Administrator

Administrator

(ዘር ያጣን ሸረት፣ አናነ ያጣን ጉርበት፣ አባመታ ይኸን)- የጉራጊኛ ተረት

አንድ የአፍሪካ ተረት እንዲህ ይላል :-
ከዕለታት አንድ ቀን ባልና ሚስት ከፍተኛ የመኩራራት ደረጃ ላይ ይደርሳሉ፡፡
ሚስት - “በሩን ዝጋና ተኛ” ትለዋለች ባሏን፡፡
ባል - “አንቺ ምን ሥራ ይዘሽ ነው እኔ በር የምዘጋው!” ይላታል፡፡
የፉክክር በር ሳይዘጋ ያድራል ወደሚለው ተረት የሚያመራ ይሆናል፡፡
ባል በመጨረሻ አንድ ዘዴ አመጣ - ውርርድ!
“ኧረ ካሁኗ ደቂቃ ጀምሮ ቃል የተነፈሰ፤ በሩን ይዝጋ” አለ፡፡
ሚስትም ተስማማች፡፡
ዝም ዝም ሆነ ነገሩ፡፡
በመካከል አንድ ለማኝ መጣና፤
“ስለማሪያም ተዘከሩኝ” አለ፡፡ መልስ የለም፡፡
“በአምላክ እህል አቅምሱኝ” አለ፡፡
የሚሰማው የለም፡፡
ገባ ወደቤት፡፡ ከዚያ ከብረት ድስቱ ውስጥ ምን የመሰለ አጥንት አግኝቶ መጋጥ ጀመረ፡፡ ባልም እያየ ዝም፡፡ ሚስትም እያየች ዝም፡፡ አንተንፍስ ብለዋላ! በማህል ለማኝ ሃይ የሚለው ስላጣ መጋጡን ቀጠለ፡፡ ለማኙ አጥንቱን ግጦ ሲጨርስ በገመድ አስሮ ሚስቲቱ አንገት ላይ አንጠለጠለው፡፡ እሷ አሁንም ዝም አለች፡፡
ቀጥሎ አንድ ውሻ መጣ፡፡ እሚስት አንገት ላይ የተንጠለጠለውን አጥንት መላስ ጀመረ። ይሄኔ ሚስቲቱ ትዕግሥቷ አለቀና፤
“ሂድ ከዚህ!” ብላ አባረረችው፡፡
ባል - “በቃ ውርርዱን ተሸንፈሻል!” አላት፡፡
ሚስት በመሸነፏ ተናዳ ኩርፊያዋን ቀጠለች፡፡ ራት ሳይበሉ ተኙ፡፡ ባዶ ሆዳቸውን አደሩ።
ጠዋት -
ባል “አየሽ ውድ ባለቤቴ፤ ከሚበልጥሽ ሰው አትወራረጂ፡፡
ትርፉ ጦም ማደር ነው!” አላት ይባላል፡፡
                                                   *    *    *
የፉክክር ቤት ሳይዘጋ ያድራል ማለት ይሄው ነው፡፡
“እኔን አይመለከትም፤ ሌላ ሰው ጠይቅ፤ እኔ አልታገልም፤ አንተው እንዳመጣብህ ታገል…እኔ በልቻለሁ፤ ያልበላው መከራውን ይይ…” ዛሬ የሀገራችን ፈሊጥ መሆኑ ብዙ አያጠያይቅም! እንዲህ ከሆነ ደግሞ ሀገር ማደጓ ዘበት ነው፡፡ ከጠዋት እስካሁን የምናየው የሀገራችን ሁኔታ ሌላው ሞቶ፣ ሌላው ተሰውቶ፣ የሚፈራውን ፍሬ እኔ ልብላ…ሌላው በቆሰለ በታሰረበት እኔ ስሜ ይጠራ፣ እኔ ዝና ላፍራበት ማለት ባህላችን እየሆነ መምጣቱ ነው፡፡
በመሠረቱ “ሁሉ ኮርቻ ላይ ከወጣ አለንጋ ማን ሊይዝ ነው?” እንደተባለው፤ ፈረሱን የሚነዳ፣ የሚለጉምና የሚያራግፍ እንዳይጠፋ ያሰጋል፡፡ ሁሉ ፖለቲከኛ፣ ሁሉ ተናጋሪ፣ ሁሉ እኔ ነኝ የሀገር ጉዳይ የሚያገባኝ ካለ፤ ፖለቲካል ሳይንስ የተማረ ሁሉ መቅለጡ ነው በአንፃሩ “እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው” ለማለት የሚቸኩል ፖለቲከኛ የበዛበትም አገር ከፍሬው ገለባው ይበዛል፡፡
ፀጋዬ ገ/መድህን በምኒልክ አንደበት እንዲህ ይለናል፡-
“…አየህ እያሱ…ያገርህን ያበሻን ቤት አሰራር ተጨባጭ አገነባብ ባጭር ምሳሌ ላስተምርህ። ያበሻ ቤቱ፣ ያበሻ ጣራው ምሰሶ ጉልላቱ፣ ያበሻ ማዕዱ፣ ምድጃና መሶቡ፣ ያበሻ አውድማው አዳራሹና አደባባዩ እንደፀሐይ ክብ ብርሃን ጮራ እንደቀለበት የሕብር ዙሪያ እንደ ክበብ ነው…ባህልህን አስጠንቅረህ ካላወቅህ አገርህም አያውቅህ! ሕዝብህንም አታውቀው! ሕዝብህን ማወቅ ማለት የህዝብህን የባህል ብልት ጠንቅቀህ መገንዘብ ነው፡፡ ህዝብህን ማወቅ ደግሞ አገርህን ማወቅ ነው፡፡ ማንነቱን ያላጤንክለትን ሕዝብ ነገ ማስተዳደሩ ያቅትሃል እያሱ፡፡”
የሕዝብ ባህሉ እስትንፋሱ ነው፡፡ መናገሩ ነው፡፡ እንደልቡ መሆኑ ነው፡፡ ተናገር ብለህ “ቀስቅሰክ” ብለህ አትከሰውም፡፡ አለበለዚያ አገር የለውም፡፡ የህዝብ መብት ማንም እንዳሻው የሚቀለብሰው፣ እንዳሻው ዳር ድንበሩን የሚወስነው አሊያም “የአተረጓጐም ጉዳይ ነው” እያለ እንዳመቸው የሚያጣምመው አይደለም፡፡
አብዛኛው ነገረ - ሥራችን “ሲያቃጥል በማንኪያ ሲበርድ በእጅ” ዓይነት የሆነው በዚሁ ምክንያት ነው፡፡ “ከባዕድ ወስደህ ወደዘመድህ ዞረህ ጉረስ”ም ሌላው ፈሊጣችን ነው፡፡
ከጥቂት ጊዜ በፊት ሁነኛ ተቃዋሚ አጣን ይሉ የነበሩ፤ ተቃዋሚ ሲመጣ የአገር እንቅፋትና አሽክላ እንደፈጠሩ አይተናል፡፡ ተቃዋሚ ሲጠፋ በራሳቸው ማህል የተቃውሞ አውሎ - ንፋስ አስነስተው ተከፋፍለው፤ ተሰነጣጥቀው፤ እርስ በርስ ጐራ ለይተው ግራና ቀኝ ተባብለው እንደተጠፋፉም ታዝበናል፡፡ በራሳቸው ዕብጠት ወደ መፈንዳት የሄዱም እንደነበሩ ምስክር ሆነናል፡፡ ግራና ቀኝ መንገደና ተባበለው መፈረጃቸውንም ሰምተናል፣ አይተናል፡፡ ሁሉንም ጉልበተኛ እስኪውጣቸው “ዲሞክራሲ የእኛ ብቻ ናት”፤ “እንደኛ ፕሮግራም የሚጥም የትም አይገኝም!”፤ ‹እንደኛ ምርጫ “Fair” and “Free” የትም የለም› ይላሉ፡፡
ታሪክ ግን ታሪክ ሆነው እንደሚቀሩ ይዘግባል፡፡ ንድፈ - ሀሳብ ቀማሪዎቻቸውም ሆኑ አፈ - ጉባኤዎቻቸው፤ ወሬ አንጓቾቻቸውም ሆኑ ወናፎቻቸው ወይም መለከተ - ጥሩምባዎቻቸው ደሞ ለሌላ መንግሥት ማንባረቃቸውን፣ ማናፈታቸውን መቀጠላቸውንም ልብ እንላለን፡፡ ይሄ ሁሉ ሆኖ ግን ህዝቡ፣ ባለ ይዞታው፣ ባለ አገሩ፤ “ክረምት የሚያወጣውን ምግብ፣ ዳገት የሚያወጣውን ጉልበት፤ ባለቤቱ ያቀዋል” የሚለው የጉራጌ ተረት ደርዙ ይሄ መሆኑን ያቃል!!

በ11 የአፍሪካ አገራት ተሰራጭቷል

          ባለፈው ማክሰኞ ማለዳ… ሲኤን ኤን ከወደ ሴራሊዮን አንዳች አሳዛኝ ነገር ስለመከሰቱ ዘገበ፡፡ በምዕራብ አፍሪካዊቷ ሃገር በሴራሊዮን የተከሰተውን አሰቃቂ የኢቦላ ቫይረስ ወረርሽኝ ለመግታት ሌት ተቀን ደፋ ቀና ሲሉ ከነበሩት ታዋቂ ሃኪሞች አንዱ ሴራሊዮናዊ ዶ/ር ሼክ ሁማር ካሃን ሞቱ፡፡ የአገሪቱ መንግስት በህክምናው መስክ ከሚኮራባቸው ዜጎቹ የመጀመሪያው እንደሆኑ በይፋ የሚናገርላቸውና “ብሄራዊ ጀግናዬ” ብሎ የሰየማቸው ታላቅ ሰው፤ ኢቦላን በመሳሰሉ በቫይረስ የሚከሰቱ በሽታዎች ህክምና ዘርፍ በአለማችን ስማቸው ጎልቶ ከሚጠቀስ ቀዳሚ የህክምና ሊቃውንትና ባለሙያዎች አንዱ የነበሩት ሃኪም አረፉ፡፡ ከአገሪቷ መዲና ፍሪታውን 185 ማይሎች ርቃ በምትገኘው ኬኔማ የተባለች ከተማ ሆስፒታል ውስጥ የኢቦላ ህክምና የሚሰጠውን ቡድን በመምራት ከፍተኛ ስራ ተጠምደው የሰነበቱት፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ የኢቦላ ተጠቂዎችን ከሞት ለማዳን አልህ አስጨራሽ ትግል ሲያደርጉ የነበሩት ዶ/ር ካሃን፣ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ ላይ ነበር፣ ህመም ቢጤ ተሰምቷቸው እንደምንም ስራቸውን ገታ አድርገው ለማረፍ ወደ አልጋ ያመሩት፡፡

ህመሙ ግን እንዳሰቡት ቀላልና ቶሎ የሚድን አልነበረም፡፡ እያደር ባሰባቸው፡፡ ካሊሁን በምትባል ከተማ ውስጥ በሚገኝ ሆስፒታል ተኝተው፣ በድንበር የለሽ የሃኪሞች ቡድን ህክምና ሲደረግላቸው ቢቆዩም አልዳኑም፡፡ ታዋቂው ሴራሊዮናዊ የኢቦላ ሃኪም በ39 ዓመታቸው ሞቱ፤ የሞታቸው ሰበብ ደግሞ ኢቦላ መሆኑ ታወቀ - ሲታገሉት የሰነበቱት ቀሳፊ በሽታ፡፡ ይህ ድንገተኛ መርዶ፣ በኢቦላ ወረርሽኝ የተመቱ የምዕራብ አፍሪካ አገራትን ብቻም አይደለም ያስደነገጠው፡፡ ከአራት ወራት በፊት በጊኒ አሃዱ ብሎ ጀምሮ ወደ ላይቤሪያ የዘለቀው፣ ፍጥነቱን ጨምሮ ወደ ሴራሊዮን የተሻገረው ይህ ክፉኛ አሰቃይቶ ገዳይ ቫይረስ፣ ድንበር ሳያግደው መሰራጨቱን ቀጥሏልና፣ የዶ/ሩ ሞት በሌሎች አገራት ብሎም አህጉራት ለሚኖሩ ዜጎች የችግሩን መባባስ የሚመሰክር መርዶ ነበር የሆነው፡፡ አዎ!... አሁን በታሪክ እጅግ አደገኛው የተባለለት የኢቦላ ወረርሽኝ አለማችንን ጭንቀት ውስጥ ከቷታል፡፡ የዓለም የጤና ድርጅት ከአስር ቀናት በፊት ነበር፣ በምዕራብ አፍሪካ በሚገኙ አገራት ከ800 በላይ ሰዎች በኢቦላ በሽታ ተይዘው በመሰቃየት ላይ እንደሚገኙ በይፋ ያስታወቀው፡፡

ድርጅቱ በወቅቱ ይህን ይበል እንጂ፣ ሲኤንኤን ግን የታማሚዎች ቁጥር ከ 1 ሺህ 200 በላይ እንደሚሆንና ቫይረሱም ከአገራቱ አልፎ በስፋት በመሰራጨት የአህጉሪቷ ብሎም የዓለም ስጋት ሊሆን እንደሚችል ባለሙያዎች የሰጡትን አስተያየት በመጥቀስ አበክሮ ተናግሮ ነበር፡፡ እንደተባለውም ኢቦላ የዓለም ስጋት ለመሆን የፈጀበት የቀናት ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ በምዕራብ አፍሪካ የተቀሰቀሰውና እስካለፈው ሳምንት ድረስ በአካባቢው 672 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት የዳረገው የኢቦላ ወረርሽኝ፣ አሁን የመላ አለም ሰሞንኛ የጭንቀት ምንጭ ሆኗል፡፡ ዛሬ ኢቦላ የአንዲት አህጉር ሶስት አገራት ራስ ምታት ብቻም አይደለም፡፡ የቶጎው አየር መንገድ ኤስካይ፣ ቫይረሱን እንዳያሰራጭ በመስጋት ወደ ሴራሊዮንና ወደ ላይቤሪያ የሚያደርጋቸውን በረራዎች ሙሉ ለሙሉ አቋርጧል፡፡ በናይጀሪያዋ ሌጎስ የኢቦላ ሟቾች ቁጥር እያሻቀበ መምጣቱን ተከትሎ፣ በመላ አገሪቱ የወረርሽኝ ስጋት አንዣቧል፡፡ ታላቁ የአገሪቱ አየር መንገድ አሪክ ኤርም፣ ቫይረሱን ፍራቻ ወደ ላይቤሪያ ድርሽ ላለማለት ምሏል፡፡ ቫይረሱ እንደተፈራው በየአቅጣጫው በመሰራጨት የአገራትን ድንበር ተሻግሮ እየገባ እንደሆነ በርካታ የዓለማችን መገናኛ ብዙሃን እየዘገቡ ነው፡፡ ዩኤስ ቱዴይ ከትናንት በስቲያ ባሰራጨው ዘገባ እንዳለው፣ የእንግሊዝና የሆንግ ኮንግ መንግስታት ከሰሞኑ የበሽታው ምልክቶች የታዩባቸውን የአውሮፕላን መንገደኞች በፍጥነት በመያዝ በተከለለ ቦታ ውስጥ እንዲቀመጡና ቫይረሱ ወደሌሎች እንዳይዛመት ለማድረግ አፋጣኝ እርምጃ ወስደዋል፡፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በበኩሉ፣ ከትናንት በስቲያ በሰጠው መግለጫ፣ የጥንቃቄ እርምጃ መውሰድ እንደሚጀምር አስታውቋል፡፡ አየር መንገዱ ከምዕራብ አፍሪካ በሚመጡ መንገደኞች ላይ ጠበቅ ያለ የጥንቃቄ የማጣራት ስራ እንደሚጀምርና ለበረራ ሰራተኞቹ ስለ በሽታው ግንዛቤ እንዲኖራቸውና ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ የሚያስችላቸው ስልጠና መስጠቱን ገልጧል፡፡ የእንግሊዝ የጤና ሚኒስቴር ባለፈው ረቡዕ ከናይጀሪያ በመነሳት በፓሪስ አድርጎ ወደ በርሚንግሃም የገባ አንድ ግለሰብ የበሽታው ምልክቶች ታይተውበት በሃኪሞች እንዲያዝ ቢደረግም፣ ኢቦላ እንደሌለበት ተረጋግጧል፤ እስካሁንም በአገሪቱ የኢቦላ ታማሚ አልተገኘም ቢልም፣ ብዙዎች ግን መስጋታቸውን አላቋረጡም። የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ጸሃፊ ፍሊፕ ሃሞንድ፣ በዚያው ዕለት ጉዳዩ የሚመለከታቸውን ከፍተኛ ባለስልጣናትና ባለሙያዎች ያሳተፈና ኢቦላን ወደ አገሪቱ እንዳይገባ ማድረግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ የመከረ አስቸኳይ ስብሰባ ያደረጉትም ጉዳዩ ስላሰጋቸው ነው፡፡ በሩቅ ያለችው አሜሪካም ብትሆን፣ ከወደ አፍሪካ የተነሳው መቅሰፍት ዜጎቿን እንዳያገኝባት ሰግታለች፡፡ ከላይቤሪያ በመነሳት ሚኒሶታ ውስጥ በተደገሰው የልጁ ልደት ላይ ለመገኘት ጓጉቶ ወደ ሚኒሶታ ሊጓዝ የተሰናዳው ዜጋዋ ፓትሪክ ሳውየር፣ ሌጎስ ውስጥ አውሮፕላን ውስጥ እያለ በኢቦላ ለሞት መዳረጉን ስትሰማ ደግሞ ስጋቱ ጨምሮባታል፡፡ በዚህም አላበቃም፡፡ በላይቤሪያ መዲና ሞንሮቪያ የህክምና እርዳታ በማድረግ ላይ የነበሩ ሌሎች ሁለት ዜጎቿ በኢቦላ ተይዘው እንደሚሰቃዩ ተረጋገጠ፡፡

እንዲህ ያለው መጥፎ ወሬ ያስደነገጣት አሜሪካ፣ በሰው አገር ያሉ ዜጎቿ ጉዳይ ቢያሳዝናትም፣ አገር ቤት ያሉት ግን እንዳይሰጉ እየመከረች ነው፡፡ ሲዲሲ የተባለው የአሜሪካ የጤና ተቋም ባለፈው ሰኞ በሰጠው መግለጫ፣ በአገሪቱ ይህ ነው የሚባል የኢቦላ ወረርሽኝ ስጋት እንደሌለ አረጋግጧል፡፡ ይህም ሆኖ ግን በሽታው አደገኛ በመሆኑ መጠንቀቅ ይበጃል ብሏል ተቋሙ፡፡ በሽታው ከተከሰተባቸው የአፍሪካ አገራት የሚመጡ መንገደኞችን ወደ አሜሪካ አለማስገባት ሁነኛ መከላከያ መላ ነው ይላሉ- የሲዲሲ ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት ዶ/ር ማርቲ ሴትሮን፡፡ በቅርቡ ከእነዚያ አገራት የመጡና የኢቦላ ምልክቶች የተሰሟቸው ሰዎችም፣ ዛሬ ነገ ሳይሉ በአፋጣኝ ወደ ህክምና መሄድ እንደሚኖርባቸው ዶክተሩ መክረዋል፡፡ በአገራቱ የሚኖሩ ዜጎችም፣ የበሽታውን መተላለፊያ መንገዶች ጠንቅቀው በመረዳት ራሳቸውን እንዲጠብቁ ተናግረዋል፡፡ የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ጸሃፊ ፍሊፕ ሃሞንድን ጠቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ሰሞኑን እንደዘገበውም፣ በመስፋፋት ላይ የሚገኘው የኢቦላ ወረርሽኝ ለእንግሊዝም ሆነ ለሌሎች የአውሮፓ አገራት ከፍተኛ ስጋት ነው፡፡

በሬዲንግ ዩኒቨርሲቲ ታዋቂ የህክምና ባለሞያ የሆኑት ዶ/ር ቤን ኒውማን በበኩላቸው፣ ኢቦላ በአገረ እንግሊዝ የመከሰት እድሉ ከፍተኛ በመሆኑ ተገቢው ጥንቃቄ እንዲደረግ ማስጠንቀቃቸውንም አስታውሷል፡፡ ጉዳዩ ያሰጋው የአውሮፓ ህብረትም፣ ወረርሽኙ ውቅያኖስ ተሻግሮ አሰቃቂ ጥፋት ሊያደርስ የማይችልበት ዕድል የለም ብሏል፡፡ የህብረቱን ከፍተኛ ባለስልጣን ሰቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ እንዳለው፣ ከሰሞኑ ስፔን ውስጥ አንድ ዜጋ በኢቦላ ተጠርጥሮ አፋጣኝ የህክምና ክትትል ተደርጎለታል፡፡ ግለሰቡ እንደተፈራው ከቫይረሱ ነጻ መሆኑ ቢረጋገጥም፣ በሌሎች የአውሮፓ አገራት የበሽታው ምልክት የሚታዩባቸው ሰዎች ቁጥር እያደገ መምጣቱንና አገራቱ ለጉዳዩ ከፍተኛ ትኩረት መስጠት እንዳለባቸው ህብረቱ መምከሩንም ዘገባው ያሳያል፡፡ ህብረቱ አባል አገራቱን ከወረርሽኙ እንዲጠነቀቁ ከማሳሰብ አልፎ፣ ወረርሽኙን ባለበት ለመግታት ችግሩ ወደ ተከሰተባቸው የአፍሪካ አገራት ከላከው 1 ነጥብ 9 ሚሊዮን ዩሮ በተጨማሪ ሁለት ሚሊዮን ዩሮ የእርዳታ ገንዘብ እንደሚልክ፣ ሃኪሞችንም ወደ አገራቱ በብዛት እንደሚያሰማራ አስታውቋል፡፡

በሽታው ኢቦላ ነውና፣ እርግጥም የመንግስታቱ ስጋት ተገቢነት ያለው ነው፡፡ ኢቦላ ምንም አይነት ክትባት ያልተገኘለትና ይህ ነው የሚባል ህክምና የሌለው ገዳይ በሽታ ነው፡፡ ብርድ ብርድ በማለትና በማንቀጥቀጥ ጀምሮ፣ የማያቋርጥ ትውከትንና ተቅማጥን በማስከተል በአፋጣኝ ለከፍተኛ ስቃይ የሚዳርገው ይህ አሰቃቂ በሽታ፣ ለህልፈተ ህይወት ሲያበቃ ጊዜ አይፈጅበትም፡፡ በዚህ ቫይረስ ከተጠቁ ታማሚዎች፣ 90 በመቶ ያህሉ መጨረሻቸው ሞት እንደሚሆን ይነገራል፡፡ የቫይረሱን የመዛመትና ሰዎችን የማጥቃቱን ፍጥነት ከፍተኛ ያደረገው ደግሞ የሚተላለፍበት መንገድ ነው፡፡ ሽንት፣ ላብ፣ ደምና አክታን የመሳሰሉ የሰውነት ፈሳሾች አማካይነት የሚደረግ የአካል ንክኪ፣ በሽታውን ከታማሚው ወደ ጤነኛው ሰው በአፋጣኝ ያስተላልፋል፡፡ ወረርሽኙ የተቀሰቀሰባቸው የምዕራብ አፍሪካ አገራት፣ በቂ የህክምና አገልግሎትና መሰረተልማት በአግባቡ ያልተሟላላቸው መሆናቸው ችግሩን የከፋ እንደሚያደርገው እየተነገረ ነው፡፡ ሲኤንኤን እንዳለው፣ ወረርሽኙ በፍጥነት በመሰራጨት የ11 የአፍሪካ አገራትን ገፈት ቀማሽ አድርጓል፡፡ መሰራጨቱንም ቀጥሏል፡፡ ዓለምም በዚህ ቀሳፊ በሽታ ስጋት ተውጣ ሰንብታለች፡፡

         የእንግሊዝ መንግስት ያለ አሽከርካሪ በራሳቸው የሚንቀሳቀሱ መኪኖች ከመጪው ጥር ወር ጀምሮ በአገሪቱ መደበኛ መንገዶች አገልግሎት ላይ እንዲውሉ መፍቀዱን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ የተሻሻለ ቴክኖሎጂ ውጤት የሆኑት እነዚህ መኪኖች፣ ተሽከርካሪዎች በሚበዙባቸው መንገዶች ላይ ያለ አሽከርካሪ ራሳቸውን ችለው መጓዝ፣ ፍጥነታቸውን መመጠን፣ አመቺ አቅጣጫዎችን መምረጥና መሰል ስራዎችን መከወን የሚችሉ ናቸው ተብሏል፡፡ የሌሎችን ተሽከርካሪዎች ሁኔታ ግምት ውስጥ ባስገባና ለአደጋ በማያጋልጥ መልኩ ራሳቸውን ችለው እንደሚንቀሳቀሱ የተነገረላቸው እነዚህ መኪኖች፣ በእያንዳንዷ ሰከንድ እንቅስቃሴያቸው አቅጣጫ ጠቋሚ ቴክኖሎጂዎችንና የሳተላይት ካርታዎችን እንደሚጠቀሙ ተገልጿል፡፡

ሾፌር አልባዎቹ መኪኖች አጠቃላይ እንቅስቃሴያቸውን የሚቆጣጠር ኮምፒውተርና በሁሉም አቅጣጫ ያለውን ሁኔታ በማሳየት አካሄዳቸውን በተገቢው መንገድ እንዲያስተካክሉ የሚያግዟቸው ካሜራዎች የተገጠሙላቸው ናቸው። መኪኖቹ አገልግሎት ላይ ከመዋላቸው በፊት ባሉት ጊዜያት የሚመለከታቸው የአገሪቱ የትራንስፖርት ተቋማት በዘርፉ ይሰራባቸው የነበሩ የመንገድ ደህንነትና የተሽከርካሪ አጠቃቀም ህጎችን እነዚህን አዳዲስ ሾፌር አልባ መኪኖች ግምት ውስጥ ባስገባ መልኩ እንዲያሻሽሉ ተጠቁሟል፡፡ የአገሪቱን ኢኮኖሚና ማህበረሰብ ወደ አዲስ ምዕራፍ የማሸጋገር ዕድል ይፈጥራል የተባለው ይህ ቴክኖሎጂ ጥቅም ላይ የሚውልበትን መንገድ በተመለከተ፣ የአገሪቱ የትራንስፖርት ዘርፍ መሃንዲሶችና የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የተሳተፉበት ጥናት ሲደረግ መቆየቱንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

እንግሊዝ ለመሰል መኪኖች ፍቃድ ብትሰጥም፣ ሌሎች አገራት ግን ጉዳዩ ስጋት ውስጥ ስለከተታቸው የሙከራ ስራ ከመስራት ባለፈ መኪኖቹ በመደበኛነት አገልግሎት ላይ እንዲውሉ አለመፍቀዳቸው ተገልጧል፡፡ ቶዮታ፣ ቢኤምደብሊው፣ መርሴድስ ቤንዝ፣ ኒሳንና ጄነራል ሞተርስን የመሳሰሉ የዓለማችን ታዋቂ የመኪና አምራች ኩባንያዎች የየራሳቸውን ሾፌር አልባ መኪኖች ዲዛይን በማድረግ ለዕይታ ማብቃት ከጀመሩ አመታት መቆጠራቸውን የጠቀሰው ዘገባው፣ ይሄም ሆኖ ግን አሜሪካን ጨምሮ የተለያዩ አገር መንግስታት ከደህንነት ስጋት ጋር በተያያዘ መኪኖቹ በብዛት ተመርተው በስራ ላይ እንዳይውሉ መከልከላቸውን አስታውሷል፡፡

         ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ በስፖርቱ ላይ አዎንታዊም አሉታዊም ሚና ይኖራቸዋል፡፡ የተሻለ ለውጥ ወይም የባሰውን ውድቀት ይፈጥራሉ፡፡ በዓለም ዙርያ በርካታ ስፖርት አፍቃሪዎች እግር ኳስ በቀላል እና ተፈጥሯዊ ባህርያቱ እንዲቀጥል ቢፈልጉም፤ የስፖርቱ ባለሙያዎች በሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መታጀቡ የእድገት መገለጫ ነው ብለው ይከራከራሉ፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ የሚሰሩ በርካታ አሰልጣኞችና የእግር ኳስ ባለሙያዎች በዘንድሮው በዓለም ዋንጫው ተግባራዊ ለሆኑ ቴክኖሎጂዎች ጠቀሜታ ድጋፋቸውን እንደገለፁ፣ የሊግ አሰልጣኞች ማህበር በቅርቡ የሰራው ጥናት አረጋግጧል፡፡ በጥናቱ እንደተገለፀው ለዳኞች ውድድር የመምራት ብቃትን ለማሳደግ ተግባራዊ የሆኑት ቴክኖሎጂዎች በ20 አገራት የሚገኙ በተለይም በአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች የሚሰሩ አሰልጣኞች በእግር ኳስ ስፖርት የቴክኖሎጂ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል 93 በመቶው ድጋፍ ሰጥተዋል፡፡

በክሪኬት፤ በራግቢ እና በሜዳ ቴኒስ የስፖርት ውድድሮች ተግባራዊ የሆኑት የዳኞችን ውሳኔ አሰጣጥ የሚደግፉ ቴክኖሎጂዎች በእግር ኳስ መስፋፋታቸው ተፈላጊ ቢሆንም፣ አንዳንዶች ሳይንስና ቴክኖሎጂ የስፖርቱን መሰረታዊ ተፈጥሮ እያደበዘዘው እንዳይቀጥል ስጋት አለን ይላሉ፡፡ ጎል ላይን፣ ውሃ እና ‹ቫኒሺንግ ስፕሬይ› ቫኒሺንግ ስፕሬይ አሁን የኢንተርኔት ቴክኖሊጂ በስፖርቱ ላይ አዎንታዊ ሚና የሚኖራቸውንና የተሻለ ለውጥ በመፍጠር ለእድገት ምክንያት የሆኑ አገልግሎቶቹን እየሰጠ ይገኛል፡፡ የስፖርቱን አሃዞች አቀናብሮ በማከማቸትና በተለያያ ስሌት መረጃ እንዲሆኑ በማስቻል የኮምፒውተር ቴክኖሎጂዎች የላቀ አስተዋፅኦ እየፈጠሩ ናቸው፡፡ እያንዳንዱን ጨዋታ በዋዜማው እና ባለቀ ማግስት ለመተንተን፤ በአሃዛዊ ቁጥሮች ለማነፃፀር፤ ለመለካትእና ለማስላት ተግባራዊ የሆኑት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂዎች ዓለም ዋንጫውን ከመቼውም የላቀ አድርገውታል፡፡ የዓለም ዋንጫው የፍፃሜ ጨዋታ 360 ዲግሪ በሚሽከረከር እና ከፍተኛ የማጉላት እና የጥራት ደረጃ ባለው አልትራ ኤችዲ ኦምኒካም ካሜራ መቀረፁ ትልቅ ስኬት ተብሏል፡፡

ይህን ዘመናዊ የካሜራ ቴክኖሎጂ ያቀረበቡት የበርሊን ዩኒቨርስቲ ሳይንቲስቶች ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ሶኒ ኩባንያ ከፊፋ ጋር በመተባበር በመላው ዓለም የሚሰራጩት ምስሎች በ4ሺ ፒክስልስ የጎላ ጥራት እንዲኖራቸው አድርጎ ተሳክቶለታል፡፡ በእያንዳንዱ የዓለም ዋንጫ በቀረፃ ላይ የሚሰማሩት 34 ግዙፍ ካሜራዎች ከ5ሺ ሰዓታት በላይ ሰርተዋል፡፡ የግብ ማረጋገጫ ቴክኖሎጂውን አስፈላጊነት ፈረንሳይ 3ለ0 ኢኳዶርን ባሸነፈችበት የ20ኛው ዓለም ዋንጫ የምድብ ጨዋታ ማጋጠሙ ይታወሳል፡፡ በዚሁ ቴክኖሎጂ አፈፃፀም ላይ መላው ዓለም የታዘበው የቴክኖሎጂውን ወሳኝ ጠቀሜታ ነበር፡፡ የጎል ላይ ቴክኖሎጂን መላው ዓለም ተቀብሎታል፡- የእግር ኳስን ተፈጥሯዊ ባህርይ ሊበርዝ ይችላል የሚል ስጋት ቢኖርም፡፡ የእግር ኳስ ደጋፊዎች ዳኞች በሚሰሯቸው ስህተቶች እና ጥፋቶች መወዛገብ ለሽንፈታቸው ምክንያት መደርደራቸውን የስፖርቱን ድባብ እና ተፈጥሯዊ ባህርይ ይገልፃል በሚል በቴክኖሎጂ እንዲቀር መደረጉን ይነቅፉታል፡፡

የጎል ላይን ቴክኖሎጂ በሚቀጥሉት ዓለም ዋንጫዎች በፍፁም ቅጣት ክልል ውስጥ በሚፈፀሙ ጥፋቶች ላይ ዳኞች ሳይታለሉ የኢሊጎሬ ውሳኔ እንዲሰጡ ለማድረግ ተግባራዊ እንዲሆን ጥሪ ያቀረቡም ነበሩ፡፡ በኳስ ግጥሚያ ላይ የቴክኖሎጂዎች ትግበራ የጨዋታውን የተሟሟቀ ሂደት፤ የፉክክር ደረጃ እና ግለት የሚያበርዱ እና የሚያስተጓጉሉ ከሆኑ ቢቀር ይሻላል በሚል የተሟገቱም አሉ፡፡ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ከባዱን ሙቀት ለመከላከል ተጨዋቾች በመሃል ግጥሚያ ላይ አቋርጠው ውሃ እንዲጠጡ የሚያስገድድ ሳይንስ ነበር፡፡ ይህ ተግባር ግን ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚያመዝን ማስረጃ በመጥቀስ የተቃወሙት ጥቂት አይደሉም፡፡ በቅጣት ምት ላይ ተጨዋቾች የሚሰሩትን የመከላከያ ግድግዳ ለማስመር ዳኞች መገልገል የጀመሩት ቫኒሺንግ ስፕሬይም ብዙም ጠቀሜታው ያልጎላ ነው፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ በሜዳ ላይ የጨዋታን ግለት የሚያበርድ ከመሆኑም በላይ በዳኛው ላይ አላግባብ ጥቃት እንዲፈፀም የሚያግዝ መሳርያ ነው በሚልም ነቅፈውታል፡፡ ይሁንና ቫኒሺንግ ስፕሬይ ቅጣት ምቶች ያለአንዳች ግርግር እንዲመቱ ሁኔታዎችን በማመቻቸቱ የሚያደንቁት አልጠፉም፡፡ ቴክኖሎጂ - ከ‹ማልያ› እስከ ‹ታኬታ› በዓለም ዋንጫው ማልያዎች፤ ሙሉ የስፖርት ትጥቆች የመጫወቻ ታኬታዎች አቅራቢ የሆኑት ሶስቱ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች አዲዳስ፣ ናይኪና ፑማ ዘንድሮ ለየብሄራዊ ቡድኖቹ ያቀረቧቸው ማልያዎች በከፍተኛ ቴክኖሎጂ የተመረቱ ናቸው፡፡

ማልያዎቹ ለከፍተኛ ደረጃ በበለፀጉ እና ሪሳይክልድ በሚሆኑ ‹‹ፖሊቲክ ፋይበርስ›› የተሰሩ፤ ተለብሰው የማያስጨንቁ፤ አየር ማስገቢያ ያላቸው፣ እንደ ቆዳ ልጥፍ ያሉ እና ቅለት ያላቸው፣ ጡንቻዎችን እንደተፈለገ ለማዘዝ የተመቹ፣ ከልክ ያለፈ ሙቀትን ለመከላከል የሚያስችሉ ናቸው፡፡ እነዚህ ብቃቶቻቸው በከፍተኛ ሳይንሳዊ ምርምርና ቴክኖሎጂ የተዘሰራላቸው ናቸው፡፡ዓለም አቀፍ የትጥቅ አቅራቢ ኩባንያዎቹ ለዓለም ዋንጫው ያቀረቧቸው ማልያዎች ርጥበት እና ላብ የሚችሉ፤ ለአተነፋፈስ የማያስቸግሩ፤ ክብደት የሌላቸው እና እንደልብ ተቀላጥፎ ለመጫወት የሚመቹ ናቸው፡፡ ናይኪ በአልባሳት የስፖርት ትጥቆቹ በርካታ የባዮ ሜካኒካል ምርምሮችን አድርጓል፡፡ አዲዳስ ደግሞ ባቀረባቸው የብሄራዊ ቡድን ማልያዎች የተጨዋቾች ስም፤ መለያቁጥር እና ልዩ ልዩ አርማዎች ከመለጠፍ ይልቅ፣ ከማልያው ጋር ተዋህደው እንዲሰሩ አድርጓል፡፡ የመጫወቻ ታኬታዎችም በቴክኖሎጂ ረቀቅ ብለው በመሰራታቸው በተለያዩ ደማቅና ሳቢ ቀለማት በጥናት እና በምክንያት ተመርተው አሽብርቀዋል፡፡ አንዳንዶቹ በክብደታቸው ቀለል ተደርገዋል፡፡

አንዳንዶቹ እንደቡትስ በቁርጭምጭሚት ላይ ሊደርስ የሚችልን ጉዳት የሚከላከል ተቀጥሎባቸዋል፡፡ በዓለም ዋንጫው በተሳተፉ 32 ብሄራዊ ቡድኖች እስከ ስምንት ትጥቅ አቅራቢዎች ቢኖሩም በቴክኖሎጂያቸው ተራቅቀው እና ገበያውን ተቆጣጥረው ያሉት ዋናዎቹ አዲዳስ እና ናይኪ ናቸው፡፡ ፑማ በቅርበት ይከተላቸዋል፡፡ ሁለቱ ኩባንያዎች ገበያውን ለመቆጣጠር የሚያደርጉት ትንቅንቅ በቴክኖሎጂ የተሻለ ሆኖ መገኘትን በማቀድ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ በእግር ኳሱ ላይ በየዓለም ዋንጫው አዳዲስ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂን በማፈራረቅ ተፅእኖ መፍጠሩ የማይቀር ይመስላል፡፡ ብራዙካ የተባለችው የአዲዳስ ኳስ ውድድሩ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ምንም አይነት ቅሬታ ስላልቀረበባትም አዲዳስን ገበያውን እንዲቆጣጠር ያስችለዋል፡፡ አዲዜሮ ኤፍ50 የተባለው የአዲዳስ ታኬታ ባደረጉ ተጨዋቾች በዓለም ዋንጫው ከገቡት 171 ጎሎች 41 በመቆጠራቸውም የምርቱን ስኬታማነት መለኪያ ሆኗል፡፡ በናይኪ ሜርኩርያል ቡት የተመዘገቡት 35 ጎሎች ናቸው፡፡ አዲዳስ ብራንድ የሆኑ ታኬታዎች 74 የናይኪ ብራንድ የሆኑ ታኬታዎች 73 ጎሎች ተቆጥሮባቸዋል፡፡ በሁለቱ ኩባንያዎች የቀረቡ ታኬታዎች በአንፀባራቂ እና ደማቅ ቀለማት መሰራታቸው ጠቃሚ ነው በሚል ኮሜንታተሮች አመስግነዋል፡፡ የታኬታዎቹ ቀለማት የተጨዋቾችን ማንነት ለመለየት ያግዛል በሚል ተደንቋል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች ታኬታዎቹ ቡትስ መምሰላቸውን ያልወደዱት ሲሆን ከቦክስ ጓንቲዎች ጋር አመሳስለዋቸዋል፡፡

         አንዳንድ ዘገባዎች በሚቀጥሉት 20 ዓመታት በዓለም እግር ኳስ ስፖርት የሮቦት ዳኞች እና የሮቦት ተጨዋቾች ማሰለፍ የሚቻልበት የስልጣኔ ደረጃ ይመጣል ይላሉ፡፡ ምናልባትም የቴክኖሎጂ ድጋፍ አስፈላጊነቱ ከታመነበት ፊፋ የተርመጠመጠበትን የሙስና ችግር የሚያጋልጥ ቴክኖሎጂ ቢፈለሰፍ ብለው የማጣጣያ ትችት ያቀረቡ መረጃዎች፤ በሚቀጥሉት ሃምሳ ዓመታት ዓለም ዋንጫ በጨረቃ ላይ ሊስተናገድ ይችላል ብለው አሹፈዋል፡፡ኤችቲቢ ኤንድ ፊልቸር ቦነስ የተባለ ተቋም የዓለማችን የእግር ኳስ ስፖርት የወደፊት አቅጣጫዎች ብሎ በሰራው ምርምር ይፋ እንዳደረገው በሚቀጥሉት 50 ዓመታት ስፖርቱ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ከፍተኛ ለውጦች ማሳየቱ የማይቀር ይመስላል፡፡ ብዙዎቹ ቴክኖሎጂዎች እስከ 2022 እ.ኤ.አ ተግባራዊ ሊሆኑ እንደሚችሉም ድምዳሜ ላይ ደርሷል፡፡

እንደተቋሙ ሪፖርት ከሆነ በሚቀጥሉት 15 ዓመታት በእግር ስፖርት በተጨዋቾች ማልያ ላይ ማንኛውንም እንቅስቃሴ ለመቅረጽ የሚችሉ በዓይን የማይታዩ ካሜራዎች ይለጠፋሉ፤ የመጫወቻ ታኬታዎች ኳስን ለመቆጣጠር መጥኖ ለመምታትና አቅጣጫ ለመገመት የሚያስችሉ ይሆናል፤ የውድድር ዳኞች ማናቸውን የጨዋታ እንቅስቃሴ ለመበታተን እንዳይገባቸው ልዩ የካሜራ ሄልሜት ሊገጠምላቸውም ይችላል፡፡ ከስምንት ዓመታት በኋላ ኳታር በምታስተናግደው 22ኛው ዓለም ዋንጫ ዙርያ ከተነሱ አከራካሪ ጉዳዮች ዋንኛው የአገሪቱ ሙቀት ለውድድሩ አይመችም የሚለው ነው፡፡ የኳታር ዓለም ዋንጫ አዘጋጆች ግን ይህ ችግር በቴክኖሎጂ የሚፈታ ነው ብለው ተከራክረዋል፡፡

እስከ 45 ዲግሪ ሴንቲግሬድ የሚደርሰው የኳታር ሙቀት በስታድዬሞች በሚገጣጠሙ እና በሚሰሩ የማቀዝቀዣ ምሰሶዎች ለእግር ኳስ ጨዋታ የተመቹ እናደርጋቸዋለን በሚል ከወዲሁ ቃል ገብተዋል፡፡ ሰሞኑንም እስከ 7.4 ሚሊዮን ዶላር የወጣበትን የማቀዝቀዣ ቴክኖሎጂን የፈተሹበት የሙከራ ተግባራትን አከናውነዋል፡፡ በርካታ ተመራማሪዎች እና ሳይንቲስቶች እግር ኳስ ከቴክኖሎጂ ጋር ተሳስሮ መቀጠሉን በመደገፍ የተለያዩ አዳዲስ ሃሳቦችን በማፍለቅ ላይ ናቸው፡፡ በሚቀጥሉት ዓለም ዋንጫዎች ተግባራዊ ቢሆኑ ተብለው ሃሳብ ከተሰጠባቸው የቴክኖሎጂ ግኝቶች የመጀመርያው ኦፍሳይድ እና ኦንሳይድ የሆኑ ኳሶችን ለመለየት እንደ ግብ ማረጋገጫ ቴክኖሎጂ አዲስ አሰራር መፈልሰፉን የጠየቁ ናቸው፡፡ ሌላው ተጨዋቾች በተጋጣሚያቸው ፋውል ሲሰራባቸው በትክክል መሰራረቱን ወይም ለማታለል መወደቁን ለማረጋገጥ የሚያስችል መሳርያም ቢኖር ተመኝተዋል፡፡ በራግቢ እና በአሜሪካን ፉትቦል ተግባራዊ የተደረገውና የሜዳ ላይ ትዕይንት በቀጥታ ተመልካች በቅርበት እየሰማ እንዲከታተል የታቀደው የቀረፃ ቴክኖሎጂም አለ፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ በተጨዋቾች ማልያዎች ላይ በሚለጠፉ ልዩ ካሜራዎች ወይንም ደግሞ በነፍሳት መልክ በሚሰሩ እና ኳስ ጨዋታውን በመካተል በሚቀርፁ ልዩ ካሜራዎች ይህን ተግባር ለማከናወን እንደሚቻልም ይገለፃል፡፡

          በዓለም የወጣቶች የአትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ለመካፈል ወደ አሜሪካ አቅንተው ከነበሩ አትሌቶች መካከል ባለፈው ቅዳሜ ድንገት ከተሰወሩትና ከቀናት ቆይታ በኋላ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ከዋሉት አራት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች መካከል ሁለቱ ከታዋቂዎቹ ‹ናይኪ›ና ‹አዲዳስ› ኩባንያዎች ጋር ስምምነት መፈራረማቸውን ኦሪጎን ላይን ድረገጽ ትናንት ዘገበ። አማኑኤል አበበ፣ ዱሬቲ ኢዳኦ፣ መዓዛ ከበደና ዘይቱና ሞሃመድ የተባሉት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች፣ ባለፈው ቅዳሜ ከልዑካን ቡድኑ ተለይተው መጥፋታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ የኦሪጎን ፖሊስ ትናንት በሰጠው መግለጫ ከጠፉት አትሌቶች መካከል ዘይቱና ሞሃመድ ከናይኪ፣ ዱሪቲ ኢዳኦ ደግሞ ከአዲዳስ ጋር የኮንትራት ስምምነት መፈራረማቸውን ከቡድኑ አሰልጣኞች ማረጋገጡን ገልጿል፡፡ የኦሪጎን ፖሊስ አትሌቶቹ ይህንን ስምምነት የተፈራረሙት ሊጠፉ አንድ ቀን ሲቀራቸው እንደነበር መግለጹን የጠቆመው ዘገባው፣ ጉዳዩን በተመለከተ ሁለቱንም ኩባንያዎች ለማነጋገር ያደረገው ሙከራ አለመሳካቱን ጠቅሷል፡፡ 

        ፖሊስ አትሌቶቹ በአሜሪካ የመቅረት ዕቅድ ይዘው እንደጠፉ ከአሰልጣኞቹ መረጃ እንዳገኘና አትሌት ዱሪቲም የፓስፖርቷን ኮፒ ለአዲዳስ ኩባንያ የኮንትራት ስራ አስኪያጅ ለመላክ እንደምትፈልግ ለአሰልጣኞቿ ጥያቄ ማቅረቧንና አሰልጣኞቹም የቡድኑ አባላት ፓስፖርት የሚገኝበትን ክፍል ቁልፍ እንደሰጧት አረጋግጫለሁ ብሏል፡፡ አሰልጣኞቹ፤ አትሌቶቹ ከጠፉ በኋላ ፓስፖርታቸውን ካስቀመጡበት እንዳጡት ተናግረዋል ያለው ዘገባው፤ ፖሊስ በደረሰው ጥቆማ መሰረት ባከናወነው ቀናትን የፈጀ ፍለጋ አትሌት ዘይቱናን በዋሽንግተን፣ ሌሎቹን ሶስት አትሌቶች ደግሞ ቤቨርተን ውስጥ እንዳገኛቸው አስረድቷል፡፡ አትሌቶቹ በአሜሪካ ለምን ያህል ጊዜ እንደሚቆዩም ሆነ ቀጣይ ዕጣ ፋንታቸው ምን ሊሆን እንደሚችል ፖሊስ ምንም አይነት መረጃ አለመስጠቱን ዘገባው ጠቁሟል፡፡

         በእንግሊዝ መንግስት የገንዘብ ድጋፍ በጋምቤላ ክልል በተከናወነ አስገዳጅ የሰፈራ ፕሮግራም፣ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ደርሶብኝ፣ ለስደት ተዳርጊያለሁ ያሉ አንድ ኢትዮጵያዊ ገበሬ፤ በአገሪቱ ላይ የመሰረቱትን ክስ ያዳመጠው የለንደን ከፍተኛ ፍርድ ቤት፤ እንግሊዝ ለኢትዮጵያ የምትሰጠው እርዳታ የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶች ለሚጥሱ ፕሮግራሞች መዋል አለመዋላቸው እንዲጣራ መወሰኑን የኢትዮጵያ መንግስት ተቃወመ፡፡ ብሉምበርግ ኒውስ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጉዳዩን በተመለከተ ለንደን በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በኩል በላከው መግለጫ፤ ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ማስተላለፉ አግባብነት እንደሌለው ገልጾ፣ ክሱ የተመሰረተው ያለምንም ተጨባጭ መረጃና የራሳቸውን ፖለቲካዊ ጥቅም ለማስከበር በሚፈልጉ ሃይሎች አነሳሽነት እንደሆነ ገልጿል፡፡

በክልሉ የተከናወኑ የሰፈራ ፕሮግራሞች በነዋሪዎች ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረቱና ማህበራዊ አገልግሎቶችን በማሻሻል የተበታተነ አሰፋፈር ባለባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ማህበረሰቦችን ተጠቃሚ የማድረግ ግባቸውን በማሳካት ረገድም ውጤታማ እንደነበሩ መግለጫው አስታውሷል፡፡ መንግስት ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ በሚያከናውነው በዚህ የሰፈራ ፕሮግራሞች ላይ መሰል ውንጀላዎችና የተዛቡ አመለካከቶች እንዲፈጠሩ ከሚያደርጉ ምክንያቶች አንዱ የሰፈራ ፕሮግራሙን ዓላማ በአግባቡ አለመረዳት ነው ብሏል፡፡ ‘ሂዩማን ራይትስ ዎች’ የተባለው አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ድርጅት በጋምቤላ ክልል የተከናወነው የሰፈራ ፕሮግራም፣ አስገዳጅና በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ለከፋ ስቃይና የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት የዳረገ ነው ማለቱን የዘገበው ብሉምበርግ ኒውስ፤ ፍርድ ቤቱ ይህን ውሳኔ ማስተላለፉ ይበል የሚያሰኝ ነው ሲል እንዳሞካሸውም ጠቁሟል፡፡

የእንግሊዝ ዓለምአቀፍ የልማት ተቋም በበኩሉ፣ “በጋምቤላ ክልል ብዙ ዜጎችን ያለፍላጎታቸው ከቀያቸው አፈናቅሏል፣ ለእስራት፣ ለድብደባና ለስቃይ ዳርጓል ለተባለው የሰፈራ ፕሮግራም” የገንዘብ እርዳታ እንዳልሰጠ መናገሩን ገልጿል፡፡ ከጋምቤላ ክልል ተፈናቅለው በኬኒያ በስደት የሚገኙ ስማቸው ያልተገለጸ ገበሬ፤ በእንግሊዝ መንግስት ላይ የመሰረቱትን ክስ የተቀበለው የለንደን ከፍተኛ ፍርድ ቤት፤ የእንግሊዝ የእርዳታ ድርጅት ለኢትዮጵያ የሚያደርገው ድጋፍ የአገሪቱን ዜጎች የሰብዓዊ መብቶች በማይጥስ ሁኔታ ጥቅም ላይ ስለመዋሉ ይጣራ ሲል ከሁለት ሳምንታት በፊት መወሰኑን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

       የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለአብራሪዎች የሚሰጠውን ስልጠና ለማሳደግ ሴስና ከተባለው አውሮፕላን አምራች ኩባንያ የገዛቸውን ‘ሴስና 172’ የተሰኙ ሶስት ተጨማሪ የስልጠና አውሮፕላኖች ባለፈው ሳምንት ወደ አገር ውስጥ ማስገባቱን ገለጸ፡፡ አየር መንገዱ ባወጣው መግለጫ፤ በቅርቡ ዲያመንድ ከተሰኘው የኦስትሪያ አውሮፕላን አምራች ኩባንያ 12 አውሮፕላኖችን ገዝቶ ማስገባቱን ጠቁሞ፣ ከሰሞኑ ያስገባቸው አዳዲስ አውሮፕላኖችም አራት መቀመጫዎች ያሏቸውና ባለ አንድ ሞተር እንደሆኑና በአሜሪካና በአውሮፓ ከአስር አመታት በፊት የጥራት ማረጋገጫ አግኝተው በተለያዩ አገራት ለስልጠና አገልግሎት በመዋል ላይ እንደሚገኙ ገልጿል፡፡ የአየር መንገዱን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማርያም በመግለጫው ላይ እንዳሉት፣ አየር መንገዱ እ.ኤ.አ በ2025 እደርስበታለሁ ብሎ ባስቀመጠውና በመተግበር ላይ በሚገኘው ስትራቴጂክ እቅድ ውስጥ ለሰው ሃይል ልማት ትኩረት የሰጠ ሲሆን፣ አውሮፕላኖቹም አየር መንገዱ የሚሰጠውን የአብራሪዎች ስልጠና ዘመናዊና ጥራቱን የጠበቀ ለማድረግ የሚያግዙ ናቸው፡፡

በስትራቴጂክ ዕቅዱ የመጨረሻ አመት በአፍሪካ መሪ የሆነ የአቪየሽን ስልጠና ማዕከል ባለቤት የመሆን ግብ አስቀምጦ በመስራት ላይ የሚገኘው አየር መንገዱ፣ አውሮፕላኖቹ በዘርፉ የሚሰጠውን የስልጠና አቅም እንደሚያሳድጉለት ገልጿል፡፡ አየር መንገዱ ከ80 ሚሊዮን ዶላር በላይ በጀት በመመደብ አካዳሚውን የማስፋፋት ፕሮጀክት በመተግበር ላይ እንደሚገኝ የጠቆመው መግለጫው፤የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአቪየሽን አካዳሚ በአፍሪካ ትልቁ የአቪየሽን ስልጠና ማዕከል መሆኑና በያዝነው የፈረንጆች አመት፣ በአፍሪካ የአየር መንገድ ማህበር ‘የአመቱ አገልግሎት ሰጪ የአቪየሽን አካዳሚ’ ተብሎ መሰየሙንም አስታውሷል፡፡ የስልጠና አካዳሚው ተማሪዎችን የመቀበል አቅም ባለፉት አራት አመታት ከፍተኛ እድገት ማሳየቱንና በአሁኑ ሰአትም አመታዊ የመቀበል አቅሙ ከ1ሺህ በላይ መድረሱን ገልጿል፡፡ በዕቅድ አመቱ መጨረሻ ይህን ቁጥር ከ4ሺህ በላይ ለማድረስ ዕቅድ ይዞ እየሰራ እንደሚገኝም ጠቁሟል፡፡

           በአሜሪካ ዳላስ አካባቢ ከፍተኛ ተወዳጅነት ካላቸውና የተለያዩ አገር ዜጎች አዘውትረው ከሚመገቧቸው የአመቱ 100 ምርጥ የምግብ አይነቶች ውስጥ፣ ክትፎ አንዱ መሆኑን ዳላስ ኦብዘርቨር ድረገጽ ዘገበ፡፡ ዳላስ ኦብዘርቨር በተለያዩ ሬስቶራንቶች በመዘዋወር የሰራውን ጥናት በመጥቀስ፣ከትናንት በስቲያ በድረ-ገጹ እንዳስነበበው፣ ዳላስ ውስጥ በሚገኘው ሼባ የተሰኘ የኢትዮጵያውያን ሬስቶራንት ውስጥ እየተዘጋጀ የሚቀርበው ክትፎ፣ በአመቱ የዳላስ አካባቢ ተወዳጅ 100 የምግብ አይነቶች ዝርዝር ውስጥ የ50ኛ ደረጃን ይዟል፡፡ ከሁሉም የምግብ አይነቶች በቀዳሚነት የተቀመጠው ኦይስተር ተብሎ የሚጠራው የባህር ውስጥ ምግብ ሲሆን፣ በተከታይነት የተቀመጠው ደግሞ፣ በባህላዊ አሰራር የሚዘጋጀው የቱርኮች ሳንዱች ነው፡፡

ቺክን ሺሽ ከባብ የተባለው ከዶሮ ስጋ የሚሰራ ምግብ በሶስተኛነት ተቀምጧል፡፡ ዝርዝሩ በዳላስ አካባቢ የሚኖሩ የስጋም ሆነ የአትክልት ተመጋቢዎች በአመቱ የበለጠ የተመገቧቸውንና ያዘወተሯቸውን የተለያዩ የዓለም አገራት የምግብ አይነቶች የያዘ ሲሆን፣ በዝርዝሩ ውስጥ የተካተቱት ምግቦች የሚገኙባቸውን ሬስቶራንቶች፣ አሰራራቸውን፣ የተለዩ የሚያደርጓቸውን መገለጫዎች ወዘተ ጠቁሟል፡፡ በዘንድሮው የዳላስ ተወዳጅ የምግብ አይነቶች ዝርዝር ውስጥ ከስጋ፣ ከእንቁላል፣ ከአትክልትና ከመሳሰሉት ምግቦች የተካተቱ ሲሆን፣ የአሳና የፓስታ ምግቦችም ተጠቅሰዋል፡፡ የሳንዱችና የበርገር አይነቶችም ከአመቱ ተወዳጅ ምግቦች ተርታ ተሰልፈዋል፡፡