Administrator

Administrator

“በዚህ ወር ሌላ የአንበጣ ወረርሽኝ ሊከሰት ይችላል” - ፋኦ የአንበጣ መንጋው ጉዳት እንዳያደርስ እየተከላከልን ነው - ግብርና ሚ/ር

     በግብርና ሚኒስቴር የእፅዋት ጥበቃ ዳይሬክተር ወ/ሮ ህይወት ለማ፤ የአንበጣው መንጋ በሱማሌ ላንድ ተራብቶ በንፋስ እየተገፋ ወደ ኢትዮጵያ መግባቱን ገልጸው፣ በሶማሌና በኦሮሚያ አካባቢ በመስኖ በሚለማ ሰባት ሄክታር ሽንኩርትና ድንች ላይ ጉዳት ማድረሱን ጠቅሰዋል፡፡ ከዚህ ውጭ የከፋ ጉዳት ሳያደርስ በቁጥጥር ስር ውሏል ያሉት ወ/ሮ ህይወት፣ ከመጋቢት አጋማሽ ጀምሮ ከሱማሌ ላንድ የገባው የአንበጣ መንጋ አሁን ያለበት እድሜው ብዙ እንዲመገብ የሚያደርገው እንዳልሆነ ጠቅሰው፣ ሚኒስቴር መ/ቤቱ የመከላከል ስራዎችን በማከናወኑ ጉዳት አላደረሰም ብለዋል፡፡ ከ30 የአንበጣ መንጋዎች ለብቻ ተለይቶ የመጣ አንድ መንጋ ሰሞኑን በአዲስ አበባ በኩል እንዳለፈና የንፋስ አቅጣጫን እየተከተለ እንደሚሄድ ወ/ሮ ህይወት ተናግረው፤ አሁን ያለው መንጋ አድጎና እንቁላል ጥሎ እንዳይራባ የመከላከል እርምጃዎች ተወስደዋል ብለዋል፡፡

ሶማሌ፣ ድሬዳዋና ኦሮሚያ ክልል ላይ የአንበጣ መንጋ እንዳለ ጠቅሰው፣ ለብቻ ተነጥሎ ወደ አዲስ አበባ የመጣው መንጋ ከምስራቅ ወደ ምዕራብ የንፋስን አቅጣጫ ተከትሎ በምዕራብ አዲስ ከአዲስአለም አለፍ ብሎ ወልመራ እንደደረሰና የአካባቢው ግብርና ጽ/ቤቶች አስፈላጊውን የመከላከል ስራ እየሰሩ መሆናቸውን ዳይሬክተሯ ተናግረዋል፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአለም የምግብ ፕሮግራም፣ በምስራቅ ኢትዮጵያ አካባቢ የተከሰተው የአንበጣ መንጋ ወረርሽኝ፣ በወቅቱ ተገቢው መፍትሄ ካልተሰጠው፣ በአርብቶ አደር ማህበረሰቡ ህልውና ላይ አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል ገለጸ፡፡ በዚህ አመት 6 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን እመግባለሁ ብሏል፡፡

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የምግብና የእርሻ ድርጅት በበኩሉ፣ የበረሃ አንበጣ መንጋ ወረርሽኙ በኢትዮጵያ፣ በሳኡዲ አረቢያና በኦማን ሊባባስ እንደሚችል ባለፈው ሳምንት ባወጣው መረጃ ጠቁሟል፡፡ የአለም የምግብ ፕሮግራም ቃል አቀባይ ኤልዛቤት ባይርስን ጠቅሶ ሮይተርስ ከጄኔቫ እንደዘገበው፣ በአገሪቱ የተከሰተው የአንበጣ ወረርሽኝ አፋጣኝ መፍትሄ ካልተበጀለት በሰብሎች ላይ ጥፋት ሊያስከትል የሚችል ነው፡፡ “በምስራቃዊ ኢትዮጵያ አካባቢዎች እየታየ ያለው የአንበጣ መንጋ ወረርሽኝ፣ የአለም የምግብ ፕሮግራምን እያሳሰበው ነው፡፡ ወረርሽኙን ለመግታት በወቅቱ ተገቢ እርምጃዎች ካልተወሰዱ፣ የአካባቢው ማህበረሰብ ህልውና አደጋ ላይ ሊወድቅ ይችላል” ብለዋል ቃል አቀባዩዋ፡፡ ባለፉት አራት ተከታታይ አመታት በአገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል የጣለው ዝናብ፣ ከሚጠበቀው አማካይ የዝናብ መጠን በታች እንደነበር ያስታወሱት ኤልዛቤት ባይርስ፣ ይህም ከአንበጣ ወረርሽኙ በተጨማሪ ለምርት መቀነስ የሚዳርግ ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ተናግረዋል፡፡

የእርስ በእርስ ጦርነትን በመሸሽ ከደቡብ ሱዳን ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ስደተኞች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱን ጠቁመው፣ የአለም የምግብ ፕሮግራም ስደተኞቹን ለመመገብ የያዘውን በጀት እያሟጠጠበት እንደሚገኝና ገንዘቡ እስከ መጪው ወር ሊያልቅ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ስድስት አመታት፣ ከ120 ሺህ በላይ ደቡብ ሱዳናውያን ስደተኞች ድንበር ተሻግረው ወደ ኢትዮጵያ የገቡ ሲሆን አብዛኞቹም በርሃብ የተደቆሱና የምግብ እጥረት ያጠቃቸው እንደሆኑ የጠቆመው የአለም የምግብ ፕሮግራም፣ ይህም በአገሪቱ የሚገኙ ስደተኞችን አጠቃላይ ቁጥር ወደ ግማሽ ሚሊዮን ከፍ እንዳደረገው ገልጿል፡፡ የአለም የምግብ ፕሮግራም ከስደተኞች በተጨማሪ የምግብ እርዳታ የሚያስፈልጋቸውን ከ1 ሚሊዮን በላይ ችግረኛ ኢትዮጵያውያን እየመገበ እንደሚገኝ ጠቁሞ፣ በዚህ አመትም 6 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን የምግብ ድጋፍ ተጠቃሚ እንደሚደርግ አስታውቋል፡፡ የአለም የምግብ ፕሮግራም የኢትዮጵያን መንግስት መረጃ በመጥቀስ፣ የምግብ እጥረት ከአምስት ኢትዮጵያውያን ህጻናት የሶስቱን ዕድገት እያቀጨጨ እንደሚገኝ መናገሩን ዘገባው ጨምሮ ጠቁሟል፡፡

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የምግብና የእርሻ ድርጅት በበኩሉ፣ ባለፈው ሳምንት ባወጣው መረጃ የበረሃ አንበጣ መንጋ ወረርሽኙ በኢትዮጵያ፣ በሳኡዲ አረቢያና በኦማን ሊባባስ እንደሚችል ገልጾ፣ በርካታ የአንበጣ መንጋዎች ከሰሜን ምዕራብ ሶማሊያ በመነሳት፣ ወደ ምስራቃዊ ኢትዮጵያ መግባታቸውን ተናግሯል፡፡ ምንም እንኳን በምስራቃዊ ኢትዮጵያ የተከሰተውን የበረሃ አንበጣ መንጋ ወረርሽኝ በቁጥጥር ስር ለማዋል የአየር ላይና የምድር እንቅስቃሴዎች ቢደረጉም፣ አንበጦቹ ሊራቡና በዚህ ወር አዳዲስ መንጋዎችን ፈጥረው የበለጠ ሊሰራጩ እንደሚችሉ ድርጅቱ ገልጿል፡፡

በአንድ ወር ከ700 በላይ ስደተኞች ድንበር ሲያቋርጡ ተይዘዋል አብዛኞቹ ተባርረው የመጡ ናቸው

      በሶማሌ ላንድ በኩል ቀይ ባህርን በጀልባ ተሻግረው ወደ ሳዑዲ አረቢያና ወደ የመን ለመሄድ ጉዞ የጀመሩ ከ700 በላይ ወጣቶች ሀረር አካባቢ እንደተያዙ የክልሉ ፖሊስ ገለፀ፡፡ ከ700 በላይ የሚሆኑት የተያዙት በአንድ ወር ውስጥ መሆኑን የጠቀሱት የሐረሪ ክልል ፖሊስ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ኮማንደር ጣሰው ቻለው ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት አብዛኞቹ ከ4ወር በፊት የሳዑዲ አረቢያ ከሳዑዲ የተባረሩ ስደኞች ተመልሰው እየሄዱ ነው በአንድ ወር ከ700 በላይ ስደተኞች ድንበር ሲያቋርጡ ተይዘዋል አብዛኞቹ ተባርረው የመጡ ናቸው መንግስት ህገወጥ ናችሁ በሚል ወደ ኢትዮጵያ የመለሳቸው ናቸው፡፡

ወጣቶች ከባሌ፣ ከጅማ፣ ከአርሲ፣ ከትግራይ ክልል ከተሞችና፣ ከደሴ በመነሳት ለህገወጥ አስኮብላዮች እስከ 5ሺ ብር በመክፈል በቅብብሎሽ ከከተማ ከተማ የተሸጋገሩ ሃረር የደረሱ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ፖሊስ፣ የህገወጥ ስደት ሰንሰለቱ ቦሳሶ ድንበርን በመሻገር በጀልባ ከ40 ሠዓት በላይ በመጓዝ ሳዑዲ አረቢያና የመን ድረስ እንደሚዘልቅ ፖሊስ አስረድቷል፡፡ ህገወጥ ስደትን መከላከል የፖሊስ የእለት ተእለት ስራ እየሆነ መምጣቱን የጠቆሙት ሃላፊው፤ ከሐረር ከተማ ወጣቶችን በድብቅ በአይሱዙ በመጫን ወደ ሶማሌ ላንድ የሚያጓጉዙ ህገወጥ ሰዎች በፖሊስ ቁጥጥር ስር እያዋሉ ነው፤ በሚያዚያ ወር ግን ህገወጥ የስዎች ዝውውር በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል ብለዋል፡፡ በሶማሌ ላንድ በኩል ባህሩን ለማቋረጥ በጀልባ ቀንና ሌሊቱን የሚደረገው ጉዞ እንደሆነ የጠቆመው ፖሊስ፣ ሰሞኑንም 80 ሰዎችን ጭኖ ይጓዝ የነበረ ጀልባ ተገልብጦ በርካታ ስደተኞች ህይወት ማለፉን አስታውሷል፡፡ በየዕለቱ ከአራት በላይ ጀልባዎች ህገወጥ ስደተኞችን በመጫን ወደ የመን ድንበር እንደሚደርሱና አንድ ጀልባ ከ80 እስከ 90 የሚደርሱ ስደተኞች እንደሚጫንም ገልጸዋል፡፡

  • • ‹‹የፓትርያርኩን ሥልጣን ይገድባል›› በሚል ተተችቷል
  • ‹‹አመራራቸውን በብቃት እንዲያከናውኑ የሚያግዝ ነው›› /የሕግ ረቂቁ/
  • ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ የሚያስተላልፉት በብሔራዊ ቋንቋ ብቻ ይኾናል

       የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ፣ ፓትርያርኩን የሚያግዝ እንደራሴ እንደሚመደብ በሚገልጽና የፓትርያርኩን ሓላፊነትና ተጠያቂነት በጉልሕ የሚያሳዩ አንቀጾችን ባካተተ የሕግ ረቂቅ ላይ እየተወያየ እንደኾነ ተገለጸ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ በ1991 ዓ.ም. ያወጣችውን ሕግ ከሌሎች ሕጎች፣ ደንቦችና መመሪያዎች ጋር በማጣጣም፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዕድገትና ነባራዊ ኹኔታዎች ጋራ በማገናዘብ ያሻሽላል የተባለው የሕግ ረቂቁ ለውይይት የቀረበው፣ ባለፈው ረቡዕ ጀምሮ በመካሔድ ላይ በሚገኘው የቅዱስ ሲኖዶሱ ኹለተኛ ዓመታዊ መደበኛ የምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ ላይ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕጎች ኹሉ የበላይ ነው የተባለው የሕገ ቤተ ክርስቲያን ማሻሻያ ረቂቁ÷ ርእሰ አበውና ለካህናቷና ለምእመናንዋ ኹሉ መንፈሳዊ አባት ለኾኑት ለፓትርያርኩ እንደራሴ እንደሚሾም በአንቀጽ 24 ላይ ማስፈሩ ተመልክቷል፡፡ እንደራሴው ‹‹ቅዱስ ፓትርያርኩ ከቤተ ክርስቲያን የተጣለበትን ሓላፊነትና መንፈሳዊ አመራር በሚጠበቀው ብቃትና ደረጃ ለማከናወን እንዲችል የሚያግዝ›› መኾኑ በሕግ ማሻሻያ ረቂቁ ተገልጧል፡ ፡

እንደራሴው የሚመደበው የቅዱስ ሲኖዶሱ አባላት ብቻ በሚሳተፉበት ምርጫ ሲኾን፣ ለምርጫው ሦስት ዕጩዎች በፓትርያርኩና በቅዱስ ሲኖዶሱ አባላት ጥቆማ እንደሚለዩ ተጠቅሷል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሃይማኖት፣ ቀኖናና ትውፊት የማስጠበቅ እንዲሁም ያለአድልዎ የማስተዳደር ሓላፊነት ላለበት ለፓትርያርኩ በእንደራሴነት የሚመረጠው ሊቀ ጳጳስ ማሟላት የሚገባው መመዘኛ በሕጉ መመልከቱ የተጠቆመ ሲኾን መመዘኛው ለእንደራሴው ከ50 - 60 ዓመት የዕድሜ ገደብ ሲያስቀመጥ፣ የአስተዳደር ችሎታና የመንፈሳዊ አመራር ልምድን፣ መንፈሳዊና ዘመናዊ ዕውቀት አጣምሮ መያዝን እንደሚጠይቅም ታውቋል፡፡ ‹‹ግለሰባዊ የሥልጣን ፈላጊነት ስሜት የሚገንበት፣ የፓትርያርኩን ሥልጣን የሚጋፋና መካሠስን የሚያበረታታ ነው›› በሚል አንቀጹን የተቃወሙ የቤተ ክህነት ሓላፊዎች፣ ምደባው አስፈላጊ ኾኖ ከተገኘም እንደራሴው በፓትርያርኩ ጥቆማ ብቻ መመረጥ እንዳለበት የቃሉ ትርጉም እንደሚያስገደድ በመጥቀስ ይከራከራሉ፡፡

የአህጉረ ስብከት የሥራ ሓላፊዎች በአንጻሩ፣ የእንደራሴው ምደባ፣ መልካም አስተዳደር እንዲሰፍንና ብልሹ አሠራር እንዲታረም የአደረጃጀትና የአሠራርለውጥ ጥናት በማድረግ ላይ ለምትገኘው ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አመራር መጠናከር የራሱ አስተዋፅኦ አለው በሚል እንደሚደግፉት ተናግረዋል፡፡ እንደራሴው ፓትርያርኩን ከማገዝ ውጭ ‹‹ለቅዱስ ፓትርያርኩ ከተሰጡት ተግባራት ውስጥ የሚጋራው የተለየ ሓላፊነት አይኖረውም፤›› በሚል በረቂቁ የሰፈረውን አንቀጽ በመጥቀስ ምደባው ፓትርያርኩን የመጋፋት ሚና እንደሌለውም ገልጸዋል፡፡ ተጠያቂነትን በተመለከተም ፓትርያርኩን ብቻ ሳይኾን ኹሉንም ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት ለቅዱስ ሲኖዶስ ተጠሪ ከማድረግ፣ በአስተዳደር በደልና በአመራር ጉድለት የካህናቱንና የምእመናኑን አመኔታና ተቀባይነት ማጣትን ጨምሮ ከሀብትና ንብረት ባለቤትነት ጋራ የተያያዙ ዝርዝር የተጠያቂነት አንቀጾች በረቂቁ በመካተታቸው በፓትርያርኩ አልያም በወቅታዊ እይታ ላይ ብቻ የታጠረ ረቂቅ እንዳልኾነ ያስረዳሉ፡፡

ጉዳዩ በዋናነት የቤተ ክርስቲያኒቱን መንፈሳዊ አመራር ከማጠናከር አንጻር ሊታይ ይገባል የሚሉ አስተያየት ሰጭዎች፣ ምልዓተ ጉባኤው የሕግ ማሻሻያ ረቂቁን በጥልቀት በማዳበር የቅዱስ ሲኖዶሱ ሉዓላዊ ሥልጣን በማንም የማይገሠስበት መሣርያ አድርጎ እንደሚያጸድቀው እንጠብቃለን ብለዋል፡፡ በሌላ በኩል፣ ፓትርያርኩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ታላላቅ በዓላት ላይ እንዳስፈላጊነቱ እየተገኘ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ የሚሰጠው እንዲሁም በብዙኃን መገናኛ መንፈሳዊ መልእክት የሚያስተላልፈው በአገሪቱ ብሔራዊ ቋንቋ ብቻ እንደሚኾን በሕግ ማሻሻያ ረቂቁ ላይ መስፈሩ ተጠቅሷል፡፡

     በዓለም ላይ በተደጋጋሚ ዝናን አትርፈው ተጠቃሽ ከሆኑት ተረቶች መካከል የሚከተለው ይገኝበታል። ደራሲ ገብረክርስቶስ ኃይለሥላሴ በፃፉት “የሉሲ ከዋክብትና ሌሎችም” በተሰኘው የውርስ ትርጉም የልጆች መልካም ሥነ - ምግባር መጽሐፍ፤ ያገኘነውን ለዛሬ ባጭሩ አቅርበነዋል። በድሮ ጊዜ በአራዊትና በወፎች መካከል ጦርነት ተደርጐ ነበር። የሌት ወፎች ከወፎች ጋር ተሰልፈው ተዋግተዋል። ነገር ግን በመጀመሪያው ጦርነት ወፎች ክፉኛ ተሸነፉ። የሌት ወፎች በሁኔታው ስለሰጉ በየዛፉ አንጓ ላይ ተደብቀው፣ የጦርነቱን የመጨረሻ ውጤት ተጠባበቁ። ድል አድራጊዎቹ አራዊት ወደቤታቸው ሲሄዱ፣ የሌት ወፎች ተደባልቀው አብረው ሄዱ። ትንሽ ከተጓዙ በኋላ፣ አራዊቱ ነቁባቸው (አወቁባቸው)። “ይቅርታ! እናንተ ከወፎች ወገን ተሰልፋችሁ የወጋችሁን አይደላችሁም እንዴ?” በማለት የሌት ወፎችን ጠየቋቸው። የሌት ወፎችም እንዲህ ሲሉ መለሱ።

“ኦ! በፍፁም! እኛ እኮ እንደ እናንተ ነን። ጥፍራችንንና ጥርሳችንን ብትመለከቱ ከእናንተ ጋር ተመሳሳይ ነው። ወንድማማቾች እኮ ነን። ወፎች እንዲህ እንደ እኛ አካል አላቸውን? በፍፁም! እኛ የአራዊት ወገን ነን! (አይጦች ነን!)” አራዊቱ ሁ ኔታውን ከ ሰሙ በ ኋላ ዝ ም አ ሉ። የ ሌት ወ ፎቹንም አ ብረዋቸው እ ንዲሆኑ ፈቀዱላቸው። ከአይጥ ተቆጠሩ ማለት ነው። በሌላ ጦርነት ወፎች ሲያሸንፉ፤ አይጦች ከወፎች ጋር አብረው ለመሄድ ወሰኑ። ዛሬ ደሞ ወፍ ሆኑ ማለት ነው። ሲጠየቁም፤ “እኛኮ እንደእናንተ ነን ክንፍ አለን” አሏቸው። ውሎ አድሮ ወፎችና አራዊት ሰላም ፈጠሩ። አራዊቱም የሌት ወፎቹን “ከእኛ ጋር አይደላችሁም” አሏቸው። ወፎቹም፤ “ከአራዊት ጋር ተሰልፋችሁ ወግታችሁናል። ሂዱልን እናንተ አይጦች! እነሱ ያዛልቋችሁ!” ብለው አገለሏቸው። የሌሊት ወፎች ከአራዊትም ሆነ ከወፎች ጋር መኖር ስላልተፈቀደላቸው፣ ከወፎችና ከአራዊት የተውጣጣው የጋራ ኮሚቴ “ከዚህ በኋላ፣ የሌት ወፎች ሆይ! ሌሊት በአየር ትከንፋላችሁ (ትበርራላችሁ)።

ምንም ጓደኛ አይኖራችሁም። ከእንግዲህ ከሚራመድም ሆነ ከሚከንፍ ተለይታችሁ ትኖራላችሁ” በማለት ወሰነባቸው። ስለዚህ ይኸው እስከዛሬም ድረስ የሌሊት ወፎች በጨለማ ይክነፈነፋሉ፣ በጨለማ ዋሻዎችም ውስጥ ይኖራሉ። የሌት ወፎች እንደ ወፎች ክንፍ ቢኖራቸውም በዛፎች አናትና ቅርንጫፎች ላይ አርፈው አያውቁም። ማንም ቢሆን ስለሌሊት ወፎች አፈጣጠርና ምንነት ደንታ የለውም።

                                                              * * *

በህይወታችን፤ በተለይም በፖለቲካ ህይወታችን ውስጥ ሁለት ቦታ መርገጥ፣ ሁለት አቋም መያዝ፣ በተለይም በፈጠነ ግልብጥብጦሽ ውስጥ እንደእስስት መቀያየር፤ ማንነትን የማጣትን ያህል አደጋ አለው። በኢትዮጵያውያን ዘንድ፤ አርበኛ ነን እያሉ የባንዳ ሥራ መሥራት በታሪክም በኑሮም የእርግማን ዒላማ መሆን ነው። “ጠላትማ ምን ጊዜም ጠላት ነው አስቀድሞ መግደል አሾክሿኪውን ነው” የሚለው የፉከራና የሽለላ ግጥም ያለዋዛ አልተገጠመም። ይሄ ግጥም፤ አይጥ ነው ብለው አቅርበውት የሌሊት ወፍ ሆኖ ለሚገኘውና፤ የሌሊት ወፍ ነው ብለው ሲያቀርቡት አይጥ ሆኖ ለሚገኝ ግለ-ሰብ፤ አልፎ ተርፎም ለሚያንሿክክና ለሚያሾከሹክ ሥራዬ ተብሎ የተፃፈ ሳይሆን አይቀርም። “የአድር - ባይነት ዥውዥው መቼም ማቆሚያ የለውም” ይላል ሌኒን። ዕውነት ነው። መወዛወዙ በራሱ ቢቀር ባልከፋ። ግን ወዲህ ሲመጣ ካንዱ ሲላተም፣ ወዲያ ሲሄድ ከሌላው ሲላተም ጦሱ ለሰው መትረፉ ነው ጣጣው።

ገጣሚና ፀሐፌ - ተውኔት መንግሥቱ ለማ፤ ስለ አንድ ሚስቱ ስለምትደበድበው ባል ሲያወሱ፤ “ሰውዬውን ሚስቱ በትግል ጥላው፤ እላዩ ላይ ተቀምጣ በቡጢ ስታነግለው፤ ጐረቤት ይደርሳል። “ምነው ምን ተፈጠረ?” ይላል ጐረቤት። ይሄኔ ባል፤ የሚስቱን የበላይነትና ነውሩን አለመቀበሉን ለጐረቤቶቹ ለማስረዳት፤ “እስካሁን ከላይ ነበርኩኝ አዲስ ግልብጥ ነኝ! አዲስ ግልብጥ ነኝ!!” እያለ ጮኸ። አቶ መንግሥቱ ይሄን ጨዋታ ያመጡት፣ ባገራችን አዲስ መንግሥት መጥቶ ሁሉም “አሸወይናዬ” ማለት ሲጀምር ነው። ያኔ እንግዲህ “ስለ አዲሱ መንግሥት ለምን አትፅፉም?” ተብለው ሲጠየቁ፤ “እኔ አዲስ ግልብጥ አይደለሁማ!” ባሉበት ወቅት ነው። አዲስ ግልብጥ መሆንና በየጊዜው መገለባበጥ የአንድ ሣንቲም ሁለት ገፅታዎች ናቸው። ከለየለት አድርባይነት ተለይተው አይታዩም። ከአንድ ፓርቲ ወጥቶ ለሌላ ፓርቲ መገበር አድር ባይነት ነው። ከአንድ መንግሥት ወጥቶ ለተቃራኒው መንግሥት እጅ ሰጥቶ ማገልገልም የአድርባይነትን ትርጉም ያሟላል። ከሁሉም በላይ ግን በልብ ማመንዘር ይከፋል። ከዚህ ይሰውረን። ከሀገራችን ችግሮች አንዱ፤ “ወደቀ ሲባል ተሰበረ” ማለታችን ነው። እንዲህ ካልሆነ ሞተን እንገኛለን ብለን ስናበቃ ያ ጉዳይ ከተከወነ፤ አዲስ ቦቃ ልናወጣለት ደሞ ሌላ ፀጉር ስንጠቃ እንጀምራለን።

ደግን ደግ ክፉን ክፉ ማለት መቻል ትልቅ ፀጋ ነው። እርግጥ፤ ዝም ማለትም ሌላው ፀጋ ነው። ቃል በማይከበርበት፣ ፕላን በወግ በማይተገበርበት አገር፣ “ካልታዘልኩ አላምንም” ማለታችን ትክክል መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ለውጥን ግን በውል ማስተዋል ተገቢ ይሆናል። “ውሃ ከዚህ ቀን እስከዚህ ቀን ድረስ ይጠፋል” ብሎ ቀድሞ ማሳወቅ፣ ውሃ አጠራቅሙ ማለት በትክክለኛ መረጃ አሰጣጥ ማመን ነው። በ ስልክም፣ በ መብራትም፣ በ ምርጫም፣ በ ሹም - ሽ ርም ወ ዘተ አ ስቀድሞ መረጃ እንድናገኝ ቢደረግ መተማመን ይበረክታል። ማንኛውም ወገናችን፤ የመከላከያ ባለስልጣን ይሁን የክልል፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ቀራቢ ይሁን ተራ ማሪ፤ ሙስና ከፈፀመ ሙሰኛ ነው! መረጃውን ማግኘትም መብታችን ነው፡፡ በተግባር ምን ማለት እንደሆነ በየቤቱ የሆነውን መቃኘት ነው። መረጃ መስጠት የመሻሻል ምልክት መሆኑን ግን በተቀዳሚ ማድነቅ መልካምነት ነው። ተግባሩ ካረካን መልካም። ውሸት ከሆነ ግን “አርሬ አይተኸኝ ነው እንጂ እኔም ሸክላ ነበርኩ” ያለውን ጀበና በማስታወስ ቸግሮን ነው እንጂ አንታለልም ማለት ግድ ይሆናል።

“5ኛው “ደስታ ለእናቴ 2005” የእናቶች ቀን፣ ነገ በካፒታል ሆቴል ከዘጠኝ ሰዓት ጀምሮ እንደሚከበር “ሱባ 16 ኢቬንትስ” አስታወቀ፡፡ በበዓሉ ላይ ታላቅ ሥራ የሰሩ ኢትዮጵያውያን እናቶች ሽልማት እንደሚበረከትላቸውና በተለያዩ ስፍራዎች በችግር ላይ ያሉ እናቶችን ለመደገፍ እንደታሰበ ተገልጿል፡፡

በኩል ፊልም ፕሮዳክሽን የተሰራው “አይራቅ” የተሰኘ ሮማንስ ፊልም፤ ነገ በአዲስ አበባና በአዳማ ከተሞች ይመረቃል፡፡ ፊልሙ በመጪው ሰኞ በአዲስ አበባ አቤል ሲኒማ በ11 ሰዓት እንደሚመረቅም አዘጋጆቹ ጠቁመዋል፡፡ በፊልሙ ሥራ ላይ ደራሲ በሀይሉ ዋሴ (ዋጄ)፣ ፕሮዲዩሰርና ዳይሬክተር ፍቅረየሱስ ድንበሩ የተሳተፉበት ሲሆን ማህደር አሰፋ፣ ሚካኤል ሚሊዮን፣ መስፍን ኃይለየሱስ እና ሌሎችም ተውነውበታል፡

ለሦስት ወራት በተለያዩ የላቲን ዳንሶች የሰለጠኑ የቡድን ዳንሰኞች፤ ዛሬ በክለብ H2O እንደሚመረቁ የማሰልጠኛ ማዕከሉ ኃላፊ ቢ-ላቲኖ አስታወቀ፡፡ የዳንስ ተመራቂዎቹ በጠቅላላ 156 ሲሆኑ ምረቃው ለ26ኛ ጊዜ የሚካሄድ እንደሆነ ታወቋል፡፡

34ኛው ግጥም በጃዝ የፊታችን ረቡዕ ከ11፡30 ጀምሮ በራስ ሆቴል እንደሚቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡ ገጣሚ ነቢይ መኮንን፣ አርቲስት ተፈሪ አለሙ፣ አርቲስት ግሩም ዘነበ፣ ገጣሚ በረከት በላይነህና ሌሎችም ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ የመግቢያ ዋጋ በነፍስ ወከፍ 50 ብር ነው፡፡

    በደራሲ ገብረክርስቶስ ኃይለስላሴ የተዘጋጀው “የሉሲ ከዋክብትና ሌሎችም” የተሰኘ የልጆች መልካም ሥነምግባር ማስተማርያ መፅሐፍ ታትሞ ለንባብ በቃ፡ አንጋፋው ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል፣ በመጽሐፉ ጀርባ ላይ በሰጠው አስተያየት፤ “በየምዕራፉ የተካተቱት ጣፋጭ ታሪኮች ለልጆችም ሆነ ለአዋቂዎች ሰፊ ትምህርት ይሰጣሉ፡፡ ግብረገባዊነትንና መልካም ዜግነትንም ያላብሳሉ” ብሏል፡፡ “ቀደም ሲል ከጓደኛቸው ጋር ያሰናዱት “ናብሊስ” የተሰኘ የመልካም ሥነምግባር መጽሐፍ፤ ከ5ኛ እስከ 8ኛ ክፍል ላሉ ተማሪዎች፣ የሥነምግባርና የሥነ ዜጋ ትምህርት ማጣቀሻ ሆኖላቸዋል” ብለዋል - ደራሲው በአዲሱ መጽሐፋቸው መግቢያ ላይ፡፡ መጽሐፉ በ30 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲ ገብረክርስቶስ፤ ከዚህ ቀደም “ቅንጅት ከየት ወደየት”፣ “እምዬ” የተሰኘ የረዥም ልብወለድ፣ “በፈተናና በጥረት የታጀበ ስኬት” የሚል የህይወት ታሪክ እና “መቀናጆ” የሚል ርዕስ ያለው የግጥም መድበል ለአንባቢያን አቅርበዋል፡፡

Saturday, 10 May 2014 13:11

አዳዲስ መፃህፍት

የመፅሃፉ ርዕስ - የግንኙነት ጥበብ ሥነ-ልቦናዊ ገፅታ
ደራሲ - አለማየሁ ፀሃዬ
የምረቃ ሥፍራ - የኢትዮጵያ ቤተ-መዛግብትና ቤተ-መፃህፍት ኤጀንሲ
ሰዓት - ጠዋት 3፡30  
*            *            *
የመፅሃፉ ርዕስ - አቤቶ ኢያሱ፤ አነሳስና አወዳደቅ
ደራሲ - አጥናፍሰገድ ይልማ
የምረቃ ሥፍራ - ጣይቱ ሆቴል
ሰዓት - ከጠዋቱ 3 ሰዓት
*            *            *
የመፅሃፉ ርዕስ - ሁለት ሶስት መልክ
ደራሲ - ሮዝ መስቲካ
ጭብጥ - እርግዝናና ልጅ ማሳደግ
የምረቃ ሥፍራ - ብርሃን ባህላዊ መዝናኛ ማእከል
ሰዓት - ከጠዋቱ 4 ሰዓት
*            *            *
የመፅሃፉ ርዕስ - የሙስና ወንጀልና የክርክር ሥነ-ሥርአት
ደራሲ - አበበ አሳመረ
ጭብጥ - ሙስናና የክርክር ስነ-ስርአቶች
ዋጋ - 59 ብር ከ 90