Administrator

Administrator

አዲሱ የበጀት ዝርዝር ስለ ሠራተኞች ደሞዝ የሚለው ነገር አለ
ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ይኖራል። የግድ ነው። ለምን? ሶስት ምክንያቶች አሉ።
ለመጪው ዓመት የተመደበው የደሞዝ በጀት(ከነመጠባበቂያው)፣ ከዘንድሮው በ66% ይበልጣል
በጀቱና መጠባበቂያው ከ11.5 ቢ ብር ወደ 19.1 ቢ ብር እንዲጨምር ተደርጓል (የ7.6 ቢ ብር ጭማሪ)
ጊዜው የምርጫ ጊዜ ነው። የመንግሥት ሠራተኞችን በከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ማንበሻበሽ ያዋጣል
ግን ማን ያውቃል! የደሞዝ ጭማሪ ላይኖር ይችላል። ለምን? ሶስት ምክንያቶች አሉ
ባልተለመደ ሁኔታ አብዛኛው የበጀት ጭማሪ “መጠባበቂያ” ተብሎ ነው የተያዘው  (6.5 ቢ. ብር)
ጊዜው የምርጫ ነው። ምርጫ ሲቃረብ ደሞዝ እንደማይጨመር አቶ መለስ ዜናዊ ተናግረው ነበር።
የመንግስት ሠራተኞች ወፍራም ጭማሪ ቢያገኙ የዋጋ ንረትና የኑሮ ውድነት ሊፈጠር ይችላል

የመንግስት ሠራተኞችን ደሞዝ በተመለከተ ለ2007 ዓ.ም የተዘጋጀው በጀት፣ ከወትሮው በተለየና ባልተለመደ ሁኔታ፤ የተምታታ ወይም የሚያምታታ ሆኗል። “ደሞዝ ይጨመራል ወይስ አይጨመርም?” ለሚለው ጥያቄ፣ ከበጀት ምደባው ቁርጥ ያለ ምላሽ ማግኘት የለብንም እንዴ? በጀት ማለትኮ እቅድ ነው። በተወሰነ ጊዜ ውስጥ፣ “ይህን ይህን ያህል ገንዘብ ከዚህና ከዚህ አገኛለሁ”፤ “ያንን ያንን ያህል ገንዘብ ለዚያና ለዚያ እከፍላለሁ” ብሎ እቅጩን መናገር አለበት፡፡ የዘንድሮው በጀት ግን፣ በተለይ የሠራተኞችን ደሞዝ በተመለከተ፣ ቁርጡን ለመናገር የፈለገ አይመስልም።
በእርግጥ በ2007 ዓ.ም ለደሞዝ ክፍያ ይውላል ተብሎ የተመደበው አጠቃላይ በጀት፣ በጣም ብዙ ነው። ከዘንድሮው ጋር ሲነፃፀር በ7.6 ቢሊዮን ብር ይበልጣል። ዘንድሮ ለደሞዝ ክፍያ ከነመጠባበቂያው ተይዞ በነበረው 11.5 ቢሊዮን ብር በጀት ላይ፣ ድንገት በአንድ ጊዜ 7.6 ቢሊዮን ብር እንዲጨመርለት የተወሰነው በምን ምክንያት ይሆን? የሠራተኞች ደሞዝ “በወፍራሙ” ካልተጨመረ በቀር ይሄን ሁሉ ገንዘብ መመደብ አስፈላጊ አይደለም። ሌላ ምክንያት ሊኖረው አይችልም። እንዴት በሉ፡፡
የደሞዝ በጀት ላይ ከፍተኛ ጭማሪ የታየበት አመት ቢኖር በ2003 ዓ.ም ነው። ያኔ ታዲያ፤ የደሞዝ በጀት በ40 በመቶ እንዲያድግ የተደረገው፤ በሌላ ምክንያት ሳይሆን ለመንግስት ሠራተኞች የደሞዝ ጭማሪ ስለተሰጠ ነው። የመጪው አመት የደሞዝ በጀት ጭማሪ ግን ከዚህም ይልቃል - ከዘንድሮው በጀት ጋር ሲነፃፀር በ66% ይበልጣል። ይህም ለመንግስት ሠራተኞች ቀላል የማይባል ደሞዝ ለመጨመር መታሰቡን ያረጋግጣል። በዚያ ላይ አስቡት።
የ2007 ምርጫ እየተቃረበ ነው። ገዢው ፓርቲ፣ የደሞዝ ጭማሪውን ለምርጫ ዘመቻ ሊጠቀምበት ከፈለገ፤ ትክክለኛው ጊዜ አሁን ነው።
ደግሞስ ብዙዎቹ የመንግስት ሠራተኞች የገዢው ፓርቲ አባላት አይደሉ? “ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ” በሚለው ፈሊጥ ዳጎስ ያለ የደሞዝ ጭማሪ ቢያሸክማቸው ማንም አይከለክለውም። በእርግጥም ሳያሳንስ የሚቆርሰው ከየራሱ ምጣድና መሶብ እስከሆነ ድረስ፣ “ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ” የሚለው አባባል ቅንጣት ስህተት አይወጣለትም። ችግሩ ምን መሰላችሁ? ለመንግስት ሠራተኞች ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ለመስጠት፣ ገንዘብ ያስፈልጋል። ገንዘቡ ደግሞ ከሰማይ አይዘንብም። ከሌሎች ዜጎች ኪስ መውሰድ የግድ ሊሆን ነው። ከሌሎች ዜጎች ማዕድ ላይ ቆርሶ መውሰድ... ይሄ ነው ችግሩ።
ሌላኛው አማራጭ የብር ኖት በገፍ ማተም ነው። ምን ዋጋ አለው? ይሄኛው አማራጭም፤ የዋጋ ንረትን በማስከተል የዜጐችን ኪስ ያኮሰምናል፡፡
የሆነ ሆኖ፤ ለደሞዝ የሚመደበው በጀት ታይቶ በማይታወቅ ከፍተኛ መጠን እንዲጨምር ተደርጓል። ከምርጫው ጋር ግንኙነት ይኑረውም አይኑረው፤ የገንዘቡ ምንጭ ምንም ይሁን ምን፤ በጀቱ ሙሉ ለሙሉ ሥራ ላይ ሊውል የሚችለው፣ ለመንግስት ሠራተኞች ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ከተደረገ ብቻ ነው። አለበለዚያ የወረቀት በጀት ሆኖ ይቀራል። ስለዚህ የመንግስት ሠራተኞች ያለ ጥርጥር ደሞዝ ይጨመርላቸዋል ብለን በእርግጠኛነት መናገር እንችላለን፡፡
ግን፤ በጀቱ የወረቀት በጀት ሆኖ ቢቀርስ?
እውነት ነው፤ መንግስት ለሠራተኞቹ ከፍተኛ የደሞዝ ጭማሪ ለመስጠት ቢወስንም፤ ሙሉ ለሙሉ የቆረጠለት አይመስልም። ለምን በሉ። የበጀት ድልድሉ፣ ከሌላው ጊዜ ይለያል። እንደወትሮው ቢሆን፣ አብዛኛው የደሞዝ በጀት፣ ለእያንዳንዱ መሥሪያ ቤት ምን ያህል እንደሚደርሰው በዝርዝር ተሸንሽኖ ይቀርባል። የተወሰነ ገንዘብ ደግሞ መጠባበቂያ ተብሎ ይቀመጣል። ለእያንዳንዱ መሥሪያ ቤት ከተመደበው የደሞዝ በጀት ባሻገር አንዳች ያልተጠበቀና ያልታሰበ ወጪ ቢያጋጥም ችግር አይፈጠርም። የደሞዝ መጠባበቂያ የሚያስፈልገው ለዚህ ለዚህ ነው። ካቻምናና ከዚያ በፊት በየአመቱ 150 ሚ. ብር  የደሞዝ መጠባበቂያ ይመደብ ነበር። አምና ደግሞ 200 ሚ. ብር። ለዘንድሮ የተቀመጠው የደሞዝ መጠባበቂያ 350 ሚ. ብር ነው።
ለመጪው አመት የተመደበው የደሞዝ መጠባበቂያ ግን፣ ከእስከዛሬው በእጅጉ በእጅጉ ይለያል። 6.5 ቢሊዮን ብር ነው የደሞዝ መጠባበቂያ ተብሎ የተመደበው። ለምን? የገንዘብ ሚኒስትሩም ሆኑ የበጀት ሰነዱ፣ በዚህ ጉዳይ ላይ ትንፍሽ ያሉት ነገር የለም። ለነገሩ፤ ጥያቄ ለመሰንዘር ትንፍሽ ያለ ፓርቲ፣ ፖለቲከኛ ወይም ምሁርም የለም። “ለ12.6 ቢሊዮን ብር መደበኛ ደሞዝ 6.5 ቢሊዮን ብር መጠባበቂያ! ኧረ እንዲህ አይነት መጠባበቂያ በታሪክ ታይቶ አይታወቅም! ምንድነው ነገሩ?” የሚል ጥያቄ እስካሁን አልቀረበም።
እንዲህ ጉዳዩ እንደተድበሰበሰ በጀቱ ቢፀድቅ፤ ምን ሊፈጠር እንደሚችል አስቡት። ምንም አይፈጠርም፡፡ መንግስት ለሠራተኞቹ ደሞዝ የመጨመርና ያለመጨመር አማራጮች ይኖሩታል። ከፈለገ ደሞዝ ይጨምራል። የበጀት እጥረት አይገጥመውም። የደሞዝ መጠባበቂያ ተብሎ የተመደበ ብዙ ገንዘብ አለለት። ካልፈለገ ደግሞ ደሞዝ አለመጨመር ይችላል። መጠባበቂያውን ትቶ፤ ለየመሥሪያ ቤቱ ተከፋፍሎ የተመደበውን የደሞዝ በጀት ብቻ ይጠቀማል። በሌላ አነጋገር፣ “መንግስት ደሞዝ ለመጨመርና ላለመጨመር እያመነታ ይሆን ነገሩን በእንጥልጥል ለማቆየት ፈልጐ ይሆን?” ብለን እንድናስብ ይገፋፋናል - ያልተለመደው የበጀት አመዳደብ፡፡
ነገር ግን በደፈናው “የደሞዝ መጠባበቂያ” ተብሎ 6.5 ቢ.ብር የተመደበው በሌላ ምክንያት ሊሆን ይችላል። የበጀት ዝግጅት ሲጀመር፣ ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ መነሳቱ አይቀርም። ከተወሰነ ክርክር በኋላ፣ ሃሳቡ ውድቅ ይሆንና፣ ዝርዝር በጀት ይዘጋጃል። የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ያዘጋጀው ሰነድ እንደሚገልፀው፤ የየመሥሪያ ቤቱ ዝርዝር የበጀት ድልድል የተዘጋጀው የደሞዝ ጭማሪ አይኖርም በሚል መመሪያ ነው፡፡ የበጀት ዝግጅቱ ከተጋመሰ በኋላ ወይም ሊጠናቀቅ ከተቃረበ በኋላ፤ መንግስት ሃሳቡን ቢቀይርስ? ማለትም፤ ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ እንደገና ይነሳል። ለምን?
የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ ስለሚዋዥቅ፤ ከዚሁ ጋር አብሮ የመንግስት ሃሳብም ቢዋዥቅ አይገርምም። ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ ከወራት በፊት ውድቅ ቢደረግ፣ ከጊዜ በኋላ ፖለቲካው ሲንገራገጭ እንደገና ደሞዝ የመጨመር ሃሳብ ይነሳል፤ ባለቀ ሰዓትም ተቀባይነት ያገኛል። ነገር ግን፣ በዝርዝር የተዘጋጀውን በጀት እንደገና ለመከለስ ቀላሉ ዘዴ ምንድነው? ለደሞዝ ጭማሪ የሚያስፈልገውን በጀት፣ በደፈናው “መጠባበቂያ” ተብሎ እንዲገባ ማድረግ ነው ቀላሉ ዘዴ።
ግን ከምር የሠራተኞች ደሞዝ ይጨመራል? አንዱ ችግር፤ 2007 ዓ.ም የምርጫ አመት መሆኑ ነው፡፡ ታስታውሱ እንደሆነ በ2002 ዓ.ም ለሠራተኞች ደሞዝ እንዲጨመርላቸው ጥያቄ ቀርቦ ነበር፡፡
የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ጥያቄውን አልተቀበሉትም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥያቄውን ውድቅ ያደረጉት “ለመንግስት ሠራተኞች ደሞዝ ሊጨመርላቸው አይገባም” በሚል አይደለም፡፡ ምርጫ በሚቃረብበት ወቅት ለመንግስት ሠራተኞች ደሞዝ መጨመር የአገሪቱን ፖለቲካ እንደሚያበላሽ የተናገሩት አቶ መለስ፤ ኢህአዴግ በምርጫ አመት የደሞዝ ጭማሪ እንደማያደርግ ተናግረው ነበር - በ2002 ዓ.ም፡፡ በ2007ስ?

     በሥልጣኔ በተራመዱት አገራት፣ ትልቁ የፖለቲካ መከራከሪያ ምን መሰላችሁ? “የመንግስት በጀት” ነው። ታስታውሱ እንደሆነ፤ ከአመት በፊት በርካታ የአሜሪካ የመንግስት መሥሪያ ቤቶች በበጀት ክርክር ሳቢያ ለሳምንታት ያህል ተዘግተው ቆይተዋል፡፡
የተፎካካሪ ፓርቲዎች የበጀት ክርክር መቼም ቢሆን አያባራም፡፡ የእንግሊዝ ፓርላማ አብዛኛውን ጊዜ የሚሟሟቀው በበጀት ሙግት ነው፡፡ የጣሊያን፣ የፈረንሳይ፣ የግሪክ፣ የስፔን መንግስታት ሲንገዳገዱና ከስልጣን ሲወርዱ የምናየው፤ የአውሮፓ መንግስታት በኢኮኖሚ ቀውስ ሲወዛገቡና ጐዳናዎች በተቃውሞ ሰልፍ ሲጥለቀለቁ የምንመለከተው በሌላ ምክንያት አይደለም፤ በበጀት ጉዳይ እንጂ፡፡ በእርግጥም የፓርቲዎችና የፖለቲከኞች የአስተሳሰብ ልዩነት፣ በተጨባጭና በግላጭ አፍጥጦና አግጥጦ የሚወጣው፣ የበጀት መጠንና አመዳደብ ላይ ነው።
ወደ ነፃ ገበያ ሥርዓት የሚያዘነብሉ ፓርቲዎች፣ ለምሳሌ በአሜሪካ ሪፐብሊካን ፓርቲ፤ የእንግሊዝ ኮንሰርቫቲቭ ፓርቲ በተቻለ መጠን የመንግስት በጀት በየጊዜው እያበጠ እንዳይሄድ ይከራከራሉ። በአብዛኛው፣ ለፍርድ ቤቶች፣ ለህግ አስከባሪና ለመከላከያ ሃይል የሚመደበው በጀት ግን እንዲቀንስ አይፈልጉም፡፡ በተቃራኒው ለነፃ ገበያ ሥርዓት ያን ያህልም ፍቅር የሌላቸውና  ገናና መንግስት እንዲኖር የሚፈልጉ ፓርቲዎች ደግሞ፤ መንግስት ሁሉም ነገር ውስጥ እንዲገባ እየገፋፉ፣ ለዚህኛውም ለዚያኛውም በጀት እንዲጨመር ይወተውታሉ። በአጭሩ፤ የፓርቲዎች የፖለቲካ አቋም በተግባር የሚገለጠው የበጀት አመዳደብ ላይ ስለሆነ አጥብቀው ይከራከራሉ።
እንደ “አለመታደል” ሆኖ፣ በኛ አገር በበጀት ጉዳይ የሚከራከርና የሚሟገት ፓርቲም ሆነ ፖለቲከኛ ብዙ አይታይም። መንግስት ለ2007 ዓ.ም ያዘጋጀው የበጀት ዝርዝር ለፓርላማ ከቀረበ ሁለት ሳምንት አለፈው። ገንዘቡም ቀላል አይደለም። ከ178 ቢሊዮን ብር በላይ ነው። ከዜጎች ጠቅላላ አመታዊ ገቢ (ምርት) ውስጥ ሩብ ያህሉ ማለት ነው። ግን፣ ስለ በጀቱ መጠንና አመዳደብ እስካሁን ለምልክት ያህል እንኳ ውይይትና ክርክር አልሰማንም።
አንደኛ፤ የበጀቱ መጠን፤ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ፣ የዜጎችን ኪስና ኑሮን ይነካል። መንግስት፤ በየአመቱ የብዙ ቢሊዮን ብር በጀት የሚመድበው ታክስ በመሰብሰብና የብር ኖት በማሳተም ነው፡፡ ታክስ የሚሰበሰበው ከዜጎች ኪስ ነው። በ2000 ዓ.ም እና በ2003 ዓ.ም እንደተደረገው መንግስት የብር ኖት በገፍ አትማለሁ የሚል ከሆነም፤ በዋጋ ንረትና በኑሮ ውድነት የዜጐች ህይወት ይጐሳቆላል፡፡ ሁለተኛ፤ የበጀቱ መጠን ብቻ ሳይሆን የበጀቱ አመዳደብም የዜጐችን ኑሮ ይነካል። ለምሳሌ… ላለፉት 7 አመታት... “በዚህ ዓመት ግንባታቸው ይጠናቀቃል” እየተባለ፣ በየአመቱ ከቢሊዮን ብር በላይ ሲመደብላቸው የነበሩ የተንዳሆ፣ የከሰም፣ ከዚያም የርብ ግድቦች... በመጪው አመትም ከቢሊዮን ብር በላይ ይመደብላቸዋል። ገንዘቡ የት እየገባ ይሆን ግንባታዎቹ ለአመታት የተጓተቱት?
ሃብት በማባከን ዋና ተጠቃሽ ሆነው ለተገኙት ዩኒቨርስቲዎች የሚመደበው በጀትስ? በትምህርት ሚኒስቴር ስር ለሚተዳደሩት ዩኒቨርስቲዎችና ተቋማት፣ ዘንድሮ 25 ቢሊዮን ብር እንደሚመደብላቸው ስንሰማ፣ ይሄ ሁሉ ብር የት ይገባ ይሆን ብለን በደንብ ማሰብ አያስፈልገንም? ይህንን እንደ ዋነኛ ሥራ የሚቆጥሩ ፖለቲከኞች የሚፈጠሩት መቼ ይሆን? ምሁራንስ?

“የሚስቅልህ ሰው ስለበዛ፣ ትክክል ነኝ ብለህ አታስብ”
(የእንግሊዞች አባባል)

ከዕለታት አንድ ቀን አንደ ቀንድ - አውጣ (Snail) ወደ አንድ ቡና ቤት ከመሸ በኋላ ይሄዳል፡፡ ከዚያም በሩን ያንኳኳል፡፡
ባለቡና ቤቱ፤ በሩን ዘጋግቶ እየጨራረሰ ነው፡፡
“ማነው?” ይላል የቡና ቤት ባለቤት፡፡
“እኔ ነኝ!” ይላል ቀንድ አውጣ፡፡
“ትንሽ መጠጣት ፈልጌ ነበር”
“መሸኮ! ከዚህ ወዲያ አላስተናግድም!”
“እረ በእግዚሃር አስተናግደኝ! ምንም ሄጄ እምዝናናበት ቦታ የለኝም፡፡ የት እንደምሄድም አላውቅም! እባክህ ተባበረኝ!”
“አያ ቀንዳውጣ! እየዘጋሁ ነው ስልህ ምንድን ነው ችግርህ? ትመለሳለህ ተመለስ አለበለዚያ ዋጋህን ታገኛለህ! ተግባባን?”
“ባለቡና ቤት፤ እኔ አንድ ነገር ሳልቀምስ ወደ መኝታዬ መሄድ አልችልም! ይገባሃል?”
“ቆይ እንግዲህ እንዲገባህ ምን ማድረግ እንደምችል አሳይሃለሁ!” እያለ የዘጋውን በር ይከፍትና ይወጣል፡፡
ቀንድ - አውጣው በሁኔታው ተደስቶና የበለጠውን ዕውነት አስረዳዋለሁ ብሎ ፍንድቅድቅ ብሏል፡፡
ሰውዬው ግን ንግግሩን ሁሉ አቋርጦ በንዴት ተወጥሮ ወደውጪ መጣና፤
“አንተ ማነኝ ብለህ ነው ይሄ ሁሉ ጉራ? ይሄ ሁሉ ያዙኝ ልቀቁኝ ማለት?” ሲል ጠየቀው፡፡
ቀንዳውጣውም፤
“ጌታዬ፤ ውሃ ጠምቶኝ ነው ያስቸገርኩህ፡፡ እባክህ…” ብሎ ሳይጨርስ፣ ባለሆቴሉ ባለ በሌለ ኀይሉ በቲራ ጠረገው፡፡ ቀንድ አውጣው ሩቅ ከመሽቀንጠሩ የተነሳ፤ የት ሄዶ እንደወደቀ እንኳን ያየው የለም!!
ከአንድ ዓመት በኋላ ቀንድ አውጣው ወደዚያው ሆቴል መጣ፡፡ ዛሬም ሰዓቱ በጣም ረፍዷል፡፡ ያ ባለ ሆቴል በሩ ሲንኳኳ፤
“ማነው?” አለ፡፡
“እኔ ነኝ!”
“ማ?”
“እኔ ቀንድ አውጣ!”
“አንተ ዛሬም ልትለክፈኝ መጣህ?”
“አይ፤ ዛሬስ አንድ ጥያቄ ብቻ ኖሮኝ ነው የመጣሁት”
ባለሆቴሉ ወጣና፤
“ምንድን ነው የፈለከው?”
ቀንዳውጣውም፤
“አንዲት ጥያቄ ብቻ ናት ያለችኝ፡፡”
“እሺ ተናገር?”
“ባለፈው ዓመት አሽቀንጥረህ ከጣልከኝ ቦታ እዚህ ለመድረስ ተጉዤ ተጉዤ፤ ይሄው ዛሬ ደረስኩኝ፡፡ ለመሆኑ ለምን ነበር እንደዛ በቲራ የመታኸኝ?!”
*    *    *
በየትኛውም ሰዓት ያረፈደ ሰው፤ ቅጣቱ እንደተጠበቀ መሆኑን አንርሳ፡፡ ማንም በመሸ ሰዓት ረግጦ ሊያሽቀነጥረን እንደሚችልም እንገንዘብ፡፡
ማዝገማችን፣ መንቀርፈፋችንና መዘግየታችን በራሱ መልክና ጊዜ ወደኛው ፊቱን አዙሮ እንደቀንድ አውጣው ሊያስመታን መቻሉ አይቀሬ ነው፡፡ ለምን ሆነ? ብለን በዓመቱ መጠየቅ ቢያንስ መሳቂያ ከመሆን አያሳልፈንም፡፡ ሌሎች ውቴላቸውን ዘግተው ሳይቆልፉ በፊት ነቅቶ መምጣት ብልህነት ነው፡፡
የሀገራችን ስሞች አስገራሚ ናቸው፡፡ በወትሮ ማዕረጉ የሹም/የንብረት ባለቤት የምንለው፤ ስሙ የኃደራ ስም ይባላል፡፡ ባላገር፣ ወታደር፣ ባላባት፣ ስደተኛ፤ ባለቤት እንዲሉ፡፡ የሀገር ባለኃደራነት መሆኑ ነው፡፡
የማኅደር ስም የሚባል አለ ደግሞ፡፡ አደራችንን አንዘንጋ የሚል የማደሪያ ስም ነው፤ ቃሉ፡፡ በየጊዜው ቃል ስንገባም “ዕውን እፈጽመዋለሁ? እንበል፡፡ የመሬት፣ የቦታ ርስት ወዘተ ንብረት ባለቤትነት ዶሴ እንደማለት ነው፡፡ የሚገርመው የማህደርም፤ የባለኃደራም ሌብነት ነበር፡፡ የዱሮ ዘመን ባለቤትነት ከዛሬ ሊለይ ይችላል፡፡ እንደ እውነቱ ግን ሁሉም ከላይ እየታዘዘ ከመፈፀሙ አኳያ፤ የቋንቋ ነገር ካልሆነ በቀር  ሁሉም ስሙ “ሙስና” ነው፡፡
የተቀብዖ ስም እንዲል መጽሐፍ ሹመት ብቻውን ፍሬ አያፈራም! የተቀባንበት፣ የተሾምንበት፣ ኃላፊነት የተቀበልንበት ስም ያው የተቀብዖ ስም ነው፡፡ ታዲያ “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋልን”፣ “ከሰው መርጦ ለሹመት፣ ከእንጨት መርጦ ለሹመት”ን እንደበቀቀን እያቀነቀንን፤ እስከመቼ እንጓዛለን? ምንም ዓይነት ኮርስ ልውሰድ፣ ዋናው ቁም ነገር፣ “ሹመቱ ለአገር እንዳገለግል፣ ኃላፊነቴን እንድወጣ ነው” እንላለን? ወይስ በሹምነቱ ዘመን ያልበላ፣ እየበላ ያለና ወደፊትም የማይበላ ማን ሹም አለ? ከበይው የሚይቋደስ፣ ባለ አላባ፣ ባለ ኮሚሽንስ ማን አለ?
ሐዲድ ተሠራ ስንል ሲመነቀል፣ አገር ያደነቀው ምሁር አፈራን ስንል፤ “አያሌው ሞኙ ሰው አማኙ” ሲለን፣ ውጪ አገር ወኪል አድርገን ስንልክ “አፍንጫችሁን ላሱ” ሲለን፤ ምን ዓይነት ተዓማኒነት ልናስተናገድ ነው?
“እያንዳንዱ አሣ አጥንት እንዳለሁ ሁሉ፤ እያንዳንዱ ሰው ስህተት አለው” ይላሉ አዋቂዎች፡፡ ሆኖም ይህን ብሂል መሠረት አድርገን ስንሳሳት፣ አውቀን ስንሳሳትና ለሁሉም ዋናው ሰበብ ማግኘት ነው ስንባል መክረማችን፤ አሳሳቢ ነው፡፡
“አንድ ‹ባሪያ› በምድር ላይ እየተጓዘ እስካለ ድረስ ያንተ ነፃ መሆን (ተዓምር) ፍፁም አልሆነም!” ይላሉ የፍልስፍና ሊቃውንት፡፡
ዕውነት ነው፡፡ የአስተሳሰብ ባርነት፣ የአመለካከት ባርነት፣ የጠባብነት ባርነት፣ የመላላት ባርነት፣ እኔን ከተከተልክ - ነፃ ነህ የመባል ባርነት፤ ዲሞክራሲን እንደፈለጉ በሚተረጉሙና በሚተገብሩ የፖለቲካ ባላባቶች መጠርነፍ ባርነት…ወዘተ ውስጥ መኮድኮድ እርግማን ነው፡፡ ስለሆነም እንዴት? ለምን? ብሎ መጠየቅ ታላቅ እርምጃ ነው!
“የመጨረሻው ከባድ የብረት በርም የሚከፈተው በትንሽ ቁልፍ ነው” (ቻርለስ ዲከንስ)
ቻርለስ ዲከንስ ትንሽ ነን ብለን ተስፋ አንቁረጥ፡፡ ችሎታና ዕውቀቱን ከያዝን የመጨረሻውን ከተምበሪ ልንከፍተው እንችላለን ሲል ነው፡፡ አንዱ የእኛ ፖለቲከኞች ችግር እራስን አሳንሶ ማየት የሚሆነው ለዚህ ነው!!
የሚከተለው አገርኛ ግጥም በልኩ ያስገነዝበናል፡፡
“ዓመት ነው?”
ዕድሜ ነው?
ስሜት ነው?
ተስፋ ነው መጪው ቀን?
ወይስ ኩራት እራት፣ ከውስጡ የቀረ፣ ትርጉም ይኖር ይሆን?”
ተስፈኝነት፣ አዎንታዊነት፣ ትዕግሥትና ጽናት ከሌሉ ለአገራችን ትግል አስተዋጽኦ አይዋጣልንም፡፡
ማርቲን ሉተር ኪንግ፤
“ዓለም ነገ ልታልቅ ነው ቢሉኝም፣ ዛሬ ዛፍ መትከሌን አልተውም” ያለን ለዚህ ነው፡፡
በአንፃሩ ትላንትም፣ አሁንም፣ ያለውን ሁኔታ እደግፋለሁ፤ አንደኛ የልማት አርበኛ ነኝ፤ አንደኛ “ኮብል ስቶኒስት ነኝ!”፤ አንደኛ አገራዊ ምሁርና የሚዲያ ተቆርቋሪ፤ የፖለቲከኛ ተንታኝ ነኝ የሚል ቢበዛ፤ ቆም ብሎ “ዕውን ነውን?” ማለት ያባት ነው! “የሚስቅልህ ሰው ስለበዛ፣ ትክክል ነኝ ብለህ አታስብ!” የሚለው የእንግሊዞች አባባል፤ ፍሬ - ጉዳይ አለው የሚባለው ለዚህ ነው፡፡


‘ሰላ በይልኝ’ በሚለው ነጠላ ዜማው ከህዝብ ጋር ተዋወቀው ድምጻዊ ጃኪ ጎሲ፣ የሙዚቃ ኮንሰርት ለማቅረብ ከታዋቂው የቢራ አምራች ኩባንያ ሄኒከን ጋር የአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ብር ስምምነት ሊፈራረም ነው፡፡
አድማስ ሬዲዮ ከአትላንታ እንደዘገበው፣ ወጣቱ ድምጻዊ ጃኪ ጎሲ ከሰሞኑ ከሄኒከን ጋር ያደርገዋል ተብሎ የሚጠበቀው ይህ ስምምነት በአዲስ አበባ ከተማ ለሚከናወን የሙዚቃ ኮንሰርት ነው፡፡ የሙዚቃ ኮንሰርቱ የሚቀርብበትን ትክክለኛ ጊዜ መናገር ባይቻልም ለመጪው የኢትዮጵያውያን አዲስ አመት ዋዜማ ሊሆን እንደሚችል ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡
በተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶችና የዓለም አገራት እየተዘዋወረ የሙዚቃ ኮንሰርቶችን በስፋት እያቀረበ የሚገኘው ድምጻዊው፣ ከወራት በፊት ከዝግጅት ክፍላችን ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ በአገር ውስጥም የሙዚቃ ኮንሰርቶችን ማዘጋጀት ዕቅድ እንዳለው መናገሩ ይታወሳል፡፡

Saturday, 14 June 2014 12:47

የፖለቲካ ጥግ

በህዝቦች ላይ ፅኑ እምነት አለኝ፡፡ እውነቱ ከተነገራቸው ማንኛውንም ብሄራዊ ቀውስ እንደሚጋፈጡት መተማመን ይቻላል፡፡ ዋናው ነገር ተጨባጩን ሃቅና ቢራውን ወደ እነሱ ማቅረብ ነው፡፡
አብርሃም ሊንከን
አንተ አንድ ካፒታሊስት አሳየኝና እኔ ደሞ መጣጩን አሳይሃለሁ፡፡
                            ማልኮልም ኤክስ
አብዮቱ ከጥበብ ጋር አስተዋወቀኝ፤ ጥበብ በተራው ከአብዮቱ ጋር አስተዋወቀኝ፡፡
አልበርት አንስታይን
ሰዎች በአንድነት በዝምታ አሲረው በተቀመጡበት ክፍል ውስጥ አንዲት እውነተኛ ቃል የሽጉጥ ተኩስ ትመስላለች፡፡
Czestaw Mitosz
ድምፅ መስጠት ልክ እንደጠብመንጃ ነው፡፡ ጠቃሚነቱ በተጠቃሚው ሰው ባህርይ ይወሰናል፡፡
ቴዎዶር ሩስቬልት
የሰው ልጅ የመጀመሪያ ሥራው ለራሱ ማሰብ ነው፡፡
ጆሴ ማርቲ
ታላቁ ዲሞክራሲያችን፤ አሁንም ድረስ ጅል ከብልህ የበለጠ ሃቀኛ ነው ብሎ የማሰብ አዝማሚያ ይታይበታል፡፡
በርትራንድ ራሰል
ምርጫ የህዝብ ነው፡፡ ውሳኔውም የእነሱ ነው፡፡ ጀርባቸውን ለእሳቱ ለመስጠትና መቀመጫቸውን ለማቃጠል ከወሰኑ፣ ቁስላቸው ላይ ለመቀመጥ ይገደዳሉ፡፡
አብርሃም ሊንከን
ዲሞክራሲ የነፃነት መገለጫ አይደለም፡፡ ዲሞክራሲ ሁለት ተኩላዎችና አንድ በግ ምሳቸውን ምን እንደሚበሉ ድምፅ መስጠት ነው፡፡ ነፃነት የሚመነጨው ተመልሰው ሊወሰዱ የማይችሉ የተወሰኑ መብቶችን ከማክበር ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ በ99 በመቶ ድምፅ እንኳን ዲሞክራሲ እውን አይሆንም፡፡
ማርቪን ሲምኪን

      ብራዚላዊው  ኔይማር ዳሲልቫ ሳንቶስ  ሮናልዶ እና ሜሲ ለዓለም ዋንጫው ድምቀት የሚሆኑ ምርጥ ተጨዋቾች ናቸው ሲል ተናገረ፡፡ በባርሴሎና ክለብ እስከ 2018 ለመጫወት የኮንትራት ውል የፈፀመው ኔይማር ዳሲልቫ ሳንቶስ በሁለት ጎሎች ዓለም ዋንጫውን መጀመሩ ለብራዚል 6ኛ የዓለም ዋንጫ ስኬት ከፍተኛ ተስፋ ያሳደረ ሆኗል፡፡ ሶስቱ ተጨዋቾች ብሄራዊ ቡድኖቻቸውን ለዓለም ዋንጫ ድል ለማብቃት ብቻ ሳይሆን በኮከብነት ለሚሰጡ ልዩ ሽልማቶች በዋና እጩነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
የ29 ዓመቱ ክርስትያኖ ሮናልዶ አገሩን በአምበልነት እየመራ በዓለም ዋንጫ ደማቅ ታሪክ የመስራት እድሉ ብራዚል ላይ የመጨረሻ ነው፡፡ ለ26 ዓመቱ ሊዮኔል ሜሲም ከዘንድሮ ዓለም ዋንጫ የተሻለ አጋጣሚ የለም፡፡
ለ22 ዓመቱ ኔይማር ዳሴልሻ ግን ይህን የስኬት ጣሪያ ለማስመዝገብ ሁለት ዓለም ዋንጫዎች ይቀሩታል፡፡
ሮናልዶና ሜሲ በክለብ ደረጃ የሚወዳደሩባቸውን ሊጎች በጎሎች  እያንበሸበሹ፤ ዋንጫዎችን እየሰበሰቡ፤ የቆዩ ሪከርዶችን እየሰባበሩና አዳዲስ እያስመዘገቡ፤ የኮከብ ተጨዋችነት ሽልማቶችን እየተፈራረቁ ሲጎናፀፉ ቆይተዋል። ብቸኛው የቀራቸው የስኬት ጣሪያ ዓለም ዋንጫ ብቻ ነው። ሁለቱም ተጨዋቾች በክለብ ደረጃ የተሳካላቸውን ያህል  በየብሄራዊ ቡድኖቻቸው የላቀ ውጤት አለማስመዝገባቸው ሁሌም  ለትችት ይዳርጋቸዋል፡፡
በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ላይ ሮናልዶ ከፖርቱጋል፤ ሊዮኔል ሜሲ ደግሞ ከአርጀንቲና ጋር 3ኛውን የዓለም ዋንጫ ተሳትፏቸውን ያደርጋሉ፡፡ ሁለቱም ተጨዋቾች በዓለም ዋንጫው አገሮቻቸውን ተሸክመው የማራዶና፤ የፔሌን፤ የክሩፍና የዚዳን ስኬት ማምጣታቸው ቢጠበቅም  የሚሳካላቸው ግን አይመስልም፡፡ ከብራዚሉ 20ኛው ዓለም ዋንጫ በፊት በሁለት ዓለም ዋንጫዎች ለአርጀንቲና 571 ደቂቃዎች የተጫወተው ሜሲ ያስመዘገበው አንድ ጎል ብቻ ሲሆን ሮናልዶም ባለፉት ሁለት ዓለም ዋንጫዎች በፖርቱጋል ማልያ 754 ደቂቃዎች ተሰልፎ ያገባው ሁለት ብቻ ነው።  ሶስት የዓለም ዋንጫ ከተሳተፉት የቀድሞ ተጨዋቾች  ጋር ሲነፃፀር ሮናልዶና ሜሲ ምን ያህል ወደኋላ እንደቀሩ ያሳያል።
ዴንማርኩ ዳል ቶማሰን 5፤ የብራዚሎቹ ፔሌ 12 ሮናልዶ 15 እንዲሁም ዘንድሮ የምንግዜም ከፍተኛ ክብረወሰኑን ከሮናልዶ ይነጥቃል የተባለው ሚሮስላቭ ክሎስ 14 የዓለም ዋንጫ ጎሎች በስማቸው አስመዝግበዋል።
ሜሲ በባርሴሎና ክለብ 277 ጨዋታዎች አድርጎ 243 ጎሎች ሲያስመዘግብ ሮናልዶ ደግሞ በ3 ክለቦች ስፖርቲንግ ሊዝበን፤ ማን ዩናይትድና ሪያል ማድሪድ 386 ጨዋታዎች በማድረግ 264  ጎሎች አስቆጥሯል፡፡
በክለብ ደረጃ ሊዮኔል ሜሲ 6 የሊግ፤ 3 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ ሌሎች ተጨማሪ 4 ዋንጫዎችን ወስዷል፡፡ ሮናልዶም በ3 ክለቦች 4 የሊግ፤ ሁለት የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ እና ሌሎች 4 ዋንጫዎችን አግኝቷል፡፡ 4 ጊዜ በዓለም ኮከብ ተጨዋቾች የወርቅ ኳስ የወሰደው ሜሲ ለአርጀንቲና በ84 ጨዋታዎች 37፤ ሁለቴ የወርቅ ኳስ የተሸለመው ሮናልዶ ለፖርቱጋል በ110 ጨዋታዎች 49 ጎሎች አላቸው፡፡


  • አገር ሲፈርስ እንዲህ ነው? ኢራቅ ለሶስት እየተሰነጠቀች ነው
  • 1ሺ የአሸባሪ ቡድን ታጣቂዎች 30ሺ የኢራቅ ወታደሮችን አሸነፉ
  • በ3 ቀናት ውስጥ ትልልቅ ከተሞችን እየወረረ ከዋና ከተማዋ ደጃፍ ደርሷል
  • አሸባሪው ቡድን በሂሊኮፕተሮች፣ በታንኮች፣ በብረት ለበስ መኪኖች ተንበሻበሸ
  • ከመንግስት ባንክ 480 ሚሊዮን ዶላር የሚሆን ጥሬ ገንዘብ አግኝተዋል
  • በአንድ ቀን ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሞሱል ከተማ ነዋሪዎች ተሰደዱ

          የኢራቅ ሁለተኛዋ ትልቅ ከተማ ሰሞኑን ለአቡበከር ተንበርክካለች። በነዳጅ ሃብት የሚታወቁ ከተሞችና አካባቢዎችን ጨምሮ ቲክሪትሪትና ሳማራ፣ የመሳሰሉ ከተሞችም እንዲሁ አቡበከር በሚመራው አሸባሪ ቡድን (አይሲስ) ስር ገብተዋል፡፡ ማክሰኞ እለት በተጀመረው ወረራ ከሶሪያ ድንበር ተነስቶ በሦስት ቀናት ባግዳድ ደጃፍ ደርሷል የአቡበከር አይሲስ፡፡   የአቡበከር ታሪክ ብዙ ባይታወቅም፤ አላማው ግን ድብቅ አይደለም። ሶሪያን፣ ኢራቅንና ሊባኖስን አንድ ላይ ጨፍልቆ፤ ከቱርክ እና ከኢራን የተወሰነ አካባቢ ቆርሶ፣ ሳውዲ ዓረቢያንና ግብፅን ጭምር በመጠቅለል ሃይማኖታዊ መንግስት ለመመስረት የተቋቋመ ነው። ሊሆን የማይችልና የማይጨበጥ ከንቱ ቅዠት ይመስላል?
አስፈሪ ቅዠት መሆኑ ባያከራክርም፤ “ሊሆን የማይችል ነገር” አይደለም፡፡ የአይሲስ የሰሞኑ ዘመቻ ለዚህ ምስክር ነው፡፡
አንድ ሺ የሚሆኑ አክራሪው ቡድን ታጣቂዎች፣ በሞሱልና በአካባቢው ላይ በከፈቱት ጥቃት 30ሺ ገደማ የመንግስት ጦር ጨርቄን ማቄን ሳይል ሸሽቶ ሄዷል - አንድ የጦር ካምፕ ውስጥ ተቀምጠው የነበሩ 20 ታንኮችና 2 ሄሊኮፕተሮችን ጨምሮ በርካታ ብረት ለበስ መኪኖችና የጦር መሳሪያዎች በአክራሪው እጅ ገብተዋል። የመኪኖቹ ብዛት ቀላል አይደለም። በመቶ የሚቆጠሩ የጦር መኪኖች ናቸው የተማረኩት። ይህም ብቻ አይደለም። የአይሲስ ተዋጊዎች ሞሱል ከሚገኘው የመንግስት ባንክ ውስጥ 480 ሚሊዮን ዶላር የሚገመት ጥሬ ገንዘብ አፍሰው ወስደዋል።
ከአንድ የጦር ካምፕ ያን ሁሉ የጦር መሳሪያና ንብረት የማረኩ የአይሲስ ታጣቂዎች፤ ከሌሎች የጦር ካምፖች ምን ያህል ምርኮ እንደሰበሰቡ ቆጥሮ ለመጨረስ አስቸጋሪ ነው፡፡ 30ሺ ያህል ወታደሮችን አሰልፈው የነበሩ ሁለት የመንግስት ክፍለ ጦሮች፤ በአንድ ምሽት ብን ብለው ጠፍተዋል፡፡ ካምፖቻቸውን እየጣሉ፣ መሳሪያቸውን እየወረወሩ፣ ወታደራዊ ልብሳቸውን እያወለቁ የሸሹት የመንግስት ወታደሮች በየአቅጣጫው ተበታትነዋል። ማምለጥ አቅቷቸው በአሸባሪው ቡድን የተማረኩ በሺ የሚቆጠሩ ወታደሮች ደግሞ እንደ እንስሳ እየታገዱ ሲገረፉና ሲደበደቡ ታይተዋል፡፡
ድንበር ተሻጋሪ ሃይማኖታዊ መንግስት ለመመስረት ዘመቻ እያካሄደ የሚገኘው አይሲስ፣ ረዥም ታሪክ የለውም። በእርግጥ ተዋጊዎቹና መሪዎቹ አዲስ አይደሉም። በኢራቅ የአልቃይዳ ወኪል በመሆን ለአመታት ሽብር ሲፈጥሩ የነበሩ ናቸው። ከአልቃይዳ ተገንጥለው አይሲስ የተሰኘውን ቡድን የመሰረቱት ግን የዛሬ አመት ገደማ ነው። “አልቃይዳ ለዘብተኛ ነው በሚል ነው” የተገነጠሉት። በሌላ አነጋገር፤ የአይሲስ ተዋጊዎች ከአልቃይዳ የባሱ የሃይማኖት አክራሪዎች ናቸው፡፡
ሶሪያ ውስጥ በስተሰሜን ሰፊ ግዛት ለመቆጣጠር ሲዋጋ የከረመው አይሲስ፤ በኢራቅ በዋና ከተሞች በርካታ የሽብርና የፍንዳታ ጥቃቶችን ከመፈፀም ቦዝኖ አያውቅም፡፡ ሰሜናዊ የኢራቅ ግዛቶችን ለመቆጣጠር ዘመቻ የጀመረው ግን በዚህ ሳምንት ነው፡፡ ማክሰኞ እለት በትልቅነቷ ከባግዳድ ቀጥላ የምትጠቀሰው ሞሱል ከተማ በአይሲስ ተወረረች የሚለውን ዘገባ ለማመን የተቸገሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ አንድ ሺ የማይሞሉ የአይሲስ ተዋጊዎች እንዴት እንዴት 30ሺ የመንግስት ጦርን ያሸንፋሉ? ግን አሸነፉ፡፡ ጦሩ ካልተዋጋ ቁጥር ብቻውን ዋጋ የለውማ፡፡
ለነገሩ የአሸባሪው ቡድን ታጣቂዎችም እንዲያ በቀላሉ ማሸነፋቸው አስገርሟቸዋል። ከከተማዋ ባንክ ገንዘብ ዘርፈው፣ ከጦር ካምፖችም የጦር መሳሪያዎችን ማርከው ወደ ሶሪያ ለማምራት እቅድ የነበራቸው የአይሲስ ታጣቂዎች፤ በሞሲል ባገኙት ፈጣን ድል ተነሳስተው ዘመቻውን ለመቀጠል እንደወሰኑ ተዘግቧል። ጊዜ አልፈጀባቸውም፡፡ ረቡዕ እለት ከሰሜን ወደ ደቡብ በመገስገስ፣ የሳዳም ሁሴን የትውልድ ስፍራ የሆነችውንና በነዳጅ ምርት የምትታወቀውን ቲክሪትን ይዘዋል።
የአይሲስ ተዋጊዎች ሐሙስ እለት ትልቁ የኢራቅ ነዳጅ ማጣሪያ የሚገኝበት የባይጂ ከተማን እንደወረሩ የገለፀው ግሎብ ኤንድ ሜይል በበኩሉ፤ በ50 መኪኖች ተጭነው የመጡት ተዋጊዎች የነዳጅ ማጣሪያውን ያልወረሩት የመንግስትን ጦር ፈርተው እንዳልሆነ ጠቅሷል። ከአካባቢው የጎሳ መሪዎች ጋር ለመስማማት ያህል ነው ወደ ነዳጅ ማጣሪያው ያልገቡት። የመንግስት ጦርማ አካባቢውን ጥሎ ጠፍቷል፡፡
በዚያው እለት ይበልጥ ወደ ደቡብ አቅጣጫ በመጓዝ  ሳማራ የተባለች ከተማ የደረሱት የአይሲስ ተዋጊዎች፤ ዘመቻችን ወደ ባግዳድ ይቀጥላል ሲሉ ዝተዋል፡፡ በእርግጥም ባግዳድ ለመግባት 80 ኪሎሜትር ነው የሚቀራቸው፡፡ በአይሲስ ግስጋሴ የተደናገጠው የባግዳድ መንግስት፣ የጦር አውሮፕላኖችንና ሄሊኮፕተሮችን በማሰማራት ድብደባ አካሂዷል።
በሰሜን ምስራቅ በኩል “የኩርዶች መሬት” ብለው የከለሉ ባለስልጣናት እጃቸውን አጣጥፈው አልተቀመጡም። ከአክራሪው ቡድን ጋር ባይዋጉም፤ የኢራቅ ጦር ጥሏቸው የሄዱ የጦር ካምፖችንና የአየር ሃይል ጣቢያዎችን ተቆጣጥረዋል። ያ ሁሉ ጦር መሳሪያ በአክራሪዎች እጅ እንዳይገባ በመስጋት አካባቢውን እንደተቆጣጠሩ የኩርድ አስተዳደር ጦር ሃይል መኮንንን ለአሶሼትድ ፕሬስ ገልፀዋል። ኪርኩክ ከተማ ሙሉ ለሙሉ በኩርድ አስተዳደር ጦር (ፐሽመርጋ) እጅ ውስጥ መሆኗም ተዘግቧል።
በሃይማኖትና በጎሳ የተቧደነው የአገሪቱ ፖለቲካ፤ አክራሪውን ቡድን የመመከት አቅም ያለው አይመስልም። “የሺዓ ሃይማኖት ተከታይ” በሚል የተቧደኑ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች ይበዙበታል የሚባለው የአገሪቱ መንግስት፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አርቅቆ ለፓርላማ ቢያቀርብም ተቀባይነት አላገኘም። “የሱኒ ሃይማኖት ተከታይ” በሚል የተቧደኑ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች ተቃውመውታል። “የኩርድ ተወላጆች” በሚል በዘር የተቧደኑ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞችም እንዲሁ። የአገሪቱ መንግስት ምን ያህል በሃይማኖትና በዘር እንደተከፋፈለ ለመረዳት ፓርላማውን ማየት ብቻ ይበቃል፡፡ አገሪቱ እንዲህ እየታመሰች፤ ከ325 የፓርላማ አባላት መካከል፤ 130 ያህሉ ብቻ ናቸው ለስብሰባ የመጡት፡፡ ቢያንስ ቢያንስ 163 አባላት ካልተገኙ ፓርላማው ምንም አይነት ውሳኔ ማስተላለፍ አይችልም፡፡
የአክራሪው ቡድን ከሁሉም በፊት ማስጠንቀቂያ ያስተላለፈው ለመንግስት ወታደሮች፣ ፖሊሶችና የደህንነት አባላት ነው። “ንስሃ ግቡ” የሚለው የቡድኑ ማስጠንቀቂያ፤ የንስሃ ቦታዎች እንደተዘጋጁ ጠቅሶ፤ ንስሃ የማይገባ ወታደርም ሆነ ፖሊስ እንደሚገደል ገልጿል። በቀን አምስቴ መስገድ ግዴታ መሆኑን ቡድኑ አሳስቦ፤ አልኮል መጠጥና ሲጋራ ተከልክሏል፤ የአገሪቱን ባንዲራ መያዝም ወንጀል ነው ብሏል። ሴቶች ከላይ እስከ ታች የሚሸፍን ልብስ ማድረግ ግዴታቸው እንደሆነና ከቤት መውጣት እንደማይችሉ ተነግሯቸዋል።
የአይሲስ ተዋጊዎች ጥብቅ የሃይማኖት ህግ በማወጃቸውና የተማረኩ ፖሊሶችን ሲገድሉ በመታየታቸው ብዙ ነዋሪዎች አካባቢውን እየሸሹ ሲሰደዱ ሰንብተዋል። ባለፉት አመታት ግማሽ ሚሊዮን ነዋሪዎቿ በስደት የሸሿት ሞሱል፤ ሰሞኑን ደግሞ ተጨማሪ ግማሽ ሚሊዮን ነዋሪዎች ከተማዋን ጥለው እንደተሰደዱ ቢቢሲ ዘግቧል። ብዙዎቹ ስደተኞች የኩርድ ተወላጆች ወደሚበዙበት አካባቢ ነው የሸሹት፡፡ የኢራቅ ግዛት ቢሆንም፤ “የኩርዶች ክልል” የራሱን ጦር አደራጅቶ አካባቢውን የሚያስተዳድር ራሱን የቻለ መንግስት ነው ማለት ይቻላል፡፡
አሁን ደግሞ አይሲስ የሱኒ ሃይማኖት ተከታዮች የሚበዙባቸውን ከተሞች እየተቆጣጠረ ነው።  ኢራቅን ሙሉ ለሙሉ መቆጣጠር ባይችል እንኳ “የሱኒዎች ግዛት” በሚል የራሱን መንግስት ለማቋቋም እንደሚሞክር ይገመታል፡፡ በስተደቡብ ደግሞ የሺዓ ሃይማኖት ተከታዮች የሚበዙበት ሌላ ግዛት አለ። ኢራቅ እንዲህ በዘር እና በሃይማኖት ተሰነጣጥቃ እየፈረሰች ነው፡
ጐረቤት አገሮችና አሜሪካ ምን አስበዋል?
በሞሱል የቱርክ ቆንስላ ውስጥ የሚሰሩ ዲፕሎማቶች፣ የልዩ ሃይል አባላት፣ ተቀጣሪዎችና ቤተሰቦችን ጨምሮ 50 የቱርክ ዜጎች በአይሲስ ተዋጊዎች እንደተያዙበት የገለፀው የቱርክ መንግስት በታጋቾቹ ላይ አንዳች ጉዳት ቢደርስ መረር ያለ የአፀፋ እርምጃ እንደሚወስድ የቱርክ መንግስት አስጠንቅቋል።
“የአይሲስ ዘመቻ ሺዓን ለማጥፋት የሚካሄድ የአሸባሪ ሱኒዎች ሴራ ነው” ብሎ የሚያስበው የኢራን መንግስት፤ እነዚህ ሃይማኖት የለሽ አረመኔ አሸባሪዎችን ከኢራቅ ምድር ለማጥፋት ድጋፍ እሰጣለሁ ብሏል፡፡ የኢራን መንግስት በተፈጥሮው ሃይማኖታዊ መንግስት ቢሆንም፤ በሺዓ እምነት ላይ እንጂ በሱኒ እምነት ላይ የተመሰረተ ሃይማኖታዊ መንግስትን አይደግፍም - “ዋነኛ ጠላት” አድርጐ ነው የሚቆጥረው፡፡ የሳዑዲ መንግስት ደግሞ በተቃራኒው፤ የሺዓ እምነትን ይቃወማል፡፡ ለዚህም ነው በመካከለኛው ምስራቅ በሃይማኖት አክራሪነት የሚነሱ ግጭቶች ላይ ኢራንና ሳዑዲ አረቢያ በጠላትነት የሚሰለፉት፡፡
የአሜሪካ ነገርስ?....
በ25 ቢሊዮን ዶላር ወጪና በአሜሪካ እርዳታ የተቋቋመው የኢራቅ መንግስት ጦር፤ አንድ ሚሊዮን የሚደርስ ቢሆንም፣ ውጤታማ አልሆነም። ከ3 ዓመት በፊት ከኢራቅ ለቅቆ የወጣው የአሜሪካ ጦር፤ ለኢራቅ መንግስት ድጋፍ ከመስጠት አይመለስም። በአይሲስ ተዋጊዎች ላይ የጦር አውሮፕላን ድብደባ እንዲያካሂድ የኢራቅ መንግስት በተደጋጋሚ ለአሜሪካ ጥያቄ እንዳቀረበና እስካሁን ተቀባይነት ሳያገኝ እንደቆየ ግሎብ ኤንድ ሜይል ዘግቧል።


አቡበከር የሺዓ ሃይማኖት ተከታዮች ላይ በመዛት ለደጋፊዎቹ ያስተላለፈው ቅስቀሳ
“ነፃ የምታወጡት ምድር ላይ የሺዓዎች እግር እንዳይደርስ አድርጉ”
“ወደ ባግዳድ ገስግሱ፤ “የምናወራርደው ሂሳብ አለ” በማለት በከተማዋ ቅጥር ሺዓዎችን ግጠሟቸው፡
ለትንፋሽ እንኳ ጊዜ እንዳትሰጧቸው፡፡”
“ሺዓዎች የተሰናከሉ ህዝቦች ናቸው፤ ሰውንና ድንጋይን የሚያመልኩ ሃይማኖት የለሾች ናቸው፡፡
የሺዓ ሃይማኖት ተከታይ የሆኑትን ፕሬዚዳንት አልማሊኪን በተመለከተ አቡበከር ምን ይላል?
“ሙታንታ ሻጭ እንጂ ፕሬዚዳንትና የጦር ሃይሎች ጠቅላይ አዛዥ መሆን አትችልም
“ኢራቅን የመቆጣጠር እድል አምልጧችኋል”
“ሺዓዎች በህይወት እስካሉ ድረስ ይረግሟችኋል”
“በነጃሳዋ ካርባላና በጣኦት አምላኪዋ ናጃፍ ላይ እንዘምታለን” (ሁለቱ ከተሞች የሺዓ ቅዱስ ስፍራዎች ናቸው)

    በስፔን ርዕሰ ከተማ በማድሪድ ወደ 15ሺ ታክሲዎች ቢኖሩም፣ ረቡዕ እለት ለምልክት ያህል አንድም ታክሲ አልነበረም። የለንደን ታክሲዎችም ድምፃቸውን አጥፍተው ውለዋል፡፡ በመኪኖቹ ፋንታ ሾፌሮች ናቸው ሲጮሁ የነበሩት፡፡ 4ሺ የለንደን ባለታክሲዎች ቅሬታቸውን ለማሰማት በከተማዋ ዋና ዋና ጐዳናዎች የተቃውሞ ሰልፍ አካሂደዋል። በጀርመንም፣ በሺ የሚቆጠሩ የታክሲ ሹፌሮች በርሊን ከተማ በሚገኘው ኦሊምፒክ ስቴዲየም ዙሪያ ተሰብስበው ተቃውሟቸውን ገልፀዋል።
የፓሪሶቹ ባለታክሲዎች የባሰባቸው ናቸው። ወደ አውሮፕላን ማረፊያ የሚወስደውን መንገድ ዘግተው ነው የቆሙት። በሌሎች ጎዳናዎች ደግሞ ታክሲያቸውን በዝግታ እያንቀራፈፉ የትራፊክ ጭንቅንቅ ሲፈጥሩ ውለዋል። ማርሴ፣ ሚላን፣ ሮም፣ ኔፕልስ... ትልልቆቹ የጣሊያን ከተሞችም ከባለታክሲዎች አድማ አላመለጡም። ባለታክሲዎች ሰው ሲያመላልሱ ሳይሆን፣ የቅስቀሳ ወረቀት ሲበትኑ ቀኑን አሳልፈውታል፡፡
ለንደን፣ ፓሪስ፣ ሮም፣ በርሊን፣ ማድሪድ... በአውሮፓ ዋና ዋና ከተሞች፣ ባለታክሲዎች በአድማ ስራ ያቆሙት ለምን ይሆን? ተፎካካሪ ስለመጣባቸው ነው። ባለ መኪና ሁሉ ተፎካካሪያቸው ሆኗል - ኡበር በተሰኘ ኩባንያ ምክንያት።
“ኡበር” አስገራሚ ኩባንያ ነው፡፡ በአሜሪካም ሆነ በአውሮፓ ከተሞች፣ የታክሲ አገልግሎት ረዥም እድሜ አስቆጥሯል - ከ80 ዓመት በላይ። ኡበር ግን፤ ገና የ5 ዓመት ጨቅላ ነው። እንዲያም ሆኖ፤ በአለም ካሉት የታክሲ አገልግሎት ድርጅቶች ሁሉ ይበልጣል። ከታላቁ የእንግሊዝ አየርመንገድም ይልቃል። አይገርምም? የድርጅቱ ቢሮ የሚገኘው አሜሪካ ሳንፍራንሲስኮ ነው። ግን በአለም ዙሪያ በመቶ ከተሞች አገልግሎት ይሰጣል። ይሄስ ይገርማል? የታክሲ አገልግሎት የሚያቀርብ ኩባንያ ነው ቢባልም፤ ታክሲዎች የሉትም። አጃኢብ ነው፡፡ እና  የኩባንያው ስራ ምንድነው?
የኩባንያው ዋና ስራ፤ ባለመኪኖችንና ተሳፋሪዎችን፣  በኢንተርኔት አገናኝቶ “ማዳበል” ነው። አሁንማ ኡበር በከፈተው ቀዳዳ ሉሎች ኩባንያዎች እየገቡ፣ ነባሩ የታክስ አገልግሎት በአጭር ጊዜ ውስጥ መልኩ ተቀይሯል፡፡
ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ 11 ሰዓት ላይ፣ ሳሪስ አካባቢ ካለው ቢሮ ወጥተው፣ የአዲስ አበባ የተለያዩ ቦታዎችን... ጎተራን፣ መስቀል አደባባይን፣ መገናኛን አቆራርጠው ኮተቤ አካባቢ ወደሚገኘው መኖሪያ ቤትዎ እንደሚያመሩ ያውቃሉ እንበል። ቶዮታም ይሁን ቢኤምደብሊው…የግልዎ አስተማማኝ መኪና ይዘዋል። ግን የነዳጅ ወጪው አልቻሉትም። በየጊዜው ይወደዳል። ሰሞኑን የነዳጅ ዋጋ እንደገና ጨምሮ የለ! ወጪውን የሚጋራ ሰው ቢያገኙ ትልቅ ግልግል ይሆን ነበር። 11 ሰዓት ላይ እርስዎ በሚሄዱበት አቅጣጫ ታክሲ ለመሳፈር የሚፈልጉ ሰዎች መኖራቸው አያጠራጥርም። የትንንሾቹ ታክሲዎች ዋጋ ቀላል አይደለም። “አነስ ባለ ዋጋ የሚያሳፍረው ባለመኪና ባገኝ” እያለ ይመኛል መኪና ያልያዘ እግረኛ፡፡
ግን ምን ዋጋ አለው? ፈላጊና ተፈላጊ፣ ባለ መኪናና ተሳፋሪ እንዴት ይገናኙ? አስቸጋሪ ነው። ማለቴ... ድሮ አስቸጋሪ ነበር። አሁን ግን ችግር የለም። ከርስዎ የሚጠበቀው ነገር ቢኖር፤ መቼ  ወዴት እንሚጓዙ የሞባይል ስልክዎ ላይ መመዝገብ ብቻ ነው - ለምሳሌ “11 ሰዓት ላይ ወደ ኮተቤ” ብለው ይመዘግባሉ፡፡ መኪና የሌለውና ተዳብሎ መሄድ የሚፈልግ ሰው በበኩሉ፤ ሞባይሉን ከኪሱ አውጥቶ ... ኮተቤ መሄድ እፈልጋለሁ ብሎ ይመዘግባል። የስማርት ፎን አሪፍነት... ነካ ነካ በማድረግ መረጃ መለዋወጥና ትዕዛዝ ማስተላለፍ ይቻላል። ባለመኪናና ተሳፋሪ ፈላጊና ተፈላጊ መገናኘት የሚችሉበት ዘዴ ተፈጠረ ማለት ነው።
 ባለመኪናው የነዳጅ ዋጋን የሚጋራለት ተሳፋሪ ያገኛል። እግረኛው ደግሞ አነስ ባለ ክፍያ የሚያሳፍር ባለመኪና ያገኛል። የድሮውን ችግር የሚያስወግድ አዲስ ዘዴ የተፈጠረው ኡበር በተሰኘው ኩባንያ ነው። ቢዝነስ ማለት፣ ችግርን የሚያስወግድ ወይም የሚያቃልል መፍትሄ ማቅረብ ነዋ። እናም ከክፍያው 20% ይወስዳል። ተሳፋሪው ሃምሳ ብር ቢከፍል፣ አርባ ብር ለባለመኪናው፣ አስር ብር ደግሞ ለኡበር ይሆናል። ተመሰጋግነው መለያየት ነው። እናም ሁሉም ተደሰተ ይባላል።
“እኛ ደስተኛ አይደለንም” ባይ ናቸው - ባለታክሲዎች።
ከአምስት አመት በፊት የተመሰረተው ኡበር፣ ዛሬ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ደንበኞችን የሚያስተናግድ የ17 ቢሊዮን ዶላር ኩባንያ ሆኗል። በእርግጥ አንዳንድ የታክሲ ሾፌሮች ራሳቸው፣ የኡበር ደንበኛ ሆነዋል። ቆመው ተሳፋሪ ሲጠብቁ ከመዋል፣ በኡበር አማካኝነት ከተሳፋሪ ጋር በኢንተርኔት አማካኝነት መገናኘት ይሻላቸዋል። ብዙ የታክሲ ሾፌሮች ግን፣ ነባሩን አሰራር መተው አልፈለጉም።    “በከተማ የትራስፖርት ቢሮ ተመዝግበው ፈቃድ ያላገኙ መኪኖች የታክሲ አገልግሎት እንዳይሰጡ የከተሞቹ ህግ ይከለክላል። ኡበር ይህንን ህግ ይጥሳል” የሚሉት ባለታክሲዎች፣ አገልግሎቱ እንዲቋረጥ ጠይቀዋል - በተቃውሞ ሰልፍና በአድማ። ግን፤ እንዲህ አይነት አገልግሎቶችን ማስቆም አይቻልም በማለት የዘገበው ቢቢሲ፤ ከሁለት መቶ አመታት በፊት፣ የእንግሊዝ ሸማኔዎች የልብስ ፋብሪካዎችን ካላወደምን ብለው ያካሄዱ የተቃውሞ ሰልፍና አመፅ ብዙም አላዛለቀም ብሏል።

“ልቡን በላው”... ፈሊጣዊ አነጋገር እንዳይመስላችሁ። በደቡብ አፍሪካ የኬፕታውን ነዋሪ የሆነው የዚምባብዌ ተወላጅ እንደ አውሬ ነው፤ የባላንጣውን ልብ ሲበላ የተገኘው። አስደንጋጩ ወንጀል የተፈፀመው በቀድሞ ፍቅረኛው ቤት ውስጥ ነው።
የፀብ ምልክት አልነበረም ብላለች የቀድሞ ፍቅረኛው። ከተለያዩ ቆይተዋል። በድብቅ የተደረገ ነገር የለም። ከሱ ተለይታ ከ62 አመት አዛውንት ጋር መኖር ጀምራለች።  ባለፈው ረቡዕ እለት የቀድሞ ፍቅረኛዋ ቤቷ ድረስ ሲመጣ፤ ክፉ ነገር እንዳልጠረጠረች ገልፃ፤ መጠጥ ገዝቼ እንዳመጣ ገንዘብ ሰጥቶኛል ብላለች።
አፍታ አልቆየችም። መጠጥ ገዝታ ስትመጣ፤ ቤቱ ደም በደም ሆኗል። የ62 ዓመቱ አዛውንት በቀድሞ ፍቅረኛዋ ተወግተው ሞተዋል። አንገታቸው በስለት ቆስሏል። ፊታቸው ተነክሷል፤ በጥርስ ተቦጭቋል። ጩኸት ሰምተው የመጡ ጎረቤቶች ወደ ቤት መግባት እንዳልቻሉና በመስኮት ለማየት እንደሞከሩ ጠቅሰው፤ የአዛውንቱን ሆድ ቀድዶ ልባቸው ቆርጦ ሲበላ አይተናል ብለዋል። በድንጋጤ የተደናበሩት ጎረቤቶች ፖሊስ ከጠሩ በኋላ ነው ወንጀለኛው የተያዘው።

       ግንቦት 9 ቀን 2006 ዓ.ም በወጣው የጋዜጣችሁ ዕትም፣ ጤና ዓምድ ላይ “የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች በአሳሳቢ ደረጃ ላይ ናቸው ተባለ” በሚል ርዕስ ያወጣችሁትን ዘገባ የኢትዮጵያ የጥርስ ህክምና ባለሙያዎች ማህበር ተመልክቶታል፡፡
በጥርስ ህክምናም ሆነ በየትኛውም የህክምና ዘርፍ ያሉ ጉድለቶችን በማሳየት እርምት እንዲደረግና ህብረተሰቡ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኝ ማሳሰባችሁ አግባብነት ያለው ነው፡፡ ሆኖም የሰራችሁት ዘገባ ማህበረሰቡን ፍርሀት ውስጥ የሚከትና የተሳሳት መረጃ የሚሰጥ  ሆኖ አግኝተነዋል፡፡
ከሁሉም በላይ በማንኛውም ዜጋ ላይ እንዲደርስ የማንመኘው ችግር የደረሰባት እህታችን፤ የኛም ጉዳይ ነችና ህመሟ ይሰማናል፤ ችግሯም ይመለከተናል፡፡ ነገር ግን ባለሙያ ያልሆኑ ጥቂት ሰዎች በሚሰሩት የተሳሳተ ስራ /በእርግጥ የተባለው ታሪክ ከተከሰተ/ ምክንያት “አብዛኞቹ ክሊኒኮች” ተብሎ መዘገቡ በእጅጉ ያሳምማል፡፡
ለመሆኑ አንድ የጥርስ ህክምና ክሊኒክ ለመክፈት የሚያስፈልገውን መስፈርት አንብባችሁታል? ታዲያ ያን ሁሉ ገንዘብ አፍስሶ፣ የተሳሳተ ስራ በመስራት የሚደሰት ባለሙያ ይኖራል? ለመሆኑ የህክምና መሳሪያዎችን መቀቀያ ማሽን ዋጋው ስንት ነው? ደግሞስ ሃኪሙ ምን ያህል ሞኝ ቢሆን ነው በአግባቡ ንፅህናው ባልተጠበቀ መሳሪያ እየሰራ ከታካሚውም በላይ እራሱን ለበሽታ የሚያጋልጠው? እውነት እናውራ ከተባለ አይመስልም!!!
ዘገባውን የሰሩት ጋዜጠኛስ መሳሪያዎቹን “አየሁ አላየሁም” የሚሉት፣ ስለህክምና መሳሪያዎቹ እውቀት ኖሯቸው ነው ወይስ የነገሯቸውን ብቻ ይዘው ነው? መቼም ስለሚሰሩት ዘገባ መረጃ ቀድሞ መጠየቅ ግዴታ ይመስለናል፡፡ በእርግጥ ዕውቀቱ፣ ችሎታውና ልምዱ የሌለው በልምድ የሚሰራ ተራ ግለሰብ የህክምና ስህተት ሰራ ቢባል ያስኬዳል፡፡ ባለሙያ ያልሆነ ሰው ምን እንደሰራና ምን እንዳጠፋ ለይቶ አያውቅምና፡፡ እንዲህ ያለው ዘገባ፣ በአሁኑ ሰዓት የህክምና ባለሙያዎች ማህበረሰቡን በምን አይነት ሁኔታ ውስጥ ሆነው እያገለገሉ እንዳሉ ካለመረዳት ወይም ለመረዳት ካለመፈለግ የመነጨ በመሆኑ ማዘናችንን እንገልፃለን፡፡
የእህታችን ታሪክ የተገለፀበት መንገድና የተብራሩት ችግሮችን ለመተቸት እውነተኛውን ታሪክ ማግኘትና መገምገም ይጠበቅብናል፡፡ ሳናነሳ የማናልፈው ግን የጥርስ ህክምና ለመስጠት የሚችሉ የተለያዩ ባለሙያዎች መኖራቸውን እንድታወቁ ሲሆን ዘገባው የሚገልፀው አይነት የጥርስ አካል አለመኖሩንና በተጠቀሰው ሆስፒታል ውስጥ የጥርስ ህክምና ክፍል እንደሌለ እንዲሁም የጥርስ ሀኪም አለመኖራቸውን ነው፡፡ አስተያየት ሰጥተዋል የተባሉት የጥርስ ሀኪምም የማህበሩ አባል አይደሉም፡፡ በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎችን ጠይቀንም የሚያውቃቸው አንድም ሰው አላገኘንም፡፡ ከአንድ ባለሙያም ይህን አይነት አስተያየት እንደማይሰጥ ስለምናምን፣ የዘገባው አላማ ሌላ ሊሆን እንደሚችል ገምተናል፡፡
ህብረተሰቡ ተገቢውን ህክምና እንዲያገኝ ማድረግ፤ ባለሙያውም ተገቢውን ስራ በተማረበት መስክ እንዲፈጽም ግዴታዎቹን በአግባቡ ተወጥቶ፣ መብቱም እንዲከበርለት መስራት የተቋቋምንበት ዋና ዓላማችን ነው፡፡ ለዚህም ሚዲያው ያለው ድርሻ ጉልህ መሆኑን ከልባችን እናምናለን፡፡ ነገር ግን የአገሪቱን አቅምና የባለሙያውን ሁኔታ ባለማጤን “አብዛኞቹ” ክሊኒኮች በሚል የወጣው ዘገባ፤ ለህብረተሰቡ የተሳሳተ መረጃ በማድረስ፣ ሥራችንን ካለውም በላይ ከባድና ውስብስብ ስለሚያደርግብን እባካችሁ በጥንቃቄ ዘግቡ እንላለን፡፡ በተረፈ ማናቸውንም መረጃዎች ለመስጠትና በዘርፉ ለሚከሰቱ ችግሮች አፋጣኝ የመፍትሔ እርምጃ ለመውሰድና በትብብር ለመስራት ፈቃደኞች መሆናችንን እንገልፃለን፡፡