Administrator

Administrator

የኢትዮጵያ ሬድዮ እና ቴሌቪዥን የስፖርት ጋዜጠኛ የሆነው መኳንንት በርሄ ላጋጠመው የደም መርጋት ህመም በደቡብ አፍሪካ ህክምናውን እየጀመረ ነው፡፡ ከትናንት በስቲያ የደም ናሙና የሰጠው የስፖርት ጋዜጠኛው፤ በትናንትናው እለት ደግሞ የዶፕለር ምርመራ አድርጎ በቀኝ እግሩ ላይ የደም ማመላለሻ ቧንቧ‹‹ ቬን›› መዘጋቱ ተረጋግጧል። ከሁለቱ ምርመራዎች ውጤት በኋላ የተዘጋውን የደም ማመላለሻ ቧንቧ የሚከፍትበትን ልዩ ህክምና በአስቸኳይ ማድረግ እንዳለበት በሃኪሞቹ ተነግሮታል፡፡ በደቡብ አፍሪካ የሚገኘው መኳንንት በርሄ ካጋጠመው የጤና እክል ሙሉ ለሙሉ ለመዳን ለሚያደርገው ከፍተኛ ህክምና ከ350 ሺ ብር በላይ ይጠበቅበታል፡፡ ለስፖርት ጋዜጠኛው ገንዘብ ማሰባሰብ ከተጀመረ አንድ ሳምንት ወዲህ ብዙም ባለመገኘቱ አሁንም ከፍተኛ ርብርብ ያስፈልጋል፡፡

ጓደኛው ትዕግስት ገመቹ በኢትዮጵያ ሬድዮ እና ቴሌቭዥን ድርጅት ሠራተኞች 43ሺ እንደተሰበሰበለት ገልፃ፤ አንዳንድ ድርጅቶች ድጋፍ ለመስጠት ቃል በገቡት መሰረት እየተጠባበቅን ነው ብላ፤ በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ገንዘቡ በሙሉ ተሰብስቦለት ህክምናው ቶሎ እንደሚጨርስ ተስፋ አደርጋለሁ ብላለች፡፡ ለህክምና የሚያስፈልገውን ገቢ ለማሰባሰብ የትእግስት ገመቹን አድራሻ ለምን መጠቀም እንዳስፈለገ ያስረዳቸው ጓደኛው ትእግስት ገመቹ፤ መኳንንት በአገር ውስጥ ስለሌለ ገንዘቡን እንዳስፈለገ ለማንቀሳቀስና ለመላክ እንዲቻል በመታሰቡ ነው ብላለች፡፡ በደቡብ አፍሪካ ሲካሄድ በቆየው የ3ኛው ቻን ቻምፒዮንሺፕ የኢትዮጵያን የምድብ 3 ጨዋታዎች በቀጥታ ስርጭት በማስተላለፍ እና የተለያዩ ዘገባዎችን በመስራት ለሙያው ያለውን ፍቅር እና ትጋት አሳይቷል፡፡ ዘገባውን በቀጥታ እየሰራ የነበረው መኳንንት በርሄ ነው ህክምናውን ለማድረግ እዛው ይገኛል፡፡ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቅድስተ ማርያም ቅርንጫፍ የባንክ ቁጥር….. 1000070999076 ወይንም ተጨማሪ መረጃ ካስፈለገ ደግሞ ጓደኛውን ትዕግስት ገመቹን ማነጋገር ይቻላል፡፡ ስልክ…0910-10-17-93

             የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኦማር ሀሰን አልበሽር ባለፈው ሰኞ በቀጥታ የአገሪቱ ቴሌቪዥን የተሰራጨ ንግግር አድርገዋል፡፡ የአልበሽር ንግግር በሶስት ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሲሆን ለመጀመርያ ጊዜ  የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካዮችን ያካተተ ነበር። በቻይና መንግስት ትብብር በተሰራው የብሉ ናይል የመሰብሰቢያ አዳራሽ ከተሳተፉት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች መካከል አልበሽር ወደ ስልጣን የመጡበትን የ1989ኙን መፈንቅለ- መንግስት በማቀነባበር ወሳኝ ሚና የተጫወቱትና በ2000 ዓ.ም ከገዢው ፓርቲ የ“ናሽናል ኮንግረስ ፓርቲ” ተገንጥለው “ኦፖዚሽን ፖፑላር ኮንግረስ” ፓርቲን ያቋቋሙት ሀሰን አልቱራቢ፣ እስከቅርብ ጊዜ ድረስ የአልበሽር አማካሪ የነበሩትና ታህሳስ ላይ የ“ለውጥ ፓርቲ”ን የመሰረቱት ጋዚ ሳላሀዲን አትባኒ እና የ“ኡማ ፓርቲ” መሪ  ሳዲቅ አልመሃዲ ይገኙበታል፡፡
አልበሽር በንግግራቸው ላይ ሶስት የለውጥ ፕሮግራሞች ያሏቸውን ነጥቦች ይፋ አድርገዋል። የመጀመሪያው ፕሮግራም ከተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች ጋር በሚደረግ ተከታታይ ውይይት አሁን በስራ ላይ ባለው የአገሪቱ ህገመንግስት እና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ በመምከር፣ ህገመንግስቱ የገዥው ፓርቲ ሰነድ ብቻ ሆኖ እንዳይቀር፣ ሁሉንም ሀይሎች ያሳተፈ ህገመንግስት ማርቀቅን ያካትታል።  ሁለተኛው ፕሮግራማቸው በአገሪቱ ውስጥ ፀጥታ እና መረጋጋትን  በማምጣት፤ሱዳንን ከአማፂያን ሽኩቻ ነፃ ማድረግ እንደሆነ የገለፁት አልበሽር፤ለዚህ ደግሞ የአቡጃ፣ የዶሃ፣ የስርት እና ሁሉን አቀፉን የሰላም ስምምነት ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቃል ብለዋል፡፡ ሶስተኛው ፕሮግራም የአገሪቱ ኢኮኖሚ እንዳይንኮታኮት እርምጃ መውሰድን የሚመለከት ሲሆን ለዚህም የኢኮኖሚ ማሻሻያ እንደሚደረግ አልበሽር ገልፀዋል፡፡ “ደቡብ ሱዳን ነፃነቷን ካወጀች በኋላ ነዳጅ መደጎማችንን እንድናቆም  በኢኮኖሚ ባለሙያዎች ስንመከር ተግባራዊ አለማድረጋችን ስህተት ነበር፡፡ በአለም ላይ የነዳጅ ዋጋ እያሻቀበ ቢመጣም  ህዝባችን ላይ ጫና እንዲፈጠር ስላልፈለግን ተግባራዊ ሳናደርገው ቀርተናል፡፡ አዲሱ የኢኮኖሚ ፓኬጅ ድሆችን አይጎዳም፤ምክንያቱም ድሆች መኪና የላቸውም፡፡ እነሱን በዘካት ቻምበር እና በደሞዝ ጭማሪ እንዳይጎዱ ማድረግ ይቻላል” ብለዋል፡፡
ሁሉም ሱዳናውያን የተሃድሶው ተሳታፊ እንዲሆኑ ጥሪ ያቀረቡት አልበሽር፤ሰላም ቅድሚያ የሚሰጠው አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል - ያለ ሰላም ፖለቲካዊም ሆነ ኢኮኖሚያዊ እድገት እንደሌለ በመጥቀስ፡፡ አልበሽር ይሄን ይበሉ እንጂ የተኩስ አቁም ስምምነትን በተመለከተ ትንፍሽ ያሉት ነገር የለም ተብሏል፡፡ “በሱዳን ውጤት የሌለው የፖለቲካ ሽኩቻ ማብቃት አለበት” በማለት ብቻ  ነው ጉዳዩን አድበስብሰው ያለፉት፡፡
  የአልበሽር የሰሞኑ ንግግር ከቀደምት ንግግሮች የሚለየው ተቃዋሚዎችን በማካተቱ ሲሆን ይሄም በ25 ዓመት የስልጣን ዘመናቸው የመጀመሪያው እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ከአስራ አራት አመት መለያያትና ተደጋጋሚ እስር በኋላ በአልበሽር ንግግር የታደሙት ሀሰን አልቱራቢ፣“ከንግግሩ የምንጠብቀውን አላገኘንም፤ስለፖለቲካ  እንቅስቃሴም ሆነ ስለሚዲያ ነፃነት ምንም አልተባለም” ሲሉ ቅሬታቸውን ሰንዝረዋል፡፡ የኡማ ፓርቲ መሪ  ሳዲቅ አልመሀዲ ግን በችኮላ አስተያየት ለመስጠት የፈለጉ አይመስሉም፡፡    “በፕሬዚዳንቱ ንግግር ላይ አስተያየት ከመስጠቴ በፊት ጉዳዩን በደንብ ማጤን ይገባኛል” ነው ያሉት፡፡ የአገሪቱን ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥምረት የሚመሩት ፋሩቅ አቡ አሊ፣ከአልበሽር ንግግር ቀደም ብለው ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ በሰጡት መግለጫ፤“ፕሬዚዳንቱ በፖሊሲያቸው ምክንያት ለተጎዱ ወገኖች በተለይ በመስከረሙ ግጭት የሞቱትን ሰዎች አስመልክቶ ይቅርታ ሲጠይቁ መስማት እፈልጋለሁ” ብለዋል። አልበሽር ግን የተባለውን  ይቅርታ ባለፈው ሰኞ ንግግራቸው ላይ  አልጠየቁም፡፡  
እንዲያም ሆኖ ግን የአልበሽር ድንገተኛ የለውጥና የህዳሴ ንግግር እንዲሁም የ“እንወያይ” ጥሪ ብዙዎችን አስገርሟል - ድንገተኛና ያልተጠበቀ በመሆኑ፡፡ አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ደግሞ ከፍርሃት የመነጨ ነው ይላሉ - የአልበሽርን የለውጥና የህዳሴ ንግግር፡፡
በደቡብ ሱዳን ያለው የፖለቲካ አለመረጋጋት በተለይም ከነዳጅ አቅርበት ጋር ተያይዞ በሰሜን ሱዳን ላይ አሉታዊ ጫናውን እንዳያሳርፍ በመፍራት የወሰዱት እርምጃ ነው የሚሉት ተንታኞች፤በሌላ በኩል የሚፈነዳበት ወቅት የማይታወቀው ነገር ግን አይቀሬው ህዝባዊ አመፅ ከመምጣቱ በፊት እድላቸውን ለመሞከር ሲሉ ያደረጉት ነው ብለዋል፡፡ ለዚህም በተለያዩ የአረብ አገሮች የተካሄዱና አሁንም ያልበረዱ ህዝባዊ አመፆችን በማስረጃነት ይጠቅሳሉ -ተንታኞቹ፡፡
አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ደግሞ የአልበሽር አዲስ የለውጥ ጥሪ  ከአለምአቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ጋር ያለባቸውን እሰጥ አገባ በአገር ውስጥ  ነፍጥ ከታጠቁ  ወገኖች ጋር በመደራደር ከራሳቸው ከሱዳናውያን የሚመጣውን ግፊት ለመቀነስ ያለመ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ አስተያየት ሰጪዎቹ እንዲህ ይበሉ እንጂ አልበሽር ቢያንስ በሰኞው ንግግራቸው መሳሪያ ከታጠቁ  ኃይሎች ጋር ስለሚደረገው ውይይት ምንም የሰጡት ፍንጭ የለም፡፡
የአልበሽር ንግግር ከመደረጉ በፊት የገዢው ፓርቲ ባለስልጣናት የተለያዩ መረጃዎችነ ለሚዲያዎች መስጠታቸውም ሌላው ትኩረት የሳበ ጉዳይ ነው፡፡ አንድ የመንግስት ባለስልጣን  ቀድመው በሰጡት አስተያየት፤ አልበሽር በንግግራቸው ሁሉን አቀፍ የሆነ የለውጥ እቅድ እንደሚያቀርቡና የሱዳንን ቀውስ ለመፍታት ሁሉንም ወገኖች ያካተተ መፍትሄ እንደሚፈለግ ሲገልፁ፤ ሌላ ባለስልጣን ለሮይተርስ  በሰጡት መግለጫ፤ አልበሽር ሁሉም ተቃዋሚ ኃይሎች የአገሪቱን ህገመንግስት እንደገና አርቅቀው መንግስትን እንዲቀላቀሉ ጥሪ ያቀርባሉ ብለው ነበር። ከአልበሽር ንግግር በኋላ የተደበላለቁ እስተያየቶች መደመጣቸውን ተከትሎ የገዢ  ፓርቲው ምክትል ሊቀመንበርና  የፓርቲ ጉዳዮች ሀላፊ ኢብራሂም ጋንዱር በሰጡት መግለጫ “በሽር ለህዝቡ ንግግራቸውን ለማቅረብ ያቀዱት ከፓርቲዎች ጋር ከተወያዩ በኋላ ነበር፤ነገር ግን ብዙ ጥርጣሬዎች እና መላምቶች ቀድመው በመናፈሳቸው ለህዝቡ ንግግር ለማድረግ ተገደዋል” ብለዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ ላይ ከተሳተፉ በኋላ የንግግራቸውን ቀጣይ ክፍል እንደሚያቀርቡና ሁለተኛው ክፍል ብዙ ጉዳዮችን ዘርዘር ባለ መልኩ እንደሚያካትት ኃላፊው ተናግረዋል፡፡
“የሱዳን ህዳሴ” የሚለው ሰነድም በገዢው ፓርቲ በኩል የቀረበ በመሆኑ የመንግስት ሰነድ አድርጎ መውሰድ እንደማይቻል የገለፁት ኢብራሂም፤ፓርቲያችን ለሱዳን ችግሮች የመፍትሄ አቅጣጫዎች እያቀረበ ሳይሆን ሌሎች የፖለቲካ ሀይሎችም የራሳቸውን ሀሳብ እንዲያመጡ እድል እየሰጠ ነው ብለዋል፡፡
በሰኞው የአልበሽር ንግግር “ብዙዎች ተስፋ ቆርጠዋል” የሚለውን አስተያየት ኢብራሂም አይቀበሉትም፡፡  “አስተያየቱ ትክክል አይደለም፤ምክንያቱም ከአልበሽር ንግግር በኋላ የተሰራ ፈጣን ቅኝት ህዝቡ  በፕሬዚደንቱ ንግግር መርካቱን ነው የሚያሳየው” ብለዋል፡፡
በአለምአቀፍ ተቋሟት ይፋ የሚደረጉ የጥናት ሪፖርቶች እንደሚያመለክቱት፤ሱዳን በሙስና፣ በልማት  እና በፕሬስ ነፃነት ረገድ  ከመጨረሻዎቹ የዓለም አገራት ተርታ ትመደባለች፡፡ ፕሬዚዳንት አልበሽርም  አስራ አንድ አመቱን ካስቆጠረው የዳርፉር ጦርነት ጋር በተያያዘ በሰዎች ግድያና በዘር ማጥፋት ወንጀል በአለምአቀፉ የወንጀለኞች ፍርድቤት የሚፈለጉ መሪ ናቸው፡፡ ባለፈው መስከረም ወር  ከነዳጅ ዋጋ ጋር ተያይዞ በሱዳን በተፈጠረ አለመረጋጋት፣ ከሁለት መቶ በላይ ሰዎች በፀጥታ ሀይሎች መገደላቸውን አምነስቲ ኢንተርናሽናል ቢገልፅም፤የአልበሽር መንግስት ቁጥሩ እጅግ የተጋነነ ነው ሲል አጣጥሎታል፡፡

በሲኒማው ዘርፍ አስተዋጽኦ ለማድረግና ለፊልም ተመልካቹ የፊልሞችን ተደራሽነት ለማስፋት እየሠራ እንደሆነ የገለፀው ባታ ሪል እስቴት፤በ22 ማዞሪያ አካባቢ ባስገነባው “ባታ ኮምኘሌክስ” ህንጻ ላይ ዘመናዊ ሲኒማ ቤት እንደሚከፍት አስታወቀ፡፡ በመዲናችን የፊልም ማሣያ ሲኒማ ቤት እጥረት እንዳለ ተገንዝቤያለሁ ያለው ድርጅቱ፤ክፍተቱን ለመሙላት በቅርቡ “አቤል ሲኒማ” ን በመክፈት አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር አስታውቋል።

በሙሉጌታ ቢያዝን የተሰናዳው ባለ “ሚኒስከርቷ” የሥነ ግጥምና አጫጭር ታሪኮች ስብስብ የተሰኘ መድበል ታትሞ ሰሞኑን ለገበያ ቀረበ፡፡ በ83 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ ግጥሞችንና ታሪኮችን ያካተተ ሲሆን በ25 ብር እየተሸጠ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ደራሲ መስፍን ኃ/ማርያም ይዘከራል “በመፃህፍት የዋጋ ተመንና ዋጋ የመፋቅ ጉዳይ” ላይ ከአከፋፋዮችና አዟሪዎች እንዲሁም ከባለድርሻ አካላት ጋር ዛሬ በብሄራዊ ቤተመዛግብትና ቤተመፃህፍት አዳራሽ ምክክር እንደሚደረግ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ገለፀ። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የመፅሃፍ ዋጋ በህትመቱ ላይ ከተገለፀው ውጪ በተለያዩ መንገዶች እየተፋቀና እየተደለዘ በተጋነነ ዋጋ ለአንባቢያን መቅረቡ እንዳሳሰበው የጠቆመው ማህበሩ፤ድርጊቱ ደራሲውንም አንባቢውንም እየጎዳ ነው ብሏል፡፡ የማህበሩ የፅ/ቤት አስተባባሪና የሬዲዮ ፕሮግራም ዋና አዘጋጅ አቶ ደሳለኝ ስዩም ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤በአሁኑ ጊዜ የመፅሃፉ ዋጋ 50 ብር ሆኖ ሳለ 0 በመጨመር 500 ብር እንዲሁም 25 ብር የሚለውን 250 ብር በማድረግ በተጋነነ ዋጋ እየተሸጠ ሲሆን ጉዳዩ በባለድርሻ አካላቱ ትኩረት እንዲያገኝ የዛሬው የምክክር መድረክ ተዘጋጅቷል ተብሏል፡፡ በሌላ በኩል ታዋቂውንና አንጋፋውን የሥነፅሁፍ መምህርና ደራሲ መስፍን ኃ/ማርያም የሚዘክር ዝግጅት በመጪው ማክሰኞ እንደሚካሄድ ማህበሩ አስታወቀ፡፡ “ዝክረ መስፍን ኃ/ማርያም” በሚል የተዘጋጀው ፕሮግራም በብሔራዊ ሙዚየም የሚቀርብ ሲሆን በእለቱ ደራሲው በኢትዮጵያ ሥነፅሁፍ ውስጥ ያበረከተው አስተዋፅኦ እየታሰበ ይመሰገናል ተብሏል፡፡

የሚውዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ መሥራች የነበረው የአርቲስት ሽመልስ አራርሶን የህይወት ታሪክ የሚዘክረው ፊልም

የፊታችን ሐሙስ በጣይቱ ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በሚካሄድ ስነ ስርዓት ይመረቃል፡፡
የአርቲስቱን 7ኛ የሙት ዓመት መታሠቢያ ምክንያት በማድረግ በቁም ነገር ሚዲያ ስቱዲዮ የተዘጋጀው ዘጋቢ ፊልም፤

የአርቲስቱ  የህይወት ጉዞና ሥራዎች ላይ ያተኩራል ተብሏል፡፡ በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ ስለአርቲስት ሽመልስ አራርሶ

የሙያ ምስክርነትና ልዩ ልዩ ኪነ-ጥበባዊ ዝግጅቶች የሚቀርቡ ሲሆን በኤክስኘረስ ባንድ ጣዕም ያላቸው ሙዚቃዎችም

ይቀርባሉ ተብሏል።

“ድብቆቹ ህገ-ደንቦች! የጽዮናውያን አለሙን የመቆጣጠር እቅድ ሰነድ” የተሰኘውና በግደይ ገ/ኪዳን የተዘጋጀው መጽሃፍ ሁለተኛ ጥራዝ ለገበያ ቀረበ፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም 24 ህገ ደንቦች የያዘውን የመጽሃፉን የመጀመሪያ ክፍል ለአንባቢያን ያቀረበ ሲሆን በዚህኛው የመጽሃፉ ክፍል ስለ ህገ-ደንቦች ታሪካዊ አመጣጥ እንዲሁም ህገ-ደንቦች እውነተኛ ናቸው፣ ወይንስ የግምት የሚሉ መከራከሪያ ሃሣቦች እንደተካተቱ ተጠቁሟል፡፡ ደራሲው ከዚህ ሌላ “ጥንታዊ ውጊያ”፣ “ህልም አጨናጋፊዎቹ”፣ “የአሜሪካ የሚስጥር ተቋም” በሚሉ ሥራዎቹም ይታወቃል፡፡

ማነው ተጠያቂ ጋዜጠኞች፤ አሰልጣኙ፤ ተጨዋቾች፤ ፌደሬሽኑ? በደቡብ አፍሪካ አዘጋጅነት ሲካሄድ የቆየው 3ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ከኢትዮጵያ ጋር በአንድ ምድብ የነበሩት ጋና እና ሊቢያ በሚያደርጉት የዋንጫ ጨዋታ ዛሬ ሊፈፀም ነው። በምድብ 3 የነበረው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በሊቢያ 1ለ0 እንዲሁም በጋና 2ለ0 መሸነፉ ይታወሳል፡፡ በዚሁ ምድብ እርስ በራስ በተገናኙበት ጊዜ ጋና እና ሊቢያ 1 እኩል አቻ ተለያይተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቡድን ያለበት ምድብ በደቡብ አፍሪካ በተደረገ አህጉራዊ ሻምፒዮና ለዋንጫ ጨዋታ የደረሱ ሁለት ቡድኖችን ሲያስገኝ የቻን የዋንጫ ጨዋታ ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡ ከዓመት በፊት እዚያው ደቡብ አፍሪካ በተስተናገደው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ቡድን በምድብ 3 ከናይጄርያ፤ ቡርኪናፋሶ እና ዛምቢያ ጋር ተደልድሎ ነበር። በምድብ ጨዋታዎች ዋልያዎቹን ናይጄርያዎች 2ለ0 እንዲሁም ቡርኪናፋሶ 4ለ0 አሸንፈው እርስ በራስ ተገናኝተው 0ለ0 አቻ ከተለያዩ በኋላ በፍፃሜ ጨዋታ ናይጄርያ 1ለ0 ቡርኪናፋሶን በማሸነፍ ዋንጫውን ወስዳለች፡፡ ሊቢያ እና ጋና ለቻን የዋንጫ ያለፉት ተጋጣሚዎቻቸውን በመለያ ምቶች አሸንፈው ነው፡፡ ጋና ናይጄርያን 4ለ1 ስታሸንፍ ሊቢያ ደግሞ ዚምባቡዌን 5ለ4 በመርታት ለፍፃሜው ደርሰዋል።

የሊቢያው አሰልጣኝ ሃቪዬር ክሌሜንቴ በወጣቶች ስብስብ የተጠናከረው ቡድናቸው ለዋንጫ ጨዋታ የደረሰበትን አስደናቂ ጥረት እንደሚከሩበት የተናገሩ ሲሆን፤ የጋና አሰልጣኝ ማክሲም ኒኮዲ በበኩላቸው በቻን ውድድር ምርጥ ብቃት ያሳዩ ወጣት ጋናውያን ዋንጫውን በመውሰድ ለጥቋቁሮቹ ክዋክብቶች የዓለም ዋንጫ እድል መነቃቃት እንዲፈጥሩ ተስፋ አድርገዋል፡፡ ሊቢያ በአህጉራዊ ውድድር ለዋንጫ ጨዋታ ስትደርስ ከ1982 እኤአ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ሲሆን በ2009 እኤአ ላይ በኮትዲቯር በተካሄደው 1ኛው ቻን ላይ በዋንጫ ጨዋታ በዲሪ ኮንጎ 2ለ0 ተሸንፋ ዋንጫውን ያጣችው ጋና ክብሩን መልሶ ለማግኘት አጋጣሚ ተፈጥሮላታል፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ለቻን ውድድር ባዘጋቸው 3.2 ሚሊዮን ዶላር የሽልማት ገንዘብ መሰረት ሻምፒዮን ቡድን 700 ሺ ዶላር፤ ለሁለተኛ ደረጃ 400ሺ ዶላር፤ ለደረጃ የሚጫወቱ ሁለት ቡድኖች እያንዳንዳቸው 250ሺ ዶላር፤ በሩብ ፍፃሜ የወደቁ አራት ቡድኖች እያንዳንዳቸው 175ሺ ዶላር፤ በምድባቸው 3ኛ ደረጃ ያገኙ 125ሺ ዶላር እንዲሁም በየምድባቸው አራተኛ ደረጃ ይዘው የጨረሱ ቡድኖች እያንዳንዳቸው 100ሺ ዶላር እንደሚከፈላቸው ታውቋል። 3ኛው የአፍሪካ አገራት የእግር ኳስ ሻምፒዮና ቻን ውድድር ዛሬ በዋንጫ ጨዋታ ኬፕታውን በሚገኘው የኬፕታውን ስታድዬም ሲደረግ የፊፋው ፕሬዝዳንት ሴፕ ብላተር በክብር እንግድነት የሚገኙ ሲሆን በታዋቂ የደቡብ አፍሪካ ሙዚቀኞች እና ዳንሰኞች ልዩ የመዝጊያ ስነስርዓት እንደሚደረግም ታውቋል፡፡ ከዋንጫ እና የደረጃ ጨዋታዎች በፊይት በቻን ውድድር በተደረጉ 28 ጨዋታዎች 72 ጎሎች የተመዘገቡ ሲሆን ይህም በአንድ የቻን ጨዋታ 2.6 ጎል በአማካይ የሚቆጠርበት ሆኗል፡፡

በደቡብ አፍሪካ መስተንግዶ የቻን ውድድር ለ3ኛ ጊዜ በስኬት እንደተከናወነ እየተገለፀ ሲሆን፤ በውድድሩ የሚመዘገብ ውጤት በወዳጅነት ጨዋታ ደረጃ ለፊፋ ወርሃዊ የእግር ኳስ ደረጃ ነጥብ የሚያሰጥ ሊሆን መብቃቱ አዲስ የለውጥ ምእራፍ ነው ተብሏል። በቻን ውድድር ተሳታፊ በሆኑ 16 ብሄራዊ ቡድኖች ለአፍሪካ እግር ኳስ ተተኪ የሚሆኑ ታዳጊ ተጨዋቾች በብዛት መታየታቸው፤ ተመጣጣኝ ፉክክሮች መደረጋቸውም ተደንቋል፡፡ በሌላ በኩል የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን በ2015 ለሚደረጉ ውድድሮች የማጣርያ ጨዋታዎች ድልድን ከሰሞኑ ይፋ አድርጓል፡፡ በ2015 እኤአ ላይ ሞሮኮ ለምታስተናግደው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በተዘጋጀው የማጣርያ ፕሮግራም ላይ 51 አገራት ተሳታፊ ሲሆኑ ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት ዓመታት በአህጉራዊ ውድድሮች ባስመዘገበችው ውጤት ለምድብ ማጣርያ በቀጥታ ካለፉት 21 አገራት አንዷ ሆናለች፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ29 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ እና በዋና ውድድር በነበረው ተሳትፎው 4 ነጥብ፤ በ2012 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ተሳትፎው 1 ነጥብ፤ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ የማጣርያ ጨዋታዎች በ7 ነጥብ አስመዝግቦ በአጠቃላይ 12 ነጥብ ለምድብ ማጣርያ ካለፉት 21 አገራት መካከል 16ኛ ደረጃ አግኝቷል፡፡ በተያያዘ ካፍ በ2015 በሀ20 እና በሀ17 ብሄራዊ ቡድኖች ለሚደረጉ የቅድመ ማጣርያ ውድድሮች የጨዋታ ድልድል አሳውቋል። ኢትዮጵያ በ2015 ሴኔጋል በምታዘጋጀው የሀ20 ሻምፒዮና በቅድመ ማጣርያ ከሲሸልስ ጋር የትገናኝ ሲሆን በደርሶ መልስ ጥላ ለማለፍ ከበቃች በሁለተኛ ዙር ማጣርያ ተጋጣሚዋ ደቡብ አፍሪካ ነች፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ2015 በሀ17 ኒጀር ለሚደረገው የታዳጊዎች አህጉራዊ ሻምፒዮና የቅድም ማጣርያ እንድትሳተፍ የቀረበውን ግብዣ ሳትቀበል ቀርታለች፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢትየጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ኃላፊዎች ዛሬ በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ከጋዜጠኞች እና ከባለድርሻ አካላት ጋር የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን የነበረውን ተሳትፎ በሚመለከት የግምገማ መድረክ ሊያወያይ እንደሆነ ታወቀ፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ፤ ተጨዋቾች እና ፌደሬሽን ከናይጄርያ ጋር በካላባር ከተደረገው የዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ጨዋታ በኋላ በተለያዩ አወዛጋቢ አጀንዳዎች ከስፖርት ጋዜጠኞች የጀመሩት ንትርክ ሰሞኑን ተባብሷል፡፡ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ የኢትየጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ኃላፊዎች ከ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውን ጨምሮ በቻን ውድድር ላይ የነበሩ ተጨዋቾች እና ከቡድኑን አባላት በኢንተርኮንቲነታል ሆቴል ስብስባ ያደረጉ ሲሆን በዚሁ መድረክ አንዳንድ ተጨዋቾች በቻን ተሳትፎ ውጤቱ የጠፋው የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች የሚሰጡት አስተያየት አዕምሯችንን በመረበሹ እና በመበጥበጡ በማለት አቤቱታ ማሰማታቸው ተነግሯል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በቻን ውድድር ያሳየው ደካማ እንቅስቃሴ እና ውጤቱ ከምን የመጣ ነው? በሚል ርዕስ በተካሄደው ስብሰባ ተጨዋቾቹ አስተያየት ሲሰጡ ከመጀመሪያው ቀን ሽንፈት በኃላ በነበሩት ሁለት ጨዋታዎች ሜዳ ውስጥ እንዴት መጫወት እንዳለብን እስክንዘነጋ ድረስ የጋዜጠኞቹ ትችት ተፅእኖ ነበረው ብለው አማርረዋል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ አዋቂ ነኝ ባይ ሰው ወደገበያ ቦታ ይሄድና “ዕጣ - ፈንታችሁን እነግራችኋለሁና ማወቅ

የምትፈልጉ ተሰብሰቡ” ይላል፡፡
ሰው ባንድ ጊዜ ይሰበሰባል፡፡ ለመጀመሪያው ሰውዬ፤ “ምን እንድረዳህ ትፈልጋለህ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ይህ ሰውዬ

አለባበሱ ለየት ያለ ነው፡፡ በጣም ደማቅ አረንጔዴ ካፖርትና አረንጓዴ ቆብ አድርጓል፡፡ አረንጔዴ ጫማም ተጫምቷል፡፡
ሰውዬውም፤ “እዚህ አገር ያልሞከርኩት ሥራ የለም፡፡ ሆኖም ሊያልፍልኝ አልቻለም፡፡ አሁን ተስፋ ወደመቁረጡ ነኝ፡፡

የመጨረሻ ዕድሌን አንተ በምትሰጠኝ ምክር እሞክራለሁና ምክርህን ለግሰኝ” አለው።
አዋቂውም፤ “ዕጣ ፈንታህ ይታየኛል፡፡ የሚያልፍልህ የተጠራቀመ ሀብት አለና እሱን ካለበት ቦታ ቆፍረህ በማውጣት

ነው፡፡ ያ ሀብት ባለቤቱ በቀላሉ ሳይወጣ ሳይወርድ፣ ሳይደክም ያገኘው በመሆኑ አይጠቀምበትም፡፡ ውድ ውድ የቤት

ዕቃዎች፣ የቅርሳቅርስ ጌጦች፣ አልማዝና ወርቆች እንዲሁም የከበረ ድንጋይ አለው፡፡ አሁን የአንተ አንድ ትልቅ ሥራ

የዚያ ሰው ቤት የት እንዳለ ማወቅ ብቻ ነው፡፡ እንደምንም ቤቱን ካገኘኸው፤ እሱ ብዙ ጊዜውን ውጪ ስለሚያሳልፍ

ልትወስድበት ትችላለህ” አለው፡፡
ሰውዬው ተደስቶ በስንት ጊዜ ካጠራቀመው ገንዘብ አውጥቶ ለአዋቂው ዋጋውን ከፈለው፡፡ አዋቂው በጣም አመስግኖት

“እንግዲህ በደማቅ አረንጔዴ ካፖርትህ፣ በጫማህና በባርሜጣህ አስታውስሃለሁ” አለው፡፡ ባለአረንጓዴ ካፖርቱ ሰው

መንገዱን ቀጠለ፡፡
አዋቂውም ሌሎች ተረኛ ሰዎችን እያነጋገረ፤ ዕጣ ፈንታቸውን መንገሩን ቀጠለ፡፡ አንዷን “ምቀኞች አሉብሽና ሰፈርሽን

ለቀሽ ሌላ ቦታ ኑሪ” ይላታል፡፡ አመስግናው ገንዘብ ከፍላ ትሄዳለች፡፡ አንዱን ደግሞ “አለቃህን ደጅ ካልጠናህ በስተቀር

አይሳካልህም፡፡ ስታየው ላንተ ደግ ይመስልሃል፤ ግን ዕድገትህን ቆልፎ ይዞብሃል” አለው፡፡ አመስግኖና ገንዘብ ከፍሎት

ይሄዳል፡፡ ሌላውን “አዲስ ሸሪክ ያዝ፡፡ እስካሁን አብሮህ ይሠራ የነበረው ሰው ምቀኛህ ነው!” ይለዋል፡፡ ይሄም ገንዘብ

ሰጥቶት አመስግኖት ይሄዳል፡፡ በዚህ ዓይነት ለብዙ ሰዓታት የዕጣ - ፈንታ ትንቢት ሲነግር ይቆያል፡፡
በድንገት አንድ ሰው ወደ አዋቂው እየሮጠ ይመጣል፡፡
“ምነው ምን ሆነህ እንዲህ እያለከለክህ መጣህ?” ሲል አዋቂው ይጠይቃል፡፡
ሲሮጥ የመጣውም ሰውዬ፤
“አዋቂ ሆይ! እኔ የሰፈርህ ሰው ነኝ፡፡ የሰፈራችን ሰዎች ሁሉ ተሰብስበው “ያን አዋቂ ከወዴት እናግኘው?” ሲባባሉ

ሰማሁ፡፡ “ለምን ፈለጋችሁት ብዬ ብጠይቅ፤ “ሌባ ቤቱ ገብቶ ያለ የሌለ ንብረቱን ጥርግርግ አድርጐ ወስዶበት ሄደ”

አሉኝ፡፡ እኔም የሰፈር ሰው ሆኜ ሳልነግርህ ብቀር ጥሩ አይሆንም!” ብዬ ስሮጥ መጣሁ አለው”
አዋቂው እጅግ ተደናግጦ ተነስቶ ወደሠፈሩ በረረ፡፡ ሰዎች ተሰብስበው አገኘ፡፡
“ምን ዓይነት ሰው ነው የሰረቀኝ? አይታችሁታል ወይ?” ሲል ጠየቀ፡፡
ሁሉም ዝም ዝም አሉ፡፡ አንድ ትንሽ ልጅ ግን፤
“እኔ አይቸዋለሁ” አለ፡፡
“ምን መሳይ ነው?” ሲል ጠየቀ አዋቂው፡፡
ልጁም፤
“አረንጌዴ ካፖርት፣ አረንጔዴ ባርሜጣ፣ አረንጔዴ ጫማ ያረገ ነው!” አለው፡፡
“አዬ ጉድ! በገዛ ጥይቴ ነዋ የተመታሁት!” ብሎ እያዘነ ወደቤቱ ገባ፡፡
*    *    *
አበሻ “ጠንቋይ ለራሱ አያውቅ!” ይላል፡፡ የሌሎችን እጣ - ፈንታ እየተናገረ የራሱን ዕጣ ፈንታ አያውቅም ለማለት ነው፡፡

አብዛኞች የታዳጊ አገር መንግሥታት የራሳቸው ቤት እየተዘረፈ ስለሌሎች አገሮች ሙስና ሲያወጉ ያመሻሉ፡፡
የብሪቲሽ ጠቅላይ ሚኒስቴር ጂም ካላግሃን ለፓርላማው ባረጉት ንግግር “ውሸት የዓለምን ግማሽ አዳርሶ ሲጨርስ፤

ዕውነት ገና ቦት - ጫማውን እያጠለቀ ነው!” ያለው ወዶ አደለም፡፡ ቀጣፊው ቢበዛበት ነው፡፡
የምንናገረው የምናወጣው መመሪያ የምንመራበት መራሄ - ፅድቅ፣ የምናቅደው እቅድ፤ የምንነድፈው ስትራቴጂ፤

መሠረታቸው ዕውነት እንጂ ባዶ ተስፋ መሆን የለበትም፡፡ ዕውነት ላይ ስንመረኮዝ አዕምሮአችንም ልቡናችንም ከፍሬ

ጉዳያችን ጋር የተቆራኘ ይሆናል፡፡ የምናፈራው ፍሬ የዚህ ውጤት ነው፡፡
ለመንገዶቻችን ሁሉ አማራጭ እናብጅላቸው፡፡ በህይወት ውስጥ አንድና ቀጥ ያለ መንገድ አይገኝም። በርካታ መንገዶች

ናቸው የመሻሻል አማራጭ የሚሰጡን፡፡
ብልጧን አይጥ ተመልከት፡፡ ኑሮዋን ለአንድ ጉድጓድ ብቻ አትሰጥም” ይላሉ ጣሊያኖች፡፡ አንድም በገዢው ፓርቲ ትይዩ

በተፃራሪ የቆሙ፣ አንድም ወግነው ያሉ ሁለት ቁምነገሮችን ማሰብ አለባቸው፡፡
አሿፊው እረኛ፤ “ተኩላ ተኩላ!” እያለ ሲቀልድ ከርሞ ዕውነተኛው ተኩላ መጥቶ በጐቹን ሲበላ ማን ያግዘው? ዋዛ ፈዛዛ

ልብ አያስገዛ! ሆነ!!”
በአንፃሩ አንድ ፀሐፊ እንዳለው፤
“እሳት! እሳት” ስትል “ቀጣፊ ነሽ” ሲሏት
ሰፈሩ ነደደ፣ በዐይናቸው እያዩት!”
የሚለውንም አንርሳ፡፡ የሀገር ጉዳይ የዋዛ ፈዛዛ አይደለም፡፡ የሚሉንን እንስማ፡፡ እሳት ከነደደ በኋላ፣ ቤት ፈርሶ ካበቃ

በኋላ አይደለም ህዝባችን አደገ ማለት ያለብን፡፡ ከህዝብ እንመካከር፡፡
ለማሰብ ከሰነፍን፣ መጥፎ ሥራ እንኳ ለመሥራት ከንቱ ከሆን፣ ያንን ለመቀበልም ከፈራን፤ ጥበብና ብስለት የሚባል

በሠፈራችን አይደርስም፡፡
ወጣቶችን በመልካም ስብዕና መቅረፅ የሁሌም ግዴታችን መሆን አለበት፡፡ “አጓጉል ትውልድ ያባቱን መቃብር ይንድ”

ነውና ታሪክን፣ ባህልን፣ ብሔረተኝነትን፣ ጀግንነትን ይዞ ያላደገ ትውልድ የማንነት ድቀት ወይም ቀውስ (Identity

crisis) ውስጥ እንደሚገባ የዓለም ታሪክ በስፋት አሳይቶናል፡፡ የወላጅ የመምህርና የመንግሥት ሦስትዮሽ ድጋፍ

ያስፈልገዋል፡፡
አንድም በግብረ - ገብነት፣ አንድም በትምህርት፣ አንድም በፖለቲካ ስብዕና ብቃት እንዲጠናና እንዲጐለብት ማድረግ

በተለይ ዛሬ ዋና ጉዳይ ነው!
ሽማግሌዎቹ ወጣቶቹን ከእናንተ እንበልጣለን ሲሉ፤ ወጣቶቹ ይሄ ምን ዓይነት የጅል አስተሳሰብ ነው እያሉ

እስከሚመራመሩና እስኪያሰላስሉ፤ ሲያረጁ፤
መላው ቀለጠ፡፡ አገር ከሰረ፡፡
“ሲዋሽ ልክ እንደምሥክር ነው” ይላሉ ሩሲያኖች፡፡ የምንዋሸው ነገር የትውልድ መዳከም ነው፡፡ ዛሬም እናስብበት!
“የምዋሸው ዕውነቴን ለመቆጠብ ብዬ ነው” አለ አሉ አያ ዋሾ፡፡ የረቀቀ ውሸት መዋሸት ካልቻልን በስተቀር ዕውነት

መናገርን መመሪያ ማድረግ ምርጥ ነገር ነው!!

          የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት የነበሩትና በአሁኑ ሰዓት የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ የሆኑት የተከበሩ አቶ ኡመድ ኡባንግ፤ ከአገር መኮብለላቸውን ምንጮቻችን ገለፁ፡፡ አቶ ኡመድ ኡባንግ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ ላይ ከሃገር መውጣታቸውን የጠቆሙት ምንጮች፤ ወደ ኢትዮጵያ እንደማይመለሱ ለሚቀርቧቸው ሰዎች መናገራቸውን አመልክተዋል። የሚኒስትር ዴኤታውን መኮብለል በተመለከተ የጠየቅናቸው የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያም፤ አቶ ኡመድ በስራ ገበታቸው ላይ እንደሌሉ ማረጋገጣቸውን ገልፀው መስሪያ ቤታቸው ለተለየ ተልዕኮ እንዳላሰማራቸውና ፈቃድ ሳይጠይቁ ከስራ ገበታቸው እንደቀሩ ተናግረዋል፡፡ ሚ/ር መስሪያ ቤታቸው ጉዳዩን እያጣራ መሆኑንም አክለው ገልፀዋል፡፡ አቶ ኡመድ ከጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንትነት የተነሱት በክልል መንግስቱ የስራ አፈፃፀም ላይ ለአንድ ሳምንት ከዘለቀ ግምገማ በኋላ ሲሆን፤ ሌሎች የክልሉ ባለስልጣናትም በዚሁ ግምገማ ከኃላፊነታቸው መነሳታቸው ይታወሳል፡፡