Administrator

Administrator

Saturday, 22 February 2014 13:19

ወግ

“አንድ ደራሲ በመግቢያው ስለ ጠቅላላ መፅሀፉ ይዘት ሲያብራራ ታላቅ ድግስ አዘጋጅቶ መግቢያ በሩ ላይ በመቆም ውስጥ ስለተዘጋጀው ምግብ ጣፋጭነት እየመሰከረ ወደ ብፌው አቅጣጫ እንደሚመራ ጋባዥ መሆኑ ነው፡፡
ደራሲውም ሆነ ጋባዡ መግቢያው ላይ ቆመው በአንድ አይነት ዜማ ታዳሚው ስለ ድግሱ በቂ ግንዛቤ ኖሮት እንዲገባ በማስረዳት ይደክማሉ፡፡ ይሄን ድግስ ለማዘጋጀት ስለ ተደከመው ድካም፣ በውጤቱም ስለተዘጋጁት አይነቶችም ያብራራሉ።
በውስጥ ስለተደገሰው ድግስ በራፍ ላይ ሆኖ የማብራራት አስፈላጊነት ወይም አላማ የታዳሚውን የመብላት ፍላጎት ማናር /አፒታይዘር/ ጭምር ሳይሆን አይቀርም፡፡ በእኔ እምነት ይህ ተግባር ተጋባዡን ጉጉ ያደርገዋል፡፡
በዚህ መፅሃፍ ውስጥ ስለተካተቱት ታሪኮች ይዘት ማውራት ካለብኝ ከአትኩሮታቸው በመነሳት እጀምራለሁ፡፡ በአንድ የማህበረሰብ ስብስብ ውስጥ (ሀገር ሊሆን ይችላል) ወሳኝ ሚና ስላላቸው፣ የየነዋሪውም ዋነኛ ግዱ ስለሆኑት ማለትም … ሀይማኖት፣ ፖለቲካና ማህበረ-ባህላዊ እሳቤ ለመዳሰስ ሞክሬያለሁ፡፡”  
ርዕስ - ሕዝብ እና ነፃነት
ደራሲ - ሚካኤል ዲኖ
ዋጋ - 44 ብር

Saturday, 22 February 2014 13:17

ሰሞኑን የወጡ መፃህፍት

ግጥም
“የሰረቀ ሌባ
በካቴና ታስሮ
በፖሊስ ተይዞ
ሲሄድ ወደ ጣቢያ
መንገድ ላይ ያይሃል
ሊሰርቅ የሚሄደው
ዕልፍ-አዕላፍ
ሌባ፡፡”
ርዕስ -
ሲጠይቁ መኖር
(የግጥም ስብሰባ)   
ደራሲ - ደረጀ ምንላርግህ
ዋጋ - 34ብር
ህትመት - አንድነት ፕሪንተርስ

        ከተመሰረተ ስልሳ አምስት አመቱን ያስቆጠረው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ አለምአቀፋዊ ተቋምነቱ እና የብዙዎችን ይሁንታ ያገኘበት ሀላፊነቱ በተግባር በሚያከናውነው ስራ አንፃር ሲመዘን ጥያቄ ላይ የወደቀ ድርጅት ነው፡፡ አሁን በሀላፊነት ላይ ያሉት የመንግስታቱ ድርጅት ዋና ፀሀፊ ባን ኪ ሙን የመንግስታቱን ድርጅት የመለወጥ ሀሳብ በተደጋጋሚ ያነሳሉ፡፡ ነገር ግን፣ ድርጅቱን በዋና ፀሀፊነት ካገለገሉ ስምንት ሰዎች ውስጥ አንዱ ብቻ ናቸው ስለ ለውጥ ምንም ተናግረው የማያውቁት፡፡ የተወሰኑ ለውጦች በተለያዩ ጊዜዎች የተደረጉ ቢሆንም፣ በዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ግን ምንም አይነት ለውጥ አለመደረጉ ጥያቄዎቹ ከጊዜ ወደ ጊዜ እንዲበረቱ አድርጓል፡፡
በድርጅቱ ላይ የሚነሱ ጥያቄዎች የአባል አገሮቹን ያህል የበዛ እና የተወሳሰበ ቢሆንም፣ በማሻሻያዎቹ ላይ ጥናት ያደረገው ዛክ ቱከር፣ ጥያቄዎቹን በሶስት ዋና ዋና ምድቦች ይከፍላቸዋል። አንደኛው ጥያቄ፡- በመንግስታቱ ድርጅት ውስጥ እንደ ባህል የተያዘውና እንደ አሰራር እየተከተለ ያለው መንገድ፣ ውሁዳን ሊሂቃንን ያካተተው የአባል አገሮች ቡድን የመንግስታቱን ድርጅትም ሆነ የአለም ፖለቲካ አድራጊ እና ፈጣሪ የሚያደርጋቸው ነው፡፡ ሁለተኛው ጥያቄ የሚያተኩረው ደግሞ፡- በመንግስታቱ ድርጅት እንደ አንድ ግብ የተቆጠረው ግሎባላይዜሽን በአባል አገሮች ሉኣላዊነት ላይ እየጋረጠ ያለው ስጋት ላይ ነው፡፡ ድርጅቱ ግጭቶችን በመከላከልም ሆነ ሰብአዊ ቀውስ በሚፈጠርበት ጊዜ ሰብአዊ አገልግሎቶችን በብቃት አይወጣም የሚለው ሶስተኛው ጥያቄ ነው፡፡
በለውጡ ላይ የድርጅቱ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ምክር ቤት ትልቅ ቦታ ሊሰጠው ይገባል። በድርጅቱ ቻርተር መሰረት የምክር ቤቱ ሚና ወደ ጥናት እና አማካሪነት ያተኮረ ነው፡፡ ነገር ግን፤ በሚሰራበት የምርምር፣ የባህል፣ የትምህርት፣ የጤና እና ተያያዥ ዘርፎች ላይ ልክ እንደ ፀጥታው ምክር ቤት  በድርጅቱ ስም ውሳኔ ማስተላለፍ የሚችልበት አቅም ሊሰጠውም ይገባል፡፡ ይህ መደረጉ ደግሞ በድርጅቱ ውሳኔ ላይ የብዙሃን ድምፅ እንዲካተት እና በተለይ በአሁኑ ወቅት ክፍተት ያለበት ከሰብአዊ ድጋፎች ጋር የተያያዙ ስራዎች ምላሽ እንዲያገኙ ያስችላል ይላል ዛክ፡፡
የመንግስታቱ ድርጅት ላይ ለውጥ ሲነሳ፣ የብዙዎችን ትኩረት የሚስበው የፀጥታው ምክር ቤት ነው፡፡ ምክር ቤቱ፤ አራቱን የሁለተኛው የአለም ጦርነት አሸናፊዎች ማለትም አሜሪካ፣ እንግሊዝ፣ ፈረንሳይ፣ ሩሲያ እና ቻይና በቋሚ አባልነት  እና በየሁለት አመቱ የሚቀያየሩ አስር ተለዋጭ  አባላትን ይይዛል፡፡ ይህ ምክር ቤት ከሰላም እና ከደህንነት ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ከፍተኛው የድርጅቱ ክንፍ በመሆኑ ማዕቀቦችን ይጥላል፣ የሀይል እርምጃዎችን ያፀድቃል ወይንም ይሽራል፡፡ ውሳኔዎችን ተግባራዊ ለማድረግ የዘጠኝ አባላት ድምፅ ሲያስፈልግ የቋሚ አባላቱ ሙሉ የስምምነት ድምፅ ግን የግድ ያስፈልጋል፡፡
የመንግስታቱ ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ላይ በሚነሱ ጥያቄዎች እና ለማሻሻያ ይረዳሉ በሚል በተጠራ የከፍተኛ ባለሙያዎች ፓናል ሪፖርቱን ለድርጅቱ አቅርቧል፡፡ በፓናሉ ላይ የመንግስታቱ ድርጅት የፀጥታው ምክርቤት የተሰጠውን ሚና መወጣት እንዳቃተው ሪፖርቱ ያሳያል፡፡ በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት ከሞላ ጎደል ሽባ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ከቀዝቃዛው ጦርነት ማብቃት በኋላ የመነቃቃት አዝማሚያ ቢታይም፣ ከተወሰኑ ውጤታማ ስራዎች በስተቀር አንድን አሳሳቢ ጉዳይ ከመከሰቱ በፊት ለመከላከል ወይም ለተፈጠረ ቀውስ መፍትሄ ከማምጣት ይልቅ የሀይል መጠላለፍ እና መቆላለፉ በመጉላቱ፣ ቋሚ የምክር ቤቱ አባሎች ጥቅም ማስጠበቂያ ሆኗል፡፡ በተለያዩ ጊዜዎች ምክር ቤቱን ለማሻሻል የተደረጉ ሙከራዎች በተለይ የምክር ቤቱ አባልነት ላይ ይደረጉ በሚባሉ ማሻሻያዎች ስምምነት ላይ ባለመደረሱ ውድቅ ሲሆኑ ተስተውለዋል፡፡
በፓናሉ ላይ የምክርቤቱን አባላት ቁጥር ከአስራ አምስት ወደ ሀያ አራት በማሳደግ ሁለት ሞዴሎች ለውይይት ቀርበው ነበር፡፡ አንዱ ሞዴል፡- ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት የሌላቸው ስድስት አዲስ የቋሚ አባላትን ማካተት ሲሆን፣ ሁለተኛው ሞዴል ደግሞ አዲስ የቋሚ አባላትም ሳይኖሩ በየአራት አመቱ የሚለዋወጥ መቀመጫ ይኑር የሚሉ ናቸው፡፡
የፀጥታው ምክር ቤትን ጉዳይ አስመልክቶ የተሰጡ ብዙ አስተያየቶች አሰራሩ መሻሻል እንዳለበት ይጠቁማሉ፡፡ አምስቱ አገሮች በሞኖፖል ጠቅልለው የያዙት ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት በራሱ ከመሰረታዊዎቹ የህግ መርሆዎች ጋር ይጋጫል፡፡ አገሮቹ ውሳኔዎች እንዲያልፉ ወይም እንዲወድቁ ድምፅ የሚሰጡት ከሰብአዊ መብቶች ወይም ከአለም አቀፍ ህግ በመነሳት ሳይሆን፣ ከራሳቸው መንግስት ጥቅም እና ፍላጎት አንፃር ነው። የፀጥታው ምክር ቤት የተቋቋመው አለም አቀፍ ሰላም እና ደህንነትለ ለማስከበር ቢሆንም እያገለገለ ያለው ግን ለየአገሮቹ የኢኮኖሚ ጥቅም እና የጡንቻ ብቃት መለኪያነት ነው፡፡ ምእራባውያኑ በአለም ላይ ዲሞክራሲን የማስፈን እውነተኛ ፍላጎት ካላቸው ሥራው መጀመር ያለበት በመንግስታቱ ድርጅት፣ በተለይም በፀጥታው ምክር ቤት ነው፡፡ ድምፅን በድምፅ የመሻር መብቱ የተሰጠው ፍትሀዊ ባልሆነ መንገድ በመሆኑ ሰላም ማምጣት አልተቻለም፡፡ ይህ አሰራር፣ ክፍፍል እና ብዙ ተቃርኖ ያላቸው ቡድኖች እንዲፈጠሩ እድል ሰጥቷል፡፡ ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት በመንግስታቱ ድርጅት ውስጥ ያለ የዲሞክራሲ መርሆችን የሚሸረሽር አሰራር ነው፡፡
በአለም ላይ ያሉ አገሮችና ህዝቦች እጣፈንታ በአምስት አገሮች ፍላጐት እንዲወሰን በመፈቀዱ ምክንያት አለማችን ይሆናሉ ተብለው የማይገመቱ እልቂቶችንና አሳዛኝ ክስተቶችን እንድታስተናግድ ምክንያት ሆኗል፡፡ የሩዋንዳው እልቂት፣ የዳርፉር እና የሶሪያ ሰብአዊ ቀውሶች እንደ ምሳሌ ይጠቀሳሉ። የመንግስታቱ ድርጅት ሩዋንዳ ውስጥ የተከሰተውን የዘር ማጥፋት እልቂት ቀድሞ መከላከል ያልቻለው ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ባላቸው አሜሪካን እና ፈረንሳይ ውሳኔ ነው፡፡ ሁለቱ አገሮች ከየጥቅሞቻቸው በመነሳት፡- አሜሪካ ከገንዘብ ጋር በተያያዘ፣ ፈረንሳይ ደግሞ አጋሮቿን ላለማጣት በሚል የግል ስሌት ውስጥ በመግባታቸው  ነው … ብዙሀን በአደባባይ እንደ በግ የታረዱት። የሲሪላንካው አማፂ ቡድን “ታሚል ታይገርስ” ላይ በመንግስት በኩል ይደርሱ የነበሩ ኢ-ሰብአዊ እርምጃዎችን ለመታደግ በሚል መንግስት ላይ ሊጣል የነበረ ማእቀብ ውድቅ የተደረገው በቻይና ሲሆን መነሻውም ቻይና ከሲሪላንካ መንግስት ጋር ያላትን ወዳጅነት ላለማሻከር ሲባል ነበር፡፡ ሶስተኛ አመቱን የያዘውና  በመንግስታቱ ድርጅት የዘመኑ ከፍተኛ ሰብአዊ ቀውስ የታየበት ነው የሚባለው የሶሪያ ጉዳይም ከዚህ ጨዋታ የዘለለ አይደለም። ለችግሩ መፍትሄ በሚል የቀረበው ረቂቅ የውሳኔ ሀሳብ፣ በቻይና እና በራሺያ ተቀባይነት ባለማግኘቱ ውድቅ እንዲሆን ተደርጓል፡፡ የበሽር አላሳድ መንግስትን የሚደግፉት ቻይና እና ራሺያ፣ የውሳኔ ሀሳቡ መንግስትን ብቻ በመኮነን ተቃዋሚ ሀይሎችን በዝምታ ያለፈው በዚሁ የውሳኔ ሀሳብ በመሆኑ ድምፃቸውን መንፈጋቸውን ይገልፃሉ፡፡ በመንግስታቱ ድርጅት የራሺያ አምባሳደር ቪታሊ ቸርኪን የአገራቸውን ውሳኔ አስመልክቶ ተጠይቀው በሰጡት አስተያየት፣ የውሳኔ ሀሳቡ ሁሉንም ወገኖች በእኩል የሚኮንን ሳይሆን የአላሳድን መንግስት በተናጠል የሚኮንን በመሆኑ አገራቸው ልትቀበለው እንደማትችል ተናግረዋል፡፡
አፍሪካ፤ ጃፓን፤ ህንድ እና የብሪክስ አገሮች የፀጥታው ምክር ቤት አሰራር ላይ የማሻሻያ ለውጥ እንዲደረግ ከሚጎተጉቱ አገሮች እና አካባቢያዊ ድርጅቶች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ አሁን ባለው አሰራር የብዙሀንን ጥቅም ማስከበር እንደማይቻል በተለያዩ ማስረጃዎች አስደግፈው ያቀርባሉ። ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዳይሆን ቢደረግም ሆነ አገሮች እና አካባቢያዊ ድርጅቶች የመብቱ ተጠቃሚ መሆን ቢችሉ እንኳን፣ የራስን ጥቅም ማስላትን አያስቀርም፤ መጠላለፉን ከማወሳሰብ በስተቀር የሚሉም አሉ፡፡

“...ሀገራችን ፀሐይ ወጥቶ! አሁንማ ፀሐይ ወጥቶልናል። ሆስፒታላችን ከተሰራልን ወዲህ ምን ችግር አለ... ሞትማ እንዲህ በቀላሉም አይደፍረን፡፡ መቼም ነብስ የእግዚሀር ናትና ሲያበቃላት መትረፊያ የላትም እንጂ... እንዲህ በምኑም በምኑም አልጋ መያዝማ ቀርቶአል፡፡ ይኼው አሁን እኔን ከበሽታ ነጻ አውጥቶኛል፡፡ እዚህ ጉያዬ ስር አንድ ሕመም ነበረብኝ... ፍልፍል አድርጎ አውጥቶ ወርውሮልኝ... ይኼው አሁን ነጻ አውጥቶኛል፡፡ ሐኪሙም አየለ የሚባለው ዶ/ር ነው...”
ከላይ ያነበባችሁት በመርሐቤቴ አለም ከተማ እናት ሆስፒታል ያገኘናቸው አባወራ እማኝነት ነው፡፡ መርሐቤቴ በአማራው ክልል የምትገኝ ስትሆን ከአዲስ አበባ በጎጃም መንገድ መካጡሪ ከተማ ሲደረስ ወደ ቀኝ በመታጠፍ ወደ /111/ አንድ መቶ አስራ አንድ ኪሎ ሜትር ጥርጊያ መንገድ ተገብቶ የምትገኝ ነች፡፡ መርሐቤቴ ተራራማ ስትሆን ዠማ የሚባል ወንዝ መሐል ለመሐል የሚጉዋዝባት እጅግ አስደናቂ ተፈጥሮአዊ ውበት ያላት ናት፡፡ በእርግጥ ከስድስት አመት በፊት መንገዱ እንዲህ በዋዛ የማይደፈር ሲሆን አሁን ግን ዳገት ቁልቁለቱ እንዳለ ቢሆንም ጥርጊያው በማማሩ በጥንቃቄ መንዳት እንጂ እንደቀድሞው ሰውን ማሰቃየቱ አብቅቶአል፡፡ እንደሀገሬው ተስፋም ብዙም ሳይቆይ ወደ አስፋልትነት ይቀየራል፡፡ ግራና ቀኙን እያዩ የተራራውን አቀማመጥ፣ ተፈጥሮአዊ ሀብቱን እያደነቁ ከአንዱ ተራራ ወደአንዱ እየተ ዙዋዙዋሩ ሲጉዋዙ ድካሙን ሳያስቡ ከመርሐቤቴ አለም ከተማ ይደርሳሉ፡፡ አለም ከተማ መሐል አደባባይ ላይ አንድ ልጅ የታቀፈ ሰው ሐውልት ያያሉ፡፡ ቀረብ ብለው ሲያጣሩ ምስሉ የሜንሽን ፎር ሜንሽን መስራች የዶ/ር ካርል ሄንዝ ቦም  ነው፡፡ ሜንሽን ፎር ሜንሽን በመርሐቤቴ ከሰራቸው የልማት ስራዎች መካከል እናት ሆስፒታል አንዱ ሲሆን በመሀል ከተማው አደባባይ ላይ የሚገኘው ሐውልት ለአስተዋጽኦው ማስታወሻ ሐገሬው ለመስራቹ ዶ/ር ካርል ያቆመለት ሐውልት ነው፡፡ እኛም ፈልገን የተጉዋዝነው እናት ሆስፒታልን ነውና በመጀመሪያ የሆስፒታሉ ስራ አስኪያጅ የሰጡትን ማብራሪያ ለንባብ እንላለን፡፡
“...እኔ አቶ ደነቀ አየለ እባላለሁ፡፡ በዚህ ሆስፒታል ቀደም ሲል የጤና መኮንን ሆኜ የሰራሁ ስሆን አሁን ደግሞ ስራ አስኪያጅ ነኝ፡፡ በአለም ከተማ እናት ሆስፒታል የተሰራው በሜንሽን ፎር ሜንሽን አማካኝት ሲሆን የመሰረት ድንጋዩ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1991 ዓ/ም ተጥሎ በ1996 ዓ/ም በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እና በሆስፒታሉ መስራች ዶ/ር ካርል ሄንዝ ቦብ ተመርቆ ህብረተሰቡን በማገልገል ላይ ይገኛል፡፡
ጥ/ ሆስፒታሉ እናት ሆስፒታል የተባለበት ምክንያት ምንድነው?
መ/    የሆስፒታሉ መጠሪያ እናት እንዲሆን የተወሰነው በመስራቹ በዶ/ር ካርል ነው፡፡ ይኼውም የመሰረት ድንጋይ በሚጣልበት ወቅት ለሚሰራው ሆስፒታልም ስም እንዲወጣ ህብረተሰቡ ተነጋግሮ ሁሉም ለምርጫ የሚሆነውን ስም በልቡ ይዞ ነበር ወደስፍራው የተሰበሰበው፡፡ ከወጣው ህብረተሰብ መካከልም ህጻናትም ይገኙ ነበር፡፡ ከህጻናቱ መካከል አንዲት በዝቅተኛ ደረጃ ከሚኖሩ ቤተሰቦች የተወለደች ልጅ በጣም ቆሽሻ፣ በዝንብ ተወርራ በሚያሳዝን ሁኔታ ቆማ ነበር፡፡ ዶ/ር ካርልም ከልጆቹ መካከል ብድግ አድርገው አቅፈው እያዘኑ ከተመለከቱዋት በሁዋላ ስሙዋ ማን እንደሆነ ጠየቁ፡፡ ስሙዋ እናት መሆኑ ሲነገራቸው  ...በቃ ሆስፒታሉ እናት ተብሎአል ብለው ወሰኑ፡፡ በጊዜው ህብረተሰቡ በተለያዩ  ስሞች ላይ ውይይት አድርጎ የነበረ ስለሆነ ለምን በሚል ቅር ቢለውም ውሳኔው በመወሰኑ ሆስፒታሉ እናት ሆስፒታል ተብሎ ተሰይሞአል፡፡ ልጅቱም በሰዎች ለሰዎች ድርጅት ከነቤተሰቦችዋ እየተረዳች ትምህርቷን እንድትቀጥል ተደርጎአል፡፡
ጥ/    ሆስፒታሉ ደረጃው ምንድነው?
መ/    አለም ከተማ እናት ሆስፒታል ደረጃው በመጀመሪያ ደረጃ ወይንም በወረዳ ደረጃ ዲስትሪክት ሆስፒታል ሆኖ የሚሰራ ነው፡፡ ከአካባቢው አቀማመጥ ጋር ተያይዞ ሌላም ተመሳሳይ የጤና ተቋም ባለመኖሩ በአካባቢው የሚኖሩ ወደ 250‚000 /ሁለት መቶ ሀምሳ ሺህ/ የሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማገልገል ላይ ነው፡፡ ከሌሎች አጎራባች ክልሎች ወይንም ዞኖች ...ለምሳሌ ከኦሮሞ የሚመጡትንም ተገልጋዮች አካቶ በርካታ ሰዎችን እያገለገለ ይገኛል፡፡ በአሁኑ ወቅት ወደ /158/ አንድ መቶ ሀምሳ ስምንት ሰራተኞችን የያዘ ሲሆን በተለይም ባለሙያዎችን በሚመለከት ከአምስት በላይ ዶክተሮች እና አንድ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ስለሚገኝ ከደረጃው በላይ እየሰራ ነው ማለት ይቻላል፡፡
ዶ/ር አየለ ተሸመ በአለም ከተማ እናት ሆስፒታል የማህጸንና ጽንስ ሐኪምና የሆስ ፒታሉ  ሜዲካል ዳይሬክተር ናቸው፡፡
ጥ/ ዶ/ር አየለ መርሐቤቴን ለስራ ከመመደብ ውጭ አስቀድሞ ያውቁዋታል?
መ/ እኔ ተወላጅነቴም እድገቴም በዚሁ በመርሐቤቴ ነው። አሁን የምኖርበት ቤት ቀደም ሲል ጤና ጣቢያ የነበረና እኔም የተወለድኩበት ማዋለጃ የነበረ ቤት ውስጥ ነው፡፡ ከህክምና ትምህርት ቤት ተመርቄ እንደወጣሁ በጠቅላላ ሐኪምነትም የሰራሁት በዚሁ ሆስፒታል ነው፡፡ ከዚያም ለአራት አመት ያህል ከ2000-2004 እንደገና ስፔሻላይዜሽን ተምሬ በመመለስ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት በመሆን በማገልገል ላይ እገኛለሁ፡፡
ጥ/  ምደባው በአጋጣሚ ነው ወይንስ በምርጫ?
መ/ እኔ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ትምህርት ቤት በጥቁር አንበሳ የመጀመሪያ ዲግሪዬን ስማር የማህጸን መፈንዳት ሪፖርት ሲደረግ ብዙዎች ከመርሐቤቴ የሚመጡ መሆናቸው የሚነገር ነበር፡፡ በጊዜው መንገዱ እጅግ አሳዛኝ እና አስቸጋሪ ስለነበር እንዲሁም የሚፈለገው ሕክምና በጊዜው በአካባቢው ካለው የጤና ጣቢያ አቅም በላይ የሆነ ችግር ስለሆነ ወላዶች በጣም ይሰቃዩ ነበር፡፡ በእርግጥ የሰዎች ለሰዎች ድርጅት አምቡላንስ ይሰጥ ስለነበር ወደአዲስ አበባ እንዲደርሱ የሚደረግ ቢሆንም ከመዘግየት የተነሳ ረጅም ጊዜ በምጥ በመቆየት ሴቶቹ ይጎዱ ነበር፡፡ እናም አንዳንድ ጊዜ የጠዋት ሪፖርት ላይ የማህጸን መፈንዳት ደርሶአል ሲባል ከየት ከመርሐቤቴ ናት? እስከማለት ድረስ መነጋገሪያ መሆኑ በጣም ያሳዝነኝ ነበር፡፡ በእርግጥ ካለው ዘርፈ ብዙ የጤና ችግር ምክንያት አንባቢው በጤና ጣቢያ ደረጃ ባለበት ጊዜም ሶስት እና አራት ሐኪሞች ይመደቡ የነበረ ቢሆንም ሐኪሞቹም በዚህ የመቆየት ፍላጎት ስለሌላቸው እና ከጤና ጣብያው አቅምም ጋር በተያያዘ በተለይም ለወላዶች በቀላሉ የማይፈቱ የጤና ጠንቆች ይገጥሙዋቸው ነበር፡፡ ስለዚህ እኔም ትምህርቴን ልጨርስ እንጂ በዚያ ገጠራማ ቦታ ገብቼ ህብረተሰቡን ማገልገል አለብኝ ብዬ ወሰንኩ፡፡ መጀመሪያ ላይ ምንም እንኩዋን ጠቅላላ ሐኪም ብሆንም የእናቶችን ችግር ስለማውቅ ከሰዎች ለሰዎች ድርጅት ጋር ተነጋግሬ ለሶስት ወር ለወላዶች የድንገተኛ ቀዶ ሕክምና ስልጠና አግኝቼ በማዋለድ ተግባር ላይ እንድሰማራ እራሴን አዘጋጀሁ፡፡ ከዚያም ከኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር በተገኘው እድል እንደገና ለስድስት ወር ባለሙያዎችን አሰልጥኜ እኔም ስራዬን እዚሁ ቀጠልኩ፡፡
ጥ/ በገጠር ሆስፒታል ውስጥ እስፔሻሊስት ይመደባልን?
መ/ በጀት ስለሌለ የገጠር ሆስፒታል ውስጥ እስፔሻሊስት አይመደብም፡፡ እናም የጤና ቢሮው እምቢ ቢልም ከዚህ የስራ አመራር ቦርድና ሽማግሌዎች ሄደው በማስፈቀዳቸው እና የእኔም ፍላጎት ስለነበረበት እንድመደብ ተደርጎ በመስራት ላይ ነኝ፡፡
ዶ/ር አየለ ተሸመ በስራቸው ያጋጠማቸውን እንዲህ ሲሉ አውግተዋል፡፡
“...አንዲት ሴት በምጥ ተይዛ በቤቷ ትቆይና ልጇን ትገላገላለች፡፡ ነገር ግን እንግዴ ልጁ እምቢ ስላለ ወደሆስፒታል ያመጡአታል፡፡ ሴትየዋ በሞት እና በህይወት መካከል ነበረች። ስለዚህም እንግዴልጁን ለማውጣት መጀመሪያ የደም ልገሳ እንደሚያስፈልግ ስንነግራቸው እንዴት ተደርጎ የሚል ነገር ተነሳ፡፡ እኛም ምንም ችግር የለውም አልንና... ባለቤቷን...
አንተ ባለቤቷ አይደለህም? አልነው... ነኝ የእርሱ መልስ ነበር፡፡ ታድያ ሚስትህ ከምትሞት አንተ ደም ስጥ... ስንለው  ...አረግ …እኔማ ገበሬ ነኝ ከየት አምጥቼ ነው ለእሷ ደም የምስጥ? መልሱ ነበር፡፡
በመቀጠልም እናትየውን አነጋገርን፡፡
አረግ ...እኔማ ልጄ ብትሞት አልሻም፡፡ ነገር ግን ...እኔ አሮጊት ነኝ ደም ከወዴት አመጣለሁ? ለእኔም አልበቃኝ... መልሳቸው ነበር፡፡ አብረው የነበሩትም ይልቁንም ሳትሞት ይስጡን እና እንውሰድ፡፡ ከሞተች መውሰጃውም አይገኝ ወደሚል ውይይት ገቡ፡፡ እኛም አይናችን እያየ እንዳትሞት ተነጋገርንና ሰዎቹን አስወጥተን ...አንድ ሰራተኛና አንድ አስታማሚ ደም ሰጥተው ህይወቷን አተረፍናት፡፡
ከዚያም ያ ደም የለገሰ ሰውየ ተናደደና ወደሰዎቹ በመሄድ ...ሴትየይቱ  እኮ ሞታለች ...ለምን አስከሬኑን አትወስዱም ሲላቸው... ከተማይቱ እስክትናወጥ ድረስ ኡኡታቸውን አቀለጡት፡፡ በሁዋላም በሉ ዝም በሉ ...እሱዋ ድናለች ሲባል ተደሰቱ፡፡  ከዚያም ወደህብረተሰቡ ሄደው ምስክርነታቸውን ሲሰጡ ለካንስ ይኼም አለ በሚል አሁን ደም የሚለግሱ ሰዎች ማህበር ተቋቁሞአል፡፡ ወደ ሁለት መቶ የሚደርሱ ሰዎች የደም ልገሳ ማህበርተኞች ሆነው ተመዝግበዋል፡፡ ስለዚህም ሰዎቹ የደም አይነታቸው፣ የሚኖሩበት አካባቢ፣ የስልክ ቁጥራቸው ተመዝግቦ የሚገኝ ስለሆነ አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ካሉበት ድረስ አምቡላንስ እየላክን እንጠራቸዋለን፡፡ ከሰራተኞቹም እኔን ጨምሮ ፈቃደኞች የሆንን በየሶስት ወሩ ደም እንሰጣለን። እናት ሆስፒታል የደም ባንክ ባይኖረውም አስፈላጊው የላቦራቶሪ ስራ እየተሰራ ለተጠቃሚዎች ደም ይሰጣል፡፡ በእርግጥ ከአዲስ አበባም ደም ባንክ የተቻለውን ያህል ደም ቢሰጠንም በቂ ስለማይሆን ከህብረተሰቡ የሚደረግልን እገዛ ችግሩን አስቀርቶልናል፡፡ ይህም ጥሩ ተሞክሮ ስለሆነ ለሌሎች እንደምሳሌ የሚነሳ ሆኖአል፡፡
ይቀጥላል፡፡

“የተሳፋሪው ፍላጎት የሆነ መሬት ላይ ማረፍ ብቻ  ነበር”
በሃዋሳ ከተማ በተለምዶ ኬሮ ሰፈር እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ተወልዶ ያደገው ወጣት ምህረቱ ገብሬ፣ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በቀድሞው ሀዋሳ ኮምቦኒ የመጀመርያ ደረጃ ት/ቤት ነው የተከታተለው። የሁለተኛ ደረጃ ማጠናቀቂያና የመሰናዶ ትምህርቱንም በቅዱስ ዳንኤል ኮምቦኒ የሁለተኛ ደረጃና የመሰናዶ ት/ቤት አጠናቋል። ከሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በ2001 ዓ.ም በሲቪል ምህንድስና የመጀመሪያ ዲግሪውን ካገኘ በኋላም፤ እስከ 2004 ዓ.ም ድረስ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በመምህርነት አገልግሏል፡፡ በመቀጠልም ነጻ የትምህርት ዕድል በማግኘት፣ ወደ ጣሊያን አምርቶ የሁለተኛ ዲግሪ ትምህርቱን በመከታተል ላይ ይገኛል፡፡
በቅርቡ ለእረፍት ወደ አገሩ የመጣውና በሃዋሳ ቆይቶ ወደ ጣሊያን ለመመለስ አውሮፕላን የተሳፈረው ምህረቱ፣ ባለፈው ሰኞ በረዳት አብራሪው ተጠልፎ ጄኔቭ እንዲያርፍ በተደረገው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 767 አውሮፕላን ውስጥ ከነበሩት 200 ገደማ ተሳፋሪዎች ውስጥ አንዱ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት በጣሊያን የሚገኘው ምህረቱ፣ የጠለፋውን አጋጣሚ በተመለከተ ጋዜጠኛ አንተነህ  ይግዛው በኢ-ሜይል ለላከለት ጥያቄዎች የሰጠውን ምላሽ  እንደሚከተለው አጠናቅረን አቅርበነዋል፡፡  

የጉዞው አጀማመር ምን ይመስል ነበር?
አርፍዶ ወደ አውሮፕላን ጣቢያ መምጣት የሚያደርሰውን ጣጣ ስለማውቀው፣ አውሮፕላኑ ከሚነሳበት 50 ደቂቃ ያህል ቀድሜ ነበር የተገኘሁት፡፡ ከምሽቱ አራት ሰዓት አካባቢ ማለት ነው፡፡ ያው ጉዞው ሲጀመር እንደሌላው ጊዜ ሁሉ ስርአቱን የጠበቀና ሰላማዊ ነበር።  አውሮፕላኑ ከበራራ ሰዓቱ ሰባት ደቂቃ ያህል ዘግይቶ ነበር የተነሳው።
አውሮፕላኑ ውስጥ አቀማመጥህ እንዴት ነበር? የት አካባቢ ነው የተቀመጥከው?
የመቀመጫዬ ቁጥር 27F ነበር። የተሳፈርንበት ቦይንግ 767 በርዝመቱ ትይዩ 7 የመቀመጫ መደዳዎች አሉት። ሁለት ሁለት መደዳዎች በሁለቱም ጥጎች እና ሶስት መደዳዎች መሃል ላይ። እኔ የተቀመጥኩት ከመሃል ሶስቱ መደዳዎች የመሃለኛዋ ወንበር ላይ ነበር። ከበስተግራዬ ያለችው ወንበር ላይ የተቀመጡት ሪካርዶ የተባሉ የ85 አመት የዕድሜ ባለጸጋ ጣሊያናዊ ነበሩ፡፡ በቀኜ በኩል እንዲሁ በግምት በስድሳዎቹ ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሌላ ጣሊያናዊ ተቀምጠው ነበር፡፡ ተዋውቀን ነበር፣ አሁን ግን ዘንግቼዋለሁ። ኢትዮጵያን ተዟዙረው እንደጎበኟት እያጫወቱኝ ነው ጉዞውን የጀመርነው፡፡
ጉዞውስ  እንዴት ነበር?
እንደማስታውሰው ጉዞው ሲጀመር ሰላማዊ ነበር። ከፓይለቱ ጋርም ግንኙነት (ኮሙኒኬሽን)  ነበረን፡፡ እኔ ድካም ስለተሰማኝ ወዲያው አሸለብኩ፡፡ በረራው ከተጀመረ በግምት ከ1 ሰዓት በኋላ የሱዳን አየር ክልል ውስጥ ይሆናል ብዬ እገምታለሁ. . . መብራት ሲበራ ከእንቅልፌ ነቃሁ፡፡ የምግብ ሰዓት መድረሱ ገብቶኛል። ወደ ፊት አሻግሬ ሳይ ሆስተሶቹ እያስተናገዱ ከእኔ ፊት 4ኛ ይሁን 5ኛ ረድፍ ደርሰዋል። ሁሉም ተዘገጃጅቶ እየተጠባበቀ ነበር። በዚህ መሃል የፕሌኑ ፍጥነት ሲጨምር ይታወቀኛል፡፡ ከፍታዉም ሲጨምር በጆሮዬ ላይ በሚሰማኝ ስሜት አስተዋልኩ። በተሳፋሪዎች ፊት ላይ የመረበሽ ስሜት ሲፈጠር አየሁ። እኛ  ኢኮኖሚ ክላስ ስለነበርን ከፊት ምን እየተካሄደ እንደነበር አላየንም። በኋላ ስሰማ ከፊት የነበሩትም የቢዝነስ ክላስ ተሳፋሪዎች ምንም መረጃ አልነበራቸውም፡፡
ከዚያም በድምጽ ማጉያው የሆነ ድምጽ ተሰማ፡፡ የረዳት አብራሪው ድምጽ ነበር።
“ተሳፋሪዎች ከ 12 ደቂቃዎች በኋላ ሚላን እናርፋለን” አለ ረዳት አብራሪው፡፡ ጥቂት ቆይቶም፣ “ስለተፈጠሩ አንዳንድ መጉላላቶች ይቅርታ እንጠይቃለን” ሲል አከለ-በእንግሊዝኛና በአማርኛ ቋንቋ። የረዳት አብራሪውን ንግግር ተከትሎ የተወሰኑ ተሳፋሪዎች ማጉረምረም ጀመሩ፡፡ አንዳንዶችም ጮክ ብለው ሲያወሩ ይሰሙ ነበር፡፡ ከኔ በስተግራ በኩል ሶስት አራት መደዳዎችን አልፎ ከፊቴ ተቀምጦ የነበረ አንድ ወፍራም ሰው፣ በጣሊያንኛ ቆጣ ብሎ እየጮኸ ተናገረ - “መጀመሪያ ሚላን ሳይሆን ሮም ነው ማረፍ ያለብን ፣ ወደ ሮም ውሰዱን!” በማለት። ሌሎችም የሰውየውን ሃሳብ ደገፉ፡፡ ምክንያቱም አብዛኛው ተሳፋሪ ወደ ሮም ነበር የሚጓዘው። ረዳት አብራሪው ሚላን ላይ እንደምናርፍ መናገሩ ብዙዎችን አበሳጭቶ ነበር፡፡  
እውነቱን ለመናገር፣ እኔ ግን ሚላን እንደምናርፍ ስሰማ ደስ ብሎኝ ነበር፡፡ ምክንያቱም እኔ ሚላን ወራጅ ነኝ፡፡ ረዳት አብራሪው የነገረን አስራ ሁለቱ ደቂቃዎች እየተገባደዱ መሆናቸው ሲገባኝ፣ ከአውሮፕላኑ ለመውረድ መዘገጃጀትና ጓዜን መሸካከፍ ሁሉ ጀመርኩ። ሆኖም  አስራ ሁለቱ ደቂቃዎች አልፈውም አውሮፕላኑ አላረፈም፡፡ ካሁን አሁን ሚላን አውሮፕላን ማረፊያ ደረስን እያልን ስንጠባበቅ፣ ሌላ አስራ ሁለት ደቂቃዎች አለፉ፡፡ አሁንም ሌላ አስራ ሁለት ደቂቃዎች---
ተሳፋሪው ሁሉ ግራ በመጋባት ሰዓቱን ደጋግሞ መመልከትና እርስ በርስ በጥርጣሬ መተያየት ጀመረ። ከአስራ ሁለት ደቂቃዎች በኋላ ሚላን ላይ ያርፋል የተባለው አውሮፕላን፣ ከአንድ ሰዓት ተኩል በላይ በአየር ላይ ቆየ፡፡ የሚገርመው ያን ያህል ጊዜ አየር ላይ መቆየቱ ብቻ አይደለም፡፡ አበራረሩ የተለየ ነበር፡፡ አንዴ ፍጥነቱን ጨምሮ ይከንፋል፣ ከዚያ ደግሞ ፍጥነቱን ይቀንስና ተረጋግቶ ይበራል፡፡ እንደገና ይፈጥናል፣ እንደገና ይረጋጋል፡፡ ግራ ገብቶን እያለን፣ ከመቅጽበት አውሮፕላኑ ማረፊያው ላይ ደርሶ ማኮብኮብ ጀመረ፡፡ ያንን ያህል ግዙፍ አውሮፕላን፣ በዚያች ጠባብ ቦታ ላይ ያለችግር ማሳረፍ መቻሉ፣ የረዳት አብራሪውን ብቃት ያሳያል፡፡ ለማንኛውም አውሮፕላኑ በሰላም አረፈና እኛም እፎይ አልን፡፡
አውሮፕላኑ ካረፈ በኋላ የተሳፋሪዎች ስሜት ምን ይመስል ነበር?
የሚገርመው ነገር፣ አውሮፕላኑ እንዳረፈ በተሳፋሪው ፊት ላይ ከታየው ደስታና እፎይታ በተጨማሪ፣ ተሳፋሪው ለረዳት አብራሪው የሰጠው አድናቆት ነበር፡፡ አብዛኛው ተሳፋሪ ስለረዳት አብራሪው ችሎታ ነበር ተደንቆ የሚያወራው፡፡ በከፍተኛ የአድናቆት ስሜት ተውጠው፣ ለረዳት አብራሪው ያላቸውን አድናቆት በጭብጨባና በፉጨት የገለፁም ነበሩ፡፡ እኔም በደመነፍስ ሳጨበጭብ ነበር፡፡ ሚላን ምድር ላይ በሰላም እንዲያሳርፈኝ ለፈጣሪዬ ያደረስኩትን ጸሎት የማውቀው እኔ ነኝ፡፡
ሚላን እንዳረፋችሁ ነበር የምታውቁት ማለት ነው?
የሚገርመው እኮ እሱ ነው!... አውሮፕላኑ መሬት ከነካ በኋላ ሁሉ፣ ተሳፋሪው በሙሉ ጣሊያን ሚላን እንዳረፈ ነበር የሚያውቀው፡፡ ሚላን እንደምናርፍ ነው ረዳት አብራሪው የነገረን፡፡ ትኬት ከፍለን የተሳፈርነውም ወደ ጣሊያን እንጂ ወደ ስዊዘርላንድ ለመሄድ አልነበረም። በዚህ ቅጽበት ጄኔቭ የምትባል ከተማ በምን ተአምር እንሄዳለን ብለን እናስብ?
ጄኔቭ መሆናችሁን ያወቃችሁት እንዴት ነው?
አውሮፕላኑ በሰላም ካረፈ በኋላ ተሳፋሪው ከጭንቀቱ ተገላግሎ መረጋጋት ጀመረ፡፡ አንዳንዶች ሞባይል ስልኮቻቸውን አውጥተው መነካካት ያዙ። በሞባይላቸው የኢንተርኔት መስመር በመጠቀም ጎግል ማፕ የተሰኘውን የአገራትና የከተሞች ካርታ የሚያሳይ ድረገጽ፣ ጂ ፒ ኤስ ከሚባለው አቅጣጫ ጠቋሚ ቴክኖሎጂ ጋር አያይዘው ሲመለከቱ፣ ፊታቸው ላይ ድንገተኛ መደናገር ሲፈጠር አየሁ፡፡ አንዱ ተሳፋሪ ሞባይሉ ላይ ያየውን መረጃ በመጠራጠር፣ የሌላኛውን ሞባይል ማየት ጀመረ፡፡ “የት ነው ያለነው?” ለሚለው ጥያቄ እርግጠኛ የሆነ መልስ የሚሰጥ ጠፋ፡፡ ግማሹ “ ኦስትሪያ ነን!” ሲል፣ ገሚሱ “የለም ፈረንሳይ ነን!” ብሎ ይመልሳል፡፡ አንዳንዱ “ጀርመን ውስጥ ነው የምንገኘው!” ይላል፡፡ ሌላው “ስዊዘርላንድ ጄኔቭ ነው ያረፍነው!” እያለ ይናገራል፡፡ ጭንቀትና ውጥረት የፈጠረው መደናገር ሊሆን እንደሚችል ያሰብኩት በኋላ ነው፡፡
 ጄኔቭ ማረፋችሁንና አውሮፕላኑ መጠለፉን ያወቃችሁት እንዴት ነበር?
እያንዳንዱ ተሳፋሪ አውሮፕላኑ ያረፈበትን አገርና ከተማ በተመለከተ የየራሱን መላምት እየሰነዘረ ግራ ተጋብቶ ጥቂት ደቂቃዎች አለፉ፡፡ በዚህ መሃል ነው፣ ድንገት የአውሮፕላኑን ዋና አብራሪ ድምጽ የሰማነው። በረራው ከተጀመረ አንስቶ የዋና አብራሪውን ድምጽ ስንሰማ ለመጀመሪያ ጊዜያችን ነበር፡፡ ዋና አብራሪው በጣሊያንኛ ቋንቋ ነበር የሚያወሩት፡፡ በጣሊያን ቆይታዬ የቀሰምኳት ቋንቋ ብዙም የምታወላዳ አልነበረችምና፣ ደቂቃዎችን ከፈጀው የአብራሪው ንግግር የተወሰነችዋን ተረድቼ፣ ቀሪውን ከጎኔ ከተቀመጡት ጣሊያናውያን ጠይቄ ለመረዳት ሞከርኩ፡፡
አብራሪው  ወደመጸዳጃ ቤት ሲወጡ ረዳት አብራሪው በር እንደዘጋባቸው፤ አውሮፕላኑን ለሰዓታት ሲያበር የቆየው ረዳት አብራሪው እንደነበር፤ አውሮፕላኑ ያረፈው ጄኔቭ መሆኑን፤ በተፈጠረው ነገር ማዘናቸውን መግለጻቸውን እንዲሁም እያንዳንዱ ተሳፋሪ የስዊዘርላንድ ፖሊሶች ለሚያደርጉት ምርመራ ተገቢውን ትብብር እንዲያደርግ ጥሪ ማስተላለፋቸውን ነገሩኝ፡፡ ተሳፋሪው ስለ ጠለፋው ያወቀው በዚህ ጊዜ ነው፡፡
ተጠልፋችሁ ያላሰባችሁት ቦታ እንዳረፋችሁ ስታውቁ ምን ተሰማችሁ?
እውነቱን ለመናገር በወቅቱ የሁሉም ተሳፋሪ ጸሎትና ምኞት በረራው በሰላም መጠናቀቁና አውሮፕላኑ አደጋ ሳያጋጥመው ማረፉ ብቻ ነበር፡፡ የተሳፋሪው ፍላጎት የትም ይሁን የት፣ ብቻ የሆነ መሬት ላይ ማረፍና ከጭንቀት መገላገል ነበር፡፡ አስበው እስኪ… ከአብራሪውም ሆነ ከሆስተሶቹ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት በሌለበት አደናጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው ለሰዓታት የበረርነው፡፡ ከዚያ ደግሞ… ሮም የማረፍ ዕቅዱ ተሰርዞ፣ ከ12 ደቂቃዎች በኋላ ሚላን እንደምናርፍ ድንገት ተነገረን፡፡ ይሁን ብለን ተቀብለን፣ አስራ ሁለቱን ደቂቃ በጉጉት ስንጠባበቅ ደግሞ፣ ለተጨማሪ አንድ ሰዓት ተኩል ያህል ጊዜ በረራው ቀጠለ፡፡ በዚያ ላይ በረራው ጤነኛ አልነበረም፡፡ አንዴ የሚፈጥን፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ የሚረጋጋ ምቾት የማይሰጥ በረራ ነበር፡፡
በዚህ ሁኔታ ውስጥ ያለ ተሳፋሪ፣ የትም ቢሆን ማረፍን እንጂ፣ማረፊያ ቦታውን አይመርጥም፡፡ እኔም ሆንኩ ሌሎች ተሳፋሪዎች ጉዳዩን ያወቅነው፣ ጠለፋው ከተጠናቀቀና አውሮፕላኑ ጄኔቭ ውስጥ በሰላም ካረፈ በኋላ ዋና አብራሪው ሲነግሩን በመሆኑ እምብዛም አልተደናገጥንም፡፡  
ከአውሮፕላኑ ስትወርዱ የነበረው ሁኔታ ምን ይመስላል?
አውሮፕላኑ ጄኔቭ ካረፈ በኋላ በግምት ለአንድ ሰአት ያህል በሩ ሳይከፈት ቆሞ ቆየ፡፡ ዋና አብራሪው ሁሉንም ነገር በግልጽ ከነገሩን በኋላ፣ ከእግር ጣታቸው እስከ ራስ ጸጉራቸው የብረት ጭንብል የለበሱ ሰዎች፣ በሩን በርግደው በፍጥነት ወደ ውስጥ ገቡ። አገባባቸውና መላ ሁኔታቸው አክሽን ፊልም የሚሰሩ ነበር የሚመስሉት፡፡ ሁኔታው እጅግ ያስጨንቅ ነበር፡፡ በመካከል አንደኛው ፖሊስ በእጁ በያዛት አነስተኛ የድምጽ ማጉያ ፈረንሳይኛ በሚመስል እንግሊዝኛ መናገር ጀመረ።
“ዚስ ኢዝ ኤ ፖሊስ ኦፔሬሾን። ዶንት ሙቭ!... ፑት ዩር ሃንድስ ኦን ዩር ሄድ!... ዶንት ሜክ ሙቪ ባይ ሞባይል (በሞባይል አትቅረጹ ማለቱ ነው)” ሲል ቀጭን ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡ ሁሉም እጆቹን አናቱ ላይ ጭኖ ድምጹንም አጥፍቶ አቀረቀረ፡፡ ተሳፋሪው በፖሊሶቹ መሪነት አንድ በአንድ ከአውሮፕላኑ እየወረደ፣ ሁለት ሁለት ጊዜ ተበርብሮ ተፈተሸ፡፡
ፍተሻው እንደተጠናቀቀም በትላልቅ ሽንጣም አውቶብሶች እየጫኑ ወደ ተርሚናሉ ወሰዱን፡፡ ተርሚናሉ ላይ ስንደርስ የሚገርም አቀባበል ተደረገልን፡፡ የምንበላው ቁርስና ሻይ ቡና እንዲሁም ለብርዱ ብርድልብስ ተዘጋጅቶ ጠበቀን፡፡ የህክምና ባለሙያዎችና የስነልቦና ባለሙያዎች እርዳታ ሊሰጡን እየተጠባበቁ ነበር፡፡ አስገራሚ አቀባበል ነው የተደረገልን።
ኢትዮጵያውያንስ አላገኛችሁም?
ተርሚናሉ ዉስጥ ገብተን ትንሽ እንደቆየን አንድ ኢትዮጵያዊ ወደ እኛ ሲመጣ ተመለከትን፡፡ ለጊዜው ስሙ ትዝ አይለኝም። ከኢትዮጵያ ኤምባሲ እንደመጣ ነገረንና ስለሁኔታው ጠየቀን። “አይዟችሁ!... ደርሰንላችኋል!...” የሚል መንፈስ ያለው ማበረታቻ ሰጠን፡፡ ከዚያም የግል ሞባይሉን ከኪሱ አውጥቶ አገር ቤት ያሉ ቤተሰቦቻችን ጋ ደውለን ደህንነታችንን እንድናረጋግጥ ራሱ እየደወለ ያገናኘን ጀመር፡፡   
በዚህ ጊዜ ነው፣ በስዊዘርላንድ የኢትዮጵያ አምባሳደር የመጡት፡፡ በአውሮፕላኑ ውስጥ የነበርን ኢትዮጵያውያንን አነጋግረው አረጋጉን፡፡ በስተመጨረሻም ከተርሚናሉ እንዲወጡ ስለታዘዙ የማስታወሻ ፎቶግራፍ አብረውን ተነሱና ጉዳያችንን በቅርብ እንደሚከታተሉ ነግረውን አበረታቱንና ሄዱ፡፡ ሌሎች ሁለት የኤምባሲው ባልደረቦችም፣የሚፈቀድላቸው ቦታዎች ላይ ሁሉ እየተገኙ ድጋፍ በማድረግ እስከመጨረሻው አብረዉን ነበሩ።
በእለቱ ስለተከሰተው ሁኔታ ምን ትላለህ?
እናቴ እንደነገረችኝ፣ በህፃንነቴ የወራት ዕድሜ ላይ እያለሁ፣ የሆነ ቀን ከታላቅ ወንድሜ መላኩ ገብሬ ጋር ከጎማ ላስቲክ የተሰራ አልጋ ላይ ተኝቼ ነበር። ቡና ስታፈላ ምንጊዜም ዕጣን ማጨስ እማትዘነጋው እናታችን፣ ያጨሰችዉን እጣን እኛ የተኛንበት አልጋ አጠገብ አስቀምጣው ኖሮ፣ እሷ ጎረቤት ደርሳ ስትመለስ ቤቱ በጭስ ተሸፍኖ ጨልሞ ጠበቃት። ጩኸቷን ለቀቀችው። ጩኸት ሰምቶ የመጣ ጎረቤት ነው አሉ ፈልጎ አግኝቶኝ በመስኮት ወደ ውጭ የወረወረኝ። ምህረቱ የተባልኩትም በዚያ ምክንያት ነው። እንዳጋጣሚ እሳቱ ቀድሞ የተያያዘው ወንድሜ በተኛበት በኩል ስለነበር እሱን ማትረፍ አልተቻለም።
የፈጣሪ ምህረት ዛሬም አልተለየኝም፡፡ በአውሮፕላኑ ላይ ሊደርስ ከሚችለው አሰቃቂ አደጋ አትርፎኛል። እንደትላንትናው ሁሉ ነገዬም በፈጣሪ እጅ እንደሆነች አምናለሁ። እርሱ ይሁን ያለው ሁሉ መልካም ነው። ቸርነቱ አይለየኝና ፍቃዱ ሆኖ ለነገ ካበቃኝ ለልጆቼ የምነግረው ተጨማሪ ታሪክ አግኝቻለሁ።
ደህና ነኝ እንኳን ብላት የማታምነኝ እናቴ ብርሃነማርያም ኪአን፣ እጮኛዬ ዮዲት ቦርሳሞን፣ ወንድሞቼን፣ ብቸኛዋን እህቴን፣ አክስቶቼን ከነቤተሰቦቻቸው፣ ጓደኞቼን፣ስለደህንነቴ የሚጨነቁልኝን ሁሉ ደህና መሆኔን ንገርልኝ። ከሁሉ አስቀድሞ ስለሆነውም ስለሚሆነዉም ክብር ሁሉ የእርሱ ነውና ፈጣሪ የሚገባዉን ክብር እና ምስጋና ይውሰድ።

Saturday, 22 February 2014 13:00

የቀልድ - ጥግ

ትንሽ     ስለ ቀልድ

ቀልድ መቼና እንዴት መጠቀም አለብን ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ ቀልድ በመደበኛም ሆነ በኢመደበኛ ንግግር ውስጥ መሠረታዊ ግብዓት ሆኖ ያገለግላል፡፡ ቀልድ ቅመም ነው፡፡ ወጥ በቅመም እንደሚጣፍጥ ሁሉ በጥንቃቄ መመረጥ፣ መመጠንና በትክክለኛው ሰዓት መጨመር ይኖርበታል፡፡ ቀልድ በትክክል ከተመጠነና ከተጨመረ በብርቱ ጥንቃቄ በበቃ ባለሙያ የተነገረውን ዲስኩር እንኳ የበለጠ አመርቂና ለታዳሚው እጅግ የሚጥም ያደርገዋል፡፡
ጆርጅ ጄሰል የተባለ ፀሐፊ፣ “ጥሩ ንግግር ልክ እንደጥሩ ካልሢ፣ ካልሢው በተሰራበት ጨርቅ ዓይነት ይወሰናል” ይላል፡፡ (የቻይናን አቃጣይ ካልሲዎች ልብ ይሏል) የቀልድ ጥግ የሚለው የአምድ-ሩብ፤ ታላላቅ ሰዎች፣ ነጋዴዎች፣ ወጣቶች፣ የጥበብ ሰዎች፤ በንግግር፣ በውይይት፣ በስብሰባ መግቢያና ሌሎች የዕለት ተዕለት የንግግር እንቅስቃሴዎቻቸው ውስጥ፤ ትኩስ የቀልድ ምንጭ እንዲሆን የታሰበና የተዘጋጀ ነው። ቀልዶቹ በዘርፍ የተከፋፈሉ ስለሆነ በአጫጭር ጭውውቶች፣ ገጠመኞች፣ ተረቦች፣ ውጋውጎች /witticisms/፣ የነገር አዋቂዎች አባባሎች፣ ተረቶችና የአንዳንድ ሀሳቦች ትርጓሜዎች ወዘተ እየተመረጠ የሚቀርብበት ነው፡፡
በመሰረቱ ቀልድ መጠቀም ያለብን አንድን መልዕክት ፅኑ ነጥብ ለማጠንከር ስንሻ ወይም የተደበረና የተኮሳተረን ታዳሚ ላላ ለማድረግ ስናስብ፤ አሊያም የከረረና የመረረ ስሜቱን በተለየ አቅጣጫ ለመቃኘት ስንፈልግ ነው፡፡
ቀልድ ሌላውን ሰው ወይም ታዳሚ ለማጥቃት የምንጠቀምበት መሆን የለበትም፡፡ ስለዚህ ከመጠቀማችን በፊት የታዳሚው ምላሽ ምን ይሆናል? ታዳሚው  ምን ይሰማዋል? ብሎ ማሰብ መልካም ነው፡፡ ለማረጋገጥ በራሳችን የቅርብ ሰው ላይ ሞክረን የሚያስከፋው መሆኑን ማጤን ይገባል፡፡
ቀልድ ለዛ የሚኖረው በቦታው ሲቀርብ፣ በሰዓቱ ስንገለገልበት ነው፡፡ ቀልድ በኮስታራ ንግግር ውስጥ ጣልቃ አስገብተን ከምንጠቀምበት ሰዎች ጀምሮ፤ ለመዝናኛ እንደማሺንገን የሚተኩሱ፣ እንደተልባ የሚንጣጡ ኮሜዲያኖች እስከሚጠቀሙበት ድረስ፤ የተለያየ የመገልገያ መንገድ አለው፡፡ ሆኖም ብዙዎች በዚህ ጉዳይ ላይ የተመራመሩ ፀሐፍት ቀልዶች አንድ ላይ እንደጥይት ዝናር ከሚደረደሩ ከቁምነገር ንግግሮች መካከል ጣልቃ ቢገቡ እንደለዘዘ ቆሎ ጥርስ ከማስቸገር ይድናሉ ይላሉ፡፡
እኛም ይህንን መንፈስ በማጠንከር የተወሰኑ ቀልዶችን ብቻ በየጊዜው እናቀርብላችኋለን፡፡
የቀልዶቹ ዘርፎች ለምሳሌ አንድ ሳምንት በሰካራሞችና በአካል ዙሪያ፣ በሌላ ሳምንት በዶክተሮችና በሕክምና ዙሪያ፣ ቀጥሎ በባንክና በባንከሮች ዙሪያ፣ ከዚያ በነጋዴዎችና በንግድ ዙሪያ እንቀጥላለን፡፡ እናንተም ያጋጠማችሁን የሰማችኋቸውን ብትልኩልን ደስ ይለናል፡፡ ሣምንት እንጀምርላችኋለን፡፡

“ቱሪዝም አሁንም ገና ጨቅላ ነው”
የአገሪቱን ቱሪዝም ምቅር ቤት የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው
አስጐብኚ ምንም ነገር አላውቅም ማለት የለበትም
ባለፈው የጥምቀት በዓል ሰሞን በጎንደር ከተከናወኑት ጉዳዮች አንዱ የጎንደር እህት ከተማ በሆነችው የፈረንሳይዋ ቬንሰን ከተማ ሁለገብ እድሳት ተደርጎለት የተጠናቀቀውን የ“ራስ ግንብ”ን ማስመረቅ ነበር፡፡
ግንቡ ራስ ሚካኤል ስሁልን ጨምሮ በርካታ የጎንደር ነገስታት ራሶች መኖርያ ስለነበር ነው፡፡ “ራስ ግንብ” የተባለው፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ ለ20 ዓመታት የፋሲል አብያተ-መንግስትን በማስጎብኘት እውቅናና አድናቆትን ካተረፉት
የቱሪዝም ከፍተኛ ኤክስፐርት አቶ ጌትነት ይግዛው ንጉሴ ጋር በጐንደር የቱሪዝም እንቅስቃሴ፣ በታሪካዊ ቅርሶች እድሳት፣
በአስጎብኝነት ህይወታቸው፣ እንዲሁም
በቱሪዝም ኢንዱስትሪና ተያያዥ
ጉዳዮች ዙርያ
ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡  

ወደ ፌደራል ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከመምጣትዎ በፊት የአፄ ፋሲል አብያተ መንግስትን ለ20 ዓመታት እንዳስጎበኙ ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ስለዚህ ጉዳይ ያጫውቱኝ …
ዌል! ይሄ ረጅም ጊዜ ነው፡፡ ለ 21 ዓመታት የቱሪስት ጋይድ ነበርኩ፤ የጎንደር አካባቢ ሲኒየር ጋይድ ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ ከዛ በኋላ የጎንደር ዓለም አቀፍ ቅርስ አስተዳደር (የአብያተ መንግስታት አስተዳደር) ማናጀር ሆንኩኝ፡፡ የዩኔስኮም ተጠሪ (ፎካል ፐርሰን) ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ የጎንደር ቅርሶች በዓለም አቀፍ ደረጃ የተመዘገቡ በመሆናቸው፣ አሁን እኔ ስራዬን ወደ ፌደራል ባህልና ቱሪዝም በመቀየር የዛሬ አንድ ዓመት ከአምስት ወር አካባቢ ጀምሮ የቱሪዝም ከፍተኛ ኤክስፐርት ሆኜ እየሰራሁ ነው፡፡
ጎንደርን ለመጎብኘት እጅግ በርካታ ቱሪስቶች ይመጣሉ፤ አንዱ ሲሄድ ሌላው እየተተካ በቀን ለብዙ ጎብኚዎች ገለፃ ማድረግ ይኖርብዎታል፡፡ አድካሚነቱ ምን ያህል ነበር?
የማስጎብኘት ሥራ የዲፕሎማሲ ስራ እንደመሆኑ የአገርን ታሪክ፣ የአገርና ህዝብን ባህል፣ የአገርን ኢኮኖሚና ፖለቲካ እያገናዘቡ፣ ህዝብንና አገርን ማዕከል በማድረግ ገለፃ የሚደረግበት ነው፡፡ እንዳልሽው የተለያየ ዓይነት ቱሪስት ነው የሚመጣው፤ ከአገር ውስጥም ከውጭም ማለቴ ነው፡፡ እጅግ በርካት የሆኑ ሰዎችን አግኝቻለሁ። ለምሳሌ የአገር መሪዎች፣ በርካታ የጥናትና ምርምር ስራ የሚሰሩ ባለሙያዎች፣ ለመዝናናትና አዲስ ተመክሮ ለመቅሰም የሚጓዙና መሰል ሰዎችን አግኝቻለሁ፡፡ ምክንያቱም ሁለት አስርት ዓመታት ቀላል አይደሉም፡፡ እንደውም ዝም ብዬ ሳስበው የያኔው ስራዬ አሁን ካለሁበት ስራ አንፃር ሲታይ እጅግ ውስብስብ ነበር፡፡ ምክንያቱም በቱሪዝም ህግ መሰረት አንድ አስጎብኚ “አላውቅም” አይልም፡፡ ስለዚህ የምትጠየቂውን ሁሉ መመለስ ይጠበቅብሻል፡፡ ስትመልሺ ታዲያ ታሪክሽን እንዳታዛቢ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ አለብሽ፡፡ ምክንያቱም አሁን በዓለማችን ውስጥ ከፍተኛ የታሪክ ሽሚያ አለ፡፡ ሃይማኖትን፣ ዘርንና ቀለምን ሳታይ ለሁሉም እኩል መስተንግዶ መስጠት ግዴታሽ ነዉ። ከዚህ አንፃር ሳየው በጣም የተወሳሰበና አድካሚ ነበር፤ ሆኖም ኃላፊነቴን በአግባቡ ተወጥቻለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡
የትምህርት ዝግጅትዎ ከቱሪዝም ሙያ ጋር የተያያዘ ነው?
የትምህርት ዝግጅቴ ከቱሪዝምና ከቅርስ አስተዳደር የወጣ አይደለም፡፡ ከሰርተፍኬት ጀምሮ እስከ ማስተርስ ዲግሪ የሰራሁት ከቱሪዝምና ከቅርስ አስተዳደር እስከ ሄሪቴጅ ማኔጅመንት ድረስ ነው። ለምሳሌ ማስተርሴን የሰራሁት በቱሪዝምና ሄሪቴጅ ማኔጅመንት፣ የመጀመሪያ ዲግሪዬ በቱሪዝም ማኔጅመንት፣ ዲፕሎማዬ በእንግሊዝ አገር ከሚገኝ ካምብሪጅ ኮሌጅ በቱሪዝም እና ትራቭል ኤጀንት ማኔጅመንት ሲሆን ሰርተፍኬቴን ያገኘሁት ደግሞ በአገራችን በቱሪዝም ዘርፍ ፈር ቀዳጅ ከሆነው CTTI ቱሪስት ጋይድ በተባለ ዘርፍ ነው፡፡ እንደምታይው ከቱሪዝም አልወጣሁም ማለት ይቻላል፡፡
አንዳንድ ጎብኚዎች በተለይም ከአውሮፓ እና ከሌሎች አህጉራት የሚመጡት የግንቦቹን አሰራር ረቂቅነት ሲመለከቱ እጃችን አለበት በማለት እንደሚሟገቱ ሰምቻለሁ፡፡ እነዚህን ዓይነት ፈታኝ ጥያቄዎች እንዴት ነበር የሚጋፈጧቸው?  
የዓለም ስልጣኔ መጀመሪያ የአፍሪካ አህጉር እንደሆነ በማስረዳት እጀምራለሁ፡፡ ምክንያቱም አገራችን የሰው ዘር መገኛ ሆና በዓለም ከታወቀችበት ጊዜ ጀምሮ እስካሁን በሌላ ዓለም ቀደምት የሰው ዘር ቅሪት አልተገኘም፡፡ ስልጣኔ የሚነሳው ደግሞ ከሰው ልጅ መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ሰው የኑሮ ጫናዎቹን ለማቃለል ደፋ ቀና ሲልና ለችግሮቹ መፍትሄ ሲፈልግ ነው ስልጣኔ እና ፈጠራ አብሮ የሚመጣው፡፡ የመጀመሪያው መልሴ ከላይ የገለፅኩት ነው፡፡ አውሮፓውያን የስልጣኔ ምንጭ አውሮፓ ናት ካሉ፣ ያ በእነሱ መልክ ነው የሚሆነው። አሜሪካኖችም እንዲያ ሲሉ በእነሱ መልክና እሳቤ ነው፡፡ ለምን ካልሽኝ … የዛሬ 400 ዓመት የተመሰረተች አገር፣ ከሶስት ሺህ ዓመት በላይ ታሪክ ካላት አገር ጋር እኩል መሆን አትችልም፡፡ የሰው ልጅ እስካለ የኪነ-ህንፃም ሆነ ሌላም ስልጣኔ ይኖራል፡፡ ይህን ሳስረዳቸው የዚያ ጥበብና ስልጣኔ ባለቤት እንደሆንን ያምናሉ፤ የመንፈስ ቅናት አድሮባቸው ካልካዱ በስተቀር ማለቴ ነው፡፡
ከኪነ-ህንፃ ጋር በተያያዘ በተለይ የውጭ ጎብኚዎች ምን ይላሉ? እንዴት ነው ስሜታቸው? ይገርምሻል! አግራሞታቸው ሰፊ ነው፡፡ ጥቁር ህዝብ ቤተ-መንግስት ውስጥ የሚኖርባት የአፍሪካ አገር መሆኗ ይገርማቸዋል፡፡ በእነሱ እምነት ቤተ-መንግስት ውስጥ የሚኖረው አውሮፓዊ ብቻ ነው፤ የታላቋ ብሪታኒያ ነገስታቶች፣ የፈረንሳይ ነገስታቶች ብቻ ይመስሏቸዋል፡፡ ይታይሽ … ከ16ኛው ክ/ዘመን መጀመሪያ አንስቶ እስከ 17ኛው ክ/ዘመን፣ በጎንደርና አካባቢዋ ከፍተኛ ቤተ-መንግስታት ተሰርተው ነበር፤ ስልጣኔውም ነበር፡፡ እንደሚታየው ግንባታው ከኖራ ጋር ተቀላቅሎ ዝም ብሎ የተሰራ ሳይሆን የኪነ-ህንፃ ልዩነቱን ጠብቆ በጥልቅ ፈጠራ የተገነባ ነው እና የኪነ-ህንፃ ጥበብ ያረፈባቸው፣ ገላጭ የሆኑ ህብረ-ህንፃዎች ናቸው፡፡ ይህን በአግራሞትና በመደመም ነው የሚመለከቱት፡፡ ከዚህ አንፃር የሚያነሱት ዘርፈ ብዙ ጥያቄዎች ማባሪያ የላቸውም፡፡
ከ400 ዓመት በላይ እድሜ ያላቸው የፋሲል አብያተ መንግስታት ግንባታዎችን ከአሁኑ ዘመን የኪነ-ጥበብ ህንፃ ጋር ማነፃፀር ይቻላል? እርስዎ ያነፃፅሩ ቢባሉ እንዴት ይገልፁታል?
እንግዲህ ውርስ ሊኖር ይችላል፤ የእውቀትና የቴክኖሎጂ ውርስ ማለቴ ነው፡፡ ነገር ግን ሙሉ በሙሉ ውርስ ይኖራል ብሎ መናገር ይከብዳል፡፡ የጎንደርን ኪነ-ህንፃዎች አንቺ ቅድም እንደገለፅሽው የውጭ ዜጎች ናቸው የገነቡት ይላሉ፤ እኔ በፍፁም በዚህ አልስማማም፡፡ የኪነ-ህንፃ ጥበብ ልክ እንደ ሙዚቃ የአለም ቋንቋ ነው፡፡ አንዲት አገር የራሷ ወጥ የሆነ የኪነ-ጥበብ ህንፃ የላትም፡፡ በምን ምክንያት ካልሽ … በእኛ በሰዎች ምክንያት፡፡ ሰው የተለያየ የህይወት ውህደት አለው፤ ይዘዋወራል፡፡ ሲዘዋወር አካባቢውን ይመስላል፤ ከአካባቢው የሚወስደውም ጥበብ ይኖራል፡፡
ያ ሰው ከሄደበት አካባቢ የወረሰውን ጥበብ፣ ሌላ ቀን የራሱ አድርጎ ይተረጉመዋል፤ ነገር ግን የነበረበት አካባቢ ተፅዕኖ ያርፍበታል፡፡ በዚህ የተነሳ ኪነ-ህንፃ የዓለም ቋንቋ ነው ይሉታል፡፡ እዚህ አካባቢ የፖርቹጋል፣ የህንድ፣ የአርመንና የሞሪሽየስ ዜጎች ነበሩ፡፡ በእርግጥ ከጎንደር በፊት የተሰሩ የአክሱም፣ የላሊበላና የየሀ ህንፃዎች አሉ፡፡ ሰዎች እስካሉ ድረስ እንኳን ጥበብ ዘርም ይቀያየራሉ፤ ከዚህ አንፃር የጎንደር ኪነ-ህንፃዎች የእነዚህ አገር ሰዎች ተፅዕኖዎች አለበት ይባላል፡፡
ከስድስቱ የፋሲል አብያተ መንግስታት አንዱ፣ በህንዳዊ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ እንደተሰራ ይነገራል። እውነት ነው?
እርግጥ አብዱልከሪም የሚባል ህንዳዊ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ በአፄ ፋሲለደስ ዘመን ነበር፡፡ እንደሚታወቀው አፄ ፋሲል አባታቸው አፄ ሱስንዮስ የካቶሊክን እምነት ለማስፋፋት ጥረት ያደርጉ ስለነበር በ1622 (ቅድመ ክርስቶስ ልደት) በርካታ ህዝብ አልቋል፡፡ አፄ ፋሲል ይህን አልተቀበሉም ነበር፡፡ የንግስና ዙፋኑን ሲይዙ 7 ሺህ ገደማ የካቶሊክ ሚሽነሪዎችን ከኢትዮጵያ አስወጥተዋል፡፡ የዛን ጊዜ ታዲያ ኢትዮጵያ ቢያንስ ለ200 ዓመት በሯን ለአውሮፓውያን  ዘግታ ነበር፤ ይህ “የጨለማ ዘመን” እያሉ የሚጠሩት ነው፡፡ ስለዚህ አብዱልከሪም የተባለው ህንዳዊ ሰውዬ ምንም እንኳ ሙስሊም ቢሆንም በኪነ-ህንፃ ጥበብ የተካነ ስለነበር፤ ከአባ ገ/እግዚያብሔር ጋር በመሆን የንጉስ አፄ ፋሲልን ቤተ መንግስት እንዲሰራ ተደርጓል፡፡ በዚህ ምክንያት የህንዶች ኪነ-ህንፃ ተፅዕኖ አለበት፡፡
እስቲ ወደ እርስዎ የአስጎብኚነት ጊዜ እንመለስ። ዝነኛ አስጎብኚ እንደነበሩና እንደነ ሲኤንኤን፣ ቢቢሲ እና መሰል ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ዘጋቢ ፊልም ለመስራት ሲመጡ፣ በሰከንድ 120 ዶላር ለእርሶ እየከፈሉ በሙያዎ ያገለግሏቸው እንደነበር ሰምቻለሁ፡፡ እውነት ነው? እስቲ ያጫውቱኝ…
ይህ እንግዲህ በፈረንጆቹ 1991 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ ያኔ “ፍሮም ፖል ቱ ፖል” የተሰኘ ፊልም ተሰርቶ ነበር፡፡ የዛን ጊዜ አብሬ ሰርቻለሁ፤ ክፍያው በሰከንድ ሳይሆን በሰዓት ነበር፡፡ በሰዓት 150 ዶላር! ለእኛ አገር ትልቅ ይመስላል እንጂ ለእነሱ በጣም ዝቅተኛ ክፍያ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ገና ከለንደን ከመነሳታቸው ከአንድ ወር በፊት ነው አፈላልገው ያገኙኝ፡፡ ከዚያም ያንን ፊልም ሰርተናል፡፡ ከቢቢሲ በኋላ ከሌሎችም የፊልም ቡድኖች ጋር ብዙ ስራዎችን ሰርተናል፡፡ ለምሳሌ ከጀርመንና ከጣሊያን፣ የፊልም ቡድኖች ጋር ሰርቻለሁ፡፡ ከፍተኛ የህይወት ልምድም አግኝቼበታለሁ፡፡
በጎንደር ከተማ የመንግስት ሰራተኛ ሆነው መኪና የነበረዎት ብቸኛው ሰው እንደነበሩም ሰምቻለሁ …
(ሳ…ቅ!) በአንዳንድ አጋጣሚ በግልሽ ቢዝነስ ስትሰሪ ገንዘብ ታገኛለሽ፡፡ ስለዚህ መኪና መግዛት ቻልኩ፡፡ የዛን ጊዜ መኪና እንደአሁኑ ውድ አልነበረም፤ እኔ በገዛሁበት ወቅት 50ሺ ነበር ዋጋው። የዛሬ 12 ዓመት አካባቢ ማለት ነው፡፡ እርግጥ ያኔ ብሩ በደንብ ዋጋ ነበረው፡፡ ስለዚህ በዚያን ወቅት መኪና መግዛት ያን ያህል የሚያስደንቅ ነገር አልነበረም፡፡
የበፊቷ መኪና ተቀየረች ወይስ…
አልተቀየረችም ራሷ ናት፤ አዲስ አበባ ነው አሁን ያለችው፡፡
ስለ አገራችን ቱሪዝም ስታስብ የሚቆጭህ ነገር ምንድን ነው?
አሁን የሚቆጨኝ ነገር የለም! እኔ ቱሪዝምን በአስተሳሰብ ደረጃ ተረድቼ ስሰራ በነበረበት ወቅት ብዙ ሰው ገና አልተረዳውም ነበር፡፡ ቱሪዝምን የምቾት፣ የቅንጦትና የመዝናናት አድርገው የሚያዩት ወገኖች ነበሩ፡፡ ቱሪዝም ግን እንደዛ አይደለም፡፡ ቱሪዝም የስራ እድል ፈጣሪ ነው፤ ዳቦ ነው፤ ሰላም ነው፤ ሁሉም ነገር ማለት ነው፡፡ አገርሽ ውስጥ ያለውን የባህልና የታሪክ ቦታዎች የምትሸጭበትና የስራ እድል የሚፈጥር ኢንዱስትሪም ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ሲታይ የዚያን ጊዜ ሰዎች ቱሪዝምን የተረዱበት አስተሳሰብ ትክክል አልነበረም፡፡ እናም ሰው መቼ በትክክል እንደሚገባው፣ ገብቶትም መቼ ወደ ቢዝነስ እንደሚቀይረውና ተጠቃሚ የሚሆንበትን ቀን እናፍቅ ነበር፡፡ በአሁኑ ሰዓት ግን ሁሉም ሰው ስለቱሪዝም ያወራል፡፡ ስለ ገፅታ ግንባታው፣ ስለ ስራ ፈጣሪነቱና ስለተያያዥ ጉዳዮች ሰው ሲናገር ስሰማ በጣም እደሰታለሁ፤
ምክንያቱም ማንም ሳይረዳሽ ብቻሽን ስለቱሪዝም የምታወሪበት ጊዜ አልፎ አሁን አጋር ስታገኚና ሰው ሲገባው በጣም ያስደስትሻል፡፡
በወሬ ብቻ ነው ወይስ በተግባርም ነው?
አገሪቱ በዚህ ቅኝት ውስጥ እየገባች ነው ብሎ መናገር ይቻላል፡፡ ምክንያቱም ወደ ኢንዱስትሪው እንሸጋገራለን የሚል እቅድ ላይ ነው ያለነው፡፡ ወደ ኢንዱስትሪ ዘመን ሲገባ የበለጠ የሚያይለው የአገልግሎቱ ዘርፍ ነው፡፡ አሁን አገራችን ወደዚያ እየሄደች ነው፡፡ የቱሪስቱ ፍሰት እየጨመረ ነው። የበላይ አመራሮችና ውሳኔ ሰጪ አካላትም ስለቱሪዝም እያቀነቀኑ ነው፡፡ የትራንስፎርሜሽን ኤጀንሲ ተቋቁሟል፡፡ ከዚያ ባሻገር የአገሪቱን የቱሪዝም ምክር ቤት የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው፡፡ ይህን ስታይ አገሪቱ ወደ ቅኝቱ ገብታለች ማለት እችላለሁ፡፡ እና ቁጭት የለኝም፤ እንዲያውም በጣም ደስታ ነኝ፡፡
ጎንደር ባሏት ታሪካዊ መስህቦች የሚገባትን ያህል ተጠቅማለች ይላሉ?
እዚህ ላይ ነው ወሬ የምናቆመው! ከተማዋ ያላትን ሀብት በአግባቡ አልምታ፣ የህብረተሰቡን ግንዛቤ አሁን ካለው የበለጠ አስፍታ፣ ህዝቡን ቀጥተኛ ተጠቃሚ አድርጋ የማስኬድ ስራ ገና ይቀራታል፡፡ ቱሪዝም ኢትዮጵያ ውስጥ የ30 እና የ40 ዓመት እድሜ ነው ያለው፡፡ ቅርስ አጠባበቅም እንደዚሁ! ምክንያቱም ቱሪዝም ካልሽ የምትሸጪው ቅርስ ስለሆነ፡፡ ኢትዮጵያ እኮ ከ80 በላይ ብሄር ብሄረሰቦች፣ ከ35ሺህ በላይ ገዳማትና ቤተክርስቲያናት፣ ከ25 በላይ ከፍታቸው ከ4ሺህ ሜ በላይ የሆኑ ተራሮች፣ በምስራቅ አፍሪካ ትልቁ የስምጥ ሸለቆ ስክራች መነሻና ሌሎች አገሮችን የሚያቋርጥ ስምጥ ሸለቆ እንዲሁም አሁንም በአይን የሚታይና አክቲቭ የሆነ እሳተ ጎመራ ያላት ናት። ይህም ሆኖ ቱሪዝም አሁንም በአገራችን ጨቅላ ነው፡፡ ይህንን ወደ ጥቅም ለመለወጥ እኔም፣ አንቺም ሌላውም በየሞያው የቤት ስራ አለበት፡፡ አለቀ፡፡
አሁን ቆመን የምንነጋገርበት ቦታ በእነ ፋሲለደስ ዘመን ራሶችና ተመሳሳይ ስልጣን የነበራቸው ሰዎች የሚኖሩበት “ራስ ግንብ” ነው፡፡ ዛሬ እዚህ ቦታ የተገናኘነውም የጎንደር እህት ከተማ በሆነችው የፈረንሳይ ቬንሰን ከተማ እድሳት ተደርጎለት የምርቃት ስነ-ስርዓቱ በመሆኑ ነው፡፡ በእድሳቱ የተነሳ “ራስ ግንብ” ብቻ ሳይሆን ሌሎችም አብያተ መንግስታት ምንነታቸውን እና የቀድሞ መስህብነታቸውን ያጣሉ የሚል ስጋት አለ፡፡ ይህ እንዳይሆን ምን ምን ቅድመ ጥንቃቄዎች ይደረጋሉ?
አሪፍ ጥያቄ ነው! አገራችን እንደምታውቂው የገንዘብ እጥረት አለባት፡፡ ይህንን ነገር ለመሸፈን ከተሞች አንዳንድ ሁነቶችን ማዘጋጀት አለባቸው፡፡ የገንዘብ ሁኔታ እንዲጎለብት የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመፍጠርና ስምምነቶችን በማድረግ፣ ከእነዚያ የአውሮፓ ከተሞች ተሞክሮዎችን ይወስዳሉ፤ በገንዘብም ይደጎማሉ፡፡ የጎንደር የቬንሰን ታሪክም ይሄ ነው፡፡
ይህን ፕሮጀክት የጀመሩት እርስዎ ነዎት ይባላል?   
ትክክል ነው! ፕሮጀክቱን የጀመርኩት እኔ ነኝ፡፡ ፕሮጀክቱን ቢያንስ ለስድስትና ለሰባት ወር ብቻዬን ነው የሰራሁት፤ ማንም ሰው አያውቅም ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ነው በግልፅ ወደ ከንቲባ ጽ/ቤትና ወደ ከተማ አስተዳደሩ ያሸጋገርነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ጎንደር የቬንስን እህት ከተማ እንደመሆኗ፣ የእነሱም ከተማ ስለሆነች ይህን ራስ ግንብ ማደስ እንደሚፈልጉና የሙዚየም፣ የሀንድክራፍትና የቱሪዝም ልማነት እንዲሆን ገንዘቡን አቀረቡ፡፡ የግንቡ ፕሮጀክት አራት ምዕራፍ ነው ያለው፡፡
አንዱ ሙዚየም ልማት ነው፡፡ ሁለተኛው የሀንድክራፍት ልማት ሲሆን ሶስተኛው ቱሪዝም ልማት ነው፡፡ አራተኛው ደግሞ ግንቡን መጠገን ነው፡፡ አሁን የተሰራው የፕሮጀክቱ አራተኛ መዕራፍ ነው፡፡ የግንቡ ጥገና አልቆ ዛሬ ሊመረቅ እስፍራው ተገኝተናል፡፡
ይህ ግንብ ሲጠገን፣ የዩኔስኮ ንብረት የዓለም ህዝብ ንብረት በመሆኑ፣ ሶስት ነገሮች መጠበቅ አለባቸው፡፡
አንደኛው ኦተንትሲቲ (የዱሮ ይዞታውን የጠበቀ መሆን አለበት)፣ ይህ ማለት ለእድሳቱ የምንጠቀመው እንጨት፣ ድንጋይና ሌሎች ቁሳቁሶችም ጭምር የዱሮ መሆን አለባቸው ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ድሮ ከነበረው ከባቢ ጋር ቅንጅት (integrity) ያለው መሆን አለበት።
ከኢትዮጵያ ኪነ-ህንፃ ሁኔታ ጋር የተስማማና የተቀናጀ መሆን አለበት፡፡ በሶስተኛ ደረጃ “ሲንክሮናይዜሽን” የሚባል ነገር አለ፡፡ ይሄ ማለት አዲስ እንጨት ለእድሳቱ ካስገባሽ አዲስ ለመሆኑ ምልክት ማስቀመጥ አለብሽ፡፡ እነዚህ ሶስት መሰረታዊ ጥንቃቄዎች ተሟልተው ሲታደሱ ቅርሱ የቀደመ ምንነቱን አያጣም፡፡ ይህ ራስ ግንብም በዚህ መሰረት ነው የታደሰው፡፡
እርስዎ ሃገርዎን እንደሚያስጎበኙት ውጭ አገራትን የመጎብኘት ዕድል ገጥመዎታል? እስቲ ስለሌሎች አገራት አስጎብኚዎች ይንገሩኝ…
ለጉብኝት የሄድኩባቸው የውጭ አገሮች ብዙ ላይሆኑ ይችላሉ፤ ነገር ግን በሌላም ስራ የሄድኩባቸው ብዙ ቦታዎች አሉ፡፡ ከአፍሪካ ብንጀምር ሱዳን፣ ኬንያ፣ ዚምባብዌ… ወደ አውሮፓ ስንመጣ ትምህርቴን አልጨረስኩም እንጂ የመጀመሪያ ስኮላርሺፕ ያገኘሁት ቡልጋሪያ ነበር። ምስራቅ አውሮፓን ብትወስጂ ሀንጋሪ፣ ራሺያ እና ሌሎችንም አውቃለሁ፡፡ ከምዕራብ አውሮፓ ፈረንሳይን አይቻለሁ፡፡ ሁለት ጊዜ የመሄድ እድል ገጥሞኛል፡፡ ህንድ ሄጃለሁ፡፡
እንግሊዝም እንዲሁ። የማስጎብኘት ሁኔታው እንደየአገሩ ይለያያል፡፡ በሄድኩባቸው ቦታዎች ሁሉ ጉብኝት አድርጌያለሁ፤ ለቬንሰንም ጉዳይ ፈረንሳይ ሄጃለሁ፣ በአስጎብኚም ጎብኝቻለሁ፡፡ አስጎብኚ ለመሆን የታሪክ ሰው መሆን ያስፈልጋል ብለው ያምናሉ?
የታሪክ ሰው መሆን ያን ያህል ላያስፈልግ ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን ጥሩ ነው፡፡ ዋናው ልብ ልንል የሚገባው አስጎብኚ ሁሉም ነገር ማለት ነው፡፡ ቀደም ሲል እንዳልኩት አስጎብኚ ምንም ነገር “አላውቅም” ማለት የለበትም፡፡
ፖለቲከኛ፣ የባዮሎጂ ሰው፣ የጂኦሎጂ ሰው፣ አርኪዎሎጂስት፣ የታሪክ ሰው፣ …ሁሉንም መሆን አለበት፡፡
ዘርፈ-ብዙ እውቀት ያስፈልገዋል፡፡

የጥብቅና ሞያን በፈቃደኝነት ላይ በተመሰረተ የሲቪክ ማኅበር ማስተዳደር አይቻልም
የሌሎች አገራት የሕግ ባለሞያዎች ወይም የጠበቃ ማኅበራት የሚሰሩት እንዴት ነው?
የህግ ባለሙያ ድርጅቶች (ፈርሞች)  ስላላቸው ፋይዳ ያብራራሉ
በቅርቡ የአገር አቀፍ የፍትህ ዘርፍ የፍትህና መልካም አስተዳደር መድረክ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በተገኙበት ተካሂዶ ነበር፡፡
በመድረኩ ላይ በተለይ ከጠበቆች የሥነምግባር ችግሮች ጋር በተገናኘ በተነሱ ጉዳዮች ዙርያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ ከጠበቆች ማህበር ፕሬዚደንት አቶ ወንድምአገኘሁ ገብረስላሴ ጋር ሰፊ ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡


የአገር አቀፍ የፍትሕ ዘርፍ የፍትሕና መልካም አስተዳደር መድረክ ጉባዔ እንዴት ነበር?
 ጥሩ ነበር፡፡ በፍትሕ ሥርአቱ ላይ የሚታዩ በርካታ ችግሮች ተነስተዋል፡፡ መፍትሔም ሊሆኑ ይችላሉ የተባሉ ኃሳቦች ቀርበዋል፡፡ ችግሮቹንም ለማቃለል እቅድም ተዘጋጅቷል፡፡ የታሰቡት ነገሮች በሙሉ እንኳን ባይሆኑ በአብዛኛው ሥራ ላይ ከዋሉ መልካም መሻሻሎች ሊታዩ ይችላሉ ብዬ እገምታለሁ፡፡
 ከተነሱት ችግሮች አንዱ የሕግ ባለሞያዎች ወይም ጠበቆች በፍትሕ አሰጣጥ ረገድ መደገፍና መርዳት ሲገባቸው ፍትሕ እንዲጨናገፍ ያደርጋሉ፣ ጉቦ ያቀባብላሉ፣ ከጥብቅና ሥነምግባር ውጭ ይሰራሉ የሚል ነው፡፡ በዚህ ወቀሳ ላይ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው?
 በስብሰባው ላይ ከፍተኛ ትኩረት ተሰቶት ከነበረው መሰረተ ሃሳብ አንዱ ሁልጊዜ ውጫዊ ምክንያቶች ላይ ብቻ ከምናተኩር የራሳችንን የውስጣችንን ሁኔታ እንመርምርና ለችግሮቻችን መፍትሔ እንስጥ የሚል ነው፡፡ በዚህም ላይ ተመስርቶ በዳኝነት ሥርዓቱ ላይ የሚታዩ ችግሮች፣ በአቃቤ ሕግ መሥሪያ ቤት ላይ የሚታዩ ችግሮች፣ በፖሊስ እና በሌሎችም ተዛማጅነት ባላቸው ተቋማት ላይ የሚታዩ በጣም በርካታ ችግሮች ተነስተዋል። እንደውም ለጉባኤው የቀረበው ሪፖርት በዋናነት ያተኮረው ችግሮች ላይ ብቻ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ይህ እንግዲህ ቀደም ሲል ከሚታዩት ሪፖርቶች ጋር ሲነፃፀር በጣም የተለየ ነው፡፡ በአብዛኛው በየቤታችን የምናነሳቸው ችግሮች በሪፖርቱ ውስጥ ተካተዋል። ችግሮቹ በዚህ አይነት መልክ ተነቅሰው ከወጡ ደግሞ ፈቃደኝነትና ቅንነት ታክሎበት መፍትሔ ሊያገኙ ይችላሉ የሚል ተስፋ ይሰጣል። ከዚህ አኳያ ሲታይ የሕግ ባለሞያዎች በተለይም ደግሞ ጠበቆችን በተመለከተ የቀረበው ሪፖርት፣ በሌሎቹ የፍትሕ ሥርዓት አካላት ላይ ከሚታየው ችግር የተለየ እንዳልሆነ ማየት ይቻላል፡፡ ጉቦ ሰጭ አለጉቦ ተቀባይ አይኖርም፡፡ ፈረንጆቹ እንደሚሉት ታንጎ ለመደነስ ሁለት ደናሾች ያስፈልጋሉ፡፡ ስለዚህ ችግሩ በሁሉም ቤት ያለ ነው ማለት ነው፡፡ እኛም ብንሆን የምንሰማቸው ስሞታዎች አሉ፡፡ እንዲያውም ብዙ ጥሩ ችሎታና ሥነምግባር ያላቸው ጠበቆች፣ ከሚያዩትና ከሚሰሙት ችግር ለመሸሽ ከሥራው የመራቅ ሁኔታ ሁሉ ይታያል፡፡ ከዚህ በፊት ቅር ያሰኘን የነበረው ወቀሳ “ጠበቆች ሲባሉ በአብዛኛው ችግር አለባቸው” የሚል አንድምታ ያለው አገላለፅ ይቀርብ ስለነበር ነው፡፡ የችግሩም ምክንያቶች ጠበቆች ብቻ እንደሆኑ በሚመስል ሁኔታ ነበረ የሚገለጸው፡፡ በዚህኛው ጉባኤ ላይ ግን አጥፊዎች ቢኖሩም ብዙዎቹ ጠበቆች  የሞያ ስነምግባራቸውን አክብረው እንደሚሰሩ፣ እንደውም ከእነዚህ ጠበቆች ጋር በመሆን ችግሩን ተጋፍጠን እናስተካክለዋለን የሚል መንፈስ የተንፀባረቀበት በመሆኑ ከቀደሙት ጊዜያት በጣም የተሻለና የተለየ ነው፡፡ እኔም ከጠበቅሁት በላይ አስደስቶኛል፡፡
 ጥብቅና ሞያ እንደመሆኑ መጠን የሞያውን ስነምግባር ሳያከብሩ መገኘትን እንዴት ያዩታል?
 እውነት ነው፤ ጥብቅና በጣም ረጅም ዕድሜ ያለው ሞያ ነው፡፡ እንደውም እስከቅርብ ዘመን ድረስ እንደ ሞያ ይቆጠር የነበረው የሕግ ሞያና ሕክምና ነበር፡፡ እነዚህ ሞያዎች የእድሜያቸውን ርዝመት ያህል በጣም በርካታ የሞያ ደንብ፣ ስነምግባርና ዲሲፕሊን ያላቸው ናቸው፡፡ ሞያ እንዲባሉ ካበቃቸውም ነገር አንዱ የሞያ ሥነምግባርና ዲሲፕሊን ያላቸው መሆናቸውም ጭምር ነው፡፡ ከዚህ አኳያ ሲታይ አንዳንድ የሞያው አባላት ጉድለት ሲታይባቸው ማሳዘኑ አይቀርም፡፡ የስነምግባርና ዲስፕሊን ጉድለቶች በሞያው ክብርና ግርማ ሞገስ ላይ የራሳቸውን ጥላ ማጥላታቸው አይቀርም፡፡ ታዲያ በዚህ ሁኔታ ጉዳቱ አመዝኖ የሚታየው ችግሩን በፈጠሩት ሰዎች ላይ ሳይሆን በአጠቃላይ በሞያው እና ስርአት ጠብቀውና አክብረው በሚሰሩ ባለሞያዎች ላይ ነው፡፡ የዚህ አይነት ችግር እየተስፋፋ ሲሄድ፣ የሚጎዳው ችግር ፈጣሪውን ሳይሆን መልካም ስነምግባር ያለውን ባለሞያ፣ የፍትሕ ሥርዓቱንና አገርን በአጠቃላይ በመሆኑ አሳሳቢ ችግር መሆኑ አይካድም፡፡ እንደግለስብ እንዲሁም እንደ የሕግ ባለሞያዎች ማኅበር መሪነቴ በጣም ያሳስበኛል፡፡ ያሳዝነኛልም። ሆኖም ግን ሁላችንም ሰዎች በመሆናችን የተለያየ አስተሳሰብ፣ እምነትና አመለካከት ሊኖረን ይችላል። በዚህም የተነሳ ምንም ጊዜ ቢሆን ከመስመር ወጣ የሚሉ ሰዎች መኖራቸው አይቀርም፡፡ የሕግ ሞያ ከዚህ ሙሉ በሙሉ ንጹህ ይሆናል ብሎ መጠበቅም አይቻልም፡፡ አልፎ አልፎ ደግሞ ሆን ተብለው ሳይሆን በአጋጣሚ የሚፈጠሩ የሥነምግባር ጉድለቶችም ይኖራሉ፡፡ ዋናው ነገር ችግሮች ለምን ይፈጠራሉ ወይም መፈጠር አልነበረባቸውም ብሎ ማማረር ብቻ ሳይሆን ችግሮች እንዳይፈጠሩ የሚረዳ፣ ችግሮች በተለያየ ሁኔታ ከተፈጠሩም በኋላ አግባብ ባለው ሁኔታ የእርምት እርምጃ የሚወስድ ተቋማዊ ስርአት ማደራጀትና በአግባቡ እንዲሰራ ማድረግ ነው፡፡ ይህ የሆነ እንደሆነ የስነምግባርም ሆነ ሌሎች ችግሮች እንደሁኔታው አፋጣኝ፣ አግባብ ያለውና ፍትሐዊ የሆነ መፍትሄ ያገኛሉ፡፡ ይሄን እውን ለማድረግ መሥራት አለብን ብዬ አምናለሁ፡፡  
እስካሁን  ይህን ችግር ለማቃለል ወይም ለማስወገድ ምን የሠራችሁት ሥራ አለ?
 ጥሩ ጥያቄ ነው፡፡ ይህንን ጥያቄ ለመመለስ ግን ትንሽ የማኅበራችንን ባሕርይ ማየት የሚያስፈልግ ይመስለኛል፡፡ ምናልባት እንደምታውቀው፣ ማኅበራችን የተቋቋመው በ1957 ዓ.ም ሲሆን ሲቋቋም የነበረው ዓላማ የመረዳጃ ዕድር መልክ የያዘ ነበር፡፡ ቀስ በቀስ እና ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ  ዓላማውን በማሻሻል የጠበቆች ማኅበር ሲባል ቆይቶ አሁን ደግሞ የሕግ ባለሞያዎች ማኅበር ለመሆን በቅቷል፡፡ በ2002 ዓ.ም ተሻሽሎ የፀደቀው የማኅበሩ ዓላማዎች፣ የፍትሕ አስተዳደር በተቀላጠፈ ሁኔታ እንዲካሄድ መርዳት፣ የፍትሕ ስርአቱ እንዲሻሻል ማገዝ፣ የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን መርዳት፣ የሕግ ሳይንስ (jurisprudence) እንዲዳብር መርዳት፣ የሙያ ሥነምግባር ደረጃውን የጠበቀ እንዲሆን መጣር፣ አቅም ለሌላቸው ሰዎች ነፃ የሕግ አገልግሎት መስጠት፣የሕብረተሰቡ የሕግ ንቃተ ህሊና እንዲድግ መስራት፣ በአባላት መካከል መቀራረብና መተባበር እንዲዳብር ማድረግ የሚሉት ወዘተ.. ሲሆኑ፣ ማንኛውም የሕግ ባለሞያ የሆነ ሰው አባል መሆን ይችላል፡፡ ማለትም ማኅበሩ የፈቃደኝነት ማኅበር ነው፡፡ ጠበቃም፣ ዓቃቤ ሕግም፣ የሕግ ት/ቤት መምሕራን፣ በመንግሥት መሥሪያ ቤት ውስጥ የሚሰሩ የሕግ ባለሙያዎችም ወዘተ. አባላት ሊሆኑ ይችላሉ። የፈቃደኝነት ማኅበር በመሆኑም ሊሰራ የሚችለው አባላቱን በማስተባበርና መልካም ሥነምግባርን መከተል እንዳለባቸው፣ የሞያው ክብርና ሞገስ እንዲያድግ የድርሻቸውን እንዲወጡ በመምከርና በማሳሰብ ነው፡፡ ይህ ደግሞ የውይይትና የሥልጠና ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት፣ማሳሰቢያዎችን ከመስጠት ያለፈ አይደለም፡፡ የስነምግባር ጉድለት የሚፈጽሙ የሕግ ባለሞያዎችን ወይም አባላቱን የሚያርምምበት ወይም የዲሲፕሊን ቅጣት የሚጥልበት ኃይልና ስልጣን የለውም፡፡ በርግጥ አባላት በውሳኔያቸው ማኅበሩ ዲሲፕሊን እንዲቆጣጠርና ጥሰት በሚፈጽሙ አባላት ላይ የቅጣት ውሳኔ እንዲያሳልፉ መስማማት ይችላሉ። ይህ ግን ሊሆን የሚችለው በአባላቱ ላይ ብቻ ሲሆን አባላቱም ቢሆኑ በዚህ ውሳኔ እስካልተስማሙ ድረስ ማኅበሩን ለቀው መውጣት ይችላሉ፡፡ ስለዚህ ማኅበሩ የራሱ የሆነ ምንም አይነት አስገዳጅ ሥልጣንና ኃይል የለውም። ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ሊያደርግ የሚችለው አባላቱ በበጎ ፈቃዳቸው የሞያው ሥነምግባር ተገዢዎች እንዲሆኑ ማበረታትና መምከር ነው። ይህንን ደግሞ አቅም በፈቀደ መጠን በማድረግ ላይ እንገኛለን፡፡ ሲጠቃለል፣ የኛ ማኅበር በአባላት የተቋቋመ የሲቪክ ማኅበር ነው፡፡ ከዚህ የተለየ ሥራ መስራት አይቸልም፡፡  የሌሎች አገር የሕግ ባለሞያ ወይም የጠበቃ ማኅበራት ግን ሰፋ ያለ ኃይልና ሥልጣን አላቸው፡፡
 እንዴት ነው የሌሎች አገራት የሕግ ባለሞያዎች ወይም የጠበቃ ማኅበራት የሚሰሩት?
የሌሎች አገራትን በተመለከተ የተለያዩ ልምዶች መጥቀስ ይቻላል፡፡ መሰረታዊው ነጥብ ግን የጠበቆች ማኅበራት ሦስት ዋና ዋና ተግባራትን ያከናውናሉ፡፡ 1. ሞያውን የማስተዳደር፣ ማለትም ፈቃድ መስጠት፣ የዲሲፕሊን ደንቦችን የማስከበርና የማስፈጸም፣ የሕግ ትምሕርት የሚሰጥበትን ደረጃ መወሰን፣ ለጠበቆች ተከታታይ የሕግ ሞያ ስልጠና መስጠት፣ ከዳኝነት አካሉና ከሕግ አስፈፃሚው አካል ጋር የጥብቅና ሞያንና ሥራን በተመለከተ ተፈፃሚ በሚሆኑ ደንቦች፣ ሥነሥርአቶች፣ የሥነምግባር ደንቦች እና በመሳሰሉት ጉዳዮች ላይ በጋራ መሥራት እና የመሳሰሉትን ሥራዎች ማከናወን፤ 2. የሕዝብ አገልግሎት ሥራዎችን መስራት፣ ማለትም፣ ከፓርላማ ጋር በመተባበር የሚሰሩ ተግባራትን ለምሳሌ በሕግ ረቂቆች ላይ በሚደረግ ዝግጅት፣ ውይይት መሳተፍ፣ አስተያየቶችን አዘጋጅቶ ማቅረብ፣ ነፃ የሕግ አገልግሎት መስጠት፣ ለሕግ የበላይነትና የፍትሕ ሥርዓቱ እንዲጠናከር መስራት፣ 3. ሞያውን መወከል፣ ይህ የሞያ ማኅበር ወይም የዩኒየን ተግባራትን የሚመለከት ሲሆን፣ ሞያውን በመንግሥትና በተለያዩ ወገኖች ዘንድ መወከል፣ ከሌሎች የሞያና ሲቪክ ማኅበራት ጋር መስራት፣ ሕግን፣ የሞያ ስነምግባርን በጠበቀ መልኩ ለአባላት መብትና ጥቅም መቆምን ይጨምራል። በብዙ ሀገራት የሞያ ማኅበራቱ መጀመሪያ በፈቃደኝነት ላይ ተመስርተው ከተቋቋሙ በኋላ ቀስ በቀስ በሕግ የተቋቋሙበት ሁኔታ ነው ያለው፣ ለምሳሌ በአሜሪካ ማኅበራቱ ሦስቱንም ተግባራት ያከናውናሉ፡፡ እንደ እንግሊዝ ባሉ ሀገራት ደግሞ የሞያ ማኅበራቱ በረጅም ጊዜ እየዳበረ የመጣ በኮመን ሎው ላይ የተመሰረተ ሦስቱንም ሥራዎች የመሥራት ሥልጣን አላቸው፡፡ የእንግሊዞቹ እንደውም ከአራት መቶና እና አምስት መቶ አመት በላይ እድሜ ያላቸው ናቸው፡፡ በፈረንሳይ ደግሞ አደረጃጀታቸው ከፍርድ ቤቶች ጋር የተያያዘ ሲሆን ሞያውን የማስተዳደር፣ ፈቃድ የመስጠት፣ የዲሲፕሊን አርምጃ የመውሰድና የሕዝብ አገልግሎት ሥራዎችን የመሥራት ስልጣን አላቸው፡፡ በህንድም የዚሁ አይነት አሰራር ነው ያለው፡፡ የብራዚል የጠበቆች ማኅበር ከ750,000 በላይ አባላት ያሉት ሲሆን የጥብቅና ሞያውን የማስተዳደር፣ ሞያውን የመወክል እና የሕዝብ አገልግሎት ተግባራትን ያከናውናል። እዚሁ አቅራቢያችን የሚገኙት የኬንያ፣ የኡጋንዳ፣ የታንዛንያ የጠበቆች ማኅበራትም በሕግ እንዲቋቋሙ ተደርገው ሞያውን በተለያየ ደረጃ የማስተዳደር፣ የመወከል እና የሕዝብ አገልግሎት ተግባራትን ያከናውናሉ፡፡ በነዚህ ማኅበራት ውስጥ አባል መሆን ግዴታ ነው፡፡ በአንዳንዶቹ ሀገራት ቀድሞ ነገር በማኅበራቱ መመዘኛ መሰረት ትምሕርት ወስዶ፣ ፈተናውን አልፎ ጠበቃ መሆን ይችላል ያልተባለ ባለሞያ፣ በማናቸውም ፍርድ ቤት ቆሞ ሊከራከር አይችልም። ስለዚህ ፈቃዱን ካገኘ በኋላም የስነምግባር ጉድለት ፈጽሞ ቢገኝ የሚቀጣው በማኅበሩ ነው፡፡ ቅጣቱም የጥብቅና ፈቃድ እስከመሰረዝ ሊደርስ ይችላል፡፡ ስለዚህ የጠበቆች ማኅበራቱ በቂ አቅምና ኃይል አላቸው፡፡ አባላቶቻቸውን ያስተምራሉ፣ ይመክራሉ፣ ይገስፃሉ፣ ይቀጣሉ፡፡  በነዚህ ደረጃዎች የማይታረም አባል ከማኅበሩ ይባረራል፤ የጥብቅና ሥራ እንዳይሰራ ይደረጋል፡፡  
ወደኛ አገር ስንመለስ ታዲያ ማኅበሮቻችን በጣም የተወሰነ ተግባር ያላቸው ሲሆኑ ሞያውን የማስተዳደር ምንም አይነት ሥልጣን ስለሌላቸው፣ የስነምግባር ጥሰቶችን የመከታተልና የማረም ሥራዎችን አይሰሩም፡፡ የዚህ አይነት አቅም የሌላቸው ማኅበራት ከኛ ሌላ በሌሎች ሀገሮች ለመኖራቸው ብዙም መረጃ የለኝም፡፡ ቢኖሩም ደግሞ መኮረጅም ካለብን የተሻለ አሰራርና ጥቅም የሚሰጡትን ልምዶች ከሀገራችን ሁኔታና ፍላጎት ጋር አጣጥመን መሆን ይኖርበታል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ስለዚህ ለሀገራችን የጥብቅና ሞያ አስተዳደር በርካታ መሻሻሎች ያስፈልጉታል፡፡
የአባላት የስነምግባር ጉዳይ አይመለከተንም እያሉ ነው?
አይመለከተንም ሳይሆን፣ ሥልጣን በሕግ የተሰጠው የጠበቆች ማኅበር ስለሌለ፣ የማኅበሮቻችን አባልነት በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ስለሆነ፣ በዚህም ምክንያት ብዙ አባላት በማናቸውም ማኅበር ውስጥ አባል ስላልሆኑ፣ አባል የሆኑትም በማናቸውም ጊዜ ለቀው መውጣት ስለሚችሉና ይህ ከማኅበር የመውጣት እርምጃቸውም የጥብቅና ፈቃዳቸውን ስለማይነካ፣ ማለትም ከማኅበሩ ወጥተውም የጥብቅና ሥራቸውን መቀጠል ስለሚችሉ አስገዳጅ የሆነ ስነምግባር የማስከበር ሥራ መሥራት እንችልም ለማለት ነው እንጂ አያገባንም ለማለት አይደለም። ስለሚያገባንማ የሲቪክ ማኅበር ብንሆንም በየጊዜው በስነምግባር ሕጉና በተያያዙ መልካም የስነምግባር ደንቦች ስልጠና እንሰጣለን፣ ውይይቶች እናዘጋጃለን፡፡ ባለፈው አመት ለምሳሌ ከጠበቆች ሥነምግባር ጋር በተያያዘ ሁለትፕሮግራሞች አዘጋጅተን የነበረ ሲሆን በዚህ አመት በእቅዳችን ውስጥ የተያዙ ሁለት ስልጠናዎች አሉ፡፡ ዋናው ለማለት የፈለግሁት ምንድነው፣ የጥብቅና ሞያን በፈቃደኝነት ላይ በተመሰረተ የሲቪክ ማኅበር ማስተዳደር አይቻልም፡፡ ቋሚ የሆነ ዘለቄታ ያለው አደረጃጀት ወይም ተቋም ያስፈልገዋል፡፡  
 የጠበቆች ማኅበር አለ አይደለ?
 የጠበቆች ማኅበር አለ፡፡ ሆኖም ግን በጠበቆች ማኅበርም ዘንድ ያለው ችግር እላይ ከገለጽኩት የተለየ አይደለም፡፡ የጠበቆች ማኅበርም ቢሆን የፈቃደኝነት ማኅበር ነው፡፡ በርግጥ የጠበቆች ማኅበር በፍትሕ ሚኒስቴር ውስጥ ባለው የጠበቆች የዲሲፕሊን ኮሚቴ አባል ቢሆንም በአጠቃላይ የጠበቆችን ስነምግባር በተመለከተ እንደ አባል ኮሚቴው ውስጥ ከመሳተፍ በቀር የማስፈጸም ኃይሉ የሕግ ባለሞያዎች ማኅበር ካለበት ችግር የተለየ አይመስለኝም፡፡  
በዚህ ችግር ዙርያ መፍትሔ ለማምጣት ለምን በትብብር አትሰሩም?
 በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ ሃሳብ እየተለዋወጥን ነው፡፡ በሁለቱም ማኅበራት አመራር በኩል በጋራ ተረዳድቶ መሥራት ጥቅም እንዳለው መተማመን ላይ ተደርሷል፡፡ አብረን እንዳንሰራም የሚያግደን ነገርም የለም፡፡ ለወደፊቱ በጋራ የምንሰራቸው በርካታ ነገሮች ስላሉ እየተመካከርን ውጤት ያለው ሥራ ልንሰራ እንደምችል አምናለሁኝ፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ በሰፊው መነጋገር እንችላለን፡፡  
ዘላቂ መፍትሔው ምንድነው ይላሉ?
 እንደኔ እንደኔ፣ መፍትሔው በሕግ የተቋቋመ ሞያውን ማስተዳደር የሚችል፣ ሁሉም ጠበቃ በየደረጃው የግዴታ አባል የሚሆንበት የጠበቆች ማኅበር ማቋቋም ቢቻል አብዛኛው ችግር የሚቀረፍ ይመስለኛል፡፡ ምናልባት እንዳደጉት ሀገሮች ሁሉንም ሥልጣን ማኅበሩ እንዲኖረው ማድረግ አይቻል ይሆናል ግን በተወሰነ ደረጃ ሞያውን የማስተዳደር ሥልጣን የግድ ማኅበራት ያስፈልጋቸዋል፡፡ ማኅበራት ያልኩበት ምክንያት በፌደራል፣ በክልል እና በአዲስ አበባ እንዲሁም በሌሎች ፌደራል ከተሞች ደረጃ ሞያውን በተወሰነም ደረጃ ቢሆን ማስተዳደር የሚችሉ፣ በየደረጃው ሞያውን የሚወክሉ፣የሕዝብ አገልግሎት የሚያከናውኑ ማኅበራት ስለሚያስፈልጉ ነው፡፡ በየደረጃው ካልሆነ አሁንም በአባላትና በማኅበሩ መካከል መራራቅ፣ ማለትም የቦታም፣ በፌደራል ስትራክቸሩ መሰረት  የአሰራርም፣ የግንኙነትም ወይም የእንቅስቃሴና የተሳትፎ ወዘተ…ይጨምራል፣ ዞሮ ዞሮ ውጤታማ የሆነ ክትትልና አርምት ማድረግ አይቻልም፡፡ በአጠቃላይ ግን ቅርጹን የማጥናትና የአሰራር ደረጃውን በጥሩ ጥናት ላይ ተመስርቶ መምረጡ እንደተጠበቀ ሆኖ ይህ መንገድ ይሰራል ብዬ የማምንበት ምክንያት በሌሎች ሀገሮች ተሞክሮ ውጤት ያመጣ እንዲያውም በአብዛኛው ሀገራት የሚሰራበት በመሆኑ ሲሆን ሌላው ደግሞ ጠበቃው በሥራ አጋጣሚ ስለሚገናኝ፣ ስለሚተዋወቅ፣ በቅርብ አብሮ ስለሚኖር ሞያውንና ሥነምግባሩን በቅርብ መነጋገር መወያየት፣ ማረም አስፈላጊም ሲሆን በማኅበሩ በኩል እርምጃ መውሰድ ስለሚችል፣ በሌላ በኩል ደግሞ የሞያው ስነምግባር መሻሻልና ተፈፃሚ ሲሆን ክብርና ሞገስ የሚሰጠው ለሞያውና ለባለሞያው ስለሆነና ይህ ደግሞ በቀጥታ የባለሞያው ዋና ጥቅም በመሆኑ ለውጥ ያመጣል ብዬ አምናለሁ፡፡ ማኅበራቱን ከበላይ ሆኖ የሚያስተባብር ደግሞ ባር ካውንስል ማቋቋም ይቻላል፡፡ ይህ በብዙ አገራት የሚሰራበት ነው። ይህ ከሆነ በኋላ አሁን ያሉት ማኅበራት አባላቱ እስከፈለጉ ድረስ ሲቪክ ማኅበራት ሆነው መቀጠል የማይችሉበት ምክንያት አይኖርም፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የጠበቆች ድርጅት ወይም የጠበቆች ፈርም ቢቋቋም፣ በጥብቅና ሞያው ጥራትና ደረጃ እንዲሁም በሥንምግባር ጥበቃ በኩል ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብዬ አምናለሁ፡፡
የጠበቆች ድርጅት ሲሉ ምን ማለትዎ ነው? ያሏቸውን ጥቅሞችስ ሊያመጣ የሚችለው እንዴት ነው? ትንሽ ቢያብራሩልን?
 በኛ አገር ጠበቆች የጥብቅና አገልግሎታቸውን የሚሰጡት በተናጠል ወይም በግል ነው፡፡ ጠበቆች እንደ ሥራ አንድ ላይ ተሰባስበው ሞያዊ አገልግሎት የሚሰጡበት ሁኔታ የለም፡፡ እንደሚታወቀው ሕግ ደግሞ በጣም ሰፊ ዘርፎች አሉት፡፡ ሕግ የማይነካው ምንም አይነት ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት የለም፡፡ ያለማጋነን ማናቸውም እንቅስቃሴ በሕግ የሚገዛ ነው፡፡ ስለዚህም የንግድ ሕግ፣ የኮንስትራክሽን፣ የትራንስፖርት፣ የተፈጥሮ ሀብት፣ የአካባቢ ጥበቃ፣ የቤተሰብ፣ የአሰሪና ሰራተኛ፣ የወንጀል፣ የባሕር፣ የውጭ ንግድ፣የመሬት፣የባንክ፣የኢንሹራንስ፣የታክስ፣የኢንቨስትመንት ወዘተ… እያለ ማናቸውንም እንቅስቃሴ የሚመሩ ሕጎች አሉ፡፡ በዚህ ሁሉ የሕግ ዘርፍ ደግሞ አንድ የሕግ ባለሞያ በቂ አውቀትና ልምድ ኖሮት የተሟላ አገልግሎት ለመስጠት ይቸገራል፡፡ በአንፃሩ ደግሞ በተለያየ የሕግ ዘርፍ ከፍ ያለ አውቀትና ልምድ ያላቸው ሰዎች ተሰባሰበው መሥራት ቢችሉ፣ በተሰባሰቡት ባለሞያዎች መካከል የሥራ ክፍፍል ይደረጋል፡፡ እያንዳንዱ ባለሞያ የተሻለ አውቀትና ልምድ ባለው መስክ የሚመጡ ሥራዎችን ይሰራል፣ በየዲፓርትመንት ይደራጃል፤ሥራውን ያከናውናል። ባለሞያዎቹ ባጋጠሙዋቸው የሕግ ጥያቄዎች ላይ ይመካከራሉ፤ ኃሳብ ይለዋወጣሉ፣ የተነሳውን የሕግ ጥያቄ እንዴት አድርገው መፍታት እንዳለባቸው መክረው ዘክረው ይወስናሉ፡፡ ይህ እንግዲህ ጥራት ያለው ሥራ እንዲሰሩ ይረዳቸዋል፡፡ ባለሞያዎቹም በሙሉ ልብ ሥራቸውን ያከናውናሉ፤ ተገልጋዩም ከፍተኛ ደረጃና ጥራት ያለው ምክር ያገኛል፣ ፍርድ ቤትም ሲወከል በደንብ በተዘጋጀ አቤቱታና ክርክር ይወከላል፡፡ ይህ በራሱ አንድ ትልቅ ችግር ይቀርፋል፡፡ ባለሞያዎች በስራ ብዛትና መደራረብ ብዙም በማያውቁት የሕግ መስክ እንዳይዳክሩ በማድረጉ ቅልጥፍናና ጥራት ያመጣላቸዋል። ከዚህ ጋር ተያይዞ ከሚፈጠር የሥነምግባር ጉድለትም ይጠብቃቸዋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ባለሞያዎቹ በቡድን  መልክ ስለሚሰሩ የእውቀትና የልምድ ጉድለትን እያሟሉ እንደሚሄዱ ሁሉ፣ የሚታዩ የሥነምግባር ጉድለት አዝማሚያዎችንም እያረሟቸው ይጓዛሉ፡፡ በሦስተኛ ደረጃ ደግሞ ፈርሙ ወይም የባለሞያዎቹ ድርጅት የተሻለ ሥራ ማግኘት የሚችለው በሥራው ደረጃና ጥራት እንዲሁም በሥነምግባር ጥንካሬው ስለሚሆን ለራሱ ለድርጅቱ ወይም ለፈርሙ ሕልውና ሲል የሥነምግባር ጉድለቶችን እንዲያርም ይገደዳል። በዚህም ጠበቆች የተሻለ አገልግሎት የሚሰጡ፣ ከፍተኛ የሥነምግባር ብቃት ያላቸው እንዲሆኑ ይረዳል፡፡
ስለዚህ በአገራችን የጠበቆች ድርጅቶች ወይም ፈርሞች እንዲቋቋሙ የሚያስችል ሕግ ቢወጣ ቀደም ብዬ እንደጠቀሱት በርካታ ችግሮችን በመፍታት ለፍትሕ ሥርአቱ መጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል የሚል እምነት አለኝ፡፡
 እስከዛሬ በዚህ ረገድ ምንም ሥራ አልተሰራም ማለት ነው?
ምንም አልተሰራም ማለት አይቻልም። ከጥቂት አመታት በፊት ፍትሕ ሚኒስቴር በጠበቆች ድርጅት ላይ ረቂቅ አዘጋጅቶ በሰፊው እንድንወያይበት አድርጎ ነበር፡፡ እኛም ይጠቅማሉ ያልናቸውን አስተያየቶች ሰጥተናል፡፡ ይህ ከሆነ አንድ ሁለት አመት የሆነው መሰለኝ፡፡ ከዚያ ወዲህ ረቂቁ ምን ላይ እንደደረሰ አልፎ አልፎ ስንጠይቅ ማስተካከያዎች እየተደረጉበት እንደሆነ ተነግሮናል። በቀደም በተካሄደው የሀገር አቀፍ የፍትሕ ዘርፍ የፍትሕና መልካም አስተዳደር መድረክ ላይም በጉዳዩ ላይ አስተያየት የሰጡ ከፍተኛ የፍትሕ ሚኒስቴር ኃላፊ፣ ሥራው እየተጠናቀቀ መሆኑን እና ብዙዎቹ ያነሳናቸው ነጥቦች በተሻሻለው ረቂቅ ውስጥ የተካተቱ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ እኛም በተሰጠው አስተያየት ከፍተኛ ተስፋ አድሮብናል፡፡  
እዚህ ላይ አንድ መጨመር የምፈልገው ነገር የጠበቆች ጅርጅት ወይም ፈርም መቋቋም ቀደም ሲል ከገለጽኩት በተጨማሪ በቀጥታ ከውጭ በሚመጣው ኢንቨስትመንት ወይም direct foreign  investment ላይም ከፍተኛ ተጽእኖ አለው፡፡ ወደ ሀገራችን የሚመጡት ኢንቨስተሮች በብዙ መልኩ የሕግ ባለሞያዎች በሚሰጡዋቸው ምክር ላይ እምነት በመጣል ውሳኔዎችን ይሰጣሉ። በአብዛኛው የዓለም ሀገራትም ለሕግ አማካሪህ፣ ለሀኪምህና ለንስሃ አባትህ የሚደበቅ ነገር የለም የሚባለው መርህ በከፍተኛ ደረጃ የሰረፀ በመሆኑ የኢንቨስትመንት ውሳኔያቸው በሚያገኙት የሕግ ምክር ላይ በከፍተኛ ደረጃ የተመሰረተ ነው። ጉዳያቸው ወደ ፍርድ ቤት ሲሄድም በሙሉ እምነት ጉዳያቸው ተገቢውን ትኩረት ተሰጥቶት ክርክሩ እንዲቀርብ እና ክትትልም እንዲደረግበት ለሚያምኑት ባለሞያ መስጠት ይፈልጋሉ፡፡ በማናቸውም ሁኔታ የሰጡት እምነት እንዳይፋለስ እንዳይደናቀፍ ይፈልጋሉ፡፡ ያ ባለሞያ ግን አንድ ብቻ ሆኖ የሚሰራ በመሆኑ ደስተኞች አይደሉም። የሕግ አማካሪያቸው ወይም ጠበቃቸው አንድና  ብቻውን የሚሰራ መሆኑ ስጋታቸውን በጣም ከፍ ያደርገዋል፡፡ የሕግ ባለሞያው ወይም ጠበቃው አንድ ችግር አጋጥሞት ፍርድ ቤት መቅረብ ባይችልስ? ቢታመምሰ? ቢሞትስ? ወዘተ. ማነው ጉዳዩን የሚከታተለው? ፋይሎቹ የት ይገኛሉ? ማነው ጉዳዩን በቀላሉ ተክቶት መሥራት የሚችለው? በነዚህና በበርካታ ጥያቄዎች ምክንያት ጉዳያቸው እንዳይበላሽ በጣም ይፈራሉ፡፡ ለዚህም ወደኛ ሀገር ኢንቨስት ለማድረግ ሲመጡ ሀገራችን ለኢንቨስትመንት ምቹ ነች ወይ? ብለው ከግምት ከሚያስገቧቸው መመዘኛዎች አንዱ ብቃት ያላቸው የሕግ ባለሞያዎች አሉ ወይ? የሕግ ድርጅቶች ወይም ፈርሞች አሉዋቸው ወይ? የሚለው ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ ከውጭ የሚመጡት ባለሀብቶች በዚህ ረገድ ደስተኞች አይደሉም፡፡ በተለይ ከፍተኛ ሥራ ሊሰሩ የሚችሉት ትላልቅ ድርጅቶች ብዙውን ጊዜ የሕግ ባለሞያ ድርጅቶች ወይም ፈርሞች ባለመኖራቸው ወደ ሀገራችን መጥተው በተለያዩ የሥራ መሥኮች መሰማራት ቢፈልጉም ይህ ጉድለት ያሳስባቸዋል፡፡
ሌላው ከዚህ ጋር መታየት ያለበት ሀገራችን ወደ ዓለም የንግድ ድርጅት ወይም WTO ለመግባት ድርድር ላይ መሆኗ ይታወቃል፡፡ የሕግ ሞያ በዚህ ረገድ ብዙ ዝግጅትና ሥራ የሚጠብቀው ይመስለኛል፡፡ ተወዳዳሪ ለመሆን ጠንካራ የጠበቆች ማኅበር ወይም ማኅበራት ያስፈልጉናል እንዲሁም የሕግ ባለሞያዎች ድርጅቶች ወይም የጠበቃ ፈርሞች ያስፈልጉናል፡፡ የነዚህ ተቋማት ያለመኖር ተወዳዳሪነታችንን መፈታተኑ አይቀርም። የሀገራችንን እና የሀገር ውስጥ ሥራዎችን እና ድርጅቶችን ጥቅምም በአግባቡ ለማስጠበቅ እንዲሁም ከውጭ የሚመጡ ድርጅቶች በተገቢው መንገድ ለመርዳትና ሀገራችንን ጠቅመው እነሱም እንዲጠቀሙ ለማስቻል የነዚህ ተቋማት በአግባቡ መደራጀት እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡
 ለመሆኑ ሞያውን የማስተዳደር ሥልጣን በሕግ ቢሰጥ ወይም ማኅበሩ በሕግ ቢቋቋም፣ሥራውን ለመስራት አቅሙ አለን ብላችሁ ታስባላችሁ?
 ሃ!ሃ! ይህ ብዙ ጊዜ የሚነሳ ጥያቄ ነው፡፡ እና በዚህ ጉዳይ ላይ ሳንነጋገር ብናልፈው ኖሮ ይቆጨኝ ነበር፡፡ በእኔ እምነት ችግር አይፈጠርም ባይ ነኝ። ቀድሞ ነገር አቅሙን የሚሰጠን እኮ ሕግ ነው። ሕጉ ሞያውን በማስተዳደር በኩል ማኅበራቱ ሊኖራቸው የሚገባውን ደረጃ ይወስናል፣ ሕጉ ማናቸውም ጠበቃ የጠበቆች ማኅበር አባል የመሆን ግዴታ አለበት የሚል ከሆነ፣ የጠበቆች ማኅበር የአባላቱን ሥነምግባርና የተከታታይ ሥልጠና እንዲወስዱ ፕሮግራም አዘጋጅቶ ያስፈጽማል የሚል ከሆነ፣ ጠበቆች በሕዝብ አገልግሎት ተግባር እንዲሳተፉ ፕሮግራም አውጥቶ ያስፈጽማል የሚል ከሆነና ሌሎችም ዝርዝር ጉዳዮችን የያዘ ሕግ ከወጣ  ማኅበሩ ወይም ማኅበራቱ ያንን ማስፈጸም የማይችሉበት ምንም ምክንያት አይኖርም፡፡ ማኅበሩ ወይም ማኅበራቱ እኮ ራሳቸውን የቻሉ ጽ/ቤቶችና ሰራተኞች ይኖሯቸዋል፡፡ ከባለሞያዎቹ ውስጥ ደግሞ ጥሩ ጥሩ ችሎታ ያሉዋቸው አባላት ለማኅበራቱ መሪነት ይመረጣሉ፡፡ የተለያዩ ኮሚቴዎች ይኖራሉ፣ አባላትም የአባልነት መዋጮዋቸውን በአግባቡ እንዲያዋጡ ስለሚደረግ የአባልነት መዋጮን መክፈል ግዴታም ስለሚሆን ሥራዎቹን ለማከናወን አስቸጋሪ አይመስለኝም፡፡ በዚያ ላይ ደግሞ መታወቅ ያለበት የሕግ ባለሞያዎች እኮ በተለይ በጥብቅና የተሰማሩት ከፍተኛ ትምሕርት ያላቸው፣ በተለያያ ደረጃ አገራቸውን በመንግሥት ሥራ ያገለገሉ፣ በግል ድርጅቶች የሰሩ፣ ከፍተኛ የአስተዳደርና የሥራ መሪነት ልምድ ጭምር ያካበቱ ናቸው፡፡ ስለዚህ እድሉ ከተፈጠረ ሞያቸውን ማገልገልና ወደ ተሻለ ደረጃ ማሸጋገር ያቅታቸዋል ብዬ አላምንም፡፡   
  ሌላ የሚያክሉት ነገር አለ?
 የተጠናከረ ተደራሽ፣ ብቁ፣ ነፃና ፍትሕን ማስፈን የሚችል የዳኝነት ሥርአት ለአንድ ሀገር ሰላምም ሆነ እድገት አጅግ አስፈላጊ ነው። ዳኝነት በአጠቃላይ የአንድ አገር ሕዝብ መብት፣ ሀብት፣ ሕይወት የሚጠበቅበት ሥርአት በመሆኑ አስፈላጊነቱን አበክሮ ለመግለጽ በቂ ቃል አይኖርም፡፡ እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ስለዚህ ዳኝነት እንዲጠናከርና በብቃት የሚሰራበት ሁኔታ እየተሻሻለ መሄዱ አስፈላጊ ነው፡፡  የዳኝነት ሥርዓቱ መጠናከር ሥንል፣ የዚህ ሥርዓት አንዱ አካል የሆነው የጠበቆች አገልግሎት፣ ነፃ የሆነና ብቃት ያለው፣ ሥነምግባር የጠበቀ የተሟላ አገልግሎት መስጠት መቻል አብሮ የሚታሰብ ነው፡፡ ምክንያቱም የፍትሕ ሥራ የሚሰራው በፍትሐብሄር ጉዳይ ሲሆን በዳኞችና በጠበቆች ነው፡፡ በወንጀል ፍትሕ ደግሞ በዳኞች፣ በተከላካይ ጠበቆች እና በአቃቤ ሕጎች ነው፡፡ ከነዚህ ውስጥ የአንዱ ወገን መጉደል ወይም መዳከም የፍትሕ ሥርአቱን በእጅጉ ይጎዳዋል፡፡ በተጨማሪም የሕግ ባለሞያዎች ከፍርድ ቤት ውጭም በበርካታ መስኮች ኢንቨስትመንትን ጨምሮ ሰፊ የሥራ ድርሻ አላቸው፡፡ ስለዚህ እነዚህ መሰረታዊ የፍትሕ ሥርአቱ አካላት እየተሻሻሉና እየተጠናከሩ መሄዳቸው ለሀገራችን ሰላም፣ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ፣ እድገትም ሆነ ልማት መሰረታዊ ሚና ያላቸው በመሆኑ፣ አሁን በተያዘው መልኩ ትኩረት ተሰጥቶት መቀጠሉና የሚጠበቅበትን አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ማድረግ ቀጠሮ የሚሰጠው ጉዳይ አይደለም የሚል እምነት አለኝ፡፡

“የሙስና አዋጁ እንደገና ሊፈተሽና ሊታይ ይገባዋል”
የአንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ ዋና ፀሃፊ የነበሩትና በአዲሱ ካቢኔ ውስጥ ሳይካተቱ የማዕከላዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ አስራት ጣሴ፤ በቅርቡ አዲስ ጉዳይ መፅሄት ላይ ባሰፈሩት ፅሁፍ “ፍ/ቤትን ደፍረዋል” በሚል ተከሰው ያለዋስትና መብት በ5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ጊዜያዊ ማረፊያ ቤት እና በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ለአስር ቀናት ከታሰሩ በኋላ ባለፈው ሰኞ ተሲያት ላይ ተለቀዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ በክሱ ዙርያ፣ በዋስትና መብትና በእስር ቆይታቸው ዙርያ ተከታዩን አጭር ቃለመጠይቅ አድርጎላቸዋል፡፡

የቀረበብዎትን ክስ እስቲ ያብራሩልን ?
ክስ የቀረበብኝ በፍትሃ ብሄር ወንጀል አንቀፅ 480 ነው፡፡ ይህ ደግሞ አንድ ሰው በችሎት ላይ ታዳሚ ሆኖ፣ በጠበቃነት ወይም በከሳሽና በተከሳሽነት ቀርቦ ያልተገባ ድርጊት ሲፈፅም የሚከሰስበት አንቀፅ  ነው፡፡ እኔም መጀመሪያ በዚህ አንቀፅ ነበር ክስ የቀረበብኝ፤ በኋላ ላይ ግን ወደ ወንጀል ዞሮ ተፈረደብኝ-  በአንቀፅ 449 ተራ ቁጥር 2(ለ)፡፡ በዚህ የወንጀል አንቀፅ… የተከሰሰ ግለሰብ ከፍተኛ ቅጣቱ የ6 ወር እስራት ነው፡፡ የፍርድ ማቅለያ አቅርብ ተባልኩ፤ ነገር ግን የለኝም አልኩ።  ምክንያቱም ጠበቃዬ አቶ ተማም አባ ቡልጉ መጀመሪያ በተከሰስኩበት አንቀፅ ነበር ክርክሩን ያቀረቡት፤ ነገር ግን ባልተከሰስኩበት አንቀፅ የ5 ወር እስር በ2 ዓመት ገደብ  ተፈርዶብኛል፡፡ ሁለት ዓመት ለኔ በጣም ረጅም ጊዜ ነው፡፡ ይሄን ነገር ፖለቲካዊ መነሾ (ፖለቲካሊ ሞቲቬትድ) እንዳለው አድርጌ ነው ማየት የምፈልገው፡፡ የ2007 ምርጫ ቀርቧል፤ በምርጫ ቅስቀሳው ላይ ንቁ ሆኜ መሳተፍ አለብኝ፤ በገዥው ፓርቲ እና መንግስት ላይ እንዲሁም በፍትህ ስርዓቱ ላይ አስተያየት መስጠት ይጠበቅብኛል፡፡ እነዚሀ ሁሉ ጉዳዮች መደረግ ባለባቸው ጊዜ ነው ይሄን እንደ ማስፈራሪያና ማሸማቀቂያ ለመጠቀም የተፈለገው። ለእኔ ብቻ ሳይሆን ለሃገሪቱ የፖለቲካ ስርዓት መሻሻል ለቆመው ተቃዋሚ ሁሉ መልእክቱ ጥሩ አይደለም ብዬ ነው የማስበው፡፡ ነገር ግን በተወሰነው ፍርድ ላይ ይግባኝ እንጠይቃለን፡፡
ወደ ማረፊያ ቤት ሲላኩ ለምን የዋስ መብት አልጠየቁም?
እንዳጋጣሚ ጠዋት ጠበቃ ይዤ ነው የቆምኩት፡፡ ፍ/ቤቱ ለከሰዓት ቀጠረን፡፡ ጠበቃዬ ሌላ ጉዳይ ስለነበራቸው፣ በእርግጠኝነት ክሱ የቀረበበት አንቀፅ ቢበዛ የሚያስቀጣው ገንዘብ ቢሆን ነው ብለውኝ ሄዱ፡፡ የኔ ፅሁፍ “ሽብርተኝነት የህወኀት ኢህአዴግ ስጋት” የሚል ሲሆን የፀረ-ሽብር ህጉን ነው በስፋት የሚተነትነው፡፡ “አኬልዳማ” እና “ጀሃዳዊ ሃረካት” የተሰኙት ዶክመንተሪ ፊልሞች በፅሁፉ የተነሱት እንደ ምሳሌ ነው፡፡ ይሄም በየጊዜው በኢሬቴድ እየተዘጋጀ የሚተላለፈው ሰውን ለማሸማቀቅ፣ ለመብቱ የሚቆመውን ሁሉ በሽብርተኝነት ለመፈረጅ ነው፤ በዚህም ደግሞ ፍትህ አልተገኘም በሚል የፍትህ ስርአቱን የሚተች ነው እንጂ በተለየ መልኩ ችሎቱን የሚዘልፍ አይደለም” የሚል መከራከሪያ የህገ-መንግስቱን አንቀፅ 29 (ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትን የሚደነግገውን) በመጥቀስ ጭምር ጠበቃዬ ከተከራከረ በኋላ ግፋ ቢል ቅጣቱ የገንዘብ ነው፤ የእስራት ቅጣት የለውም ብሎኝ ነበር፡፡ ከሰዓት በኋላ ግን ፍ/ቤቱ “ጥፋተኛ ሆነው ስላገኘንዎት በቀጥታ ፖሊስ ወደ ማረፊያ ክፍል እንዲወስድዎ” የሚል ትዕዛዝ አስተላለፈ። በዚያ መሃል የዋስትና መብቴን በተመለከተ ፍ/ቤቱ ይጠይቀኛል ብዬ ነበር የጠበቅሁት፤ ዝም ሲለኝ ግን መጠየቅ የማልችል መሰለኝና እኔም ዝም አልኩ፡፡ በዚህ ምክንያት ቃል በቃል የዋስትና መብቴ ይጠበቅ የሚል ጥያቄ አላነሳሁም፤ ነገር ግን ፍ/ቤቱ “በዚህን ያህል ዋስትና ተለቀዋል፤ በውጭ ሆነው ይከራከሩ” የሚል ትዕዛዝ ማስተላለፍ ይችል ነበር፡፡ ከትእዛዙ በኋላም ወደ አምስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ተወስጄ ከአርብ እስከ ሰኞ ያሉትን ቀናት እዚያ ካሳለፍኩ በኋላ ቀሪዎቹን ቀናት ደግሞ በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት እንድቆይ ተደርጓል፡፡
በማረሚያ ቤት የገጠምዎት ችግር ነበር?
በጭራሽ! በግሌ አንድም ማዋከብና ማንገላታት አልገጠመኝም፡፡ ከእስረኞቹ የተደረገልኝ አቀባበልም ጥሩ ነበር፡፡ በርካታ እስረኞች አውቀውኛል፡፡
በእውነት የእስር ጊዜዬ የተመቸ እንዲሆን አድርገውልኛል፡፡ መጀመሪያ ያስገቡኝ ዞን አንድ የሚባለው ውስጥ ነበር። 1602 እስረኞች ነበሩ፤ ሁላችንም መሬት ነበር የምንተኛው፡፡
ለኔ ጥሩ ቦታ በመስጠት ተንከባክበውኛል። የማረሚያ ቤቱ ኃላፊዎች እና ፖሊሶችም ያደረሱብኝ ምንም ጫና እና እንግልት የለም፤ ማንንም እስረኛ እንደሚያስተናግዱት አስተናግደውኛል፡፡
የፍ/ቤቱ የገደብ ውሳኔ አስተያየት እንዳልሰጥ ታስቦ የተደረገ ይመስላል ብለዋል፡፡ ከአሁን በኋላ አስተያየቶችና ትችቶችን ከመሰንዘር ይቆጠባሉ ማለት ነው? ውሳኔው ተፅዕኖ ይፈጥርብዎታል?
በምንም አይነት አይፈጥርብኝም፡፡ በምንም ሁኔታ ተፅዕኖ ሊፈጥርብኝ አይችልም፤ አይገባምም፡፡  ይሄን ተፅዕኖ ለመቋቋም የማልችል ከሆነ፣ እንደ ፖለቲከኛ ብቻ ሳይሆን እንደ ዜጋም ለመኖር ያስቸግረኛል፤ ስለዚህ በምንም መመዘኛ ተፅዕኖ አያደርግብኝም፤ ነገም ተመልሼ መታሰር ካለብኝም እታሰራለሁ፡፡ እነ አንዷለምም፣ እስክንድርም፣ በቀለ ገርባም እኮ እድሜ ልክ ተፈርዶባቸው ለዲሞክራሲ የሚፈለገውን ዋጋ እየከፈሉ ነው፡፡ የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ ብቀበለውም በኔ አቋም ላይ የሚያመጣው አንዳችም ለውጥ የለም፡፡
በእስር ቤት ቆይታዎ ምን ታዘቡ?
በእውነት በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በቆየሁባቸው ስምንት ቀናት በዚህች ሃገር የፍትህ ስርአቱ እንዴት ፈታኝ እንደሆነ ተረድቻለሁ፡፡ በዚህች ሃገር ፈታኙ ጉዳይ የፍትህ ጉዳይ እንደሆነ፣ የልማቱም ተግዳሮት የፍትህ እጦት መሆኑን፣ የሃገር ሰላምና መረጋጋትን የሚፈትነውም የፍትህ አለመኖር እንደሆነ ለመታዘብ ችያለሁ፡፡ ሌሎችም በርከት ያሉ ጉዳዮች አሉ፡፡ ለወደፊት በማስረጃ እስደግፎ ማቅረብ ይጠይቃል፡፡ ሁኔታዎች ከፈቀዱ በዝርዝር ለማቅረብ ፍቃደኛ ነኝ፡፡ በዚህ አጋጣሚ አንዱ የታዘብኩት፣ እኛ ፖለቲከኞቹ ብዙ ጊዜ ሰጥተን የምንተቸው የፀረ-ሽብር አዋጁን ነው፤ በማረሚያ ቤት ቆይታዬ የተረዳሁት ግን፣ የፀረ - ሙስናም አዋጅ ሊፈተሽና ሊታይ እንደሚገባው ነው፡፡ ይህ አዋጅም በአንድ ወይም በሌላ መንገድ የፖለቲካ ባላንጣን ማጥቂያ መሳሪያ ሊሆን እንደሚችል ታዝቤአለሁ፡፡ የማረሚያ ቤት አያያዝ ባልተፃፈ ህግ የሚመራበት ሁኔታ እንዳለም ተረድቻለሁ፡፡ አንድም የግል ጋዜጣ እና መፅሄት ማረሚያ ቤት ሲገባ አላየሁም፡፡ ይሄ የሰብአዊ መብት ጥሰት ነው፤ ስለዚህ በአጠቃላይ የፍትህ ስርዓቱ መፈተሽ አለበት፡፡
ለስንተኛ ጊዜ ነው የታሰሩት?
በዚህ ስርዓት ለሁለተኛ ጊዜ ነው የታሰርኩት፤ በምርጫ 97ም ታስሬ ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት የድርጅት አሰሪዎች ስለሰራተኞቻቸው ዳተኝነት ይወያያሉ፡፡
አንደኛው፡-
“እኔ መቼም እንደሚገባኝ፤ እኔ ድርጅት ውስጥ እንዳለው እንደ አቶ እገሌ ደደብ፣ ደንቆሮ ሰራተኛ በዓለም ቢዞሩ አይገኝም ባይ ነኝ፡፡”
ሁለተኛው፤
“ለምን እንዲህ አልክ? ምን አጥፍቶ አግኝተኸው ነው?” አለው፡፡
“ይህን ዳተኛው ቆይ ልጥራውና ምን ዓይነት ደደብ እንደሆነ ላሳይህ”
የተባለው ሰውዬ ተጠርቶ መጣ፡፡
“ይሄኔ አሰሪው ይህን አምስት ብር ይዘህ ሂድና ማርቼዲስ መኪና ገዝተህልኝ ና”፤ አለው፡፡ ሰራተኛው ዝም ብሎ ገንዘቡን ተቀበለና ሄደ፡፡”
ሁለተኛው፤
“አይ ወዳጄ የዛሬ ሰራተኛ ሰራተኛ መስሎሃል? የእኔን ሰራተኛ ጉድ ብትሰማ ምን ልትል ነው?”
አንደኛው፤
“እንዴት?! አሁን ከነገርኩህ የበለጠ ደደብ ሰራተኛ ይኖራል እንዴ?”
ሁለተኛው፤
“ቆይ ላስጠራውና ምን ዓይነት ጉደኛ እንደሆነ አሳይሃለሁ” አለና፤ የተባለውን ሰራተኛ አስጠርቶ፤
ወደ ሰራተኞች ክበብ ሂድና እኔ እዛ መኖር አለመኖሬን አይተህ ና” አለው፡፡ ሰራተኛው እሺ ብሎ ምንም ሳይል፣ ጥያቄም ሳይጠይቅ፣ ወጥቶ ወደ ክበቡ ሄደ፡፡
እደጅ ሁለቱ ሰራተኞች ይገናኛሉ፡፡ ጉዱ እዚህ ላይ ነው፡፡ ሁለተኛ የተላከው ሰራተኛ ለመጀመሪያው እንዲህ አለው፣
“አለቆቻችን ደደቦች መሆናቸውን አየህልኝ?”
“ምን ትጠራጠራለህ? አገር ያወቃቸው ደደቦችኮ ናቸው፡፡ የእኔ አሰሪ ምን እንዳለኝ ታውቃለህ?”
“ምን አለህ?”
“5 ብር ሰጥቶኝ ማርቼዲስ መኪና ገዝተህ ና አለ፡፡ የደደብነቱ ደደብነት ግን ምን እንደሆነ ታውቃለህ? ምን ዓይነት ቀለም ያለው መኪና እንደሚፈልግ ሳይነግረኝ!”
“ኧረ ያንተ አለቃ በምን ጣሙ? የእኔው አለቃ ምን እንዳለኝ ታውቃለህ?”
“ምን አለህ?”
“ሂድና ክበብ ውስጥ እኔ መኖር አለመኖሬን አይተህ ና አለኝ፡፡ የደደብነቱ፤ ደደብነት እኔን ማንከራተት መፈለጉ ነው እንጂ፤ እስቲ ምናለበት ስልኩን ብድግ አድርጎ፣ ክበብ ደውሎ አለሁ የለሁም ብሎ ቢያረጋግጥ!!” አለ፡፡     
*      *      *
ዕውነተኛ ሰራተኛ የሌለው አገር ለውጥ አያመጣም፡፡ ልቡ ዳተኛ የሆነ ትውልድ ለውጥ አያመጣም፡፡ መሰረቱ የተናደ ህብረተሰብ ልመልስህ ቢሉት አይንድም፡፡ “መንገድ ሲበላሽ ትራፊክ ይበዛል፤ አገር ሲበላሽ ጃርት ያፈራል፤” ይላሉ ህንዶች፡፡ ሥነ-ልቦናችን በአሉታዊነት ነቅዟል። ያለሸር፣ ያለጥፋት፣ ያለሌብነት፣ ያለ ቢሮክራሲ ጥልፍልፍ … የሚታይ ደግ ነገር ጠፍቷል፡፡ አንድ ፋይል ካንድ ክፍል ሌላ ክፍል እንዲሄድ ገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ በስልክ ቀና መልስ ለማግነት እንኳን ገንዘብ አስፈልጓል፡፡ ምናልባት ፈገግ ለማለትም ገንዘብ የሚያስፈልግበት ዘመን ሳይመጣ አይቀርም፡፡ ስለመልካም አስተዳደር ማውራት የሚቻለው የፀዳ አዕምሮ ሲኖር ነው፡፡ የጌታ-ሎሌ አስተሳሰብ እያለ የስራ ሂደት ባለቤትነት ዘበት መሆኑን አንርሳ፡፡
የጀርመን ግንብ በአደባባይ እንዲፈርስ ተደረገ እንጂ ግንቡ ጭንቅላታችን ውስጥ አለ”፤ ይላሉ ጀርመኖች፡፡
ፍጥነት አስፈላጊ ቢሆንም፣ ምን ተይዞ ጉዞ ማለትን አንዘንጋ፡፡ ከአሁኑ፤ ከውሃ ልኩ ያላስተዋልነው ነገር ነገ ጠልፎ ሊጥለን ይችላል፡፡ ያለውን ችግር የለም፣ የሌለውን ችግር አለ ማለት ፈረንጆቹ Denial የሚሉት በሽታ ነው፡፡ እያወቁ መካድ! ይሄ ለማይቀለበስ (irreversible) ችግር ከዳረገን አለቀልን ማለት ነው፡፡
አንዴ የተቀጠፈች አበባ ለዘለዓለም ትሞታለች፤ ይለናል ኦማር ካህያም፡፡ (A flower once pluck’d forever dies)፡፡ የምንፈልገውን ማወቅ ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ካፒታሊዝም ከፈለግን የካፒታሊዝምን ትክክለኛ አውታሮች እንጨብጥ፡፡ የራሳችን ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት የምንገነባ ከሆነ፤ በወጉ ቀርፀነው፣ በወጉ መሬት ላይ አስፍረነው፣ በወጉ ተግብረነው መንገዱ ይሄ ነው እንበል፡፡ አንዱ አንድ አዞ ሌላው ሌላ እያዘዘ፤ ከተምታታ፤ ስራም አይሰራ፣ ለውጥም አይመጣ። ይሆናል ሲሉን አህያ አረድን፡፡
አይሆንም ሲሉን አውጥተን ጣልን፡፡
ለምን ጣላችሁት፣ ይሆን ነበርኮ ቢሉን
ወጥተን ብንፈልግ አጣን!
እንደተባለው የኦሮምኛ አገላለፅ፤ ሌሎች ያሉንን እየሰማንና ዕውነት ነው እያልን፣ አደጋችሁ ሲሉ እሺ፣ አላደጋችሁም ሲሉን እሺ እያልን፤ መሸነጋገል አይገባንም፡፡ ሁሉም ለየራሱ ጥቅም እንደሚሮጥና ግሎባላይዜሽን የራሱ መዘዝ፤ የራሱ አባዜ እንዳለው ላንዲትም ደቂቃ መዘንጋት አይገባም፡፡
“መንግሥት ዝሆን ነው፡፡ ሁሉን ነገር ዞሮ አያይም፤ ማሳየት ያስፈልጋል” ያለው የድሬደዋ ገበሬ አባባል አይረሴ ነው፡፡ ዐይን ያለው የሰው ያስፈልጋል፡፡ የሰው ጎዶሎ የሰው ድርጭት፣ መፃጉእ ነው እንዲያፈራ፤ የሰው ተራራ የሰው ዋርካ፣ ጀግና ነው እያፈራ ይላልና ልባም ዜጋ ለማፍራት መጣር አለብን፡፡ ሰራተኛ ትውልድ፣ ጠያቂ ትውልድ፣ ተፋላሚ ትውልድ፣ ማፍራት አለብን፡፡ መንገድ የሚመራ ሰውና ድርጅት የሚመራ፣ ህዝብ የሚመራ፤ ባትሪው እጁ ላይ ነው። ባትሪውን አብርቶ ዐይኑን ከጨፈነም፣ ዐይኑን ገልጦ ባትሪውን ካጠፋም፤ መንገዱ አይሳካም፡፡ ሁሉ ነገር ከጨላለመ በኋላ እገሌ ነው እገሌ ነው እያሉ መወነጃጀል፤ “ዐይን-አውጣ ሌባ ሰርቆ ያፋልጋል” ከመባል አያመልጥም! ልብና ልቡና ይስጠን!!