Administrator

Administrator

  • ዋና ቢዝነስ፡ መጽሐፍ፣ ሲዲ፣ ዲቪዲ፣ የኤሌክትሮኒስ እቃ፣ ልብስ፣ ምግብ በኢንተርኔት መሸጥና በአካል ማድረስ
  • በአመት የ74 ቢሊዮን ዶላር ሸቀጦችንና አገልግሎቶችን ይሸጣል
  • አምና ሩብ ቢሊዮን ዶላር አትርፏል
  • የኩባንያው ሃብት 40 ቢሊዮን ዶላር ይገመታል
  • 120ሺ ገደማ ሰራተኞች አሉት

በኢንተርኔት ጎብኚዎች ብዛት በአለም 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል
ከሳምንት በኋላ፣ አዲስ ታሪክ ይሰራል የተባለለትና “3ዲ” ስክሪን ያለው ሞባይል ስልክ ለገበያ እንደሚያቀርብ ያበሰረው አማዞን ዶት ኮም፤ እቃ የሚያደርሱ ሰው አልባ በራሪዎችን ሰርቶ እንዳጠናቀቀ ገለጿል።
አመት ሙሉ ሲወራለት የነበረው የአማዞን አዲስ ሞባይል ስልክ በወሬ አልቀረም።  አይፎን እና ጋላክሲ ከመሳሰሉ ስማርትፎኖች በምን እንደሚለይ በዝርዝር ባይገለፅም፤ በስክሪን ቴክኖሎጂው የላቀ እንደሚሆን ተገምቷል። ምስሎችን በአካል የማየት ያህል አንዳች የ3ዲ ቴክኖሎጂ ጥቅም ላይ እንዳዋለ ኩባንያው ጠቁሟል። ዋጋው ገና አልታወቀም።
የተለያዩ ሸቀጦችን በኢንተርኔት በመሸጥና ሸቀጦቹን ለደንበኞች በአካል በማድረስ የሚታወቀው አማዞን፤ አዲሱን የሞባይል ስልክ ለሚገዙ ደንበኞች ተመሳሳይ አገልግሎት መስጠቱ አይቀርም።
የቀረ ነገር ቢኖር፣ እቃዎችን ለደንበኞች የሚያደርስ ሰው አልባ በራሪ (ድሮን) ብቻ ነው። አማዞን እንደሚለው፣ ያለ አብራሪ እቃ ለማጓጓዝ የተሰሩት ሚኒ ሄሊኮፕተሮች በተግባር ተሞክረዋል። አደጋ የማድረስ ወይም የመጋጨት ስጋት የለባቸውም። በራሪዎቹ ሚኒ ሄሊኮፕተሮች ለአገልግሎት ዝግጁ ናቸው። እና ምንድነው የሚጠብቁት? የአውሮፕላን በረራዎችን ለመቆጣጠር በመንግስት የወጡ ህጎች እስኪሻሻሉ ድረስ፣ ሰው አልባ አውሮፕላኖችንም ሆነ ሄሊኮፕተሮችን በብዛት መጠቀም አይቻልም። ህጎች እስኪሻሻሉ እየጠበቅሁ ነው የሚለው አማዞን፤ “ፕራይም ኤር” የተሰኙት ሚኒ ሄሊኮፕተሮች በአመት ውስጥ ለደንበኞች እቃ የማመላለስ አገልግሎት ይጀምራሉ የሚል ተስፋ እንዳለው ገልጿል።
ታዲያ የእቃው ክብደት ከ2 ኪሎ ግራም መብለጥ የለበትም። ቦታውም  ከ17 ኪ. ሜትር በላይ መራቅ አይኖርበትም። እናም በኢንተርኔት አማካኝነት ያዘዙት እቃ በግማሽ ሰዓት ውስጥ ከቤትዎ ደጃፍ ከች ይላል - በሰው አልባ ሚኒ ሄሊኮፕተር።

Saturday, 07 June 2014 14:23

የግጥም ጥግ

ዛሬስ ስሌቱ ስንት ሆነ?

“መሬት፣ሴትና ሀገር…፣ አንድ ናቸው”
አትበሉኝ፤ አንድነታቸው ከሩቅ ይቀፋል፣
ሶስቱም ባንድ ላይ የከሸፉ እንደሁ፣ ነገረ
ትምህርት ባፉ ይደፋል…!
የ‘ውነት፣ የ‘ውቀት ሀቲታችን፣ እንደ
ፈርስ እጣቢ ይከረፋል፤
ሰብአዊነት እስከ መለኪያው፣ በየጎሰኛው
ከርስ ሰጥሞ ይነጥፋል፤
በዘመን እርከን ሳይገደብ፣ ትውልድም
በትውልዱ ይጣፋል!
ታዲያ እኛ እንኳ፣ እናስላው ጎበዝ
የአዙሪት ርዕዮትዓለሙን  ጣጣ፣
‹‹የዜሮ ድምር ፖለቲካችን››፣ ዛሬም
‹‹ነጋቲቭ›› እንዳይመጣ…!
        መስከረም፣ 1998ዓ.ም.

 ሩሲያዊው ቢሊየነር ድሚትሪ ራይቦሎቭሌቭ፤ በቅርቡ ከቀድሞ ሚስቱ ጋር የፈፀመውን ፍቺ እንደ ድንገተኛ የቢዝነስ ኪሳራ መቁጠሩ አይቀርም። የኢትዮጵያ ታላቁ ህዳሴ ግድብን እኮ ነው ክፈላት የተባለው፡፡ ቢሊዬነሩ 27 ዓመት በትዳር አብራው ከዘለቀችው ኢሌና ጋር ፍቺ መፈፀሙን ተከትሎ የስዊስ ፍ/ቤት የቀድሞ ባለቤቱ 4.8ቢ. ዶላር ብት ልትካፈል ይገባል ሲል ወስኗል፡፡ የኢሌና ጠበቃ በሰጠው መግለጫ “እጅግ ውድ ፍቺ ነው” ብሎታል። ይሄ እጅግ ውድ የፍቺ ክፍያ ለድሚትሪ ከፍተኛ ኪሳራ ሲሆን ለቀድሞ ሚስቱ ግን የማይታመን የሃብት ጎርፍ ነው፡፡
የዛሬ 15 ዓመት ደግሞ ሌላ ውድ ፍቺ ተፈጽሟል። አውስትራሊያዊው የሚዲያ ከበርቴና ለ32 ዓመታት በትዳር አብራው የኖረችው የ3 ልጆቹ እናት አና ሙድሮክ፤ እ.ኤ.አ በ1999 ዓ.ም ፍቺ ሲፈጽሙ ፍ/ቤት ለሚስትየው የ1.7 ቢሊዮን ዶላር ሃብት (110 ሚ.ዶላር ካሽ ይጨምራል) እንድትካፈል ነበር የወሰነላት። ከሃብት ክፍፍሉም በኋላ ሁለቱም የየራሳቸውን ህይወት ቀጥለዋል፡፡ በእርግጥ ሩፐርት ሙድሮክ በ38 ዓመት ከምታንሰው ዌንዲ ዴንግ ጋር ትዳር የመሰረተው ፍቺ በፈፀመ በ17ኛ ቀኑ ነበር ሳይፈታ በፊት ያዘጋጀ እኮ ነው የሚመስለው፡፡ አናም በበኩሏ፤ ከወራት ቆይታ በኋላ አንድ ኢንቨስተር አግብታለች፡፡ በሃብት ላይ ሃብት አትሉም፡፡ እነ አሜሪካን በመሳሰሉ የበለፀጉ አገራት፤ ቢሊዬነሮችን አግብቶ መፍታት አትራፊ ኢንቨስትመንት እየሆነ ነው፡፡

ውድ እግዚአብሔር፡-
ስቴፕለር ከታላላቅ ፈጠራዎችህ አንዱ ይመስለኛል፡፡
        ሩት
- የ5ዓመት ህፃን

ውድ እግዚአብሔር፡-
ቀናተኛ ዓምላክ ነህ ሲባል ምን ማለት ነው? እኔ እኮ ሁሉ ነገር ያለህ ነበር የሚመስለኝ፡፡
                        ጆን
- የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
የሰንበት ት/ቤት ለምን እሁድ ሆነ? የእረፍት ቀናችን እኮ ነው፡፡
        ራሄል
 - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
በእናትህ ትንሽዬ ፈረስ ላክልኝ፡፡ ብትፈልግ መዝገብህን ማየት ትችላለህ፡፡ ምንም ጠይቄህ አላውቅም፡፡
                        ብሩስ
- የ 5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ምናልባት ቃየንና አቤል የየራሳቸው ክፍል ቢኖራቸው ኖሮ አይገዳደሉም ነበር፡፡
ላሪ
 - የ8 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
አንዳንዴ የፀሎት ጊዜም ባይሆን ስለአንተ አስባለሁ፡፡
ማርሻ - የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
ለአንተ ከሚሰሩልህ ሰዎች ሁሉ የበለጠ የምወዳቸው ኖህና ዳዊትን ነው፡፡
ሳሚ
- የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር፡-
በመፅሃፍ ቅዱስ ላይ እንዳለው ሰውዬ 900 ዓመት መኖር እፈልጋለሁ፡፡ እወድሃለሁ እሺ፡፡
ዶን
- የ6 ዓመት ህፃን

በአብዱል ፈታህ አብደላህ አዘጋጅነት በኮንሶ የባህል ህግ ላይ ጥናት ተደርጐበት የተዘጋጀው “ሤራ አታ ኾንሶ” የተሰኘ መጽሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ መጽሐፉ ትኩረት ያደረገው በኮንሶ የባህል ህግ ስርዓት ላይ ሲሆን በጥናቱ ውስጥ የኮንሶ የአገር ሽማግሌዎችና የአካባቢው ተወላጅ ምሁራን ተሳትፈውበታል፡፡ በ197 ገፆች የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ በኮንሶ የባህል ህግ ስርዓት ላይ ትኩረት ቢያደርግም አጠቃላይ የማህበረሰቡን ባህል፣ ወግ፣ ቋንቋና ሃይማኖታዊ ሁነቶች ይቃኛል፡፡ መጽሐፉ በኢትዮጵያ የፍትህ ሥርዓቶች ማዕከልና በኮንሶ ወረዳ አስተዳደር ትብብር ታትሞ በነፃ ለአንባቢያን ደርሷል፡፡ በተያያዘ ዜና የቱሪዝምና እና የሙዚየም ማውጫዎችን በማሳተም የሚታወቀው ሀገሬ ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን፤ የኮንሶ ህፃናት ስለ አካባቢያቸው የቱሪዝም መስህቦች እንዲያውቁ የሚረዳቸውን “ኮንሶን ለህፃናት” የተሰኘ የቱሪዝም መጽሐፍ ለንባብ ያበቃ ሲሆን “ሴራ አታ ኾንሶ” ከተባለው መጽሐፍ ጋር በኮንሶ ካራት ከተማ ባለፈው ሳምንት ተመርቋል፡፡

መቀመጫውን አሜሪካ ሂዩስተንና ኢትዮጵያ በማድረግ በቴአትር ዘርፍ የሚንቀሳቀሰው ዮሐንስ ቴአትር ፕሮዳክሽን፤ “ደላሎቹ” የተሰኘውን ቴአትር በሚቀጥለው ሳምንት እሁድ  ለእይታ ያበቃል፡፡ የምርቃት ስነስርዓቱ በዕለቱ ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት በሀዋላ ሴንትራል ሆቴል እንደሚካሄድም ድርጅቱ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በኤርሚያስ ጌታቸው ተደርሶ፣ በህይወት አራጌ በተዘጋጀው በዚህ ቴአትር ላይ ችሮታው ከልካይ፣ ህይወት አራጌ፣ ኤርሚያስ ጌታሁንና ሌሎች አንጋፋና ወጣት ተዋንያን እንደሚሳተፉበት ለማወቅ ተችሏል፡

በዶ/ር መልካሙ ታደሰ የተዘጋጀው “የጐጆ ድርጅት” (Home business) የተሰኘ መጽሐፍ ዛሬ ከቀኑ በ8 ሰዓት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የባህል ማዕከል ይመረቃል፡፡ መጽሐፉ በዋናነት ዜጐች እውቀታቸውን፣ ችሎታቸውን እንዲሁም ትርፍ ጊዜያቸውን በመጠቀም ከመኖሪያ ቤታቸው ተጨማሪ ገቢ በማግኘት፣ ራሳቸውንና አገራቸውን ተጠቃሚ የሚያደርጉበትን መንገድ ያመላክታል ተብሏል፡፡ በምረቃው ላይ በመጽሐፉ ዙሪያ ውይይት እንደሚደረግ ታውቋል፡፡

በደራሲ ልዑል ግርማ የተዘጋጀው “ፍቅርና ትግል” የአጫጭር ልቦለዶች መድበል ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ መፅሀፉ በፍቅር ታሪኮችና በማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥን ሲሆን በ287 ገፆች የተቀነበበ ነው፡፡ በ45 ብር ለገበያ እንደቀረበም ታውቋል፡፡ ደራሲ ልዑል ግርማ ከዚህ ቀደም “አራት አርባ አራት” የተሰኘ አነጋጋሪ ረዥም ልብ-ወለድ የፃፈ ሲሆን “የወንድሜ ሚስት” የተሰኘ የአጭር ልብወለድ መድበል ለንባብ ማብቃቱ የሚታወስ ነው፡፡

በአርቲስትና የፎቶግራፍ ባለሙያ ወንድወሰን በየነ የተዘጋጀውና “A Glimpse of Ethiopian II” የተሰኘ የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽን በራዲሰን ብሉ ሆቴል ይከፈታል፡፡ ኤግዚቢሽኑ የፊታችን ሐሙስ ተከፍቶ እስከ ግንቦት 15 ቀን 2006 ዓ.ም ለተመልካች ክፍት ሆኖ የሚቆይ ሲሆን በኤግዚቢሽኑ መልክአምድር፣ አሮጌ ቤቶችንና ሌሎች ተፈጥሯዊ ነገሮችን የሚያስቃኙ ፎቶግራፎች እንደሚቀርቡ ታውቋል፡፡

በደራሲ ደሳለኝ ስዩም የተፃፈው “የታሰረ ፍትህ” የተሰኘ ኢ-ልብወለድ መጽሐፍ ታትሞ ለገበያ ቀረበ፡፡ የመጽሐፉ ጭብጥ በህዝብና በገዢው ፓርቲ ዙሪያ የሚያጠነጥን ነው ተብሏል፡፡ በ3 ምዕራፎችና በ148 ገፆች የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ በ35 ብር ከ50 እየተሸጠ ነው፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም “ደም የተፋ ብዕር” የሚል የግጥም መድበልና “የጠረፍ ህልሞች” የተሰኘ ረዥም ልብወለድ ለአንባቢያን ማድረሱ ይታወቃል፡፡