ በአየር ጠባይ ሳቢያ ነው አደጋ የደረሰባቸው። የሁለቱ አደጋዎች በተቀራራቢ ጊዜ መከሰት አጠቃላዩን ኢንዱስትሪ ስጋት ላይ የሚጥልም ሆነ፣ ተሳፋሪዎች የአውሮፕላን ጉዞ አደገኛ ነው ብለው እንዲደመድሙ የሚያስችላቸው አይደለም” ብለዋል በፍራንሲስኮ አትሞስፌር ምርምር ተቋም የጉዞ ተንታኝ የሆኑት ሄነሪ ሃርቲልት፡፡

ጆን ቤቲ የተባሉት የበረራ ደህንነት ፋውንዴሽን ፕሬዚደንትም ቢሆኑ፣ የአቪየሽን ኢንዱስትሪው እንደተባለው ደህንነት የጎደለውና መንገደኞችን ስጋት ላይ የሚጥል፣ ሌላ አማራጭ እንዲወስዱ የሚያነሳሳበት ደረጃ ላይ አይደለም ባይ ናቸው፡፡ “ባለፉት አስርት አመታት የአለማቀፉ የንግድ አቪየሽን ደህንነት እጅግ የሚገርም ደረጃ ላይ ደርሷል። አልፎ አልፎ መሰል አደጋዎች ሊፈጠሩ ቢችሉም፣ ክስተቶቹ የኢንዱስትሪውን አስተማማኝነት ጥያቄ ውስጥ አያስገቡትም። አደጋዎቹ አሳዛኝ ናቸው፤ የንግድ አቪየሽንም አሁንም ድረስ መቢገርም ሁኔታ ደህንነቱ የተረጋገጠ ነው!” ብለዋል ቤቲ፡፡ አመቱ ለአየር መንገዶች የመከራ ነበር የሚሉ ተበራክተዋል፡፡ የስታር ዶት ኮሙ ዘጋቢ ቫኔሳ ሉ ግን፣ ይህ አመት የአለማችን የንግድ አቪየሽን ከቀደምት አመታት የተሻለ ከአደጋ ነጻ የነበረበት ነው፡፡ የአለማቀፉ የአቪየሽን ደህንነት ኔትዎርክ ፕሬዚደንት ጠቅሶ ዘጋቢው እንዳለው፣ በዚህ አመት የተከሰቱ አደጋዎች ቁጥር ባለፉት አስር አመታት ከተከሰቱት አደጋዎች አማካይ ቁጥር በእጅጉ ያነሰ ነው፡፡ እርግጥ በአንድ አደጋ ለሞት የሚዳረጉ የአውሮፕላን ተሳፋሪዎች ቁጥር እየጨመረ መጥቷል፡፡

በቅርቡ በተከሰከሱት ሁለቱ የማሌዢያ አውሮፕላኖች ብቻ 537 ሰዎች ለሞት ተዳርገዋል፡፡ ዘስታር ዶት ኮም እንደዘገበው፣ በዚህ አመት ብቻ በአለማችን 11 አሰቃቂ የአውሮፕላን አደጋዎች ተከስተዋል፡፡ የአለማቀፉን የአየር ትራንስፖርት ማህበር መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ባለፈው አመት በተከሰቱ መሰል 11 አደጋዎች የሞቱ ሰዎች ቁጥር 210 ነበር፡፡ ባለፈው አመት በአለማቀፍ ደረጃ ከ36 ሚሊዮን በላይ በረራዎች ተደርገው፣ ከ3 ቢሊዮን በላይ መንገደኞች ያለምንም አደጋ ካሰቡበት መድረሳቸቸውንም መረጃው ያስታውሳል። በመሆኑም የኢንዱስትሪው ደህንነት አደጋ ላይ ነው ብሎ ለመደምደም የሚያበቃ ምንም ነገር የለም፡፡ በቅርብ የተከሰተውን የማሌዢያው አየር መንገድ አደጋ ተከትሎ ስጋት ውስጥ የገቡት መንገደኞችና አየርመንገዶች ብቻም አይደሉም፡፡ የአውሮፕላን ኢንሹራንስ ኩባንያዎች ጭምርም እንጂ፡፡

ኒውዮርክ ታይምስ ከሰሞኑ እንደዘገበው፣ ለአየር መንገዶች የአደጋ ዋስትና የሚሰጡ ታላላቅ የኢንሹራንስ ኩባንያዎች በተደጋጋሚ በሚከሰቱ አደጋዎች ሳቢያ የሚያወጡት ወጪ እየናረ በመምጣቱ ጭንቀት ውስጥ ገብተዋል፡፡ በተለይ ደግሞ በጦርነት ቀጠናዎች አካባቢ ለሚንቀሳቀሱ አውሮፕላኖች ዋስትና የሚሰጡ የኢንሹራንስ ኩባንያዎች የችግሩ ዋነኛ ገፈት ቀማሽ ሆነዋል፡፡ የጦርነት አደጋ ዋስትና ደንበኞቻቸው ከሆኑ አየር መንገዶች በአመት በድምሩ 65 ሚሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ የሚሰበስቡ የኢንሹራንስ ኩባንያዎች፣ ባለፉት አምስት ወራት ብቻ በአውሮፕላኖች ላይ ለተከሰቱ አደጋዎች 600 ሚሊዮን ዶላር የካሳ ክፍያ መክፈላቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ኩባንያዎቹ ምን ያህል ለከፍተኛ ወጪ እንደተዳረጉና የኪሳራ ሰለባ እየሆኑ እንደሚገኙ ገልጧል፡፡ ተደጋግመው የሚሰሙት የአውሮፕላን አደጋዎች መንገደኞችን ስጋት ውስጥ ከቷቸዋል። ዘጋርዲያን ከትናንት በስቲያ ባስነበበው ጽሁፉ እንዳለው፣ ተደጋግመው የተከሰቱት የአውሮፕላን አደጋዎች አንዳንዶች ይህን የትራንስፖርት ዘርፍ በጥርጣሬና በስጋት እንዲያዩት አድርገዋቸዋል፡፡ በአውሮፕላን መጓዝ ለመሞት ፈቅዶ ትኬት መቁረጥ ነው ብለው ማሰብ የጀመሩ አልታጡም። ዘጋርዲያን ግን፣ ይህ ጅልነት ነው ይላል፡፡

የአለማቀፉን የሲቪል አቪየሽን ድርጅት መረጃ ጠቅሶ ዘጋርዲያን እንደጻፈው፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት በአለማቀፍ ደረጃ በተደረጉ በረራዎች የተከሰቱ አደጋዎች ሲሰሉ፣ ከ300 ሺህ በአንዱ ላይ ብቻ ነው አደጋ የተከሰተው፡፡ ይህም በአውሮፕላን አደጋ እሞት ይሆን የሚለው ስጋት ከንቱ መሆኑን ያሳያል ይላል ዘገባው፡፡ እንዲህ ያለ ስጋት የገባችሁ መንገደኞች፣ ከአደጋው ይልቅ ስጋቱ ይገላችኋል ያለው ዘጋርዲያን፣ ለዚህም የአሜሪካውን የመንትያ ህንጻዎች አደጋ በዋቢነት ይጠቅሳል፡፡ አደጋው በተከሰተ በቀጣዩ አመት በርካታ አሜሪካውያን አውሮፕላን ትተው መኪና ወደመጠቀም ዞሩ። የአውሮፕላን ተጠቃሚዎች ቁጥር እስከ 20 በመቶ ቀነሰ፡፡ በአንጻሩ ደግሞ መኪና ተጠቃሚው በመብዛቱ መንገዶች ተጣበቡ፡፡ ረጅም ርቀት ማሽከርከር ታዲያ፣ ከአውሮፕላን የባሰ ለአደጋ የሚያጋልጥ አስጊ ነገር ወደመሆን ተሸጋገረ፡፡ በአቪየሽን መስክ ጥናት በማድረግ የሚታወቁትን ጀርመናዊ ፕሮፌሰር ገርድ ጊገንዘርን ጥናት ጠቅሶ ዘገባው እንደጠቆመው፣ በዚያው አመት በአገሪቱ በመኪና አደጋ ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች ቁጥር በ1 ሺህ 595 ጭማሪ አሳየ፡፡ ቀስበቀስም አርም አውሮፕላን ብለው የነበሩ መንገደኞች ምርጫ በማጣት ፊታቸውን ወደ አውሮፕላን መልሰው አዞሩ፡፡

============

ባለፉት ሰባት ወራት በአለማችን የተከሰቱ የአቪየሽን አደጋዎች

ሃምሌ 24 የታይዋን አየር መንገድ አውሮፕላን ሃምሌ 23 የአልጀሪያ አየር መንገድ አውሮፕላን

ሃምሌ 23 የትራንስ ኤዥያ አየር መንገድ አውሮፕላን ሃምሌ 17 የማሌዢያ አየር መንገድ አውሮፕላን

ሃምሌ 7 የቬትናም አየር ሃይል አውሮፕላን

ሃምሌ 5 በፖላንድ የግል አየር መንገድ አውሮፕላን

ሃምሌ 2 የስካይዋርድ ኢንተርናሽናል አቪየሽን አውሮፕላን ሰኔ 14 የዩክሬን አየር ሃይል አውሮፕላን

ግንቦት 31 የማሳቹሴትስ የግል ቻርተርድ አውሮፕላን ግንቦት 17 የላኦስ አየር ሃይል አውሮፕላን ግንቦት 8 የአሊሳና ኮሎምቢያ አየር መንገድ አውሮፕላን ሚያዝያ 20 የሱሜን ኡርሂሊዩሊሜሊጃት አየር መንገድ አውሮፕላን ሚያዝያ 19 የሊኒያስ ኤሪያስ ኮመርሺያሌስ አየርመንገድ አውሮፕላን

ሚያዝያ 8 የሃጊላንድ አቪየሽን ሰርቪስስ አውሮፕላን

መጋቢት 28 የህንድ አየር ሃይል አውሮፕላን መጋቢት 22 የስካይዳይቭ ካቦልቸር አየርመንገድ አውሮፕላን

መጋቢት 18 የሄሊኮፕተርስ ኢንክ ኮሞ ቲቪ ሄሊኮፕተር

መጋቢት 8 የማሌዢያ አየርመንገድ አውሮፕላን

የካቲት 26 የማኦይ አየርመንገድ አውሮፕላን

የካቲት 21 የሊቢያ ኤር ካርጎ አውሮፕላን

የካቲት 16 የኔፓል አየር መንገድ አውሮፕላን

ጥር 20 የስኳላ ሱፐርየራ ዲ አቪየቴ ሲልቫ አውሮፕላን

ጥር 18 የትራንስ ጉያና አየር መንገድ አውሮፕላን

           ከእያንዳንዱ ስኬታማ ወንድ በስተጀርባ ሴት ትኖራለች የሚለው አመለካከት ከዓለም ዋንጫው ጋር በተያያዘ ሲያነጋግር ሰንብቷል፡፡ የታዋቂ እግር ኳስ ተጨዋቾች ሚስቶች፤ እጮኛዎችና የፍቅር ጓደኞች የእንግሊዝ ሚዲያዎች ‹‹ዋግስ› የሚል ስም አውጥተውላቸዋል፡፡ ከዝነኛ ስፖርተኞች ጋር ግንኙነት ያላቸው ሴቶች እንደማለት ነው፡፡ በዓለም ዋንጫው ሰሞን ሴቶቹ ከየብሄራዊ ቡድኑ ተጨዋቾች ጋር በነበራቸው ግንኙነት ዙርያ አሰልጣኞች ያወጧቸው አንዳንድ የስነምግባር ደንቦች አወዛግበዋል፡፡ በተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃናት የዝናቸው መጠን፤ ቁንጅናቸው፤ ለእግር ኳስ ባላቸው ፍቅር፤ ስለውድድሩ በሚሰጧቸው አስተያየቶች እየተነፃፀሩ ደረጃ ሲሰጣቸውም ነበር፡፡ ባሎቻቸውን ፤ እጮኛዎቻቸው እና ፍቅረኛዎቻቸውን ተጨዋቾችን ለማበረታት በየስታድዬሙ ማልያዎችን በመልበስ እና ባንዲራዎችን በማውለብለብ ድጋፍ በመስጠት ታውቀዋል። እነዚህ በዓለም ዋንጫው የደመቁ ሴቶች ልዩ ልዩ ሙያዎች ያላቸው ናቸው፡፡ ብዙዎቹ ሞዴሎች ናቸው። ተዋናዮች፣ ሙዚቀኞች፣ ጋዜጠኞችና የቤት እመቤቶችም ከመካከላቸው ይገኙበታል፡፡

ከጀርመን ጀርባ የነበረው ምስጥራዊ ግብረኃይል የጀርመን ብሄራዊ ቡድን 20ኛውን ዓለም ዋንጫ አሸንፎ በተሸለመበት የመዝጊያ ስነስርዓት የተጨዋቾች ሚስቶች፤ ፍቅረኛዎች፤ ጓደኞች እና ቤተሰቦች በጋራ ደስታቸውን ሲገልፁ መላው ዓለም በትዝብት የተከታተለው ነበር፡፡ በጀርመን ቡድን ዙርያ የተሰባሰቡት እነዚህ ሴቶች በዓለም ዋንጫው ተሳታፊ ቡድኖች ከታዩ ድጋፎች እንደተሳካላቸው የተለያዩ ዘገባዎች አውስተዋል፡፡ ዴይሊ ሜል ባቀረበው ዘገባ እንዳብራራው ለዓለም ዋንጫ ስኬት የቡድን አንድነት እና የላቀ ብቃት እንዲሁም የአሰልጣኞች የታክቲክ ፍልስፍና ከፍተኛ አስተዋፅኦ ቢኖራቸውም ፆታዊ ፍቅር የማይናቅ ሚና እንደነበረው የጀርመን ድል አረጋግጧል፡፡ የጀርመን ተጨዋቾች ሴቶቻቸውን ቁጥር አንድ ደጋፊዎቻን እያሉ ሲጠሯቸው ነበር፡፡ የተጨዋቾች ሚስቶች፤ ፍቅረኞች እና ቤተሰቦች የሻምፒዮናነት ሜዳልያውን በማጥለቅና ከሻምፒዮኖቹ ጋር ፎቶ በመነሳት እድለኞች ነበሩ። አንዳንዶቹ እንደውም ዋንጫዋን በመንካት እና በማቀፍ የማይገኝ ታሪክ ሰርተዋል፡፡ ከጀርመን የዓለም ዋንጫ ድል በኋላ በነበረው ፓርቲ ከፍተኛ ትኩረት አግኝተው ከነበሩ ዝነኛ ሴቶች ግንባር ቀደሟ በዋንጫው ጨዋታ ለጀርመን ድጋፍ የሰጠችው በርባዶሳዊቷ ሙዚቀኛ ሪሃና ነበረች፡፡

ሪሃና ከጀርመን ተጨዋቾች ጋር ባላት የቀረበ ግንኙት ከሻምፒዮናዎች ጋር አብራ መዝናናቷን ያወሳው ዴይሊ ሜል ጋዜጣ፤ ዓለም ዋንጫዋን በመንካት የፊፋ ስነምግባር እስከመተላለፍ መድረሷን በመጥቀስ ትችት አቅርቦባታል፡፡ ፊፋ ዓለም ዋንጫን ከመንግስታት መሪዎች ከአሸናፊ ብሄራዊ ቡድን አባላት በስተቀር ማንም እንዳይነካ የሚከለክል የስነምግባር ደንብ ነበረው፡፡ ሪሃና ግን ወደ ጀርመን ብሄራዊ ቡድን ሰርጋ በመግባት እንደፈለገች ፎቶዎች ተነስታ በሶሽያል ሚዲያ አሰራጭታለች፡፡ ሚሮስላቭ ክሎሰ፤ ሽዋንስታይገር እና ፖዶሎስኪ ዋና ምክንያቶች ነበሩ፡፡ ሜሲቲ ኦዚል ማልያውን አውልቆ ለሪሃና እንደሸለማትም ዴይሊ ሜል አትቷል፡፡ ጀርመን ዓለም ዋንጫውን ያሸነፈችበትን ግብ ያስቆጠረው ማርዮ ጎትዜ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ፍቅረኛውን አን ካተሪን ብሮሜል ፍቅሩን እየገለፀ በተደጋጋሚ ሲያመሰግናት ታይቷል፡፡ ‹‹በዚህ ታሪካዊ ድል የቤተሰቤ እና የፍቅረኛዬ አና ድጋፍ ልዩ ነበር፡፡ ሁሉም በእኔ ውጤታማነት ሙሉ እምነት ነበራቸው›› በማለት ማርዮ ጎትዜ የሴቶቹን ሚና ገልፆታል። ጎትዜ የጎሏን ያገባው መታሰቢያነት ለዚህችው የ25 ዓመት እጮኛው አድርጓታል፡፡

አና ካተሪን ብሮሜል በጀርመን የተሳካላት ሞዴል ስትሆን በፒያኖ ተጫዋችነትም እየታወቀች ነው፡፡ ዓለም ዋንጫውን ያደመቁት ሌሎች ሴቶች ጀርመንን የደገፉ ሴቶች በድል አድራጊነት ቢንበሻበሹም በዓለም ዋንጫው በርካታ ሴቶች በየሚደግፏቸው ብሄራዊ ቡድኖች ድምቀት ፈጥረዋል፡፡ የጣሊያኑ አጥቂ ማርዮ ባላቶሊ ዓለም ዋንጫው ሳይጀመር በዋዜማው ሰሞን እጮኛውን በማግኘቱ ቀዳሚውን ትኩረት መሳብ ችሎ ነበር፡፡ 100ሺ ፓውንድ በሚያወጣ ቀለበት ፋኒ ኔጉሻ ከተባለች ፍቅረኛው ጋር የተተጫጨው በብራዚል የባህር ዳርቻ ላይ ነው፡፡ ፋኒ የራሷ ስም የተፃፈበትን የጣሊያን ማልያ በመልበስ ሁሉንም የምድብ ጨዋታዎች ከሌሎች የጣሊያን ተጨዋቾች ሚስቶች እና ፍቅረኛሞች ጋር በየስታድዬሙ በመገኘት ተከታትላለች። ከሮናልዶ ጋር የፍቅር ጓደኝነት ከጀመረች 4 ዓመታት ያስቆጠረችው የ28 ዓመቷ ሩስያዊት ሱፕር ሞዴል ኤሪና ሻይክ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች በተሰጣት ሽፋን በቁንጅናዋ፤ በገቢዋ ከፍተኛነት የሚወዳደራት አልነበረም፡፡ የስፔን ብሄራዊ ቡድን ተከላካይ የሆነው ጄራርድ ፒኬ ጋር በፍቅር ጓደኝነት ከተሳሰረች 11 ዓመት ያለፋት ሻኪራ ደግሞ ዓለም ዋንጫ በሙዚቃዋ የገነነችበት ሆኗል፡፡ በ2010 እኤአ ለዓለም ዋንጫ ዜማ የነበረውን ዋካ ዋካ የሰራችው ሻኪም ለእግር ኳሱ ዓለም በመቅረብ የሚፎካከራት የለም፡፡ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ የመዝጊያው ስነስርዓት ላይ ደግሞ የሙዚቃ ኮንሰርቱ ዋና ሙዚቀኛ ኮሎምቢያዊቷ ስትሆን፤ በ2006፣ በ2010 እና በ2014 እ.ኤ.አ ላይ በተከናወኑት የዓለም ዋንጫ የመዝጊያ ስነስርዓቶች ሙዚቃ በማቅረብ የመጀመርያ ሆናለች፡፡ ኮሎምቢያዊቷ በ2010 እ.ኤ.አ የሠራችው “ዋካ ዋካ” የተሰኘው የዓለም ዋንጫ መሪ ዜማ ከዓለም ዋንጫ ዘፈኖች ከፍተኛውን ሽያጭ ያገኘ ነው፡፡ ሻኪራ በመላው ዓለም የአልበሞቿን 70 ሚሊዮን ቅጂዎች በመሸጥ የተሳካላት የላቲን ሙዚቃ ንግስት ናት፡፡

የሊዮኔል ሜሲን የበኩር ልጅ ቲያጐን የወለደችው አንቶኔላ ሬኩዞ በዓለም ዋንጫው ከታዩ እናቶች ተወዳጅነት ያተረፈችው ናት፡፡ ሜሲ 27ኛ ዓመት የልደት በዓሉን ከኢራን ጋር በተደረገ ጨዋታ ላይ አንድ ጎል አስቆጥሮ ሲያከብር አንቶኔላ ከልጃቸው ጋር በስታድዬም ተገኝታ ደስታዋን ገልፃለች፡፡ እስከፍጫሜው ድረስም አንድም የአርጀንቲና ጨዋታ አላመለጣትም፡፡ የዋይኔ ሩኒ የትዳር አጋር የሆነችው ኮሊን ሩኒ ሌላዋ አነጋጋሪ ሴት ናት፡፡ ኮሊን በራሷ ወጭ በዓለም ዋንጫው ሰሞን ካይ እና ክሌይ የተባሉ ሁለት ልጆቿን ይዛ ብራዚል በመገኘት ድጋፍ የሰጠች ነበረች፡፡ የ28 ዓመቷ ኮሊን ከእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሚስቶች ወጭዋን ሸፍና ብራዚል በመጓዝ እና በአሳፋሪ ውጤት በጊዜ በመመለስ የምትጠቀስ ሆናለች፡፡ አብረዋት የ4 ዓመት ልጃቸው ካይ እና ገና 1 ዓመት የደፈነው ሌላ ወንድሙን ይዛ እንግሊዝ በመጨረሻው የዓለም ዋንጫው የምድብ ጨዋታ ከውድድር ውጭ ስትሆን ታድመዋል፡፡ ታዳጊ ሞዴል የሆነችው የኔይማር ጓደኛ ብሩና ማርኪውዚን፤ የዌስሊ ሽናይደር ሚስትና በሙያዋ ተዋናይት የሆነችው ዮላንቴ ሽናይደር ካቡ፤ እንዲሁም ታዋቂ ጋዜጠኛ የሆነችው የኤከር ካስያስ ሚስት ሱዛን ካርቦኔ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ስማቸው ከተነሱ ሴቶች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ የፈረንሳይ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሚስቶች እና ፍቅረኞች ቡድናቸው ስታድዬም ገብተው በመደገፍ ተደንቀዋል፡፡

የባካሪ ሳኛ እና የፓትሪስ ኤቭራ ሴቶች በአስጨፋሪነታቸው አልተቻሉም ነበር፡፡በኡራጋይና ጣሊያን ብሄራዊ ቡድኖች የሚገኙ ተጨዋቾች ግንኙነት ያላቸው ሴቶች ያረፉባቸው በየአቅራቢያቸው የሚገኙ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴሎች ናቸው። የሆላንዱ አሰልጣኝ ሊውስ ቫንጋል በአንዳንድ ግጥሚያዎች ዋዜማ ለተጨዋቾቻቸው ከቤተሰባቸው ጋር የሚገናኙበትን እረፍት በመፍቀድ ልዩ ውሳኔ አድርገዋል፡፡ የፍቅር ግንኙነት ይጠቅማል፤ ይጎዳል? ከዓለም ዋንጫ ጋር በተያያዘ ስለ ሴቶቹ መዘገብ የተጀመረው ውድድሩ ከመጀመሩ ሁለት እና ሶስት ወራት ቀድሞ ነበር፡፡ ከ32 ብሄራዊ ቡድኖች መካከል አብዛኛዎቹ የተጨዋቾች ሚስቶች፤ እጮኛዎችና ጓደኞች በዓለም ዋንጫው ስለሚኖራቸው ሚና የተለያዩ መመርያዎች አውጥተዋል፡፡ አንዳንድ አሰልጣኞች ከቡድናቸው አቅራቢያ ሴቶች፤ ልጆችና ሌሎች የቤተሰብ አባላት መኖራቸው ተጨዋቾች የልምምድ ሰዓቶችን እንዳያከብሩ፤ በተለያዩ ሁኔታዎች ሃሳብ እንዲገባቸው እና ትኩረታቸውን እንዲያጡ ያደርጋል የሚሉ ምክንያቶችን በመደርደር ጥብቅ ደንቦችን ለማውጣት ተገደዋል፡፡ ተጨዋቾች ከሚስቶቻቸው፤ ከፍቅረኞች እና ከሴት ጓደኞቻቸው ጋር በየጨዋታው ዋዜማ የወሲብ ግንኙነት የሚገድቡ ደንቦች አወዛግበዋል፡፡ አንዳንድ አሰልጣኞች ተጨዋቾች ማናቸውንም የፍቅር ግንኙነት ማድረጋቸው ውጤት ያበላሻል የሚል አቋም ነበራቸው፡፡ የራሽያ፣ ቦስኒያ፣ ቺሊና ሜክሲኮ አሰልጣኞች ምሳሌ ናቸው፡፡

ሌሎች ደግሞ ተጨዋቾች በነፃነት የፈለጉትን እንዲያደርጉ ፈቅደዋል፡፡ ጀርመን፣ ስፔን፣ አሜሪካ፣ አውስትራሊያ፣ ጣሊያን፣ ሆላንድ፣ ስዊዘርላንድና ኡራጋይ ናቸው፡፡ የቦስኒያ እና ሜክሲኮ አሰልጣኞች ከጨዋታ በፊት የሚፈፀም የወሲብ ግንኙነት የአካል ብቃት ያጓድላል በሚል ሲከለክሉ የትኛውም ፕሮፌሽናል ተጨዋች ያለ ወሲብ አንድ ወር ቢያሳልፍ ምንም ችግር አይፈጠርበትም በሚል መከራከርያ ነው፡፡ የብራዚል አሰልጣኝ የነበሩት ሊውስ ፍሊፕ ስኮላሬ በበኩላቸው ክልከላውን ቢደግፉም መመርያቸውን ለዘብ በማድረግ ተጨዋቾች ወሲብ ከፈፀሙ ከልክ ባለፈ ሁኔታ እንዳይሆን በማሳሰብ ነበር፡፡ የስፔን አሰልጣኝ ቪሴንቴ ዴልቦስኬ ማናቸውም ግንኙነት ግጥሚያ በሌለባቸው የእረፍት ቀናት ብቻ እንዲሆን ሲፈቅዱ የአውስትራሊያ፤ የፈረንሳይ እና የአሜሪካ አሰልጣኞች በበኩላቸው በተለያየ ደረጃ ቁጥብ ግንኙነት እንዲኖር አሳስበዋል፡፡

የናይጄርያው አሰልጣኝ ስቴፈን ኬሺ በበኩላቸው ትዳር የመሰረቱ ተጨዋቾች ከሚስቶቻቸው እና ቤተሰባቸው ጋር ግንኙነት እንዲኖራቸው ቢፈቅዱም ከማንኛውም የሴት ጓደኛ ወይም ፍቅረኛ ለሚደረግ ግንኙነት ግን ፈቃድ አልሰጥም ብለዋል፡፡ የቺሊ አሰልጣኝ ደግሞ ተጨዋቾቻቸው ቡድናቸውን ለጥሎ ማለፍ ምእራፍ ካበቁ በኋላ ለማናቸውም ግንኙነት ነፃነት ሰጥተዋል፡፡ የሆላንዱ አሰልጣኝ ሊውስ ቫንጋል ደግሞ ቡድናቸው ያለፈው ዓለም ዋንጫ ሻምፒዮኗን ስፔን 5ለ1 ካሸነፈበት ጨዋታ በፊት ተጨዋቾቹ ባረፉበት ሆቴል ሚስቶቻቸው፤ ፍቅረኞቻቸው እና ጓደኞቻቸው የጉብኝት ሰዓት እንዲፈቀድላቸው በመወሰናቸው ተሳክቶላቸዋል፡፡ ብዙ የእግር ኳስ አሰልጣኞች ከጨዋታ በፊት ተጨዋቾች ወሲብ ማድረግ የለባቸውም የሚል አመለካከትን ይቀበሉታል፡፡ ከጨዋታ በፊት ወሲብ መፈፀም የተጨዋችን ጉልበት ያባክናል፣ ኃይል ያሳጣል እንዲሁም የስነልቦና ዝግጅትን ያቃውሳል በሚልም ያስረዳሉ፡፡ አንዳንዶች ግን የሴቶቹ በዓለም ዋንጫ አካባቢ መገኘት ተጨዋቾች በሞራል እንዲነቃቁ ያደርጋል በሚል እምነት ሰርተዋል፡፡ ስታድዬም ገብተው ድጋፍ የሚሰጡበትን እድል እንደሚፈጥር እና ዝነኛ ሴቶች ከሆኑ ደግሞ የብሄራዊ ቡድኖችን ማልያ በማስተዋወቅ፤ የሚዲያ ሽፋን በማግኘት ብዙ መልካም ገፅታዎችን በመፍጠር ያላቸው አስተዋፅኦ መናቅ እንደሌለብትም የሚያስረዱ አሉ፡፡