Administrator

Administrator

Saturday, 16 August 2014 11:18

የፍቅር ጥግ

ባሎች እንደ እሳት ናቸው፤ ካልተከታተሏቸው ይጠፋሉ፡፡
Zsa Zsa Gabor
(ትውልደ ሃንጋሪ አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይ)
ሚስቶች ለወጣት ወንዶች ውሽሞች፣ ለጎልማሶች ጓደኞች፣ ለአዛውንቶች ነርሶች ናቸው፡፡
ፍራንሲስ ቤከን
(እንግሊዛዊ ፈላስፋ፣ የፖለቲካ ሊቅና የህግ ባለሙያ)
ከ13 ዓመት ተኩል ዕድሜዬ ጀምሮ ከአስር ሺ ሴቶች ጋር ተኝቻለሁ፡፡
ጆርጅስ ሳይመን
(ትውልደ ቤልጂየም ፈረንሳዊ ፀሐፊ)
ሚስቱ ግን “ትክክለኛው ቁጥር ከ1200 አይበልጥም” ብላለች
በየምስቅልቅሉ አንድ ወዳጅ፣ በየወደቡ አንድ ሚስት አገኛለሁ፡፡
ቻርልስ ዲብዲን
(እንግሊዛዊ ተዋናይ፣ አቀናባሪና ጸሐፌ ተውኔት)
ሴቶች እንደ ባንክ ናቸው፤ ሰብሮ መግባት ትልቅ ሥራ ነው፡፡
ጆ ኦርቶን
(እንግሊዛዊ ፀሃፌ ተውኔት)
ፍቅር የሌለበት ትዳርና ትዳር የሌለበት ፍቅር አንድ ናቸው፡፡
ኬኔዝ ክላርክ
(እንግሊዛዊ የሥነ-ጥበብ ታሪክ ምሁር)
ገንዘብ ፍቅር ስለማይገዛልኝ፣ ለገንዘብ ብዙም ደንታ የለኝ፡፡
ጆን ሊኖን
(እንግሊዛዊ የሮክ ሙዚቃ አቀንቃኝ)

     ብራዚል ካዘጋጀችው 20ኛው ዓለም ዋንጫ 1 ወር ካለፈ በኋላ የዓለም ስፖርት አፍቃሪ ትኩረት ወደ አምስቱ የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች ዞሮ ቆይቷል፡፡ አምስቱ የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ፤ የስፔን ፕሪሚዬራ ሊጋ፤ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ፤ የጣሊያን ሴሪኤና የፈረንሳይ ሊግ 1 ሲሆኑ በሚቀጥሉት 9 ወራት በከፍተኛ ደረጃ ፉክክር ይደረግባቸዋል፡፡ ከሊጎቹ ከተከፈተ አንድ ሳምንት ያለፈው የፈረንሳይ ሊግ 1 ነው፡፡ ዛሬ እና ነገ  የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ሲጀመር፤ በሚቀጥለው ሳምንት  የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋና የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋ እንዲሁም የጣሊያን ሴሪ ኤ ከሁለት ሳምንት በኋላ ይከፈታሉ፡፡
ዩሮ ቶፕ ፉት የተባለ የእግር ኳስ ድረገፅ በሊግና በአህጉራዊ ሻምፒዮናዎች  ያለውን የፉክክር ደረጃና ውጤት በማስላት  ለሊጎቹ ባወጣው ደረጃ የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ በ5887 ነጥብ አንደኛ መሆኑን አመልክቷል፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ5298 ነጥብ፤ የጣሊያኑ ሴሪ ኤ በ3428 ነጥብ እንዲሁም የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ3348 ነጥብ እስከ 4ኛ ደረጃ ተከታትለው ሲወስዱ፤ የፈረንሳዩ ሊግ 1 በ1877 ነጥብ አምስተኛነቱን 2520 ነጥብ ባስመዘገበው የፖርቱጋሉ ሊግ ተነጥቆ 6ኛ ነው፡፡
በሌላ በኩል ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ አሃዛዊ እና ታሪካዊ መረጃዎች አሰባሳቢ ተቋም የሆነው አይኤፍኤችኤችኤስ በ2014 የዓለም ምርጥ የእግር ኳስ ሊጎች  ደረጃ ባወጣበት ወቅት በ1155 ነጥብ አንደኛ የሆነው የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ ነው፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ1128 ነጥብ፤ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ1056 ነጥብ እንዲሁም የጣሊያኑ ሴሪ ኤ በ927 ነጥብ እስከ 4ኛ ደረጃ ተከታትለው ሲወስዱ፤ የፈረንሳዩ ሊግ 1 በ796 ነጥብ በብራዚል እና በአርጀንቲና የሊግ ውድድሮች ተበልጦ 7ኛ ነው፡፡ ከዓለም ዋንጫ በኋላ የአውሮፓ ክለቦች   ለአዲሱ የ2014 — 15 የውድድር ዘመን በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ቅድመ ዝግጅት በማድረግ ሰንብተዋል፡፡ ላለፉት 6 ሳምንታት ደግሞ በክረምቱ የተጨዋቾች ዝውውር ገበያ ተሯሩጠዋል፡፡  በውድድር ዘመኑ  ተጠናክረው ለመቅረብ በተለይ በአምስቱ ትልልቅ የአውሮፓ ሊጎች የሚገኙ 25 ክለቦች በገበያው ንቁ ተሳትፎ ነበራቸው፡፡ በ2014 15 የውድድር ዘመን የስፔን ላሊጋ ባርሴሎና ሪያል ማድሪድ ባሰባሰቧቸው ምርጥ ተጨዋቾች ትኩረት ቢያገኝም ከአምስት በላይ የእንግሊዝ ክለቦች በዝውውር ገበያው በርካታ ምርጥ ተጨዋቾችን በማስፈረም መጠናከራቸው ለፕሪሚዬር ሊጉ ሻምፒዮናነት ከባድ ፉክክር እንዲጠበቅ ምክንያት ሆኗል፡፡ ሁለቱ ሊጎች በክረምቱ የዝውውር መስኮት የነበራቸው ወጭ የገበያውን 63 በመቶውን የሸፈነ ነው፡፡ በአንፃሩ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ እና የጣሊያን ሴሪኤ ክለቦች ወጭያቸው በግማሽ ያነሰ ነበር፡፡
ከአውሮፓ ሊጎች ሁለቱ የስፔን ክለቦች ባርሴሎና እና ሪያል ማድሪድ 190.2 ሚሊዮን ዶላር እና 146.3 ሚሊዮን ዶላር ከፍተኛውን ወጭ ያስመዘገቡ ናቸው፡፡ ቼልሲ 124.36  ፤ማን ዩናይትድ 97.62 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም የፈረንሳዩ ፒኤስጂ እና የስፔኑ አትሌቲኮ ማድሪድ እያንዳንዳቸው 78.20 ሚሊዮን ዶላር በላይ  ወጭ  እስከ አምስት ያለውን ተከታታይ ደረጃ አግኝተዋል፡፡በዝውውር ገበያው ውድ ሂሳብ የወጣው በባርሴሎና ሲሆን አወዛጋቢውን የኡራጋይ ተጨዋች ሊውስ ስዋሬዝ በ89.3 ሚሊዮን ዶላር ከሊቨርፑል ላይ የገዛበት ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ከፍተኛው ሂሳብ የተከፈለው በሪያል ማድሪድ ሲሆን ኮሎምቢያዊውን ጄምስ ሮድሪጌዝ ከፈረንሳዩ ክለብ ሞናኮ ለማስፈረም 88.2 ሚሊዮን ዶላር አውጥቷል፡፡ ቼልሲ ብራዚላዊውን ዴቭድ ሊውስ ለፈረንሳዩ ክለብ ፓሪስ ሴንትዠርመን የሸጠበት 54.57 ሚሊዮን ዶላር ሂሳብ ፤ አሁንም ቼልሲ ስፔናዊውን ዲያጎ ኮስታ ከአትሌቲኮ ማድሪድ በ41.9 ሚሊዮን ዶላር የገዛበት እንዲሁም አርሰናል ቺሊያዊውን አጥቂ አሌክሲ ሳንቼዝ ከባርሴሎና ለማዛወር የከፈለው 41.67 ሚሊዮን ዶላር ተከታታይ ደረጃ ይወስዳሉ፡፡
የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ዛሬ ሲጀመር  ሌስተር ሲቲ፤ በርንሌይ እና ኪውንስ ፓርክ ሬንጀርስ ሊጉን የተቀላቀሉ አዲስ ክለቦች ናቸው፡፡ በውድድር ዘመኑ ከሚጠበቁ ፍጥጫዎች ዋንኛው በአዲሱ የማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ሊውስ ቫንጋል እና በቼልሲው ጆሴ ሞውሪንሆ መካከል ለሻምፒዮናነት የሚደረገው እሰጥ አገባ የሞላበት ፉክክር ነው፡፡ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግን ጨምሮ በተለያዩ ሊጎች አራት ክለቦችን ለሊግ ሻምፒዮናነት ያበቁት ሆላንዳዊው ሊውስ ቫንጋል  የማንችስተር ዩናይትድን የሃያልነት ክብር ለመመለስ ተስፋ ተጥሎባቸዋል፡፡
በዛሬዎቹ የመክፈቻ ጨዋታዎች ለዋንጫ ከሚፎካከሩት አምስቱ ክለቦች መካከል የሚጫወቱት ከሜዳው ውጭ ኪውፒአርን የሚገጥመው ቼልሲ እና በኦልድትራፎርድ ስዋንሴን የሚያስተናግደው ማንዩናይትድ ይሆናሉ፡፡ ሌሎቹ ትልልቅ ክለቦች በነገው እለት የመክፈቻ ግጥሚያቸውን ያደርጋሉ፡፡ ያለፈው ዓመት የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ማንቸስተር ሲቲ የውድድር ዘመኑን የሚከፍተው ከሜዳው ውጭ ከኒውካስትል ዩናይትድ ጋር በሚያደርገው ፍልሚያ ነው፡፡ በሌላ በኩል ባለፈው የውድድር ዘመን የኤፍ ኤካፕ ዋንጫን ያነሳውና ከሳምንት በፊት የሊግ ካፕ ዋንጫን ማንቸስተር ሲቲን በመርታት የውድድር ዘመኑን በዋንጫ ድል የከፈተው አርሰናል በሜዳው ከክሪስታል ፓላስ ጋር ይጫወታል፡፡ በሌላ በኩል በታሪኩ ለ84ኛ ጊዜ በሚደረገው የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ ከሚሳተፉ 20 ክለቦች ሰባቱ አዳዲስ አሰልጣኞች በመያዝ በውድድሩ ሲገቡ ባርሴሎና፤ ዲፖርቲቮ ላካሩኛ እና ሴልታ ቪጎ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ላሊጋው ከመጀመሩ አንድ ወር ቀደም ብሎ ማነጋገር የጀመረው ሊውስ ስዋሬዝ በባርሴሎና ክለብ የሚኖረው ሚና ነው፡፡ በክለቡ ባርሴሎና ከኔይማር እና ከሜሲ ጋር የሚጫወትበት አሰላለፍ እና ፉክክር ማነጋገሩን ቀጥሏል፡፡ ስዋሬዝ ንክሻውን ስላለመድገሙ በተነሱ ክርክሮችም ሰፊ ሽፋን ሲያገኝ ሰንብቷል፡፡

ባለፉት 10 ዓመታት በዓለም እግር ኳስ የቢሊዬነሮች ሚና እና የኢንቨስትመንት ድርሻ እያደገ መጥቷል፡፡ በተለይ በአውሮፓ አምስት ታላላቅ ሊጎች   በቢሊዬነሮች ሙሉ ለሙሉ በባለቤትነት በመያዛቸውና በከፍተኛ የአክሲዮን ድርሻ ኢንቨስት ስለተደረገባቸው  የፉክክር ደረጃቸውን ያሳደጉ ከ10 በላይ ክለቦች ናቸው፡፡ በአንፃሩ  የቢሊዬነሮች ኢንቨስትመንት ያለደረሰላቸው በርካታ የአውሮፓ  ክለቦች ምንም እንኳን በየሊጎቹ በቴሌቭዥን ስርጭት መብት እና በተያያዥ ንግዶች  ገቢያቸው ቢጠናከርም በዋንጫ ተፎካካሪነታቸው ያን ያህል እየተሳካላቸው አይደለም፡፡  በክለቦች ደረጃ በሚደረጉ የውስጥ ውድድሮች እና አህጉራዊ ሻምፒዮናዎች ላይ በሚገኝ ስኬት ቢሊዬነሮች ተማርከዋል፡፡ ወደ እግር ኳሱ የመሳባቸው ዋና ምክንያት ትርፋማነቱ  እንደሆነም ይገለፃል፡፡
ታዋቂው የቢዝነስ መፅሄት ፎርብስ በሰራው ጥናት  መሰረት በመላው ዓለም በእግር ኳስ ክለብ  ሙሉ ባለቤትነት እና የአክሲዮን ድርሻ ያላቸው ቢሊዬነሮች ከ50 በላይ ሆነዋል፡፡ እነዚህ ቢሊዬነሮች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች የተሳካላቸው ሲሆኑ አሜሪካውያን ነጋዴዎች፤ ኤስያውያን  ቱጃሮች፤ የአረቡ ዓለም ንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት፤ የራሽያ ቢሊየነሮች ዋና ዋናዎቹ  ናቸው፡፡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ተወዳዳሪ ከሆኑ 20 ክለቦች መካከል 7 ያህሉ ከሌላ አገር በመጡ ቢሊዬነር ኢንቨስተሮች የተያዙ ናቸው፡፡  ባለፉት ሶስት እና አራት ዓመታት የቢሊዬነሮችን ትኩረት በመሳብ የስፔንና የፈረንሳይ ክለቦችም እየቀናቸው ናቸው፡፡
የአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች በአፍሪካ፤በኤስያ በዓረቡ ዓለም እና በሰሜን አሜሪካ በሚያገኙት ትኩረት ቢሊዬነሮቹ  ይማረካሉ። ከፍተኛ ኢንቨስትመንት በመላው ዓለም ለሚያንቀሳቅሱባቸው ኩባንያዎች የክለቦቹ ስኬት አስደናቂ የገፅታ ግንባታ ያስገኝላቸዋል። የእግር ኳስ ክለቦች እንደ አሰተማማኝ  ንብረት መታየታቸው ሌላው ጉልህ ጠቀሜታ ነው፡፡ በዓለም እግር ኳስ ክለቦች  አጠቃላይ የዋጋ ግምት በተሰራው ደረጃ  የስፔኑ ክለብ ሪያል ማድሪድ በ3.4 ቢሊዮን ዶላር ዋጋው በመተመን አንደኛ ደረጃ  ሲይዝ ባርሴሎና በ3.2 ቢሊዮን ዶላር ይከተለዋል፡፡  ማንችስተር ዩናይትድ በ3.17 ቢሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃ ሲያገኝ፤ ባየር ሙኒክ በ1.85 ቢሊዮን ዶላር፤ አርሰናል በ1.33 ቢሊዮን ዶላር፤ ቼልሲ በ901 ሚሊዮን ዶላር፤ ማንችስተር ሲቲ በ689 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም ሊቨርፑል በ651 ሚሊዮን ዶላር አጠቃላይ የዋጋ ተመናቸው ተከታታይ ደረጃ አላቸው፡፡ እንደ ፎርብስ መፅሄት ጥናት በአጠቃላይ የዋጋ ግምታቸው እስከ 20 ደረጃ የተሰጣቸው የእግር ኳስ ክለቦች አማካይ ተመን  968 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን ይህም ካለፈው የውድድር ዘመን በ26 በመቶ እድገት ማሳየቱን ጠቁሟል፡፡
በእግር ኳስ ስፖርት እየተጠናከረ የመጣው የቢሊዬነሮች ኢንቨስትመንት  በየሊጎቹ ለዋንጫ የሚፎካከሩ ክለቦችን አብዝቷል፡፡ የክለቦችን የተጨዋች ስብስብ በማጠናከር እና የዝውውር እና የደሞዝ ክፍያቸውን በማሳደግ ተጠቃሚ እያደረጋቸው ነው፡፡ የቢሊዬነሮቹ ኢንቨስትመንት  ጎን ለጎን አሉታዊ ተፅኖዎችን ማሳደሩም አልቀረም፡፡ በአውሮፓ አምስት ታላላቅ ሊጎች በቢሊዬነሮቹ በጀት የሚንቀሳቅሱ  ክለቦች ውስጥ ያሉ ተጨዋቾች፤ አሰልጣኞች እና ሌሎች ባለሙያዎች በየክለቦቻቸው ለረጅም ጊዜ በታማኝነት የሚያገለግሉበትን ሁኔታ ሲያቀዘቅዝባቸው፤ ደጋፊዎች በክለቦቻቸው ያላቸውን ሚናም በከፍተኛ ደረጃ እየቀነሰ መሆኑ  ይተቻል፡፡  
አብራሞቪችና ሌሎች የሩስያ ቱጃሮች
በእግር ኳስ ክለብ ባለቤትነት  በጣም ስኬታማ የሚባሉትና በፈርቀዳጅነት የሚጠቀሱት ራሽያዊው ሮማን አብራሞቪች ናቸው። የነዳጅ ኩባንያ ባለቤት የሆኑት አብራሞቪች በቼልሲ ክለብ ባለቤትነት 12 ዓመታት አስቆጥረዋል፡፡  በመጀመርያዎቹ 3 እና አራት አመታት ብዙም ባይሳካላቸውም ካለፉት 5 ዓመታት ወዲህ ግን የላቁ ክብሮችን  በማግኘት  ተክሰዋል፡፡
አብራሞቪች ቼልሲን  በባለቤትነት ከያዙት በኋላ የተገኙ ስኬቶች ገንዘብ ያመጣቸው እንጅ በተመጣጣኝ የፉክክር ደረጃ የተገኙ አይደለም በሚል በተደጋጋሚ ትችት ቀርቧል፡፡ የምዕራብ ለንደኑ ክለብ ቼልሲ 3 የፕሪሚዬር ሊግ፤ አራት የኤፍኤ ካፕ፤ 2 የሊግ ካፕ እና በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮን በመሆን የሻምፒዮንስ ሊግ እና የዩሮፓ ሊግ የዋንጫ ክብሮችን  አግኝቷል፡፡  አብራሞቪች ክለቡን ከያዙት ግዜ ጀምሮ ከ1.3 ቢሊዮን ዶላር በላይ ወጭ አድርገውበታል፡፡ በየዝውውር መስኮቱ ወቅት በአማካይ 50 ሚሊዮን ዶላር በማውጣት ምርጥ ተጨዋች የሚገዛ ክለብ ሆኗል። አብራሞቪች ቼልሲን የገዙት በ334 ሚሊዮን ዶላር ነበር፡፡ አሁን ሊሸጡት ቢፈልጉ ክለቡ ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ያወጣል፡፡
ከአብራሞቪች በኋላ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ብቻ ሳይሆን በሌሎች የአውሮፓ ትልልቅ ሊጎች እና በአገራቸው ባሉ ክለቦችም ከ5 በላይ የራሽያ ቢሊዬነሮች  ኢንቨስት አድርገዋል፡፡ አንደኛው ቢሊዬነር በአርሰናል ክለብ ድርሻ ያላቸውና ክለቡ የሚመካበትን የኤምሬትስ ስታድዬም እንዲገነባ ከፍተኛ ድርሻ የነበራቸው አሊሸር ኡስማኖቭ ናቸው፡፡ ሌላኛው ደግሞ የፈረንሳይ ክለብ የሆነውን ሞናኮን በባለቤትነት የያዙት ዲምትሪ ራይቦሎቬሌቭ ናቸው፡፡ ሌሎቹ የራሽያ ቢሊዬነሮች በአገሮቻቸው ባሉ ክለቦችም አስደናቂ ኢንቨስትመንት አድርገዋል፡፡ የእንግሊዙ ክለብ ቼልሲ ባለቤት አብራሞቪች በራሽያ ያለውን ዜንት ፒትስበርግ በመደገፍ ሲሰሩ ቆይተዋል፡፡ በ2011 እኤአ  ከተመሰረተ 20 ዓመት የሚሆነው ወጣት ክለብ አንዚ ማክቻሃቻካላ ሌላ   ቢሊዬነር በመግዛት ወደ አህጉራዊ ውድድር አሳድገውታል፡፡
ሼክ መንሱንና የዓረቡ ዓለም ኢንቨስትመንት
የመካከለኛው ምስራቅ በተለይ በኳታር እና በዱባይ ያሉ የንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት ካለፉት አምስት አመታት ወዲህ በአውሮፓ እግር ኳስ በስፋት ተሰማርተዋል፡፡ እነዚህ የአረቡ አለም ቢሊዬነሮች ክለቦችን በባለቤትነት በመያዝ ብቻ ሳይሆን በትልልቅ ኩባንያዎቻቸው የማልያ፤ የስታድዬም ግንባታ የስፖንሰርሺፕ ድጋፎችን በስፋት በመስጠት ጥቂት የማይባሉ ክለቦችን አጠናክረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በአውሮፓ እግር ኳስ የመካከለኛው ምስራቅ አየር መንገዶች ከ20 የአውሮፓ ትልልቅ ክለቦች በሰባቱ ስፖንሰርሺፕ ሰጥተዋል፡፡ ኳታር ኤርላይንስ በባርሴሎና፤ ፍላይ ኤምሬትስ በሪያል ማድሪድ፤ በፒኤስጂ፤ በአርሰናል እና በኤሲ ሚላን፤ ኢትሃድ ኤርዌይስ በማንችስተር ሲቲ የማልያ ስፖንሰሮች  ናቸው። ከዓረቡ ዓለም የእግር ኳስ ኢንቨስትመንት አድራጊ ቢሊዬነሮች ግዙፍ ለውጥ የታየው በእንግሊዙ ክለብ ማንችስተር ሲቲ ነው። ማንችስተር ሲቲ የአቡዳቢ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ባለቤቶች በሆኑት የኳታር ንጉሳዊ ቤተሰብ ከ6 ዓመት በፊት ተይዟል፡፡ የአቡዳቢ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ያለው ሃብት እስከ  22 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ነው፡፡ የሚያስተዳድሩት ሼክ መንሱን ቢን ዛይድ  ሲቲን የገዙት በ321 ሚሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንታቸውም ነበር። ባለፉት 5 ዓመታት ክለቡን ለማጠናከር ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ፈሰስ አድርገዋል፡፡  ማንችስተር ሲቲ በአቡዳቢ ኢንቨስትመንት ግሩፕ መደገፍ ከጀመረ ወዲህ ከ44 ዓመት በኋላ የመጀመርያውን የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮናነት ማግኘቱ እና ከዚያም ሁለተኛውን መድገሙ ይታወቃል፡፡ ባለፉት ሶስት አመታት ክለቡ በእንግሊዝ እና በአውሮፓ ደረጃ የላቀ ውጤት እና ተፎካካሪነት እንዲኖረው ማድረግ ተችሏል፡፡
በ2011 እኤአ ላይ ታዋቂውን ፓሪስ ሴንትዠርመን ባበለቤትነት የያዘው የኳታር ኢንቨስትመንት አውቶሪቲ ነው፡፡ ይህ ባለቤትነት ፒኤስጂን የፈረንሳይ አንደኛ ሃብታም ክለብ አድርጎታል፡፡ ክለቡ ከ20   ዓመታት በኋላ የሊግ ሻምዮን ለመሆን በቅቷል፡፡ ባለቤቶቹ ክለቡን ለማጠናከር በተጨዋቾች ግዢ ብቻ ከ300 ሚሊዮን ዶላር በላይ አውጥቷል፡፡
በፕሪሚዬር ሊግ የተማረኩት አሜሪካውያና ኤስያውያን
ቢያንስ በስድስት የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች ላይ በባለቤት እና በአክሲዮን ድርሻ ያላቸው አሜሪካውያን ቢሊዬነሮች ናቸው፡፡ ሌርነር በአስቶንቪላ፤ የግሌዘር ቤተሰብ በማንችስተር ዩናይትድ፤ ስታን ክሮንኬ በአርሰናል፤ ኢሊስ ኾርት በሰንደር ላንድ ጆርጅ ኤሊት እና ቶም ሂክስ በሊቨርፑል ኢንቨስት ያደረጉ አሜሪካውያን ናቸው፡፡ የፉልሃምና የሰንደርላንድ ክለቦች ላይ ኢንቨስት ያደረጉ ሌሎች ሁለት  ቢሊዬነሮችም አሉ፡፡ አሜሪካውያኑ ከቤዝቦል እና ፉትቦል ክለቦች ባለቤትነት ወደ አትራፊው ፕሪሚዬር ሊግ ኢንቨስት የማድረግ ፍላጎታቸው አድጓል፡፡ በዋናነት በቲቪ ስርጭት ሊጉ በመላው ዓለም የሚያገኘው ሽፋን እና ተወዳጅነት በመማረካቸው ነው፡፡ ኤስያውያንም በአውሮፓ እግር ኳስ ኢንቨስትመንት ንቁ ተሳትፎ ማድረግ ከጀመሩ ቆይተዋል፡፡ በተለይ በደቡብ ኤስያ ባሉ አገራት ያሉ ቢሊዬነሮች በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ኢንቨስት እያደረጉ ናቸው፡፡  ኪውፒ አር፤ካርዲፍሲቲ፤ ሌስተርሲቲ በኤስያውያን ቢሊዬነሮች ባለቤትነት ተይዘዋል፡፡ ሲንጋፖራዊው ቢሊዬነር ፒተር ሊም የስፔኑን ክለብ ቫሌንሽያ በባለቤትነት የተቆጣጠሩት ባለፈው አመት ነው፡፡ ቢሊዬነሩ ቫሌንሽያን ሲረከቡ የራሳቸው እግር ኳስ ክለብ በባለቤትነት ለማስተዳደር የረጅም ግዜ ህልሜን አሳክቻለሁ ብለዋል፡፡
ክለቦች  ያሏቸው ቢሊዬነሮችና የሃብታቸው ደረጃ
በዓለም ታዋቂ የእግር ኳስ ክለብ ባለቤቶችና አክሲዮን ድርሻ ያላቸውን ባለሃብቶች ያላቸውን የሃብት ግምት በማስላት እስከ 20ኛ ደረጃ ያወጣላቸው “ዌልዝ ኤክስ” የተባለ የመረጃ ተቋም  ነው፡፡ እንደ ዌልዝ ኤክስ መረጃ  በተለይ በአውሮፓ ታላላቅ ሊጐችና በአሜሪካ ሜጀር ሶከር  ሊግ በሚወዳደሩ ክለቦች ሙሉ  ባለቤትነትና ከፍተኛ አክሲዮን ድርሻ  ያላቸው ቢሊዬነሮች ሃብት የተመዘገበላቸው ከፍተኛው 73 ዝቅተኛው 5 ቢሊዮን ዶላር ነው፡፡ በአጠቃላይ የሃብታቸው ግምት ወደ 290 ቢሊዮን ዶላር ይጠጋል፡፡ ዌልዝ ኤክስ በክለብ ባለቤት ቢሊዬነሮች ላይ በሰራው ደረጃ መሰረት እስከ 20ኛ  11 የተለያዩ አገራት ዜጋ ቢሊዬነሮች ተካትተዋል፡፡ በአጠቃላይ የሃብታቸው ግምት ወደ 290 ቢሊዮን ዶላር ይጠጋል፡፡ ከ1 እስከ አምስት ደረጃ የሚሰጣቸው ቢሊዬነሮች የክለብ ባለቤቶች  የሚከተሉት ናቸው፡፡ ዌልዝ ኤክስ በሃብት ግምት እና መረጃ የታወቀ ተቀማጭነቱን በሲንጋፖር ያደረገና በአምስቱም አህጉራት የሚንቀሳቀሰ ተቋም ነው፡፡
1.ካርሎስ ስሊም
የሃብት ግምት — 73 ቢሊዮን ዶላር
በሶስት ክለቦች የአክሲዮን ድርሻ አላቸው ሁለቱ ፓችዋ እና ሌዎን የተባሉ የሜክሲኮ ክለቦች ሲሆኑ አንደኛው ደግሞ የስፔኑ ክለብ ሪያል ኦቪዬዶ ነው፡፡
ሜክሲኳዊ የቴሎኮም ኢንቨስተር ካርሎስ ስሊም 74 ዓመታቸው ሲሆን ከ2010 እኤአ ጀምሮ የዓለም ሃብታሞችን ደረጃ በየዓመቱ በአንደኝነት እየመሩ ናቸው፡፡ ግሩፖ ካርሶ በተባለ ግዙፍ ኩባንያቸው በቴሌኮም፤ በሪል ስቴት፤ በአየር መንገድ፤ በሚድያ፤ ቤክኖሎጂ እና በፋይናንስ ኢንቨስትመንታቸው በበርካታ የሜክሲኮ ኩባንያዎች ከፍተኛ ድርሻ አላቸው፡፡ በተለይ በ49 ቢሊዮን ዶላር ካፒታል የሚንቀሳቀሰው አሜሪካ ሞቪል የላቲን አሜሪካ ግዙፉ የቴልኮም ኩባንያ ነው፡፡
2.አማንስዮ ኦርቴጋ
የሃብት ግምት 65.6 ቢሊዮን ዶላር
ክለብ ዲፖርቲቮ ላካሩኛ
ኢንድቴክስ ግሩፕ የተባለ ግዙፍ ዓለም አቀፍ ኩባንያን በፕሬዝዳንትነት የሚያስተዳድሩት የ78 ዓመቱ አማንስዮ ኦርቴጋ በስፔን እና በዓለም አቀፍ የፋሽን ኢንዱስትሪ ከፍተኛ ዝና ያላቸው በሃብታቸው ግምት በዓለም ሶስተኛ ዴጃ ላይ ይገኛሉ፡፡ አመንስዮ ኦርቴጋ በዲፖርቲቮ ላካሩኛ ክለብ ባለቤትነት ለየት የሚያደርጋቸው እያንዳንዱን የክለቡ ጨዋታ ከክለቡ ቀንደኛ ደጋፊዎች ጋር በመመልከት ዝነኛ መሆናቸው ነው፡፡
3. አሊሸር ኡስማኖቭ
የሃብት ግምት 18.6
ክለብ አርሰናል
ራሽያዊው  በማእድን ቁፈራ እና በብረታብረት ኢንዱስትሪ በሚንቀሳቀስ ኩባንያቸው የናጠጡ ሃብታም ለመሆን የበቁ ናቸው። አሊሸር ኡስማኖቭ በታዋቂው ሲልከን ቫሊ ከፍተኛ የአክሲዮን ድርሻ አላቸው፡፡ ኡስማኖቭ በ2007 እኤአ ላይ በሰሜን ለነድኑ ክለብ አርሰናል 17 በመቶ ድርሻ በመግዛት ክለቡን ሲደግፉት ቆይተዋል፡፡
4.ጆርጅ ሶሮስ
የሃብት ግምት 19.6 ቢሊዮን ዶላር
ክለብ ማንችስተር ዩናይትድ
አሜሪካዊ ነጋዴ ጆርጅ ሶሮስ በማንችስተር ዩናይትድ ክለብ 7.85 በመቶ ከፍተኛው የአክሲዮን ድርሻ አላቸው፡፡ በኦልድትራፎርዱ ክለብ ኢንቨስት ያደረጉት ሶሮስ ፈንድ ማኔጅመንት በተባለ ኩባንያቸው ነው፡፡
5. ፖል አለን
የሃብት ግምት 15 ቢሊዮን ዶላር
ክለብ ሲያትል ሳውንድረስ  
አሜሪካዊ ነጋዴ ፖል አለን ታላቁን የማይክሮሶፍት ኩባንያ ከመሰረቱ ባለሃብቶች ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ናቸው፡፡
ህንዳዊው ላክሺም ሚታል በ15 ቢሊዮን ዶላር በኪውንስ ፓርክ ሬንጀርስ፤ ሪህና አኬሜቶቭ በ15 ቢሊዮን ዶላር በዩክሬን ሊግ በሚወዳደረው ሻካታር ዶንቴስክ፤ ፈረንሳዊው ፍራንኮይስ ሄነሪ ፒናልት በ14 ቢሊዮን ዶላር በሊግ 1 በሚወዳደረው ስታድ ዲ ሬኔስ፣ ራሽያዊው ሮማን አብራሞቪች በ12 ቢሊዮን ዶላር በቼልሲ እንዲሁም ጆን ፍሬድክሰን በ12 ቢሊዮን ዶላር በኖርዌይ ሊግ በሚወዳደረው ቫሌሬንጋ  ክለብ እስከ 10 ያለውን ደረጃ ወስደዋል፡፡  እስከ 20ኛ ባለው ደረጃ የሞናኮ ክለብ ባለቤት ራሽያዊው ዲምትሪ ራይቦሎቬሌቭ በ10 ቢሊዮን ዶላር ፤ የኤሲሚላን  ክለብ ባለቤት ሲልቭዮ በርልስኮኒ በ7 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም የማንችስተር ሲቲው ሼክ መንሱር ቢንዘየድ በ7 ቢሊዮን ዶላር ከ12 እስከ 15ኛ ደረጃ ሲሰጣቸው፤ በአርሰናል ክለብ 38 በመቶ ድርሻ ያላቸው አሜሪካዊ ቢሊዬነር ስታን ክሮንኬ በ4 ቢሊዮን ዶላር 19ኛ ደረጃ አላቸው፡፡


በከፍተኛ ድብርትና በመንፈስ ጭንቀት ሲሰቃይ ነበር
ታዋቂው የሆሊውድ የፊልም ተዋናይና ኮሜዲያን አሜሪካዊው ሮቢን ዊሊያምስ በተወለደ በ63 አመቱ ባለፈው ሰኞ ከቀትር በኋላ ከሳን ፍራንሲስኮ በስተሰሜን ቲቡሮን አቅራቢያ በሚገኘው መኖሪያ ቤቱ መኝታ ቤት ውስጥ ራሱን በቀበቶ በማነቅ እንዳጠፋ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
‘ጉድሞርኒንግ ቬትናም’ና ‘ዴድ ፖየትስ ሶሳይቲ’ን በመሳሰሉ በርካታ ተወዳጅ ፊልሞቹ የሚታወቀውና የኦስካር ተሸላሚው ተዋናይ ሮቢን ዊሊያምስ፣ ለረጅም ጊዜያት በከፍተኛ ድብርትና በመንፈስ ጭንቀት ይሰቃይ እንደነበርና በቅርቡም ወደ አእምሮ ህክምና መስጫና ማገገሚያ ማዕከል አምርቶ ከዚህ ቀደም አቋርጦት የነበረውን ህክምና መከታተልና እንክብካቤ ማግኘት ጀምሮ እንደነበር ፖሊስን ጠቅሶ ዘገባው አስረድቷል፡፡
ተዋናዩ የአልኮል መጠጥ ሱስ ተጠቂ እንደነበር የጠቆመው ዘገባው፣ ከዚህ ሱስ ለመውጣት የሚያደርገውን ትግል በኮሜዲ ስራዎቹ ውስጥ በግልጽ ይናገር እንደነበር ገልጧል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ የተዋናዩን ሞት አስመልክተው ለቤተሰቦቹ በላኩት የሃዘን መግለጫ መልዕክት፣ “ሮቢን ዊሊያምስ ውስጣችንን ኮርኩሮ ሲያስቀን፣ ልባችንን ሰርስሮ ሲያስለቅሰን ኖሮ ያለፈ ልዩ ሰው ነው፡፡ እሱ በሰው አገር ከሚገኙ ወታደሮቻችን፣ በገዛ አገራችን ጎዳናዎች ላይ ተገልለው እስከሚገኙ ዜጎች በሁሉም ልብ ውስጥ አሻራውን ማስቀመጥ የቻለ ድንቅ ሰው ነው” ብለዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ1951 ኤሊኖይስ ውስጥ የተወለደው ሮቢን ዊሊያምስ በተለያዩ የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ላይ ለረጅም አመታት የስታንዳፕ ኮሜዲ ስራዎቹን ሲያቀርብ የቆየ ሲሆን፣ እ.ኤ.አ በ1998 በምርጥ ረዳት ተዋናይነት የኦስካር ተሸላሚ ያደረገውን ‘ጉድ ዊል ሃንቲንግ’ ጨምሮ በበርካታ ተወዳጅ ፊልሞች ላይ በመስራት የትወና ብቃቱን ያስመሰከረ ተዋናይ ነበር፡፡ በርካታ የሆሊውድ ተዋንያንና አለማቀፍ አርቲስቶች የሃዘን መግለጫቸውን እየሰጡለትና ድንቅ የትወና ችሎታውን በተለያዩ የዓለማችን ታዋቂ መገናኛ ብዙሃን እየመሰከሩ የሚገኙለት ሮቢን ዊሊያምስ፣ ከቀድሞ ትዳሩ ያፈራቸው የሶስት ልጆች አባት መሆኑን ዘገባው ገልጧል፡፡

ከ900 በላይ የሚሆኑ የዓለማችን ታዋቂ ደራሲያን ከመጽሃፍት ሽያጭ ጋር በተያያዘ በደል ፈጽመህብናል፤ አንተ በሚሊዮኖች ዶላር እያፈስክ እኛ ግን ማግኘት የሚገባንን ያህል ገንዘብ እያገኘን አይደለም፤  ህልውናችን አደጋ ላይ ወድቋል፤ የምትከተለውን የመጽሃፍት ሽያጭ አሰራር በአፋጣኝ አስተካክል ሲሉ አማዞን ለተሰኘው የድረገጽ ሽያጭ ኩባንያ ማመልከቻ ማስገባታቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ከአለማችን ታላላቅ አሳታሚ ኩባንያዎች አንዱ በሆነው ‘ሃቼቴ’ አማካይነት መጽሃፍቶቻቸውን እያሳተሙ ለንባብ ሲያበቁ የቆዩት እነዚህ ታዋቂ ደራሲያን፣ ከአሳታሚው መጽሃፍቱን እየተረከበ ለገበያ የሚያቀርበው አማዞን እየተከተለው የሚገኘው የሽያጭ ስርዓት ከመጽሃፍቶቻችን ሽያጭ ተገቢውን ገንዘብ እንዳናገኝ የሚያደርግ ነው በማለት ነው አቤቱታቸውን ያቀረቡት፡፡
ደራሲያኑ ለአማዞን በላኩትና በኒውዮርክ ታይምስ ጋዜጣ ላይ ታትሞ ለንባብ በበቃው በዚህ ማመልከቻ እንዳሉት፣ አማዞን መጽሃፍትን በወቅቱ ለደንበኞቹ አለማድረሱ፣ የቅድመ ክፍያ ትዕዛዞችን መቀበል ማቆሙና ጄኪ ሮውሊንግና ስቴፋኒ ሜየርን በመሳሰሉ አንዳንድ የኣለማችን ታዋቂ ደራሲያን መጽሃፍት ላይ የነበረውን ዋጋ ቅናሽ ማቆሙ የሚገባንን ጥቅም እንዳናገኝ አድርጎናል ብለዋል፡፡
አማዞን ከመጽሃፍት ባለፈ ማንኛውንም የሸቀጥ አይነት ለገበያ የሚያቀርብ ከአለማችን ታላላቅ ኩባንያዎች አንዱ የመሆን ህልሙን ለማሳካት በጀመረው ጉዞ ውስጥ የኛ ድርሻ ከፍተኛ ነው ያሉት ደራሲያኑ፣ ኩባንያው የደራሲያኑን ስራዎች ሲሸጥ በቆየባቸው አመታት በሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር ማፍራቱን አስታውሰዋል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን አማዞን ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ የጀመረው አዲስ የሽያጭ አሰራር፣ ብዙ ሃብት ያካበተባቸውን ደራሲያን የሚጎዳና ህልውናቸውን አደጋ ላይ የሚጥል በመሆኑ አሰራሩን በአፋጣኝ እንዲያስተካክል ለመጠየቅ መገደዳቸውን በጋራ ባስገቡት ማመልከቻ እንደገለጹ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሃቼቴ በተባለው አሳታሚ ኩባንያ አማካይነት ስራቸውን ለአንባቢ ከሚያደርሱትና ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከታቸው ማልኮም ግላድዌል፣ ጄምስ ፓተርሰንና ዶና ታርትን የመሳሰሉ ደራሲያን በተጨማሪም፣ በሌሎች አሳታሚዎች የሚያሳትሙ ጆን ግሪሻምና ሴተፈን ኪንግን የመሳሰሉ ሌሎች የአለማችን ዝነኛ ደራሲያንም የአማዞንን ድርጊት በመቃወም በማመልከቻው ላይ ፊርማቸውን አስቀምጠዋል፡፡  አማዞን ከአሳታሚው ኩባንያ ጋር ባደረገው ስምምነት የደራሲያኑን መጽሃፍት በድረገጽ አማካይነት ሲሸጥ ቢቆይም፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በሽያጩ ላይ ያልተገባ ድርጊት ይፈጸማል በሚል በመካከላቸው አለመስማማት ተፈጥሯል፡፡
አማዞን በቅርቡ ባወጣው መግለጫ በድረገጽ አማካይነት ለሽያጭ የሚበቁ ኤሌክትሮኒክ መጽሃፍት አብዛኞቹ በ9.99 ዶላር መሸጥ ሲገባቸው በ14.99 ዶላር እየተሸጡ እንደሚገኙና ዋጋቸው ያለአግባብ ውድ መሆኑን በመጥቀስ የዋጋ ቅናሽ ማድረግ እንደሚገባ ተናግሮ ነበር፡፡
ዋጋን በመቀነስ ብዙ መጽሃፍትን መሸጥና ከብዛት ትርፍን ማሳደግና ከሚገኘው ትርፍም ለአሳታሚው ኩባንያም ሆነ ለደራሲያኑም የተወሰነ ገንዘብ መስጠት እንደሚቻል በገለጸበት ወቅት፣ ከ 7 ሺህ በላይ ደራሲያን ጉዳዩን በመደገፍ ከአማዞን ጋር ለመስራት መፈራረማቸውንም ዘገባው አስታውሷል።

  • የአገሬ ሴቶች ሆይ!... እስከቻላችሁት ድምጻችሁን ከፍ አድርጋችሁ ሳቁ!”
  • የቱርክ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዕጩ ተወዳዳሪ

    የቱርኩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ቡለንት አሪንክ ባለፈው ሳምንት ሴቶች በአደባባይ ድምጻቸውን ጎላ አድርገው መሳቅ የለባቸውም ብለው መናገራቸውን ተከትሎ፣ በአገሪቱ የሴቶች መብት ተሟጋቾች ክስ እንደተመሰረተባቸውና በተለያዩ መገናኛ ብዙሃንና በማህበራዊ ድረገጾች የሚሰነዘርባቸው ነቀፌታና ትችት እየተበራከተ መምጣቱን ሲ ኤን ኤን ዘገበ፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባሳለፍነው ሳምንት፣ “ሴቶች ሰው በተሰበሰበበት ጎላ አድርገው መሳቅ የለባቸውም፣ ነውር የሆነን ነገር ለይተው ሊያውቁና ‘አንገት ደፊ’ ሆነው ሊኖሩ ይገባል፣ ወንዶችም ‘ሴት አውል’ መሆን የለባቸውም!” በማለት ከሳምንት በፊት የተናገሩ ሲሆን፣ የጾታዊ መብቶች ተሟጋቾች የሴቶችን መብቶች ህጎች የሚጥስና የጥቃት ሰለባ እንዲሆኑ የሚዳርግ ህገወጥ ተግባር ፈጽመዋል በሚል በምክትል ጠ/ሚኒስትሩ ላይ ክስ መስርተዋል፡፡ በምክትል ጠ/ሚኒስትሩ ንግግር የተበሳጩ በመቶዎች የሚቆጠሩ የአገሪቱ ሴቶች በአደባባይ ሲስቁ የተነሷቸውን ፎቶግራፎችና ተቃውሟቸውን የሚገልጹ መልዕክቶቻቸውን በድረገጾች ላይ በስፋት ማሰራጨታቸውን እንደተያያዙትም ሲ ኤን ኤን በዘገባው ገልጧል።
በትዊተር ገጽ ላይ ጉዳዩን በተመለከተ ከ 160 ሺህ በላይ ምልልሶች መደረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ አብዛኞቹ አስተያየቶች የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግር የሚተቹ እንደሆኑና ዜጎችም በባለስልጣኑ አባባል የተበሳጩ መሆናቸውን ገልጧል፡፡ በቱርክ ሴቶች ላይ የሚደረገው ጭቆና በአደባባይ አትሳቁ ከሚለው የባለስልጣኑ ንግግር የዘለለና እጅግ ስር የሰደደ ነው ያለው ሲ ኤን ኤን፣ 40 በመቶ የሚሆኑት የአገሪቱ ሴቶች የአስከፊ የቤት ውስጥ ጥቃት ሰለባ ሆነው ኑሯቸውን እንደሚገፉ ገልጧል፡፡ በዚህ ሳምንት በሚካሄደው የቱርክ የመጀመሪያ ዙር ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ላይ የአሁኑ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዋነኛ ተፎካካሪ እንደሆኑ የሚነገርላቸው አንድ ተወዳዳሪ ሴቶች አትሳቁ የሚለውን የሰሞኑን የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር በተመለከተ በትዊተር ገጻቸው ላይ ለአገራቸው ሴቶች ባስተላላፉት መልዕክት፣ “የአገሬ ሴቶች ሆይ!... እስከምትችሉት ድረስ ድምጻችሁን ከፍ አድርጋችሁ ሳቁ!” ብለዋል፡፡

በአገራችን የሚከበሩ መንፈሳዊና ብሄራዊ ፌስቲቪሎችን የሚያስቃኝ “የኢትዮጵያ ፌስቲቫል ማውጫ” የተሰኘ መፅሀፍ ሰሞኑን ታትሞ የወጣ ሲሆን በነፃ እንደሚሰራጭ ታውቋል፡፡ መፅሀፉ ከ15 በላይ የመስቀል በዓል አከባበሮች፣ በተለያዩ አምስት አካባቢዎች የሚካሄዱ የጥምቀት በዓላት፣ የገና፣ የመውሊድ እና የአረፋ እንዲሁም የአሸንዳ፣ የእሬቻና ፍቼ በዓላትን ጨምሮ በርካታ ፌስቲቫሎችን ያካተተ ሲሆን፤ በዓላቱ መቼና እንዴት እንዲሁም ለምን እንደሚከበሩ መረጃ ይሰጣል፡፡ ማውጫው ለሀገር ውስጥ ጎብኚዎች፣ ተመራማሪዎች፣ ለመገናኛ ብዙሃንና ለአስጎብኚዎች በነፃ ይሰራጫል ተብሏል፡፡

በአቶ ተክሉ አብርሃ በእንግሊዝኛ ተፅፎ፣ በመምህርና ጋዜጠኛ ግርማይ ገ/ፃዲቅ ወደ አማርኛ የተመለሰው “የሰቆቃው ዘመን በታጋይ ህይወት ውስጥ” የተሰኘው በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተ መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡
መፅሀፉ የደርግን ዘመን አስከፊነት፣ በፊውዳሉ ስርዓት ኢትዮጵያ ምን ያህል ኋላቀርነት ጠናውቷት እንደነበር፣ ስለ ኢህአፓና ሌሎች የወቅቱ ሁነቶች ላይ ትኩረት አድርጓል፡፡ በ23 ምዕራፎች ተከፋፍሎ በ376 ገፆች የቀረበው መፅሀፉ፤ ለአገር ውስጥ በ100 ብር፣ ለውጭ አገር በ20 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡
በሌላ በኩል፣ “መስፍን ኃብተማሪያም፣ ህይወቱና ስራዎቹ” በሚል ርዕስ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ በነገው እለት ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በብሄራዊ ቤተመፃህፍትና ቤተመዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ውይይት እንደሚያካሂድ አስታወቀ፡፡
በዕለቱ የደራሲው ስራዎች የሚዳሰሱ ሲሆን የውይይት መነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት ደራሲና ሃያሲ አቶ አለማየሁ ገላጋይ እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በተለያዩ የዓለም አገራት ከፍተኛ ነውጥ በፈጠሩ ሰላዮች ላይ ያተኮረው የፈቃዱ ሺፈታ “አገራትን ያናወጡ ሰላዮች” የተሰኘ መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ 135 ገፆች ያሉት መፅሀፉ፤ በ40 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡
በየዓመቱ የአለም ድንቃድንቅ ታሪኮችን ከሚያወጣው “ጊነስ ቡክ ኦፍ ሪከርድስ” ተመርጠው ወደ አማርኛ የተተረጎሙ አስደናቂ ታሪኮችን የያዘ “ጊነስ የዓለም ድንቃድንቅ ታሪኮች” መፅሀፍ ለአንባቢያን ደረሰ፡፡ በ126 ገፆች የተሰናዳውን መፅሃፍ ተርጎሞ ያቀረበው እስክንድር ስዩም ሲሆን መፅሀፉ በ37 ብር ከ45 ሳንቲም እየተሸጠ ነው፡፡

በእንግሊዝ የአልኮል መጠጦች በተጠቃሚዎች ላይ የሚያደርሷቸውን ዘርፈ ብዙ የጤና ችግሮች ለመቅረፍ አምራቾች በመጠጦቹ ላይ የማስጠንቀቂያ መልዕክት ጽፈው ለገበያ እንዲያቀርቡ የሚያስገድድ ህግ እንዲወጣ በፓርላማ አባላት ቡድን ለእንግሊዝ መንግስት ጥያቄ መቅረቡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የአልኮል መጠጦች የሚያደርሱትን ችግር በተመለከተ ትኩረት ሰጥቶ የሚሰራውና ሁሉንም የአገሪቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአባልነት ያቀፈው የፓርላማ ቡድን ለመንግስት ያቀረበው የመፍትሄ ሃሳብ እንደሚለው፣ አምራቾች የአልኮል መጠጦችን ጎጂነት የሚገልጹ ጽሁፎችን በምርቶቻቸው ላይ እንዲለጥፉ መገደድ ይኖርባቸዋል፡፡
በእንግሊዝ ከአልኮል መጠጦች ተጠቃሚነት ጋር በተያያዙ የሚከሰቱ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን ለማቃለል ያግዛሉ ተብለው በቡድኑ የቀረቡት የመፍትሄ ሃሳቦች 10 ሲሆኑ፣ ቡድኑ ለሃሳቦቹ ተቀባይነትና ተፈጻሚነት የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡ ለሁሉም የአገሪቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
ቡድኑ ለመንግስት ባቀረበው የመፍትሄ ሃሳቦች ሰነድ፤ የጤና ማስጠንቀቂያዎች በሲጋራ ምርቶች ላይ መለጠፍ የተለመደ መሆኑን ጠቅሶ፣ በአልኮል መጠጦች ላይ ግን የመጠጡን ይዘትና በውስጡ የሚገኙትን ንጥረነገሮች ከመግለጽ ያለፉ ጽሁፎች እንደማይወጡ ገልጧል፡፡
በመሆኑም የአልኮል መጠጦች የሚያደርሷቸውን የጤና ችግሮች፣ ውስጣዊ ቅንብራቸውንና የንጥረ ነገር ይዞታቸውን ወዘተ ለተጠቃሚዎች የሚገልጹ የማስጠንቀቂያ መልዕክት ይዘው ገበያ ላይ እንዲውሉ የሚያስገድድ ህግ ሊወጣ ይገባል ብሏል፤ ቡድኑ ለመንግስት ባቀረበው የመፍትሄ ሃሳቦች ሰነድ ውስጥ ከተካተቱት ጉዳዮች መካከል፣ ጠጥቶ የማሽከርከር ገደብ እንዲሻሻል፣ በአልኮል ገበያ ላይ ጠበቅ ያለ የህግ እርምጃ እንዲወሰድ፣ አስገዳጅ የዋጋ ተመን እንዲወጣ የሚጠይቁ ይገኙባቸዋል፡፡
ከአልኮል ጋር ተያያዥ በሆኑ ጉዳዮች ለህብረተሰቡ ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ብሄራዊ ዘመቻ እንዲጀመር፣ ለማህበራዊ ሰራተኞች ሆነ ለጤና ባለሙያዎች ስልጠና የሚሰጥበት መንገድ እንዲፈጠር፣ ከአልኮል ሱሰኝነት ለመውጣት የሚያስችለውን ህክምና ሽፋን አሁን ካለበት 6 በመቶ ወደ 15 በመቶ ከፍ ለማድረግ የሚያስችሉ ስራዎች እንዲሰሩም ቡድኑ ጠይቋል፡፡
የእንግሊዝ መንግስት ቃል አቀባይ በበኩላቸው፣ የአገሪቱ መንግስት ከመጠን በላይ የሆነ የአልኮል ተጠቃሚነትን ለመቀነስና ህብረተሰቡ የአልኮልን ጎጂነት በተመለከተ ግንዛቤ እንዲጨብጥ የሚያስችሉ ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን ጠቁመው፣ ርካሽና አደገኛ የሆኑ የአልኮል መጠጥ አይነቶች ለገበያ እንዳይቀርቡ በህግ መከልከሉንም አስታውሰዋል፡፡ የወግ አጥባቂ ፓርቲ አባልና የቡድኑ ሊቀመንበር የሆኑት ትሬሲ ክሮች እንዳሉት፣ በእንግሊዝ በየአመቱ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሰዎች ከአልኮል ጋር ተያያዥነት ባላቸው በሽታዎች ተጠቅተው በህክምና ተቋማት ይረዳሉ፡፡ በጉበት በሽታ የሚጠቁ እድሜያቸው ከ30 አመት በታች የሆኑ ዜጎች ቁጥርም ባለፉት 20 አመታት ከእጥፍ ላይ ጨምሯል፡፡
አልኮል በአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ የሚያደርሰው ኪሳራ 21 ሚሊዮን ፓውንድ ደርሷል ያሉት ክሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ቡድኑ ላቀረባቸው የመፍትሄ ሃሳቦች ተፈጻሚነት ትኩረት ሰጥተው መስራታቸው፣ የአልኮል መጠጦች በአገሪቱ ትልቅ የጤና ችግር መንስኤዎች ሆነው እንዳይቀጥሉ የሚያስችል በጎ ጅምር ይሆናል ሲሉም አክለዋል።
አልኮል ኮንሰርን የተባለው የአገሪቱ ተቋም ዋና ስራ አስፈጻሚ ጃኪ ባላርድ በበኩላቸው፣ የአልኮል መጠጦችን በተመለከተ አስቸኳይ እርምጃ መወሰድ እንደሚኖርበት ገልጸው፣ የአልኮል መጠጦች 60 ያህል ከሚደርሱ የጤና ጉዳዮች ጋር ተያያዥነት እንዳላቸው ጨምረው አስረድተዋል፡፡