Administrator

Administrator

Friday, 26 July 2024 20:23

"አዘቦት"

የዩንቨርሲቲ ተማሪ ነው፣ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ይጽፋል፣ ሞጋች ነው፣ የውይይት ባሕሉ ድንቅ ነው፣ መጻሕፍት ቆንጆ አድርጎ መተንተን ያውቅበታል፣ ምልከታውን እወድለታለሁ...ሌላም ሌላም!  አሁን ደግሞ "አዘቦት" የተሰኘ የአጭል አጭር ታሪኮችን/Post card stories ይዞልን ቀርቧል።

የት ማግኘት እንችላለን? ቢሉ በእጅ ስልክዎ፥ #afro read app የሞባይል መተግበሪያ ላይ በ50 ብር ብቻ ሸምተው ማንበብ ይቻላል!

 Sirak Wondemu ን በሀሳብ አግዙት፤ አንብቡለትም፤ በሀሳብ የሚያምን ትሁት ወንድማችን ነው፤ ዕድሜው ከእኔ ብዙ ቢያንስም ስራዎቹ ትልቅ እንደሆኑ እመሰክራለሁ፤ በእኔ ይሁንባችሁ አንብቡት ትወዱታላችሁ! ሰሞኑን በሰፊው እመለሳለሁ።

መልካም ዕድል ለታናሽ ወንድማችን!

በደራሲ እያዩ ዳኛው የተሰናዳውና “ናዋዥ” የተሰኘው አዲስ የግለ ታሪክ መፅሐፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ መፅሐፉ በዋናነት በደራሲው የግል ህይወት ላይ የሚያጠነጥን ቢሆንም፤ ኢትዮጵያዊያን በሱዳንና በሊቢያ በኩል ወደ አውሮፓ ለመግባት የሚያደርጉትን አስከፊና አስቸጋሪ የስደት ህይወት የሚያሳይ ነው ተብሏል፡፡

ነዋሪነቱን በጀርመን ያደረገው ደራሲ እያዩ ዳኛው፤ መፅሐፉ ከደቡብ ጎንደር ክምር ድንጋይ እስከ ጣሊያን የወደብ ከተማ ትራፓኒ የዘለቀውን የስደትና የውጣ ውረድ ጉዞ የሚዳስስ መሆኑን  ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡

 “ናዋዥ”፤ደራሲው ልጅነቱን የአፍላ ወጣትነቱን፣ የኢትዮጵያውያንን የስደት ኑሮ፣ በሱዳንና በሰሃራ በረሃ ለማቋረጥ ስደተኞች የሚከፍሉትን መስዋዕትነት እንዲሁም በመንግሥት አልባዋ ሊቢያ የነበረውን ኑሮና በሜድትራንያን ባህር የሚያጋጥምን ፈተና ያስቃኛል፡፡

በ470 ገፅ የተቀነበበው “ናዋዥ”፤ የግለ ታሪክ መፅሐፍ በ500 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

የዓለማችንን ምርጥና ስመጥር የአጭር ልብወለድ ድርሰቶችን ትርጉም የያዘው “ደማቆቹ“ የተሰኘ መድበል በገበያ ላይ ውሏል፡፡ መጽሐፉ ከአሥራ አራት በላይ ደራስያንን ሥራዎች ያካተተ ሲሆን፤ ከእነዚህም ውስጥ አርነስት ሄሚንግዌይ፣ አየን ራንድ፣ ገብርኤል ጋርሺያ ማርኩዌዝ፣ አንቷን ቼኮቭ፣ ናጂብ ማህፉዝ፣ ማርጋሬት አትዉድና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡

በ254 ገጾች የተቀነበበው መድበሉ፤ አሥራ ስድስት የተለያዩ ርዝመት ያላቸውን የገናና ደራስያን ሥራዎች ያካተተ ነው፡፡ “ደማቆቹ” የተሰኘውን መድበል በዋናነት የሚያከፋፍለው የጃፋር መጻሕፍት መደብር ሲሆን፤ በ400 ብር ለገበያ እንደቀረበ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የዚህ መጽሐፍ ተርጓሚ ከዚህ ቀደም “የንፋስ ህልምና ሌሎች ታሪኮች”፣ “አፍሮጋዳ” ፣ “መሬት-አየር-ሰማይ”፣ “የሰከረ እውነታ”፣ “እስቲ ሙዚቃ”፣ “ነጸብራቅ” እና “ይመስላል ዘላለም” በሚሉ የአጭር ልብወለድና የመጣጥፍ ስብስብ ሥራዎቹ በአንባቢያን ዘንድ ይታወቃል፡፡

ደራሲ ሌሊሳ ግርማ፤ ላለፉት ረዥም ዓመታት፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ አጭር ልብወለዶችንና ወጎችን በአምደኝነት በመጻፍም የሚታወቅ ትጉህ የብዕር ሰው ነው፡፡

Monday, 22 July 2024 20:20

ምርኮኛው ባለቅኔ

“ባጠቃላይ፣ እናርጅና እናውጋ፣ ጌራወርቅ ሞጋች፣ አመራማሪ፣ ገሳጭና አስደማሚ ዐሳቦችን በምናቡ ሸምኖ በማቅረብ
ውስብስቡን ኑባሬንና ልቡናችንን ባላየነው አድማስ በርብረን እንድንገነዘብ ያደረገበት ሸጋ መድበል ነው፡፡ ይህ የፈጠራ ሥራ
በኪነት ሚዛን የከያኒውን ክህሎት መስክረን፣ ያለ ንፍገት ሥሙን በደማቅ ቀለም እንድንጽፍ የሚገፋ ነው፡፡--


እናርጅና እናውጋ (2015) በጌራወርቅ ጥላዬ የተጻፈ የግጥም መድበል ነው፡፡ መድበሉ መልከ ብዙ የሕይወት ገጾች በወርድና ቁመታቸው የተፈተሹበት ነው፡፡ በመድበሉ ውስጥ የቀረቡ ግጥሞች አጀንዳና ድምጸት መልከ ብዙ መሆኑ ደግሞ የገጣሚውን አቅም በግልፅ ያሳያል፡፡ ይህ ማለት፣ የጌራወርቅ ግጥሞች እንደ አንዳንድ ጥቂት ገጣሚያን ሥራዎች በተመሳሳይ ድምጸት ሥር የወደቁ፣ በተመሳሳይ ጭብጥ (recurrent subject) ዙሪያ የሚሽከረከሩ አይደሉም፡፡       
በእናርጅና እናውጋ የገጣሚው የቋንቋ ባለሟልነት፣ የምሰላ ክህሎት፣ የገለጻ ጠቢብነትና የምናብ ጥልቀት ተንፀባርቋል፡፡ በመድበሉ ውስጥ የቀረቡት ግጥሞች ምት ልክ ሆኖ መገኘትም ዜማው ስሙር እንዲሆን ረድቷል፡፡ ቀጥለው የቀረቡት ጥቂት ስንኞች ይህን ሐተታ በዋቢነት ያስረግጣሉ፡     
እንደ ደብር መርገፍ፣ እንደ ጸናጽሉ
ወዲህ ወዲያ ብዬ፣ ወዳንቺ ተመለስኹ
አፈር ለሚበላው ላፈር ጦም እያደርኹ፡፡
እህል ውኃ ከወሰደኝ፣ ካፍሽ አፋፍ የነጠቀኝ፣
ቢመልሰኝ ላንቺ ማጀት …
ልሣለምሽ እንደ ደብር፣ ልስገድልሽ እንደ ታቦት፤
በዐይኔ ቅንድብ አመልክቼ፣ በአኮቴት ሥመለከት፣
ካድባር - ካውጋር፣ ሳውጠነጥን ያንቺን ሕይወት …
መኖርሽ በኗሪሽ ውስጥ ጠፍቶ አየሁት፡፡
(ጌራወርቅ፣ 2015፡ገጽ 21)
ወይዘሪት እምዬ! መሆንሽ ምን ነውሳ …?
ቀባሪ እንዳጣ ሬሳ፣ በሰው እንደተረሳ፣
ዳዋ እንደወረሰው እንደ ገበሬ ማሳ፤
ምላሱ ከላንቃው እንደተጣበቀ፣
ገላው እንደልብሱ በላዩ እንዳለቀ፣
በወንጭፍ ድንጋይ ምት እንደተሰበረ እንደበኩር እሸት፣
ሞት እንደተጸየፋት፤ ኑሮ እንዳቀለላት፤ ደካማ አሮጊት፣
ጎታታ፣ ዳተኛ፣ እንደጉፋያ ከብት፣
በሚታየኝ ኹነት፣ ይሁን ያንቺ ሕይወት?
(ጌራወርቅ፣ 2015፡ገጽ 22-23)
ማሳ ሲሆን እንቅልፋችን፣
ስንፍናችን ፍሬ አፍርቶ፤

ኩራት ሲሆን ብልግናችን፣
ትዕቢታችን አፍ አውጥቶ፤

ገድል ሲሆን ውርደታችን
 ታ’ምር አይሆን ውድቀታችን፡፡

ለፍቅር ልብ ባንረታ፣
እንደ በሬ ጥልን ጠምደን፣
ለጦርነት ስንበረታ፤
ቀን ይነሣል፤ ዘመን ወድቆ፣
ሲደናበር ጊዜ ቃዥቶ፡፡

ለከንቱ አውድማ፣
… በባዶ ባድማ፤
ስንደክም ለሥጋ፣
ክረምት አልፈን በጋ፤
ነፍሳችን ብንገፋው፣ አድርገን እንዳይሆን
ካልተፈጠረ አነስን፣ ከሞተ ሰው ሳይሆን፡፡
(ጌራወርቅ፣ 2015፡ገጽ 94)
ጌራወርቅ ሥጋና ደምን ዘልቀው ስሜትን የሚሸነትሩ ቅኔያትን በመከየን የተካነ ልኂቅ ነው፡፡ የሐዘን ትካዜው የነፍስ ቅኝትን ያደፈርሳል፡፡ የፀፀት ኑዛዜው ልብ ያደማል፡፡ የፍቅር እንጉርጉሮው ማዕበሉ ያላጋል፡፡ የቁጭት እሮሮው ረመጡ ያጋያል፡፡ የኂስ ሾተሉ ኅሊና ያቆስላል፡፡ የመፃኢው ጊዜ ትንቢቱ በፍርሃት ያርዳል፡፡ ደም አንተክታኪ ሽለላው ፍም ያስጨብጣል፡፡
ጌራወርቅ ከሌሎች ባለቅኔዎች በበለጠ የውበት ምርኮኛ ነው፤ የፍቅር ተማላይ፡፡ የውበት ምርኮኛነቱ በሴት ቁንጅና ይገለጣል፡፡ በግጥሞቹ ውስጥ በምናብ ሥሎ ያቀረባቸው ሴቶች በአካል ቁመናቸው አምሣለ አማልክት ናቸው፡፡ ባለቅኔው በፍቅር ምርኮ ልደርላችሁ፣ ሠልጡኑብኝ የሚላቸው፣ ክሱት ምግባራቸውን እያወሳ የሚያወድሳቸው ሴት ገጸባሕርያትም እንከን የለሽ ሰብዕናን የተሸለሙ ናቸው፡፡ የሚከተሉት ስኝኞች ለእዚህ ዐሳብ ዋቢነት የቀረቡ ናቸው፡   
የሚያስፈራስ! እንደመሸበር
የሚያስፈራስ! እንዳለማፈር
የሚያስፈራስ! እንደ ሲኦል መንገድ
አንቺን ለይቶ! ዐይቶ! አለመውደድ፡፡
            
ዐይንሽ አስደንባሪ፣ አፍንጫሽ አቀበት
ይጥላል ከንፈርሽ የጥርሶችሽ ውበት፤
መልክሽ እንቆቅልሽ ባገር የሚፈታ!
አንደበትሽ ቅኔ ግጥም በአንድምታ!
ልብሽ የመለኮት ምሥጢር የሚረታ!
አትገኝም እንጂ በዕድሜ ልክ ሱባዔ፣
አንቺን ያገኘ ነው፣ ፍቅር ማስመስከሪያ! የገነት ጉባኤ፡፡

ታምኖ እንደኖረ በጌታው ቤት ሲኖር
ለንጉሡ አስከሬን እንደሚሞት አሽከር፤
አልታደለም እንጂ አንቺን ሰው ሊያፈቅር!
አልመጠነም እንጂ ሰው አንቺን ለማፍቀር!
ተመርጦ! ተለይቶ! አንቺን ሰው ቢያፈቅር?!
ለጥላሽ ይሞታል እንኳን ላፍሽ ከንፈር፡፡
(ጌራወርቅ፣ 2015፡ገጽ 92-93)

እንኮይ የእንኮይ መሥክ መሣይ አበቄለሽ
ንጋት እያየሁሽ እጠላለሁ ሲመሽ፤
ወተት፣ ያጓት ፍሬ በሚያስንቀው ጥርስሽ
ሳልጠጣው፣ ሳልጎርሰው ብገድፍ በፈገግታሽ
ምን - ትዋብ? ስላቸው፣ ተዋበች እያሉ
ባርብ አፈር አልኩኝ ለቁንጅናሽ ቃሉ፡፡
(ጌራወርቅ፣ 2015፡ገጽ 102)
ዘቢብ - ዕጣን - ጧፍ ነው የደጅሽ አምኃ
አልማዝ የሚፈሰው ቀለመ ወርቅ ውኃ፡፡
አፍሽ ሥላሣየኝ የልብሽን ጸዳል
ገዳሙ፣ ገዳሙ ልበልሽ ሥራውባል
የሽፋልሽ ጽድቀት ከኃጢያት ያነጻል
የወደደሽ ወዶ ከሞት ይታረቃል፡፡  
(ጌራወርቅ፣ 2015፡ገጽ 103-104)
እናርጅና እናውጋ እንደ ሀገር የተጣባንን ክፉ ደዌ በጥልቀት የሚዳስሱ፣ የዘመኑን መልክ የሚያሳዩ ግጥሞች የቀረቡበት መድበል ነው፡፡ በመድበሉ ገጣሚው የተንሻፈፈ አመለካከታችንን ኮንኖ፣ የእዚሁ እኩይ አመለካከታችን ዳፋ መጥፎ መሆኑን ነግሮናል፡፡
ባጠቃላይ፣ እናርጅና እናውጋ፣ ጌራወርቅ ሞጋች፣ አመራማሪ፣ ገሳጭና አስደማሚ ዐሳቦችን በምናቡ ሸምኖ በማቅረብ ውስብስቡን ኑባሬንና ልቡናችንን ባላየነው አድማስ በርብረን እንድንገነዘብ ያደረገበት ሸጋ መድበል ነው፡፡ ይህ የፈጠራ ሥራ በኪነት ሚዛን የከያኒውን ክህሎት መስክረን፣ ያለ ንፍገት ሥሙን በደማቅ ቀለም እንድንጽፍ የሚገፋ ነው፡፡
***
ከአዘጋጁ፦መኮንን ደፍሮ ልብ ወለድ ጸሐፊ፣ ገጣሚ እና የሥነ ጽሑፍ ኀያሲ ነው፡፡ የባችለር እና የማስተርስ ድግሪውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በፍልስፍና አግኝቷል፡፡ በተማረው የሙያ መስክ በተለያዩ የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲዎች ፍልስፍና አስተምሯል፡፡ ጸሐፊው ወደ ፊት ለህትመት የሚበቁ የተለያዩ የልብ ወለድ፣ የኢ-ልብ ወለድ እና የግጥም ሥራዎችን አዘጋጅቷል፡፡


Sunday, 21 July 2024 00:00

ዝክረ - ነቢይ መኮንን

የእኛ ሰው በአሜሪካ



ከአዘጋጁ
አንጋፋው ገጣሚ ነቢይ መኮንን በአዲስ አድማስ ላይ ከፍተኛ ተወዳጅነትና ተነባቢነት ካስገኙለት ሥራዎቹ
መካከል “የእኛ ሰው በአሜሪካ” የተሰኘው ተከታታይ የጉዞ ማስታወሻው ተጠቃሽ ነው፡፡ ስለዚህም በዚህ ነቢይን
በምናስታውስበት “ዝክረ- ነቢይ መኮንን” አምድ ላይ ህዳር 4 ቀን 1997 ዓ.ም የወጣውን “የእኛ ሰው በአሜሪካ” ለዛሬ
በድጋሚ አቅርበነዋል፤ ሥራዎቹን ለማስታወስ፡፡



የዚህን ሳምንት የእኛ ሰው በአሜሪካ በማጠናቀር ላይ ሳለሁ አንድ የዘወትር አንባቢያችንና ወዳጃችን የሚከተለውን ግጥምና ማስታወሻ ላከልኝ፡፡ እነሆ፡-
Gone are the days of youth
Upon torture, imprisonment & death;
Blurred were your futures
Along with the reachable skies
All these mess in your twenties
Withstanding the hardships;
    Blocked were your Global trend
    Darkening the bright cloud
    Damn! The Ideological blade
    That made y’r wisdom unfinished;
Lost are the ‘Jolly Jacks’
Along with their ‘bell-bottoms’
Except some within the states;
    We are lucky having mirror
    Which reveals us the Global sphere;
Kindness, despite all these
Feeding knowledge for the freed ones
Tikimt 22/97- by Bahiru Jemal
Dear Nebiy,
I dedicate the untitled poem exclusively for you & y’r passed away campus & prison – mates and also for your colleagues (friends) who live abroad.
Dear Nebiy,
I was extremely & uniquely touched by your travel story series on Tikimt 20,97 That’s  why, I consider you as a mirror b/n your times & ours. But due to the holy month – Ramadan & some busy staff I was unable to contribute for so long. Any-way, I will keep in touch!
Wishing you all the best
ይሄ ወዳጃችን አብዛኛውን ጊዜ በእንግሊዝኛ መፃፍ ይቀናዋል፡፡ ግጥሙንም ማስታወሻውንም ከላይ እንዳያችሁት ነው የላከው፡፡ በግርድፉና በፍጥነት ለመተርጎም በመሞከር ለአንባቢያን እንደሚከተለው አቅርቤዋለሁ፡፡
    ገና በለጋ እድሜ አለፉ እኒያ ቀናት
በሥቃይ በግርፊያ፣ በእሥራትና ሞት፡፡
ነበር ጭጋጋማ - ደብዛዛ ነገአችሁ
ሰማይ ርቆ ላይርቅ እየኖረ አብሯችሁ፡፡
ለግላጋው እድሜያችሁ፤ ገና ሃያን ሳይዘል
ላያችሁ አለቀ ያ ሁሉ ምስቅልቅል!
አላንበረከከ፤ አልፈታችሁ ገና
አልበገራችሁም መከራና ጫና፡፡
    ብሩህ ሰማያችሁ ፊት-ገፁ ጨፍግጎ
ዓለም-አቀፍ ጉዞው እርምጃችሁ ታጥሮ
መንገዱ ተዘጋ፣ ዳመናው ታውሮ!!
ለአበባችሁ መርገፍ
ለጠቢባን ቅጭት - ለጥበብ መጨንገፍ
እኩዩ ምክንያት፤
ይረገም! ያ ሾተል፣
የአስተዋይ ሾተላይ፣ ያ የርዮት  ስለት፡፡
ይረገም!
    ወደቀ በጊዜው ከነወረት ስሙ
‘ጆሊጃክ’ አለፈ፣ ከ’ነቤል ቦተሙ’
ተረፈ-ጆሊጃክ በወሬ ሊነገር
አሜሪካ ሄዶ ከሰፈረው በቀር፡፡
ታድለናል ግና፣ እኛ አለን መስተዋት
ዓለምን የሚያሳይ፣ እኛኑ እሚከስት
ምን ቢከፋ አባዜው፣ መከራ እንግልቱ
አለ መስተዋቱ
ደግነት ያደለው፣ ካኖረው በወቅቱ
ያየውን የሚያሳይ በሩህሩነቱ
እውቀት የሚመግብ፣ ነፃ ለወጡቱ!!
ጥቅምት 22/97
እኔ፣ የፍሎሪዳው ወዳጄ እና ፍንዳታዋ ወንድሙ አንድ ሆቴል ተቀምጠን ከቢራው እየደጋገምን ሳለ እኛም እየሞቀን፣ ውይይታችንም እየሞቀው፣ እየደመቀ መጣ፡፡
“ለምን ኢትዮጵያ ውስጥ የግል ጋዜጣ የለም አልሽ፣ ፍንዳታ?” ብዬ ጠየቅኋት፡፡
“ያለ ስለማይመስለኝ፡፡ እኔ እዛ እያለሁ ጥቂት ናቸው ያነበብኳቸው፡፡ እነሱም በጣም ተራ ናቸው”
“‘ተራ’ ስትይ ምን ማለትሽ ነው?”
“በቃ ምንም የሚጥም ነገር አጣበታለሁ”
“ባንቺ ግምት ብቁ የሚመስልሽ ጋዜጣ ምን መምሰል አለበት?”
“ሙድ ያለው መሆን አለበት፡፡ ስልህ፣ አለ አይደል Ethics ነገሩን (ሥነ-ምግባሩን) የሚጠብቅ፣ ደሞ Professional የሆነ (ሙያዊ ብቃት ያለው) ደሞ Design (አጠቃላይ ቅርፀ-ተውህቦ) ያስፈልገዋል፡፡ ንገራቸው የምታውቃቸው ካሉ በእናትህ፡፡ በጣም ሙድ- ያለው Design ያድርጉበት…”
ወዳጄ ታላቅ ወንድሟ እንደገና ትእግስቱ አለቀ፡፡ “ምን ’ሙድ ያለው፣‘ ’ሙድ ያው‘ ትላለህ? በትክክል ወይ በአማርኛ ወይ በእንግሊዝኛ ተናገር፡፡ ዝም ብለህ መካከል ቤት እየዳከርክ አታደናግር”
ፍንዳታዋ አቋርጣው እንዳልሰማ ቀጠለች፡፡
“እዚህ አገር ያየሁዋቸው ጋዜጦች ሁሉ ብታያቸው ያላቸው ዲዛይን ነፍ ነው (በርካታ ነው) ማለቴ መዓት አይነት ዲዛይን ነው ያላቸው፡፡”
“ግንኮ ፍንዳታ፤… ሥነ ምግባርም፣ ሙያዊ ብቃትም፣ ቅርፃዊ ጥራትም በኢትዮጵያ ደረጃ ያላቸውም ያሉ ይመስለኛል፡፡ ግን እንዳልሺው ለብዙ ጊዜ ብዙ ጋዜጣ ካላነበብሽ እድገቱም፣ ጥራቱም፣ ደረጃውም በቀላሉ ሊታዩሽ አይችልም፡፡ አንቺ ብቻ አይደለሽም ብዙ ትላልቅ ሰዎች አጋጥመውኛል በአሜሪካ፡፡ አንድ ጊዜ የፈረጁትን ነገር እንደያዙ ያሉ ቁጥራቸው ቀላል አይደለም፡፡ They are stuck in time ለማለትም ይቻላል፡፡ (ያኔ ከሚያውቁት ጉዳይ ጋር ተቆራኝተው አሁንም እንደዚያው የሚያስቡ)
ለማንኛውም እሺ፤ ለማውቃቸው አዘጋጆች እነግርልሻለሁ፡፡ እስቲ ከዚህ ትንሽ ወጣ ያለ ጥያቄ ልጠይቅሽ?”
“fine!” (መልካም ቀጥል፤ ማለቷ ነው)
“ለመሆኑ እዚህ ከመጣሽ ለቤተሰብ ሳንቲም ልከሽ ታውቂያለሽ?”
“አዎን… ግን ተጠንቀቅ ነቢይ፣ ወንድም ጋሼ እንዳይቀየምህ?” አለች፣ ሽርደዳዊ ሳቅ  እየሳቀች፡፡
“ለምን ይቀየማል…”
ወንድም ጋሼ ጣልቃ ገባ በተራው፡፡
“ምን መሰለህ? ሁሌ እቺ ፍንዳታ ምን የምትለው ነገር አላት መሰለህ? ‘እነ ወንድም ጋሼ ይሄን ያህል አመት ኖረው የረባ ገንዘብ ሳይልኩ እኛ ‘ዲቪ’ዎቹ እናት አባታችንን በደምብ አድርገን Handle እናደርጋቸዋለን’ (እንንከባከባቸዋለን) እያለች ስትሞጣሞጥ አንድ ጊዜ ተጋጭቻት ነበር”
“ታዲያ እውነት አይደለም እንዴ?” አልኩት ነገሩን ለማስረገጥ፡፡
ይሄኔ ፍንዳታዋ ጣልቃ ገብታ፤
“እውነት ነው እንጂ -- Let me read you the fashionable poem about ‘Findata’. I don’t know the poet; ግን ሙድ ያለው ግጥም ነው፡፡ (ስለፍንዳታ የተገጠመ የአሁን ጊዜ ግጥም ላንብብላችሁ፡፡ ገጣሚውን አላውቅም) I have it here (ይቻትላችሁ) አለችና አንዲት የተጣጠፈች፣ ብዙ ጊዜ ያገለገለች የምትመስል ወረቅ አወጣችና ማንበብ ጀመረች፡-
ነባር - ነባሮቹ፣
“Oldie’s እና Senior” እየተባባሉ
አገረ-አሜሪካ አናስገባም አሉ፡፡
“እኔ በሱዳን ነኝ፣ እኔ በድንበር ነኝ
የዲቪ አደለሁም፣ ከነሱ አትደባልቁኝ”
እያሉ ቢኩራሩም፤
ወደ አገር ቤታቸው፣ ዱዲ ቤሳ አልላኩም፡፡
’ዲቪና ፍንዳታ‘ ተብሎ ሲታማ
’የማያድግ ጥጃ‘ ተብሎ ሲታማ
’ድክሞ ነገር ነው‘ ተብሎ ሲታማ
’ፖለቲካ አይገባው‘ ተብሎ ሲታማ
’አይማር አያድግ‘ ተብሎ ሲታማ
’ወጣት ዱሮ ቀረ‘ ተብሎ ሲታማ
አባቱን አሻረ የፈነዳውማ!!
ቤት ሰራ ለእናቱ ሳይሰርቅ ሳይቀማ፡፡
ሌት ተቀን ፈጋና በላብ በጉልበቱ
የዶላርን ምሥጢር አሳየ ለስንቱ”
ፈርማ የማይነበብ
መታሰቢያነቱ፡- ለተኛው አንጋፋና ዐይኑን ለገለጠው ፍንዳታ ቢሆን ብለን ሦስታችን ተስማማን፡፡
ፍንዳታዋ አንብባ ስትጨርስ እኔ አጨበጨብኩኝ፡፡ ፍንዳታዋ የቀኝ አውራ ጣቷን ቀስራ፤
“Thank you m-a-n!” አለች (አመሰግናለሁ ወዳጄ፤ እንደማለት)
ወዳጄ ፊት ላይ ግራ የመጋባት መንፈስ ነው የማነብበው፡፡ ምናልባት ፍንዳታዋ ያነበበችውን ግጥም በጥሞና አድምጬ ከማድነቅ ጀምሬ በማጨብጨቤም ጭምር ስለደገፍኩ ይሆን ግራ-ገብ መንፈስ የታየበት፡፡ በበኩሌ ፍንዳታ ሆና፣ የአሜሪካ ወግ ታክሎባት፣ ከኢትዮጵያ ባገኘችው የወረደ ነው በሚባለው የትምህርት ደረጃ መሰረቷ አንፃር፣ እንዲህ ለግጥም ስሜት ያዳበረች ወጣት ፍሎሪዳ ውስጥ ማግኘቴ፣ ልዩ ስሜት ነው የጫረብኝ፡፡ አንድ በጣም ግር ያለኝ ነገር ግን የፍንዳታዋ ታላቅ ወንድም ወዳጄ ግጥሙን ከእኔው እኩል እንደ አዲስ የሚሰማ መምሰሉ ነው፡፡ ይህንን ግርታዬን ላጠራ ወደ ወዳጄ ዞሬ፣
“ይህንን ግጥም ሰምተኸው አታውቅም ነበር ወይ?” አልኩት፡፡
“በጭራሽ” አለ ፍርጥም ብሎ፡፡
“ለምን?”
“አላነበበልኝማ!”
ፍንዳታዋ ለዚህ መልስ ይኖራታል በሚል ፊቴን ወደሷ መልሼ በጠያቂ አይን አፈጠጥኩባት፡፡
“Well, I haven’t had an opportunity like this” (እንዲህ ያለ አጋጣሚ አልነበረኝም)
“ምን ማለት ነው ይሄ?” አለ ታላቋ ትንሽ ረገብ ብሎ፡፡ ምናልባት በሆዱ ’መቼም ወንድም ጋሼ አይሰማኝም ብዬ ነው ማለቷ አይቀርም‘ ብሎ ሳይገምት አይቀርም፡፡
ፍንዳታዋ ቀጥላ፣
“You know Nebiy, till today, I also didn’t know ወንድም ጋሼ  appreciates poetry let alone write one!” (አየህ ነቢይ እኔም እስከዛሬ ድረስ ወንድም ጋሼ ግጥም መጻፍ ቀርቶ ማድነቁን አላውቅም ነበር፡፡)
“እንዴ ታላቅና ታናሽ ወንድምም ተጠፋፍታችኋላ? ታዋቂው ኢትዮጵያዊ ገጣሚና ፀሃፊ-ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን፣ በአንደኛው ቴያትሩ ላይ ’ከመርገምት ሁሉ የከፋው መርገምት፣ ቋንቋ ለቋንቋ መጠፋፋት‘ ይላል፡፡ እናንተ አብራችሁ እየኖራችሁ የተጠፋፋችሁበት ክፍተት አስገርሞኛል”
“እንግዲህ መገናኛችን አንተ ሆንክ ማለት ነው”
እኔም፤
“የፍንዳታዋ ነገር ያስገረመኝኮ ከምንጫወተው ጨዋታ ጋር በሚጣጣም መልኩ ግጥሙን በቦታው ማስገባቷ ነው፡፡ በጣም rare ነው (አንዳንዴ ብቻ የሚከሰት) እንደዚህ ጨዋታና ግጥም ግጥምጥም የሚልበት ሁኔታ፡፡ ሁኔታዎች ቢመቻቹላችሁ ሁለታችሁ የምትገናኙበት ቦታ አለ፡፡ ፍፁም የሆነ ውህደትም ባይሆን እንደልብ የሚያወራጭ ድንበርና የጋራ ሜዳ አላችሁ፡፡ አንተም የፓብሎ ኔሩዳን ግጥም ላክልኝ፡፡ አንቺ ደግሞ ይቺን ስለፍንዳታና ስለነባሩ የአሜሪካ ስደተኛ በተናፅሮ የተፃፈች ግጥም አመጣሺልኝ፡፡ ይሄ እንግዲህ የእናንተ የመንታዎቹ የግጥም ባላባሊቾዎች መገናኛ ነጥብ ነው፡፡ እኔ ደግሞ እንደ ሦስተኛ ቅርንጫፍ ብጨመር ብዬ የላክልኝን የፓብሎ ኔሩዳን ግጥም ተርጉሜ ይዤ መጥቻለሁ፡፡ ቆይተን እናነበዋለን”
“ኦ ምንም ቆይተን ምናምን ማለት የለም፣ ‘የሰው በልቶ አያድሩም ተኝቶ’ ነው፡፡ አሁኑኑ ታነብልናለህ፤ በቃ ታነብልናለህ” አለና አፋጠጠኝ፡፡
ፍንዳታዋም፤
“እኔም ከወንድም ጋሼ ጋር ነው አቋሜ - Read us, while the discussion is still fresh m-an” አለች፡፡ (ውይይቱ ገና ትኩስ እያለ አሁኑኑ ብታነብልን ነው እሚሻለው)
እቺ ፍንዳታ ብዙ ጊዜ ቆይተው እንግሊዝኛውን እንደሚያውገረግሩትና እንደሚያወላክፉት አበሾች አይነት አይደለችም፡፡ ጥሩ እንግሊዝኛ አቀነባበርና ፍሰት ያለው አድርጋ ማውራት ትችልበታለች፡፡ በጣም ነው የምትገርመው፡፡ ያው ሌላው ስደተኛ ፈሊጥ እንዳለው ሁሉ፣ ሴቶች ጸጉራቸውን ካንዱ ወገን ወደ ሌላው በአንገታቸው ጎተት እንደሚያደርጉት አይነት፣ እሷም በወንድ ኩራት፣ ሪቫኗን በጭንቅላቷ ንቅናቄ ካንዱ ወደሌላው ወንጨፍ እያደረገች- “ማን” (man) የሚለውን የእንግሊዝኛ ቃል ሚ-ያ-ን ብላ በቄንጥኛ ጎተት ታደርገዋለች እንጂ ጤና እንግሊዝኛ ትናገራለች፡፡
ወዳጄ በተጨማሪ ስለግጥም ንባቡ ማጠናከሪያ ሰጠ፡-
“በዛ ላይ ነቢይ አንተ ስታነበው ድምፅህ ውስጥ የሆነ ቃናና ለዛ አለው፡፡ ትዝ ይልሃል ዱሮ-‘ድምፁን እንዳልረሳው በናትህ ድገምልኝ‘ ስልህ፡፡ ’ድምፁን ነው እንጂ!‘ እልህ አልነበረም?”
ትንሽ አሽኮረመመኝ፡፡ አንዳንዴ አድናቆትን በፊት ለፊት መቀበል ባለመልመዳችን የተነሳ፣ ፊታችን ስማችን ሲነሳ አንዴ ጣራ አንዴ ምድር እያዩ መሽኮርመም ይቀናናል፡፡ በጣም የሚቸግር እንቅስቃሴ እንድናሳይ ያደርገናል- ያላለቀ ንድፍ ስዕል ያስመስለናል፡፡ ለዚህ ነው አበሻ ’እፊቱ ስለሆነ አይደለም!‘ ብሎ እሚጀምረው፡፡
አሜሪካ ግን እንደዛ አይደለም ያፋጥጣሉ፡፡
አነበብኩላቸው፡፡
ስጨርስ ፍንዳታዋ አጨበጨበች፡፡ ወዳጄም fantastic! (ድንቅ ነው) አለና፤
“ይገርማል የዱሮ ነገራችንን እንደገና ቀሰቀስክብኝ፡፡ እዚህ ከመጣሁ እንደዚህ አይነት ምሽት አምሽቼኮ አላውቅም ባባትህ!”
“ኦ እንዲያውም አንድ ነገር አስታወስከኝ፡፡ እኛ እዛ ሞተሃል እያልን ስናማህ እንዴት ተረፍክ? አልነገርከኝም’ኮ”
“ታሪኩ ረጅም ነው፡፡”
“ግዴለም ባጭሩ ንገረንና እኔም ብዙ ሳይመሽብኝ ወደ ሆቴሌ ልሂድ!”
“መልካም”

ታላቁን ሁለገብ ከያኒና የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረውን ነቢይ መኮንንን ለማክበርና ለማመስገን ታልሞ የተዘጋጀው፣ “ዝክረ ነቢይ መኮንን”፣ ባለፈው ሰኞ ሐምሌ 8 ቀን 2016 ዓ.ም ምሽት በዋቢሸበሌ ሆቴል፣ የኪነት አድናቂዎችና የጥበብ ቤተኞች ይገኙበታል በታደሙበት  በውበትና በድምቀት ተከናውኗል።
አዲስ አድማስ ባዘጋጀው በዚህ መርሃ ግብር ላይ ታዋቂ የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች፣ አንጋፋ ጋዜጠኞችና ደራስያን እንዲሁም የሥነ-ጽሁፍ ባለሙያዎች ስለነቢይ መኮንን የሚያውቁትን መስክረዋል- ገጠመኞቻቸውን አጋርተዋል።
አንጋፋው የማስታወቂያና ፊልም ባለሙያ አርቲስት ተስፋዬ ማሞ፣ መድረኩን በጥበባዊ ለዛ እያዋዛ የመራውና ያጋፈረው ሲሆን፤ እርሱም በወዳጅነት ለረዥም ዓመታት  ስለሚያውቀው ነቢይ መኮንን በየአፍታው ለታዳሚው አውግቷል- መድረኩንም በራሱ በነቢይ ግጥሞች አድምቆታል። ተስፋዬ ለምሽቱ ታዳምያን ካቀረባቸው ግጥሞች መካከል ነቢይ በ1997 ዓ.ም ወደ አማርኛ የተረጎመው የገጣሚ አንድሬ ቼዲድ ግጥም ይገኝበታል። “ይታያችሁ” ይላል ርዕሱ።
ይታይችሁ
ይታያችሁ እስቲ…  
ያ ሰፊ ውቅያኖስ፣ እንደ ፅጌ ደርቋል፤
እንደ አበባ ጠውልጓል።
የዛፉም ቅርንጫፍ ከችሮ በድኗል
የወፍ ማረፊያ እንኳን፣
መሆን አቅቶታል።
ይታይችሁ ግና፤
ከአድማስ ወዲያ ማዶ፤
ሞት ከስቶ ገርጥቶም
የሟችን ትንሳኤ፣
ዳግም ሲያለመልም!
 በዚህ “ዝክረ- ነቢይ” መርሃ ግብር ላይ ነቢይ መኮንን ብቻ አይደለም የተከበረውና የተዘከረው። ከዓመታት በፊት ህይወቱ ያለፈው ባለራዕዩና የአዲስ አድማስ ጠንሳሹ አሰፋ ጎሳዬም በትላልቅ ሃሳቦቹና እውን በሆኑ ሥራዎቹ፤ እንዲሁም በውብ ሰብዕናስ ተደጋግሞ ተነስቷል- ተወድሷልም። ነቢይን ሲያነሱ አሰፋ ጎሳዬን አለማንሳት አይቻልም። ሁለቱም የአዲስ አድማስን እንቁዎች ነበሩ። ነቢይን፣ አሰፋን፣ አዲስ አድማስን ብዙዎች በአንድ ላይ ነው የሚያውቋቸው።
ለዚህም ነው ስለነቢይ ለመናገር መድረክ ላይ የወጣው አንጋፋው ደራሲና ጋዜጠኛ ዘነበ ወላ፣ መግቢያው ላይ በስፋት ስለ አሰፋ ጎሳዬ ያወሳው ትዝታዎቹን ያነሳው። በቅጡ ተዘጋጅቶ የመጣበት ጉዳይ በመሆኑ ግን ወደ ነቢይ በቀላሉ ለመሸጋገር አልከበደውም። እናም እርሱ የሚያውቀውን ነቢይ መኮንን ለታዳሚው አስተዋውቋል”… ነቢይ በጣም ሰው ይወዳል፣ የተማረ ነው፣ መሃይም ነው ሳይል አጠገቡ ካለው ጋር ያወራል፣ ይጫወታል፣ የምታስቡትን ይጋራል። ይሄ የአንድ ትልቅ ደራሲ ባህርይ ነው። … ነቢይ ሲተርክልህ ጥሩ የማድመጥ ብቃት ያስፈልግሃል… ከፍተኛ ኢነርጂ ከሌለህ… ወራጅ ነው የምትሆነው…. ይበዛብሃል…. ይጠልቅብሃል…. የመገንዘብ አቅምህ እዚያ ጋ ካልደረሰ፣ ትፋታለህና ጥሩ አድማጭ መሆን ይፈልጋል…” ብሏል።
ዘነበ ወላ፤ ነቢይ በደርግ ዘመን  ያሰቃዩትና የገረፉት እንዲሁም በወህኒ ቤት ዓመት በእስር ያጉሩት ባለስልጣናት ላይ ቂም እንዳልያዘና አንዳንዶቹን ሲያገኛቸውም እንደሚወራቸው በመግለፅ፤ “ነቢይ በጣም ይቅር ባይና ሆደ-ሰፊ ነው” ሲል አድናቆትን ቸሮታል። እውነቱን ነው። ዘነበ ጥሩ አስተውሏል። ነቢይ እንኳን የደርግ ሹመኞችንና ገራፊዎችን ቀርቶ ራሱን ሥርዓቱን- ደርግን ሲረግምና ሲያወግዝ ተሰምቶ አይታወቅም። ነቢይ ማለት በአጭሩ በየሳምንቱ በአዲስ አድማስ ላይ ሲጽፋቸው የኖራቸው ርዕሰ አንቀጻት ማለት ነው። (ከዚህ የተለየ ነቢይ እኔ በበኩሌ አላውቅም) ፅንፈኝነትና ጨለምተኝነት አያውቀውም። እርግማንና ውግዘት ውስጥ የለበትም።
ሁሌም ብሩህና ተስፈኛ ነው- ነቢይ መኮንን። ግጥሞቹም በአብዛኛው የሚያንፀባርቁት ብሩህ ተስፈኝነትን ነው።
ወደ ዝክረ-ነቢይ መኮንን እንመለስ። ሌላው በመርሃ ግብሩ ላይ ምስክርነቱን የሰጠው ደግሞ የአሃዱ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ስራ አስኪያጅ የሆነው አንጋፋው ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ ነበር። በነገራችን ላይ ጥበቡ ዘንድ ደውዬ በዝግጅቱ ላይ ስለነቢይ እንዲናገር ስጠይቀው የሰጠኝ መልስ፡- “እርሱ በተጠራበት ሁሉ ሲሄድ አይደል እንዴ የኖረው፤ ኧረ እመጣለሁ፤ ይኼ የሁላችንም ሃላፊነት ነው።” የሚል ርዕስ ነበር።  ጋዜጠኛ ጥበቡ ነቢይን በሁለት መልኩ  ነው አንስቶ ያስታወሰው፣ ያከበረው፣ ዘከረው። አንደኛው ከጥቂት ዓመታት በፊት የሆነ ነው። ሰዓሊና ገጣሚ ገብረክርስቶስ ደስታ ላይ ከህልፈቱ በፊት በተናዘዘው መሰረት፣ ስዕሎቹን ከጀርመን ሙኒክ ወደ አዲስ አበባ የማስመጣት ፕሮጀክት  ተቀርጾ ነበር።
ስዕሎቹን ለማስመጣት ሎቢ ይደረግ ነበርና ለዚያ ዝግጅት ተካሂዶ ነበር። ታዲያ የዝግጅቱ ጥሪ ላይ የሚለው “ገጣሚና ሰዓሊ ገብረክርስቶስ ደስታ” ነበር። ይኼኔ ሰዓሊያኑ እነ በቀለ መኮንንና እነ እሸቱ  ጥሩነህ ለገብረክርስቶስ መቅደም ያለበት ሰዓሊነቱ ነው በሚል “ሰዓሊና ገጣሚ” መባል አለበት ብለው መከራከራቸውን ያስታውሳል፣ ጋዜጠኛ ጥበቡ። በዚህ የተነሳ ቤቱ ለሁለት ተከፈለ፣  “ገጣሚነቱ ነው የሚቀድመው ወይስ ሰዓሊነቱ” በሚል። በዚህ  መሃል አሁን በህይወት የሌለውና በሥነ-ግጥም  ላይ ከፍተኛ ጥናትና ምርምር ያደረገው የሥነ-ፅሁፍ ባለሙያው ብርሃኑ ገበየሁ፤ “እንደውም ገብሬ ሙዚቀኛ ነው፣ ዘፋኝ ነው” ብሎ ግጥሞቹን በዜማ ማቅረብ ጀመረ። ከዚያ ደግሞ ነቢይ መኮንን የተለየ ሃሳብ ማቅረቡን ይገልፃል- ጥበቡ።
“እናንተ ገጣሚም በሉት ሰዓሊም በሉት ሙዚቀኛም በሉት… ገብረክርስቶስ ደስታ ግን የሳይንስ ሰው ነው” ብሎ ስዕሎቹን ከሳይንስ አንፃር ተነተናቸው። ለምሳሌ፡- ቀራኒዮ… የኢየሱስን ስቅለት በደም ብቻ የሳለውን…በማንሳት ሳይንስ ነው፤ የባዮሎጂ ባግራውንድ ስላለውነው…አለ። ባዮሎጂ ስለተማረ የኢየሱስ ክርስቶስን ስዕል በደሙ ነው የሳለው… ብሎ በማስረጃነት አቀረበ። ከዚያ ደግሞ የባህር ቅርድዶች  የሚለው ግጥም… አንድ ድንጋይ አንስተን የሆነ ባህር… ወይም ውሃ ላይ ስንወረውር… እንደዚህ የሚሄዱ ሞገዶች አሉ…. ስለነሱ የገጠመው… የሳይንስ ሰው መሆኑን ነው የሚሳየው… በሚል ግጥሞቹን…. ስዕሎቹን ከሳይንስ አንፃር በደንብ ተነተናቸው…. ሲል አውግቷል። ይኼም ራሱ ነቢይ የኬምስትሪ ተማሪ፣ ኬሚስት ስለነበር… ሁለቱ…. ነቢይና  ገብረክርስቶስ በጣም የሚያይዝ የራሳቸው ባክግራውንድ… ከሳይንስ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ያሳየበት ነውና… በዚያ ዝግጅት የገብረክርስቶስ  ስዕሎች ወደ አገር ቤት እንዲመጡ በጣም ትልቅ አስተዋፅኦ ካደረጉ……. (እነ በቀለ መኮንን ጨምሮ) አንዱ መሆኑን በማውሳት፣ ብዙም የማይታወቀውን የነቢይን አበርክቶ አጉልቶ አሳይቷል- ጥበቡ- በለጠ።
ጋዜጠኛ ጥበቡ በዚህ ብቻ አላበቃም። ነቢይን ከአዲስ አድማስ  ዋና አዘጋጅነቱ አንፃርም ያበረከተውን አስተዋፅኦ አፅንኦት ሰጥቶ አንስቶታል። ጥበቡም እንደ ዘነበ ሁሉ ታዲያ፣ አሰፋ ጎሳዬን ከአዲስ አድማስና ከአጠቃላይ የጋዜጠኞች ህትመት ጋር አያይዞ አውስቶታል- አወድሶታል። አስገራሚው ግጥምጥሞች ሁለቱ የአዲስ አድማስ እንቁዎች በዚህች ምሽት በአንድ ላይ መዘከር መወደሳቸው  ነው።  በዕቅድ ሳይሆን በአጋጣሚ፤ በአዘጋጆቹ ፍላጎት ሳይሆን በተናጋሪዎቹ የልቦና ፈቃድ! ግሩም ነው በዝክረ- ነቢይ መርሃ ግብር ስለነቢይ የተናገሩትና የመሰከሩት ሁለቱ ብቻ አልነበሩም። ሰዓሊና ቀራፂ በቀለ መኮንን፣ የሥነ-ፅሁፍ ባለሙያው ባዩልኝ አያሌው።
ሻምበል አፈወርቅ ዮሐንስ ልጅ- ዮሐንስ አፈወርቅ፣ የፊዚክስ ፕሮፌሰሩና የነቢይ ወዳጅ ዶ/ር ሙሉጌታ…፣ አንጋፋው ደራሲና ሃያሲ አለማየሁ ገላጋይ… ገጣሚ ነቢይን  ከታዳሚዎቹ ጋር በህብረት ዕፁብ ድንቅ ነው። የነቢይ ነፍስ በሃሴት ጮቤ ትረግጣለች ብዬ አምናለሁ የአሰፋም ጭምር።

የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የሥራ ሃላፊዎች በሙስናና በሃብት ምዝበራ ተጠርጥረው  በቁጥጥር ስር ዋሉ።
በቁጥጥር ስር ከዋሉት  ሃላፊዎች መካከል የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሀብታሙ አበበ እና ምክትል ፕሬዚዳንቱ ዶ/ር ታምራት ታገሰ  ይገኙበታል።

የዋቸሞ ዩኒቨርስቲ ለአንድ የዩኒቨርስቲው የፋይናንስ ቡድን መሪ የ790 ቀናት አበል እንዲሁም ለሌላኛው የፋይናንስ የቡድን መሪ ደግሞ በስድስት ወራት ውስጥ ብቻ የ1,469 ቀናት (1,056,854 ብር) አበል እንደተከፈላቸው ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በዩኒቨርሲቲው የሀብት ምዝበራ ላይ አተኩሮ በሰራው  የምርመራ ዘጋቢ ፊልም ላይ  ማቅረቡ ይታወሳል።

 በተጨማሪም  የዩኒቨርስቲው ፋይናንስ ሳያውቅ 1.4 ቢሊዮን ብር ለኦክስጅን ማምረቻ በሚል በህገወጥ መንገድ መንቀሳቀሱንና ፍቃድ የሌለው የኮንስትራክሽን ድርጅት ግንባታውን እንዲሰራ ያለ ጨረታ እንደተሰጠው በምርመራ ውጤቱ ተገልጿል። በዚህ የተነሳ ዛሬ አመራሮቹ በቁጥጥር ሥር ውለዋል::

ኬሮድ የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር ለአራተኛ ጊዜ በትናንትናው ዕለት በወልቂጤ ከተማ ተካሂዷል። የ15 ኪሎሜትር የሩጫ ውድድርን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች ስፖርታዊ ፍልሚያዎች ተደርገዋል።

የባሕል እና ስፖርት ሚኒሰቴር የስፖርት ሚኒስትር ደኤታ አምባሳደር መስፍን ቸርነት፣ አትሌት ሰለሞን ባረጋ፣ እንዲሁም ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች በውድድሩ ላይ ተገኝተዋል። መነሻውን ከወልቂጤ ዩኒቨርስቲ ባደረገው ውድድር ብርቱ ፍልሚያ እንደታየበት ለማወቅ ተችሏል።

ሚኒስትር ደኤታው አምባሳደር መስፍን ቸርነት "እንደኬሮድ መሰል የሩጫ ውድድሮች ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው። በዚህ ውድድር ያሸነፋችሁ እና የተወዳደራችሁ አትሌቶች ጠንክራችሁ ቀጥሉ። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ምስጢሩ ሕብረ ብሔራዊ አትሌቶችን ማግኘቱ ነው። በሁሉም አቅጣጫ እንደእነዚህ ዓይነት ውድድሮች መካሄድ ይኖርባቸዋል።" በማለት ተናግረዋል። አያይዘውም ለኬሮድ የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር አዘጋጆች ምስጋናቸውን ገልጸዋል።

የኬሮድ የስፖርት እና የልማት ማሕበር ቦርድ ሰብሳቢ አትሌት ተሰማ አብሽሮ የወልቂጤ ከተማ ነዋሪዎች እና ተወዳዳሪ አትሌቶች በውድድሩ በማሳተፋቸው ምስጋናውን ገልፆ፤ "ኬሮድ ሩጫ በቡታጅራ፣ ወራቤ እና ሆሳዕና በተለያዩ ክልሎች ላይ ውድድሩን ለማዘጋጀት ዕቅድ አለው። የኬሮድ ዓላማ ሰላምን መስበክ ነው። ሕብረተሰቡ ሊደግፈን ይገባል።" ሲል ተናግሯል። የፓሪስ ኦሎምፒክ ተሳታፊ ለሆኑ አትሌቶች መልካም ምኞቱን አስተላልፏል።

በአንድ ኪሎሜትር የዊልቸር ውድድር በሴቶች፤ አንደኛ አብነት ጌትነት የወርቅ ሜዳልያ እና 5 ሺህ ብር፣ ሁለተኛ እምነት ከበደ የብር እና 3 ሺህ ብር፣ ሶስተኛ ሰዓዳ አብደላ የነሐስ ሜዳልያ እና 2 ሺህ ብር ተሸላሚዎች ሆነዋል። በወንዶች ውድድር ደግሞ፣ አንደኛ አቡበክር ጀማል የወርቅ ሜዳልያ እና 5 ሺህ ብር፤ ሁለተኛ ዳዊት ዮሴፍ የብር ሜዳልያ እና የ3 ሺህ ብር እና ሶስተኛ ዳንኤል ዲባባ የነሐስ ሜዳልያ እና የ2 ሺህ ብር ሽልማት ተሸላሚዎች መሆናቸው ታውቀዋል።

በ15 ኪሎሜትር የሴቶች ሩጫ ውድድር አንደኛ መብርሂት ግደይ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የወርቅ ሜዳልያ እና የ100 ሺህ ብር፤ ሁለተኛ መቅደስ ሽመልስ በግል የብር ሜዳልያ እና የ50 ሺህ ብር እና ሶስተኛ ኑኖ ሻንቆ ከኦሮሚያ ፖሊስ የነሐስ ሜዳልያ እና የ25 ሺህ ብር ተሸላሚዎች ለመሆን በቅተዋል። በወንዶች ደግሞ፣ አንደኛ ጨምዴሳ ደበላ በግል የወርቅ ሜዳልያ እና የ100 ሺህ ብር፤ ሁለተኛ ዘነበ አየለ ከዘቢዳር አትሌቲክስ ክለብ የብር ሜዳልያ እና 50 ሺህ ብር እና ሶስተኛ ጂግሳ ታደሰ በግል የነሐስ ሜዳልያ እና 25 ሺህ ብር ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።

እንዲሁም አሸናፊ አትሌቶች ለወከሏቸው የስፖርት ክለቦች የዋንጫ ሽልማት ከውድድሩ የክብር ዕንግዶች እጅ ተቀብለዋል።

"ለኢትዮጵያ ሰላም እሮጣለሁ" በሚለው የዘንድሮው የኬሮድ የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር በተጨማሪነት የሕዝባዊ ሩጫ ውድድር እንደተካሄደና ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ ደረጃ ለወጡ ተሳታፊዎች ሜዳልያ እንደተሰጣቸው ለማወቅ ተችሏል።

Saturday, 20 July 2024 21:24

18091 ፕሮጀክቶች - በዓመት!

• አዲስ አበባ ፈካ፣ ጸዳ፣ ነቃ ነቃ ያለችበት ዓመት ነው 2016።
• ከተማዋ ቀንና ሌሊት በሥራ የተጠመደችበት ዓመትም ነው


በጥበብ ካልተጉ 18091 ሺ ፕሮጀክቶችን መሥራትና አሳምረው ለውጤት ማድረስ፣ ጀምረው መጨረስ አይችሉም።
ዓመቱን ሙሉ በብርቱ ተምረው ከሠሩ ነው የፈተና ውጤት የሚያምረው፤ የወደፊት ተስፋ የሚፈካው፤ መንፈስ የሚነቃቃው። እንቁጣጣሹም ከተማውም የሚደምቀው።
የሌሎች አድናቂና የዳር ተመልካች ሆነን የምንቀርበት ምክንያት የለም የሚል የእልህ ስሜት ውስጣችን ሲያነሣሣ፣ በዚህም ሌት ተቀን ስንሠራ፣ በሙያ ፍቅርና በብርቱ መንፈስ ስንጥር ነው፣ ኑሮም አገርም በበጎ የሚቀየረው።
ደግሞም መልካም የሥራ ውጤት ሲያዩ የብዙዎች መንፈስ እየተነቃቃ ስሜታቸውንም እንደሚገልጹና ለሥራ እንደሚነሣሡ፣ የፒያሣ-አራት ኪሎ የኮሪደር ልማት የተመረቀ ጊዜ አይተናል። ይሄው በጎ መንፈስ በሌሎቹ የኮሪደር ልማት የምረቃ አጋጣሚዎችም ተመሳሳይ በጎ መንፈስ እየተደጋገመ ሲደምቅ ተመልክተናል።
ከተረጂነትና ከውርደት መላቀቅ ብቻ ሳይሆን፣ ለኢትዮጵያ አኩሪ ታሪክ የሚመጥን አዲስ ተጨማሪ ታሪክ የማይፈጠርበት ምክንያት የለም። ወደ ዕድገትና ወደ ብልጽግና በመገሥገሥም አዲስ አበባ የሥራ መዲና፣ ኢትዮጵያ የስኬት ምሳሌ ተብለው እንዲጠቀሱ ማድረግም ይቻላል። እንደሚቻል ብቻ ሳይሆን፣ እውን እንደሚሆን ከንቲባዋ ሲገልጹ… ሌላ ምሥጢር የለውም፤ ሠርተን አገራችንን እንለውጣለን በማለት እንደተናገሩ እናስታውሳለን።
ዘንድሮ የተሠሩና የተጠናቀቁ ፕሮጀክቶችም የዚህ ግሥጋሤ ጅምርና ምስክር ናቸው ማለት ይቻላል።
አንዳንዶቹ ፕሮጀክቶች በአካልና በግላጭ ደምቀው የሚታዩ ሥራዎች ናቸው። ከቅርብም ከሩቅም በርካታ ሺህ የከማዋ ነዋሪዎች ከየአካባቢያቸው እየመጡ የዐድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየምን ጎብኝተዋል። በኮሪደር ልማት የተስፋፉና የተሻሻሉ መንገዶችን፣ አምረው የተሠሩ የእግረኛና የብስክሌት መስመሮችን፣ በዛፎችና በመብራቶች ደምቀው የተዋቡ አካባቢዎችን እየተዘዋወሩ አይተዋል። ዘና ለማለት ልጆቻቸውን ይዘው ጎራ ማለት ሲያዘወትሩም ታዝባችሁ ይሆናል። “የከተማዋን የፕሮጀክቶች አፈጻጸም ሪፖርት በአካል እንደመመልከት” ልትቆጥሩት ትችላላችሁ።
በእርግጥ ሁሉንም ፕሮጀክት ሁሉንም የሥራ ውጤት እየዞርን የመጎብኘትና የመመልከት ዕድል ይኖረናል ማለት አይደለም። ግን ችግር የለውም። ከንቲባ አዳነች አቤቤና የቢሮ ኀላፊዎች ሰሞኑን ለከተማዋ ምክር ቤት ያቀረቡትን ዓመታዊ የሥራ ሪፖርት ዐጠር ዐጠር አድርገን መቃኘት እንችላለን።
ዓድዋ የጥቁር ህዝቦች ድል
ከግንባታው ግዙፍነትና ፍጥነት ጋር፣ በውበቱና በታሪካዊነቱ የተደነቅንበትና የኮራንበት የዓድዋ ድል መታሠቢያ ሙዚየም፣ የዓመቱ ማሳያ ዓርማ ነው። ግንባታው ሲጠናቀቅና ሲመረቅ ታስታውሳላችሁ። ድንቅ ነው።
በማግሥቱ ውስጣችንን ዙሪያችንን ስንመለከት ግን… በደስታና በምስጋና ንግግሮች ፋንታ፣ እልፍ ጥያቄዎች እየተደራረቡ ይመጣሉ። “ታዲያ ሌሎች እልፍ ፕሮጀክቶችስ ለምን በፍጥነትና በጥራት ማጠናቀቅ አይቻልም?” የሚሉ ሐሳቦች በሚሊዮኖች አእምሮ ውስጥ ይፈጠራሉ።
ታሪካዊው ሕንጻ ተገንብቶ በእውን ሲመረቅ በማየታችን የደስታና የእርካታ መንፈስ ባይርቀንም እንኳ… በቦታው የእልህ ስሜቶች እየተወለዱ፣ “ሌት ተቀን በመትጋት፣ ተጨማሪ ታሪክ መሥራት”… እያሉ ይወተውቱናል።
ከዚያ ወዲህ ብዙ ሥራዎች ሲፋጠኑና ሲጠናቀቁ ብናይ ታዲያ ምን ይገርማል?
የዐድዋ ድል መታሰቢያ ግንባታ ብዙ ልምድ አግኝተንበታል በማለት በዓመታዊ ሪፖርት የተናገሩት ከንቲባ አዳነች አቤቤ፣ የፕሮጀክት ክትትልና አመራር ልምድ አግኝተንበታል። የኮሪደር ልማት በፍጥነት ተግባራዊ እንዲሆን ጠቅሞናል ብለዋል።
የኮሪደር ልማትም በተራው፣ የከተማዋን የኢኮኖሚና የሥራ ከማፋጠን፣ ለኑሮ ጽዱና የተዋበ አካባቢ ከመፍጠር በተጨማሪ በርካታ ትሩፋቶችን ይዞ እንደመጣ ከንቲባዋ በሪፖርታቸው ጠቅሰዋል።
ግንባታዎችን በጥራት የመምራት “ዲሲፕሊንና” በፍጥነት ለውጤት የማብቃት ተጨማሪ ልምድ አግኝተናል።
የሥራ ባህል ለማሳደግ ችለናል ብለዋል - ከንቲባዋ።
በሕዝባችን ዘንድ የልማት ፍላጎት እየጨመረ መጥቷል። ሌሎች የከተማዋ ነዋሪዎች ልማቱ ወደ አካባቢያቸው እንዲመጣ ጥያቄ እያቀረቡ ነው ሲሉ ከንቲባዋ ተናግረዋል።
በእርግጥም ደግሞ የኮሪደር ልማት በሌሎች አካባቢዎችም እንደሚቀጥል ከንቲባዋ ሲገልጹ፣ ጥናት የተካሄደባቸውና ለሥራ የተዘጋጁ ፕሮጀክቶች እንዳሉ ጠቅሰዋል።
በሌላ አነጋገር፣ 2016 ዓ.ም. እልፍ የፕሮጀክቶች ስኬት የተመዘገበበት ዓመት ሆኗል። ይህም በሪፖርት እየተዘረዘረ ቀርቧል። ነገር ግን፣ በዚህ ብቻ ረክቶ መቀመጥ የለም። እንዲያውም ለሚቀጥለው ዓመት አስበልጦ ለመሥራት መነሻና መንደርደሪያ ብርታት እንደሚሆን ከንቲባዋ ጠቁመዋል።  “የአዲስ አበባ ልማት ሁሉንም ማኅበረሰብ ያቀፈና ማንንም ወደኋላ ያልተወ ነው” ብለዋል።
እንግዲህ የመጪውን ዓመት ለመገመት የዘንድሮውን ማየት ነው።

በመንግሥትና በበጎ አድራጎት ሥራ  ከ18091 ሺህ በላይ ፕሮጀክቶች የተጠናቀቁበት ዓመት
በፍጥነት እየተጠናቀቁ ለአገልግሎት ከበቁት ግንባታዎች መካከል አንዳንዶቹ “ሜጋ ፕሮጀክቶች” ተብለው የሚጠቀሱ ናቸው።
የዓደዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም
ለነገዋ የሴቶች ተሃድሶ እና ክህሎት ማበልፀጊያ ማዕከል
ቃሊቲ - ቱሉዲምቱ - ቂሊንጦ መንገድ ተሻጋሪ ድልድዮች
3 ግዙፍ የገበያ ማዕከላት
የጉለሌ የተቀናጀ ልማት
የፒያሣ አራት ኪሎ፣ የሜክሲኮ ሳር ቤት የመሳሰሉ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች
እስቲ ከእነዚህ መካከል አንዳንዶችን ለማየት ሌሎችንም አለፍ አለፍ እያልን ለመጥቀስ እንሞክር።

’’ለነገዋ ’’10 ሺ ሴቶችን እየተቀበለ ሥልጠና የሚሰጥ ማዕከል
የተሻለ  ይገባታል
የሴቶች ተሃድሶ እና የክህሎት ማበልጸጊያ ማዕከል ተገንብቶ ሥልጠናዎችን መስጠት ጀምሯል። ዕምቅ ዐቅማቸውን እንዲጠቀሙ፣ ሕይወታቸውን እንዲመሩ፣ ኑሯቸውን እንዲያሻሽሉ፣ ችግር ሳይበግራቸው እንዲያንሰራሩ፣ ከራሳቸውም አልፈው ለሌላ እንዲተርፉ ነው የሥልጠናዎቹ ፋይዳ።
የማዕከሉ ትልቅነት ከዩኒቨርስቲ አይተናነስም። በአንድ ጊዜ 10ሺ ሴቶችን ተቀብሎ ሥልጠና የመስጠት ዐቅም አለው። ግን ከዚያም በላይ ነው። ጠለላና ከለላ ይሆናል። ማደሪያ ክፍሎች ተሟልተውለታል። ለልብስና ለምግብ አይቸገሩም። የሴቶች ህልምና  ራዕይ፣ መተማመኛና አለኝታ፣ ሥንቅና ተስፋ ነው ማለት ይቻላል።
“ቀዳማይ ልጅነት
(የሕፃናት ማቆያ እንክብካቤና ትምህርት)
 አዲስ አበባ ህጻናት የሚያድጉባት ምቹ ከተማ
“የቀዳማይ ልጅነት” በሚል ስያሜ የተጀመሩት ፕሮጀክቶች፣ ዋና ዓላማቸው የሕፃናትን የአእምሮና የአካል ዕድገት ላይ ያተኮረ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ግን፣ በመቶ ሺ ለሚቆጠሩ ቤተሰቦችና ወላጆች ትልቅ ድጋፍ ይሆንላቸዋል። ልጆችን ለጎረቤቶች አደራ እየሰጡ፣ ከአክስትና ከአያት ጋር እንዲውል እየወሰዱ፣ ወደ መደበኛ ሥራ መሄድ በዛሬ ዘመን አይቻልም። ብዙ እናቶች ልጆችን ማሳደግ ማለት፣ በመደበኛ ሥራ ጋር መለያየትና ቤት ውስጥ መዋል ማለት ይሆንባቸዋል።
“የቀዳማይ ልጅነት” በሚል ስያሜ እየተስፋፉ ያሉ የሕፃናት ማቆያ አገልግሎቶች፣ ለልጆች ዕድገት ብቻ ሳይሆን ለሴቶች ትልቅ ትርጉም አላቸው። ሕፃናት  በተለይ እናቶች በየተሰማሩበት የሙያና የሥራ መስክ ላይ የዕድገት ጉዟቸው እንዳይስተጓጎል ጥሩ ዕድል ያገኙበታል።
አዲስ አበባ “ሕፃናትን ለማሳደግ ምርጧ አፍሪካዊት ከተማ” ትሆናለች ብለን እየሠራን ነው። ከ320ሺ ገደማ ሕፃናት “የቀዳማይ ልጅነት ትምህርትና እንክብካቤ” እንዲያገኙ ክትትልና ድጋፍ ተደርጓል ብለዋል - ከንቲባዋ።
ለዚህም ነው ከ3680 በላይ የመዋዕለ ሕፃናት መምህራን ሠልጥነው ወደ ሥራ የተሰማሩት።
5200 የሕፃናትንና የእናቶችን ጤንነት እንዲሁም የልጆችን ዕድገት ቤት ለቤት እየተከታተሉ ምክር የሚሰጡ ባለሙያዎችም ተመርቀው ሥራ ጀምረዋል።
10800 ነብሰ ጡር እናቶች እና ሕፃናት የአልሚ ምግብ ድጋፍ አግኝተዋል።
ዋናው ጤና - የትልልቅ ሆስፒታሎች ግንባታ!
ከ2.6 ሚሊዮን በላይ ነዋሪዎች በጤና ተቋማት አገልግሎት እንደተስተናገዱና አገልግሎት እንዳገኙ ዓመታዊው ሪፖርት ይገልጻል። ብዙዎቹ ተመላላሽ ታካሚዎች ናቸው። በየጊዜው እየተስተናገዱ ሕክምናቸውን ይከታተላሉ፤ የጤና አገልግሎት ያገኛሉ። ለተመላላሽ ታካሚዎች የተሰጡ የአገልግሎት መስተንግዶዎች በአጠቃላይ ከ13 ሚሊየን ይበልጣሉ።
ከ190 ሺህ በላይ እናቶች የቅድመ ወሊድ ክትትል የጤና አገልግሎች እንዳገኙና በጤና ተቋማት የሚወልዱ እናቶች እንደጨመረ ገልጸው፣ በዚህም ምክንያቶ የእናቶች ሞት እንደቀነሰ ተናግረዋል።
የጤና ተቋማት የወሊድ አገልግሎት በመስፋፋቱ፣ ከመቶ ሺህ ወሊዶች ውስጥ በእናቶች ላይ የሚያጋጥመው የሞት አደጋ ከ34 በታች ሆኗል። ለታዳጊ አገራት በዓለም ጤና ድርጅት የወጣውን መስፈርትና በአገራዊ ራዕይ የተዘጋጀውን ግብ ለማሳካት ተችሏል። ግን በዚህ አያበቃም። የእናቶች ጤንነትና ደህንነት ይበልጥ እየተሻሻለ እንደሚሄድ አያጠራጥርም።
የሆስፒታሎችና የጤና ጣቢያዎች አገልግሎት እየተስፋፋ ቁጥራቸውም እየጨመረ ነው። የዘውዲቱ መታሰቢያና የጥሩነሽ ቤጂንግ ሆስፒታሎች፣ እንዲሁም የራስ ደስታ ዳምጠውና የዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታሎች ነባር ዐቅማቸውና አገልግሎታቸው እንዲስፋፋ፣ ተጨማሪ ሕንጻዎች እየተሠሩ ነው፤ የሙያ መሣሪያዎች እየተሟሉ ነው። የሕንጻዎቹ ግንባታ ከ50 በመቶ አልፏል።
ሦስት አዳዲስ ጤና ጣቢያዎች በአዲሱ ዓመት አገልግሎት እንዲጀምሩ እየተዘጋጁ ነው።
ሁለት ትልልቅ ሆስፒታሎችም እየተገነቡ ግማሽ ላይ ደርሰዋል። በሚቀጥለው ዓመት አገልግሎት ለመስጠት ይበቃሉ ብለዋል የጤና ቢሮ ኀላፊ ዶ/ር ዮሐንስ።
በኮልፌ ቀራኒዮ የተጀመረው የዘመናዊ ሆስፒታል ግንባታ 68% እንደደረሰ የገለጹት የከተማዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፣ ሆስፒታሉ 520 በላይ ክፍሎችና 423 አልጋዎች እንደሚኖሩት ተናግረዋል።
ንፋስ ስልክ ላፍቶ ሆስፒታልም ከትልልቆቹ መካከል የሚመደብ ነው። ግንባታ ወደ ስድሳ በመቶ ደርሷል። 520 ክፍሎችና 370 አልጋዎች ይኖሩታል ብለዋል - ከንቲባዋ።
ትውልድን መገንባት - የተማሪዎች ውጤት ዘንድሮ ተሻሽሏል።
የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ቁጥር ዘንድሮ ከ626 ሺህ በላይ፣ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ቁጥር ከ232 ሺህ በላይ ማድረስ ችለናል ብለዋል - ከንቲባዋ።
“የመዋዕለ ሕፃናት” ትምህርት ሲታከልበት፣ የተማሪዎች ቁጥር ከ1 ሚሊዮን 175 ሺህ በላይ ሆኗል።
ከበጎ አድራጎት የገንዘብ፣ የዐይነትና የሙያ ድጋፎችን ለማሰባሰብ በተደረገው ጥረት 6.4 ቢሊዮን ብር ተገኝቷል። ይህም ተማሪዎችን ለማገዝ ጠቅሟል። በተማሪዎች ምገባ 780 ሺህ በላይ ተማሪዎች በቀን ሁለት ጊዜ መመገብ ችለዋል። የተማሪዎች የደንብ ልብስ፣ የትምህርት ቁሳቁስና የመምህራን የሥራ ልብስ ተሟልቶ እንደቀረበም ተገልጿል። ደብተር፣ ስክርቢቶ፣ የትምህርት ቤት ልብስ ለልጆች ማሟላት የስንትና ስንት ቤተሰብ ራስ ምታት እንደነበረ ማን ሊረሳው ይችላል? ወላጆች ይመሰክራሉ።
በእርግጥ መጻሕፍት አቅርቦትም ወጪው ቀላል እንዳልሆነ የከተማዋ የትምህርት ቢሮ ኀላፊ ተናግረዋል። እንደ አዲስ የተዘጋጁትን የመማሪያ መጻሕፍት ለሁሉም ተማሪዎች ለማዳረስ በቢሊዮን ብሮች የሚቆጠር በጀት ይጠይቃል። ቢሆንም ለሁሉም ተማሪዎች ማዳረስ ተችሏል። የትምህርት ጥራት ከመማሪያ መጻሕፍት ውጭ አይታሰብምና። ደግሞስ ከንቲባዋ፣ “ትልቁ ሥራችን የትውልድ ግንባታችን ነው” ብለው የለ!
ዘንድሮ የተማሪዎች ውጤት መሻሻሉ ደግሞ ይበል የሚያሰኝ ነው።
ከሳምንት በፊት በይፋ የተገለጸውን የ8ኛ ክፍል የፈተና ውጤት በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል።  በፈተናው 50 ነጥብና ከዚያ በላይ ውጤት ያገኙ ተማሪዎች ብዙ ናቸው።
በቀን የመንግሥት ትምህርት ቤት ተማሪዎች 82.4 በመቶ ያህሉ፣ በቀን የግል ትምህርት ቤት ተማሪዎች ደግሞ 96 በመቶ ያህሉ ከ50 ነጥብ በላይ ውጤት በማግኘት አልፈዋል ብለዋል፤ሃላፊው።
ከ290 ሺህ በላይ ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል አግኝተዋል
የጤናውም፣ የትምህርቱም፣ የኮሪደር ልማቱም… ሁሉም ፕሮጀክቶችና ጥረቶች፣ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ፣ “ነዋሪዎች ሠርተው ኑሯቸውን እንዲያሻሽሉ የሚያግዙ ናቸው” ማለት ይቻላል።
የኢንቨስትመንትና የንግድ ፈቃድ አመዘጋገብን በዘመናዊ አሠራር በማሻሻል ፈጣን አገልግሎት መስጠት፣ ገበያን ማረጋጋት፣ የማምረቻና የገበያ ማዕከላትን መገንባትና ማዘጋጀት… እነዚህና ተመሳሳይ ጥረቶች በሙሉ፣ የነዋሪዎች የመተዳደሪያ ሥራ እንዲሳካና አዳዲስ የሥራ ዕድሎች በብዛት እንዲፈጠሩ የሚጠቅሙ ናቸው።
በእርግጥ ደግሞ፣ ዘንድሮ ለ330 ሺህ ነጋዴዎች የንግድ ፈቃድ ዕድሳት ከማከናወን በተጨማሪ፣ ለ78 ሺህ ያህል አዲስ ንግድ ፍቃድ እንደተሰጠ የከተማዋ የንግድ ቢሮ ኀላፊ ገልጸዋል።
1919 የኢንቨስትመንት ፈቃዶች ታድሰዋል። 2619 አዲስ የኢንቨስትመንት ፈቃዶችም ተሰጥተዋል።
ከ7500 በላይ ኢንተርፕራይዞች የ2.5 ቢሊዮን ብር የብድር አገልግሎት እንዳገኙ ያወሱት ከንቲባ አዳነች፣ ቀድሞ ከተሰጠው ብድር 2.6 ቢሊዮን ብር ማስመለስ እንደተቻለ ጠቅሰዋል። 466 አምራች ኢንዱስትሪዎችም የመሳሪያ ሊዝ ተጠቃሚ ሆነዋል።
በትልልቅ ኢንቨስትመንቶችና በፕሮጀክቶች፣ በአነስተኛና በመካከለኛ ተቋማት አማካኝነት በአጠቃላይ ከ290 ሺህ በላይ ነዋሪዎች ቋሚ የሥራ ዕድል እንዳገኙም ተጠቅሷል። 50 መቶ ያህሉም ሴቶች ናቸው ተብሏል።

በሩቅ ምስራቅ የሚተረክ አንድ አፈ - ታሪክ አለ፡፡ አንዳንዶች ከቪክቶር ሁጎ መጽሐፍ ባለታሪኩ ከዣን ቫልዣ ጋር ያዛምዱታል፡፡
ከእለታት አንድ ቀን አንድ በጣም ሀብታምና ዝነኛ ሌባ ነበር፡፡ ከማን ይስረቅ ከማን ምንም አይጨንቀውም፡፡ እሱ መስረቁን እንጂ የተሰረቀባቸው ህዝቦች ምን ያህል እንደሚከፉም ለአንዲት አፍታ አስቦበት አያውቅም፡፡ ብዙ ሰዎች መስረቁን እንዲተው ጠይቀውታል፡፡ የተሻለ ኑሮ እንዲኖርም ሙከራ አድርገዋል፡፡ ያስፈራሩትም ነበሩ፡፡ ግን አልሰማ ብሏል፡፡
አንድ ማታ አንድ ቤት ሰብሮ ይገባል፡፡ የማን ቤት ይሁን የማን አላወቀም፡፡ ሆኖም ከውጪ ሲያዩት ውድ ዕቃና ንብረት ያለው ይመስላል፡፡ ሌባው በመስኮት ዘሎ ሲገባ ከዚያ ቤት ሊሰረቅ የሚችል በጣም ጥቂት ንብረት ብቻ ነው ያለው፡፡
“በከንቱ ዕውቀቴን፣ ጊዜዬንና ጉልበቴን አባከንኩኝ” አለ ለራሱ፤ “ከዚህ የሚወሰድ ነገር አለመኖሩን ቅንጣት ጥርጣሬ ኖሮኝ ቢሆን፣ በጭራሽ አልሞክረውም ነበር፡፡” ሆኖም ይሄን ሁሉ ለፍቶ፣ ስንት ዕውቀትና ጥበብ ያፈሰሰበትን ነገር ትቶ ባዶ እጁን ወደ ቤቱ ለመሄድ አልፈለገም፡፡ መሬት ላይ ብዙ የታሰረ ልብስ አየ፡፡ ስለሆነም ያንን ለመዝረፍ ወሰነ፡፡
ልብሱን በመሰብሰብ ላይ እያለ አንድ ድምፅ ሰማ፡፡ ዘወር ሲልም ከጀርባው አንድ ሽማግሌ ሰው ቆመው አየ፡፡ የተሸከመውን ልብስ መሬት ላይ ዘርግፎ ጥሎ መሮጥ ጀመረ፡፡
ሽማግሌውም፤
“አንድ ጊዜ ቆይ፣ እባክህ አንዴ ቆይ፡፡ አትሂድ፡፡ እኔ አግዝሃለሁ፡፡ ብቻህን ይሄን ሁሉ ተሸክሞ ለመሄድ ይከብድሃል፡፡ እንካፈልና እንሸከመው፡፡ ግማሽ እኔ እይዛለሁ፡፡ ግማሹን አንተ ያዝ”
ሌባው፣ ሽማግሌው ሰውዬ ሌባ ሌባ መሆናቸውን ገመተ፡፡ ግማሽ ግማሽ መሸከም ያለባቸው ለምን እንደሆነ ግን ሊገባው አልቻለም፡፡ ምክንያቱም ቀድሞ የገቡት እሳቸው ናቸውና ብዙውን እጅ እኔ ልውሰድ ማለት ነበረባቸው፡፡
“እሺ ሊያግዙኝ ይችላሉ” አለ ሌባው፡፡ “እርስዎ ግን ግማሹን አይወስዱም፡፡ ትንሽ ነገር ልሰጥዎት እችላለሁ - ድካምዎትን አይቼ፡፡”
“እሺ ይሁን ግዴለም እንዳልክ” አሉ ሽማግሌው፤ የየድርሻቸውን ተሸከሙና ከቤት ወጥተው መንገድ ጀመሩ፡፡
ከጥቂት ጊዜ በኋላ ሌባው የሽማግሌው መንቀራፈፍ አሰለቸው፡፡ “ቶሎ ቶሎ ተራመዱ እንጂ” አላቸው በሹክሹክታ፡፡ “ካልፈጠኑ’ኮ መያዛችን ነው፡፡ ከመንጋቱ በፊት መደበቂያዬ ቦታ መድረስ ይኖርብናል፡፡ ፍጠኑ!”
ሽማግሌው በተቻላቸው ፍጥነት ሁሉ ተውተረተሩ፡፡ ግን የተሸከሙት በጣም ከብዷቸዋል፡፡ ሌባው፤ አሁንም አሁንም ፍጠኑ እያለ ያዋክባቸዋል፡፡ “እንዲህ ቀርፋፋ መሆንዎትን ባውቅ ኖሮ መጀመሪያውኑ እንድትሸከሙልኝ አልፈቅድም ነበር! ወይኔ ሰውዬው!” እያለ ቁጭቱን ገለፀ፡፡
በመጨረሻ ሌባው መሸሸጊያ ቤት ደረሱ፡፡
“አሁን እንግዲህ እነዚያን ሁለት ጥቅሎች ያንሱ፡፡ ስላገዙኝ እነሱን ውሰዱ፡፡ ከዛሬ በኋላ ሁለተኛ አይንዎትን ለማየት አልፈልግም” አላቸው፡፡
ሽማግሌው ተሸክመውት የነበረውን ሁለት ጥቅል መሬት ላይ ድንገት ወረወሩት፡፡ ከዚያም ወንበሩ ላይ ዘፍ ብለው ተቀመጡና፤
“እኔ ምንም ልብስ አልፈልግም፡፡ እኔ እንዲያው ልረዳህ ብዬ ነው የመጣሁት፡፡ አየህ ሰብረኸው የገባኸው ቤት የእኔ የራሴ ቤት ነው፡፡ የወሰድከው ልብስም በሙሉ የእኔ ነው፡፡ ’ይሄንን ለመስረቅ የተገደድከው እንዴት ቢቸግርህ ነው‘ ብዬ አሰብኩ፡፡ ስለዚህም በተጨማሪ ምን ልረዳህ እንደምችል አመዛዝኜ በሸክም ልረዳህ ወሰንኩ፡፡
አሁን እንግዲህ የት እንደምኖር አሳምረህ አውቀሃል፡፡ ሌላም ነገር ባስፈለገህ ሰዓት በተጨማሪ መጥተህ መውሰድ ትችላለህ፡፡ ቤቴ ቤትህ ነው፡፡ ማንኛውንም ነገር መውሰድ ትችላለህ፡፡ የእኔ ንብረት የአንተም ንብረት ነው፡፡”
ሌባው ጆሮውን ማመን አቃተው፡፡ በመጀመሪያ እንደቀልድም መሰለው፡፡ የምር መሆኑን ሲያውቅ ግን “በዐይኔ በብረቱ የሆነውን ነገር ሁሉ ባላይ ኖሮ በጭራሽ አላምንም ነበር፡፡ የገዛ ንብረትዎ ሲሰረቅ ማሳሰር ሲችሉ ፈቅደው ዝም አሉኝ፣ ይባስ ብለው በሸክም እረዱኝ፡፡ በዛ ላይ እንደልቤ እየፈነጨሁ ስሰድብዎ ታግሰው ሲያበቁ፣ በመጨረሻ ደግሞ ሀብቴ ሁሉ ሀብትህ ነው ብለው ሰጡኝ፡፡ ለእኔ ከዚህ በላይ ቅጣት የለም!! ከዚህ በላይም በህይወቴ የተማርኩት ነገር የለም!!” አለ፡፡
***
ሌባም፣ ሀብታምም ከሆነ ሰው ይሰውረን ማለት ደግ ነው፡፡ እንደ ሽማግሌው ሆደ - ሰፊ ህዝብ ሲኖር፣ የሚማር ሌባ አይገኝም፡፡ አንዱ ሲሳካ አንዱ ይጎድላል፡፡ ይቅርታ የሚያደርግ ሲገኝ፣ ይቅርታ የሚደረግለት ሰው አይገኝም፡፡ ይቅርታ ጠያቂ ሲገኝ፣ ተጠያቂው አይገኝም፡፡ ሁለቱ ሰምሮ እንዲገኝ ጥረት የሚያደርጉ ሁነኛ አዛውንቶች ካልተገኙ አገር የቂም፣ የበቀል፣ የእልህ፣ የእኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል፣ የሁሉን ለእኔ፣ የልስረቅ አግዙኝ….አገር ትሆናለች፡፡ ሲነገር፣ ሲመከር፣ ማስጠንቀቂያ ሲሰጥ የማይሰማ መጨረሻው አያምርም፡፡ ስለሆነም አገርም ለውጥ እርሟ ይሆናል፡፡
ሰውም “የሚስቴ ውሽማ መታኝ፣ ያሳደግሁት ውሻ ነከሰኝ፡፡ ቁጭ ብዬ አደርኩ ገርሞኝ” ሲል ይኖራል፡፡ አንድ ጊዜ የጀርመን ፕሬዚዳንት በሆሎኮስት በአይሁዶች ላይ ስለተፈፀመው ጭፍጨፋ ለእስራኤል ፓርላማ ሲናገሩ፡-
“ዛሬ የእሥራኤል ህዝብ እያየኝ በዚያን ዘመን ስለተገደሉ፣ አሁን የትም ሄጄ ይቅርታ ልጠይቃቸው ለማልችላቸው ሰዎች፣ በሀፍረት እጅ እነሳለሁ” ብለው ነበር፡፡ በማናቸውም ወቅት ይቅርታ ለመጠየቅ ዝግጁ የሆነ መሪና የፖለቲካ ሀላፊ፣ እንዲሁም ይቅርታ ለማድረግ ዝግጁ የሆነ ተበዳይ መኖር እጅግ ወሳኝ ነው፡፡ የሰላም ቁልፍ ይሄው ነውና፡፡ ለይቅርታ አንዱ ቁልፍ ነገር፣ ሌላውም ሰው እንደኔ ሊያስብ ይችላል የሚል ከቡድን ስሜት የራቀና የጠራ አስተሳሰብ ነው፡፡ አንድ ኢትዮጵያዊ ስለተማሪ ንቅናቄ በፃፈው አንድ መጣጥፍ፤ “ለነሱ ቡድን የገበረውን የሚነዳ ከብት ይሆናልና ይነዱታል፡፡ የሚጠሉት ቢኖር የሚያስብ ሰው ነው…” ብሎ ነበር፡፡ ይሄ አባዜ ዛሬም አልለቀቀንም፡፡ ግትር የቡድን ስሜት ለሀገር እንዳልበጀ አለ፡፡
የኢትዮጵያ ታሪክ ዘውድ - ጫኝ፣ አስጫኝና አድራጊ ፈጣሪ ይዞ ሲጓዝ የኖረ እንጂ ከልብ ለህዝቡ ያሰበ አልነበረም፡፡ የራስን ዕምነት የሁሉ ዕምነት አድርጎ መውሰድ ሌላው አደጋ ነው፡፡ እንዲህ ያለ ግትር እምነት እንደ ዕፅ ዐይነ - ሥጋንና ዓይነ - ህሊናን ይጋርዳልና ዛሬም በብርቱ መታሰብ ያለበት ጉዳይ ነው፡፡
ይቅርታ የመጠያየቅ ባህል ልበ - ብሩህነትንና ልበ - ንጹነትን ይጠይቃል፡፡ ይህ ባህል ለአገርና ለህዝብ መንገድ ቀዳጅ መሆኑን አምኖ ዕብሪት ትቶ፣ ክፋትን አስወግዶ፣ የመጣው ይምጣን ትቶ መጓዝን ይጠይቃል፡፡  ወደድንም ጠላንም በቁርጠኝነት መደረግ ያለበት ሁነኛ ነገር ነው፡፡ ሁሉን በመናቅ፣ ሁሉን ዝቅ አድርጎ፣ ሁሉን በማንጓጠጥ፣ ሁሉን አወቀ አላወቀ ምን ለውጥ ያመጣ፣ በማለት የበላይነትንና የውስጠ - ምኞት እርካታን ብቻ ለማሳካት መደገግ ከቶም የትም የሚያደርስ አይደለም፡፡ ካልሆነ ለታዋቂው የጀርመን የሙዚቃ ቀማሪ እንደተሰጠው አባባል፤ “ከመካከላችሁ ያልሰደብኩት ሰው ካለ፣ እሱን ይቅርታ እጠይቀዋለሁ” ብሏል የተባለውን ዓይነት የዕቡይ ፌዝ ይሆናል፡፡ ይሄ ደግሞ የብዙ ዕድሜ ምልክት አይደለም!

Page 1 of 714