Administrator

Administrator

        በየመን በረሃ የአልቃይዳ ድብቅ ካምፕ ውስጥ የነበሩ 55 የቡድኑ መሪዎችና ታጣቂዎች ሰሞኑን መገደላቸውን የዘገበው አሶሼትድ ፕሬስ፣ ጥቃቱ የተፈፀመው በአሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላን (ድሮን) እንደሆነ ገልጿል፡፡
የአሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላኖች ከነባር የስለላ ቅኝት በተጨማሪ የሚሳኤል ጥቃት መፈፀም የጀመሩት በቀድሞው ፕሬዚዳንት ጆርጅ ቡሽ ትዕዛዝ ቢሆንም፤ የአውሮፕላኖቹ ስምሪት እጥፍ ድርብ የተበራከተው በፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ዘመን ነው - በአፍጋኒስታን፣ በኢራቅ፣ በፓኪስታን፣ በየመን፣ በሶማሊያ፣ በሊቢያ ወዘተ፡፡
የሰው አልባ አውሮፕላኖች ስምሪት ለማበርከትም ነው፤ አውሮፕላኖቹን የሚቆጣጠሩ አብራሪዎችም በብዛት እየሰለጠኑ ሲመረቁ የቆዩት፡፡ ዛሬ ወደ 10ሺ ከሚጠጉ የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን አብራሪዎች መካከል 5ሺ ያህሎቹ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ለመቆጣጠር የሰለጠኑ ፓይለቶች ናቸው፡፡
አሜሪካ የጦር ካምፕ ውስጥ በኮምፒዩተሮች ቁሳቁሶችና ስክሪኖች ያሸበረቀ ቢሮ ውስጥ በስራ የተጠመዱት የድሮን ፓይለቶች፤ ጌም የሚጫወቱ ነው የሚመስሉት፡፡ ግን የምር ጦርነት ውስጥ ናቸው፡፡ በየመን ሰማይ የስለላ ካሜራዎችንና ሚሳዬሎችን የተሸከመ ሰው አልባ አውሮፕላን አልቃይዳ ካምፕ ላይ ጥቃት እንዲሰነዝር ትዕዛዝ እየሰጡት ነው፡፡
ከአስር ሺ ኪሎ ሜትር ርቀት ሆነው ይዋጋሉ፡፡ ምን አለፋችሁ? የአልቃይዳ ዋና መሪዎችና ወታደራዊ መሪዎች በአብዛኛው የተገደሉት በድሮን ሚሳዬል ነው፡፡ ውጤታማነታቸውን በማየትም፤ የአሜሪካ ኮንግረስ፣ ለውጤታማ ድሮን አብራሪዎች የጦር ሜዳ ኒሻን ለመስጠት የሚያስችል ህግ አዘጋጅቷል፡፡ በአካል የጦር ሜዳን ባይረግጡም፤ ለውጊያ አደጋዎች ባይጋለጡም፤ በውጊያ የጦርነት ድል ሲያስመዘግቡ የጀብድ ኒሻን ሊበረከትላቸው እንደሚገባ ይገልፃል - አዲሱ ህግ፡፡ ግን በዚሁ የሚያበቃ አይመስልም፡፡ የዛሬዎቹ ሰው አልባ የጦር አውሮፕላኖች፣ የርቀት ተቆጣጣሪ ፓይለት ያስፈልጋቸዋል፡፡
አሁን እየተሰሩ የሚገኙ አዳዲስ የጦር አውሮፕላኖች ግን የርቀት ተቆጣጣሪ ፓይለት አያስፈልጋቸውም፡፡ ራሳቸው ችለውታል እኮ! ሃላፊነት እየተቀበሉ የመሰማራትና ወታደራዊ እርምጃ የመውሰድ አቅም አላቸው፡፡ ያኔስ የጀብድ ኒሻንና ወታደራዊ ማዕረግ ለማን ይበረከታል? ለአውሮፕላኖቹ፡፡

       ከኢትዮጵያ በእጥፍ የሚበልጥ ሕዝብ የያዘችው ናይጄሪያ በአንድ ምሽት፣ ተዓምረኛ የኢኮኖሚ እድገት አስመዘገበች - 90 በመቶ እድገት። እውነት ነው። ግን፣ “አስመዘገበች” የሚለውን ቃል በቸልታ አትዝለሉት።
ነገሩ ቀላል አይደለም። በፈጣን እድገት እየተንደረደረች መሆኗ የሚነገርላት ኢትዮጵያ፣ አሁን ካለችበት ደረጃ ተነስታ በተዓምረኛ ፍጥነት የ90 በመቶ እድገት እውን ለማድረግ፣ ሰባት አመታት ይፈጅባታል - ከ2500 ቀናት በላይ መሆኑ ነው።
ዎልስትሪት ጆርናል (wsj) እንደዘገበው፤ እስከ መጋቢት 20 ቀን ድረስ፣ በጠቅላላ የኢኮኖሚ ምርት፣ ደቡብ አፍሪካ የአህጉሩ ቀዳሚ ነበረች። የደቡብ አፍሪካ አመታዊ የምርት መጠን 370 ቢሊዮን ዶላር ይገመታል። ከኢትዮጵያ በአስር እጥፍ የሚበልጥ ማለት ነው። በሁለተኛ ደረጃ ላይ ደግሞ ናይጄሪያ ነበረች - በ270 ቢሊዮን ዶላር አመታዊ ምርት።
ይሄ የደረጃ ሰንጠረዥ ከመጋቢት 21 ቀን በኋላ ተቀይሯል። ናይጄሪያ በጠቅላላ አመታዊ ምርት፣ የአፍሪካ ቁንጮ መሆኗን አውጃለች - ለዚያውም በሰፊ ልዩነት። የአገሪቱ አመታዊ ምርት 510 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ ነው የተገለፀው። በሌላ አነጋገር፤ ናይጄሪያ በአንድ ምሽት የ240 ቢሊዮን ዶላር (ወደ ሩብ ትሪሊዮን ዶላር የተጠጋ) እድገት አስመዝግባለች። ኢትዮጵያ በፈጣን እድገት ብትገሰግስ፣ አመታዊ ምርቷ ሩብ ትሪሊዮን ዶላር የሚደርሰው ከ20 ዓመት በኋላ ነው። በናይጄሪያ የአንድ ምሽት ጉዳይ ሆኗል።
ጉደኛውን የናይጄሪያ ዜና የዘገቡ እነ wsj እና ዘ ኢኮኖሚስት የመሳሰሉ የሚዲያ ተቋማት፤ ነገሩ ትንግርት ወይም ምትሃት እንደሚመስል ገልፀዋል። ግን፣ “ሐሰት ነው” ወይም “ስህተት ነው” ብለው አልተቹም። የናይጄሪያ አመታዊ ምርት፣ ከግማሽ ትሪሊዮን በላይ ነው በሚል ተስማምተዋል።
ግን፤ በምንኖርባት ዓለምም ሆነ በሌላ ዓለም፤ “ተዓምር”፣ “ትንግርት”፣ “ምትሃት” የሚባል ነገር የለም። እና ናይጄሪያ በአንድ ምሽት ያስመዘገበችው ወደ ሩብ ትሪሊዮን ዶላር የተጠጋ እድገት፣ “የናይጄሪያ ብሔራዊ ተዓምራት” ውስጥ የማይካተት ከሆነ ምን ተብሎ ሊሰየም ነው? ትክክለኛው ስያሜ፣ “የናይጄሪያ መንግስታዊ ዝርክርክነት” የሚል ነው።
የአንድ አገር አመታዊ ምርት ምን ያህል እንደደረሰ የሚታወቀው፣ ጓዳ ጎድጓዳውን፣ ፋብሪካና ገበያውን፣ የእርሻ ማሳና የከብቶች በረትን ሁሉ እያግበሰበሱ ቆጠራ በማካሄድ አይደለም። በየአመቱ አገር ምድሩን ማሰስ አይቻልም። ታዲያ በመላ አገሪቱ፣ 15 ሚሊዮን የገበሬ ቤተሰቦች ቢኖሩ፤ የሁሉንም አመታዊ ምርት በድምር ለማወቅ ምን መላ አለ? ለምሳሌ፣ ከአንድ ሺ ገበሬዎች መሃል የአንዱ ገበሬ ምርት ላይ በማተኮር ጥናት ማካሄድና በአንድ ሺ ማባዛት ነው መፍትሄው። በዚህ የናሙና ጥናት፣ የ15ሺ ገበሬዎችን የምርት መጠን ላይ መረጃ ይሰባሰባል። ከዚያ፤ ይህ ውጤት በአንድ ሺ ይባዛል - ጠቅላላ የአገሪቱ ገበሬዎች አመታዊ ምርት ለማወቅ። በአንድ ሺ ማባዛት የሚያስፈልገው፤ የአንድ ገበሬ ምርት፣ የአንድ ሺ ገበሬዎችን ምርት ይወክላል ከሚል የጥናት መነሻ ስለተነሳን ነው።
አስር ሺ ትልልቅና ትናንሽ ፋብሪካዎች ቢኖሩ፤ የአንድ ሺ ናሙና ፋብሪካዎችን እንቅስቃሴ በማጥናት በመቶ ማባዛት ይቻላል። የትራንስፖርት፣  የጤና፣ የስልክ፣ የኤሌክትሪክ፣ የባንክ፣ የሸቀጥ አቅርቦት የመሳሰሉ አገልግሎቶችም ላይ ተመሳሳይ የናሙና ጥናት ይካሄድና፤ እንደ ውክልናው ክብደት (weighted mean) በመቶም ይሁን በሺ  እያባዛን ጠቅላላ አመታዊ የአገልግሎት ወይም የምርት መጠን ላይ እንደርሳለን። በሌላ አነጋገር፤ እያንዳንዱ ዘርፍና ንዑስ ዘርፍ፤ እያንዳንዱ አካባቢና መረጃ ... ከላይ እስከ ታች በኢኮኖሚ ውስጥ ምን ያህል ድርሻ እንዳለው በቅጡ ተገንዘበን፣ እንደ የድርሻ ተገቢውን የውክልና ክብደት እስከሰጠነው ድረስ፤ አስተማማኝ ቀመርና ስሌት ይኖረናል ማለት ነው።
በሆነ ምክንያት፣ የውክልናው መጠን ወይም ክብደት ከአመት አመት ቢቀያየርስ? ከጊዜ ወደ ጊዜ ብዙ ነገሮች እንደሚቀየሩ አይካድም። የሕዝብ ብዛትን መጥቀስ ይቻላል። ግን ችግር የለውም። በየአመቱ የሚከሰቱና የተለመዱ ጥቃቅን ለውጦችን ሳንዘነጋ በቀመራችንና በስሌታችን ውስጥ በማስገባት መስመር እናስይዘዋለን። በየአመቱ የገጠር የሕዝብ ብዛት በምን ያህል እንደሚጨምር ይታወቃላ። ግን ባልተለመደ ሁኔታና ፍጥነት፤ ለምሳሌ የአገሪቱ የገበሬዎች ብዛት ወደ አስር ሚሊዮን ቢቀንስ ወይም ወደ ሃያ ሚሊዮን ቢያሻቅብስ? ያኔ ለናሙና ጥናት የምንጠቀምበት ቀመርና ስሌት ላይ ችግር ይፈጠራል። ለምሳሌ፤ ከሃያ አመት በፊት፣ የአበባ እርሻ በአገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ ከቁጥር የሚገባ ድርሻ አልነበረውም።
የፊልምና የቪዲዮ ዝግጅትም እንዲሁ። የዛሬውን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ፤ በቀድሞው ቀመርና ስሌት ለመመዘን ስንሞክር፣ የምናገኘው ውጤት የተሳሳተ ይሆናል። የናይጄሪያ መንግስት ሲጠቀምበት የቆየው ቀመርና ስሌትም እንዲሁ፤ ከሃያ አመታት በፊት የነበረውን የኢኮኖሚ መዋቅር ላይ የተመሰረተ ስለሆነ የዛሬውን ሁኔታ በትክክል የማሳየት አቅም አልነበረውም። በናይጄሪያ ባልተለመደ ፍጥነት የተስፋፉት የቴሌኮምና የባንክ አገልግሎት፤ የቴክኖሎጂና የኮንስትራክሽን ቢዝነስ፣ እንዲሁም የፊልምና የቪዲዮ ሥራዎች፤ በኢኮኖሚ ውስጥ ያላቸው ድርሻ እየፈረጠመ መጥቷል። ለሃያ አመታት ያልተለወጠው የመንግስት ቀመርና ስሌት ግን፤ በኢኮኖሚ ውስጥ እየጎሉ ለመጡት ለውጦች ተመጣጣኝ የውክልና ክብደት የሚሰጥ አይደለም። እናም የአገሪቱን አመታዊ ጠቅላላ ምርት በትክክል የማወቅ ወይም የመገመት አቅም አልነበረውም። በየአመቱም የግምቱ ስህተት እየተደራረበ ነው የመጣው። ከሳምንት በፊት የመንግስት ቀመርና ስሌት ተለወጠ። ለሃያ አመታት የተጠራቀመው ስህተትም ተስተካከለ። ይሄ ተዐምር አይደለም። ለበርካታ አመታት የዘለቀ ዝርክርክነት እንጂ።

“ካዛኪስታን” የምትባለውን አገር እስከነመፈጠሯ ባታውቋት ችግር የለውም፡፡ የትም ብትሄዱ፣ የካዛኮችን ምድር የሚያውቅ ብዙ አታገኙም፡፡ እንዲያውም፤ ቱሪስቶች ወደ አገራችን ዝር የማይሉት ለምንድነው በማለት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ማማረር ከጀመሩ ውለው አድረዋል፡፡ ለነገሩ እንኳን በአካል ይቅርና ካዛኪስታንን በስም የሚያውቁ ሰዎች ጥቂት ናቸው፡፡ እነዚህ ጥቂት ሰዎችስ እንዴት አወቋት? እንግሊዛዊው ኮሜዲያን “ቦራት”፣ በካዛኪስታን ላይ የሚሳለቅ ፊልም ስለሰራ ነው፡፡
ፊልሙ በመላው አለም መታየት የጀመረ ጊዜ፣ የካዛኪስታን መንግስት የእገዳ መመሪያ አውጥቶ ነበር፡፡ ለምን መሰላችሁ? በካዛኮች ምድር፣ ያለመንግስት ፈቃድ፣ ያለ ባለስልጣን ይሁንታ መጽሐፍ ማሳተምም ሆነ ፊልም መሥራት አይቻልም፡፡ በአገራችን በደርግ ዘመን እንደነበረው፤ በሳንሱር ጽ/ቤት ታይቶና ተመርምሮ፣ ተቆራርጦና ተበርዞ ነው ለፊልምና ለመጽሐፍ ዝግጅት ፈቃድ የሚሰጠው፡፡ ያው፣ ካዛኪስታንም እንደኛው አገር፣ በኮሙኒዝም ውስጥ የነበረች እና በራሺያ ቅኝ ግዛት ስር የቆየች አገር ስለሆነች፣ የሳንሱር አሰራር ገና አልለቀቃቸውም፡፡ አሁንም የመንግስት ስልጣን በአንድ ፓርቲና በአንድ መሪ የተያዘ ነው፡፡ አሁንም ኢኮኖሚው በአብዛኛው በመንግስት ቁጥጥር ስር ነው፡፡ ቱሪስት እና ኢንቨስተር ወደ ካዛኪስታን ዝር የማይለው በዚህ ምክንያት አይደለም እንዴ?!
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት በዚህ አይስማሙም፡፡ አንደኛው ችግር የአገሪቱ የህዝብ ቁጥር 7 ሚሊዮን ብቻ መሆኑ ነው ይላሉ ፕሬዚዳንቱ፡፡ ነገር ግን ሁለት ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሞንጐሊያ፣ በርካታ የውጭ ቱሪስቶችንና ኢንቨስተሮችን ለመሳብ ችላለች፡፡ ሞንጐሊያማ ምን ሃሳብ አላት እድለኛ ነች፡፡ የአገር ገጽታን የሚያበላሽ እዳ የለባትም፡፡ ካዛኪስታን ግን እድሏ አልሰምር ብሎ ገጽታዋን ጥላሸት የሚቀቡ ነገረኞችን ተጐራበተች፡፡ ይህ አልበቃ ብሎ ስሟን አሳደፉት፡፡ እነ ማን? እነ ፓኪስታን፣ አፍጋኒስታን ናቸዋ፡፡ ስማቸው ተመሳሳይ ስለሆነ ብቻ፣ ካዛኪስታን የሽብርና የትርምስ አገር ትመስላለች፡፡ ሞንጐሊያ ከዚህ ጥላሸት ነፃ ነች፡፡ ስለዚህ መፍትሔው እንደሞንጐሊያ መሆን ነው፡፡ አፍጋኒስታን ማለት የአፍጋን ቦታ እንደማለት ነው፡፡ ካዛኪስታን ደግሞ የካዛክ ቦታ፡፡ ሞንጐሊያ ማለት የሞንጐል ምድር ስለሆነ፣ የካዛኪስታንን ስም ወደ ካዛኪያ እንቀይረው ብለዋል - ፕሬዚዳንቱ፡፡

“መሣሣት የሰው ነው፡፡ ይቅር ማለት ግን የመለኮት!”
(to err is human, to forgive is divine)
ሁለት ሰዎች ከሩቅ አንድ የአውሬ ቅርፅ ያያሉ፡፡
አንደኛው፤
    “ያ የምናየው እኮ ጅብ ነው” አለ፡፡
ሁለተኛው
    “ያ የምናየው እኮ አሞራ ነው” አለ፡፡
አንደኛው፤
    “እንወራረድ?”
ሁለተኛው፤
    “በፈለከው እንወራረድ!”
አንደኛው፤
    “እኔ አንድ በቅሎ አገባ!”
ሁለተኛው
    “እኔም በቅሎ ከነመረሻቷ አገባ!”
መልካም፡፡ ቀረብ ብለን እንየው፡፡ እየተጠጉ መጡ፡፡
አንደኛው፤
    “አሁንም በአቋምህ ፀንተሃል? አሞራ ነው የምትል?”
ሁለተኛው፤
    “ከፈራህ አንተ አቋምህን ቀይር እንጂ እኔ አሞራ ነው ብያለሁ አሞራ ነው!”
አንደኛው፤
    “እኔ ፈሪ ብሆን ጅብ መሆኑን እያየሁ ቀርበን እናረጋግጥ እልሃለሁ?!” አለ በቁጣ፡፡
እየቀረቡ መጡ፡፡
የእንስሳው ቅርፅ አሁንም አልተለየም፡፡
ተያይዘው ቀረቡ፡፡
እጅግ እየተጠጉ ሲመጡ፤ ያ ያዩት እንስሳ አሞራ ኖሮ ተነስቶ በረረ፡፡
ሁለተኛው ሰው፤
    “ይኼው በረረ፡፡ አሞራነቱ ተረጋግጧል፤ ተበልተሃል!”
አንደኛው፤
    “በጭራሽ አልተበላሁም!”
ሁለተኛው፤
    “እንዴት? ለምን? አስረዳኛ?!”
ይሄኔ አንደኛው፤
    “ቢበርም ጅብ ነው! መብረር የሚችል ጅብ መኖር አለመኖሩን በምን ታውቃለህ? አለው፡፡”
                                            *     *      *
በህይወታችን ውስጥ የዋሸነው፣ የካድነውና በዕንቢ-ባይ ግትርነት አንቀበለውም ያልነው፤ በርካታ ነገር አለ፡፡ የሁሉ ቁልፍ፤ ስህተትን አምኖ፣ ተቀብሎ ራስን ለማረም ዝግጁ መሆን ነው!!
ይቅርታ መጠየቅና ይቅር ማለት የዘመኑ ምርጥ አጀንዳ ነው - በተለይ በኢትዮጵያ - በተለይ በዳግማይ ትንሣኤ ሰሞን! ሰሞኑን “በአይዶል” ፕሮግራም በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያየናት ልጅ፤ ከፋሲካ እስከ ዳግማይ ትንሣዔ ብሎም እስካገራችን ዕውነተኛ ትንሣዔ ድረስ፣ ከተማርን ከተመካከርንባት፣ ልዩ ተምሣሌት፣ ልዩ አርአያ ናት፡፡ “መሣሣት የሰው ነው፤ ይቅር ማለት ግን የመለኮት” የሚለው አባባል ትርጓሜው” እዚህ ጋ ይመጣል፡፡ የዋሸነውን፣ ለማታለል ያደረግነውን ለማሳመን መንገዱ ይሄ ነው ብለን ሰው ሁሉ/ ህዝብ ሁሉ እንዲያምነን ላደረግነው ነገር፤ ቆይተን፣ ተፀፅተን፣ ለራሳችን ህሊና ተገዝተን፣ ንሥሐ መግባት መልመድን የመሰለ መንፈሣዊ አብዮት የለም፡፡ ያን መሣይ መንፈሣዊ ለውጥ አይገኝም!! እስከዛሬ፤ በቀደሙትም ሆነ አሁን ባሉት ፓርቲዎች ዘንድ፣ በቀደሙት መንግሥታትም፣ አሁን ባለው መንግሥትም ዘንድ የማይታወቀው፤ እጅግ ቁልፍ ነገር፤ “ተሳስቻለሁ… ይቅርታ” ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያየናት የ“አይዶል” ተወዳዳሪ ድምፃዊት ያሳየችንና ያስተማረችን ጉዳይ ይሄው ነው፡፡ በእኛ ግንዛቤ፤ ተወዳዳሪዋ በድምፃዊ አረጋኸኝ ወራሽ ቤት በልጅነቷ በቤት ሠራተኝነት ተቀጥራ፣ ቀጣሪውን ማለትም አርቲስቱን ስለራሷ ህይወት ዋሽታዋለች፡፡ አርቲስቱ በሰማው አሳዛኝ የህይወት ታሪክ ልቡ ተነክቷል፡፡ ትምህርት እንድትጀምርም ያደርጋል፡፡ ልጅቱ ድንገት ከቤት ትጠፋለች፡፡
ዛሬ ግን አርቲስቱ በዳኝነት በተገኘበት መድረክ፤ የ“አይዶል” ድምፃዊት ተፈታኝ ሆና ስትቀርብ ድምጿን ካሰማች በኋላ፤ “ከመዳኘቱ በፊት አንድ ነገር ለመናገር እፈልጋለሁ አለች፡፡” ዳኞቹ ፀጥ አሉ፡፡
እዚህ መካከል አንድ የማውቀው ሰው አለ፡፡ እሱም ግር ብሎት ካልሆነ ያውቀኛል፡፡ እሱ ቤት በልጅነቴ ተቀጥሬ ነበር፡፡ ሁኔታዬንና የውሸት ታሪኬን ሰምቶ፤ አምኖኝ፣ ት/ቤት አስገብቶኝ፤ እኔ ግን ከቤቱ ጠፍቼ ሄጃለሁ፡፡ ያ ሰው፤ ድምፃዊ አረጋኸኝ ወራሽ ነው… እሱ ቤተሰቦቼን ሊያፈላልግ ሞክሯል ግን አልተሳካለትም፡፡
“እኔም ተመልሼ ሁኔታውን ለመግለጽ ሁኔታውም ድፍረቱም አልነበረኝም፡፡” የምትለው አርቲስት፤ “ዛሬ ግን ዕውነቱን ለማሳወቅ እፈልጋለሁ፡፡ ስለቤተሰቦቼ አለመኖርና ስራ ስለማጣቴ ሁሉ ያወራሁት ውሸት መሆኑን ዛሬ በግልጽ ማስረዳት እፈልጋለሁ፤ ይቅርታ እንዲያደርግልኝም እጠይቃለሁ” ነው የንሥሐዋ መንፈስ! የዳግማይ ትንሣዔ መሪ መልዕክት (1) “ልናጠፋ እንችላለን ግን ይቅርታ ጠይቀን ቀሪውን ህይወት ማስተካከል እንችላለን” ነው፡፡ ልብ እንበል፤ ልጅቱ ለአረጋኸኝ ወራሽ ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ህዝብ ነው ንሥሐዋን የተናገረችው! አቤት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ይሄን ቢያውቁ! አቤት ገዢው ፓርቲ ይሄን ቢችልበት አቤት በየደረጃው ይቅርታ መጠየቅ አልባ የሆነ ኃላፊ፣ አለቃ እና የበላይ ይህን ቢረዳ! አቤት አበሻ በጠቅላላ፤ ይሄ ቢገባው!
ሁለተኛው የፋሲካና የዳግማይ ትንሣዔ ግብረገባዊ ትምህርት (The Moral of the Story) የ “ጆሲ ኢን ዘ ሐውስ” ገድል ነው፡፡ የማን ያለብሽ ዲቦን ልጆችና እህት አንድ መጠለያ ለማስገኘት ጆሲ ያረገው ጥረት የወቅቱ መልዕክት ነው፡፡
ትምህርት 1) ከኢትዮጵያ የቤት - ነክ ቢሮክራሲ ጋር፣ ውጣ ውረዱን ችሎ፣ ታግሦ፣ ተቻችሎ ውጤት ማስገኘት
ትምህርት 2) እያንዳንዱን ክስተት በካሜራ ቀርፆ፣ መንግሥትም አምኖበት ለዕይታ መብቃቱ፤
ትምህርት 3) የመንግሥት ፈቃደኝነትና አዎንታዊ እርምጃዎች መረጋገጥ
ትምህርት 4) በየደረጃው ያሉ ስፖንሰሮች ሀ) የደብረዘይት መናፈሻ ቦታው ስፖንሰርሺፕ ለ)የመጓጓዣ መኪናው  ሐ) የአዋሳ ኮሜዲያን መምጣት መ) የጋሽ አበራ ሞላ መምጣት ሠ)የቤት - ዕደሳ ላይ የተሳተፉት ስፖንሰር ድርጅቶች መኖር ረ) የቤት ዕቃዎች ለማሟላት አስተዋጽኦ ያደረጉ ስፖንሰሮች መኖር ሰ) ለልጆቹ ትምህርት መቀጠል የት/ቤቶችና የዩኒቨርሲቲዎች ትብብር፣ ሸ) የኮምፒዩተር እገዛ ለማድረግ የተባበሩ ኮምፒዩተር አስመጪዎች     
ትምህርት 5) የልጆቹ መኖሪያ ጐረቤቶችን ማሰባሰብና ጉዳዩን እንዲረዱ ማድረግ፣ ሰው                   የአካባቢው ውጤት መሆኑን ይነግረናል፡፡
እኒህን ሁሉ ስፖንሰሮችና ነዋሪዎች አስተባብሮ ዓይነተኛና አርአያዊ ተግባር መፈፀሙ ጆሲን ድንቅ የሚያሰኘው ነው፡፡ ማስታወቂያ ሰሪዎች እንማር! አገር አልሚዎች እንማር! የተቀደሰ ተግባር፣ ለተቀደሰ ትንሣኤ እንደሚያበቃን ለማረጋገጥ የጆሲ ዚን ዘ ሐውስን ተምሳሌትነት እንገንዘብ፡፡ አንድ ቤተሰብ መገንባት ሙሉ አገር መገንባት ነው፤ “አምሣ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ ለአምሣ ሰው ጌጡ ነው” ነው መንፈሱ፡፡ በርካታ ስፖንሰሮች ለመዝናኛ ስፖንሰር እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ ይመሰገናሉም፡፡ ሆኖም ዛሬ የተሻለ ስፖንሰራዊ ተግባር አይተናል፡፡ በየማስታወቂያዎች ውስጥ መዝናኛ ብቻ ሳይሆን ቁምነገር፣ ለሀገር የሚጠቅም ጉዳይ፣ መካተት እንደሚችል በአጽንኦት ይጠቁመናል፡፡ ለብዙዎቻችን ትምህርት ነው፡፡ ሁሉን አቀፍ የስፖንሰርሺፕ እንቅስቃሴ አገር ያለማል፡፡ እንደ ጆሲ ያለ ልባዊና ልባም ሥራ ምን መምሰል እንዳለበት ታላቅ ደርዝ፣ ታላቅ ፍሬ - ጉዳይ ያስጨብጠናል፡፡ አገር የሚመራ ይህን ይገንዘብ፣ ማስታወቂያ የሚሠራ ይሄን ይገንዘብ፤ አገርን የሚያስብ ይሄን ይገንዘብ፡፡ “መልካም ሥራ ሥራና ሠይጣን ይፈር” የሚለው የሼክስፒር ጥቅስ ትልቅ ትርጉም የሚኖረው ዛሬና እዚህ ላይ ነው!!

 በግድቡ ላይ ለሚከሰት አደጋ፣ ሙሉ ለሙሉ ተጠያቂ የማደርገው ግብጽን ነው ብላለች - ሱዳን
“በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጽኑ እምነት አለን፣ የገንዘብ ጉዳይ አያሰጋንም!” - ሳሊኒ ኮንስትራክሽን

ግብፅ ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ አለማቀፍ የገንዘብ ብድሮች፣ ከውጭ መንግስታት እንዳይገኙ በማድረግ ግንባታውን ለማደናቀፍ እያሴረች ነው ስትል ሱዳን አወገዘች፡፡
የሱዳን ምስራቃዊ ብሉ ናይል ግዛት ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት ሁሴን አህመድ፣ ኢትዮጵያ በማከናወን ላይ ለምትገኘው የታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ የሚውሉ አለማቀፍ ብድሮችን እንዳታገኝ ለማድረግ በግብጽ በኩል በድብቅ እየተከናወኑ ያሉት አግባብ ያልሆኑ ተግባራት፣ ግድቡ በገንዘብ እጥረት ሳቢያ ከሚፈለገው የጥራት ደረጃ በታች እንዲሰራና ለአደጋ እንዲጋለጥ ሊያደርጉ ይችላሉ በማለት ድርጊቱን ማውገዛቸውን ሱማሌላንድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
ግድቡ ከሚፈለገው የግንባታ ጥራት በታች የሚሰራ ከሆነ፣ በረጅም ጊዜ ሂደት የሚፈርስበት ዕድል እንደሚኖርና ተያይዞ የሚከሰተው የጎርፍ አደጋም ሱዳንን ክፉኛ ሊጎዳ የሚችል በመሆኑ፣ ሱዳን የግብጽን ድርጊት አጥብቃ እንደምትቃወመውና ለሚደርሰው አደጋ ሙሉ በሙሉ ተጠያቂ እንደምታደርጋት ባለስልጣኑ መናገራቸውን ዘገባው ያስረዳል፡፡
የሱዳን ምስራቃዊ ብሉ ናይል ግዛት፣ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ከሚከናወንባት የቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልሏ ጉባ ጋር በቅርብ ርቀት የሚካለል እንደመሆኑ፣ በግድቡ ላይ የመፍረስ አደጋ ቢከሰት፣ ግዛቱ በጎርፍ አደጋ ሙሉ ለሙሉ ሊወድም እንደሚችል ባለሙያዎች የሰጡትን አስተያየት ያቀረበው ዘገባው፣ ይህም የግዛቱን ባለስልጣናት እንዳሳሰባቸው ጠቁሟል፡፡
ግብጽ በግድቡ ላይ ባለቤትነት እንዲኖራት እንጂ፣ ስለ አካባቢው ደህንነት ደንታ የላትም ያሉት ባለስልጣኑ፣ የግድቡን ግንባታ በራሷ ወጪ ለማከናወንና በበላይነት ለማስተዳደር ከመጀመሪያ አንስቶ ፍላጎት እንደነበራት ተናግረዋል፡፡
“በግንባታ ጥራት መጓደል ሰበብ በግድቡ ላይ ለሚፈጠር የመፍረስ አደጋና ከዚያ ጋር ተያይዞ በግዛታችን ላይ ለሚከሰት የጎርፍ አደጋ፣ ሱዳን ሙሉ ለሙሉ ተጠያቂ የምታደርገው ግብጽን ነው” ያሉት ባለስልጣኑ፣ ግብጽ አስር አገራት በጋራ በሚጠቀሙበት የአባይ ወንዝ ላይ ኢኮኖሚዋን ሙሉ ለሙሉ ጥገኛ ከማድረግ ይልቅ፣ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዋን በሌሎች መስኮችም ማስፋፋት እንደሚኖርባት ተናግረዋል፡፡
ግብጽ ከረጅም አመታት በፊት የገነባችው አስዋን ግድብ፣ የኑብያ ህዝቦችን ህልውና ክፉኛ መጉዳቱንና ጥንታዊ የዕደ-ጥበብ ስራዎችን ማውደሙን ያስታወሱት ባለስልጣኑ፣ ይሄም ሆኖ ግን የትኛውም አገር የግድቡን ግንባታ እንዳልተቃወመና ስራዋን ለማደናቀፍ እንዳልሞከረ ገልጸዋል፡፡
የሱዳኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ካርቲም፣ ባለፈው ጥቅምት ወር ግብጽ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ ያነሳችውን ተቃውሞ እንደተቹት የጠቀሰው ዘገባው፣ ሚኒስትሩ በተለይም የግብጽ መገናኛ ብዙሃን ግድቡን በተመለከተ መሰረተ ቢስ መረጃዎችን እያናፈሱ ነው በማለት መክሰሳቸውንና የግድቡ መገንባት ሊያስከትላቸው ይችላሉ ተብለው ከሚጠቀሱ ማናቸውም አይነት ችግሮች ይልቅ፣ ጠቀሜታው እጅግ የጎላ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው መናገራቸውን አስታውሷል፡፡
ተቀማጭነቱ በአውሮፓ የሆነው ስቶክሆልም ኢንተርናሽናል ዋተር ኢንስቲትዩት የተባለ አለማቀፍ ተቋም፣ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መገንባት፣ ግብጽ ለደለል ቁጥጥርና በትነት ሳቢያ የሚጠፋውን ውሃ ለማስቀረት ታወጣው የነበረውን በሚሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር ገንዘብ የሚያስቀርላት በመሆኑ፣ ለኢትዮጵያ ገንዘብ መክፈል ይገባታል ማለቱንም ዘገባው ጨምሮ አስታውሷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት፣ በዜጎቹ የገንዘብ መዋጮ የተጀመረው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ፣ በተያዘለት ዕቅድ መሰረት ግንባታው እየተከናወነ እንደሚገኝ፣ ከግድቡ ግንባታ ጋር በተያያዘ የገንዘብ ችግር እንደማይገጥመውና በታሰበው የጥራት ደረጃና በተያዘለት የጊዜ ገደብ ተሰርቶ እንደሚጠናቀቅ በተደጋጋሚ መግለጹ ይታወቃል፡፡
የሮይተርስ ዘጋቢ አሮን ማሾ በበኩሉ፣ የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በማከናወን ላይ የሚገኘው ግንባር ቀደሙ የጣሊያን ኮንስትራክሽን ኩባንያ ሳሊኒ፣ ከግንባታው ጋር የተያያዙ ክፍያዎች በሙሉ በወቅቱ እየተፈጸሙለት እንደሆነ  ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
የኮንስትራክሽን ኩባንያው፣ የኢትዮጵያ መንግስት በቀጣይም የግድቡን ግንባታ ለማጠናቀቅ የሚያስፈልገውን በቢሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር ቀሪ ገንዘብ በማሟላት ረገድ፣ ችግር ይገጥመኛል ብሎ እንደማያስብና ከፋይናንስ እጥረት ጋር በተያያዘ ምንም አይነት የሚያሰጋው ነገር እንደሌለ መናገሩን የሮይተርስ ዘገባ ጨምሮ ገልጧል፡፡ “በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጽኑ እምነት አለን፣ የገንዘብ ጉዳይ አያሰጋንም!” ብሏል ሳሊኒ ለሮይተርስ፡፡

“ቦርድ” ለሚወጡ ወታደሮች የ2 በመቶ ክፍያ ተጨመረ

የመከላከያ ሚኒስቴር እንደአስፈላጊነቱ እያየ የጦር መኮንኖችን የአገልግሎት ዘመንና የጡረታ መሰናበቻ እድሜ በሁለት ዓመት ለማራዘም የነበረው ሥልጣን እንደተሻሻለ ምንጮች ገለፁ፡፡ የመከላከያ ኃይል አባላት የሥራ ዘመናቸውን በ3 ወይም በ5 ዓመት ማራዘም በአዲሱ አሰራር ተፈቅዷል፡፡ የጡረታ እድሜ በ5 ዓመት የሚራዘመው ለከፍተኛ መኮንኖች እንደሆነ ምንጮች ጠቅሰው፤ ከከፍተኛ መኮንን በታች ደግሞ ካሁን ቀደም የነበረው የሁለት ዓመት ማራዘሚያ ወደ ሶስት አመት ከፍ እንዲል መደረጉን ገልፀዋል፡፡
ከዚሁ የጡረታ ማራዘምያ አዲስ አሰራር ጋር፤በ“ቦርድ” ለሚሰናበቱ የመከላከያ ኃይል አባላት የሁለት በመቶ ክፍያ ተጨምሯል፡፡ የመከላከያ ሠራዊት አባል በተለያዩ ምክንያቶች “ቦርድ” እንዲወጣ ሲወሰን፣ ወርሃዊ ክፍያው የደሞዙ አርባ አምስት በመቶ የነበረ ሲሆን አሁን አርባ ሰባት በመቶ እንዲሆን ተወስኗል፡፡

የፌደራል ባለስልጣናት ጣልቃ ገብተው ሲያረጋጉ ሰንብተዋል

የድሬደዋ ዩኒቨርስቲ የሶማሌ ክልል መስተዳድር የባለቤትነት ጥያቄ ተነስቶበት ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ በሚሊሻ ተቆጣጥሮት የነበረ ሲሆን የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተ/ማርያም፣ የቀድሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ አዲሱ ለገሠ፣ የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ተፈራ ደርበውን ጨምሮ ሌሎች የፌደራል ባለስልጣናት በጉዳዩ ጣልቃ ገብተው ማረጋጋታቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የዩኒቨርስቲው ባለቤት እኔ ነኝ የሚል ጥያቄ ያነሣው ሶማሌ ክልል ቦታውን በክልሉ ሚሊሻዎች አስከብቦ የክልሉን ባንዲራ ሰቅሎ የነበረ ሲሆን፣ የፌደራል ባለስልጣናቱ በጉዳዩ ጣልቃ መግባታቸውን ተከትሎ ክልሉ ሐሙስ እለት ሚሊሻዎቹን ከአካባቢው ቢያስወጣም የክልሉ ባንዲራ አሁንም በዩኒቨርስቲው አካባቢ እየተውለበለበ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
የድሬደዋ ዩኒቨርስቲ የሚገኘው በድሬደዋ አስተዳደር በኩል “ቀበሌ 02” ተብሎ የሚጠራ ሲሆን፤ የሶማሌ ክልል መስተዳድር በበኩሉ፤ ዩኒቨርስቲው አጠገብ “በሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ቦረን ገጠር አስተዳደር” የሚል ታፔላ እንደተከለ ምንጮች ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኙ መኖሪያ ቤቶችም ባለሁለት ካርታ መሆናቸውን የገለፁት ነዋሪዎች፣ በሶማሌ ክልል እና በድሬደዋ ከተማ አስተዳደር ካርታ የወጣላቸው እንደሆኑ ጠቁመዋል፡፡ እንዲሁም ዩኒቨርስቲው ጀርባ የሚገኙ ገበሬዎች ባነሱት የመሬት ጥያቄ ምክንያት ያለ አጥር ክፍቱን የተቀመጠ መሆኑንም ምንጮች ገልፀዋል፡፡

ለውጪ ገበያ የሚቀርበውን የጥጥ ክር ምርት በእጥፍ ያሳድጋል
ኢትዮጵያን በአለም ከታወቁት ጥቂት የጥጥ ክር አምራች አገራት አንዷ ለማድረግ ያቀደው ኤስቪፒ ቴክስታይልስ በኮምቦልቻ በ11 ቢሊዮን ብር ወጪ ዘመናዊ የጥጥ ክር ፋብሪካ ሊገነባ መሆኑን አስታወቀ፡፡
በኮምቦልቻ የሚገነባው ፋብሪካው  በቀን እስከ 272.9 ቶን የሚደርስ ምርጥ የጥጥ ክር የማምረት አቅም እንዳለው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ፋብሪካው ምርት ሲጀምር፣ አገሪቱ በአሁኑ ጊዜ ለውጭ ገበያ የምታቀርበውን ጥራቱን የጠበቀ የጥጥ ክር ምርት፣ በእጥፍ እንደሚያሳድገው የተገለፀ ሲሆን የአገሪቱን የልማት እቅድ መሰረት አድርጎ የተቀረጸው ፕሮጀክቱ፣ በአሁኑ ጊዜ ከቅድመ ዝግጅት ደረጃ አልፎ ወደ ትግበራ እንቅስቃሴ ለመሸጋገር እያኮበኮበ ነው ተብሏል፡፡
የፋብሪካው መገንባት በውጭ ንግዱ ዘርፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት ሲሆን ለበርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች የስራ ዕድል እንደሚፈጥርና  የተለያዩ ጥቅሞችን እንደሚያስገኝ ተነግሯል፡፡
እ.ኤ.አ በ1898 ዓ.ም  የተመሰረተውና የፕሮጀክቱ ባለቤት የሆነው የህንዱ ፒቲ ግሩፕ፣ በስሩ በርካታ ኩባንያዎችን የሚያስተዳድር ሲሆን  በጨርቃ ጨርቅ፣ በፋይናንስ፣ በሸቀጣሸቀጥ፣ በሪል እስቴትና በጌጣጌጦች የንግድ  ስራዎች ላይ በመሰማራት ትርፋማ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል ተብሏል፡፡

Saturday, 19 April 2014 12:47

የቀልድ - ጥግ

እንደ አረቄ ጠርሙስ መጠጥን ታግሶ የሚያስቀምጥ የለም።
*   *   *
አንድ ሰካራም አንድ ማስታወቂያ ሰሌዳ ፊት ለፊት ቆሞ፤
“አይቻልም! በጭራሽ አይቻልም!” እያለ ያልጎመጉማል። አንድ ፖሊስ ያዳምጠው ነበረና፤
“ምንድን ነው የማይቻለው” ሲል ይጠይቀዋል።
ሰካራሙም፤
“ተመልከት ምን እንደሚል” እያለ ወደ ሰሌዳው ያሳየዋል - ፅሁፉን ያነበዋል፡-
Drink Canada Dry
ይሄ እንዴት ይቻላል? ካናዳን በደረቁ መጠጣት፤ በጭራሽ አይቻልም። ባይሆን በረዶና ሎሚ ከሰጡ ይቻል ይሆናል …. በደረቁ ግን በጭራሽ አይቻልም!! እያለ እያልጎመጎመ መንገዱን ቀጠለ።    
አንድ የሰከረ ሰው እንደድንገት ትኩስ የተቆፈረ መቃብር አጠገብ ይደርስና ሳያስበው ጉድጓድ ውስጥ ይወድቃል። ለመውጣት ቢሞክር ያቅተዋል።
በአጋጣሚ ሌላ ሰካራም በዚያ መቃብር አጠገብ ሲያልፍ ያየዋል። ሁለተኛው ሰካራም አካፋ አንስቶ በመጀመሪያው ሰካራም ላይ አፈር ይሞላበት ጀመር።
የወደቀው ሰካራም፤ “ጎበዝ በእግዚሃር አውጣኝ በጣም እየቀዘቀዘኝ፣ እየበረደኝኮ ነው”
ሁለተኛው፤ አፈር ማልበሱን እየቀጠለ፤
“እንዴት አይበርድህ ወንድሜ! አፈር ስላለበስክ እኮ ነው!!”
*   *   *
አንድ የብቃት ማረጋገጫ ባለሙያ ወደ ሁለት ተላላኪዎች ይመጣና፤ አንደኛዋን፤
“እዚህ ምንድነው ሥራሽ?” ይላታል።
ተላላኪዋ የቢሮክራሲው ሻጥር/ቀይ ጥብጣብ/፣ የአለቆች ሰውነቷን ማሻሸት፣ ቅፆች ማመላለስ፣ የየቢሮው ፖለቲካ፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ የብቃት ማገራገጫ ባለሙያዎች ንትረካ አስመርሯታልና፤ “ምንም ሥራ አልሰራም!” አለችው።
የብቃት ማረጋገጫ ባለሙያውም፤
“መልካም። እዘግበዋለሁ” አለና ፃፍ ፃፍ አደረገ። ቀጥሎም ወደ ሁለተኛዋ ተላላኪ ዞሮ፤
“አንቺስ ምን እየሰራሽ ነው?” አላት።
ይቺኛዋም በሥራዋ የተማረረች ነበረችና፤
“እኔም ምንም አልሰራም!” አለችው።
የሥራ ብቃት ማረጋገጫ ባለሙያውም፤
“አሃ! የሥራ መደራረብ አለ ማለት ነው ሁለታችሁ ጋ” አለ።
    (አይ ቢ.ፒ.አር?)
*   *   *
የአሳንስር አስተናጋጅ ምሬት
የአሳንስር አስተናጋጅ ምሬት የታሪኮችን መጨረሻ አለማወቁ ነው!
*   *   *
ሰባኪ ለአንድ ትንሽ ልጅ፤
“ልጄ በየማታው ፀሎት ታደርሳለህ?”
“አዎን አባባ!”
“ጠዋት ጠዋትስ እንደዚያው ትፀልያለህ?”
“አይ”
“ለምን?”
“ቀን ቀን ስለማልፈራ!”

ጥራት የሚለካው በደንበኛ እርካታ ነው
ዶ/ር ኢ/ር ዳንኤል ቅጣው በ1972 ዓ.ም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በሜካኒካል ኢንጅነሪንግ በከፍተኛ ማዕረግ ተመረቁ።
በተማሩበት ዩኒቨርሲቲ በረዳት መምህርነትና በመምህርነት ለሁለት ዓመት ከሠሩ በኋላ፣ ለሁለተኛ ዲግሪያቸው ጣሊያን ሄዱ። በጣሊያን ፖሊቴክኒኮ ዲ ቶሪኖ እና ፖሊቲክኒኮ ዲ ሚላኖ የሚባሉ ሁለት ከፍተኛ ዩኑቨርሲቲዎች አሉ። ዶ/ር ኢ/ር ዳንኤል በፖሊቴክኒኮ ዲ ቶሪኖ ትምህርታቸውን ተከታትለው ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በኢንዱስትሪያል ኢንጅነሪንግ ተመርቀው በ1977 ዓ.ም ወደ አገራቸው ተመልሰው በአ.አ.ዩ ሜካኒካል ኢንጅነሪንግ ሲያስተምሩ ቆዩ።
በ1988 ዓ.ም ለሦስተኛ ዲግሪያቸው ተመልሰው ወደ ጣሊያን ሄዱ። እዚያም ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በተማሩበት በፖሊቴክኒኮ ዲ ቶሪኖ ዩኒቨርሲቲ የዶክትሬት ዲግሩ ትምህርታቸውን ተከታትለው በ1992 ዓ.ም በኢንዱስትሪያል ኢንጅነሪንግ በዶክትሬት ዲግሪ ተመረቁ፡ ከዚያ እንደተመለሱ እስካሁን ድረስ በአ.አ.ዩ በስኩል ኦር ሜካኒካል አንድ ኢንዱስትሩ የትምህርት ክፍል በተባባሪ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ በመምህርነት እየሰሩ ነው። የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መንግሥቱ አበበ ከዶ/ር ኢ/ር ዳንኤል ቅጣው ጋር በጥራትና በምርታማነት ዙሪያ ያደረገውን ቃለ ምልልስ እነሆ!

ጥራት ወይም ኳሊቲ ምንድነው?
ይህ ጥያቄ በጣም አጭር ነገር ግን በጣም በጣም ሰፊ ምላሽ ያለው ሐሳብ ነው። ጥራት ወይም ኳሊቲ የምንለው ሐሳብ፣ እንደቃል ሳይሆን እንደፍልስፍና የሚታይ ነው። የአዕምሮ መለወጥን የሚጠይቅ፣ ደንበኛን ከደንበኛ የሚያያይዝ፣ ከደንበኛ ፍላጐት ጋር የተገናኘ ነው። የጥራት ትርጉም አሰጣጥ፣ በብዙዎች ዘንድ ስህተት ፈጥሯል። አንዳንድ ጊዜ የሚያብለጨልጭ፣ ከፍተኛ ዋጋ ያለው ወይም ለየት ያለ ነገር፣ …”ኳሊቲ ነው” ሲባል እንሰማለን። ኳሊቲ ክራቫት አስሯል፤ ኳሊቲ ልብስ ለብሷል፣ ኳሊቲ ጫማ አድርጓል… ይባላል። እነዚህ ነገሮች፣ ኳሊቲ የሚባለው ጽንሰ ሐሳብ ውስጥ ሊኖሩ ይችላሉ፤ ነገር ግን የኳሊቲ ፅንሰ ሐሳብ ይህ ብቻ አይደለም።
ጥራት ወይም ኳሊቲ በአጭሩ፣ ደንበኛው የሚፈልገውን አገልግሎትም ሆነ ዕቃ ልክ ደንበኛው እንደሚፈልገው ወይም ከሚፈልገው በተሻለ ሁኔታ፣ ደንበኛው በሚፈልገው ጊዜ፣ በሚፈልገው ብዛት፣ ሊገዛ በሚችለው አቅም ማቅረብ ማለት ነው። ለምሳሌ፣ አንድ ሰው “ከአንድ ግመልና ከአንድ ቮልቮ ከባድ መኪና የቱ ነው ጥራት ያለው?” ተብሎ ቢጠየቅ፣ ለጥራት ባለው ግንዛቤ መሠረት “ቮልቮ ነው” ሊል ይችላል። ግን እንደዚያ አይደለም። በረሃ ውስጥ ከሆነ ቮልቮ ሊሄድ አይችልም፤ ስለዚህ እንደተጠቃሚው ወይም እንደደንበኛው ፍላጐት በረሃ ውስጥ ከሆነ ግመል ጥሩና የተሻለ ስለሚሆን ጥራት አለው ማለት ነው። አውራ ጐዳና ላይ ከሆነ ግን ግመል አይደለም የሚያስፈልገው። ጥራት ያለው ቮልቮ ሊሆን ይችላል። ስለዚህ ጥራት፤ የተጠቃሚውን (የደንበኛውን) ፍላጐት፣ ቦታ፣ አቅም፣ አካባቢ… ያገናዘበ ነው ማለት ነው።
ጥራት ማለት ከደንበኛ ጋር የተያያዘ ነው ብለውናል። ስለዚህ ባገራችን የጥራት ትርጉም በኀብረተሰቡ ውስጥ እንዲሰርፅ ልጆቻችንን፣ ከመዋዕለ ሕፃናት ጀምሮ ደንበኛ ማክበርን ልናስተምራቸው ይገባል። ስለጥራት ከተነሳ፣ የደንበኛ መኖር የግድ ነው። አገልግሎትና ቁስ መቀባበል ብቻ፣ ዕቃ መሸጥና ያለመሸጥ፣ በፋብሪካ ውስጥ ጥሩ ዕቃ ማምረት ወይም ያለማምረት ብቻ አይደለም። እርስ በርስ ስንገናኝ ጀምሮ አንዱ የሌላው ደንበኛ ነው። ሕፃናት ዕቃ ሲነጣጠቁ… ዕቃ የሌለው ልጅ፣ ዕቃ ያለው ልጅ ደንበኛ ነው። “እባክህን፣ ይህን ዕቃህን ልጠቀምበት?” ብሎ እንዲጠይቅ ብናስተምረው ወይም ይህን ፍልስፍና እውስጡ ብናሰርፅ ማክበር እየለመደ ያድጋል። ያደጉ አገሮች ከሚታወቁባቸው ዋና ዋና ነገሮች አንዱ ደንበኛን ማክበር ነው።
በአሜሪካ አንድ ሰው ዕቃ ገዝቶ፣ እቤቱ ከደረሰ በኋላ ዕቃው ባይስማማው፣ ወደገዛበት ሱቅ ተመልሶ “አልፈልገውም፣ መልሼዋለሁ” በማለት ገንዘቡን መቀበል ወይም ሌላ የሚፈልገውን ዕቃ ለውጦ መውሰድ ይችላል። ይኼ አሰራር የመጣው ደንበኛውን ከማክበር ነው። የሠራተኞቹን ደሞዝ የሚከፍለውና ለዚያ ድርጅት መኖር ምክንያቱ ደንበኛው ነው።
ወደ አውሮፓ ስንሄድም ደንበኛ ይከበራል፤ የተሸጠ ዕቃ ይመለሳል። ከአሜሪካኖቹ የተለየ አውሮፓውያኑ ያወጡት ሕግ አለ። “ዕቃውን የገዛህበትን ቲኬት መያዝ አለብህ፤ ዓርማው ወይም ታጉ መኖር አለበት” የሚል ነው። ይሄ ስለኳሊቲ ያላቸው ግንዛቤ ከአሜካውያኑ ያነሰ መሆኑን ያሳያል። ወደ እኛ አገር ስንመጣ ደግሞ፣ ጥሩ ባለሱቅ ከሆነ በትላልቅ ፊደሎች “የተሸጠ ዕቃ አይመለስም” የሚል ጽፎ ፊት ለፊት ይለጥፋል። ይኼ ደንበኛን ካለማክበር የሚመነጭ ነው። ጥራት የተመሠረተበትን ያለማወቅና ያለመረዳት የሚያመጣው ችግር ነው። ስለጥራት፣ ስለደንበኛ አያያዝ ማን አስተማረን? ማንም! ብዙ ጊዜ “ደንበኛ ንጉሥ ነው” እየተባለ ሲነገር እንሰማለን። በየሱቁና በየድርጅቱም ተለጥፎ እናያለን። ግን ደንበኛ አይከበርም። ይህ የሚያሳየው፣ ከቃሉ እንጂ ከጽንሰ ሐሳቡ ጋር እንደማንተዋወቅ ነው። ስለዚህ የአመለካከታችን አወቃቀር መለወጥ አለበት፣ የአስተሳሰብና የአመለካከታችንን ውቅር መለወጥ (የፓራዳይም ሺፍት) ያስፈልገናል።
መንገድ ላይ በመኪና ስሄድ በጣም አዝናለሁ። ብዙ ጊዜ መኪኖች እርስበርስ ተዘጋግተው ይቆማሉ። መዘጋጋቱ የሚፈጠረው መንገዶቹ በመጥበባቸው ወይም ተሽከርካሪዎቹ በመብዛታቸው ብቻ አይደለም። እርስበርስ ስለማንከባበር ነው። የመኪና መንገድ ስንጠቀም፣ አንዳችን የሌላችን ደንበኛ ነን። እኔ ከቀኜ ለሚመጣ መኪና ቅድሚያ የመስጠት ኃላፊነትና ግዴታ አለብኝ። ከጐኔ ያለው አሽከርካሪ ደንበኛዬ ነው፤ እኔ ደግሞ የእሱ ደንበኛ ነኝ። ብንከባበር፣ እሱም ይሄዳል፣ እኔም እሄዳለሁ። ጥቁርና ነጭ በተቀባ የእግረኛ ማቋረጫ (ዜብራ) ላይ የእግረኛ መብት አናከብርም። ባለመኪና አይደለን፣ ጉልበተኞች ነን። እንዲያ መሆን የጥራት ፍልስፍናን ግንዛቤያችን ዝቅተኛ ነው ማለት ነው። ዜብራ ላይ ስደርስ መኪናዬን አቁሜ ለእግረኞች  “እለፉ” የሚል ምልክት ስሰጣቸው በጣም ያመሰግኑኛል። የሚፈልጉትን ነገር ስላደረግሁላቸው ደስ ብሏቸው ነው። አላወቁትም እንጂ መብታቸው እኮ ነው። አብዛኞቻችን ግን ጥራትን ከምርት ጋር ብቻ ነው የምናያይዘው…
ጥራት ስንል፣ በፍፁም ከሸቀጥ (ኮሞዲቲ) ጋር ብቻ የተያያዘ  አይደለም። ለምሳሌ አንድ ሐኪም፣ ታካሚ ደንበኞች አሉት። እነሱ በመኖራቸው ነው ሐኪሙ የሚሰራው። ስለዚህ ደንበኞቹን (ታካሚዎቹን) ተንከባክቦ መያዝ አለበት። እዚህ ላይ አንባቢ እንዲረዳኝ የምፈልገው፣ የሐኪሞችን የሥራ መደራረብና ጫና እንዲሁም የቁጥራቸውን ማነስ፣ ግምት ውስጥ ሳላስገባ አይደለም። ግን መሆን የነበረበትን ነው የምናገረው። ችግሬ ምን እንደሆነ ጠይቆ ሳይረዳና ሳይመረምረኝ፣ ገና በሩን እንደገባሁ፣ አቀርቅሮ ወረቀት እየጻፈ፣ “ምንህን ነው ያመመህ?” በማለት ይጠይቀኛል እንጂ እንደሰውና እንደንበኛው አያየኝም፤ አያስተናግደኝም። ይኼ የጥራት ፍልስፍና ማነስ ስለሆነ ሐኪሞች አዕምሮአቸውን (አመለካከታቸውን) መለወጥ አለባቸው። በሌላውም ዘርፍ እንዲሁ ነው።
እኛ አስተማሪዎች፤ ተማሪዎቻችንን እንዴት ነው የምናየው? ተማሪ ባይኖር እኔ‘ኮ ሥራ የለኝም። ምርምር መሥራት እችላለሁ። ነገር ግን የማስተርስና የዶክትሬት ተማሪዎች ከሌሉ እንዴት ምርምር መሥራት እችላለሁ? አልችልም። ተማሪዎቼ የእኔ ኃላፊዎችና ደንበኞች ስለሆኑ ላከብራቸው ይገባል። ይህ ማለት ግን የማይገባቸውን ውጤት መስጠት፣ በማይሆን ሁኔታ ማባባል፣ ትከሻ ላይ አውጥቶ መሸከም ማለት አይደለም። እንደሰው፣ እንደደንበኛ መታየትና መከበር ይገባቸዋል ማለቴ ነው። ይኼ ነው ጥራት ማለት። ጥራት ከደንበኛ ከተለየ ትርጉም የለምውም ማለት ነው፤ ደንበኛ ሳይኖር ስለ ጥራት ማውራት አንችልም።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ እኮ የሚሠራው(የሚኖረው) እኔና ሌሎች ተሳፋሪዎች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ስንሆንለት ነው። ስለዚህ፣ ተሳፋሪውን በሚገባ መንከባከብና ማስተናገድ አለበት። ሲዘገይ፣ “ይቅርታ ዘግይተናል፤ ለዚህ ጥፋታችንም ማካካሻ እናደርጋለን” በማለት የደንበኞቹን ቅሬታ ማስወገድ አለበት። አስተማሪም ሲያረፍድ፤ “ይቅርታ እንዲህ ዓይነት ችግር አጋጥሞኝ ነው” ብሎ ትክክለኛውን ምክንያት በመንገር፣ ተማሪዎቹን ይቅርታ መጠየቅ አለበት። ምክንያቱም አስተማሪውንና ተማሪውን የሚያገናኘው ኮርሱ ወይም ትምህርቱ ነው። ለምሳሌ ነገ ለተማሪዎቼ የጥራት ኮርስ አስተምራለሁ። ኮርሱ፣ ለእኔ ምርቴ ነው። እሱን ነው የምሸጥላቸው። ኮርሱን ካልገዙኝ ወይም “ዳንኤል የተባለው አስተማሪ ሁለተኛ ክፍላችን እንዳይገባ” ብለው ከከለከሉኝ፣ ሥራዬን አጣለሁ ማለት ነው። ስለዚህ ደስ ብሏቸው ኮርሱን እንዲገዙኝ መትጋት አለብኝ። ነገር ግን ዲግሪውን ስለሚፈልጉት በማስፈራራት ወይም “ምን ታመጣላችሁ!” በሚል ስሜት ኮርሱን መስጠት የለብኝም። እንዲህ ያለው አሠራር ከጥራት ፍልስፍና ውጭ ነው።
ለመሆኑ ጥራት በምን ይለካል?
ጥራት በደንበኛው እርካታ ነው የሚለካው። የመንገድ ጥራት፣ የልብስ ጥራት ወይም የምርትና የአገልግሎት ጥራት ስንል ደንበኛው ባዘዘውና በጠየቀው መመሪያ ነው ወይ የተሠራለት? ብለን መፈተሽ እንችላለን። ለምሳሌ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን፣ መንገድ የሚሠሩለትን ኮንትራክተሮች ጋብዞ ያወዳድራል። ደንበኛው የመንገዶች ባለሥልጣን ነው። እኛ ደግሞ ከእኛ በተሰበሰበ ታክስ መንገዱ ስለሚሠራና ተጠቃሚዎች ስለሆንን ተጨማሪ ደንበኞች ነን። ባለሥልጣን መ/ቤቱ እንዲሠራለት የሚፈልገውን ዓይነት መንገድ ዝርዝር መመሪያ (ስፔሲፊኬሽን) ያቀርባል። የሚሠራው መንገድ ሳይበላሽ ለ10 ዓመት የሚያገለግል፣ ወጣ ገባ የሌለው፤ 8፣ 12፣ 14፣ …ሜትር ስፋት ያለው፣ በሁለቱም ጐን ውሃ ወደ ውጭ የሚያፈስ የመንገድ ትከሻ ያለው፣ መንገዱ ተሠርቶ ሲያልቅ፣ ቁልቁለት ወይም መጠምዘዣ መኖሩን የሚጠቁም ምልክት ያለው፣ የጥገናው ወጪ አነስተኛ የሆነ… ብሎ ፍላጐቱን በመግለጽ አወዳድሮ ኮንትራቱን ለአሸናፊው ድርጅት ይሰጣል።
እንግዲህ ጥራት የምንለው ደንበኛው በፈለገው ዝርዝር መመሪያ መሠረት መሠራቱን ነው። አንዳንድ ጊዜ ደንበኛው ፍላጐቱን በትክክል ያስቀምጣል። አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ያሰበውንና የፈለገውን ነገር በትክክል ላይገልጽ ይችላል። ስለዚህ ጥራት ማለት የተገለፀውንና ያልተገለፀውን የደንበኛውን ፍላጐት ጭምር ማርካት ማለት ነው። በዚህ ነው ጥራት የሚለካው።
የጥራት መለኪያና መመዘኛ የሚባሉ አውታሮች (ዳይመንሽኖች) አሉ። ለምሳሌ፣ ይኼ ከዚህኛው ይበልጣል ወይም ይሻላል ለማለት ተመሳሳይ ይዘት ያላቸውን ነገሮች ነው የምናወዳድረው። ፈረስን ከፈረስ እንጂ ከበግ ጋር አናወዳድርም። እንዲህ በምናደርግበት ጊዜ ሲስተሙን ኳሊቲ ዳይመንሽን እንለዋለን። አንደኛው የጥራት መለኪያ ፋንኪሽናሊቲ፣ የምንፈልገውን ነገር ይሠራል ወይ የሚለው ነው። ሁለተኛው ፐርፎርማንስ፣ የመሥራት አቅምና ብቃቱ ነው። ለምሳሌ አንድ የልብስ ስፌት መኪና 8 ሰዓት ይሠራል ከተባለ፣ በተከታታይ ለ8 ሰዓት ያለ አንዳች እክል ይሠራል ወይ? ማለት ነው።
ሌላው ሪያሊቢሊቲ (አስተማማኝነት) ነው። ጥገና አስፈላጊ ነገር ቢሆንም፣ በአዲስነቱ ምን ያህል ጊዜ ሳይበላሽ በአስተማማኝነት ይሠራል? ወይም በመጀመሪያውና በሁለተኛው ጥገና መካከል ባለው ጊዜ በአስተማማኝነት ይሠራል? የሚለው ነው። ሌላው የጥራት መመዘኛ ደግሞ ኮንፎርሚቲ የምንለው ነው። ሌላው ደግሞ ዱረቢሊቲ ነው። ዱረቢሊቲ ስንል ጥንካሬውን ማለታችን ነው። ለረዥም ጊዜ ምንም ሳይሆን ይሠራል? ሰርቪስ ላደርገው ወይም ቢበላሽ ላሠራው እችላለሁ? የሚለው ነው።
ማማርም አንዱ የጥራት መለኪያ ነው። አንዱ፣ ይህን ነገር እወደዋለሁ ይላል። ለምን ወይም በምን ወደድከው? ሲባል ምክንያት የለውም። “በቃ እወደዋለሁ” ነው መልሱ። ሌላው ደግሞ ብዙዎቹን የጥራት መመዘኛዎች ቢያሟላም “ይህን ነገር አልወደውም” ሊል ይችላል። የሚጠላበትን ምክንያት ግን አያውቀውም። እንግዲህ በእነዚህ መመዘኛዎች ለክተን ነው አንድን ነገር ከፍተኛ ጥራት ያለው ወይም ጥራቱ ዝቅተኛ ነው ማለት የምንችለው። ጥራት ምንድነው? ስትለኝ ጥያቄው ቀላል መልሱ ግን ሰፊ ነው ያልኩህ ለዚህ ነው። እኛ ስለጥራት (ኳሊቲ) ሁለት ኮርስ ነው የምንሰጠው። በ15 እና 20 ደቂቃ ስለጥራት አውርተን አንጨርስም። ታዋቂው የዓለማችን ሳይንቲስት አልበርት አነስታይን፤ “አንድን ነገር በቀላሉ ለመንገደኛ ሰው ማስረዳት ካልቻልክ ሥራህን አታውቀውም ማለት ነው” እንዳለው እንዳይሆንብኝ እፈራለሁ።
ህብረተሰቡ ስለጥራት ያለው ግንዛቤ ምን ይመስላል?
ኅብረተሰብ የሚለዋወጥ (ዳይናሚክ) ስለሆነ ብዙ ጊዜ ይቀያየራል። ከባላገር ልነሳ፤ የጥራት ፅንሰ ሐሳብ (ኮንሰፕት) አላቸው ወይ? አዎ! በሚገባ አላቸው። ቤታቸው ንፁህ ነው፤ የተቀደደ ልብስ በመርፌ ጥርቅም አድርገው ሰፍተው ነው የሚለብሱት፤ ቤታቸውን አዛባ ለቅልቀው ነው የሚኖሩት። መደብ አለች፣ ጓሳ ትነሰነሳለች፤ በሳምንቱ ተጠርጐ ይስተካከላል፤ አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ ያደርጋሉ። ጥራት (ኳሊቲ) ፎቅ ቤት ውስጥ መኖር ማለት አይደለም። ከብቶቻቸውን ጧት በጊዜ ያስወጣሉ፤ ማታ በጊዜ ያስገባሉ። እሳታቸውን በጊዜ ያዳፍናሉ፤ ጧት ደግሞ በጊዜ ተነስተው ያነዳሉ። እነዚህን ባለሙያ እንላቸዋለን። በባላገር ሚስት ስትመርጥ፣ በጧት ጭስ ከሚጨስበት ቤት ምረጥ ነው የምትባለው። እናቲቱ ባለሙያ ከሆነች ልጅቱም ባለሙያ ትሆናለች ነው ሃሳቡ። ባላገር ውስጥ የጥራት ፅንሰ ሐሳብና አመለካከት (ኮንሰፕት) አለ። ይህ አመለካከት ግን ማደግ አለበት።
ከተማ ውስጥስ እንዴት ነው? ከተማ ውስጥ የጥራት ፅንሰ ሐሳብ በጣም ትንሽ ነው። ሁሉም ሰው የጥራት ፅንሰ ሐሳቡን መንግሥት ላይ ጥሎታል። ደጁ ላይ ቆሻሻ እያየ መንግሥት ይጥረገው ብሎ ያልፋል። አጠገቡ ያለ ቦይ ተደፍኖ እያየ “የመንግሥት ሠራተኞች ይጥረጉት” ብሎ ይሄዳል። ከቤቱ ጠርጐ ያወጣውን ቆሻሻ ፊት ለፊቱ ባለ ቦይ ውስጥ ይጥላል፤ ውሃ የጠጣበትን መያዣ የትም ይወረውራል። ኧረ ብዙ ጉድለት ይታያል። መሠራት ያለበት ነገር አልተሠራም።
ጥራት የሚቆምባቸው ሁለት ምሰሶዎች አሉ። አንደኛው መሠረታዊ ሐሳብ “Keep and try the first time and every time”  ይላል። አንድን ሥራ ከመጀመሪያ አንስቶ በትክክል መሥራት የሚል ነው መሠረተ ሐሳቡ። ለስህተት ምንም ዕድል ያለመስጠት። “ቆይ በኋላ አስተካክላለሁ” ማለት በፍፁም አይገባም። ሁለተኛው የጥራት መሠረተ ሐሳብ፣ “There is always a way for improvement” የሚል ነው። ለመሻሻል ሁልጊዜ ዕድል አለ ማለት ነው። ዛሬ ከምሠራው ሥራ፣ ነገ የምሠራው የተሻለ መሆን አለበት። እነዚህ መሠረታዊ ሐሳቦች ሲጣመሩ፣ አንደኛ ጠንቃቆች እንሆናለን፤ ጊዜም ሳናባክን እንሠራለን።
ለምሳሌ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በታሪኩ የቴክኒክ ችግር ገጥሞት አያውቅም፤ የምንኮራበት አየር መንገድ ነው። ነገር ግን ብዙ ጊዜ በመዘግየት ይታማል። መዘግየት አለ ማለት ነው። ለምንድነው የሚዘገየው? ብለን ስንጠይቅ They do it the second time ማለት ነው። በመጀመሪያው ጊዜ በትክክል ሠርተውት ቢሆን ኖሮ መዘግየት አይፈጠርም ነበር። መጀመሪያ ቴክኒሻኑ ይሠራል፣ ከዚያም ተቆጣጣሪው ይመጣና “ይኼ ትክክል አይደለም” ይላል። ቴክኒሻኑ “ኦ ለካስ ይህቺ አልተስተካከለችም” ይልና ያስተካክላል። ስለዚህ በመጀመሪያውና በሁለተኛው ማስተካከል መኻል ያለው ጊዜ መዘግየትን ይፈጥራል። መዘግየት ደግሞ ጥራትን ያስተጓጉላል።
ሁለተኛው ምሰሶ ለመሻሻል ዕድል መስጠት ነው። ይህም ሁልጊዜ ከሌላው መማር እንደሚችልና እንደሚሻሻል የሚያሳይ ነው። ከአንተ ጋር ስንነጋገርና “ይህ ሰው በዚህ ጉዳይ ላይ የተሻለ ሐሳብ ሊኖረው ይችላል” ብዬ ማሰብ ስጀምር፣ አከብርሃለሁ። ደንበኛዬ ነህና ካንተ እውቀት እወስዳለሁ። ዛሬ ከአንተ ጋር ስለዋልኩ እውቀት አግኝቼ እሄዳለሁ ማለት ነው። እነዚህ ሁለቱ የጥራት ዋነኛ መሠረተ ሐሳቦች፣ ምሰሶዎች (ፒላርስ) ናቸው።
እነዚህ የጥራት ምሰሶዎች በአገራችን አሉ? ከተባለ፣ የሉም ማለት ይከብዳል። አሉ፣ ግን በጣም በጥቂቱ ነው ያሉት። በሥራዬ አጋጣሚ ብዙ አገሮች ዞሬአለሁ። በአሜሪካና በአውሮፓ የትም አገር ሽንት ቤት ውስጥ “ከተጠቀማችሁ በኋላ ውሃ ልቀቁ” የሚል ጽሑፍ አይቼ አላውቅም። ወደ አገራችን ስንመጣ ግን “ትልቅ” የተባለ ሆቴል ውስጥ ይሄ ማሳሰቢያ ተጽፎ ይታያል። ምን ማለት ነው? እኔ ሽንት ቤቱን ከተጠቀምኩ በኋላ ቀጥሎ የሚመጣ ሰው ደንበኛዬ ነው። እኔ ሽንት ቤቱን በምጠብቅበት ሁኔታ እሱም እንደሚጠብቅ አውቄ እሱን ማክበር አለብኝ። በምዕራብ አገሮች ይህ ስለገባቸው በት/ቤት መፀዳጃ ቤቶች ውስጥ እንኳ አይጻፍም። እኛ አገር ለምን ይጻፋል? ለጥራት ያለን ግንዛቤ ዝቅተኛ ስለሆነ  ነው። ይህን ይህን ሳይ “ምን ይሻላል?” የሚለው ብዙ ጊዜ ያሳስበኛል። አዲሱ ትውልድ ስለጥራት ያለው ግንዛቤ እንዲያድግ ካስፈለገ ያለን አስተሳሰብ ሙሉ በሙሉ መለወጥ አለበት።
ለምሳሌ እኔና አንተ ደንበኞች ነን። እኔ አንተን ለማስደሰት፣ እኔ እሱን ብሆን ኖሮ እንዴት እንዲሆንልኝ እፈልጋለሁ? ሰዓት እንዲያከበርልኝ እፈልጋለሁ። ጥያቄዬ ሁሉ በቅንነት እንዲመለስልኝ እፈልጋለሁ… በማለት ማሰብ አለብኝ። ይህን ካደረግሁ አንተ ደስ ይልሃል። በሁሉም ቦታ ደንበኞቻችንን ማስደሰት ስንፈልግ፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ “እናንተ እንዲደረግላችሁ የምትፈልጉትን እናንተም አድርጉላቸው” የሚለውን ማሰብ ያስፈልጋል። ይሄ አባባል የጥራት ዋነኛ መመሪያ ነው። ይሄንን መመሪያ መተግበር ወሳኝ ነው። እንግዲህ የጥራት ፅንሰ-ሃሳብ እንዲተገበር ከታች ከጽዳት ሠራተኛው እስከ ላይኛው ባለሥልጣን ድረስ የልቡና ውቅር (ስትራክቸር)፣ የአስተሳሰብና የአመለካከት ለውጥ (የፓራዳይም ሺፍት) መደረግ አለበት።
ለጥራት ያለ የአመለካከት ለውጥ (ፓራዳይም ሺፍት) እንዴት ነው የሚመጣው?
እንደ ዕንቁላልና ዶሮዋ የተሳሰረ ነው፤ ጥራትና ምርታማነት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ናቸው። ጥራት ከሌለ ተወዳዳሪነትና ዕድገት የለም። በመጀመሪያ በኅብረተሰቡ ውስጥ ግንዛቤ መፍጠር ያስፈልጋል። ሰው ሁሉ እንዲያውቀው ማድረግ የግድ ነው። ጋዜጦች፣ ቴሌቪዥኖች፣ ሬዲዮኖች፣ በአጠቃላይ ሚዲያው፣ የጥራት ሐሳብ በኅብረተሰቡ ውስጥ በሚገባ እንዲሰርጽ በብዛት መሥራት አለባቸው። እኔ እግር ኳስ በጣም ስለምወድ በየሬዲዮ ጣቢያው ስለኳስ ሲያወሩ በጣም ደስ ይለኛል። ነገር ግን ለስፖርቱ የተሰጠው ጊዜ ግማሽ ያህል እንኳ የጥራትን መሠረተ ሐሳብ ለማስረፅ ቢውል አገሪቷ የት በደረሰች።
መጀመሪያ ግንዛቤ መፍጠር ነው፤ ቀጥሎ እርምጃ መውሰድ። ሰው ግንዛቤ ካገኘ በኋላ እያንዳንዱ ግለሰብ መለወጥ አለበት። በሶስተኛ ደረጃ ራሱን እያሻሸለ ሳለ መታገል አለበት። ለምሳሌ ታክሲ ውስጥ ተደራርባችሁ ተቀመጡ ሲባል ትክክል ስላልሆነ መቃወም አለበት። “ፋዘር ወይም ማዘር ጠጋ በሉ” ማለት ከጥራት መሠረተ ሐሳብ ጋር አይሄድም። ስለዚህ መቃወም አለበት። በየትም ቦታ ቢሆን እያንዳንዱ ግለሰብ ትክክል ያልሆነ ነገር ሲያይ ዝም ማለት የለበትም። ህብረተሰቡ መምራት አለበት። ይህንን ለማድረግ ደግሞ ግንዛቤው መዳበር አለበት። ትያትረኞች ጸሐፊዎች፣ ገጣሚዎች፣ አርቲስቶች፣ …. ጥራት ላይ መሥራት አለባቸው። ትያትር በህብረተሰቡ ውስጥ የበለጠ ተፅዕኖ መፍጠር የሚችለው በጥራት ላይ ሲሰራ ነው። ስለ ጥራት ማስተማርያ የአየር ሰዓት መኖር አለበት። ስለ ጥራት ካስተማርን በኋላ እርምጃ መውሰድና ሮል ሞዴሎች (አርአያዎች) መፍጠር አለብን።
ለምሳሌ አበበ ቢቂላን ብንወስድ በሩጫ ጥሩ ሮል ሞዴል ነው። ግን ለቢዝነሱ ጥሩ ሞዴል አይደለም። ከአበበ በኋላ ኃይሌ ገ/ሥላሴ መጣ። ኃይሌ ጥሩ የቢዝነስ ሞዴል ስለሆነ ከእሱ በኋላ የመጡት በሆቴልና በሌላ የቢዝነስ ዘርፍ ተሰማሩ። በጥራትም ሮል ሞዴሎች ስለሚያስፈልጉን መሸለምና ማበረታታት ያስፈልገናል። ለዚህ ደግም የሽልማት ድርጅት ያስፈልገናል። ይህ ነገር በህብረተሰቡ ውስጥ ሲደጋገም ባህል ይሆናል። ይህቺ አገር ምን ያሳድጋታል ብትለኝ፣ ጥራትና ምርታማነትን ማሳደግ…  ነው የምለው።
በዚህ ረገድ አዲሱ ትውልድ (ወጣት፣ ሕፃናት፣ ሴቶች) ላይ መሠራት አለበት።  ለሴቶች ቦታና ዋጋ መስጠት ይገባል። በት/ቤቶች ደግሞ አሁን ያሉት መምህራን ከጥራት ግንዛቤ ውጭ ስለሆኑ፣ የአሰልጣኞች ስልጠና ፕሮግራም ያስፈልጋል። የትምህርት ካሪኩለሙም መቀየር (የፓራዳይም ሺፍት ማድረግ) ይኖርበታል። የሽምደዳ ካሪኩለም መቀየር አለበት።
ልጆች፣ ተፈጥሮን ወደዋትና ተንከባክበው እንዲይዟት ማበረታታት ያስፈልጋል። እፅዋት ከተንከባከቡ በውስጡ ለሚኖሩት ነፍሳት አክብሮት ይሰጣሉ። ተፈጥሮን የሚወዱ፣ ደንበኞቻቸውን የሚያከብሩና የሚደራደሩ ወጣቶችን ማፍራት አለብን። መደራደር ስል እናቶችን ማስተማር ያለብን አንድ ነገር አለ። ልጆቻቸው እንዲያጠኑ ሲፈልጉ፤ “አጥኑ፤ ያለበለዚያ ትመታላችሁ” አይደለም ማለት ያለባቸው።
እናት፤ “አጥኑ፣ ካላጠናችሁ ቴሌቪዥን አይከፈትም”
ልጆች፤ “ስንት ቀን ነው የምናጠናው?”
እናት “በሳምንት ስድስት ቀን”
ልጆች “አራት ቀን”
እናት፤ “የለም! አምስት ቀን”… እየተባባሉ መደራደርን መልመድ አለባቸው። ከልጅነታቸው ጀምሮ መደራደር ካላስተማርናቸው አድገው የፓርቲ መሪ ሲሆኑ አይደራደሩም። “ወይ እሞታለሁ፤ ወይ እገለብጣለሁ” ነው የሚሉት። የጥራት ጉዳይ ይህን ያህል ጥልቅ እንደሆነ አንባብያን እንዲረዱልኝ እፈልጋለሁ።
በአገራችን የሚታየውን የምርትም ሆነ የአገልግሎት ጥራት ማነስ እንዴት ይገልጹታል?
 በእኛ አገር አብዛኛውን ጊዜ ሰራተኛው ችሎታ የለውም ሲባል እንሰማለን። ነገር ግን ከ80 እስከ 90 በመቶ የጥራትና የምርታማነት ችግር ሲስተሙ (አሰራሩ ላይ) ነው። ስለዚህ ሲስተሙ መለወጥ አለበት። ሲስተሙ ትክክል ሲሆን ሠራተኛው ትክክል ይሆናል። ለምሳሌ፣ ውልና ማስረጃን ያየን እንደሆነ ሰራተኞቹ አልተቀየሩም። ወይም ፈረንጅ አልመጣም። ሲስተሙ ስለተስተካከለላቸው፣ ሁለት ቀን የሚፈጀውን ሥራ በ30 ደቂቃ ይሠሩታል። ነገር ግን ሲስተሙ ተስተካክሎ ብቻ መቆም የለበትም። ልምድና ባህል መሆን አለበት። አንድ ሰው ቆሞ እንዲህ አድርግ፣ አታድርግ ማለት የለበትም። ያለበለዚያ ወደ ኋላ ይመለሳል።
ፋብሪካዎችም የሲስተም ችግር አለባቸው። እሱንም ማስተካከል ያስፈልጋል። ከዚህ ጋር ሌላው አስፈላጊ ነገር ስልጠና ነው። በተለይ ስለ ጥራትና ምርታማነት ስናወራ ከስልጠና ውጭ ሊሆን አይችልም። የስልጠና ክፍለ ጊዜ ያላቸው ድርጅቶች ስንት ናቸው? ስንል በጣም ጥቂት ናቸው። አቶ ታዲዮስ ሐረገወርቅ ምክትል ሚኒስትር ከነበሩበት ጊዜ ጀምሮ ዩኒቨርሲቲዬን እየወከልኩ በስልጠና ጉዳይ ስለምሰራ ብዙ ድርጅቶችን አይቻለሁ። አብዛኞቹ የስልጠና ክፍለጊዜ የላቸውም። ምናልባት አንድ ሰው “የሥልጠና ኃላፊ” ተብሎ ሊቀመጥ ይችላል። ነገር ግን ጥራት ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎች ሲወጡ፣ የሥልጠና ክፍል ኖሯቸው መመሪያ አዘጋጅተው፣ ቤተመጻሕፍት አስቀምጠው ሰራተኞቻቸውን የሚያሰለጥኑ ድርጅቶች ጥቂት ናቸው። ቴሌ፣ አየር መንገድ፣ አውራ ጎዳና፣ ከክልሎችም እንዲሁ… ይኼ ምንድነው የሚያሳየው? የጥራት ፍልስፍና ፅንሰ ሐሳብ አልገባንም ማለት ነው። ሥልጠናን ሲስተማችን ውስጥ አላስገባንም።
ማነው ሲስተሙን መቀየር ያለበት?
የሚገርመው ነገር የግሉ ዘርፍ ነበር ቢፒአር የተባለውን የለውጥ ሂደት መምራት የነበረበት። ቢፒአር አተገባበሩ ትክክል ከሆነ መሰረታዊ አሰራሩ ጥሩ ነው፤ አምንበታለሁ። ይህ የለውጥ ሐሳብ ከግሉ ዘርፍ መምጣት ነበረበት። ነገር ግን መንግሥት ቀደመው። ለምን? ቢባል፣ በታዳጊ አገር ያለው የግሉ ዘርፍ ዕድሜ ጨቅላ ስለሆነና ስላልጎለበተ ነው። ስለዚህ ኃላፊነቱን መንግሥት ወሰደ። መንግሥት ይህን ኃላፊነት ሲወስድ ግን ሁሉንም እኔ መስራት አለብኝ ማለት የለበትም። ይህን የሚሰሩ የግል ዘርፎችን አደራጅቶ እየሰሩ ከስህተታቸው እንዲማሩ መልቀቅ ያለበት ይመስለኛል። እርግጠኛ ያልሆንኩት በምርምርና በዳታ የተደገፈ መረጃ ስለሌለኝ ነው።
የጥራት ፍልስፍናን መሠረተ ሐሳብ ተግባራዊ በማድረግ የተለወጠና ለአብነት የምንጠቅሰው አገር አለ?
አዎ! ለምሳሌ ሲንጋፖርን መጥቀስ እንችላለን። ሲንጋፖር እ.ኤ.አ በ1966 ነው ከቅኝ ግዛት ነፃ የወጣችው። 50 ዓመት እንኳ አልሞላትም። ከዚያን ጊዜ አንስቶ እስከ 1980 ድረስ ሲስተም እያስተካከሉ ቆዩ። ከዚያም ሊ ኳን የተባለ ጠቅላይ ሚኒስትራቸው “ምርታማነት የአዕምሮ መቀየር ነው። ከአሁን ጀምሮ በዚህ አቅጣጫ ነው የምንሄደው” በማለት አወጀ። ይህን የለውጥ ሂደት የሚመራ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የሚመራ ኮሚቴ አቋቋመ።
ለአምስት ዓመት የህብረተሰቡን የምርታማነትና የጥራት ግንዛቤ ሲያሳድጉ ቆዩ። ቴሌቪዥኑ፣ ሬዲዮው፣ ጋዜጣው፣ መጽሔቱ፣ ዘፈኑ… በየመንገዱ ላይ የሚሰቀሉትና በየግድግዳው የሚለጠፉት ፖስተሮች፣ .. ሁሉ የቆየ አመለካከት መለወጥና አዲሱን የለውጥና የዕድገት ትሩፋቶች ማስተማር ነበር ሥራቸው። ከዚህ በኋላ ወደ ተግባር እርምጃ ገቡና የለውጥ ሂደቱን የሚመሩ የተለያዩ ተቋማትን አቋቋሙ። በዚህ ዓይነት ሲሰሩ ቆይተው የሕዝባቸውን አዕምሮ ቀየሩት። ከ20 ዓመት በኋላ እ.ኤ.አ በ2000 ዓ.ም 12 መመዘኛዎች ባሉት ግሎባል ፕሮዳክቲቪቲ ኢንዴክስ በተባለው የምርታማነት መለኪያ ከዓለም አገራት ጋር ተወዳድረው 3ኛ ወጡ። ከዚያ በኋላ ደግሞ ለውጥ ያገኙበትን አሰራር (ሲስተም) የራሳቸው አደረጉት።  የህልውናቸው አካልና መገለጫ ሆነ። በመቀጠል ደግሞ የራሳቸው ባደረጉት ሲስተም አዲስ ነገር ወደ መፍጠር (ኢኖቬሽን) ገቡ።
በሲንጋፖር አንድ ቢሮ አንኳኩተህ የምትፈልገውን ስትጠይቅ፣ የተቀበለህ ሰው ጉዳዩ የማይመለከተው ከሆነ፣ የሚመለከተው ጋ ይወስድሃል ወይም ወደሚመለከተው ሰው ጋ ወደሚወስድህ ሰው ያደርስሃል እንጂ “አይ! እኔ አላውቅም” አይልህም። የአገር ጉዳይ ነዋ! የታክሲ ሹፌሩ ከአየር ማረፊያ ወደምታርፍበት ሆቴል ሲወስድህ፣ ስለአገሩ እያወራልህ ነው። “ይህ ቦታ በፊት እንዲህ ነበር፤ እኛ ነን እንዲህ ያሳመርነውና የለወጥነው። ይህ ደግሞ …” እያለ በማውራት ሆቴል ያደርስሃል። እሱ ምን ሰራ? ብትል በሙያው በአቅሙ “ይህ የመንግሥት ሳይሆን የእኔ ጉዳይ ነው” በማለት በዜግነቱ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ተወጥቶ ይሆናል። ይኼ ነው የምርታማነት ፅንሰ ሀሳብ።  የሚገርመው ነገር እንደ እኛው ኋላቀር የነበረችው ሲንጋፖር እዚህ “ተአምራዊ” የሚመስል ፈጣን ዕድገት ላይ የደረሰችው በ48 ዓመት ነው።    
ድሮ የጃፓን ምርት ጥራት እንደሌለው ለመግለጽ፣ “ኪሽ ኪሽ የጃፓን ዕቃ ወድቆ የማይነሳ” ወይም “አወይ ሞሶሎኒ አወይ ሞሶሎኒ ተሰባብረህ ቀረህ እንደ ጃፓን ሶኒ” ይባል ነበር። አሁን ግን ጃፓን የዓለምን ኢኮኖሚ ከሚመሩት ቀዳሚ አገራት አንዷ ነች። እንዴት ለዚህ በቃች?
ጃፓንም እንደ ሲንጋፖር ምሳሌ የምትሆን አገር ናት። እንደተባለው ምርቷ ጥራት የሌለው ነበር። ከ2ኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ---------- የተባሉ አሜሪካውያን በአገራቸው ስለጥራትና ስለምርታማነት ጮኸው ጮኸው የሚሰማቸው ቢያጡ፣ ወደ ጃፓን ሄዱ። እዚያም 150 ሥራ አስኪያጆችን ሰብስበው ስለጥራትና ምርታማነት አወሯቸው። “አሁን የነገርናችሁን ተግባራዊ ካደረጋችሁ በአምስት ዓመት ውስጥ ለውጥ ታመጣላችሁ” አሏቸው። እነዚያ ሥራ አስኪያጆች ጠንክረው በመስራታቸው በአምስት ዓመት ሳይሆን በሦስት ዓመት ለውጥ አመጡ። እነጃፓንንና ሲንጋፖርን ከቀየረ፣ የእኛንም አገር ይቀይራል ማለት ነው።
ወደዚያ የሚወስደው ጉዞ ተጀምሯል?
ጥሩ ተስፋ ሰጪ ጅምሮች አሉ። ካይዘን በጣም ጥሩ ጅምር ነው። እንዲህ ዓይነት ጅምሮችን ማነቃቃትና ማበረታታት፣ ከፍ እንዲሉና እንዲልቁ ማገዝ፤ ሰራተኞቹ ደግሞ በፍፁም የተለወጡ እንዲሆኑ በየጊዜው ሥልጠና፣ እውቅና፣ አክብሮትና ሽልማት መስጠት ያስፈልጋል።