Administrator

Administrator

      ባለፉት 5 ዓለም ዋንጫዎ ኮከብ ግብ አግቢ ች ለግማሽ ፍፃሜ ከደረሰ 4 ቡድኖች ተገኝቷል፡፡ ግማሽ ፍፃሜ መግባት 7 ጨዋታ ማድረግ በመሆኑ ለፉክክር ያለውን እድል ያሰፋዋል፡፡ በኮከብ ግብ አግቢነት ፉክክር የኮሎምቢያው ጀምስ ሮድሪጌዝ በ6 ጎሎች እየመራ ነው፡፡ የጀርመኑ ቶማስ ሙለር በ5 ጎሎች የሚከተለው ሲሆን ሊዮኔል ሜሲ እና ኔይማር ዳሲልቫ በ4 ጎሎች ሶስተኛ ደረጃ አላቸው፡፡ ቶማስ ሙለር እና ሊዮኔል ሜሲ በዋንጫው ጨዋታ ከ1 በላይ ካገቡ ለወርቅ ጫማው ሽልማት እድል የሚኖራቸው ሲሆን እያንዳንዳቸው እኩል 3 ጎል ያስመዘገቡት የሆላንዶቹ ሮበን እና ቫንፕርሲ በደረጃ ጨዋታ ከሃትሪክ በላይ ጎል ካስመዘገቡም ሊያሸንፉ ይችላሉ፡፡ የጀርመኑ ቶማስ ሙለር በዋንጫ ጨዋታ አንድ ግብ በማስቆጠር በሁለት ተከታታይ ዓለም ዋንጫዎች በኮከብ ግብ አግቢነት በመጨረስ የወርቅ ጫማ ለመሸለም እድል የሚኖረው 3 ለጎል የበቁ ኳሶችን በማቀበል ነው፡፡ በኮከብ ተጨዋችነት የወርቅ ኳስ ተፎካካሪዎች የሆኑት የኮሎምቢያው ጀምስ ሮድሪጌዝ፤ የጀርመኑ ቶማስ ሙለር እና የአርጀንቲናው ሊዮኔል ሜሲ ናቸው፡፡ 

የኮሎምቢያው ጀምስ በ5 ጨዋታ 6 ጐል በማግባት  በ3 ግጥሚያዎች የጨዋታው ኮከብ ሽልማቶችን በመውሰድ እና ተጨማሪ ለጎል የበቁ ሁለት ኳሶችን በማቀበል ፉክክሩን እየመራ ነው፡፡ በዓለም ዋንጫው በ4 ግጥሚያዎች የጨዋታው ኮከብ ሆኖ የተመረጠው ሊዮኔል ሜሲ በዋንጫ ጨዋታ በሚኖረው ብቃት በኮከብ ተጨዋችነት የወርቅ ኳስ ለመሸለም ሰፊ እድል ይዟል፡፡ በዓለም ዋንጫው ኮከብ በረኛነት የወርቅ ጓንት ለመሸለም ሶስት በረኞች ዋና ተፎካካሪዎች ናቸው፡፡  የአርጀንቲናው ሰርጂዬ ሮሜሮ በ4 ጨዋታዎች ጐል አልገባበትም፡፡ የጀርመኑ ማኒዌል ኑዌር  ደግሞ በ3 ጨዋታ ጎል ያልተቆጠረበት ሲሆን በፍፃሜው የሚኖረው ብቃት ለመሸለም ሰፊ እድል አለው፡፡ በሶስት ግጥሚያዎች የጨዋታው ኮከብ ለመሆን የበቃው የኮስታሪካው ግብ ጠባቂ ኪዬሎር ናቫስ ሌላው ተፎካካሪ ነው፡፡

የውጤት ደረጃ ከ5 እስከ 32
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ዛሬ እና ነገ በሚደረጉት ሁለት የደረጃ እና የዋንጫ ጨዋታዎች ላይ የሚሳተፉት አራቱ ቡድኖች ብራዚል፤ ሆላንድ፤ ጀርመንና አርጀንቲና በአጠቃላይ ውጤት ከ1 እስከ 4 የሚኖራቸውን ደረጃ ይወስናሉ፡፡  እስከ ሩብ ፍፃሜ ለመሳተፍ የበቁት 28 ቡድኖች ደግሞ ከ5ኛ ደረጃ ጀምሮ እስከ 28ኛ በቅደም ተከተል በውጤታቸው ደረጃ ተሰጥቷቸዋል፡፡ ለሩብ ፍፃሜ የበቁት እና እያንዳንዳቸው 14 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ የሚከፈላቸው 4 ብሄራዊ ቡድኖች ኮሎምቢያ፤ ቤልጅዬም ፈረንሳይና ኮስታሪካ  ከ5 እስከ 8ኛ ደረጃ ያገኛሉ፡፡ 16 ቡድኖች ለደረሱበት ጥሎ ማለፍ የበቁት እና እያንዳንዳቸው 9 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ የሚከፈላቸው 8 ብሄራዊ ቡድኖች ቺሊ፤  ሜክሲኮ፤ ስዊዘርላንድ፤ ኡራጋይ፤ ግሪክ፤ አልጄርያ፤ አሜሪካ እና ናይጄርያ ከ9 እስከ 16ኛ ደረጃ ያገኛሉ፡፡ በምድብ ማጣርያ ተሳትፏቸው የተወሰኑት እና እያንዳንዳቸው 8 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ሽልማት የሚከፈላቸው 16 ብሄራዊ ቡድኖች ኢኳዶር፤ ፖርቱጋል፤ ክሮሽያ፤ ቦስኒያ፤ አይቬሪኮስት፤ ጣሊያን፤ ስፔን፤ ራሽያ፤ ጋና፤ እንግሊዝ ደቡብ ኮርያ፤ ኢራን፤ ጃፓን፤ አውስትራሊያ፤ ሆንዱራስ እና ካሜሮን ከ17 እስከ 32ኛ ደረጃ ተሰጥቷቸዋል፡፡

ከስፖንሰሮች የተሳካለት አዲዳስ ነው
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ  በከፍተኛ ደረጃ የማስተዋወቅ እና የማሻሻጥ ዘመቻ ካደረጉት ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ስኬታማ የሆነው የጀርመኑ የስፖርት ትጥቅ አምራች ኩባንያ አዲዳስ ነው፡፡ ፊፋ በዓለም ዋንጫው በአጋርነት ከሰሩት 8 ስፖንሰሮች 1.53 ቢሊዮን ዶላር አግኝቷል፡፡
አዲዳስ ከ20ኛው ዓለም ዋንጫ በተያያዘ ለማስተዋቂያ እና ለገበያ ማስፋት ዘመቻው ወጭ ያደረገው 85 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን በውድድሩ ያቀረባት ብራዙካ የተባለች ኳስ ባተረፈችው ተወዳጅነት እንዲሁም ታኬታና ማልያ ያቀረበላቸው 9 ብሄራዊ ቡድኖች በተለይ ጀርመን ባስመዘገቡት ስኬት እስከ  2.7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ይጠብቃል፡፡ በዚህ ገቢም በዓለም ዋንጫው ስኬታማ በመሆን የጀርመኑ አዲዳስ ግንባር ቀደም ይሆናል፡፡
የቅርብ ተቀናቃኙ የሆነው የአሜሪካው የስፖርት ትጥቅ አምራች ኩባንያ በዓለም ዋንጫው የማስተዋወቅ እና የማሻሻጥ ዘመቻው  70 ሚሊዮን ዶላር ወጭ አድርጎ  እስከ 1.9 ቢሊዮን ዶላር ገቢ በመጠበቅ ይከተላል፡፡ ለናይኪ ገበያ መቀነስ የማልያ እና የትጥቅ ስፖንሰር ከሆነለቻቸው አስር ብሄራዊ ቡድኖች በተለይ አዘጋጇ ብራዚል ለዋንጫ አለመድረሷ ነው፡፡ ከሌሎች የዓለም ዋንጫ ስፖንሰሮች ለማስተዋወቅ እና ለማሻሻጥ ዘመቻው ኮካ ኮላ በብራዚል ብቻ 600 ሚሊዮን ዶላር ወጭ ማድረጉ ከፍተኛው ሆኖ ይጠቀሳል፡፡

    ጀርመንና አርጀንቲና በዓለም ዋንጫ 5 የሻምፕዮናነት ክብሮች  አግኝተዋል፡፡ ነገ በዓለም ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታ የሚገናኙት በታሪክ ለሶስተኛ ጊዜ ይሆናል፡፡  በሁለቱ የዓለም ዋንጫ ጨዋታዎች በ1986 እኤአ ላይ አርንጀቲና ስታሽንፍ በ1990 እኤአ ደግሞ ጀርመን አሸንፋለች፡፡ ከ20ኛው የዓለም ዋንጫ የፍፃሜ ፍልሚያ በፊት የአውሮፓዋ ጀርመን ለ3 ጊዜያት (በ1954፤ በ1974 እና በ1990 እኤአ) እንዲሁም አርጀንቲና ለ2 ጊዜያት (በ1978 እና በ1986 እኤአ) የዓለም ሻምፒዮን ሆነዋል፡፡ የእነዚህ የዓለም ዋንጫ ድሎች ታሪክ ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡
በፊፋ የወርቅ ኢዮቤልዩ የደመቀው የጀርመን የመጀመርያ ድል
በ1954 እ.ኤ.አ 5ኛው ዓለም ዋንጫ  በአውሮፓዊቷ አገር ስዊዘርላንድ የተካሄደ ነበር፡፡   ሁለተኛው ዓለም ጦርነት ትኩሳት ከረገበ ከ8 ዓመታት በኋላ ነው፡፡ ይህ ዓለም ዋንጫ ከዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ፊፋ 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ ክብረ በዓል ጋር መያያዙ ልዩ ያደርገዋል፡፡ የዓለም ዋንጫ የቴሌቨዥን ስርጭት በጥቁርና ነጭ ለመጀመርያ ጊዜ የተከናወነበትም ነበር፡፡ በሌላ በኩል  በአጠቃላይ 140 ጐሎች ከመረብ ማረፋቸውና ባንድ ጨዋታ በአማካይ 5.38 ጐሎች መመዝገቡ እስካሁን በሪከርድነት ቆይቷል፡፡ በ5ኛው የዓለም ዋንጫ ፍፃሜ ጨዋታ ላይ የተገናኙት ምዕራብ ጀርመንና ሃንጋሪ ነበሩ፡፡ የጀርመን ብሄራዊ ቡድን በካፒታሊዝም ስርዓት ይተዳደር በነበረው የአገሪቱ ክፍል ተወካይነት ምእራብ ጀርመን ተብሎ የተሳተፈ ነበር፡፡   በ1950ዎቹ ምርጥ ከሚባሉ  ቡድኖች አንዱ የነበረውና እነ ፈረንስ ፑሽካሽ፣ ቦዝስክ ኮሲስኮና ሀይ ድግኡቲ የሚገኙበት የሃንጋሪ ብሄራዊ ቡድን ደግሞ የውድድሩ አስደናቂ አቋም ያሳየ ነበር፡፡ የፍፃሜው ፍልሚያ በስዊዘርላንዷ በርን ከተማ በሚገኘው የዋንክድሮፍ ስታድዮም ሲካሄድ ከ60ሺ በላይ ተመልካች ነበረው፡፡ የሃንጋሪ  ቡድን 2ለ0 ሲመራ ቢቆይም ከኋላ ተነስቶ 3 ጐሎችን በማስቆጠር 3ለ2 በሆነ ውጤት የምዕራብ ጀርመን  ብሄራዊ ቡድን አሸነፈ፡፡ ስለሆነም የመጀመሪያው የሻምፒዮንነት ክብር በማግኘት  የጁሌዬስ ሪሜት ዋንጫን ተቀዳጅቷል፡፡ የምእራብ ጀርመን ደጋፊዎች ብሄራዊ ቡድናቸው የጁሌዬስ ሪሜት ዋንጫን ሲረከብ በስታድዬሙ ምእራብና ምስራቅ ጀርመንን የሚያዋህደውን መዝሙር እንዳሰሙ ታሪክ ያስታውሳል፡፡
የአሁኗ ዓለም ዋንጫ ለሽልማት ቀርባ ለአስተናጋጇ ጀርመን  ሁለተኛ ድል
10ኛውን የዓለም ዋንጫ  በ1974 እ.ኤ.አ  ላይ የተካሄደው በምዕራብ ጀርመን ነበር፡፡  በ9 ዓለም ዋንጫዎች ለሻምፒዮኑ አገር ስትሸለም የቆየችው የጁሌስ ሪሜት ዋንጫ በአዲስ ተቀይራ የቀረበችበት ዓለም ዋንጫ ነበር፡፡ የጁሊዬስ ሪሜት ዋንጫን  ብራዚል ለሶስተኛ ጊዜ ወስዳ በማስቀረቷ  አዲሷ የፊፋ ዓለም ዋንጫ መሰራቷ አስፈላጊ ሆኗል፡፡ አዲስ የዋንጫ  ሽልማት ከ7 የተለያዩ አገሮች ቀራፂዎች የሰሯቸው 53 የተለያዩ ዲዛይኖች ለውድድር ቀረቡ፡፡ በጣሊያናዊው ቀራፂ ሲልቪዮ ጋዚንጋ  የቀረበችው ዋንጫ ተመረጠች፡፡ 10ኛው ዓለም ዋንጫ ከቀዳሚዎቹ 9 ዓለም ዋንጫዎች ልዩ ካደረጉት ሁኔታዎች አንዱ በባለቀለም ቴሌቪዥን ስርጭት ማግኘቱ ነበር፡፡ በሌላ በኩል የሆላንዳዊያን የ‹ቶታል ፉትቦል› የአጨዋወት ፍልስፍና የሚወሳ ታሪክ ነበር፡፡ በዋንጫው ጨዋታ የምዕራብ ጀርመን ብሔራዊ ቡድን እና በቶታል ፉትቦል የተደነቀው የሆላንድ ብሄራዊ ቡድን ተገናኙ፡፡ ምዕራብ ጀርመን  በብሄራዊ ቡድኑ አምበል  ፍራንዝ ቤከንባወር  እና  በዋና አሰልጣኝ ሄልሙት ሾን  የተመራ ነበር፡፡ ሆላንድ ደግሞ በአሰልጣኝ ሩኒስ ሚሸልስና በታዋቂው ተጨዋች ዮሃን ክሮይፍ አስደናቂ አቋም በማሳየት ለዋንጫው የታጨ ነበር፡፡  የምዕራብ ጀርመን ብሔራዊ ቡድን 2ለ1 በማሸነፍ አዲሷን የዓለም ዋንጫ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲሁም በውድድሩ ታሪክ ሁለተኛው የዓለም ሻምፒዮናነት ክብር አስመዘገበ፡፡ ለምዕራብ ጀርመን የማሸነፊያዋን ግብ ያስቆጠረው ዘ ቦምበር በሚል ቅል ስሙ የሚታወቀው ገርድ ሙለር ነበር፡፡ ጀርመናዊያን ቄሳሩ እያሉ በሚያሞግሱት ፍራንዝ ቤከንባወር የተመራው ብሔራዊ ቡድኑ ውስጥ ሚዬርና በርቲ ቮጎትስ የተባሉ ምርጥ ተጨዋቾች ይታወሳሉ፡፡
የአርጀንቲና የመጀመርያ ድል
በ1978 እ.ኤ.አ 11ኛውን  የዓለም ዋንጫ የማስተናገድ እድል ያገኘችው አርጀንቲና ናት፡፡ በ1ኛው ዓለም ዋንጫ ለፍፃሜ ተጫውታ ዋንጫውን በኡራጋይ ከተነጠቀች ከ48 ዓመታት በኋላ ወደ እግር ኳስ ሃያልነቷ ለመመለስ የበቃችበት ነበር፡፡  በዓለም ዋንጫው ዋዜማ አርጀንቲናን ያስተዳድር የነበረው መንግስት በመፈንቅለ መንግስት  ተገልብጦ አምባገነኑ መሪ ጄኔራል ቪዴላ ስልጣን መያዛቸው ነበር፡፡ ስለሆነም የዓለም ዋንጫው መሰናዶ በጄኔራል ቪዴላ መንግስት በሰብአዊ መብት ጥሰትና በአምባገነናዊ ስርአቱ ከበርካታ አገራት ተቃውሞ የተሰነዘርበት ነበር፡፡ የሻምፒዮናነት ክብሩን ለመጀመርያ ጊዜ ለማግኘት ተስፋ በማድረግ በ11ኛው የዓለም ዋንጫ ለፍፃሜ ጨዋታ የቀረቡት አስተናጋጇ አርጀንቲና እና ሆላንድ  ነበሩ፡፡ የፈረንሳዩ ለኢክዊፔ ጋዜጣ እና ሌሎች አለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃናት አስቀድመው ከተደረጉት 10 የዓለም ዋንጫዎች ምርጡ የፍፃሜ ፍልሚያ ተብሎ ነበር፡፡ አርጀንቲና 3ለ1 በሆነ ውጤት ሆላንድን በማሸነፍ  በታሪኳ ለመጀመርያ ጊዜ የዓለም ዋንጫ ድል አግኝታለች፡፡ በወቅቱ የአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድንን በዋና አሰልጣኝነት የመሩት ሴዛር ሜኖቲ ከቡድናቸው የ17 ዓመቱን ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና መቀነሳቸው ቢያስተቻቸውም ቡድናቸው የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን ተከትሎት በነበረው ውበትን የተላበሰ አጨዋወት  አድናቆት አትርፈውበታል፡፡ ከተጨዋቾች አምበል የነበረው ዳንኤል ፓሳሬላ እና ማርዮ ኬምፐስ የተባለው አጥቂ ከፍተኛ አድናቆት ያተረፉ  ነበሩ፡፡ የውድድሩ ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ የጨረሰው ማርዮ ኬምፕስ በአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን ከነበሩ  ተጨዋቾች መካከል  በፕሮፌሽናልነት በስፔን ላሊጋ ለሚወዳደረው ሻሌንሺያ ክለብ በመጫወት ብቸኛው ነበር፡፡
በማራዶና ጀብድ የአርጀንቲና ሁለተኛ ድል
13ኛው የዓለም ዋንጫ በ1986 እ.ኤ.አ ላይ በሰሜንና መካከለኛው አሜሪካ ዞን የምትገኘው ሜክሲኮ ጊዜ ያስተናገደችው ነበር፡፡  ይህ ዓለም ዋንጫ በመስተንግዶ ማራኪነት፤ በስታድዬሞች በታየው ሜክሲኳውያን ማዕበል የተባለው ድጋፍ አሰጣጥና በአርጀንቲናዊው ኮከብ ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና ባሳየው የላቀ ችሎታ የማይረሳ  ነው፡፡  በዚህ ዓለም ዋንጫ ላይ በፍፃሜ ጨዋታ የተገናኙት አርጀንቲና ከምእራብ ጀርመን ጋር ነበር፡፡ ከ115ሺ በላይ ተመልካች ባስተናገደው ታላቁ አዝቴካ ስታድዬም የሁለቱ ቡድኖች ፍልሚያ 2ለ2 በሆነ ውጤት እስከ 83ኛው ደቂቃ ቆየ፡፡  ማራዶና ለቡድን አጋሩ ጆርጌ ቡርቻጋ አመቻችቶ ያቀበለው ምርጥ ኳስ አማካኝነት  የማሸነፊያ ጎል ተመዘገበችና በአርጀንቲና 3ለ2 አሸናፊነት ተጠናቀቀ፡፡ ከ30 ሚሊዮን በላይ አርጀንቲናውያንም በድሉ ፌሽታ መላው አገራቸውን በደስታ አጠልቅልቀው ደስታቸውን ገልፀዋል፡፡ አርጀንቲናን በአምበልነት እየመራ ለታላቁ የዓለም ዋንጫ ድል የበቃው ማራዶና  በአንድ ተጨዋች ጀብደኛነት ውድድረን ማሸነፍ እንደሚቻል ያሳየበት ነበር፡፡ አርጀንቲና እስከዋንጫው ባደረገችው ግስጋሴ ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና አምስት ጎሎችን ከማግባቱም በላይ ለሌሎች  አምስት ግቦች መመዝገብ ምክንያትም ሆኗል፡፡ ማራዶና በምርጥ ችሎታው ዓለምን ማንበርከክ ቢችልም በተለይ በእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ላይ በእጁ ያስቆጠራት ግብ ግን የብዙዎችን አድናቆት ወደ ቁጣ ቀይራዋለች፡፡ በወቅቱ ለንባብ የበቃው የፈረንሳዩ ጋዜጣ ሌኢክዌፔ ማራዶናን ‹‹ግማሽ መልዓክ ግማሽ ሰይጣን››  ብሎታል፡፡
የዓለም ዋንጫ ድል ሃትሪክ በጀርመን  
14ኛው ዓለም ዋንጫ በ1990 እኤአ ላይ በጣሊያን አዘጋጅነት የተደረገ ነው፡፡ በውድድሩ ታሪክ  ዝቅተኛ የግብ ብዛት የተመዘገበበት ወቅት ነበር፡፡ አዘጋጇ ጣሊያን በግማሽ ፍፃሜው ከጨዋታ ውጪ የሆነችው በአርጀንቲና ተሸንፋ ነበር፡፡ ዲያጎ አርማንዶ ማራዶና በአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን ስለነበር ግን በክለብ ደረጃ የሚጫወትበት ናፖሊ ክለብ ደጋፊዎች ግራ ተጋብተው ነበር፡፡ ጣልያን ትተው እሱን እንደግፍ በሚል ተወዛግበዋል፡፡
በዚህ ዓለም ዋንጫ በፍፃሜ ጨዋታ የተገናኙት  በታሪክ ለሁለተኛ ጊዜ አርጀንቲና እና ምዕራብ ጀርመን ነበሩ፡፡ በሮም ኦሎምፒክ ስታድዬም በተደረገው ጨዋታ የምእራብ ጀርመን ብሔራዊ ቡድን  አርጀንቲናን 1ለ0 ረታ፡፡ ከአራት ዓመት በፊት በፍፃሜ ጨዋታ በታላቁ አዝቴካ ስታድዬም በማራዶና በተመራችው አርጀንቲና የደረሰበትን ሽንፈት በመበቀል ለ3ኛ ጊዜ የዓለም ሻምፒዮን መሆን ችሏል፡፡ በወቅቱ የቡድኑ አሰልጣኝ የነበረው ፍራንዝ ቤከን ባወር ደግሞ የዓለም ዋንጫን በተጨዋችነት በ1974 እኤአ ላይ ካሸነፈ ከ16 ዓመታት በኋላ በአሰልጣኝነት በማሸነፍ በውድድሩ ታሪክ አስደናቂ ክብረወሰን አስመዝግቧል፡፡

“ግብረ ሰዶማውያን
በድንጋይ ተወግረው መሞት አለባቸው”
የተለያዩ የአለማችን ሀገራት እንደሚከተሉት የፖለቲካ ስርአት በተለያዩ ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ የተለያየ አቋም ያራምዳሉ፡፡ ለምሳሌ የግብረ ሰዶማዊነትን ጉዳይ በተመለከተ ለአሜሪካና ለአውሮፓ መንግስታት ነገሩ የዜጎች ሰብአዊ መብት ጉዳይ ሲሆን ለአብዛኞቹ የአፍሪካ መንግስታት ደግሞ ምንም አይነት ተቀባይነት የሌለው የወንጀል ድርጊት ተደርጎ ይቆጠራል፡፡
ከጥቂት ወራት በፊት የኡጋንዳ መንግስት ግብረ ሰዶማዊነት በወንጀል የሚያስቀጣ የተከለከለ ድርጊት መሆኑን የሚደነግግ ህግ አውጥቶ በስራ ላይ አውሏል፡፡ በፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒ የሚመራው የኡጋንዳ መንግስት፣ ይህን ህግ በማውጣቱ የተነሳ ከአሜሪካና ከበርካታ የአውሮፓ መንግስታት እንዲሁም ከሌሎች የመብት ተሟጋች ነን ከሚሉ መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች የዜጎቹን ሰብአዊ መብት ጥሷል ወይም አላስከበረም በሚል ያልተቋረጠ የውግዘት ናዳ ወርዶበታል፡፡
በተለይ የአሜሪካ መንግስት በቅርቡ ባወጣው መግለጫ፤ የኡጋንዳ መንግስት ግብረ ሰዶማዊነትን በመከልከል ያወጣውን ህግ ባስቸኳይ ካልሰረዘ ማዕቀብ እንደሚጣልበት አስጠንቅቋል፡፡ ባለፈው ሳምንት ግን ከአሜሪካ ኦክላሆማ ግዛት ግብረ ሰዶማዊነት በተመለከተ አንድ ለየት ያለ ነገር ሲነገር ተደምጧል፡፡ ለአክላሆማ ከተማ ምክር ቤት ምርጫ የቲ ፓርቲን ወክለው የሚወዳደሩት ስኮት ኤስክ፤ ግብረ ሰዶማዊነትን መቃወም ብቻ ሳይሆን ግብረ ሰዶማውያን የሆኑ ሁሉ የብሉይ ኪዳን መጽሀፍ ቅዱስ አስርቱ ትዕዛዝ እንደሚደነግገው በድንጋይ ተወግረው እንዲገደሉ እንደሚፈልጉ በምረጡኝ ቅስቀሳቸው ወቅት በግልጽ አሳውቀዋል፡፡
የሮማ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ፍራንሲስ በቅርቡ ግብረ ሰዶማዊነትን በተመለከተ “ግብረ ሰዶማውያንን ለመተቸትና በእነሱ ላይ ለመፍረድ እኔ ማን ነኝ?” በማለት የሰጡትን መግለጫ በተመለከተም ስኮት ኤስክ በፌስቡክ ገፃቸው ስለ ግብረሰዶም አስፀያፊነት በመጽሀፍ ቅዱስ የተፃፈውን በመጥቀስ፣ ለግብረ ሰዶማውያን የሚገባው ቅጣት በድንጋይ ተወግሮ መሞት እንደሆነ በማስፈር ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ይሄ የምርጫ ቅስቀሳ ንግግር የተደመጠው ከአሜሪካዋ ግዛት ከኦክላሆማ መሆኑ ብዙዎችን በግርምታ አፍ አሲዟል፡፡

Saturday, 12 July 2014 12:44

የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቅሌት

    መንግስታት ከምንጊዜውም በበለጠ ቅሌት ውስጥ የሚዘፈቁበት ጊዜ አለ ከተባለ በምርጫ ወቅት ነው። የየሀገሮቻቸው ብሄራዊ የምርጫ ጊዜ ሲቃረብ ጀምሮ እስከሚጠናቀቅበት ጊዜ ድረስ መንግስታት የማይሰሩት ቅሌት የለም፡፡ አንዳንዱ መንግስት ያሰጉኛል የሚላቸውን ተፎካካሪዎቹን እዚህ ግባ የማይባል ሰበብ አስባብ በመፍጠር ከያሉበት ለቃቅሞ ወህኒ ያጉራል፡፡
አንዳንዱ መንግስት ደግሞ ተቃዋሚዎቹን ብቻ ሳይሆን ጋዜጠኞችንም ጨምሮ ያስራል፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ግንባር ቀደም ተፎካካሪያቸውን ብቻ ለይተው ከጨዋታ ውጭ የሚያደርግ ኮሚክ የምርጫ ህግ ያወጣሉ፡፡ ለምሳሌ የምያንማር (በርማ) ወታደራዊ ደርግ በ2008 ዓ.ም ያወጣው የምርጫ ህግ፣ የውጪ ሀገር ዜጋ ባል ያላቸው በርማውያን ፖለቲከኞች ለፕሬዚዳንታዊ ምርጫ መወዳደር እንደማይችሉ ይደነግጋል፡፡
ይህ አስቂኝ የምርጫ ህግ ለየትኛው ፖለቲከኛ ተብሎና የትኛውን ፖለቲከኛ ከምርጫ ጨዋታ ውጭ ለማድረግ ታስቦ እንደወጣ በጣም ግልጽ ነው። በሚቀጥለው አመት በምያንማር በሚደረገው ምርጫ ከፍተኛ የማሸነፍ እድል ያላቸው ዝነኛዋ የነፃነትና የመብት ታጋይ ኦንግ ሳን ሱኪ ብቻ ናቸው። እንግሊዛዊ ባል ያላቸው ፖለቲከኛም ከእሳቸው ውጭ ማንም አልነበረም፡፡ እናም የምርጫ ህጉ ታቅዶና በሚገባም ታስቦበት የወጣው፣ ምርጫውን በቀላሉ እንደሚያሸንፉ የታመነውን ኦንግ ሳን ሱኪን ከጨዋታ ውጪ ለማድረግ ነው፡፡
እንደ ፖላንድ አይነት መንግስቶች የሚሰሩት ቅሌት ደግሞ ትንሽ ረቀቅ ያለ ነው፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ የፖላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶናልድ ተስክ፤ በሚቀጥለው አመት በሚደረገው ጠቅላላ ምርጫ ፓርቲያቸው “ሲቪክ “ፕላትፎርም” ፓርቲ ማሸነፍ እንዲችል የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትራቸውን ይጠሩና ከወዲሁ አንድ ነገር እንዲያደርጉ ያዟቸዋል፡፡
ምኒስትሩም በጉዳይ ላይ ካሰቡበት በኋላ አሁን ባለው የፖላንድ የኢኮኖሚ ሁኔታ በሀገሪቱ የወለድ መጠን ላይ መጠነኛ ቅናሽ ማድረግ ከተቻለ፣ ገዢው የሲቪክ ፕላትፎርም ፓርቲ በቀጣዩ ምርጫ የተሻለ ድጋፍ ማግኘት እንደሚችል ይገምታሉ፡፡   
ከዚያም ቀጥ ብለው ወደ ፖላንድ ማዕከላዊ ባንክ ዋና መስሪያ ቤት ያመራሉ፡፡ የባንኩ ገዢ ከሆኑት ከማሪክ ቤልካ ጋር እንደተገናኙም ቀጣዩ ምርጫ ከመካሄዱ በፊት በወለድ መጠኑ ላይ መጠነኛ ቅናሽ በማድረግ ገዢው ፓርቲ በምርጫው እንዲያሸንፍ የበኩላቸውን እገዛ እንዲያደርጉ ጥያቄአቸውን ያቀርቡላቸዋል፡፡
የባንኩ ገዢ ማሪክ ቤልካም በበኩላቸው፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶናልድ ተስክ የገንዘብ ሚኒስትሩን ከስልጣናቸው ካባረሩላቸው የተጠየቁትን እንደሚፈጽሙ ለሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሩ አረጋገጡላቸው፡፡ የጉዳዩ ዝርዝር ሪፖርት የቀረበላቸው ጠቅላይ ምኒስትር ዶናልድ ተስክም ለአፍታም እንኳ ሳያመነቱ ኢኮኖሚውን በወጉ መምራት ተስኖታል የሚል መናኛ ሰበብ በመፍጠር የገንዘብ ሚኒስትሩን ከስልጣኑ አባረሩ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩና የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሩ ይህን ሁሉ ነገር የሰሩት በከፍተኛ ጥንቃቄና ምስጢር ነበር፡፡ ሆኖም ግን ባለፈው ሳምንት አንድ ጉድ ወጣ። የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከጠቅላይ ሚኒስትሩና ከማዕከላዊ ባንክ ገዢ ጋር ያደረጉት ንግግር በምስጢር ቴፕ ተቀርፆ ይፋ ወጣ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶናልድ ተስክም ስልጣን እንዲለቁ ተጠየቁ፡፡ እሳቸው ግን ስልጣን መልቀቁን በጄ አላሉም፡፡ ይልቁንም የሀገሪቱን ርዕሰ መንግስት ንግግር በድብቅ መቅዳት ከመፈንቅለ መንግስት የማይተናነስ ወንጀል መሆኑን በመግለፅ ክስ ለመመስረት እንደሚገደዱ አስጠነቀቁ፡፡ የሌባ ዓይነ ደረቅ…ይሏል ይሄ ነው!!

አንደኛው የአለም ጦርነት የተጀመረበትና እንግሊዝ ወደ ጦርነቱ የገባችበት 100ኛ ዓመት፣ በመላው እንግሊዝ መብራት በማጥፋት፣ በጨለማ ውስጥ በሚከናወኑ የተለያዩ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶችና ፌስቲቫሎች እንዲሁም በዌስት ሚንስቴር አቤይ በሚከናወን የሻማ ማብራት ስነ-ስርዓት እንደሚከበር ቢቢሲ ዘገበ፡፡ በመጪው ነሃሴ 4 ሊካሄድ በታሰበው በዚህ ዝግጅት፤ በመላው እንግሊዝ የሚገኙ የመንግስትና የግል ድርጅቶች፣ የግለሰብ መኖሪያ ቤቶች፣ የንግድ ተቋማትና የተለያዩ ኩባንያዎች በዕለቱ ለአንድ ሰዓት ያህል አምፖሎቻቸውን አጥፍተው ሻማ በመለኮስ የጦርነቱን መጀመር እንዲያስታውሱ አዘጋጆቹ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
እንግሊዝ በጀርመን ላይ ጦርነት ያወጀችበትን ይህን ዕለት በአገሪቱ የሚገኙ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች መብራት በማጥፋት እንደሚዘክሩት ተስፋ አለን ያሉት አዘጋጆቹ፣ ይህ ፕሮጀክት በኪነጥበባዊና ባህላዊ ስራዎች የጦርነትን አስከፊነት የመግለጽ ዓላማ ይዞ መነሳቱን ተናግረዋል፡፡
ጦርነቱ በይፋ በታወጀበት ዕለት ዋዜማ፣ የወቅቱ የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ጸሃፊ ሰር ኤድዋርድ ግሬይ “በመላ አውሮፓ የሚገኙ አምፖሎች ሁሉ ሊጠፉ ነው፤ በህይወት ሳለን ዳግም ተመልሰው ሲበሩ ላናያቸው እንችላለን!” በማለት ለህዝቡ መልዕክታቸውን ማስተላለፋቸውን ያስታወሰው የቢቢሲ ዘገባ፣ ከእሳቸው የዘር ሃረግ የተገኙት አንድሪያን ግሬቭስ የተባሉ ግለሰብ ፕሮጀክቱን በተመለከተ ከትናንት በስቲያ መግለጫ መስጠታቸውን ገልጿል፡፡
አንድሪያን ግሬቭስን ጠቅሶ ቢቢሲ እንዳለው፣ የተለያዩ ዝግጅቶችን ባካተተው በዚህ ፕሮጀክት፣ በአለማቀፍ ደረጃ ታዋቂነትን ያተረፉ አራት የተለያዩ አገራት ዝነኛ አርቲስቶች ጦርነቱን የሚያስታውሱ የስዕል፣ የፊልምና የሙዚቃ ስራዎቻቸውን በስኮትላንድ፣ በዌልስ፣ በሰሜን አየርላንድና በእንግሊዝ በሚገኙ የስነጥበብ ጋለሪዎችና ሲኒማ ቤቶች ለእይታ ያቀርባሉ፡፡የእንግሊዝን ፓርላማ ጨምሮ ታላላቅ የእንግሊዝ ተቋማት በዕለቱ ለአንድ ሰዓት ያህል መብራቶቻቸውን እንደሚያጠፉ የገለጸው ዘገባው፣ ቢቢሲን ጨምሮ ታዋቂ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ደግሞ የስቱዲዮዋቸውን ብርሃን እንደሚያደበዝዙ ይጠበቃል ብሏል፡፡

ባለፈው መጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ 239 ሰዎችን አሳፍሮ ከኳላላምፑር በመነሳት ወደ ቤጂንግ በመብረር ላይ እያለ ድንገት የገባበት የጠፋውን የማሌዢያ አየር መንገድ አውሮፕላን ለማግኘት የተጀመረውና ይህ ነው የሚባል የተጨበጠ ውጤት ያልተገኘበት ፍለጋ አስርት አመታትን ሊፈጅ እንደሚችል የኩባንያው አንድ የስራ ሃላፊ መናገራቸውን ዘ ቴሌግራፍ ዘገበ፡፡
የአየር መንገዱ የንግድ እንቅስቃሴ ዳይሬክተር ሃግ ዳንሌቪ ከሳምንታት በፊት ከኢቭኒንግ ስታንዳርድ ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ ድንገት በተሰወረው ኤም ኤች 370 ቦይንግ 777 አውሮፕላን ላይ፣ የሆነ የማይገባ ድርጊት ተፈጽሞበታል ብለው እንደሚያስቡና ወደመነሻው ለመመለስ በሚሞክርበት ጊዜም ፈታኝ የሆኑ ነገሮች ተጋርጠውበት ሳይሳካለት እንደቀረ መናገራቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡
አውሮፕላኑ በደቡባዊ የህንድ ውቅያኖስ አካባቢ ሳይወድቅ እንዳልቀረ የገለጹት ዳንሌቪ፣ አወዳደቁ የከፋ ሊሆን እንደሚችልና ውቅያኖሱ ውስጥ ከሚገኙ ተራሮች ጋር ከተጋጨም ስብርባሪው ርቆ ሊሄድና ሊበታተን እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
ከዚህ አንጻርም የአውሮፕላኑን ስብርባሪ ለማግኘት የሚደረገው ጥረት እጅግ ፈታኝ ሆኖ ሊቀጥልና ምናልባትም አስርት አመታትን ሊፈጅ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡
አውሮፕላኑ ከጠፋ ከቀናት በኋላ፣ ፍለጋውን በተመለከተ ከአንድ የአገሪቱ ከፍተኛ ሚንስትር ጋር ቃለ መጠይቅ እንዳደረገ ያስታወሰው ዘ ቴሌግራፍ፤ ሚንስትሩ በወቅቱ በሰጡት ምላሽ፤ ፍለጋው ሳምንታትን ግፋ ቢልም ወራትን ብቻ ሊፈጅ እንደሚችል ነግረውኝ ነበር ብሏል፡፡

የጐንደር ዩኒቨርስቲን የ60 አመት ጉዞ የሚዘክር “የስልሳ ገፆች ወግ” የተሰኘ መጽሐፍ ታትሞ ለንባብ በቃ፡፡ በጋዜጠኛ አብርሃም ዘሪሁን የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ በሁለት ምዕራፎች የተቀናበረ ሲሆን የመጀመሪያው ምዕራፍ ስለ ጐንደር ዩኒቨርስቲ አመሠራረትና ዛሬ የደረሰበትን ደረጃ ሲተነትን ሁለተኛው ምዕራፍ ለዩኒቨርስቲው እድገት አስተዋጽኦ ያበረከቱ ምሁራንን ይዘክራል፡፡
የመጽሐፉ ዋጋ 100 ብር ሲሆን ገቢው ለዩኒቨርስቲው ይውላል ተብሏል፡፡
በሌላ በኩል፤ በአሸናፊ ውዱ የተፃፈው “ሚስት መሆን” የተሰኘ የወግ መጽሐፍ ከትናንት በስቲያ ሀሙስ ምሽት ሰዓት በራስ ሆቴል ተመርቋል፡፡ በ196 ገፆች የተቀነበበው መጽሐፉ፤ በአንድ ሚስቱን በሞት ያጣ ባልና ከሴት ልጁ ጋር አጉል ድርጊት ውስጥ በገባ አባት ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን ሲሆን በ50 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነትና በፆረና ተጋድሎ እውነተኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥነው “የኢትዮ - ኤርትራ ጦርነትና የፆረና ተጋድሎ” የተሰኘ መፅሀፍ በትላንትናው እለት በሂልተን ሆቴል ተመርቋል፡፡ በምክትል አስር አለቃ የማታወርቅ ተገኝ ተፅፎ በዳዕሮ አድቨርታይዚንግ የተዘጋጀው ይህ መፅሀፍ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት የተከሰቱ ተጋድላችን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል ተብሏል፡፡
በምረቃ ሥነስርአቱ ላይ የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ የጦር መኮንኖች፣ የታሪክ ምሁራንና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተው ነበር፡፡  

         በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደተሳለ የተነገረለትና ፓሪስ ውስጥ ከሚገኘው ‘ሚዩዜ ዲ ኢሆሜ’ ሙዚየም እኤአ በ1989 የተሰረቀው የቅዱስ ዮሃንስን ምስል የሚያሳይ ጥንታዊ የኢትዮጵያ ስዕል፣ ከሰሞኑ ዱሮውት በተባለ አጫራች ድርጅት አማካይነት ማይሰን ፒያሳ ውስጥ በተዘጋጀ ጨረታ ለሽያጭ ቀርቦ መገኘቱን ዘ ፊጋሮ የተባለው የአገሪቱ ጋዜጣ ባለፈው ሰኞ ዘግቧል፡፡
እኤአ በ1932 ማርሴል ግሪአውሌ የተባሉ የኢትኖግራፊ ባለሙያ ከዳካር እስከ ጅቡቲ ባደረጉት የጥናት ጉዞ በእጃቸው እንዳስገቡትና አባ አንጦንዮስ በተባለ ደብር ውስጥ እንደነበረ የተነገረለት ይህ ጥንታዊ የኢትዮጵያ ስዕል፣ ወደ ሙዚየሙ ከመግባቱ በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ለተመልካች የቀረበው ፈረንሳይ ውስጥ በሚገኝ ቤተክርስቲያን ነበር ተብሏል፡፡
ባለሙያው ቤተክርስቲያኑ መሰል ጥንታዊና ውድ ስዕሎችን ለማሰቀመጥ ምቹ አለመሆኑን በመግለጽ ስዕሎቹን በዘይት ቀለም አስመስለው በማሰራት ለመተካትና ዋናውን ቅጂ ለማውጣት እንዲችሉ ያቀረቡት ጥያቄ በአካባቢው የቤተክህነት አስተዳዳሪዎች ፈቃድ ማግኘቱ የተገለጸ ሲሆን፣ በወቅቱ የኢትዮጵያ መንግስት የውጭ ጉዳይ ሚንስትር የስዕሉን ከቤተክርስቲያኑ መውጣት ቢቃወሙም የስልጣን ላይ የነበሩት የፈረንሳይ ንጉስ ግን ድጋፋቸውን ለባለሙያው መስጠታቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
በግለሰቡ እጅ ላይ ለተወሰነ ጊዜ ቆይቶ፣ ፓሪስ ውስጥ ወደሚገኘው ‘ሚዩዜ ዲ ኢሆሜ’ ሙዚየም እንዲገባ የተደረገው  ይህ ስዕል፣ እኤአ በ1989 ከሙዚየሙ የስዕል ስብስቦች መካከል ድንገት እንደተሰወረና ማን እንደሰረቀው ሳይታወቅ ደብዛው ጠፍቶ እንደኖረ ተነግሯል፡፡
ከ25 አመታት በኋላ ታዲያ፣ ጃክ ሜርሲየር የተባሉ በኢትዮጵያ ዙሪያ የተለያዩ ጥናቶችን በመስራት የሚታወቁ ምሁር ናቸው፣ ደብዛው ጠፍቶ የኖረውን ይህን ጥንታዊ ስዕል በጨረታ ሊሸጥ ቀርቦ ባለበት ሁኔታ ሰሞኑን ድንገት ያገኙት፡፡ የእኒህን ምሁር ጥቆማ የተቀበለው ሙዚየሙ አጫራቹን ድርጅት በማግኘት ስለጉዳዩ ያነጋገረ ሲሆን፣ ስዕሉን ለጨረታ ያቀረበችው ነዋሪነቱ በፈረንሳይ የሆነው የታዋቂው ኩባዊ ሰዓሊ ጃኪን ፌረር ባለቤት መሆኗ ታውቋል፡፡
 ሴትዮዋ ስዕሉ ከሙዚየሙ ከጠፋ ከጥቂት አመታት በኋላ ከአንድ ገበያ እንደገዛችው ተናግራለች፡፡ በወቅቱ ስዕሉን ከሙዚየሙ ማን እንደሰረቀውም ሆነ ለእሷ እንደሸጠላት አሁንም ድረስ የተጨበጠ ነገር አልተገኘም፡፡
ስዕሉ ግን ሙዚየሙ ከሴትዮዋ ጋር ባደረገው ስምምነት ሊሸጥ ከቀረበበት ጨረታ እንዲወጣ የተደረገ ሲሆን፣ በቀጣይም ኳይ ብራንሊ ውስጥ በሚገኘው የስዕል ማዕከል ውስጥ ከሚገኙት የሌሎች 11 ቅዱሳን ስዕሎች ጋር እንዲቀላቀል የሚደረግ መሆኑ ተገልጧል፡፡



የጣሊያኗ ቬነስ በአንደኛ ደረጃ ተቀምጣለች


ዩኔስኮ በአለም ቅርስነት ከመዘገባቸው የኢትዮጵያ ቅርሶችና የቱሪስት መስህቦች መካከል የሚጠቀሱት ጥንታዊ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙባት የላሊበላ ከተማ፣ ‘አንድ ሰው በህይወት ዘመኑ ሊያያቸው የሚገባቸው 50 ምርጥ የአለማችን ከተሞች’ በማለት ታዋቂው ሃፊንግተን ፖስት ጋዜጣ ከጠቀሳቸው ከተሞች ተርታ ተመደበች፡፡
ጋዜጣው በቅርቡ ሚኑቢ ዶት ኔት በተባለ ድረገጽ አማካይነት የአለማችን ጎብኝዎች የሚያደንቋቸውን ታላላቅ የቱሪስት መዳረሻዎች እንዲጠቁሙ በማድረግ ባሰባሰበው መረጃ፣ በጎብኝዎቹ ከተመረጡ 50 የአለማችን ከተሞች ዝርዝር ውስጥ ላሊበላ 17ኛ ቦታ ላይ መቀመጧን ታዲያስ መጽሄት በሳምንቱ መጀመሪያ ዘግቧል፡፡
ላሊበላ ከኢትዮጵያ ታላላቅ ቅዱስ ከተሞች አንዷ ናት ያለው ሃፊንግተን ፖስት፣ በውስጧ የያዘቻቸው ጥንታዊ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትም በመላው አለም የሚታወቁ ድንቅ መስህቦች መሆናቸውን ገልጧል፡፡
ከጥንታዊ የአገራት ርዕሰ መዲናዎች፣ እስከ እስያ ዘመናዊ ከተሞች በመላው አለም የተለያዩ ክፍሎች የሚገኙ ከተሞችን ባካተተው በዚህ ዝርዝር ውስጥ ቀዳሚነትን ያገኘችው የጣሊያኗ ቬነስ ናት፡፡ የሚያማምሩ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች፣ ገራሚ አብያተ ክርስቲያናት፣ ማራኪ ቤቶች፣ ምቾት የሚለግሱ መጠጥ ቤቶች ብዙ ብዙ ማራኪ ነገሮች የሞሉባት ቬነስ፣ ከአለም ከተሞች አምሳያ የሌላት ምርጥ ከተማ ናት ብሏታል ጋዜጣው፡፡
የስፔን ነገስታት መናገሻ ውብ ከተማ፣ ጎብኝዎች በብርቱካናማ አበቦች የተዋቡ ጠባብ መንገዶቿን ተከትለው በመጓዝ ማራኪ ጥንታዊ ህንጻዎችን አሻግረው እየቃኙ መንፈሳቸውን የሚያድሱባት አይነግቡና ቀልብ አማላይ ከተማ በማለት ሁለተኛ ደረጃ የሰጣት ደግሞ የስፔኗን ሲቪሊ ነው፡፡
 ኒዮርክ ሲቱን ሶስተኛዋ መታየት ያለባት የአለማችን ቀልብ ገዢ ከተማ ያላት ሃፊንግተን ፖስት፤ የትም ዙሩ የትም፣ እንደ ኒዮርክ ሲቲ መንፈስን ገዝቶ በአድናቆት የሚያፈዝ የኪነጥበብ፣ የባህል፣ የምግብ አሰራርና የንግድ እንቅስቃሴ በአንድ ላይ ተዋህደው የሚገኙባት ከተማ በየትኛውም የአለም ጥግ አታገኙም ብሏል፡፡
የህንዷን ላህሳ በመንፈሳዊ ማዕከልነቷና በማራኪ የተፈጥሮ ገጽታዋ፣ የብራዚሏን ሪዮ ዲ ጄኔሮ በውበቷ፣ የእንግሊዟን ለንደን በምርጥ ሙዚየሞቿና በጎብኝዎች ተመራጭ ከሆኑ የአለማችን ቀዳሚ ከተሞች አንዷ በመሆኗ በተከታታይ እስከ ስድስተኛ ያለውን ቦታ ሰጥቷቸዋል፡፡ የሞሮኮዋ ማራኬች፣ የዮርዳኖሷ ፔትራ፣ የጣሊያኗ ሮምና የህንዷ ቫራናሲም አንድ ሰው በህይወት ዘመኑ ሳለ ሳያያቸው ማለፍ የሌለባቸው ከተሞች ናቸው ተብለዋል፡፡