Administrator

Administrator

(በጓድየ ብሽየ ኤረማ) - የቤተ ጉራጌ ምሳሌያዊ አነጋገር


አንድ በጣም ባለፀጋ የሆኑ የተከበሩ ባላባት ባንድ መንደር ይኖራሉ። ጌታዬ ጌታዬ የማይላቸው የለም። እኚህ የተከበሩ ባላባት፣ አንድ ብርቄ የሚባል አሽከር ነበራቸው። ብርቄ አሽከርነት ያምርበታል። ሲልኩት ወዴት፣ ሲጠሩት አቤት ማለት ይችልበታል፡፡ ዘወትር ግብር ገብቶ፣ ድግሱ ተበልቶ ጌትየውን ብርቄ እጅ ሲያስታጥብ፤
“ሰማህ ወይ ብርቄ” ይሉታል።
“አቤት ጌታዬ” ይላል ብርቄ።
“አሁን እኔ ብሞት ምን ታደርግ ይመስልሃል?”
“ጌታዬ እርስዎ ከዚህ አለም ተለይተው፣ እኔ አዚህ ቤት አልቀመጥም”
“ታዲያ ምን ትሆናለህ?”
“እመንናለሁ። ዓለም በቃኝ እላለሁ። ጀርባዬን ለዓለም፣ ፊቴን ለገዳም እሰጣለሁ”
“ተው አታረገውም ብርቄ?”
“በጭራሽ። እርስዎ ሞተው እኔ እዚህ ቤት አንዲት ቀን እህል ውሃ አልቀምስም!”
“መልካም። ለዚህ ታማኝነትህ አንድ ኩታ ተሸልመሃል!”
 ብርቄ እጅ ነስቶ ኩታውን ያገኛል።
ሌላ ቀን “ብርቄ እኔ ብሞት ምን ታደርጋለህ?” ይሉታል።
“ምን ያጠያይቃል ጌታዬ? መመነን ነዋ! ከእርስዎ ወዲያ ዓለም ለምኔ!” ይላል።
“ብርሌ ጠጅ ስጡት ይባላል!”
ሌላ ቀን። “ብርቄ እኔ ብሞት ምን ታደርጋለህ?”
“ዕለቱን ቅሌን ጨርቄን ሳልል ወደ ገዳም ነዋ ጌታዬ!”
“ዕውነት ታደርገዋለህ ብርቄ?”
“አይጠራጠሩ ጌታዬ! ምን ቀረኝ ብዬ እዚህ ቤት እቀመጣለሁ?”
“እኔ እምልህ ብርቄ?”
“አቤት ጌታዬ?”
“እንዲያው ለነገሩ ከእኔ ቀድመህ መሞት ታስቦህ ያውቃል? አንዳንዴ ለምን እኔ ቀድሜዎት ልሙት እንኳ አትለኝም?”
ብርቄም ትንሽ አሰብ አድርጎ፤
“አይ ጌታዬ ሳላስበው ቀርቼ መሰለዎት? አስቤዋለሁ። ግን ከተናገርኩ የጌታዬን ሞት የተሸማሁ እንዳይመስልብኝ ብዬ ነው።”
ሌላ ቀን። ብርቄን ጠርተው ደግመው በጨዋታ መሀል፤
“ከእኔ ቀድመህ የምትሞት አይመስልህም?”
“ኧረ በጭራሽ ጌታዬ!”
“ለምን?”
“እኔ ከሞትኩ ማን እንደኔ ያለቅስልዎታል ጌታዬ! ኧረ በጭራሽ እግዜር እንደዚያ ያለ ነገር አያድርስብን!! እርስዎ ከሞቱ ግን እዚች ቤት አንዲት ጀምበር አላድርም - ወደ ገዳም ነው!”
“ይሄን ያህል ትወደኛለሃ?”
ከባድ ጉርሻ ያጎርሱትና “ጠጅ ስጡት!” ብለው ያዙለታል።
ጌታዬው እንዳሉት እሳቸው ቀድመውት ሞቱ። ከሚስታቸው አንድ ትንሽ ወንድ ልጅ ብቻ ነው ያላቸው። ሚስታቸው 6 ወር ካዘኑና መንፈቃቸውን ካወጡ በኋላ ሌላ ባል አገቡ። ብርቄም ያዲሱ ጌታ አሽከር ሆነ። “እርስዎ ከሞቱ  እመንናለሁ ጌታዬ!” ማለቱን ቀጠለ።
አንድ ቀን አዲሱ ጌታው ግብር አግብተው፣ ሰው በድንኳን ግጥም ብሎ እየተበላ እየተጠጣ፣ ብርቄ እንደ ልማዱ ተፍ ተፍ እያለ እያስተናገደ ሳለ፣ አንድ አዝማሪ ተነስቶ መሰንቆውን እየገዘገዘ ጨዋታ ጀመረ።
ድምፁን አዝልጎ፤ “ትላንትና ማታ ጌታዬን አግኝቼ” አለና ጀመረ። ህዝቡ በከፊል፣ አዝማሪው የሞቱትን ጌታ በማንሳቱ “ምን ሊል ይሆን?” በሚል አይነት ፀጥ አለ። አዝማሪው ደገመና፤
“ትላንትና ማታ ጌታዬን አግኝቼ
….ሚስቴስ ደህና ናት ወይ? (ወደ ሚስትየው እያየ)
…ልጄስ አደገ ወይ? (ወደ ልጅየው እያየ)
…ብርቄስ መ…ነ…ነ ወይ?” (ወደ ብርቄ ቀና ብሎ) ብለው ቢጠይቁኝ፤
ሚስትዎ ደህና ናቸው ልጅዎትም አድጓል።
(ቆም አድርጎ ወደ ብርቄ እያየና እያንዳንዱን ቃ  እየረገጠ)
..ብ..ር..ቄ..ም አ..ል…መ..ነ..ነ…ም!! ብዬ ብነግራቸው
አይ ጉድ! አይ ጉድ! አይ ጉድ! ያሉበት ረገፈ ጣታቸው!!”
ሲል ገጠመ። ሰው ሁሉ ወደ ብርቄ ተመለከተ። ብርቄን የሰው ዐይን ከአገር አስወጣው።
*  *  *
ለእምነታቸው የሚኖሩ፣ ማተባቸውን የማይበጥሱ፣ የተናገሩትን የማያፈርሱ፣ በምላሳቸው የማይኖሩ ብቻ ናቸው በህዝብ የሚታመኑ። ቤታቸውንና አለቃቸውን ለማስደሰት ወይም ለመሸንገል ሲሉ ብቻ “አቤት!” “ወዴት!” የሚሉ የየሥርዓቱ አሸርጋጅ ይሆናሉ እንጂ፣ በየተደገሰበት ሁሉ ከበሮ መቺ ይሆናሉ እንጂ፣ ለህሊናቸውና ለእምነታቸው አያድሩም።
“ህዝቡን ልናገለግል”፣ “ሀገርን ልናድን”፣ “ምድር ሰማዩን ልናለማ”፣ “የህዝቡን የአኗኗር ዘይቤ ልንለውጥ”፣ “ከተማ ልናሰፋ”፣ “የገጠሩን ህዝብ ልናሰለጥን”፣ ወዘተ የሚል አይነት ቃል መግባትና “ይህ ካልሆነ ወንበሬን እለቃለሁ”፣ “ይህ ካልሆነ የጓዶች አጥንት እሾህ ሆኖ ይውጋኝ!”፣ “ይህ ካልሆነ ማናቸውንም ፍዳ ልቀበል!” ማለት የተለመደ ሆኗል። እንደ ብርቄ “እርስዎ ከሞቱ በቃ እመንናለሁ” ማለት። ከዚያ ምንም ለውጥ ሳያመጣ ሲቀር ለአዲሱ ጌታ ማደር። አይንን በጨው ታጥቦ “ዛሬም እንደትላንት በአላማ ጽናት ራእዬን እውን ለማድረግ እስከመጨረሻው የደም ጠብታ፣ እስከመጨረሻው አንድ ሰው፣ እታገላለሁ” ሲሉ ቃለ መሀላ ማዥጎድጎድ። ጌታዬ ከሞቱ እዚች አገር አንዲት ቀን አልውልም አላድርም ማለት!.. ቃል መግባት… ዕቅድ ማቀድ…. ፖሊሲ መንደፍ….በየወንዙ መማል….. መማማል መመሪያ ማውጣት ….አዋጅ ማወጅ…. በየፌርማታው አበጀህ አበጀህ መባባል…. መግለጫ ማውጣት…. መጽሀፍ መግለጥ… ፕሮጄክት መቅረጽ… መርቆ መክፈት… መጨባበጥ… “ከመቼውም በበለጠ በአዲስ መንፈስ ተነስተናል” ማለት… ትላንትናን በላጲስ ማጥፋት…ነገን በእርሳስ መሳል…ተግባርና “አፈፃፀም” ግን የለም። ቃል ይፈርሳል። ቃል ይበላል። የሚወገዝ ይወገዛል። መካድ። መካካድ ይቀጥላል። የሚረገም ይረገማል። በትብብር በደቦ፣ በብዙኃን ድምፅ መራገም እንጂ ከልብ የሚሆን ምንም ነገር የለም እንደ ማለት ነው። “ሲቸግር የእንጀራ እናትን እምዬ  ይሏል” ነውና፣ የትላንቶቹን ለመርገም የትላንት ወዲያውን መጥቀስና ማወደስ ይቀጥላል።
አዲስ መፈክር ይቀመራል። በህብረት ያንን መፈክር ማስገር ይቀጥላል። በልብ መክዳት፣ በአካል አለሁ ማለት ይዘወተራል። እስከሌላ መከዳዳት… እስከሌላ ቃል ማፍረስ… “ልጅ እገሌ”፣ “ጓድ እገሌ”፣ “ክቡር እምክቡራን” መባባል። ሆኖም “በጨለማ ማፍጠጥ ደንቆሮን መቆጣት ነው” እንደሚባለው ልብ ውስጥ እውነተኛው ፍቅር፣ እውነተኛው አገር መውደድ፣ እውነተኛው ለህዝብ የመቆም ስሜት ሳይኖር፣ ዓላማና እቅድን በስራ ላይ ማዋል ከቶም ዘበት ነገር ነው። መሪና መሪ፣ አለቃና አለቃ፣ ፓርቲና ፓርቲ፣ ባለስልጣንና ባለስልጣን፣ ዜጋና ዜጋ በመካከላቸው ልባዊ መተማመን ከሌለ ሥራ አይሰራም። ዕቅድ አይፈፀምም። ፕሮግራም አይተገበርም። ቃል ህይወት አይሆንም። ይስሙላ፣ ለበጣ፣ የአደባባይ ማስመሰል፣ የሸንጎ ዲስኩር፣ የስብሰባ ንግግር ብቻ ሆኖ ይቀራል።
የሀገራችን አንዱ አንኳር ችግር፣ ከእቅድ ነዳፊ እስከ ፈፃሚው ድረስ ልባዊ መተማመን አለመኖር ነው። “ይህን ያለው ይህን ሊል ፈልጎ ነው” በሚል የግራ ትርጉም የታጠረ አስተሳሰብ ይበዛል። ቡድንና ቡድን አይተማመንም። መስመሩን ሳይሆን በመስመሮች ማህል ማንበብ (Between the lines እንዲሉ) ነው ፈሊጡ። በውስጥ የተቀበረ ፍላጎት (Hidden Motive) ካለ ምንዛሪ ይበዛል። ቅጥያና ዘርፍ እያበዙ “ትርጉም የኔ”፣ “ስርዝ ያንተ”፣ “ቅንፍ የነሱ” ማለት ቋንቋ ይሆናል። አፍአዊ የሆነ ያሸበረቀ ቃል ሲበዛ ተግባር ባዶውን ይቀራል። ዞሮ ዞሮ ወሳኙ ግን ልባችን ውስጥ ምን አለ የሚለው ነው። ልባችን ትግል እያሰበ፣ አፋችን ድል ቢያወራ ዋጋ የለውም። ልባችን ሹመት እያሰበ፣ አፋችን የኢኮኖሚ ልማት ቢያወራ ነገ የሚጋለጥ ከንቱ ዲስኩር ይሆናል። ሁሉም የሚያስተጋባውና የሚተገብረው ጥንት የተሰራበትን ንጥረ-ነገር ነው፤ የውስጡን። የጠዋቱን።
እውነተኛ ፍሬ ከእውነተኛ ተግባር፣ ከእውነተኛ እምነት ነው የሚገኘው። ያ ሳይኖር ፍሬ መጠበቅ ከንቱ ነው። ነጭ ባህር ዛፍ ላይ፣ ቀይ ባህር ዛፍ አይበቅልም ማለትም ይሄው ነው።

•  በክልሉ በቀጠለው የጸጥታ ችግር ሳቢያ ነው ተብሏል


በአማራ ክልል የሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች በክልሉ እየተባባሰ በመጣው የጸጥታ ችግር ሳቢያ የዘንድሮን የተማሪዎች ቅበላ ጊዜ  ላልተወሰነ ጊዜ ማራዘማቸው ተነገረ፡፡

ዩኒቨርሲቲዎቹ ተማሪዎቻቸውን ለመቀበል በይፋ ጥሪ አድርገው የነበረ ቢሆንም፣ በክልሉ በቀጠለው ግጭት ሳቢያ የቅበላ ጊዜያቸውውን ላልተወሰነ ጊዜ ማራዘማቸው ታውቋል፡፡ ደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ፣ኢንጅብራ ዩኒቨርሲቲ፣ ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ፣ ወሎ ዩኒቨርሲቲና ደብረታቦር ዩኒቨርሲቲ የቅበላ ጊዜያቸውን ያራዘሙ ሲሆን፤ ባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ደግሞ ለተማሪዎች ያደረገውን ጥሪ ከትስስር ገጹ ላይ ማንሳቱ ተዘግቧል፡፡

የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ካሉት 9 ካምፓሶች ውስጥ ሁለቱ ማለትም፡- ዘንዘሊማ እና ሰባታሚት ጥበበ ጊዮን ካምፓሶች በጸጥታ ችግር ሳቢያ መዘጋታቸው  ተነግሯል፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞ በአማራ ክልል ከመንግሥት ጋር በመዋጋት ላይ  የሚገኘው ታጣቂው የፋኖ ቡድን፣ የክልሉን ዋና መንገዶች ሙሉ በሙሉ መዝጋቱ ተነግሯል፡፡ መንገዶቹ የተዘጉት ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ጀምሮ ሲሆን፤በዚህም የተነሳ የተሽከርካሪዎች እንቅስቃሴ በእጅጉ መገደቡ ነው የተጠቆመው፡፡

የፋኖ ታጣቂዎች ከመንግሥት ጋር ግጭት ውስጥ የገቡት ባለፈው ዓመት ሲሆን፤ ይህም በክልሉ ከፍተኛ ሰብአዊና ቁሳዊ ቀውስ አስከትሏል፡፡ በርካታ ቁጥር ያላቸው ተማሪዎችም ከትምህርት ገበታቸው መስተጓጎላቸው ይታወቃል፡፡

በሌላ በኩል፣ ባለፈው ሳምንት የመከላከያ ሃይልና የአማራ ክልላዊ መንግሥት በፋኖ ታጣቂዎች ላይ ከፍተኛ ወታደራዊ ዘመቻ መጀመራቸውን አስታውቀዋል፡፡

በአማራና ኦሮሚያ ክልል በቀጠሉ ግጭቶች ውስጥ የሚሳተፉ አካላት የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲፈጽሙ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) ጥሪ አቅርቧል።
ኢሰመጉ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ባወጣው መግለጫ፤ በዜጎች ላይ የሚፈጸሙ ግድያዎች፣ እገታና አፍኖ የመሰወር ተግባር በእጅጉ እየተስፋፋ መምጣቱን በመጠቆም፣በዚህም ምክንያት የሰዎች በህይወት የመኖር መብትና የአካል ደህንነት መብት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን አስታውቋል።
ለእነዚህ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ምክንያቱ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ተባብሰው የቀጠሉ ግጭቶች መሆናቸውን የገለጸው ኢሰመጉ፤ ግጭቶቹ በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ጥሪ ያቀረበ ቢሆንም፣ የሚመለከታቸው የፌደራልና የክልል መንግስታት፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶቹን ለማስቆም በሚፈለገው ደረጃ  አለመንቀሳቀሳቸውን አመልክቷል፡፡
 ተቋሙ በመግለጫው ተፈጽመዋል ያላቸውን የሰብአዊ መብት ጥሰቶች በመረጃ አስደግፎ አቅርቧል፡፡  ለአብነት ያህል፣ በአማራ ክልል ዋና ከተማ ባሕርዳር፣ አባይ ማዶ “አየር ጤና” ተብሎ በሚጠራው አካባቢ፣ መስከረም 11 ቀን 2017 ዓ.ም. የጋብቻ ስነ ስርዓታቸውን ለማከናወን ሲዘጋጁ፣ ሙሽሪት፣ ሚዜዋ እንዲሁም አንድ የቅርብ ዘመዷና ሰርጉን ለመታደም ከተገኙት ውስጥ 1 ሰው፣ በድምሩ 4 ሰዎች፣ በታጠቁ ሃይሎች ታግተው ወዳልታወቀ ስፍራ እንደተወሰዱ ኢሰመጉ  አብራርቷል። እኒህ ሰርገኞች ከተወሰዱበት ዕለት ጀምሮ፣ ኢሰመጉ ይህን መግለጫ እስካወጣበት ዕለት ድረስ፣ በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ለማወቅ አለመቻሉን ገልጿል።
መስከረም 15 ቀን 2017 ዓ.ም. በምዕራብ ጎጃም ዞን፣ ቡሬ ወረዳ በዞኑ አገረ ስብከት ስር ከሚገኘው፣ የቁጭ ማዓልትን ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን፣ አገልጋዮችና በርካታ ቁጥር ያላቸው የቄስ ተማሪዎች በመንግስት አካላት ታስረው እንደነበር ያስታወሰው ኢሰመጉ፤ በጉዳዩ ላይ ክትትል ሲያደርግ መቆየቱንና እነዚህ ታሳሪዎች  መስከረም 23 ቀን 2107 ዓ.ም. መለቀቃቸውን ማወቁን በመግለጫው ጠቁሟል፡፡
ከመስከረም 19 ቀን 2017 ዓ.ም. ጀምሮ በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ የወሎና የደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ መምሕራንና የደብረ ብርሃን ከተማ የትምህርት ቤት ሃላፊዎች፣ ከክልል እስከ ወረዳ ያሉ በመንግስት የጸጥታ መዋቅር ውስጥ ያሉ አመራሮችና ባለሞያዎች፣ እንዲሁም  በመንግስት መስሪያ ቤት የሚያገለግሉ ሰራተኞችና የማሕበረሰብ አባላት በጅምላ መታሰራቸውንም ኢሰመጉ  አስታውቋል፡፡
በአማራና ኦሮሚያ ክልል በቀጠሉ ግጭቶች ውስጥ የሚሳተፉ ሁሉም አካላት፣ “ያለምንም ቅድመ ሁኔታ” የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲያደርጉ ጥሪ ያቀረበው ኢሰመጉ፤ ችግሮች በሰላማዊ መንገድ የሚፈቱበትን ሁኔታም እንዲያመቻቹ አሳስቧል። ከዚህ በተጓዳኝም፣ እነዚህ አካላት በማንኛውም ግጭት ውስጥ አለም አቀፋዊ የሰብዓዊ መብቶችን ጥሰት ከመፈጸም እንዲቆጠቡ አበክሮ ጠይቋል፡፡
በተመሳሳይ፣ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ባለፈው ሳምንት ባወጣው የሩብ ዓመት ሪፖርቱ፣ በአማራ ክልል የተኩስ አቁም ተደርጎ፣ ለግጭቱ ሰላማዊ መፍትሄ እንዲፈለግ ጥሪ ማቅረቡን  መዘገባችን ይታወሳል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ባለፈው ማክሰኞ ባወጣው መግለጫ፣ ከመስከረም 18 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ፣ በአማራ ክልል በሚገኙ ዋና ዋና ከተሞች ምሁራንና ሲቪል ሰራተኞችን ጨምሮ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በዘፈቀደ በጅምላ መታገታቸውን አስታውቋል፡፡

በላዕላይ ፀለምቲ ወረዳ፣ ሰዎች  ምንነቱ ባልታወቀ በሽታ ምክንያት እየሞቱ መሆኑን የክልሉ ጤና ቢሮ ገለጸ። በዚሁ ምንነቱ ባልታወቀ በሽታ ሳቢያ  ቁጥራቸው ቀላል ያልሆነ ሕጻናት ለሞት መዳረጋቸው ተነግሯል።
በወረዳው “ደገርባይ” በተባለ የገጠር ቀበሌ፣ ከሁለት ዓመት ዕድሜ በታች የሆኑ አምስት ሕጻናት፤ “ምጫራ” እና “ዲማ” በተባሉ ቀበሌያት ደግሞ ሁለት ሕጻናት ለሞት መዳረጋቸውን ቢሮው ባወጣው መግለጫ ጠቅሷል። በዚሁ መግለጫ እንዳብራራው፤ ሕጻናቱ የሞቱት ከመስከረም 1 እስከ 19 ቀን 2017 ዓ.ም. ድረስ መሆኑን ከአካባቢው ነዋሪዎች ማረጋገጡን ጠቁሟል።
ታማሚዎች ከሚያሳዩዋቸው ምልክቶች መካከል ትውከት፣ መዝለፍለፍና የሆድ ማበጥ መሆናቸውን የጠቀሰው የክልሉ ጤና ቢሮ፤ ወረዳው ከጊዜያዊ ክልሉ የአስተዳደር መዋቅር ውጪ በመሆኑ በቦታው ተገኝቶ በሽታውን ለመፈተሽ፣ ብሎም አስፈላጊውን የሕክምና እገዛ ለማድረግ ሁኔታዎች አልፈቀዱም ብሏል።
“አሁን የሚስተዋለውን አደገኛ ሁኔታ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር፣ የፌዴራል ጤና ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢኒስቲትዩትን ጨምሮ ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ሊያውቁት ይገባል። አስፈላጊውን እገዛ እንዲያደርጉም እየሰራን ነው” ብሏል፣ የክልሉ ጤና ቢሮ።
የትግራይ ክልል ጤና ቢሮ፣ ከዓለም ጤና ድርጅትና የተባበሩት መንግስታት የሕጻናት አድን ድርጅት (ዩኒሴፍ)፣ እንዲሁም ከሌሎች የሕክምና ባለሞያዎች ጋር በመሆን የሕክምና ድጋፍ ለማድረስ መግባባት ላይ መደረሱን አመልክቷል።
ከዚህ ቀደም በትግራይ ክልል ዓዲያቦ ወረዳ፣ የኮሌራ በሽታ በወረርሽኝ መልኩ ተስፋፍቶ በርካቶችን ማጥቃቱን መዘገባችን አይዘነጋም።



የኢትዮጵያና ሶማሊያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መሻከር ለአልሸባብና ተመሳሳይ ሽብርተኛ ቡድኖች መጠናከር ዕድል ፈጥሯል ተባለ፡፡ በሰሜናዊ ሶማሊያ የእስላሚክ ስቴት (አይኤስ) ታጣቂዎች ቁጥር  በእጥፍ መጨመሩን በአፍሪካ የአሜሪካ ጦር ዕዝ (አፍሪኮም) አስታወቋል፡፡
በስፍራው የአይኤስ ታጣቂዎች ቁጥር በሁለት ዕጥፍ ማደጉን የተናገሩት የዕዙ ዋና አዛዥ ማይክል ላንግሊ፤ ቡድኑ በአካባቢው አዳዲስ ታጣቂዎችን እየመለመለ ከመሆኑም በተጨማሪ በተለያዩ አገራት የሚገኙ አባላቱን በስፍራው እያከማቸ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
አዛዡ ከአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ፤ በአሁኑ ወቅት በስፍራው የሚገኙ የአይኤስ ታጣቂዎች ቁጥር፣ ባለፈው ዓመት ከነበረው በሁለት እጥፍ ማደጉን ተናግረዋል፡፡ በዚህም መሰረት በሰሜን ሶማሊያ እስከ 6 መቶ የሚደርሱ የቡድኑ አባላት እየተንቀሳቀሱ ሊሆን እንደሚችል የተገመተ ሲሆን፤ የኢትዮጵያና ሶማሊያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መሻከር የሽብር መከላከል ስራውን እንዳዳከመው ተገልጿል።
በተመሳሳይ ሁኔታ፣ የአፍሪኮም ዋና አዛዥ ማይክል ላንግሊ የአልሸባብ ወታደራዊ አቅም በሰው ሃይልና ጦር መሳሪያ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ እንደሚገኝ  ተናግረዋል፡፡ ከ12 እስከ 13 ሺ ተዋጊዎች እንዳሉት የሚነገርለት አልሸባብ፤በሶማሊያና ኢትዮጵያ መካከል የተፈጠረውን ዲፕሎማሲያዊ ውጥረት እንደ ጥሩ አጋጣሚ እየተጠቀመበት እንደሚገኝ ዋና አዛዡ ጠቁመዋል፡፡
በተጨማሪም በሁለቱ አገራት መካከል የተፈጠረው ክፍተት የሽብር መከላከል ስራውን እንደጎዳው ገልጸው፣ አገራቱ በጋራ በሰሩበት ወቅት የቡድኑን አቅም በከፍተኛ ሁኔታ ማዳከም ችለው እንደነበረ አውስተዋል፡፡
በደቡብ ምዕራብ የአገሪቱ ክፍል መንግስት በከፈተው ወታደራዊ ዘመቻ ተሸንፎ በርካታ ቦታዎችን ለቆ የነበረው አልሸባብ፣ ማዕከላዊ ሶማሊያን ጨምሮ በሌሎች ስፍራዎች በመንግስት ጦር የተወሰዱበትን ስፍራዎች በድጋሚ እየተቆጣጠረ ነው ተብሏል፡፡ በዚህም ምክንያት በአካባቢው የሚገኘው የሽብር እንቅስቃሴ ማደግ ለቀጣናው አገራት፣ ለዓለምአቀፍ ሰላምና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ እክል ሊሆን እንደሚችል ተነግሯል፡፡

በቅርቡ የንብ ባንክ ፕሬዚዳንት ሆነው ተሹመው የነበሩት ዶ/ር እመቤት መለሰ፣ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ሆነው መሾማቸው ተሰምቷል።

የገንዘብ ሚኒስቴር መስከረም 20 ቀን 2017 ዓ.ም  በፃፈው  ደብዳቤ ላይ እንደተገለጸው፤ ዶ/ር እመቤት መለሰ  ከጥቅምት 1 ቀን 2017 ዓ.ም. ጀምሮ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ  ፕሬዚዳንት ሆነው ተሹመዋል።

ዶ/ር እመቤት፣ የልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ከመሆናቸውም በፊት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ስትራቴጂ ፕላኒንግና ትራንስፎርሜሽን ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው ማገልገላቸው ይታወቃል፡፡

የፖሊሲ ባንኩን ላለፉት 4 ዓመታት በፕሬዚዳንትነት ሲመሩ የነበሩት ዶ/ር ዮሐንስ አያለዉ  በግል ምክንያት ከኃላፊነታቸው መልቀቃቸውን ካስታወቁ በኋላ፣ የአማራ ባንክ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሆነዉ በቅርቡ መሾማቸው ይታወሳል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ፣ ለአምስት ባንክ ላልሆኑ የውጭ ምንዛሪ ቢሮዎች የሥራ ፈቃድ መስጠቱን በዛሬው ዕለት አስታወቀ፡፡

 ብሔራዊ ባንክ፣ የውጭ ምንዛሪ አገልግሎትን ተደራሽነት ለማስፋፋትና የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሪ ግኝት ለማዳበር ከባንክ ጋር ዝምድና ለሌላቸው የግል የውጭ ምንዛሪ ቢሮዎች ፈቃድ ለመስጠት የሚያስችል መመሪያ ማውጣቱ ይታወሳል፡፡

በዚሁ መሠረት፣ አምስት ድርጅቶች ተፈላጊውን መስፈርት ማሟላታቸው ተረጋግጦ የሥራ ፈቃድ እንደተሰጣቸው ተመልክቷል፡፡  እነዚህ ድርጅቶችም፡- ዱግዳ ፊደሊቲ ኢንቨስትመንት ኃ.የተ.የግ.ማ፣ ኢትዮ ኢንዲፕንደንት ፎረን ኤክስቼንጅ ቢሮ፣ ግሎባል ኢንዲፐንደንት ፎረን ኤክስቼንጅ ቢሮ፣ ሮበስት ኢንዲፐንደንት ፎረን ኤክስቼንጅ ቢሮ እና  ዮጋ ፎሬክስ ቢሮ  መሆናቸውን ባንኩ ገልጿል፡፡


የውጭ ምንዛሪ ቢሮዎች በዋናነት የሚያካሂዱት የውጭ ምንዛሪ ሽያጭም ሆነ ግዥ ወዲያውኑ የሚፈጸም (spot transaction) ብቻ እንደሚሆን ተነግሯል፡፡

የውጭ ምንዛሪ ቢሮዎች ያለ ጉምሩክ ዴክላራሲዮን ከደንበኞች እስከ 10 ሺ የአሜሪካን ዶላር፣ የጉምሩክ ፈቃድ ከሚያቀርቡት ደግሞ ከዚያ በላይ የውጭ ምንዛሪ በጥሬ ገንዘብ መግዛት እንደሚችሉ ተገልጿል፡፡ በተጨማሪም፣ ተፈላጊ የጉዞ መረጃ ላላቸው የግል ተጓዦች እስከ 5 ሺ የአሜሪካን ዶላር፣ ለንግድ ሥራ ተጓዦች ደግሞ እስከ 10 ሺ የአሜሪካን ዶላር በጥሬ ገንዘብ መሸጥ ይችላሉ ተብሏል፡፡

 የውጭ ምንዛሪ ቢሮዎች በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የወጡ የአሠራር፣ የደህንነት፣ ሪፖርት አደራረግና የመዝገብ አያያዝ መስፈርቶችን በአግባቡ ተግባራዊ ስለማድረጋቸው ባንኩ ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል የሚያደርግ መሆኑን አስታውቋል፡፡

አርቲስት ዘለቀ ገሰሰ ያዘጋጀውን “ኑ፣ እንመካከር” የተሰኘ  አዲስ የሙዚቃ ክሊፕ ትናንት መስከረም 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ለአገራዊ ምክክር ኮሚሽን አስረክቧል።

ይዘቱን በአገራዊ ምክክር አስፈላጊነት ላይ ባደረገው በዚህ የሙዚቃ ክሊፕ ላይ በርካታ ባለሞያዎች እንደተሳተፉ አርቲስት ዘለቀ ገሰሰ ለጋዜጠኞች ተናግሯል።

 የሙዚቃውን ቅንብር ካሙዙ ካሳ እንደሰራው የገለጸው አርቲስቱ፤ በሥራው ላይ ለተሳተፉ ባለሞያዎችና ዕገዛ ላደረጉ ወገኖች ምስጋናውን አቅርቧል።

“የመገናኛ ብዙኃን ዘፈኑን በተደጋጋሚ ሊያጫውቱት ይገባል” በማለት በአጽንዖት የተናገረው አርቲስት ዘለቀ፣ ወደፊት ሙዚቃው በተለያዩ የአገሪቱ ቋንቋዎች እንደሚዘጋጅ አስረድቷል።

በሌላ በኩል፣ የአዲስ አበባ ዳያስፖራዎች ማሕበር፣ ለአገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ የምክክር አጀንዳዎችን እንዳስረከበም ተሰምቷል፡፡

-አምነስቲ ኢንተርናሽናል-

በአማራ ክልል በሚገኙ ዋና ዋና ከተሞች በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በዘፈቀደ በጅምላ መታገታቸውን ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች አምነስቲ ኢንተርናሽናል አስታወቀ።

አምነስቲ ትላንት ማክሰኞ  መስከረም 21 ቀን 2017 ዓ. ም. ባወጣው መግለጫ፤”ይህ የዘፈቀደ የጅምላ እገታ፣ የህግ የበላይነት መሸርሸርን የሚያባብስ ነው፡፡” ብሏል፡፡

ከመስከረም 18 ቀን 2017 ዓ. ም. ጀምሮ በአማራ ክልል፣ ምሁራንና ሲቪል ሠራተኞችን ጨምሮ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በጅምላ ተይዘው መታገታቸውን ሪፖርቶች እንደደረሱት ተቋሙ  ገልጿል።

የአምነስቲ ኢንተርናሽናል የምሥራቅና ደቡብ አፍሪካ ቀጠናዊ ኃላፊ ቲጌሬ ቻጉታ፤ “የኢትዮጵያ ወታደሮችና ፖሊሶች በአማራ ክልል የከፈቱት የዘፈቀደ እገታ ዘመቻ፣ መንግሥት የሕግ የበላይነትን ሙሉ በሙሉ ችላ ማለቱን ያሳያል” ብለዋል፤ በመግለጫው፡፡

 “የመንግሥት ባለሥልጣናቱ ሰዎቹን ከመያዛቸው አስቀድሞ የእስር ማዘዣም ይሁን ፍተሻ ለማድረግ ፈቃድ አላሳዩም” ያሉት ቲጌሬ ቻጉታ፤ “የታገቱት ሰዎችም በህጉ መሠረት በ48 ሰዓታት ውስጥ ፍርድ ቤት አልቀረቡም” ብለዋል።

የዓይን እማኞች ለአምነስቲ እንደጠቆሙት፤ በአማራ ክልል በሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ያሉ ምሁራን በጅምላ ከታገቱት መካከል ይገኙበታል፡፡

“የኢትዮጵያ መንግሥት ይህንን የዘፈቀደ የጅምላ እገታ በአፋጣኝ ማቆም አለበት። በታገቱት ሰዎች ላይ ሕግን ተከትሎ ክስ መመሥረትና የሕግ ሥርዓትን መከተል ይገባዋል። አሊያም ሰዎቹን መልቀቅ አለበት። መንግሥት የዘፈቀደ እገታን ለጭቆና ማዋልን ማቆም አለበት” ሲሉም ኃላፊዋ አሳስበዋል፡፡

ባለፉት ጥቂት ወራት የኢትዮጵያ መንግሥት በጋዜጠኞችና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ላይ ማስፈራሪያ፣ ተከታታይ ጥቃትና ወከባ  ማድረጉን ያስታወሰው አምነስቲ፤በዚህም ምክንያት ብዙዎች እየተሰደዱ ነው፤ ብሏል።

ብላክ ዳይመንድ የህትመትና ማስታወቂያ ማሰልጠኛ አካዳሚ፣ ከወረቀት ህትመት ውጪ በሃገራችን የመጀመሪያውን የህትመትና ማስታወቂያ ሥልጠና በይፋ መጀመሩን አስታወቀ፡፡
የብላይክ ዳይመንድ አድቨርታይዚንግ መሥራቾችና አመራሮች በዛሬው ዕለት ከሰዓት በኋላ 22 ማዞሪያ ወርቁ ህንጻ ገባ ብሎ በሚገኘው የልህቀት ማዕከል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
የሥልጠና አካዳሚው ሥራ መጀመሩን አስመልክቶ በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተነገረው፤ ከነገ መስከረም 22 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ የሰልጣኞች ምዝገባ የሚጀመር ሲሆን፤ አካዳሚው የተለያዩ አጫጭር የቀንና የማታ የሥልጠና መርሃግብሮችን በመስጠት ሥልጠናውን ይጀምራል ተብሏል፡፡
ብላክ ዳይመንድ የህትመትና ማስታወቂያ ማሰልጠኛ አካዳሚ ከሚሰጣቸው ሥልጠናዎች መካከል፡- የባነር፣ ስቲከር ህትመት ማሽነሪ ባለሙያነት፣ ሲኤንሲ መቁረጫ ማሽነሪ ባለሙያነት፣ የህትመትና ግራፊክስ ዲዛይን ሥራዎች፣ የላይት ቦክስ ማስታወቂያ ባለሙያነት፣ የኒዮን ላይት ማስታወቂያ ባለሙያነትና ሌሎችም ይገኙባቸዋል፡፡
ተቋሙ በማስታወቂያ፣ በህትመት ማሽንና ግራፊክስ የሚታየውን የሰለጠነ ባለሙያ ክፍተት ለመሙላት ከነገ ጀምሮ ሰልጣኞችን መመዝገብ እንደሚጀምር ነው ያስታወቀው፡፡
ዛሬ በተሰጠው መግለጫ ላይ እንደተጠቆመው፤ ሥልጠናዎቹ እስከ ሦስት ወር የሚደርሱ በሰርተፊኬት ደረጃ የሚሰጡ አጫጭር ኮርሶች ናቸው፡፡
በባለራዕይ ወጣቶች የተቋቋመው ብላክ ዳይመንድ አድቨርታይዚንግ፣ ላለፉት በርካታ ዓመታት የተለያዩ የህትመትና ማስታወቂያ ሥራዎችን በጥራትና በብቃት በመሥራት በደንበኞቹ ዘንድ ስምና ዝናን ያተረፈ ሲሆን፤ ሥራውንም በተለያዩ ዘርፎች አስፋፍቶ እየሰራ የሚገኝ ተቋም ነው፡፡
Page 1 of 726