Administrator

Administrator

Saturday, 22 November 2014 12:33

ማህሌት

የሆነ ያልገባው ነገር አለ፡፡ ስለ ህይወቱ? … ስለ እናቱ? በተለይ ስለ አባቱ? … በጥቂቱ ደግሞ ስለ ትምህርቱ፡፡ እንደ ድሮው አይደለም እሱነቱ፡፡ “ኤሊየን” ስለመሆኑ እንደ ድሮው ከዚህ ስምንት አመት በፊት አያምንም፡፡ እንኳንስ… አፍ አውጥቶ መናገር፡፡
የአስራ አንደኛ ክፍል ትምህርት እንደሚወራለት ከባድ አይደለም፡፡ ትንሽ አስተማሪዎቹ የሚሉትን መስማት ብቻ ነው የሚጠበቅበት፡፡ ደብተር ይዞ አያውቅም፡፡ አስተማሪ ተብዬዎቹ የሚያወሩትን ሰምቶ ፈተና በተባለው ወረቀት ላይ ሲደግምላቸው ይደሰታሉ፡፡ ሲደሰቱ “አንደኛ” ወጥተሃል ይሉታል፡፡
ዘጠነኛ ክፍል እያለ እንደዚያ አስደስቷቸው ነበር፡፡ አመቱን ሙሉ እነሱ የሚሉትን እንደ “ፓሮት” ደገመላቸው፡፡ አመቱን ሙሉ፡- ማለትም ሁለት ሴሚስተር ያህል “አንደኛ” ነህ አሉት፡፡ “አንደኛ” እና “አንተ ነህ” አሉት፡፡ ስሙ እና እውነተኛ ማንነቱ የጠፋው ሲመስለው፤ አስረኛ ክፍል አስተማሪዎቹ የሚሉትን መድገም አቆመ፡፡ “አንተ አይደለህም” ቢሉትም  አልጣሉትም፡፡ “ወደቀ” ብለው አሾፉበት እንጂ ሰርተፍኬቱ ላይ “ወደቀ” ብለው አልፃፉበትም፡፡
ዘጠነኛ ክፍለ ፊት ወንበር መጀመሪያ መደዳ ነበር የሚቀመጠው፡፡ አስረኛ ክፍል መጨረሻ መደዳ ተቀምጦ “ሮበርት ሉድለምን” እያነበበ፣ በደረጃ መጨረሻ እየወጣ አመቱን ጨረሰ፡፡ መጨረሻ መደዳ የሚቀመጡት ፊት የሚቀመጡትን እንደ “ባንዳ” እንደሚቆጥሯቸው የተረዳው ከእነሱ መሀል ሲቀመጥ ነበር፡፡ ፊት ወንበር የሚቀመጡት ኋላ ያሉትን ምን ብለው እንደሚጠሯቸው ግን በመሀላቸው ሳለ አልነገራቸውም፡፡
ከኋለኛው መደዳ ረድፈኞች ወደ አስራ አንደኛ ክፍል ያለፉት የተወሰኑት ናቸው፡፡ ከተወሰኑት መሀል ማህሌት አንዷ ናት፡፡ በመጀመሪያው ሴሚስተር ከሮበርት ሉድለም መፅሐፍ ማህሌትን ወደ ማጥናት አደገ፡፡ የእሷን ትኩረት ለመሳብ ሲል መሆን አለበት… ኋላ መደዳ ተቀምጦ ፊት ተቀማጮቹ የሚታሙበትን ነገር ማድረግ ጀመረ፡፡ ማጥናት፤ በአጭር ቋንቋ አስተማሪው የሚያዘውን ሁሉ ማድረግ፡፡ የሚደግመውን መድገም፡፡ ተመልሶ ፓሮት ሆነ፡፡
አስተማሪዎች ይገርሙታል፡፡ እነሱ ያሉትን ሁሉ አንድ ሳያስቀር ኮፒ አድርጎ የሚገለብጠውን ልጅ የፈተና ወረቀት ሲያርሙ፣ የእስክሪብቷቸው የቀይ ቀለም ጭነት ራሱ ይለሰልሳል፡፡ የሚወዱትን ልጃቸውን ጭንቅላት የሚያሹ ነው የሚመስሉት፡፡ “መቶ ከመቶ”፣ “ስልሳ ከስልሳ”… “ኤክሰለንት”… በ“Very Good” እና በ“Excellent” መትረየስ ወረዱበት፡፡ “አንተ ነህ” አሉት፡፡
ከማህሌት ጋር ለመተዋወቅ ቀላል ነበር፡፡ ያው ምክኒያት አያስፈልግም፡፡ “እቺን ነገር አሳየኝ!” “ያቺን ነገር አሳየኝ?”…
ስሙ አስተማሪዎቹ እንደሚጠሩት “አንተ ነህ” ሳይሆን...፣ ሚልኪ እንደሆነ አስረግጦ ነገራት፡፡ የተለያየ ቦታ፣ የተለያዩ ሰዎች የሚያወጡለት ስም እንዳለ ግን ደበቃት፡፡ የዛሬ አስር ዓመት ገደማ በነበረበት ሰፈር “Ace” እያሉ እንደሚጠሩት፣ ጥሪውን ግን ሰፈር ሲቀይር እንደተለወጠ መናገር ዋጋ የለውም፡፡ አባቱ የሚጠራው ስምም አለ፡፡ መውደድ ሰጥቶ መቀበል ነው፡፡ አይን ስለ አይን፣ ጥርስ ስለ ጥርስ፡፡
አሁን ከማህሌት ጋር ሚልኪ በሚለው ስሙ ነው መቀራረብ የፈለገው፡፡ መታወቂያው ላይም ስም አለው፡፡ በሱም ስም ሰዎች ይጠሩታል፡፡ ሁሉንም ጥሪ አቤት ብሎ ይቀበላል፡፡ ከነብሱ አንደበት ራሱን የሚመራበትን ስም ግን በአፉ ለራሱ እንኳን ቢሆን ጮክ ብሎ አይደግምም፡፡ ጉልበቱ የት እንደሚገኝ እንደ መግለፅ ይመስለዋል፡፡ ሳምሶን ጉልበቱን ፀጉሩ ላይ አስቀምጦ፣ ፀጉሩ እንደ በግ ሲሸለት፣ በግ እንደመሰለው …. እሱም ስሙን ምላሱ ላይ አስቀምጦት፣ ምላስ ያላቸው ሁሉ በእሱ ጉልበት እጣ ፈንታቸውን እንዲሸከሙ አይፈቀድላቸውም፡፡
ከማህሌት ጋር ተግባባ፡፡ ከማህሌት ጋር ሲቀራረብ፣ ከራሱም ማንነት ጋር ሆነ፡፡ አስተማሪዎች ማን እንደሆነ እየደጋገሙ ከሚደሰኩሩለት ራቅ ያለ ሶስተኛ ማዕዘን ላይ የተቀመረ መሆኑ ለራሱ ይሰማዋል፡፡ ቢሰማውም ይሄንን ሶስተኛ ማንነቱን ወደደው፡፡ ከወትሮው የሦስት መአዘን አቋሙ ጋር የሚስማማ ነገር ስላለው፡፡
በፊት እናቱ ከአባቱ ጋር አንድ ላይ በሚኖሩበት ጊዜ፣ እሱ የእናቱንም ሆነ አባቱን ወይንም አባቱ እሱን እንደሚያየው ወይንም እናቱ እሱን በምታየው አንፃር ራሱን ተመልክቶ አያውቅም፡፡ ሁሌም ሶስት መአዘን ይይዛል፡፡
በዚያ የልጅነት ዘመን ጎረቤቱ ያሉት እዮብ እና ናትናኤል ምርጥ ጓደኞቹ ነበሩ፡፡ ሁለቱም እሱን እንደሚያዩት .. የራሱን እይታ አመቻችቶ አያውቅም፡፡ የእዮብ እና የናትናኤል አባት ኢንጂነሩ በጣም ያደንቁት ነበር፡፡ “Ace” የሚለውን ለእነሱ እይታ የሚሆን ስም አውጥተው እንዲፀድቅ አድርገዋል፡፡ እነሱ እሱን እንደሚያዩት እንጂ እሱ እነሱን መልሶ እንደሚያያቸው… በማየት እና በመታየት መሀል ትልቅ ክፍተት እንዳለ አይገነዘቡትም ነበር፡፡ እነሱ እሱን ለመካብ የሚሰጡትን ስም እንጂ እሱ እነሱን ለማድነቅ ያወጣላቸውን ስያሜ አያውቁትም፡፡ እነሱ በሚያዩበት አለም ሁሉንም ብያኔ ለመስጠት የሚያስችል ንግስና እንዳላቸው፣ እሱም በራሱ ዓለም ውስጥ ለሚታዩት ነገሮች ብያኔ የመስጫ ልዕልና መጎናፀፉ ይረሳቸዋል፡፡
ከማህሌት ጋር ሲሆን አፍቃሪ እና ተፈቃሪ … ከመምህሮቹ ጋር ሲሆን ተማሪና አስተማሪ … ከእናቱ ጋር ሲሆን በአንድ ጊዜ ልጅ እና ወላጅ መሆን እንደሚችል ማንም አይገነዘብለትም፡፡ አብዛኛው ሰው የሚታየው አሀዳዊ መንገድ ብቻ ነው፡፡ የራሱ መንገድ፡፡ የራሱ ፍላጎት መንገድ፡፡ ኤስ ግን ሶስት መንገድ በአንድ ጊዜ ይታየዋል፡፡
በማህሌት ላይ የሚያየው መንገድ የዚህን ባህርይ የተላበሰ ነው፡፡ አንደኛው መንገድ እሱ እሷን ለማፍቀር፣ ጓደኛ ለመሆን፣ አብሮ ለመሰንበት የሚያሳየው ፍላጎት የሱ ፈቃድ ነው፡፡ ሁለተኛው ማህሌት ከሱ የምትፈልገው፣ እንዲሆንላት የምትመኘው፣ የሷ እምነት፣ እሱን በመቆጣጠር የሚፈጠረው መንገድ ነው፡፡ ሶስተኛው ከሁሉም ውጭ የሆነው ነው፡፡ ሁሉንም መሆን እና አለመሆን በአንድ ላይ የሚችለው መንገድ ነው፡፡ ይህ መንገድ እንደ እውነተኛው ስሙ እውነተኛው “ህቡዕ” ምንነቱ አድርጐ ይቆጥረዋል፡፡
የማህሌት መንገድ እና የእሱ መንገድ፤ ከዚያ ሶስተኛው መንገድ፡፡ ማህሌትን እያስጠናት እሱ ደግሞ እሷን ያጠናት ጀመር፡፡ እሷም እያጠናች እንደምታጠናው ያውቃል፡፡ ሁለቱንም ጥናቶች ከውጭ ሆኖ ሶስተኛው መአዘኑ ላይ ይቆምና ይከታተላል፡፡ ሲከታተል አስተማሪዎቹን፣ ተማሪዎቹን እናቱን፣ ህይወቱን አንድ ላይ ጠቅልሎ ነው፡፡
የማህሌትን ውጤት ዝቅ ካለበት ከፍ ሲል እያየ፣ የራሱን ከፍ ካለበት እንዲወርድ ፈቀደ፡፡ የአስተማሪዎቹ እይታ ስለሱ ወይንም ስለሷ …  ስለ እሷና እሱ መርገብገቡ ከማይርገበገበው መአቀፋዊ ምዘናው ላይ ሆኖ እንደገና ይለካል፡፡
ከአስተማሪዎቹ መሀል አንደኛው… ግጭት ለመፍጠር ከመንጋው መምህርነት ወጥቶ ወደነሱ ግንኙነት ተጠጋ፡፡ አስተማሪው የባይሎጂ ትምህርት የሚሰጥ ብቻ ሳይሆን ለትምህርቱ ሰውየውም የተሰጠ መሆኑ በስፋት ይነገርለታል፡፡ የሚነገርለትን ያለ ይሉኝታ ከመናገርም ሰውየው ራሱ አይቦዝንም፡፡ ለትምህርቱ ባሳየው ተነሳሽነት ብዙ ሽልማቶችን ሰብስቧል፡፡ ባዮሎጂ ህይወትን የሚያጠና በመሆኑ፣ አስተማሪው ከህይወት አይነቶች መርጦ ቆንጆ ሴቶችን መመርመር ይወዳል፡፡ የወደደውን ይመረምራል፡፡ ማህሌት የቆንጆ ሴቶችን መስፈርት የምታሟላ “እስፒስመን” ናት፡፡
በተሰጠው ክፍለ ጊዜ በጥቁሩ ሰሌዳ ላይ የሚፅፈውን ፅፎ ወይንም የሚያብራራውን አብራርቶ … ትንፋሽ ለመውሰድ የሚያመራው ወደ ማህሌት አቅጣጫ ነው፡፡ ደብተሯን ያገላብጣል፡፡ ደብተሯን በእጁ፣ መልኳንና ተክለ ሰውነቷን በአይኑ፡፡ ስህተት ሊያገኝባት ይታትራል፡፡ የሚፈልገውን ባያገኝም በአለባበሷ ላይ እንደ አባት ይሆንና ተግሳፅ ይሰጣል፡፡ እንደ አባት የጀመረው ምክር እንደ አጎት ይመስልና እንደ መሸታ ቤት ተስተናጋጅ ሆኖ ይጨርሳል፡፡ በተለያየ ጊዜ ቢሮ ጠርቷት ከባዮሎጂ ጋር በጣም ስለሚገናኙ የፆታዊ ባህሪዎች በጥያቄ መልክ አቅርቦለታል፡፡ አቅርቦልኛል ብላዋለች ኤስን፡፡
ሰው ሰማም አልሰማም፣ ሰውየው ለልጅቱ አንዳች ጥላቻ አለው፡፡ ተንጠራርተው የሚደርሱበትን ነገር እንደሚጠሉ ሰዎች ይመስላል… ማህሌትን ሲያያት የሚያሳየው መንገሽገሽ፡፡
“ንፍጥ” የሚል ስድብ ወደሷ አቅጣጫ ይሰነዘራል፡፡ የባዮሎጂ ተራ አስከባሪ በመሆኑ፣ ለትምህርቱ አምልኮት ያላቸው የፈተናውን ወንዝ ለመሻገር ይስቁለታል፡፡ ኤስ በዚህ ሁሉ ውስጥ የተመልካች ስፍራውን ይዞ ይታዘባል፡፡ መታዘብ ባበዛ ቁጥር ለምን ወደ አንዳች አቅጣጫ እያደገ መሆኑ እንደሚሰማው ለራሱም ማስረዳት አይችልም፡፡
ከእለታት በአንዱ ቀን በሰሌዳው ላይ የተለቀለቀውን ጽሑፍ ተማሪዎቹ እንደ እርግብ በእስክሪብቶው መንቁራቸው እየለቀሙ ሳሉ… እህሉን ያፈሰሰላቸው መምህር ወደ ማህሌት መቀመጫ ሄዶ፣ እለታዊ ጉንተላውን አከናወነ፡፡ በመቀጠል ነጭ ጋውኑን አንዘርፍፎ ከእሷ አንድ ረድፍ በቀደመው ወንበር ላይ ተቀምጦ፣ አስተማሪው የራሱን ጽሑፍ በተማሪ አይን ከኋላ ሆኖ መገምገም ጀመረ፡፡
ኤስ እንደ ሌሎቹ የተፃፈለትን ሁሉ አይለቅምም፡፡ ከሮበርት ሉድለም ወደ ጄምስ ካለቬል ድርሰት አድጓል፡፡ “ሾ ጋንን” እያነበበ ነው፡፡ አስተማሪው ሲያነብ ያየዋል ግን አይተናኮለውም፡፡ “አንተ ነህ” የሚለው ማዕረጉ፣ የሌላው ተማሪ ግዴታ እንዳይመለከተው መንገድ ሰጥቶታል፡፡ ግን ይህ የባዮሎጂ መምህር ስህተት ቢያገኝበት ሊጥለው እንደሚፈልግም ያውቃል፡፡ ከመከባበር ይሁን… ከመገማገም የመጣ መፈራራት በመሃላቸው ሰፍኗል፡፡ ኤስ ከማህሌት ጐን መቀመጡ የአስተማሪው የቀድሞ ፍቅር ወደ “ቆይ ጠብቅ” ሲቀየርበት ይታወቀዋል፡፡
ኤስ እና ማህሌት ከተቀመጡበት መደዳ ፊለፊት የተዘረፈጠው የባዮሎጂ አዋቂ በፈዘዘበት አንድ ነገር ተከሰተ፡፡ ኤስ ልጅ በነበረበት ወቅት አንድ ነገር ከመከሰቱ ጥቂት ቅጽበት ቀደም ብሎ የሚከሰተውን ነገር ያውቀው ነበር፡፡ ለምሳሌ አስተማሪ በሰሌዳው ላይ የሚያሰፍረውን ጽሑፍ ጥቂት ቀደም ብሎ ሰፍሮ ይታየው ነበር፡፡ ግን ይህ ችሎታውን ሳያዳብረው፣ ከሰው ተወራርዶ ሳይረታበት፣ በራሱ ውስጥ እንደያዘው እድሜው ከፍ እያለ ሲመጣ ቀስ በቀስ ችሎታው ጠፋበት፡፡
ጠፍቶበት ቆይቶ ልክ በዛች ቅፅበት አስተማሪው ከፊለፊቱ የእነሱን ዴክስ ተደግፎ በተቀመጠበት፣ ያ የተዘነጋ ችሎታው ድንገት ተከሰተለት፡፡ ማህሌት ቀጥላ የምታከናውነው ተግባር ታየው፡፡ ታየው፤ ግን ነገሩን ከመከሰት ለማቆም ምንም እርምጃ አልወሰደም፡፡ ሶስተኛው መአዘን ላይ ያቆመው ዋነኛው ሚዛን፣ የተከሰተውን ተግባር መግታት ይችል የነበረውን የእሱን እጅ ከውስጥ ያዘበት፡፡ Kay sera sera
ማህሌት ከሰሌዳው ላይ መገልበጧን ድንገት አቆመች፡፡ በፈጣን ትልልቅ ፊደል ለአስተማሪው እንዳይሰማው አድርጋ፣ ከጀርባ በነጩ ጋውን ላይ “የሰው ንፍጥ” ብላ ፃፈች፡፡
*    *    *
የትምህርት ጊዜ አለቀ፡፡ ሰውየውም የእውቀት ማቀበያ መሳሪያዎቹን (ቾክ እና ዳስተር) አንከብክቦ ወደሚቀጥለው ክፍሉ አመራ፡፡
ተቀያሪው አስተማሪ አንድ እግሩ አጠር የሚል፣ ጮክ ባለ ድምጽ የአማርኛን ሰዋሰው የሚያስጨብጥ ሰው ነበር፡፡ አስጨብጦ ሲጨርስ ረዘም ካለው እግሩ አጠር ወዳለው ወርዶ እረፍት ይወስዳል፡፡ መናገር ሊጀምር ሲል እንደገና ከአጭሩ ወደ ረጅሙ ይወጣል፡፡ ሁሉም አስተማሪዎች ቅጽል ስም አላቸው፡፡ ቅጽል ስሞች በአብዛኛው የሚወጡት ፊት መደዳ ከሚቀመጡት ተማሪዎች አይደለም፡፡ ጭቆና ከላይ ወደ ታች እንደሚበረታው፣ ቅጽል ስም ደግሞ ከታች ወደ ላይ የሚስፈነጥር ፍላፃ ነው፡፡ ፍላፃው ግን በተወረወረበት አካል ጆሮ ውስጥ ብዙውን ጊዜ አይገባም፡፡ እኩል እግር የሌለውን አስተማሪ “ሲትሮይን” በሚል ስም ነው ኋለኞቹ የሚጠሩት፡፡
ሲትሮይን፤ ትምህርቱን አስተላልፎ ለማብቃት ሁለት የቁመት ማጠር እና የማስረዘም ያህል ጊዜ ሲቀሩት፣ የክፍሉ በር በእርግጫ በመሰለ ሀይል ተመትቶ ተከፈተ፡፡ የባዮሎጂው መምህር የሹራብ ሰደርያ እና ጉርድ ሸሚዝ እንጂ ነጩን ጋውን አልለበሰም፡፡
ነጩ ጋውን እንደ ኤግዚቢት በዩኒት ሊደሩ እጅ ተይዟል፡፡ ዩኒት ሊደሩ በጣም ረጅምና በጣም ጥቁር አስፈሪ ሰው ነው፡፡ እውቀት ባያንሰውም ችግርን በዱላ በማስከበር ተፈሪነትን ያተረፈ ሰው ነው፡፡ ከዱላ ላለፈ እንቢ ባይነት… (ለምሳሌ ሌባ) ሽጉጥ አውጥቶ ሲያባርር ያዩ ተማሪዎች፣ በዚያች ቅጽበት እዚያው ክፍል ውስጥ ነበሩ፡፡
ነጩ ጋውን በሰሌዳው አናት ላይ ግማሽ በተመታች ሚስማር ላይ ተሰቀለ፡፡ ዩኒት ሊደሩ ወደ ኤግዚቢቱ እጁን እየቀሰረ…
“ማን ይሄንን ጽሑፍ እንደፃፈ ሳታወጡ…ትምህርት በዚህ ክፍል አይቀጥልም፡፡ አሁን እዚሁ ይሄንን የፃፍክ ግለሰብ ራስህን ካጋለጥክ፣ ግለሰቡ ብቻህን ከዚህ ትምህርት ቤት ትወጣለህ፡፡ ካልሆነ ሁላችሁንም አንድ ላይ…”
ተጠበቀ፤ ማንም መናገር አልቻለም፡፡ ለወትሮው አይኑ ከማህሌት ላይ የማይነቀለው ባዮሎጂ መምህር ወደ ማህሌት አቅጣጫ ለቅጽበት እንኳን አልተመለከተም፡፡ ማህሌት በጠረጴዛው ስር የኤስን እጅ ጭምቅ አደረገችው “ጉዴ ፈላ” ማለቷ ይሁን ወይንም “ከዚህ አውጣኝ” ግልጽ አልሆነለትም፡፡
የተማሪው አፍ ነጭ ሆኗል፡፡ ትምህርት ማለት እውቀት ብቻ ሳይሆን የህልውናም ብቸኛ መንገድ ነው፡፡ ከትምህርት ቤት መባረር ማለት ከምድረ ገጽ መሰረዝም ማለት ነው፡፡ አይኖች በጥርጣሬ እርስ በራስ ተያዩ፡፡ ባዮሎጂ አስተማሪው ሌላ ክፍል እንዳልተፃፈበት ሲትሮይን ለሚባለው አስተማሪ ማስረጃ እየጠቀሰ ነው፡፡
“አታወጡም?” ለመጨረሻ ጊዜ ዩኒት ሊደሩ ጠየቀ፡፡ መልስ ጠፋ፡፡ የሰዉ ፊት ሁሉ የጦጣ መስሏል፡፡
“የሁላችሁም የአማርኛ ደብተር ሰብስቡ” አለ ዩኒት ሊደሩ፡፡ ኤስ የአማርኛ ደብተሩ እንደ መጽሐፍ ንባቡ ባይገፋለትም የራሱን ደብተር ከላይ፣ የማህሌትን ከስር አድርጐ አስረከበ፡፡ ማህሌት በጠረጴዛው ላይ ተደፍታ እያለቀሰች ነው፡፡ እያለቀሰች ስለነበረች፣ ሚልኪ በደብተሮቹ ላይ የሰራውን ነገር አልተመለከተችም፡፡
ክፍሉ ተዘግቶ እያንዳንዱ ደብተር በጋውኑ ላይ ከሰፈረው እጅ ጽሑፍ ጋር በጥንቃቄ እየተመሳከረ ተመረመረ፡፡ ዩኒት ሊደሩ፣ ባለ ጥቃቱ ባዮሎጂ አስተማሪ እና ሲትሮይን ለብዙ ፔሬዶች ተማሪው ባለበት ደብተሮቹን ሲያተራምሱ ቆዩ፡፡ በስተመጨረሻ አንድ ደብተር ነጥሮ ወጣ፡፡ ሦስቱም አስተማሪዎች ወንጀለኛው የዚያ እጅ ጽሑፍ ባለቤት መሆኑን መቶ ፐርሰንት ተስማሙበት፡፡ የተማሪው ስም ተነበበ፡፡
ኤስ ስሙ እስኪጠራ አልጠበቀም፡፡ ዝግጁ ሆኖ ነበር፡፡ “አቤት” ብሎ ተነሳ፡፡ የማህሌት ፊት ምን እንደሚመስል ለማየት መጓጓቱ ለእሱ ብቻ ነው የሚታወቀው፡፡ “ኤስ” በዩኒት ሊደሩ እየተገፈተረ ከክፍሉ ወጥቶ ሄደ፡፡
ከሄደ በኋላ ማንም አይቶት አያውቅም፡፡ አንድ አመት ተቀጥቶ ይመለሳል ብለው ጓደኞቹ ቢያስቡም ሳይሆን ቀረ፡፡ ማህሌት ሚስጥሯን ይዛ እንደተብሰለሰለች ትምህርቷን ጨረሰች፡፡ እንዲያውም ማለፊያ ውጤት አግኝታ የንግድ ስራ ትምህርት ቤት ተቀላቀለች፡፡


ለመቄዶንያ 500ሺ ብር አበረከተ

በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የክፍያ ካርድ ያስተዋወቀው ዳሽን ባንክ፤ አሁን ደግሞ የአሜሪካ ኤክስፕረስ ካርድ፣ የሞባይልና ኤጀንሲ (ውክልና) አገልግሎት በቅርብ እንደሚጀምር ተገለፀ፡፡
የአሜሪካ ኤክስፕረስ ካርድ ከፍተኛ ገንዘብ የሚያንቀሳቅሱ ሀብታሞች የሚጠቀሙበት “ፕሪስቲጂየስ ካርድ” ነው ያሉት  የዳሽን  ባንክ የፕሮሞሽን ዋና ክፍል ኃላፊ አቶ እስጢፋኖስ በፍቃዱ፤ ከውጭ የሚመጡ ሀብታሞች ካርዱን ስለሚጠቀሙ ለውጭ ምንዛሬ ዕድገት ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል ብለዋል፡፡ በቪዛ ካርድ እንዳደረግነው ሁሉ፣ የአሜሪካን ኤክስፕረስ ብራንድ ያላቸውን ካርዶች አምርተን ከጥር ጀምሮ ለህዝቡ እናድላለን ያሉት ኃላፊው፣ ካርዱ በአሜሪካ የሚያስገኛቸውን ጥቅሞች እዚህም ያስገኛል ብለዋል፡፡
አንድ ሰው በአሜሪካ በኤክስፕረስ ካርዱ ፒዛ ገዝቶ በመብላቱ ብቻ 40  ዶላር ሊመለስለት ይችላል፡፡ እዚህም የካርዱን አገልግሎት በሚሰጡ ማዕከላት ለምሳሌ እንደ ካልዲስ ወይም ሌላ ካፌ ፒዛ በልቶ፣ ወተት ወይም ማኪያቶ ጠጥቶ ካርዱን ሲሰጣቸው 40 ብር ሊመልሱለት ወይም የመቶ ብር ዕቃ ገዝቶ 80 ብር ሊመለስለት እንደሚችል አስረድተዋል፡፡
ዳሽን ባንክ ከትንሽ እስከ ትልቅ የፕላቲንየም፣ የብርና የወርቅ ብራንድ ያላቸው አሜሪካን ኤክስፕረስ ካርዶች ያዘጋጀ ሲሆን እንደ ግለሰቡ ፍላጐት የ100ሺ፣ የ300 ሺና የ500 ሺና ብር ካርድ ሊዘጋጅለት እንደሚችል ታውቋል፡፡
ዳሽን ባንክ፣ በአገራችን ያልነበረ አዲስ የሞባይልና ኤጀንሲ (የውክልና) አገልግሎት በሚቀጥለው ታህሳስ ወር ለመጀመር ዝግጅት ማጠናቀቁን አስታውቋል፡፡ ሞባይልና  ኤጀንሲ ማለት፣ ዳሽን ባንክ ቅርንጫፍ በሌለው አካባቢ አገልግሎት የሚሰጥ በማህበረሰቡ የተወደደና የተመረጠ ወኪል ማለት እንደሆነ አቶ እስጢፋኖስ ገልፀዋል፡፡
ዳሽን ባንክ ቅርንጫፍ በሌለው ትንሽ ከተማ ማህበረሰቡ የሚወደውና የሚያምነው ነዳጅ ማደያ፣ ሱፐርማርኬት፣ ወይም ከሌላ ድርጅት ጋር ውክልና ይፈራረማል፡፡ ውሉ የተሰጠው ድርጅት የተወሰነ ገንዘብ (200ሺ፣ 300 ሺ፣… ብር) እንዲያሲዝ ይደረጋል፡፡ ከዚያም፣ አዲስ አበባ፣ ጎንደር፣ መቀሌ፣ ጂማ፣ ሐዋሳ፣ ድሬደዋ፣ …. ያለ የዳሽን ባንክ ደንበኛ፣ ሞባይልና ኤጀንሲ ወዳለበት ቀበሌ ገበሬ ማኅበር፣ መንደር ወይም ትንሽ ከተማ፣ … ለሚኖር ዘመድ ወይም የንግድ ባልደረባ፣ … እንዲሰጠው ገንዘብ ዳሽን ባንክ ያስገባል፡፡
ባንኩም፣ ለላኪው፣ ተቀባይ ገንዘቡን የሚቀበልበትን ሚስጢራዊ ቁጥር ወይም ኮድ ይሰጠዋል፡፡ ከዚያም ለሞባይልና ኤጀንሲው (ወኪሉ) ደውሎ፣ እንዲህ ዓይነት ኮድ ለሚያቀርብልህ ሰው ወይም ድርጅት፣ ይህን ያህል ብር ክፈለው የሚል መልእክት ያስተላልፍና ወኪሉ ካስቀመጠው ገንዘብ ላይ የከፈለው ገንዘብ እንዲቀነስ ይደረጋል፡፡ በመጨረሻም፣ ወኪሉ ለሰጠው አገልሎግት ባንኩ ኮሚሽን ይከፍለዋል በማለት አስረድተዋል፡፡
በሌላ በኩል የዳሽን ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ መቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከልን “ብቸኛ የዓመቱ ምርጥ በጐ አድራጐት ድርጅት” በማለት የ500ሺ ብር የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን የማዕከሉ መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ ቢንያም በለጠ አስታወቁ፡፡
መቄዶንያ በአሁኑ ወቅት 715 አረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማንን በተለይም የአልጋ ቁራኛ የሆኑ፣ ለመመገብም ሆነ ለመፀዳዳት የሰው ድጋፍ የሚያስፈልጋቸውን ወገኖች ከወደቁበት ጐዳና በማንሳት፣ የምግብ፣ የልብስ፣ የሕክምና፣ የተሟላ ቤተሰባዊ ፍቅርና እንክብካቤ እያደረገ መሆኑን አቶ ቢንያም ጠቅሰው፤ ዳሽን ባንክ ለሦስት ዓመታት በተከታታይ የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን አስታውቀዋል፡፡
ባንኩ ባደረገላቸው ድጋፍም የብዙ ወገኖችን ሕይወት ማትረፋቸውን ገልፀው፤ ሌሎች ባንኮችና ድርጅቶች አርአያውን ተከትለው ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡
በድርጅታችን የአንድ ሰው የቀን ወጪ 20 ብር ነው ያሉት ሥራ አስኪያጁ፤ የ715 ወገኖች የቀን ወጪ 14,300 ብር፣ የወር ወጪ 429ሺህ ብር፣ የዓመት ደግሞ 5 ሚ. 219 ሺ 500 ብር ይሆናል ብለዋል፡፡ ዳሽን ባንክ ዘንድሮ ለማዕከሉ ባደረገው ድጋፍ፤ ተጨማሪ 70 ሰዎችን ከጐዳና ማንሳታቸውን ጠቅሰው፤ በተረጂ ወገኖች ስም ምስጋና አቅርበዋል፡፡
በቅርቡም “ዓለም ገነት ቆርቆሮ ፋብሪካ” ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል 500ሺ ብር የሚገመት የዓይነት ድጋፍ ማድረጉ ይታወቃል፡፡

አዋሽ ኢንሹራንስ ኩባንያ በአገሪቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው አዲስ የኢንሹራንስ ሶፍትዌር አሰርቶ ስራ ላይ ማዋሉን አስታወቀ፡፡ ኩባንያው በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ ውጤማታና ቀልጣፋ አገልግሎት ለደንበኞቹ ለመስጠት፣ የተቀናጀ የጠቅላላ መድን የመረጃ ሥርዓት (General Insurance Information System - Glls) ሶፍትዌር ማሰራቱን የጠቀሱት የኩባንያው ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ፀጋዬ ከሚሴ፤ ሶፍትዌሩን የሰራው የህንዱ ኩባንያ ኢንፎዥን፣ አማካሪው ደግሞ አገር በቀሉ ናሽናል ኮንሰልቲንግ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ዛሬ የደረስንበት ስኬት በሀገሪቷ የኢንሹራንስ ኢንዱስትሪ ውስጥ የተሟላ የቴክኖሎጂ መፍትሄ በመፍጠር ረገድ እንደ መልካም መነሻ ይታያል ያሉት ሥራ አስኪያጁ፤ በየክልሉ ያሉት ቅርንጫፎቻችን በሙሉ ይህንን አዲስ ሶፍትዌር ስለሚጠቀሙና የመረጃ ሥርዓቱ በኔትዎርክ የታገዘ በመሆኑ፣ የኩባንያው የሥራ አመራሮች የእያንዳንዱን ቅርንጫፍ ዝርዝር ሥራ በመከታተል ተገቢውን ድጋፍ በፍጥነት ይሰጣሉ ብለዋል፡፡ በመረጃ ሥርዓቱ አማካይነት ሪፖርቶችን በአጭር ጊዜ ውስጥ በማግኘት መረጃና ዕውቀት ላይ የተመሰረተ የማኔጅመንት ውሳኔ መስጠት እንደሚቻል ገልጸው፤ በውል ሰነዶች ውስጥ ያሉ መረጃዎች ሁሉ በሲስተሙ ውስጥ ስለተጠቃለሉ የሁሉም  ደንበኞች የውል፣ የካሣ፣ የጠለፋ ዋስትና፣ የገበያ ልማትና የፋይናንስ መረጃዎች በቀላሉ የሚናበቡ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
በውላቸው መሰረት ሶፍትዌሩን የሰራውና አማካሪው በየጊዜው ማሻሻያ እንደሚያደርጉና ይሄም ለኩባንያው ራዕይ መሳካት ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወት የገለፁት ሥራ አስኪያጁ፤ በዚህም “ግንባር ቀደምና ተመራጭ መድን ሰጪ መሆን” የሚለውን የኩባንያችንን ራዕይ እናሳካለን ብለዋል፡፡ ለሶፍትዌሩ 2.5 ሚሊዮን፣ ለሃርድዌሩ ደግሞ 3 ሚሊዮን ብር ወጪ መደረጉንም ገልጸዋል፡፡  

ከአገር ውጭ የሚደረጉ ጉዞዎችንና የትምህርት ክፍያ ማረጋገጫ ዋስትናዎችን መስጠት እንደጀመረ የገለፀው ኢትዮ ለይፍ ኤንድ ጀነራል ኢንሹራንስ አክሲዮን ማህበር፤ ይህም አገልግሎቱን የተሟላ ለማድረግ እንደሚያስችለው የድርጅቱ ኃላፊዎች ከትናንት በስቲያ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታወቁ፡፡
በአገሪቱ የኢንሹራንስ ገበያ ውስጥ አዳዲስ አሠራሮች ናቸው ከተባሉት ከእነዚህ የመድን ዋስትናዎች በተጨማሪ የህክምና፣ የዕድሜ ልክ፣ የኢንዶውመንት፣ የብድር ዕዳ ማስወገጃ፣ የእሳት ቃጠሎና የመብረቅ፣ የአበባ እርሻ፣ የሠራተኞች ጉዳት ካሳ፣ የምሕንድስና መድንና ሌሎች የዋስትና ዓይነቶችንም ለአገልግሎት ማቅረቡን አስታውቋል፡፡
በጥቅምት ወር 2001 ዓ.ም ከብሔራዊ ባንክ በተሰጠው ፍቃድ መሰረት ሥራ የጀመረው አክስዮን ማህበሩ፤ በአሁኑ ወቅት 58ሺ አክሲዮኖችን ለሽያጭ ማቅረቡንና የአገልግሎት አድማሱን በማስፋት ሚሊዮኖችን ለማገልገል ዝግጅቱን ማጠናቀቁን ገልጿል፡፡ በ
ቅርቡ በአዲስ አበባና በኦሮሚያ ክልል ሁለት ቅርንጫፎቹን በመክፈት የቅርንጫፍ ቢሮዎቹን ቁጥር ወደ 15 ከፍ ለማድረግ ማቀዱንም ኃላፊዎቹ ገልፀዋል፡፡

Saturday, 22 November 2014 12:15

ፊታውራሪ እርጅና

ባለ ጋሻ ጀግሬው ሰልፍ የሚያምርለት፣
አጀቡ አስፈሪ ጦር የበዛለት፣
ሠራዊተ ብዙ ፊታውራሪ እርጅና፣
ረጋ ብሎ ይመጣል ሞት ያስከትልና፡፡
    ስሜት ሲደበዝዝ፣
አካል ሲቀዘቅዝ፣
ዕይታ ሲደክም፣
አእምሮ ሲያዘግም፣
አደብ ይገዛሉ ህዋሳት በመላ፣
ሰውነት ይበርዳል ላይሞቅም ላይፈላ፡፡
ሆድ ጠግቦ ላይበላ ጉረሮ እህል ላይውጥ፣
ጉልበት ላይሆንለት ጦርን ሮጣ ማምለጥ፣
ነገርን አስታውሶ ለመናገር ፈጥኖ፣
እንደ ቀድሞ አይሆንም ጠፍቷልና ተንኖ፡፡
ዕቅድና ዓላማ እርግፍ አርጐ ትቶ፣
በትዝታ መኖር ምሃት፣ ተስፋ ጠፍቶ፡፡
እንስት ተባዕትን፣ ተባዕት እንስትን፣
ላይፈቃቀዱ ያሰንፋል ስሜትን፡፡
ጣፋጩ መራር ነው የሞቀው ቀዝቃዛ፣
በስተርጅና ሁሉም ይሆናል ጐምዛዛ፡፡
        ተው እርጅና፣
        ብቻህን ና!
ይህ ሁሉ ሳያንስህ ስኳሩን፣ ግፊቱን፣
ሪሁን፣ ራስ ምታቱን፣ ውጋት፣ ቁርጥማቱን፣
ነጭናጫ መሆኑን መነዝነዝ ዕለቱን፣
በትንሽ ትልቁ ፈጥኖ መከፋቱን፣
አንጋግተህ ያመጣህ ጨካኝ ነህ እርጅና፣
በስንት ጣዕሙ ሞት ይገባው ምስጋና፡፡
ኧረ ተው እርጀና አንተ ጅራታም፣
ምነው ጓዝህ በዛ (ሆንክና/ሆንክብኝ?) ኮተታም!
    ተው እርጅና፣
    ብቻህን ና!
ጥሩ ስም የሰጠህ ንገረን ማነው?
እርጅና እያሉ የጠሩህ ምነው?
እስቲ ከሞት ጋራ ተነጋገሩና፣
ከነ ተከታይህ በአንድ ላይ ሁኑና፣
እናንት? ሁለታችሁ ስብሰባ ግቡና፣
ስምህን ለውጡ ተመካከሩና፡፡
ሌላ ስም ይውጣልህ ከሞት ያላነሰ፣
ሥራህ ቢበዛ እንጂ መች ከእሱ ቀነሰ?
እናም…. ይኸው ወቀስኩህ ላትሰማኝ ነገር፣
 (ከእለታት ቀን ቆጥረህ መከሰትህ ሳይቀር?)
በሥራ በስፖርቱ አካሌን አጥብቄ፣
እጠብቅሃለሁ (አልቀርም) ወድቄ፡፡
ጦሬን ይዤ መጣሁ ደረስሁ ብትለኝም፣
እኔ አለሁ፣ አንተም ና ሥጋት አይገባኝም፡፡
በል እንግዲህ እርጅና - በቸር ያገናኘን
እስከዚያው ድረስ፣
አንተም አርጅተህ ሙት
- ወደ ልጅነቴ እኔም ልመለስ፡፡
*    *    *
ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ኅዳር 2007 ዓ.ም

Saturday, 22 November 2014 12:12

ፊታውራሪ እርጅና

ባለ ጋሻ ጀግሬው ሰልፍ የሚያምርለት፣
አጀቡ አስፈሪ ጦር የበዛለት፣
ሠራዊተ ብዙ ፊታውራሪ እርጅና፣
ረጋ ብሎ ይመጣል ሞት ያስከትልና፡፡
    ስሜት ሲደበዝዝ፣
አካል ሲቀዘቅዝ፣
ዕይታ ሲደክም፣
አእምሮ ሲያዘግም፣
አደብ ይገዛሉ ህዋሳት በመላ፣
ሰውነት ይበርዳል ላይሞቅም ላይፈላ፡፡
ሆድ ጠግቦ ላይበላ ጉረሮ እህል ላይውጥ፣
ጉልበት ላይሆንለት ጦርን ሮጣ ማምለጥ፣
ነገርን አስታውሶ ለመናገር ፈጥኖ፣
እንደ ቀድሞ አይሆንም ጠፍቷልና ተንኖ፡፡
ዕቅድና ዓላማ እርግፍ አርጐ ትቶ፣
በትዝታ መኖር ምሃት፣ ተስፋ ጠፍቶ፡፡
እንስት ተባዕትን፣ ተባዕት እንስትን፣
ላይፈቃቀዱ ያሰንፋል ስሜትን፡፡
ጣፋጩ መራር ነው የሞቀው ቀዝቃዛ፣
በስተርጅና ሁሉም ይሆናል ጐምዛዛ፡፡
        ተው እርጅና፣
        ብቻህን ና!
ይህ ሁሉ ሳያንስህ ስኳሩን፣ ግፊቱን፣
ሪሁን፣ ራስ ምታቱን፣ ውጋት፣ ቁርጥማቱን፣
ነጭናጫ መሆኑን መነዝነዝ ዕለቱን፣
በትንሽ ትልቁ ፈጥኖ መከፋቱን፣
አንጋግተህ ያመጣህ ጨካኝ ነህ እርጅና፣
በስንት ጣዕሙ ሞት ይገባው ምስጋና፡፡
ኧረ ተው እርጀና አንተ ጅራታም፣
ምነው ጓዝህ በዛ (ሆንክና/ሆንክብኝ?) ኮተታም!
    ተው እርጅና፣
    ብቻህን ና!
ጥሩ ስም የሰጠህ ንገረን ማነው?
እርጅና እያሉ የጠሩህ ምነው?
እስቲ ከሞት ጋራ ተነጋገሩና፣
ከነ ተከታይህ በአንድ ላይ ሁኑና፣
እናንት? ሁለታችሁ ስብሰባ ግቡና፣
ስምህን ለውጡ ተመካከሩና፡፡
ሌላ ስም ይውጣልህ ከሞት ያላነሰ፣
ሥራህ ቢበዛ እንጂ መች ከእሱ ቀነሰ?
እናም…. ይኸው ወቀስኩህ ላትሰማኝ ነገር፣
 (ከእለታት ቀን ቆጥረህ መከሰትህ ሳይቀር?)
በሥራ በስፖርቱ አካሌን አጥብቄ፣
እጠብቅሃለሁ (አልቀርም) ወድቄ፡፡
ጦሬን ይዤ መጣሁ ደረስሁ ብትለኝም፣
እኔ አለሁ፣ አንተም ና ሥጋት አይገባኝም፡፡
በል እንግዲህ እርጅና - በቸር ያገናኘን
እስከዚያው ድረስ፣
አንተም አርጅተህ ሙት
- ወደ ልጅነቴ እኔም ልመለስ፡፡
*    *    *
ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ኅዳር 2007 ዓ.ም

አሀዱ ኣባይነህ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ ነው፡፡ በሙያው ለአስራ ስምንት አመታት ሲሰራ ቆይቷል፡፡ በ90ዎቹ ዓመታት በዝቅተኛ ወጪ የዛፍ ላይ መኖሪያ ቤት ሰርቶ ነበር፡፡ በቅርቡ ደግሞ በአዲስ አበባ ከፈራረሱ ቤቶች ላይ ከተሰበሰቡ የተለያዩ ቁሳቁሶች እየሱስ በመባል በሚታወቀው አካባቢ እጅግ ውብ የሆነ ቤት ሰርቷል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ የኪነ-ህንፃ ባለሙያውን በሰራው ቤትና በአጠቃላይ በሙያው ዙሪያ አነጋግራዋለች፡፡


ከቤቶች ፍርስራሽ አዲስ ቤት የመገንባት ሃሳብ እንዴት መጣ?
ቤቱን የሰራሁለት ሰው ዶክተር ኤርሚያስ ሙሉጌታ ይባላል፡፡ ጥንታዊ ቁሶችን በጣም ይወዳል፡፡ እናም በከተማዋ ከሚፈርሱ ቤቶች ላይ መስኮቶች፣ በሮች፣ ሸክላዎች፣ የወለል ጣውላዎችና የደረጃ ድንጋዮችን ከገዛ በኋላ፣ በእነዚህ ቁሳቁሶች ቤት እፈልጋለሁ አለኝ፡፡
የሥራው ሂደት ምን ይመስላል?
የመጀመሪያው ስራ ቁሳቁሶችን መለየት ነበር፡፡ በብዛት ትላልቅ ቢሞች፣ በሮችና መስኮቶች ነበሩ፡፡ መስኮቶቹና በሮቹ ከተለያዩ ቦታዎች የተሰበሰቡ ናቸው፡፡ በመጀመሪያ እነሱን ወደ ንድፍ፣ ከዚያ ወደ ዲዛይን ለወጥኳቸው፡፡ የተሰበሰቡት በሮችና መስኮቶች ዲዛይኑ ላይ መለያ ተሰጥቷቸው ተቀመጡ፡፡ ቤቱን ዲዛይን አድርጌ ስጨርስ ደግሞ መስኮቶቹና በሮቹ በተሰጣቸው ስያሜ መሰረት እንዲገጠሙ ተደረጉ፡፡
የቁሳቁሶቹ አሰባሰብ እንዴት ነበር?
በየቦታው ቤት የሚያፈርሱ ሰዎች የዶክተር አድራሻ አላቸው፡፡ ቤት ሊያፈርሱ ሲሉ ደውለው እዚህ ቦታ ቤት ልናፈርስ ስለሆነ ናና የምትፈልገው ነገር ካለ ተመልከት ይሉታል፡፡ በነገራችን ላይ ይሄን ቤት ከሰራሁ በኋላ፣ በተመሳሳይ መልኩ ከፍራሽ ቤቶች በተሰበሰቡ ቁሳቁሶች ሌሎች ቤቶችንም ሰርቻለሁ፡፡
ከወጪ አንፃር እንዴት ነው?
ወጪው ጥሩ ነው፡፡ አዲስ ቁሳቁሶች ከመግዛት ይረክሳል፡፡ አንዳንዶቹ በሮች የተገዙት ስምንት መቶና ዘጠኝ መቶ ብር ነው፡፡ አዲሱ ይገዛ ቢባል ወደ 20 ሺ ብር የሚጠጋ ወጪ ይጠይቃል፡፡ ነገር ግን መስኮቶቹና በሮቹ ከተለያዩ ቤቶች ፍራሽ ላይ የተወሰዱ በመሆናቸው ቀለማቸው የተዘበራረቀ ነበር፡፡ ማፅዳቱና ወጥ የሆነ መልክ እንዲይዙ ማድረጉ ጊዜ ወስዷል፤ የተወሰነ ወጪም ጠይቋል፡፡ በሮቹና መስኮቶቹን ለማፅዳት በኦክሲጅን ቀለማቸው ተልጦ እንዲሸበሸብ ከተደረገ በኋላ፣ በብርጭቆ ወረቀት ታሽተው ቫርኒሽ ተቀብተው ነው ተመሳሳይ መልክ የያዙት፡፡ ሸክላዎቹም ሲመጡ ከሲሚንቶ ላይ ስለወጡ ነጭ ነበሩ፤ በብርጭቆ ወረቀት ታሽተውና ተቀብተው ነው ጥቅም ላይ የዋሉት፡፡ የተለያዩ አይነት ድንጋዮችንም ተጠቅመናል፡፡ ከአምቦና ከትግራይም አስመጥተናል፡፡
ከተለያዩ ቦታዎች የመጡ ቁሳቁሶች እንዴት ሊጣጣሙ ቻሉ?
 እዚህ ቤት ላይ ሸክላና ድንጋይ እንዲሁም ሸክላና እንጨት ተቀላቅለው ተሰርተዋል፡፡ መጣጣሙ የመጣው ሁሉም የተፈጥሮ ስለሆኑ ነው፡፡ እዚህ ቤት ላይ አልሙኒየም ብንከት አንድነቱ አይጠበቅም፡፡ እንጨትና ድንጋይ አብሮ ይሄዳል፡፡ ተፈጥሮም እንደዚያ ነው የቀላቀለቻቸው፡፡ ዛፍ አፈር ላይ ነው የሚበቅለው፤ ስለዚህ ሸክላና እንጨት ላይጣጣሙ አይችሉም፡፡ ውበት ግኡዝ ነገር አይደለም፡፡ የሃሳቦች ውሁድ ነው፡፡ አንድ የሚያምር የፅጌረዳ አበባ ሳይ ያማረበት ምክንያት ምንድን ነው ብዬ፣ የቀለም ውህደቱንና አወቃቀሩን እማርበታለሁ፡፡ ዛፍ ስናይም በጣም ያምረናል፡፡ ለምን ያምረናል ስንል ምናልባት ከተፈጠርን ጊዜ ጀምሮ ስናየው ስለኖርን ይሆናል፡፡ ዛፍ ውስጥ ግን የምንማራቸው የተፈጥሮ ህግጋት አሉ፡፡ የዛፍ ቅርንጫፍ የት ጋ እንደሚወጣ አናውቅም፤ ግርምት ነው፤ ስለዚህ ከዛፍ የግንድ አበቃቀል አግራሞት የሚፈጥሩ ክስተቶች ተምሬያለሁ፡፡ እዚህ ቤት ውስጥ ልክ እንደ ዛፍ ግንድ ግርምት የሚፈጥሩ ሊያደርጉ የሚችሉ ነገሮችን አስገብቻለሁ፡፡
ኪነ-ህንፃ ሳይንስ ነው አርት በሚል ስለሚደረገው ሙግት ምን ትላለህ?
ይሄ ፀሀይ ብርሀን ነው ሙቀት ብሎ እንደ መሟገት ነው፡፡ በጣም የተያያዙና የማይለያዩ ናቸው፡፡ ስለ አርት ስናወራ፣ አርቱ ያለ ሳይንሱ አይሆንም፡፡ ሳይንሱን ካየን ለአንድ ህንፃ ንፅህና አጠባበቅ የፍሳሽ ማስወገጃው በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ውሀ ሪሳይክል ማድረግ ወይም ማጠራቀም በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ብርሀን በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ እዚህ ቤት በማታ መብራቶቹ በርተው ብትመጪ አሁን ከምታይው ጋር በምንም አይገናኝም፣ በጣም የተለየ ነው፡፡ እኛ ሳይንስ የምንለው በአብዛኛው ከቴክኖሎጂ አንፃር ነው፡፡ ብርሀንን በቀለም  እንረዳዋለን፡፡ ይህ ቤት የጠዋት ብርሀን ሲያርፍበትና የማታ ብርሀን ሲያርፍበት ለቤቱ የሚሰጠውና የሚፈጥረው ቀለም በጣም የተለያየ ነው፡፡
አርቱን ካየን ደግሞ አሁን ለምሳሌ እዚህ ቤት ብዙ ቁሳቁሶችን ተጠቅመናል፡፡ እነዚህ ቁሳቁሶች ኮተት እንዳይመስሉ ግን ብዙ ለፍተናል፡፡ በይዘት፣ በመጠን፣ በቀለም ወዘተ… እንዲጣጣሙ በማድረግ ውበቱ እንዲጠበቅ እናደጋለን ይሄ ጥበብ ነው፡፡ እርስ በእርስ ሊስማሙ በሚችሉ ቁሳቁሶች መስራት ለአይን ሻካራ የሆኑ ነገሮች እንዳይኖሩ ያግዛል፡፡ መስኮት የቤት አይን ነው፤ ስለዚህ ነው እያንዳንዱ የዚህ ቤት መስኮት ሲከፈት አይን ጥሩ እይታ ያለው ነገር ላይ እንዲያርፍ የተደረገው፡፡
ከተለመደው የቤት አሰራር ሂደት በተለየ መንገድ ነው ቤቱን የሰራኸው፡፡ ምን ዓይነት ስሜት ፈጠረብህ?
እንደዚህ ቤት ነፃ ሆኜ የሰራሁት ስራ የለም፡፡ ከባለቤቱ ጋር እየተወያየንና እየተስማማን ነው የሰራነው፡፡ በጣም ነፃነት ስለነበረኝ እጅግ ደስ እያለኝ ነው የሰራሁት፡፡ ህንፃ ልክ እንደ ልጅ ነው፡፡ የኪነ-ህንፃ ባለሙያውና የሚያሰራው ሰው እንደ አባትና ልጅ ናቸው፡፡ ሁለቱ የማይስማሙ ከሆነ ልጁ ጥሩ አይሆንም፡፡ ተስማምተው በደንብ መስራት ከቻሉ ውጤቱ ጥሩ ይሆናል፡፡ ባለሙያው ቤቱን አምጦ የሚወልድ ቢሆንም ባለቤትም ቤቱ ምን ያህል ስፋት ይኖረዋል፣ በጀቱ ምን ያህል ነው  ወዘተ… የሚለውን ይወስናል፡፡ ጥሩ ስራ ስትሰሪ መተማመኑ ይመጣል፡፡ ከዚያ ደግሞ ነፃነት ይገኛል፡፡ ይህን ቤት ስሰራ አስቤ ያላደረግሁት፣ ነገር ግን ሌላ ስራ ላይ አደርገዋለሁ ብዬ ያሰብኩት ነገር አለ፡፡ ይኸውም ከዩኒቨርስቲዎች ጋር ተነጋግሬ፣  የኪነ ህንፃ ተማሪዎች ሳይት ላይ መጥተው ከቁፋሮ ጀምሮ ባሉ ስራዎች ላይ እንዲሳተፉ ማድረግ ነው፡፡
ለምንድነው ተማሪዎቹን ማሳተፍ የፈለግኸው?
ለምሳሌ የዚህ ቤት ስራ አራት አመት ነው የፈጀው፡፡ ከቁፋሮ ጀምሮ በዚህ ቤት ስራ ላይ የተሳተፈ ተማሪ፣ ትምህርቱን ጨርሶ ሲወጣ ነገሮችን የሚያይበት አይን የተለየ ይሆናል፡፡ አንድ የተሞላ ኮንክሪት ድሮዊንግ ላይ በቃ አንድ መስመር ነው፡፡ እዚያ አንድ መስመር ላይ ግን ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ብረት፣ ኮንክሪት፣ ኮንዲዩት፣ ፎርም ወርክ፣ የመብራት ኬብል፣ የመብራት መስመር፣ አሸዋ፣ሲሚንቶ፡ ጠጠር እንዲሁም ከዚያ በላይ ደግሞ ወዛደሩና ወዛደሯ አሉ፡፡ ከእነሱ መሀል ምሳ የበላ አለ፤ ያልበላ አለ፣ ከቤት ሰራተኝነት ወጥታ ይሄ ይሻላል ያለች አለች፣ ወደ ቀድሞ ብመለስ ይሻላል በሚል እያመነታች ያለች ትኖራለች፤ሁለቱም ያልተመቻት ደግሞ አለች፡፡ አንድ ተማሪ ይህንን ሁሉ አውቆ ከት/ቤት ሲወጣ ብዙ ነገሮችን ይዞ ይወጣል፡፡
ግቢው እጅግ ባማሩ አበቦችም የተሞላ ነው፡፡ ብዙ ጥረት እንደተደረገበት ያስታውቃል…
አዎ፤ በግቢው ውስጥ 300 የአበባ ዝርያዎች አሉ፡፡ ወደፊት የዕፅዋት አጥኚ (ቦታኒስት) መጥቶ ስለ ዝርያቸው የሚገልፅ ነገር እንዲሰራ ዶክተር እቅድ ይዟል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን ከብዙ ዓመታት በፊት ሰዎች እንደ ዛሬ ሳይሰለጥኑ በፊት፤ በአንዲት ትንሽ ከተማ አንድ እንደ ተዓምር የሚቆጠር ነገር ተፈጸመ፡፡ አንድ ቀንድ ያለው ጉጉት በአቅራቢያው ከሚገኘው ጫካ መጥቶ ከአንድ ሰው ግቢ ከሚገኝ የእህልና የከብት መኖ፣ እንዲሁም ጥራጥሬ መጋዘን  ውስጥ ይገባል፡፡ ሲነጋ እንዳይወጣ፤ ሌሎች ዶሮዎች ያዩኝና ልዩ ዓይነት ወፍ መሆኔን ሲረዱ ይጮሃሉ፡፡ ስለዚህ ዝም ብዬ ልቀመጥ ብሎ ወሰነ፡፡
ጠዋት የግቢው አሽከር ለከብቶች መኖ ሊወስድ ሲመጣ ጉጉቱን ጣራው አግዳሚ ላይ ሆኖ አየውና ደንግጦ “ጭራቅ! ጭራቅ!” እያለ እየጮኸ ወደ ጌትየው ሄዶ ተናገረ፡፡ የቤቱ ጌታም “አይ አንተ!  አንተንኮ እንደ እጄ መዳፍ ነው የማውቅህ፡፡ በሰፊ ሜዳ ቁራና ጥንብ - አንሣ የማባረር ልብ አለህ! አንዲት ጫጩት አንድ ጠባብ ቦታ ሞታ ብታይ ግን ወደዚያ ለመቅረብ ትልቅ ዱላ ፍለጋ ትሄዳለህ፡፡ ይሄን ጭራቅ ያልከውን እኔ ራሴ ሄጄ አየዋለሁ፡፡  ውሸት ቢሆን ወዮልህ!”
ጌትዬው  ወደ መጋዘን ገብቶ ሲያይ በድንጋጤ ተስፈንጥሮ ወጣ፡፡ ሮጦ ወደ ጎረቤቶቹ ሄዶ “ጎበዝ ማለቃችን ነው፡፡ አንድ አደገኛ ፍጡር ግቢዬ ገብቷል! ወጥቶ ወደ ከተማ ከገባ ህዝብ ማለቁ ነው፡፡ እንረዳዳና እዚሁ እርምጃ እንውሰድበት!” አለ፡፡
ወሬው ወዲያው ከመንደር መንደር በረረ፡፡ ከመንገድ መንገድ ሮጠ፡፡ ሰዉ ከፊሉ  ገጀራ፣ ከፊሉ ቆንጨራ፣  ከፊሉ ጦር፣ አካፋም፣ ማጭድም እያየዘ ወደግቢው ይመጣ ጀመር፡፡ ሰራዊት እንጂ አንድ ቀንዳም - ጉጉት ሊገድል የመጣ አይመስልም፡፡ በመጨረሻ ጭራሽ የከተማው ከንቲባ በሌሎች ሹማምንት ታጅበው መጡ፡፡ በተማው ለጥንቃቄ በየገበያው ምሽግ አሰርተዋል፡፡ አንድ የጎበዝ አለቃ ወደጉጉቱ ሄዶ ነበር፡፡ ድምፁን ሲሰማ በርግጎ ተመለሰ፡፡ ሌሎች ሁለት ሰዎች ሞከሩ፡፡
 ጉጉቱ ዓይኑን እያጉረጠረጠ በፍርሃት የሚያወጣው ድምፅ መብረቅ የመታቸው ያህል አስደግንጧቸው ዘለው ወጡ፡፡ በመጨረሻ አንድ መንዲስ የሚያህል ሰው፣ ያገሩ ጦረኛ ነው የሚባል ጀግና፣ ከጉጉቱ ሊተናነቅ ወስኖ መጣ፡፡ ከዛም በፉከራ ቃና “አንድን ጭራቅ “ጉድ! ጉድ!” በማለትና ዐይን ዐይኑን በማየት ልታባርሩት አትችሉም፡፡ ሁልሺም ቡከን ነሽ፡፡ ይሄን ጭራቅ ቀንዱን ይዤ ከጣራው ማውረድ አለብኝ! አለ፡፡ ሁለቱም የመጋዘኑ በር ብርግድ ብሎ ተከፈተ፡፡ አሁን ጉጉቱ ከጣራው  አግዳሚ እንጨት ላይ ተቀምጦ ቁልጭ ብሎ ይታያል፡፡ ጀግናው መሰላል አምጡልኝ አለ፡፡ መጣለት፡፡ ሰው ከፊሉ “ደፋር!” “አምበሳ!” አለው፡፡ ከፊሉ ይፀልይለት ጀመር፡፡
ጀግናው ወደ ጉጉቱ እየቀረበ ሄደ፡፡ ጉጉቱ ሁኔታውን በመጠራጠር የህዝቡን ጩኸት በመስማትና ምንም መውጫ እንደሌለው በማሰብ፤ ክንፎቹን አርገበገበ፡፡ ኩምቢውን ከፈተ፡፡ መንቆሩን ለጦርነት ያዘጋጀ መሰለ፡፡ ኩ-ፍ-ኩ-ኩ-ህ!” እያለ በፍጥነት መጮህ ጀመረ፡፡ ሰው “በለው!” “ያዘው” “አሳየው!” እያለ ከሥር ይጮህ ጀመር፡፡
“አይ ያገሬ ሰው! እኔ ያለሁበት ቦታ ቆመሽ ቢሆን አዳሜ ትንፍሽ አትይም ነበር!”
ጥቂት እርከን ለመውጣት ሞከረና ጀግናው፤ መርበትበት፣ መራድ ጀመረ፡፡ ቀስ እያለ በደረጃው ወረደ፡፡ ሰውም “አውሬው በትንፋሹ መርዞት ነው እንጂ የእኛ ጀግና እንዲህ ያለ ሰው አልነበረም፡፡ ለመሆኑ እንዲህ ያለ አውሬ ፊት ቆመን ህይወታችንን ማጥፋት አለብን እንዴ?” እያለ መንሾካሾክ ጀመረ፡፡ “ከተማችንን እንዳያጠፋ ምንድንነው የምናደርገው ማለት ቀጠለ?”  በመጨረሻ ከንቲባው መፍትሄ አመጡ፡፡
“ከመዘጋጃ ቤቱ ወጪ ተደርጎ ለመጋዘኑ ባለቤት የገንዘብ ካሳ እንስጥ፡፡ ለእህሉም. ለጭዱም፣ ለነዶውም መግዣ ይካካስለትና መጋዘኑ ከነአደገኛው አውሬ ይቃጠል! አሁን ለኢኮኖሚ የምናስብበት ጊዜ አይደለም!” ብራቮ ተባለ! ተጨበጨበ!
መጋዘኑ በአራቱም አቅጣጫ እሳት ተለቀቀበት፡፡ ምስኪኑ ወፍ በነበልባል ተለብልቦ አሰቃቂ ሞት ሞተ!
*          *           *
ነገሩ “አይ መሬት ያለ ሰው!” ያልነውን ያስታውሰናል፡፡ ነገርን በቅጡ አለማየት አሳቻ ፍፃሜ ላይ ያደርሰናል፡፡ ስለሆነም ወፍ አይተን ጭራቅ አየን እንላለን፡፡ አገሬው መንገኛ ከሆነ እንግዲህ  ይህንኑ ጭራቅ ጭራና ቀንድ ጨምሮለት ያልሆነ  ስዕል ፈጥሮ መዐት ይፈጥራል፡፡ የሰማህ ላልሰማህ የተባለ ይመስል እንደአዋጅ - ቃል ወሬ ይለፍፋል፡፡ ከዚያ ያገሩ ሹማምንት ያገባናል በሚል በተሳሳተው ነገር ላይ መመሪያ ይጨምሩበታል፡፡ መፍትሄ የማይፈጥር፣ ችግር ብቻ የሚያወራ ህዝብ ያልታደለ ነው፡፡ ኑሮ እንጉርጉሮ እንዳይሆን ማሰብ ያሻል! በወሬ የሚኖር ሰው፣ ነገር ያባብሳል እንጂ አንድ የመፍትሔ ጠጠር አይጥልም፡፡ ጎበዙን በለው! በለው! ለማለት የተፈጠሩ ይመስል፤ “በቅሎ ግዙ ግዙ አንድ አምሌ ላያግዙ!” ይሆናል ግርግሩ፡፡ ራሳችን በፈጠርነው የተሳሳተ ምስል “አስፈሪ! አደገኛ! …” እያልን፤ እሱኑም ፈርተን፤ ሌላውንም አስፈርተን፣ እሳት እንለኩሳለን! ይሄው ነው የአገራችን ፖለቲካ ነገረ - ሥራ!
“ጥፋታችንን አናምን፣ ሀጢያታችንን አንቀበል
ሁሌ ዝግጁና ፈጣን፣ በሌላው ላይ ለመቸከል
ደባ ነው መንገዳችን ሰርክ
ለእምዬ የአብዬን እከክ፣ በጥበብ ቅብ ለመላከክ!”
እንዳለው ገጣሚው፣ ራሳችን የሰራነውን ጥፋት በፈረደበት የበታች ወይም ቀን የጣለው ላይ መላከክ ነው ስራችን፡፡ ጥንት በአንድ አገር ዕምነት. ፍየል የዋህ ናት ትባል ነበር፤ አሉ፡፡
በሥርየት ቀን ቄስ ፍየሏ ጭንቅላት ለይ እጁን አድርጎ፣ የህዝቡን ሀጢያት ይናዘዛል፡፡ ጥፋት ሁሉ ወደ የዋህ ፍየል ይሄዳል፡፡ ይተላለፋል፡፡ ከዚያ ፍየሏ ወደ በረሀ ትነዳለች፡፡ እዛው ትቀራለች፡፡ የሰዉን ኃጢያት ሁሉ ይዛለት ጠፋች ማለት ነው፡፡ እንግዲህ Scapegoat የሚለው የፈረንጆች ቃል ከዚህ ነው የመጣው” ሊባል ይችላል፡፡ በሌላ ላይ ማሳበብ፣ በሌሎች ላይ መጫን ነው የአበሻ ኑሮ ዘዴ፡፡ ማዖ የባህል አብዮቱ ከሽፎ ክፉኛ ሲወድቅበት ምንም ይቅርታ አልጠየቀም፡፡ ይልቁንም በከፍተኛው የፓርቲ አመራር አባል ላይ ላከከ፡፡ የግል ፀሐፊውንም እንኳ ከወንጀሉ ነፃ አላደረጋትም፡፡ የእኛን ጨምሮ በየትም አገር በዘመቻም፣ በፕሬስም፣ በማፍረስም፣ በመገንባትም አንዳንድ የዋህ ፍየል አይጠፋም፡፡ ያውም እንደ ሰበብ ተደርጎ ሲቆጠር የማያጉረመርም ፍየል! ሌላ ምሣሌ:- ጥንት ጃንሆይ ለፀሐፊ ትዕዛዙ በቃል መመሪያ ይሰጡ ነበር አሉ፡፡ ያ መመሪያ ወደ ሥራ ተመንዝሮ ውጤቱ ሰናይ ከሆነ ምስጋናው ለጃንሆይ ይሆናል፡፡ ያልተሳካ ከሆነ ግን እርግማኑ ከፀሐፊ ትዕዛዝ ራስ አይወርድም፡፡ ዓለም የሥርዓተ- መላከክ (escapegoatism) ዓለም ነው፡፡
በተግባርና በወሬ መካከል ያለው ገደል - አከል ርቀት ሳይገደብ ለውጥ ማምጣት ከባድ ነው፡፡ ወሬ - ናፈቅ ትውልድ አገር ይሸረሽራል! “ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው” የሚለው የአበው አነጋገር ቧልት አይደለም፡፡ “ወሬ ሲበዛ ጥበብ ዋዛ” እንደማለት ነው፡፡ ወሬ ሲበዛ ያልተሰራው ተሰራ፣ ያላሸነፈው አሸነፈ፣ ያልቀናው ቀና ማለትን ይወልዳል፡፡ ከጊዜ ብዛት ሰው ያምናል፡፡ ከዚያ ውሸት ሁሉ ዕውነት ይመስላል፡፡ “ወሬ ሲበዛ ጭቃ ከግድግዳ ተፍረክርኮ ይወድቃል፡፡ ሙቀጫም  ለጭፈራ ይነሳል” የሚለው የወላይታ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!

15 ቢ. ብር የፈጁትን የነፋስ ተርባይኖች፤ በ5 ቢ.ብር የውሃ ግድብ መተካት ይቻላል
ከ10 ቢ. ብር በላይ ሃብት በከንቱ ባከነ፤ እንደ ዘበት በነፋስ ተወሰደ ማለት ነው
በረሃብተኛ ድሃ አገር፣ ይሄ ሁሉ ብክነት እብደት ነው? ወንጀል ነው? ወይስ ምን?
ግን፤ ወይ ነገሬ አላልነውም፤ ወይ አብረን አጨብጭበናል፤ ወይ በዝምታ ፈቅደናል
የግድብ ግንባታን የሚቃወሙ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች፣ መጫወቻቸው አድርገውናል
ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ፤ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖችን፤ “የድህነት ጠበቃ” ብለዋቸው ነበር

አገር    አመት    የነፋስ ተርባይኖች አቅም (ሺሜዋ)    በአመት ያመነጩት ሃይል (ሺ ጊዋሃ)    የተርባይኖቹ ብቃት
ጀርመን    2005    31    50    18%
ፈረንሳይ    2005    7.6    15    22%
ፖላንድ    2005    2.5    5.6    25%
ብሪታኒያ    2005    8.7    19    25%
ስፔን    2005    23    49    24%
ጣሊያን    2005    8    13.6    19%
አሜሪካ    2001    4    6.7    19%

በውሃ ግድብ የኤሌክትሪክ ሃይል የሚያመነጩ ጣቢያዎች ብቃትስ?    ከ40 – 50%
መንግስት ባለፈው ወር የተፈራረመውን ውል ጨምሮ፣ በነፋስ ተርባይን ኤሌክትሪክ የሚያመነጩ ሶስት ጣቢያዎችን ለማቋቋም 770 ሚሊዮን ዶላር ገደማ ሃብት አፍስሷል። ቀላል ገንዘብ አይደለም። ከ15.4 ቢሊዮን ብር በላይ ነው። የሶስቱ ጣቢያዎች ኤሌክትሪክ የማመንጨት አቅም ተደማምሮ ስንት እንደሆነ ደግሞ ተመልከቱ - 325 ሜጋዋት ብቻ ነው። በቃ፡፡ እና …ለዚህ ነው ያ ሁሉ ገንዘብ እየፈሰሰ ያለው? በገንዘብ መጫወት ይሉሃል፣ ይሄ ነው።
ለንፅፅር ያህል የህዳሴ ግድብ፤ ከነፋስ ተርባይኖቹ ጋር የሚመጣጠን የማመንጨት “አቅም” ለመፍጠር ምን ያህል ገንዘብ እንደሚፈጅበት ማስላት እንችላለን። ከግልገል ጊቤ ጣቢያዎች ጋር፣ አልያም ከተከዜ ወይም ከጣና በለስ ግድቦች ጋርም ማነፃፀር ይቻላል። የግድቦቹ አማካይ የግንባታ ወጪ፣ ዝቅተኛ ነው፡፡ ለአንድ ሜጋዋት 1.2 ሚሊዮን ዶላር አይደርስም። በዚህ ሂሳብ፣ ባለ 325 ሜጋዋት ማመንጫ ግድብ ለመገንባት፣ ቢበዛ ቢበዛ በአማካይ 390 ሚሊዮን ዶላር ቢፈጅ ነው (ማለትም፣ ከስምንት ቢሊዮን ብር በታች)። ለነፋስ ተርባይ ሲሆን ግን፣ ከ15 ቢሊዮን ብር በላይ!
ታዲያ፤ በአነስተኛ ወጪ፣ ከውሃ ሃይል ኤሌክትሪክ የሚያመነጩ ግድቦችንና ጣቢያዎችን መገንባት እየተቻለ፣ ያ ሁሉ ገንዘብ ለምን በነፋስ ተርባይን ይባክናል? እንዴ! ከሰባት ቢሊዮን ብር የሚበልጥ ልዩነትኮ፣ በጣም በጣም ብዙ ነው። በየእለቱና በየሰዓቱ መብራት እየተቋረጠ ስራ የሚስተጓጎለው፣ ፋብሪካዎች የሚከስሩት፣ ጨለማ ውስጥ የምናድረው፤ የኤሌክትሪክ ማሰራጫና ማከፋፈያ ተቋማት በማርጀታቸውና በማነሳቸው ነው ተብሎ የለ! በከንቱ የሚባክነውን ገንዘብ፣ ለዚህ ለዚህ ማዋል ይቻል ነበር።
“መቼም፣ የበርካታ ቢሊዮን ብር ሃብት በከንቱ እንዲባክን አይደረግም፤ አንዳች አሳማኝ ምክንያት መኖር አለበት” የሚል ሃሳብ ይመጣላችሁ ይሆናል። ‘ሃሳብ’ ሳይሆን፣ ‘ምኞት’ ብትሉት ይሻላል - ለዚያውም የማይጨበጥ ምኞት። አንዳችም አሳማኝ ምክንያት የሚያቀርብላችሁ አታገኙም። በነፋስ ተርባይን አማካኝት የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጨት፣ በጣም ከፍተኛ ወጪ እንደሚፈጅ...፣ በይፋ የሚታወቅ፣ በቁጥር የተሰላ፣ ማንም ጤናማ ሰው ሊክደው የማይችል ሃቅ ነው።
አስገራሚው ነገር፣ የነፋስ ተርባይኖች ችግር፣ ብዙ ገንዘብ መፍጀታቸው ብቻ አይደለም። ለካ አንዳንዴ የአገራችን ሰዎች “የባሰ አታምጣ” የሚሉት ወደው አይደለም! በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሚባለው ነው። በብዙ ወጪ የተተከሉት የነፋስ ተርባይኖች፣ የታቀደላቸውን ያህል ውጤታማ አይደሉም። ኤሌክትሪክ የማመንጨት ብቃታቸው አነስተኛ ነው። የአቅማቸውን 30 በመቶ ያህል እንኳ ብቃት የላቸውም። በውሃ ግድብ አማካኝነት ኤሌክትሪክ የሚያመነጩ ጣቢያዎች ግን፣ የአቅማቸውን 48 በመቶ በሚደርስ የላቀ ብቃት ኤሌክትሪክ እንደሚያመነጩ የኢትዮጵያ የበርካታ አመታት መረጃ ያሳያል። ይህን ለማረጋገጥና የአምና መረጃዎችን ለማየት፤ ብሔራዊ ባንክ በየሶስት ወሩ የሚያወጣቸውን ሪፖርቶች ተመልከቱ። አልያም ከአስር አመታት በፊት የነበረውን መረጃ፣ ከኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ሪፖርቶች ታገኛላችሁ።  
በአጭሩ፣ የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎችን እና የውሃ ግድብ ጣቢያዎችን ስናነፃፅር፣ የነፋስ ተርባይኖች ኪሳራና ብክነት እጥፍ ድርብ መሆኑን በማያጠራጥር መንገድ መገንዘብ እንችላለን። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች፣ የግንባታ ወጪ በግማሽ ያህል ቅናሽ ነው። ኤሌክትሪክ የማመንጨት ብቃታቸው ደግሞ ከነፋስ ተርባይኖች በ70 በመቶ ያህል ይልቃል።
እንዲያውም፣ ወደ ፊት የነፋስ ተርባይኖቹ ብቃት ይባስ እየቀነሰ መሄዱ አይቀርም። ለምን በሉ። አንደኛ ነገር፣ የነፋስ ተርባይኖች እድሜ በጨመረ ቁጥር፣ ብቃታቸው እየወረደ ይሄዳል። ሁለተኛ ነገር፣ ለነፋስ ተርባይኖች እጅግ በጣም ተስማሚ የሆኑ ነፋስ የሚበዛባቸውና የሚዘወትርባቸው ቦታዎች ናቸው አሁን ጥቅም ላይ የዋሉት። ወደ ፊት ተመሳሳይ ቦታ ለማግኘት አስቸጋሪ ነው። እናም የነፋስ ተርባይኖች ብቃት ከ25 በመቶ በታች መውረድ አይቀርለትም።
የነፋስ ተርባይኖች ብቃት 30 በመቶ እንኳ መድረስ ያልቻለው በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም። በሁሉም የአውሮፓ አገራትና በአሜሪካ ጭምር፣ ላለፉት በርካታ አመታት በተጨባጭ የተመዘገበ መረጃ ነው። የነፋስ ተርባይን አፍቃሪ ተቋማት ራሳቸው የሚያቀርቡትን መረጃ ብቻ ልጥቀስላችሁ። የነፋስ ተርባይኖችን ለማስፋፋት መንግስታት ተጨማሪ ድጎማ መስጠት ይኖርባቸዋል እያለ ዘመቻ የሚያካሂደው የጀርመን ተቋም HSH NORDBANK፤ ባለፈው መስከረም ወር Sector Study WIND ENERGY በሚል ርዕስ ካቀረበው አመታዊ ሪፖርት የተወሰዱ ጥቂት መረጃዎችን እነሆ።
ከአመት በፊት በ2005 ዓ.ም፤ ጀርመን ውስጥ የሚገኙ ባለ 31ሺ ሜጋዋት የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎች፣ 50ሺ ጊዋሃ ሃይል አመንጭተዋል ይላል ሪፖርቱ። ይህም ማለት የተርባይኖቹ ብቃት 18% ገደማ እንደሆነ ያረጋግጣል። የአሜሪካም ተመሳሳይ ነው። በ2001 ወደ አራት ሺህ ሜጋዋት የሚጠጋ አቅም ያላቸው የነፋስ ተርባይኖች በ19% የብቃት ደረጃ 7ሺ ጊዋሃ የኤሌክትሪክ ሃይል እንዳመነጩ፣ የአሜሪካ የኢነርጂ መስሪያ ቤት ገልጿል - እየተገባደደ ባለው የፈረንጆች አመት ባወጣው ሪፖርት።
የብሪታኒያ ትንሽ ይሻላል። የ8.7ሺ ሜጋዋት አቅም ያላቸው የነፋስ ተርባይኖች፣ በአመት ውስጥ ያመነጩት የሃይል መጠን 19 ሺ ጊዋሃ ነው። (ማለትም ተርባይኖቹ የሚሰሩት በ25% ብቃት ነው)። ምን አለፋችሁ? በየትኛውም የአውሮፓ አገር፣ በየትኛውም ጊዜ፣ የነፋስ ተርባይኖች ብቃት 30% ደርሶ እንደማያውቅ፤ HSH NORDBANK ያወጣው ሪፖርት ያስረዳል። ከተርባይኖቹ እድሜ ጋርም፣ ብቃታቸው ወደ ሃያ በመቶ ይወርዳል።
ነፋስ ተርባይኖች ብቃት፣ በአንዳንዶቹ አገራት ከ20 በመቶ ሊበልጥ የቻለው አንዳች ተአምረኛ ዘዴ ስለፈጠሩ አይደለም። በመሬት ላይ ሳይሆን በባህር ላይ የተተከሉ ተርባይኖችን ስለሚጠቀሙ ነው ልዩነት የተፈጠረው። ምድር ላይ ከሚተከሉት ተርባይኖች ይልቅ የባህር ላይ ተርባይኖች፤ በጥቂቱም ቢሆን የላቀ ብቃት አላቸው። እንዲያም ሆኖ፤ ብዙም ለውጥ የለውም። አንደኛ፣ የባህር ላይ ተርባይኖች ያን ያህልም የሚያስመካ ልዩነት አያመጡም። ሁለተኛ ነገር፤ ባህር ለሌላቸው እንደ ኢትዮጵያ ለመሳሰሉ አገራት፤ ትርጉም የለውም። ምን ለማለት ፈልጌ ነው? ነጋ ጠባ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖችና አጨብጫቢዎች ከሚለፍፉት ስብከት በተቃራኒ፤ የነፋስ ተርባይኖች ብቃት ውሎ አድሮ በተጨባጭ 20% ገደማ እንደሚሆን ለመግለፅ ፈልጌ ነው።
በውሃ ግድብ አማካኝነት የኤሌክትሪክ ሃይል የሚያመነጩ ጣቢያዎች ግን፣ ከብዙ አመታት አገልግሎት በኋላም በአማካይ 48 በመቶ ገደማ መሆኑን ደግሞ አትርሱ። ለዚህ ማረጋገጫ፣ ከኤሌክትሪክ ኮርፖሬሽንና ከብሄራዊ ባንክ የ2006 ዓ.ም ሪፖርቶች በተጨማሪ፣ ሌላ መረጃ ትፈልጉ ይሆናል። Study on the Energy Sector in Ethiopia በሚል በጃፓን ኤምባሲ የተዘጋጀውን የጥናት ሰነድ መቃኘት ትችላላችሁ፡፡ እስከ 2000 ዓ.ም ድረስ በነበረው መረጃ መሰረት፣ የኤሌክትሪክ ሃይል የሚያመነጩ ግድቦች በድምር “ባለ 670 ሜጋዋት” እንደነበሩ በማስታወስ፤ በአማካይ በአመት 2.84 ጊዋሃ ሃይል ያመነጩ እንደነበር ጥናቱ ይገልፃል። (የግድቦቹ ብቃት ከ48% በላይ ነበር ማለት ነው።) የአምና መረጃዎችን ብንመለከትም፣ ተመሳሳይ ውጤት እናገኛለን።    
የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎችና የውሃ ግድብ ጣቢያዎች፤ ኤሌክትሪክ የማመንጨት ብቃታቸው እንዲያ የሚራራቀው ያለምክንያት አይደለም። የመኪና ሞተርን እንደ ምሳሌ በመውሰድ ልዩነቱን ለማሳየት ልሞክር። ሞተሩ የአቅሙን ያህል ለመስራት ነዳጅ ያስፈልገው የለ? የነፋስ ተርባይኖች፣ መንቀሳቀሻ ነዳጃቸው “ነፋስ” ነው። ለውሃ ግድብ ጣቢያዎች ደግሞ፤ ነዳጃቸው ውሃ ነው። እንዲህ የየራሳቸው “ነዳጅ” ቢኖራቸውም፤ የነዳጅ አጠቃቀማቸው ግን ይለያል። የነፋስ ተርባይኖች ነዳጃቸውን (ነፋስን) መቆጣጠርና ማጠራቀም አይችሉም። የነዳጅ መቆጣጠሪያና ማርሽ እንደ ሌለው መኪና ቁጠሩት - ለአቀበቱም ለቁልቁለቱም፣ ሲቆምም ሲጓዝም ነዳጁን ይጠቀማል። ነዳጅ ሲቋረጥበት፣ ከማጠራቀሚያ አውጥቶ መጠቀም አይችልም። ነዳጅ ሲያልቅበት በጀሪካን እስኪመጣለት ድረስ መኪናውን አቁሞ እንደሚጠባበቅ ሾፌር ማለት ነው። የውሃ ግድቦች ግን፤ የነዳጃቸው (የውሃ) መጠንን እየተቆጣጠሩ መልቀቅ፤ ብዙ የኤሌክትሪክ ሃይል በማያስፈልግበት ወቅትም ውሃውን ይዘው ማቆየትና ማጠራቀም ይችላሉ። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች፤ የኤሌክትሪክ ሃይል የማመንጨት ብቃታቸው ከፍተኛ የሚሆነው በዚህ ዋና ምክንያት ነው።እዚህ ላይ፤ አንድ ቀላል ጥያቄ ቢነሳ አይገርምም። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች ብቃት በእጥፍ የሚበልጥ ከሆነ፤ ወጪያቸው ደግሞ በግማሽ ያህል ቅናሽ ከሆነ ለምንድነው የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎችን ለመገንባት ሃብት የሚባክነው? ወጪያቸው እጥፍ ነው፤ ብቃታቸው ደግሞ በግማሽ የወረደ መሆኑ እየታወቀ!
በነፋስ ተርባይኖች ምትክ 325 ሜጋዋት የሚያመነጭ ግድብ ቢገነባ ኖሮ፣ ወጪው በ7.6 ቢሊዮን ብር ያነሰ ይሆን ነበር። ከዚህም በተጨማሪ፣ የግድብ ሃይል ማመንጫ ብቃት 48% ገደማ ስለሆነ፤ በየአመቱ 1300 ጊዋሃ ሃይል ማመንጨት በቻለ ነበር። የነፋስ ተርባይኖች ግን፤ ወጪያቸው በእጥፍ ቢበልጥም፤ በየአመቱ የሚመነጩት ሃይል 800 ጊዋሃ ገደማ ብቻ ነው።ልዩነቱ እጥፍ ድርብ ነው። የነፋስና የግድብ ማመንጫ ጣቢያዎቹ “ባለ 325 ሜጋዋት” የሚል ስያሜ ቢለጠፍባቸውም፤ ወጪያቸውና ብቃታቸው በጣም ይራራቃል። የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎች፤ ወጪያቸው ከፍተኛ፣ ብቃታቸው ደግሞ ዝቅተኛ ነው። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች ደግሞ ወጪያቸው ዝቅተኛ፣ ብቃታቸው ግን ከፍተኛ። እንዳያችሁት፣ “ባለ 325 ሜጋዋት” የተሰኙት የነፋስ ተርባይኖች በአመት 800 ሜዋሃ ገደማ ብቻ ነው ማመንጨት የሚችሉት። የዚህን ያህል የኤሌክትሪክ ሃይል ለማመንጨትማ፤ ባለ 190 ሜጋዋት የግድብ ማመንጫ ጣቢያ መገንባት በቂ ነው - ለዚያውም ወጪው 230 ሚሊዮን ዶላር አይሞላም - ከ5 ቢሊዮን ብር በታች መሆኑ ነው። እንግዲህ አስቡት፤ ይህችኑ የሃይል መጠን ለማመንጨት ነው ከ15 ቢሊዮን ዶላር በሚበልጥ ወጪ ለነፋስ ተርባይን ጣቢያዎች  እየፈሰሰ ያለው። በሌላ አነጋገር፤ ከ10 ቢሊዮን ብር በላይ ሀብት በከንቱ እንዲባክን ተደርጓል። እብደት፣ ወንጀል ወይስ ምን? የጊዜ ጉዳይ እንጂ፤ በዚህ ብክነት ላይ የተሳተፉና የተባበሩ ሃላፊዎች ውሎ አድኖ ተጠያቂ መሆናቸው አይቀርም፡፡ እስከዚያው ግን መብራት በየሰዓቱ እየተቋረጠብን እንቀጥላለን፡፡ ለነገሩ፤ አስር ቢሊዮን ብር በከንቱ ለነፋስ ሲበተን እያየን ዝምታን የመረጥን ሰዎችስ፤ መብራት ሲቋረጥብን ቢውል ቢያድር ይገርማል፡፡ የእጃችንን ነው ያገኘነው፡፡  

በ 6 ወራት 8 አዳዲስ አውሮፕላኖችን አስገባለሁ ብሏል

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በምዕራብ አፍሪካ አገራት የተቀሰቀሰው የኢቦላ ቫይረስ በፈጠረው ስጋት ምክንያት የመንገደኞች ቁጥር በመቀነሱ፣ በወር ከ8 ሚ. ዶላር በላይ ገቢ እያጣ እንደሆነ ሮይተርስ ትናንት ዘገበ፡፡
የአየር መንገዱን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማርያምን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ኢቦላ ለአየር መንገዱ ከየትኛውም አለማቀፍ የኢኮኖሚ ቀውስ በበለጠ በእንቅስቃሴው ላይ ተጽዕኖ የሚፈጥር ተግዳሮት ሆኖበታል፡፡
ምንም እንኳን በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው የአየር መንገዱ ዋነኛ ማዕከል፣ በኢቦላ ቫይረስ ከተጠቁት የምዕራብ አፍሪካ አገራት የረጅም ሰዓታት በረራ የሚወስድ ርቀት ላይ ቢገኝም፣ በሽታው በአየር መንገዱ ተጓዦች ቁጥር ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ መፍጠሩ አልቀረም ያሉት አቶ ተወልደ፤ ሁኔታው በመጪዎቹ ጥቂት ወራት ውስጥ እንደሚቀየርና የመንገደኞች ቁጥርም ወደነበረበት እንደሚመለስ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡በአገራቱ የተቀሰቀሰው የኢቦላ ወረርሽኝ፣ በመላ አህጉሪቱ ከሚደረጉ በረራዎች በአብዛኞቹ ላይ ተጽዕኖ መፍጠሩንና በሽታው ለአፍሪካ አየር መንገዶች ዋነኛው ስጋት መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
ኢቦላ ወደ አፍሪካ አገራት በሚጓዙ መንገደኞች ላይ ስጋት መፍጠሩን የጠቀሰው ዘገባው፤ በተለይም በእስያውያን  መንገደኞች ዘንድ ያለውን ፍላጎት እንዲቀንስ አድርጎታል፡፡ በዘርፉ የሚታዩ የገበያ ችግሮች እንዳሉ ሆነው፣ አየር መንገዱ የቀየሳቸውን የረጅም ጊዜ የዕድገት ዕቅዶች መተግበሩን እንደሚቀጥል ገልጸው፣ እስከ መጪው 2015 የመጀመሪያዎቹ ስድስት ወራት፣ 3 ቦይንግ 787-8 ድሪምላይነር አውሮፕላኖችን ጨምሮ 8 አዳዲስ አውሮፕላኖችን ገዝቶ በስራ ላይ እንደሚያሰማራ አስረድተዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሁለት ቦይንግ 777 የጭነት አውሮፕላኖችን ለመግዛት የሚውል የ41.4 ሚሊዮን ዶላር ብድር አይኤንጂ ካፒታል ከተባለ አሜሪካ የፋይናንስ ተቋም ማግኘቱን ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የገንዘብ ብድሩ መገኘቱና አውሮፕላኖቹ መገዛታቸው፣ በአፍሪካ ትልቁ የጭነት አየር መንገድ ሆኖ የመዝለቅ ዕቅድ ለያዘው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አቅምንና የአገልግሎት ጥራትን በማሳደግ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ተገልጿል፡፡