Administrator

Administrator

ከእለታት አንድ ቀን በህይወቱ ሁሉ ነገር የተሳካለት ሚስትም፣ ልጆችም አፍርቶ ጥሩ ስራ እየሰራ የሚኖር ሰው ነበር፡፡ በህይወቱ ግን፤ ቅር የሚለው አንድ ሰው ነበር፡፡ ስለዚህም አንድ ቀን፤
“ዕውነት መጥፋቷ በጣም ቅር ይለኛል” አላት ለባለቤቱ፡፡
“እንግዲያው እውነትን ራስህ ፈልጋት” አለች ባለቤቱ፡፡
ሰውየው ሁሉንም ንብረቱንና ቤቱን ሁሉ ለባለቤቱ ተወላት፣ በስሟ አደረገላትና ተሰናበታት፡፡
ከዚህ በኋላ ወደ መንገድ ወጥቶ ዕውነትን ለማግኘት ከለማኝ ጀምሮ ማነጋገር ጀመረ፡፡
ተራሮችን ፈተሸ፡፡ ሸለቆዎችን አየ፡፡ ትናንሽ መንደሮችንና ከተሞችን ጎበኘ፡፡ ጫካዎችን ዳሰሰ። በሰፋፊ ባህር ዳርቻዎች ሁሉ ዞረ፡፡ ጨለማን አየ፡፡ የቆሸሹ ቦታዎችንና በአበባ የተሞሉ አትክልት ቦታዎችን ሁሉ ዘልቆ አስተዋለ፡፡ ቀኖችን አጠና፡፡ ሳምንታትን ቃኘ፡፡ ወራትን ተመራመረ፡፡ ዕውነትን አላገኛትም፡፡
አንድ ቀን ከተራራ አናት ላይ፤ አንድ ትንሽ ዋሻ ውስጥ እውነትን አገኛት፡፡
እውነት አንዲት የጃጀች አሮጊት ናት፡፡ ብልህ ናት፡፡ አስተዋይ ናት፡፡ በመላ ድዷ ላይ የሚታየው አንድ ጥርስ ብቻ ነው፡፡ ፀጉሯ ሸብቶ በትናንሹ ተገምዶ ወደ ማጅራቷ ወርዶ ቅባት የበዛበት ቀጭን ዛብ ፈጥሯል፡፡ የፊቷ ቆዳ የደረቀ ብራና ከመምሰሉም ባሻገር በአጥንቷ ላይ ያላግባብ የተጣበቀ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ ይህ ሁሉ እንዳለ ሆኖ፤ በእድሜ ብዛት የተንጨፋረረ እጇን በለሆሳስ ስታወዛውዝ፣ ድምጿን ዝቅ አድርጋ ስታወጣውና በዜማና ጥርት ባለ ምት የተቃኘ ቅላፄ ስትሰጠው ሰውዬው አየና፤ እውነትን ማግኘቱ ገባው፡፡
ከእሷ ጋር አንድ አመት ከአንድ ቀን ለመቆየት ወሰነ፡፡ የምታስተምረውን ሁሉ ተማረ፡፡ አንድ አመት ከአንድ ቀኑ እንደተገባደደ፤ በዋሻው መግቢያ በር ላይ ቆሞ፤ ወደ ቤቱ ለመሄድ እየተዘጋጀ፤
“የእውነት እመቤት ሆይ! እስካሁን ይሄን ያህል እውነት አጎናፀፍሽኝ፡፡ ማወቅ ያለብኝን እውነትም ሰጠሽኝ፡፡ ከዚህ ተለይቼ ስሄድ ግን ለውለታሽ አንድ ካሳ ልሰጥሽ የግድ ነው፡፡ ስለዚህ፤ ምን ባደርግልሽ ትወጃለሽ?”
እመቤት እውነት ወደ አንድ አቅጣጫ ጭንቅላቷን ዘመም አድርጋ ማሰብ ጀመረች፡፡ ከዚያም የአረጀ ጣቷን ወደ ላይ ከፍ አድርጋ አንስታ፤
“ወደፊት ወደ ዘመዶችህና ማህበረሰብህ ስትሄድ፣ መቼም ስለእኔ መናገርህ አይቀርም፡፡”
“አዎ መናገሬማ አይቀርም፡፡”
“ያኔ አደራህን፤ ወጣትና ቆንጅዬ መሆኔን ንገራቸው” አለችው፡፡
***
ከላይ የተነገረውን ተረት የሰሙ አያሌ ፈላስፎች፣ ስለ እውነት ያላቸውን ግምት በተለያየ አቅጣጫ ገልፀውታል፡፡
አንደኛ፡ እውነት፤ አሮጊት ሆና ስታበቃ፣ ስለራሷ የሚነገረው እውነት የወጣት እንዲሆን ትፈልጋለች፡፡
ሁለተኛ፡ እውነት፤ አስቀያሚ ሆና ስታበቃ፣ አስቀያሚ መሆንዋን መገንዘብ እንዲቻል የማትሻ መሆኗን ይጠቁማል፡፡
ሶስተኛ፡ እውነት፡ እውነት ትሁን እንጂ ስለእሷ የሚነገረው የተለየና ስሟን የሚያስጠራ መሆኑን መፈለጓን ልታሳይ ትመኛለች፡፡
አራተኛ፡ እውነት፤ እርጅናዋ ሳይሆን ወጣትነቷ እንዲታይላት እንደምትፈልግ መገንዘብ ተፈላጊ መሆኑን አስተውሉ ትላለች፡፡
አምስተኛ፡ እውነት፤ ምን አስቀያሚና መልከ-ጥፉ ብትሆን፣ ቆንጆና ወጣት መሆንዋን በመንገር ስለራሷ ለመዋሸት መቻልዋን ለማረጋገጥ ትፈልጋለች፡፡
በሀገራችን አያሌ እውነቶች ውሸት የሚመስሉበት፤ አያሌ ውሸቶችም እውነት የሚመስሉበት ሁኔታ መኖሩን ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ እውነት አንፃራዊ ነው የሚለው እውነታ በተደጋጋሚ የተወሳ ቢሆንም፤ አንፃራዊነቱ በማን እይታ እንደሆነ ማስተዋልም አንድ አይነተኛ አስተውሎትን መጠየቁ ዋና ነገር ነው፡፡ የተማረ ሁሉ የተማረ ተብሎ መወሰዱ፤ ያልተማረም ሆኖ እንደተማረ የሚያስቆጥር የልምድና የስልጣን አቅም ሊያበጅ መቻሉ፤ አገር-ወዳድ የሚመስለው ሁሉ አገር-ወዳድ አለመሆኑ፤ ዝም ያለ ሁሉ ከአላዋቂ መቆጠሩ፤ በአንፃሩ የሚናገር ሁሉ አዋቂ መምሰሉ፤ በአንድ ወንበር ላይ ረጅም ጊዜ የተቀመጠ ሁሉ ለወንበሩ በልክ የተሰፋ መምሰሉ፤ ለውጥ የጠየቀ ሁሉ ተፃራሪና  አፍራሽ ተብሎ መፈረጁ ወዘተ… በአንድ ታሪካዊ ወቅት እውነት ከተባሉ የማያወላውል እውነት እንደሆኑ መጣፋቸው በተደጋጋሚ የሚታዩና የታዩ ነገሮች ናቸው፡፡ ስለ ዲሞክራሲ የለፈፈ ዲሞክራሲያዊ፣ ስለ ፍትህ የለፈፈ ፍትሃዊ፣ ስለ መልካም አስተዳደር የተናገረ መልካም አስተዳደር ወዘተ… ተደርጎ መታሰቡ፤ ሁልጊዜ እውነት ነው ወይ? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ በተግባር የተፈተሹ አያሌ ሰዎች የሚለፍፉትን አልሆኑምና እውን የሚሰብኩትን የሚተገብሩ ሰዎች ናቸውን? ብሎ፤ ቆም ብሎ ማሰብ ያባት ነው፡፡ ስለማያምኑበት ነገር ጮክ ብለው የሚናገሩ ጥቂቶች አይደሉም። “አስተውለህ ተናገር፤ ዋኝተህ ተሻገር” መባል ያለባቸው ጥቂቶች አይደሉም፡፡ በእውቀት፣ በልምድ፣ በመስዋእትነትና በመሳሰሉ መለኪያዎች ሳይሆን ጠባብ-የወፍ ቤት ያስተቃቅፋል በሚለው መሰረት ብቻ ያወቁ፣ ልምድ ያዳበሩና ለጉዳዩ አግባብ ያላቸው በመምሰል ወደ ሰገነቱ የተጠጉ ምን ያህል ናቸው? መስሎ- በማደርና በማስመሰል ካባ ከሞቀው ጎራ የተቀላቀሉ ምን ያህል ናቸው? ተቃዋሚ በመምሰልስ ብቻ ሃቀኛ ለመምሰል የሚሞክሩ ሃሳዊ-መሲሃን ምን ያህሉ ናቸው? በሙስና ተዘፍቀው ስለ ሙስና የሚያወሩስ? ይህን መመርመር ተገቢ ነው፡፡
“ጉንዳን መንገድ ሳይቸግረው ይጋጫል” እንዲሉ፣ በሆነ ባልሆነው ለግጭት ሲሉ የሚጋጩ ምን ያህል ጠብ-ጫሪዎች አሉ? ያጠያይቃል፡፡ ያነጋግራል፡፡ በጠቡ ማን ተጠቃሚ ይሆናል? የሚለውም የዛኑ ያህል ያጠያይቃል፡፡ ጠብ ያለሽ በዳቦ ማለት እንደ ትግል ሥልት ከተያዘ፣ አገር የጠብ መናኸሪያ እንዳትሆን ያሰጋል፡፡ በፍርሃት ላይ የተመሰረተ፣ በአለማወቅ ላይ የተመሰረተ፣ በሀገርና በህዝብ ጥቅም ላይ ያልተመሰረተ አካሄድን ተጠንቅቆ ማስወገድ ያሻል፡፡ በማናቸውም ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ገዢና ተገዢ፣ ተዋናይና ተንቀሳቃሽ፣ ተቃዋሚና ተቃውሞ-ተቀባይ ምኔም ተለዋጭ ናቸው፡፡ አገርና ማረፊያቸው መድረክ ብቻ ነዋሪ ናቸው፡፡ ኢኮኖሚ ቢዳከም፣ ፖለቲካ ቢጣመም፣ ማህበራዊ ህይወት ቢቃወስ፤ አገር ነዋሪ ናት! ገደል የገባ ነው እንጂ ገደል ይሰበራል ወይ? ይላሉ አበው፡፡ ይሄንኑ ሊያስረዱን መሆኑን በጥሞና ማስተዋል ይበጃል፡፡
እንግዲህ አሮጌውን 2015 ዓ.ም ሸኝተን፣ አዲሱን 2016 ዓ.ም ልንቀበል ዋዜማ ላይ ነን፡፡ ከሁለት ቀናት በኋላ አዲሱ ዓመት ይጠባል፡፡ አዲሱ ዓመት በእውነት አዲስ እንዲሆን አምስቱ ህዋሶቻችንን በሚገባ እናንቃቸው፡፡ ዐይናችን በቅጡ ይይ፡፡ ጆሮአችን በተገቢው መጠን ይከፈት፡፡ ምላሳችን ሃቅ ይልመድ፡፡ አፍንጫችን መዓዛ ይለይ፡፡ እጃችን መጨበጥ ይወቅ፡፡ ከአምስቱ ህዋሶቻችን የሚያመልጥ አንዳችም የአገር ጉዳይ የለም፡፡ ልብ ለልብ፣ አዕምሮ ለአዕምሮ፣ ቋንቋ ለቋንቋ የማንጠፋፋበት፣ የምንደማመጥበት፣ አዲስ ሃሳብ የምንቀበልበት የሰለጠነ መድረክ ይፈጠር ዘንድ ጠባቡ እንዲሰፋ፣ አምባገነኑ እንዲገራ፣ ጥጋበኛው እንዲበርድለት፣ አመጸኛው እንዲገታ፣ ለእኔ ብቻ ባዩ እንዲያጋራ፣ ዕብሪተኛው እንዲጨምት፣ ዳተኛው እንዲተጋ፣ ሃሞት-የለሹ እንዲጀግን፣ ሞራለ-ቢሱ እንዲጸና፣ መሃይሙ እንዲማር --- አዲሱን ዓመት በቀና ልቦና ማየትና  ዝግጁ መሆን ይገባናል፡፡
መልካም አዲስ ዓመት!!

በመዲናዋ የምሽት ክለብ የሚያቀነቅኑ ድምጻውያን 100 ሺ ብር ለግሰዋል
“እናንተን መንገድ ላይ የበትንን ዕለት ነው ኢትዮጵያ የታመመችው” -ፕሮሞተር ሰለሞን ገ/ማርያም-
የቀድሞ ሠራዊት አባላት ማህበር፣ ዛሬ የሚከበረውን ”የትውልድ ቀን” ምክንያት በማድረግ በችግር ላይ ለሚገኙ ከ100 በላይ  የቀድሞ ሰራዊት አባላት ለአዲስ ዓመት መዋያ የሚሆን የገንዘብ ድጋፍ አደረገ፡፡

የቀድሞ ሰራዊት አባላት ማህበር ፕሬዚዳንት ሃምሳ አለቃ ብርሃኑ ዛሬ 9 ሰዓት ላይ በአራዳ ክፍለከተማ አዳራሽ በድጋፍ አሰጣጥ ሥነሥርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ “እናንተ የአገር ባለውለታ ናችሁ፤ አገር በውስጥም በውጭም ጠላቶች ስትፈተን መስዋዕትነት ከፍላችሁ ለዛሬ አድርሳችኋታል፤ለዚህ ነው መንግሥት የተውልድ ቀን ብሎ በሰየመው በዛሬው ዕለት ከቅን ኢትዮጵያውያን ያሰባሰብነውን የገንዘብ ድጋፍ ልናደርግላችሁ የተሰባሰብነው፡፡” ብለዋል፡፡

የማህበሩ የውጭ ድጋፍ አሰባሳቢ ፕሮሞተር ሰለሞን ገ/ማርያም በበኩሉ፤ “እናንተ የአገር ባለውለታ ናችሁ፤ በየዓመቱ እናንተ ፊት ቆሜ ተመሳሳይ ነገር ነው የምናገረው፤ እንደ አገር እናንተ የአገር ባለውለታ መሆናችሁን ሁሉም ሲረዳ ነገሮች ይለወጡ ይሆናል፤እኛ አሁንም የምናደርግላችሁን ከቁምነገር አትቁጠሩት፤ እናንተ ነፍሳችሁን ሰጥታችሁ ነው አገራችሁን ያቆያችሁት፡፡” ሲል ተናግሯል፡፡

“እናንተ ላይ የፈጸምነው ግፍ ነው ኢትዮጵያ ላይ የምናየውን ችግር ያመጣው፤ እናንተን መንገድ ላይ የበትንን ዕለት ነው ኢትዮጵያ የታመመችው፤እናንተን ይቅርታ የጠየቅን ዕለት ሁሉም ነገር ይለወጣል ብዬ አስባለሁ” ብሏል፤ ፕሮሞተር ሰለሞን፡፡

 የገንዘብ ድጋፉን በአገር ውስጥና በውጭ ከሚገኙ ደጋግና ቀና ኢትዮጵያውያን ማሰባሰባቸውን የገለጸው የማህበሩ የውጭ ድጋፍ አሰባሳቢ ፕሮሞተር  ሰለሞን፤ ድጋፉን ላደረጉት ወገኖች ሁሉ በቀድሞ ሰራዊት አባላት ማህበር ስም ያመሰገነ ሲሆን ለለጋሾቹም የዕውቅና ሰርተፊኬት ተበርክቶላቸዋል፡፡

ድጋፉን ካደረጉት መካከል እዚሁ በመዲናችን  ፓስዎርድ ላውንጅ (በሌላ ስሙ ፍቅር ኮተት) በተባለ የምሽት ክለብ  የሚያቀነቅኑ ሦስት ድምጻውያን (ካሣሁን እሸቱ፣ አዲስ ሙላትና ታረቀኝ ሙሉ) የሚገኙበት ሲሆን፤የአንድ ምሽት ገቢያቸውን 100ሺ ብር መለገሳቸው ታውቋል፡፡
በተመሳሳይ፤ የጃሞ ትሬዲንግ ባለቤት 50ሺ ብር፣ በውጭ የሚኖር ሳምሶን ተሾመ የተባለ ኢትዮጵያዊ 50ሺ ብር፣ ጠበቃ ሼክስፒር ፈይሳ 30ሺ ብር፣ የትሬይ ትሬዲንግ ባለቤት ደግሞ 25ሺ ብር ለቀድሞ ሰራዊት አባላት ድጋፍ አድርገዋል፡፡
 
በዛሬው ዕለት  የገንዘብ ድጋፍ  ከተደረገላቸው መካከል የአምስት ልጆች እናት የሆኑትና  ባለቤታቸው  በጦርነት ከተሰዋ አንድ ዓመት ቢሆነውም፣ መርዶውን የሰሙት ከሰሞኑ መሆኑን ለአዲስ አድማስ የተናገሩት  ወ/ሮ አበበች ድሪባ ይገኙበታል፡፡

 ለአዲስ ዓመት በዓል በተደረገላቸው ድጋፍ ደስተኛ መሆናቸውን በመግለጽ፣ ማህበሩን ያመሰገኑት ወ/ሮ አበበች፤ ከዚህ ቀደም ሻይ ቡና እየሸጡ ቤተሰባቸውን ያስተዳድሩ እንደነበር ጠቁመው፣ አሁን ግን የሚሰሩበት ቦታ በመፍረሱ ለችግር መዳረጋቸውን ተናግረዋል፡፡ መንግሥት የተሻለ ድጋፍ ቢያደርግላቸው እንደሚወዱ የገለጹት  እኒሁ እናት፤ በተለይ ለእርሳቸውና ልጆቻቸው መንግሥት  ማረፊያ ቤት እንዲሰጣቸው ተማጽነዋል፡፡

 የቴሌግራም ቻናልችንን  በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

ኤግል ኮሌጅ በመጀመሪያ ድግሪ መርሃግብር ያስተማራቸውን 405 ተማሪዎች፣ በትላንትናው ዕለት ቅዳሜ  ከጠዋቱ 2፡00 እስከ 5፡30 በኦሮሚያ ባህል አዳራሽ አስመረቀ፡፡
ከማኔጅመንት የትምህርት ክፍል የላቀ ውጤት በማስመዝገብ የዋንጫ አሸናፊ የሆነው ተመራቂ ዮናስ ገ/አማኑኤል፤ በትጋት የሰራና የደከመ ተማሪ ሁሌ ለላቀ ውጤት እንደሚበቃ ተናግሯል፡፡

 ቂሊንጦ ዋልያ ፋብሪካ እንደሚሰራ ለአዲስ አድማስ የጠቀሰው  ተመራቂው፣ ለሁለተኛ ድግሪው የመማር ዕቅድ እንዳለው ጠቁሟል፡፡
ከአካውንቲንግና ፋይናንስ የትምህርት ክፍል 3.4 በማምጣት በከፍተኛ ውጤት የተመረቀችው ወጣት ቃልኪዳን አንጋሳ በበኩሏ፤ ከሥራ ጋር  መማር ከባድ ቢሆንም ተግታ በማጥናት ለዚህ ውጤት መብቃቷን ተናግራለች፡፡

”መጀመሪያ ላይ አጋዥ መምህራን በቀላሉ ስለማናገኝ ትንሽ ተቸግረን ነበር፤ ነገር ግን ጥሩ መምህራን ነበሩን፤ ኮሌጁም ጥራት ያለው ትምህርት ነው የሚሰጠው፡፡” ስትልም አክላለች - ተመራቂዋ፡፡

የኤግል ኮሌጅ ምክትል ዲን ዶ/ር ሃብታሙ አበራ ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት፤ ኮሌጁ በ2011 ዓ.ም በትምህርት ባለሙያዎች የተመሰረተ ሲሆን፣ ዓምና 114 ተማሪዎችን አሰልጥኖ ማስመረቁን አስታውሰዋል፡፡
 
“ኮሌጃችን የትምህርት ጥራት ላይ አይደራደርም ፤ እኛ ለጥራት ነው የምንሰራው፤ጥራትና ትርፍ ደግሞ አብሮ አይሄድም፤” ያሉት ምክትል ዲኑ፤ በአሁኑ ተጨባጭ ሁኔታ እዚህ አገር ኮሌጅ ከፍቶ ትርፍ ለማግኘት መሞከር ከባድ ነው ብለዋል፤ መሰረታዊ ወጪዎችን መሸፈን እስከተቻለ ድረስ ብዙ ለማትረፍ እንደማይጨነቁ በመግለጽ፡፡
ኤግል ኮሌጅ ተማሪዎችን በተለያዩ የትምህርት መርሃግብሮች አሰልጥኖ ሲያስመርቅ የዘንድሮው ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡

ኮሌጁ ከኢፌዲሪ ትምህርትና ሥልጠና ባለሥልጣን ባገኘው ዕውቅና መሰረት፣ ከመማር ማስተማር በተጨማሪ በጥናትና ምርምር ሥራዎች ላይ በንቃት የሚሳተፍ ሲሆን፤በማህበረሰብ አገልግሎት በዙሪያው ላሉ የመንግሥትና የግል ተቋማት የማህበረሰብ ተኮር ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት፣ ማህበረሰባዊ ሃላፊነቱን እየተወጣ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 የቴሌግራም ቻናልችንን  በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

,

  በባሮክ ኤቨንት ኦርጋናይዘር የተዘጋጀው “መርካቶን በሚሊኒየም” የአዲስ ዓመት የንግድ ኤግዚቢሽንና ባዛር፣ ባለፈው ቅዳሜ ከሰዓት በኋላ በሚሊኒየም አዳራሽ በይፋ ተከፍቷል፡፡
 እስከ ጳጉሜ 6 ቀን 2015 ዓ.ም ለ17 ቀናት የሚዘልቀው የንግድ ባዛሩ፤ ለሸማቹ ማህበረሰብ መሰረታዊና የበዓል ፍጆታዎች በስፋትና በቅናሽ የሚቀርብበት መድረክ ነው ተብሏል፡፡
“ይዝናኑ ይሸምቱ“ በሚል በሚካሄደው በዚህ የአውዳመት የንግድ ባዛር ላይ፣ የ40 በመቶ የዋጋ ቅናሽ እንደሚደረግ  ተጠቁሟል፡፡ “መርካቶን በሚሊኒየም” በተሰኘው የንግድ ባዛር ላይ  በርካታ የአገር ውስጥና የባህርማዶ አምራቾች፣ አስመጭና ላኪዎች እንዲሁም ጅምላ አከፋፋይና ችርቻሮ ነጋዴዎች እንደሚሳተፉበት ታውቋል፡፡
አዘጋጆቹ በሰጡት  መግለጫ፤ ይሄ  ታላቅ የአውዳመት የንግድ ትርኢት፤ ነጋዴዎች ለሸማቹ እጅግ ቅናሽ በሆነ ዋጋ ጥራት ያላቸው ፍጆታዎችን በሰፊ አማራጭና ዓይነት የሚሸጡበት፣ ሻጭና ገዥ በአንድ ቦታ ላይ የሚገበያዩበት፤ እንዲሁም መሰረታዊና የበዓል ፍጆታዎች በስፋት የሚቀርቡበት ይሆናል ብለዋል፡፡
እስከ አዲስ ዓመት ዋዜማ ለተከታታይ ቀናት የሚዘልቀው የንግድ ኤግዚቢሽንና ባዛሩ፣ ትርፍን ብቻ ታላሚ አድርጎ የተዘጋጀ አይደለም የተባለ ሲሆን፤ ባለፈው ቅዳሜም  የተከፈተው ባልተለመደ መልኩ  500 ለሚሆኑ የከተማዋ ነዋሪዎች  ማዕድ በማጋራት ነው።
ከዚህ በተጨማሪም፣ 15 የሚሆኑ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ሥራቸውንና ዓላማቸውን ለህብረተሰቡ የሚያስተዋውቁበት ቦታ በዚሁ በሚሊኒየም አዳራሽ በነጻ እንደተሰጣቸው የባዛሩ አዘጋጆች አስታውቀዋል፡፡    
 “መርካቶን በሚሊኒየም”  የንግድ ባዛር፣ የተለያዩ ምርቶችና የበዓል ፍጆታዎች ለሽያጭ የሚቀርቡበት  ብቻ ሳይሆን ህብረተሰቡ የሚዝናናበትም መድረክ ነው ያሉት አዘጋጆቹ፤ ለዚህም በየቀኑ ታዋቂና ተወዳጅ ድምጻውያን የሚያቀነቅኑበት የሙዚቃ ድግስ እንደሚቀርብ ጠቁመዋል፡፡  


 • አምና ከ400 በላይ፣ ዘንድሮ ከ300 በላይ ሰዎች ህይወት በትራፊክ አደጋ ተቀጥፏል - ትራፊክ ፖሊስ


         በአገሪቱ እንዲሁም በመዲናዋ  እየተከሰተ ያለውን የትራፊክ አደጋ በከፍተኛ ደረጃ ይቀንሳል የተባለ በተሽከርካሪዎች  ላይ የሚገጠም አውቶማቲክ አደጋ ጠቋሚ መሳሪያ ይፋ ተደረገ።
አዲሱ የቴክኖሎጂ ፈጠራ የተሰራው አቶ ጎይቶኦም ገ/ዮሐንስ በተባሉ የፈጠራ ባለሙያ ሲሆን፤ በዚህም የፈጠራ ሥራቸው ከአዕምሮአዊ ንብረት ባለስልጣን ፓተንት ማግኘታቸው ታውቋል። ከትራንስፖርትና ሎጂስቲክ ሚኒስቴር እንዲሁም ከአጋር ተቋማትም የድጋፍ ደብዳቤና ዕውቅና አግኝተዋል ተብሏል።
የፈጠራ ባለሙያው አቶ ጎይቶኦም ገ/ዮሐንስ፣ ይህን የፈጠራ ሥራቸውን አስመልክቶ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ በሃርመኒ ሆቴል ለባለድርሻ አካላትና ለሚዲያ ባለሙያዎች መግለጫና ማብራሪያ  ሰጥተዋል።
የፈጠራ ባለሙያው በመጀመሪያ ስለ ትራፊክ አደጋ ያብራራሉ፤ ”በተለምዶ አንድ አሽከርካሪ እያሽከረከረ ሳለ ከፊት ለፊቱ ከቀኝ ወደ ግራ የሚያቋርጡ እግረኞች፣ ተሽከርካሪዎች ወይም እንስሳት ሲያጋጥሙት፣ የተሽከርካሪውን ፍጥነት ቀንሶ በመቆም በግራ ስኮፒዮ ሲመለከት በሱ ግራ በኩል ደርቦ የሚመጣ ተሽከርካሪ ካየ፣ ግራ እጁን አውጥቶ በማወዛወዝ፣ በግራ በኩል ደርቦ ለመጣው አሽከርካሪ ፍጥነቱን እንዲቀንስና እንዲቆም በማድረግ፣ ከቆመው ተሽከርካሪ በኩል በሚሻገሩት እግረኞችም ሆነ ተሽከርካሪዎች ላይ አደጋ እንዳይደርስ ያደርጋል፡፡”
ባለሙያው ማብራሪያቸውን ሲቀጥሉም፤ “ነገር ግን በተቃራኒ በኩል እግረኞችም ሆኑ ተሽከርካሪዎች ከግራ ወደ ቀኝ በሚያቋርጡበት ጊዜ፣ በቆመው ተሽከርካሪ ቀኝ ጎን ደርቦ ለሚመጣው አሽከርካሪ ምልክት መስጠት ስለማይቻል ከ80 በመቶ በላይ በእግረኞች ላይ የሚደርሰው አደጋ ከፍተኛውን ድርሻ የሚይዘው በቀኝ ጎን ደርቦ በሚመጣ አሽከርካሪ የሚከሰተው  ነው፡፡ ይህም የሚሆነው ልክ እንደ ግራ እጃችን ቀኝ እጃችንን አውጥተን ምልክት ለመስጠት ስለሚያዳግተን፣ እንደ አማራጭ የምንጠቀመው ሃዛርድ ወይም ቀይ ፍሬቻን በማብራት ነው፡፡ ሆኖም በእጃችን የምንሰጠውን ያህል አያግዝም፡፡ በዚህ የተነሳ ደርቦ የሚመጣው ተሽከርካሪ ፍጥነቱን ጨምሮ በመሄድ ከፍተኛ አደጋ ያደርሳል፡፡” ይላሉ፡፡
አዲሱ የፈጠራ ሥራቸው ይህን ችግር ትርጉም ባለው መልኩ እንደሚፈታው የተናገሩት አቶ ጎይቶኦም፤ የቴክኖሎጂ ፈጠራው መኪና ተከልለው በሚሻገሩ እግረኞች ላይ የሚደርስን አደጋ በከፍተኛ ደረጃ ለመከላከል  የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡ ይህ አውቶማቲክ አደጋ ጠቋሚ መሳሪያ፣ በተሽከርካሪው ዳሽ ቦርድ ላይ በቀኝ ወይም በግራ በኩል  የሚገጠም መሆኑንም አክለው ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ትራፊክ ጽ/ቤትን ወክለው በመግለጫው ላይ የተገኙት ኮማንደር ሙሉጌታ በሰጡት አስተያየት፤ ክቡሩን የሰው ልጅ ህይወት ለመታደግ አንድ ሰው እንዲህ ያለ የፈጠራ ሥራ ይዞ ሲመጣ በእጅጉ ሊመሰገንና ሊታገዝ ይገባዋል ብለዋል።
አምና በመዲናዋ በደረሰ የትራፊክ አደጋ ከ400 በላይ ሰዎች ህይወት መጥፋቱን እንዲሁም ዘንድሮ ከ300 በላይ ሰዎች ህይወት መቀጠፉን የጠቆሙት ኮማንደር ሙሉጌታ፤ የትራፊክ አደጋን በሂደት ዜሮ ማድረግ የምንችለው በዚህ ዓይነት አገር በቀል የቴክኖሎጂ ፈጠራ ብቻ ነው ብለዋል።
ሌላው የትራፊክ ጽ/ቤት ተወካይ በበኩላቸው፤ በዚህ አሁን በተሰራው የቴክኖሎጂ ፈጠራ የትራፊክ አደጋን ሙሉ በሙሉ ባንቀንሰው እንኳን ወደ ግማሽ ልናደርሰው እንችላለን ብለዋል፤ ለፈጠራ ሥራው ባለቤት  ትልቅ አክብሮት እንዳላቸው በመግለጽ፡፡
ከትራፊክ ጽ/ቤት የተወከሉትን ሃላፊዎች ጨምሮ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በአቶ ጎይቶኦም የፈጠራ ክህሎት የተሰራው የቴክኖሎጂ ፈጠራ፣ የትራፊክ አደጋን በመቀነስ ረገድ እጅግ ጉልህ ሚና እንደሚኖረው እምነታቸውን የገለጹ ቢሆንም፣ ከፍተኛ ስጋት እንዳላቸውም አልሸሸጉም፡፡ ይኸውም የቴክኖሎጂ ፈጠራው በፋይናንስ እጦት አሊያም በሌላ ምክንያት ተግባራዊ ሳይሆን እንዳይቀር የሚል ነው ስጋታቸው፡፡
የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ ከሚኖረው ከፍተኛ አስተዋጽኦ  አንጻር የቴክኖሎጂ ፈጠራው በፍጥነት ወደ ትግበራ መግባት አለበት  ያሉት ባለድርሻ አካላቱ፤ ለዚህም ባለሃብቶችና የሚመለከታቸው ወገኖች ሁሉ ተባብረው ይህን ፕሮጀክት እውን እንዲያደርጉት አበክረው  ጠይቀዋል።
ፕሮጀክቱን በገንዘብ የሚደግፉ አጋሮችን እያፈላለግን ነው ያሉት የፈጠራ ባለቤቱ አቶ ጎይቶኦም በበኩላቸው፤ “አይዲያን ፋይናንስ” የማድረግ አሰራር ለጀመረው የኢትዮጵያ ልማት ባንክም ማመልከቻ ማስገባታቸውን ገልጸዋል።
አሁን 40 ሚ. ብር ብናገኝ በሁሉም ክልሎች  ወደ ትግበራ መግባት እንጀምራለን” ያሉት የፈጠራ ባለሙያው፤ ”ያን ያህል ገንዘብ ካልተገኘ ብለን ግን አንቀመጥም፣ ባገኘነው ያህል የማምረት ሥራ ውስጥ  እንገባለን” ብለዋል።
በመጨረሻም በሰጡት የማረጋገጫ ቃል፤ “ከዚህ በኋላ ይህ ፕሮጀክት ወደ ኋላ  እንደማይመለስ ቃል እገባለሁ፤ ከባለሃብቶችና የፋይናንስ ተቋማት ጋር አጋርነት በመፍጠር ተግባራዊ ይደረጋል” ብለዋል፤ አቶ ጎይቶኦም ገ/ዮሐንስ፡፡

 የእንግሊዝ ዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንት (ቢ.አይ.አይ) እና የኔዘርላንድ የሥራ ፈጠራና ልማት ባንክ  (ኤፍ.ኤም.ኦ)  እያንዳንዳቸው 20 ሚሊየን ዶላር፣ በድምሩ 40 ሚሊየን ዶላር ብድር  ለዳሸን ባንክ  ማቅረባቸውን ሰሞኑን  ይፋ አድርገዋል፡፡
 ይህ የብድር አቅርቦት ኢትዮጵያ ለውጪ ገበያ የምታቀርበውን የግብርና ምርት ለማሳደግና በእጅጉ አስፈላጊ የሆነውን የውጪ ምንዛሬ አቅርቦት ለማሻሻል ያስችላል ተብሏል፡፡
ቢ.አይ.አይ እና ኤፍ.ኤም.ኦ ለዳሸን ባንክ ያቀረቡት ብድር፤ በኢትዮጵያ 80% የህብረተሰብ ክፍል በተሰማራበት፣ ለጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት 39% ድርሻ ላለውና ለወጪ ንግዱ 90% አስተዋጽኦ ለሚያበረክተው  የግብርና ዘርፍ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግ  ተነግሯል፡፡
የቀረበው ብድር ባንኩ የውጭ ምንዛሪ ግኝትን ለማሳደግ ለሚያደርገው ጥረት የበኩሉን እገዛ እንደሚያደርግ የተጠቆመ ሲሆን፤ በተለይ በእርሻ ስራ ላይ ለተሰማሩ ምርታማነትን ለመጨመር የሚያስችሉ ግብአቶችን በማሟላት ከኤክስፖርት የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ አስተዋጽኦ ያበረክታል ተብሏል፡፡
የፋይናንስ ተቋማት ትብብር ለግሉ ዘርፍ እድገት ጉልህ ሚና እንዳለው የሚታወቅ ሲሆን፤ በዚህ ትብብር ቢአይአይ እና ኤፍኤምኦ፣. የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እ.ኤ.አ በ2021 አዲስ ባወጣው የውጭ ምንዛሪ ማቀላጠፊያ መመሪያ መሠረት፣ በኢትዮጵያ ለሚገኝ የፋይናንስ ተቋም በውጭ ምንዛሪ የቀረበ የረዥም ጊዜ ብድር ሲሰጡ የመጀመሪያዎቹ ናቸው፡፡ ይህ ፋና ወጊ ተግባር ገበያውን በማነቃቃት ከዓለም አቀፍ መዋዕለ-ንዋይ አቅራቢዎች ተጨማሪ ሀብት ለማሰባሰብ የሚያስችል መተማመንን ለመገንባት እንደሚያግዝ ተጠቁሟል፡፡
በዚህ ትብብር ቢአይአይ እና ኤፍኤምኦ ከዳሸን ባንክ ጋር በአመራር ስጋት አስተዳደር፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በማህበራዊና ስርዓተ - ጾታ ዘርፎች ዙሪያ ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን በኢትዮጵያ ለማስተዋወቅና ለማስረፅ  በቅርበት ይሰራሉ ተብሏል፡፡
የዳሸን ባንክ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አስፋው ዓለሙ ብድሩን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፤ ”ተምሳሌታዊ በሆነው ቢአይአይ እና ኤፍኤምኦ በትብብር የሰጡን ብድር የውጭ ምንዛሪ ማመንጨት የሚችሉ የሀገር ውስጥ ባለሀብቶች ከውጭ የፋይናንስ ተቋማት በኢትዮጵያውያን ባንኮች በኩል ፋይናንስ ማግኘት የሚችሉበትን የብሄራዊ ባንክ መመሪያ ተግባራዊ በማድረግ ፋና ወጊ በመሆናችን ደስታችን የላቀ ነው፡፡ በውጭ ምንዛሪ የቀረበው ብድር በውጭ ንግድ ላይ የተሰማሩ ደንበኞችን ለማገዝ እንደሚውልና ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በእጅጉ የሚያስፈልገውን የውጭ ምንዛሪ ባንካችን ከሁለቱ ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ጋር በመስራቱ ለሀገር የሚተርፍ በርካታ ልምድ፣ እውቀትና የአሰራር ዘይቤ ተቀስሟል፡፡ ባንካችን ከሁለቱ የልማት አጋሮቹ ላገኘው ድጋፍ ከፍተኛ ምስጋና አለን።” ሲሉ ገልጸዋል፡፡
ሁለቱ ተቋማት በዳሸን ባንክ ውጤታማነትና በኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ ላይ ሙሉ እምነት በመጣል የፋይናንስ አቅርቦት በማድረጋቸው፣ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸውም ዋና ስራ አስፈጻሚው ተናግረዋል፡፡


የቢአይአይ ዋና ስራ አስፈጻሚና የፋይናንሺያል አገልግሎት ኃላፊ ስቴፈን ፕሪስትሊ፤ በአለም አቀፍ ኢንቨስትመንት ላይ የመጀመሪያዎቹ ተቋማት በመሆናቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸው፣ ቢአይአይ በኢትዮጵያ ከ50 አመታት በፊት ኢንቨስት ማድረጉንም አስታውቀዋል፡፡
“በዚህ የፋይናንስ አቅርቦት ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እየከፈተ ወዳለው ገበያ ቀድመን ለመግባት ከቀዳሚዎቹ ውስጥ በመሆናችን ኩራት ተሰምቶናል፡፡ ባለፉት 50 ዓመታት ቢአይአይ በኢትዮጵያ ቀዳሚ መዋዕለ-ነዋይ አፍሳሽ ሆኖ ቆይቷል፡፡  ከኤፍኤምኦ ጋር የደረስንበት አጋርነት ወደ ኢትዮጵያ የፋይናንስ ዘርፍ በልማት የፋይናንስ አቅራቢዎችና የንግድ መዋዕለ-ንዋይ አንቀሳቃሾች ትብብር ሊመጣ የሚችለውን ከፍ ያለ ሀብት አመላካች ነው፡፡” ሲሉ ገልጸዋል፡፡
የኤፍኤምኦ የፋይናንሺያል ኢንስቲትዩሽን ዲፓርትመንት ዳይሬክተር ማርኒክስ ሞንስፎርት በበኩላቸው፤ “ዳሸን ባንክና  ኢትዮጵያ  የውጭ ቀጥታ መዋዕለ-ንዋይና የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት እንዲያገኙ በሚያስችለው በዚህ ፈር ቀዳጅ አጋጣሚ በመሳተፋችን ደስተኞች ነን፡፡
በእጅጉ አስፈላጊ የሆነውን በውጭ ምንዛሪ ብድር በውጪ ንግድ ላይ ያተኮረ ግብርና በመደገፍ ለሥራ ፈጠራና በገጠር አካባቢ የፋይናንስ አካታችነትን በማስፈን አስተዋጽኦ ማድረግ ህልማችን ነው፡፡ ለዚህ ታላቅ ትብብር ዳሸን ባንክንና ቢአይአይን እናመሰግናለን፡፡” ብለዋል፡፡





 ላለፉት አመታት በአገልግሎት ጥራታቸውና በዋጋቸው ተመራጭ የሆኑ የስልክ ምርቶችን ለአገራችን ገበያ ሲያቀርብ የቆየው አያቴል ሞባይል ቴክኖሎጂና ዲዛይን ኩባንያ፤ በአዳዲስ ፈጠራዎች የተሰራውንና ዘመኑ የደረሰበትን የቴክኖሎጂ ደረጃ የሚያሳዩ ኤስ 23+ የተሰኘ አዲስ ሞባይልን በኢትዮጵያ አስመረቀ፡፡
በአገራችን ገበያ በትራንሽን ማኑፋክቸሪንግ ኩባንያ ስር በመስራት አያቴል ብራንድ ስልኮቹን ለአገራችን ገበያ በማቅረብ ላይ የሚገኘው አያቴል ሞባይል ኩባንያ የተለያዩ ሞዴል ስልኮችን በማምረት ለአገራችን ገበያ ሲያቀርብ ቆይቷል፡፡
የዘመኑ የካሜራ ቴክኖሎጂ የተገጠመለትና በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የሚደገፍ ነው የተባለው አዲሱ አያቴል 23+ ሞዴል ስልክ የፊት ለፊቱ 32 ሜጋ ፒክስልና ዋናው ኋላ ካሜራ 50 ሜጋ ፒክስል የያዘና ጥራት ያላቸውን ምስሎች በዝቅተኛ ብርሃን ውስጥም ሆነ በርቀት  ለማንሳት አቅምና ብቃት ያለው መሆኑ በምርቃት ፕሮግረሙ ላይ ተገልጿል፡፡
የአያቴል ሞባይል ኢትዮጵያ ብራንድ ኃላፊ ሚስተር ኤሞን ጃ በዚሁ የምርቃ ፕሮግራም ላይ እንደተናገሩት ለኩባንያው አዲስ የሆነውን 23+ ሞዴል ስልክ በአለም ገበያ ከመቅረቡ በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ ለማስመረቅ መምረጡ ኩባንያው ለኢትዮጵያና ለዜጎቿ የሚሰጠውን ከፍ ያለ ግምት ማሳያ ነው ብለዋል፡፡
16 ጂቢ ራምና 256 ጂቢ ሜሞሪ የተገጠመለት አዲሱ አያቴል ኤስ 23+ በአንድ ጊዜ ብዙ ስራዎችን ለመስራት የሚስችልና ከፍ ያሉ የግራፊክስ ስራዎችን የመስራት የሚስችል አቅም ያለው እንደሆነም ነው በምርቃት ፕሮግረሙ ላይ የተገለፀው አያቴል በአለም አቀፍ ደረጃ ከ50 በላይ በሚሆኑ አዳዲስ ገበያዎች ውስጥ የሚንቀሳቀስ አለም አቀፍ ብራንድ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡



 የአምባሳደር ሆቴልና አፓርትመንት ሥራ አስኪያጅ በፕሬዚዳንትነት ተሾመዋል


        የአዲስ አበባ ሆቴልና ቱሪዝም በለሙያዎች ማህበር ባለፈው ማክሰኞ ነሀሴ 23 ቀን 2015 ዓ.ም ላምበረት አካባቢ በሚገኘው በሀይሌ ግራንድ ሆቴል በይፋ ተመስርቶ ስራ ጀመረ። ማህበሩ ሐምሌ 6 ቀን 2015 ዓ.ም ከሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለልጣን ህጋዊ ሰውነት አግኝቶ መመስረቱን በዕለቱ ለመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ተብራርቷል፡፡
ማህበሩ የአምባሳደር ሆቴልና አፓርትመን ማናጀር የሆኑትን፣ በሆቴልና ቱሪዝም ዘርፍ ከ15 ዓመታት በላይ ልምድ ያካበቱትን፣ በግላቸው የሆቴልና ቱሪዝም ስልጠና ሲሰጡ የቆዩትንና በርካታ ሆቴሎች በማደራጀትና በማማከር ንቁ ተሳትፎ ያደረጉትን አቶ አሸናፊ ሙሉጌታን በፕሬዚዳንትነት ሾሟል፡፡
የማህበሩ መስራች አባላት በሆቴልና ቱሪዝም በዘርፉ ከፍተኛ ልምድ እውቀትና ብቃት  ያላቸው እንዲሁም ለኢንዱስትሪው እድገት የሚቆረቆሩ እንደሆኑ የማህበሩ ፕሬዚዳንት ገልፀዋል፡፡
መስራቾቹ ማህበሩ ከመመስረቱ በፊት “በሙያዬ ለሀገሬ” የተሰኘ የበጎ ተግባር ንቅናቄ ሲያካሂዱ መቆየታቸውን ያብራሩት ፕሬዚዳንቱ በዚህ ንቅናቄ በአዲስ አበባና የተለያዩ ክልሎች በተለይም በኮቪድ 19 ወቅት በርካታ በጎ ተግባራትን ሲያከናውኑ እንደቆዩ ተገልጿል፡፡
ይህም የበጎ ተግባር ንቅናቄ ህልማቸው የነበረውን ይህን ማህበር ለማቋቋም መንደርደሪያ እንደሆናቸው ጨምረው ገልፀዋል፡፡
ከዚህ በኋላ በሆቴልና ቱሪዝም ዘርፍ ያለውን የስነ ምግባር፣ የእውቀትና ክህሎት ክፍተት እንዲሁም የፖሊሲና የህግ ማዕቀፍን ትኩረት ማነስ ለመቅረፍ በርትተው እንደሚሰሩ የገለፁት የማህበሩ ሃላፊዎች ማህበሩ ለባለሙያዎች የመብት መከበርና ተጠቃሚነት፣ የስልጠናና የትምህርት እድሎች እንዲሁም የመሰረተ ልማት ግንባታ መሟላት የበኩሉን አስተዋፅኦ በማድረግ፣ ለኢንዱስትሪው እድገት ወሳኝ ሚና እንደሚጫወት ቃል ገብቷል፡፡ አዲስ አበባ ከኒውዮርክና ከጄኔቭ ቀጥላ ሶስተኛዋ የበርካታ ዲፕሎማቶች መቀመጫ መሆኗን የጠቀሱት የማህበሩ ሃላፊዎች፤ ለዚህች ትልቅ ከተማ የሆቴልና ቱሪዝም አገልግሎት መዘመን፣ ለሀገር ውስጥና ለውጪ ጎብኚዎች የሚመችና የሚመጥን ሙያዊ ልህቀትና ክህሎት እንዲኖር ማህበሩ ከአባላቱ ጋር አበክሮ እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡ ማህበሩ እስከ ምስረታው እለት ድረስ ከ280 በላይ አባባትን መመዝገቡንም አስታውቋል፡፡
በምስረታ በዓሉ ላይ የቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ስለሺ ግርማ፣ የአዲስ አበባ ባህል ኪነጥበብና ቱሪዝም ቢሮ ሃላፊ ሂሩት ካሳው (ዶ/ር) እና ሌሎች በርካታ የዘርፉ ተዋንያንና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል፡፡


 አንድ አዞ ከሚስቱ ጋር በጣም ጥልቅ፣ ጨለማና በፈጣኑ የሚወርድ ወንዝ ውስጥ ይኖር ነበር፡፡ አንድ ቀን ሚስትየው “የዝንጀሮ ልብ አምሮኛል፡፡ በጣም በጣም ርቦኛል፡፡ እንደምንም ብለህ አንድ እንኳን አምጣልኝ እባክህ” ትለዋለች ለባሏ፡፡
“ዝንጀሮ የሚኖረው መሬት ላይ፣ እኛ የምንኖረው ውሃ ውስጥ፤ እንዴት አድርጌ ዝንጀሮ ለመያዝ እችላለሁ? ከራበሽ ሌላ ነገር ብዪ እንጂ የዝንጀሮ ልብ ላገኝልሽ አልችልም፤ የእኔ ቆንጆ!” አላት፡፡
“የኔ ጌታ! እኔ ዕውነቴን ነው የምልህ፤ ልብ ካላገኘሁ መሞቴ ነው፡፡ እንደምንም ብለህ አንድ ፈልግልኝ” ብላ ዓይኗን ከርተት ከርተት እያደረገች ለመነችው፡፡
ባልየው ከወንዙ  ዳርቻ የሚኖር አንድ ቆንጆ ዝንጀሮ እንዳለ ያውቃል፡፡ ግን ያ ዝንጀሮ ጀግና፣ ቀልጣፋና ብልህ መሆኑንም ጭምር ያውቃል፡፡ እሱን፤ እንኳን ገድሎ ልቡን ማግኘት ይቅርና አባርሮ መያዝ እንኳ እንዴት ከባድ ድካም መሆኑን ያውቀዋል፡፡
ያም ሆኖ ባለቤቱ በጣም ስለተማጸነችው ምርጫ አጣ፡፡ ስለዚህም ያንን ዝንጀሮ ማታለል አለብኝ ብሎ አሰበና ዘዴ ዘየደ፡፡ መላው እንዲህ ነው፡- በየቀኑ ከወንዙ ዳርቻ ወጥቶ ፀሀይ ላይ ለጥ ብሎ መተኛት፡፡ ዝንጀሮው ወደ እዚያ ሲመጣ ምንም ፍላጎት ያለው ሳያስመስል ማጨዋወት፡፡ በቃ፡፡
ዝንጀሮው መጣ፡፡ አዞው ማጨዋወቱን ቀጠለ፡፡ ዝንጀሮው ግን በጣም ቀርቦ አልጫወት አለ፡፡ ከአዞ ጋር ብዙ መቀራረብ አጉል እንደሆነ ገብቶታል፡፡ የአዞን ጥርስ ስለት አሳምሮ ያውቀዋል፡፡
እንዲህ እንዲህ እያሉ ሰነባበቱና አንድ ቀን አዞው እንዲህ አለ፤
“በዚህኛው የወንዙ ዳርቻ ያለውን ዛፍ ፍሬ ብቻ ለምን ትበላለህ? በወዲያኛው ዳርቻምኮ በጣም የሚያማምሩ የበሰሉ ፍሬዎች አሉ!”
ዝንጀሮውም፤ “ያማ የማይገኝ ነገር ነው፡፡ እንዴት ብዬ እዚያ ድረስ እሄዳለሁ? ያውም እንዲህ ፈጥኖ በሚፈሰው ወንዝ አቋርጬ እንዴት ብዬ እሻገራለሁ?” አለ፡፡
አዞ፤ “ለእሱ እኳ እኔ አለሁ፤ አዝዬህ በአንድ አፍታ አደርስሃለሁ፡፡” አለና ሰፊ አዟዊ ፈገግታ አሳየው፡፡
ዝንጀሮውም፤ “እንደዚያማ ከረዳኸኝ በጣም እድለኛ ነኝ፡፡ ደግሞም አምንሃለሁ፡፡ አንተ ሽማግሌ አዞ ነህ ሽማግሌ አይዋሽም”
አዞው ከውሃው ወጣ ብሎ ወደ ዳርቻው ተጠጋለትና ዝንጀሮ ፊጥ ብሎ ወገቡ ላይ ሰፈረ፡፡ አዞው ጥሩ ዋናተኛ በመሆኑ ዝንጀሮውን በጥሩ ምቾት ይዞት ይፈስስ ጀመር፡፡
ሆኖም ግማሽ መንገድ እንደሄዱ እዚያ ጨለማና ጥልቅ ወንዝ ውስጥ ይዞት ስምጥ አለ፡፡
ዝንጀሮም፤ “ኸረ! ሰመጥንኮ! ቀስ በል እባክህ!” አለው፡፡
አዞውም፤- “አሁን አለቀልህ፡፡ በቃ ልገልህ እኮ ነው! ለመሆኑ እዚያኛው ዳርቻ ድረስ አዝዬህ የምሄደው በምን ዕዳዬ ነው? ለጽድቅ ብዬ እንዳይመስልህ ወዳጄ፤ ገድዬህ ልብህን ለመውሰድ ፈልጌ ነው፡፡ ባለቤቴ የዝንጀሮ ልብ ካልበላሁ ሞቼ እገኛለሁ ብላኝ ነው”
ዝንጀሮውም ጥቂት አሰበና፤ “አያ አዞ! የልብህን ስለነገርከኝ በጣም አመሰግናለሁ፡፡ ቢያንስ ምን እንደምትፈልግ አሁን ገባኝ፡፡ ግን አንድ ነገር ማወቅ አለብህ፤ ዝንጀሮዎችኮ ልባቸውን በደረታቸው ውስጥ ይዘው ከቦታ ቦታ አይዘዋወሩም፡፡ ምክንያቱን መቼም ሳታውቀው አትቀርም፡፡ ያው ከዛፍ ዛፍ ሲዘሉ ልባቸው እንዳይታጠፍና እንዳይሰባበር ብለው ነው፡፡ እኛኮ ልባችንን በሰውነታችን ውስጥ ይዘን አይደለም የምንንቀሳቀሰው፡፡”
አዞም በነገሩ ተገርሞ፤ “ታዲያ የት ታስቀምጡታላችሁ?” ሲል ጠየቀው፡፡
“እዚያ ጥለነው የመጣነው ጫካ ውስጥ ነዋ! ከዛፎቹ ፍራፍሬዎች መካከልኮ ነው የምንደብቀው” አለና መለሰ፡፡
አዞ፤ “ይገርምሃል፤ ይህንን በጭራሽ አላውቅም ነበር!”
ዝንጀሮ፤ “እንዴ ዓለም ያወቀውን ነገር?! በእርግጥም አንዳፍታ መልሰህ ብትወስደኝኮ፣ ከፍራፍሬዎቹ መካከል ያስቀመጥኩበትን ቦታ አሳይህ ነበር፡፡”
አዞ፤ “ወይ አቶ ዝንጀሮ! በጣም ደግ እንስሳ ነህ አንተ!” አለና ይዞት ወደ ጫካው መመለስ ጀመረ፡፡ እንዲያውም ልብ ለማግኘት በጣም  ስለጓጓ፣ ከቅድሙ በጣም ፍጥነት ጨመረ፡፡ ‘በቃ ሚስቴ የዝንጀሮ ልብ ልታገኝ ነው -አረፍኩ!’ አለ ሳያውቀው ጮክ ብሎ፡፡
ከወንዙ ዳርቻ ሲደርሱ ግን ዝንጀሮ ሆይ፣ ከአዞው ጀርባ ተፈናጥሮ ዘሎ መሬት ዱብ አለ፡፡ ከዚያም፤
“አንተ ጅል ሽማግሌ አዞ! ለመሆኑ በየት አገር ነው ‘ዝንጀሮ ልቡን ጫካ ያስቀምጣል’ ሲባል የሰማኸው?” ደግሞ ባስቀምጥስ ናና ስረቀኝ ብዬ የማሳይህ ይመስልሃል? አየህ አንተ ግዙፍ ነህ፣ ጠንካራ ነህ፣ ኃይለኛና ሁሉን የሚቆራርጥ ጥርስ ያለህ ነህ፡፡ ሆኖም አንጎል የለህም፣ ልብ የለህም፡፡”
ዝንጀሮ ይህን ብሎ ወደ ጫካው እየበረረ ተሰወረ!
***
ልብ ማግኘት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ ልብ መግዛት የሚችል ደግሞ ጥሞና ስክነትና ብልህነት ያለው ነው። በአጉል ድፍረትና በጉልበት የሚመጣን ኃይለኛ ሰው፣ ብልሀት ያለው አነስተኛ ሰው በቀላሉ ይረታዋል፡፡ በሙሉ ልብና በስክነት የተሰላ የጊዜ፣ የቦታና የተግባር ቅንጅት ካለ አገር ታድጋች፡፡ ህዝብ ይጎለብታል። ማናቸውም የፖለቲካ ፓርቲም ሆነ ድርጅት አሊያ ግለሰብ ደህና ልብ ካላገኘ ህዝባዊ አደራን በአግባቡ አይጠብቅም፡፡ ጉልበተኝነትን ከብልህነት ይልቅ ይመርጣልና የበታቾቹን ሁሉ ለመጉዳት ይነሳል፡፡ የዚህ ዓይነቱ መሪ፣ ኃላፊ ወይም የበላይ አለቃ እንደ አዞው በእጁ የገባውን ልብ ጭምር ያጣል፡፡ የፎከረበትን ያፍርበታል፡፡ በስንት መስዋእትነት የተገኘውን ድል እንደ አዞው ሁሉ እርባና - ቢስ ያደርገዋል፡፡
በሀገራችን የተካሄዱ ለውጦች ሁሉ፣ የተካሄዱ እንቀስቃሴዎች ሁሉ፣ የተደረጉ ጦርነቶች ሁሉ የሚጠቁሙት አንድ ቁምነገር አለ፡፡ ሁሉም አሳይቶ - የመንሳት (Missed opportunity) መንገድን ያመላከቱ እንጅ ድልን ያስጨበጡና በእጅ ያቆዩ አይደሉም፡፡ በሰላም በክብ ጠረጴዛ ለሚያልቅ ጉዳይ ሁሉ ጦር ይመዘዛል፡፡ ከሩቅ ያነጣጠሩበትን ባላንጣ በመቀየም ሰበብ ቅርብ ያለውና ልንሰራበት የምንችለው እድል ያመልጣል፡፡ በጊዜያዊነት ስልጣን ላይ የወጣ ዘለዓለማዊ ነኝ ብሎ ተደላድሎ እስኪቀመጥ፣ በኩርፊያ ጊዜና ቦታ እንዲያመቻች እንፈቅድለታለን፡፡ ከመደራደር ይልቅ መግደርደርን በመምረጥ፣ ተገቢው ሰው በተገቢው ቦታ እንዳይቀመጥ አጋጣሚውን እናባክናለን፡፡ ፓርቲና ፓርቲ መክረው ዘክረው፣ ልብ ገዝተው፣ አቅም አበጅተው፣ ለለውጥ እንዳይሰለፉ እርስ በርስ ሲታኮሱ ለበያቸው ሲሳይ ይሆናሉ፡፡ በፍጭቱ ውስጥ ቀንቶት ሥልጣን የያዘውን ሁሉ እንደትክክለኛ፣ በለስ ያልቀናውን ደግሞ እንደ ስህተተኛ እየቆጠሩ ቢያንስ በሀሳብ ደረጃ እንኳ ርቱዕ አቅጣጫን አለመያዝ አሳዛኝ ነው፡፡ በወህኒ ፀፀት በስተቀር ደጅ በህይወት እያሉ ስህተትን ማረም ተችሎ የሚያውቅ አይመስልም፡፡
በዘላቂነት አሳይቶ-ነሳን የማለት እሮሮ በቀር ተዘጋጅቶ የመጠበቅ፣ አስቦ የመንቀሳቀስ፣ አጋጣሚን ሲሆን ቀምቶ፣ ካልሆነም የተገኘውን ምቹ ሁኔታ ተጠቅሞ ለአገር የሚበጅ ነገር መሥራት አልለመድ ያለ ነገር ሆኗል፡፡ ይሄኛው አንዱ ገጹ ሆኖ፤ በሌላ በኩል ደግሞ “አታስገባኝ እንጂ ውጣልኝ ማለትስ ያስቸግርሃል” እንዲል መጽሀፍ፣ አንዴ የገቡበትን ነገር ስህተትም ቢሆን አቋሜን በጭራሽ አልለቅም ብሎ ሙጭጭ ማለት ፍፁም የተለመደ ተግባር ሆኗል፡፡ ያም ሌላው ኪሳራ ነው፡፡ አሳይቶ - ነሳኝ የማለት የፀፀተኝነት ባህል እንደ ድርቅ በተደጋጋሚ እየመታን፣ መንግስት በተለወጠ ቁጥር “የት ይደርሳል የተባለ ባህር ዛፍ ቀበሌ ቆረጠው!” ስንል እንከርማለን፡፡ አጋጣሚን በጊዜ፣ አጋጣሚን በቦታ፣ አጋጣሚን በንቃት ተጠንቅቆ ማየት፣ ሌላ ዕድል ያለማበላሸትን ዋስትና ያስጨብጣል፡፡
ያም ሆኖ አጋጣሚዎች ሳይመቻቹ፣ ህሊናዊና ነባራዊ ሁኔታዎች ሳይበስሉ፣ የተደከመበት ፍሬ መጎምራት ቀርቶ ለዐይን እንኳ ሳይጠጥር፣ ባልተባ ልሳን ዘራፍ ቢል፣ “የማይበላ ንፍሮ ሳይፈለፈል ይበስላል” ሆኖ ቁጭ ይላል ነገሩ ሁሉ፡፡ ከጧት የተማሪ እንቅስቃሴ ስሜት፣ ከረፋድ ሰክነት-አልባ የፓርቲ ንቅንቄ፣ ከከሰዓት በኋላው የትጥቅ ትግል ትኩሳት ሳንላቀቅ፤ በሥራም፣ በፖለቲካም ኃላፊነት ላይ ከተቀመጥን የበሰለውን ጥሬ እናደርጋለን፡፡ የእጃችንን ፈልቅቀው እንዲወስዱብን በር ከፍተን እናስገባለን፡፡ የዐይናችን አፎት ይጠብቅና ያየነውን እንዳላየን እንሆናለን፡፡ ከህዝብ የምንሸሽገው ይበዛል፡፡ እንደተማሪነት ስሜታዊነት ይጋልብብናል። ብስለት ሳይሆን ድፍረት ይፀናወተናል፡፡ አገር ሙሉውን ደክሞ ያፈራውን ምርት፤ ያዘመረውን አዝመራ፣ አንጡራ ሀብታችንን ቅርሳችንን ሁሉ በአንድ በመከራ የቆየችውን ሀገር በህልውና ማቆየት ከፍተኛ ኃላፊነት ነው፡፡ አለበለዚያ “ተጨንቀው ያመጡትን ዕንባ ዝንብ ይልሰዋል” ነውና ነገረ-ሥራችን ሁሉ፣ ወልዶ አሳድጎ ለባዳ ይሆናል፡፡ እንደ ዝንጀሮይቱ ‘ልቤን ጫካ አኑሬው ነው’ ማለቱ ብቻ ልብን አያድንም! ገጣሚው እንዳለው፡
“ይልቁንም አለ አንድ ሀቅ
የነገውን ነገ ነው የሚያቅ፤
ጭብጥ እንዳይፈለቀቅ
የያዝነውን እንዳንለቅ
ሻካራ እጅን ብቻ ሳይሆን፣ ልብንም ጭምር ነው ማጥበቅ!”



በትግራይ ክልል ውስጥ ከጳጉሜ 2 ሊካሄድ ታስቦ የነበረው ሰላማዊ ሰልፍ መታገዱ ተገለጸ፡፡
በክልሉ ስርነቀል ለውጥ ለማምጣት ያለመ ነው የተባለው ይኸው ሰላማዊ ሰልፍ፤ በውናት፣ ሳልሳይ ወያነና ባይቶና ትግራይ ፓርቲ አማካኝነት መጠራቱ የተነገረ ሲሆን ሰላማዊ ሰልፉ በአዲሱ የመቀሌ ከተማ አስተዳደር መታገዱ ታውቋል፡፡
የከተማ አስተዳደሩ ትናንት ለሰላማዊ ሰልፉ አዘጋጆች በላከው ደብዳቤ፤ የከተማ አስተዳደሩ ለሰላማዊ ሰልፍ የፀጥታ ጥበቃ ማድረግ እንደማይችል ነው ያሳወቀው፡፡
የሰላማዊ ሰልፍ ጥያቄው ህገመንግስታዊ ነው ያለው የከተማ አስተዳደሩ፤ ደብዳቤ ሰላማዊ ሰልፍ የተጠራበት ወቅት የበዓል ዋዜማ በመሆኑና ግርግር የሚበዛበት ወቅት በመሆኑ የትራንስፖርት እንቅስቃሴን ሊያውክ ስለሚችልና ለሰላማዊ ሰልፍ በቂ የፀጥታ ጥበቃ ለማድረግ አስቸጋሪ በመሆኑ ሰልፉ ሊካሄድ አይችልም ብሏል፡፡

Page 3 of 665