Administrator

Administrator

እኔ የምላችሁ ግን … ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ ስንት ዓመቱ ነው? ይሄንን ቀላል ጥያቄ የምጠይቃችሁ ወድጄ እንዳይመስላችሁ፡፡ ግራ ቢገባኝ ነው፡፡ ሌላም ጥያቄ አለኝ - ያለፈው ሥርዓት ከተገረሰሰ ምን ያህል ጊዜ ሆነው? (ውዥንብሩ መጥራት አለበት!) አንዳንዴ ያለፈው ሥርዓት “አስማተኛ” ይመስለኛል፡፡ ለምን መሰላችሁ? አንዳንድ ሰዎች አሁንም ከ24 ዓመት በኋላ እንኳን ስለሱ ማውራት አልተዉም፡፡ ለሁሉ ነገር ያለፈውን ሥርዓት ካልጠሩ አይሆንላቸውም - በተለይ የኢህአዴግ ካድሬዎች፡፡ (ፍሬሾቹን ማለቴ ነው!)
 ሰሞኑን EBC ባቀረበው የዜና ዘገባ ላይ “…የሴቶች ጥቃት ያለፈው ሥርዓት ችግር ስለሆነ እንታገለዋለን…” (really?!) የሚል ነገር የሰማሁ መሰለኝ፡፡ እውነቱን ልንገራችሁ አይደል … ራሱ ኢህአዴግም እንኳን  የሴቶች ጥቃት “ያለፈው ሥርዓት” ችግር ነው አይልም፡፡ እንዲያ ካለማ--- ያለፈው ሥርዓት አልተገረሰሰም ማለት ነው፡፡ ወይም ደግሞ እንዳልኩት “አስተማኛ” ነው፡፡ (መቃብር እየፈነቀለ የሚወጣ!)
ይሄውላችሁ --- በሴቶች ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶች ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በዓይነትም በመጠንም እየጨመሩ ለመምጣታቸው ከፖሊስ ፕሮግራም የበለጠ ማስረጃ የለም፡፡ (የሴቶች መብት ተሟጋቾችም ምስክር ናቸው!) አስገድዶ መድፈር፣ አሲድ መድፋት፣ ከባድ ድብደባና የአካል ማጉደል እንዲሁም አሰቃቂ ግድያዎች…በእጅጉ በርክተዋል፡፡ (ሰብዓዊ ልማት ተዘንግቷል!)
እናም--- የሰሞኑ የEBC ዘገባ blame shifting (“የእምዬን ወደ አብዬ”) እንጂ ሌላ ሊሆን አይችልም፡፡ ሃቁን እንነጋገር ከተባለ --- የሴቶች ጥቃት  “ያለፈው ሥርዓት” ችግር ሳይሆን የእኛው የራሳችን ችግር ነው፡፡ (የኋላ ቀርነት፣ የትምህርት አለመስፋፋት፣ የግንዛቤ ማነስ፣ የአመለካከት ችግር ወዘተ…) ነገርዬው እምብዛም ከስርዓት ጋር የሚያያዝ አልመሰለኝም (ፖለቲካ እኮ አይደለም!) የግድ የሥርዓት ችግር ነው ከተባለም ባለቤቱ የአሁኑ ሥርዓት ነው፡፡ እናሳ? … እናማ በሴቶች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ወዳለፈው ሥርዓት ለማሻገር ከመታተር ይልቅ እውነታውን ተቀብሎ ለመፍትሄ መትጋት ይሻላል፡፡ (ያለፈው ሥርዓት ከበቂ በላይ የራሱ ኃጢያቶች እንዳሉት አንዘንጋ!!)
ይሄውላችሁ ----- እንኳንስ በቅርብ ዓመታት እየተባባሰ የመጣው “የሴቶች ጥቃት” ይቅርና በእርግጥም ካለፈው ሥርዓት የተወረሱ ናቸው የሚባሉት (እነ ድህነት፣ ሙስና፣ የስልጣን ጥመኝነት፣ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት፣ የነፃነት አፈና፣ የፍትህ መጓደል ወዘተ…) ቢሆኑም እንኳ --- 20 ዓመት ስላለፋቸው  ውርስነታቸው አብቅቷል፡፡ (ከአባት የተወረሰ ንብረትም እኮ ለዘላለም በውርስነት አይጠራም!) ከምሬ እኮ ነው… ከአሁን በኋላ ችግሮችን ባለፈው ሥርዓት ማሳበብ ራስን ለትዝብት ማጋለጥ ነው፡፡
በመጨረሻ አንድ ሃሳብ ላቅርብ፡ ከፆታዊ ጥቃቶች አንዱ የሆነው አስገድዶ መድፈር፣ ለምን በፀረ ሽብር ህጉ ውስጥ አይካተትም? ይሄ እኮ… ሥርዓቱን ወይም ህገመንግስቱን በኃይል ለመናድ ከመሞከር ፈፅሞ አይተናነስም፡፡ ሴቶች ላይ ጥቃት መፈጸም - ቤተሰብን --- ህዝብን --- መንግስትን ---- አገርን --- ማሸበር ነው!!

Saturday, 20 December 2014 13:19

የፀሃፍት ጥግ

(ስለ ምርጫ)
* ከአዲስ ምርጫ የምንማረው ነገር ቢኖር ከቀድሞው ምርጫ ምንም አለመማራችንን ነው፡፡
ጌራልድ ባርዛን
* ምርጫ የምናካሂድበት ብቸኛው ምክንያት ከህዝብ የተሰበሰበው አስተያየት ትክክል መሆኑን ለማወቅ እንደሆነ ተሰምቷችሁ ያውቃል?
ሮበርት ኦርቤን
* በኦሎምፒክ ሁለተኛ ሆኖ መጨረስ ብር ያሸልማል፡፡ በፖለቲካ ሁለተኛ ሆኖ መጨረስ ግን ያስረሳል፡፡
ሪቻርድ ኒክሰን
* በፖለቲካው ዓለም ሴቶች ደብዳቤ ይተይባሉ፤ ቴምብር ይለጥፋሉ፤ በራሪ ወረቀት ያሰራጫሉ፡፡ ከዚያም ከምርጫው ይወጣሉ፡፡ ወንዶች ይመረጣሉ፡፡
ክላሬ ቡዝ ሉሴ
* እጩ ተመራጭ ከመንገድ ማዶ ሆናችሁ ከለያችሁ የምርጫ ወቅት ሪቅ አይደለም ማለት ነው፡፡
ኪን ሁባርድ -
* የምርጫ ድምፅ መመዘን እንጂ መቆጠር የለበትም፡፡
ጆን ክሪስቶፍ ፍሬድሪክ ቮን ሺለር
* የነፃ ምርጫ ችግሩ ማን እንደሚያሸንፍ ቀድሞ አለመታወቁ ነው፡፡
ሊኦኒድ ብሬዥኔቭ
* የምርጫው ውጤት የሚወሰነው ድምፅ በሚሰጡ ሰዎች ሳይሆን ድምፁን በሚቆጥሩ ሰዎች ነው፡፡
ጆሴፍ ስታሊን
* እንግሊዞች ነፃ ነን ብለው ያስባሉ፡፡ ነፃ የሚሆኑት ግን በፓርላማ አባላት ምርጫ ወቅት ብቻ ነው፡፡
ዣን ዣኪዩስ ሩሶ
* ሰዎች ከአደን በኋላ፣ በጦርነት ወቅት ወይም ከምርጫ በፊት የሚዋሹትን ያህል መቼም አይዋሹም፡፡
ኦቶ ቫን ቢስማርክ

Saturday, 20 December 2014 12:47

ይድረስ ለህፃናት መምህራን

“ህፃናትን በፍቅር እናስተምራቸው”

     ልጆቼ የአምስትና የሶስት አመት ህፃናት ናቸው፡፡ የሚማሩት አንድ ትምህርት ቤት ሲሆን ትልቋ መካከለኛ የመዋዕለ ህፃናት፣ ትንሿ ደግሞ ጀማሪ የመዋዕለ ህፃናት ተማሪዎች ናቸው፡፡ ብዙ ጊዜ ከአንደበታቸው የማይጠፉ ሁለት አባሎች አሉ - “loser” እና “ shame on you” የሚሉ ናቸው፡፡ አንድ ቀን እኒህን አሉታዊ አባባሎች ከየት እንዳመጧቸው ስጠይቃቸው፣ ከትምህርት ቤት መሆኑን ነገሩኝ - ያውም ከመምህራኖቻቸው፡፡
ልጆቼ በሚማሩበት ት/ቤት መምህራን የህጻናቱን የዕለት ውሎ ለወላጆች ሪፖርት የሚያደርጉበትና ወላጆችም መመልከታቸውን ከአስተያየት ጋር (ካላቸው ማለት ነው) አክለው ፈርመው የሚልኩበት “ኮሙኒኬሽን ቡክ የሚሉት ትልቅ ጥራዝ አለ፡፡ በሌሎቹም የግል ት/ቤቶች ይኖራል ብዬ አምናለሁ፡፡
አንድ ቀን ታዲያ በመጀመሪያዋ ልጄ የ “ኮሙኒኬሽን ቡክ” ላይ ዲሲፕሊን በሚለው ስር “ጥሩ” የሚል አስተያየት ሰፍሮ በማየቴ (ከወትሮው ዝቅ ያለ ነው) ምክንያቱን ጠየቅኋት፡፡
እሷም “ግድግዳ ላይ ስለፃፍኩ ነው…” አለችኝ
“ይቅርታ ጠየቅሽ?”
“አዎ፤ መጀመርያ የቅጣት ወንበር ላይ ተቀመጥኩና የክፍል ልጆች ጮክ ብለው “loser እና  shame on you” እንዲሉኝ ሚስ አዘዘቻቸው፡፡ ከዚያም ሚስን ይቅርታ ጠይቄ ወደ መቀመጫዬ ተመለስኩ” በማለት ሂደቱን አስረዳችኝ፡፡ ከዚህ ቀደም እንዲህ ያለ ነገር ሰምቼ ስለማላውቅ ደነገጥኩ፡፡ ሃሳብም ገባኝ፡፡ “አንቺም ሌሎችን እንደዛ ብለሽ ታውቂያለሽ?” ጠየቅኋት፤ ልጄን፡፡ “አዎ ብዙ ቀን እከሌ እና እከሌን ብለናቸዋል”፡፡ የልጄ መልስ ነበር፡፡ በከተማችን በሚገኙ አምስት የግል ትምህርት ቤቶች ተማሪ የሆኑ ህፃናትን ጠይቄ ድርጊቱ በእነሱም ት/ቤቶች እንደሚፈፀም ለማወቅ ችያለሁ፡፡ ልጆች በስነስርአት ታንፀው እንዲያድጉ ከተፈለገ፣ ያጠፉት ጥፋት ምን እንደሆነ በትክክል ተረድተው፣ ከጥፋታቸው እንዲቆጠቡ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ ቅጣት ያልተገባ ባህርይን ወይም ድርጊትን ለመቀነስ ብሎም ለማስወገድ እንደሚያግዝ አያከራክርም፡፡ ሆኖም በተለይ በህፃንነት ዕድሜ ባሉ ተማሪዎች ላይ የሚፈፀመው ቅጣት ጥንቃቄ የተሞላበትና ያልተፈለገ ውጤት የማያመጣ መሆን ይገባዋል፡፡
ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በልጆች ስነልቦና ላይ የሰሩትና በሙያቸው መምህር የሆኑት አቶ ማናዬ አደላ፤ ህፃናትን እንዴት ከጥፋት እንዲቆጠቡ ማድረግ እንደሚቻል ያስረዳሉ፤ “የመጀመሪያው አማራጭ የህፃናትን መልካም ስነምግባር ማበረታታት፣ ህፃናቱ ጥሩ ባህርይ እንዲላበሱ ያደርጋል፤ እግረመንገዱንም መጥፎውን እንዳይቀጥሉበት ይከለከላል፡፡ ነገር ግን በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴያቸው ከስነ ምግባር ውጭ የሆኑ ነገሮችን መልመዳቸው ስለማይቀር ተገቢ ማረሚያ መንገዶችን መጠቀም ይገባል፡፡ ከማረሚያ መንገዶቹ አንዱ ቅጣት የምንለው ነው፡፡” የሚሉት አቶ ማናዬ፤ በስነልቦና ሙያ ቅጣት ሁለት አይነት ነው፡- አዎንታዊና አሉታዊ ቅጣት” በማለት ያብራራሉ፡፡
“አሉታዊ ቅጣት በድርጊት (አካላዊ ቅጣት ማለት ነው) ወይም በቃላት የሚፈፀሙ ናቸው፡፡ ይህ አይነቱ ቅጣት አካላዊ ጉዳትና ስነልቦናዊ ተፅዕኖ ስላለው በፍፁም አይመከርም፡፡ አዎንታዊ ቅጣት የሚባለው ምንም አይነት ስነልቦናዊና አካላዊ ጉዳት በህፃናቱ ላይ ሳያደርሱ፣ ከመሰረታዊ ፍላጎቶች ውጪ የሆኑ ነገሮችን እንደ መቀጣጫ በማስቀረት ስህተታቸውን  ደግመው እንዳይፈፅሙ ማስተማር አይነት ዘዴዎችን ያካተተ ነው፡፡” ይላሉ - ባለሙያው፡፡   
በህፃናት ላይ የሚሰነዘር ስድብና ማላገጥ የህፃናቱን በራስ የመተማመን መንፈስ ይጎዳል፣ ከሌሎች ጋር ሊኖራቸው የሚገባ መቀራረብን ያሳጣል፣ ለትምህርት ያላቸውን ተነሳሽነት ይገድለዋል፣ ፍርሀት በውስጣቸው  እንዲፈጠር በማድረግ የፈጠ አቅማቸውን ያዳክማል ያጠፋል ፣ ሌሎች ነገሮችን እንዳይሞክሩ ያደርጋል፣ የበታችነት ስሜት ይፈጥራል፡፡ ከዚያም አልፎ ትምህርት ቤትን እንዲጠሉና አንሄድም እንዲሉ ያደርጋል፣ የቀጣውን አስተማሪ ከእነሚያስተምረው ትምህርት ጭምር እንዲጠሉ ያደርጋል” ብለዋል፡፡
ህፃናት መቀጣት ያለባቸው በመምህራቸው ብቻ እንደሆነ የሚናገሩት ባለሙያው፤ ተማሪን እያስጨበጨቡ  በቅጣት ላይ ማሳተፍ በተለይ በአቻ እድሜ ላይ ሲሆን የሚፈጥረው አሉታዊ ተፅዕኖ እጅግ ከባድ ነው ባይ ናቸው፡፡ በተመሳሳይ እድሜ ላይ ያሉ ልጆች  በመምህራቸው ትዕዛዝ የክፍላቸውን ተማሪ  “loser” እና  “shame on you” የመሳሰሉ አባባሎችን በመጠቀም እንዲያሾፉበት ሲደረግ ተማሪው ላይ የበታችነት ስሜት ይፈጠራል፤ ይህ ደግሞ በህፃናት ላይ መፈፀም ከሌለባቸው ድርጊቶች አንዱ ነው፡፡ ምክንያቱም የበታችነት ስሜት የሚሰማው ህፃን ተወዳዳሪነቱ ይቀንሳል፣ በራስ የመተማመን ስሜት ያጣል፣ በአጠቃላይም እጅግ አፍራሽ ውጤት የሚያስከትል ድርጊት ነው ይላሉ፤ አቶ ማናዬ፡፡ከሁለት አመት እስከ ሰባት አመትና ከሰባት እስከ አስራ አንድ አመት ያሉት ጊዜያት እጅግ ጥንቃቄ የሚያስፈልጋቸው፣ በህፃናት እድገት ላይ ወሳኝ ጊዜያት ናቸው ያሉት ባለሙያው፤ በዴቨሎፕመንታል ሳይኮሎጂ እጅግ ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል የሚባሉ የእድሜ ደረጃዎች መሆናቸውንም ይናገራሉ፡፡ ይህ እድሜ የልጆችን ሁለንተናዊ እድገት ማበረታቻ እንጂ ማጨናገፊያ መሆን የለበትም፡፡ አስተማሪዎች እጅግ ብልጠት የታከለበት ቅጣትን በመጠቀም ተገቢ ያልሆኑ ባህርያትን ማረም እንዳለባቸውም ባለሙያው ያስረዳሉ፡፡
 የልጆቼ ትምህርት ቤት ሄጄ ዳይሬክተሯን አነጋግሬ ነበር፡፡ “ልጆች እንዴት ከትምህርት ቤት ስድብ ተምረው ይመጣሉ፤ ስድቦቹ ለመዋዕለ ህፃናት ተማሪዎች ብቻ ሳይሆን ለአዋቂም እንኳን እጅግ የሚያሸማቅቁ ናቸው፣ እንዲህ አይነት አባባሎች በትምህርት ቤቱ እንዳይበረታቱ ሊደረግ ይገባል” በሚል ያቀረብኩትን ሃሳብ በቀናነት ተቀብለውኛል፡፡ ለመምህራኑ ተከታታይ ስልጠናዎችን ለመስጠት በዝግጅት ላይ እንደሆኑም ዳይሬክተሯ ጠቁመውኛል፡፡ ሌሎች ትምህርት ቤቶችም እንዲህ ያለ የህፃናትን በራስ የመተማመን ስሜት የሚጐዳ ስድብና ድርጊት ከመፈፀም በመታቀብ፣ ያጠፉ ህፃናትን አስተማሪ በሆነና ሰብዕናቸውን በማይጐዳ መልኩ መቅጣት ይኖርባቸዋል፡፡
በለጋ እድሜ ላይ ያሉ ህፃናትን መስደብና ማሾፊያ ማድረግ በትምህርታቸውና በማህበራዊ ህይወታቸው ላይ ትልቅ ጉዳት እንደሚያስከትል መገንዘብ ይገባል፡፡  ህፃናትን በፍቅር እናስተምራቸው!!

የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት በንግድ ምልክት፣ በአዕምሮ ፈጠራና በዲዛይን (ንድፍ) ላይ ጥበቃ ለማድረግ በዓለም አቀፉ የአዕምሮ ንብረት ድርጅት (World Intellectual Property Organization) WIPO ትብብር አዲስ የዲጂታል አሰራር መዘርጋቱን አስታውቋል፡፡ ከዚህ ቀደም በማኑዋል የአዕምሮ ንብረቶችን ይመዘግብና ይቀበል የነበረው መስሪያ ቤቱ፤ ከተባበሩት መንግስታት ስፔሻላይዝድ ድርጅቶች አንዱ በሆነው “ዋይፖ” በተደረገለት ድጋፍ በ2.ሚሊዮን ዶላር የተገዙ ሶፍትዌሮችን፣ ሰርቨሮችን፣ ኮምፒዩተሮችንና ፕሪንተሮችን በማስገባት Intellectual Property Automation System (IPAS) ሲስተምን ይፋ አድርጓል፡፡ በእለቱ የዋይፖ ተወካዮች በኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት በመገኘት የዘረጉትን ሲስተም ለጋዜጠኞችና ለጽ/ቤቱ ከፍተኛ አመራሮች አስጎብኝተዋል፡፡ በጉብኝቱ ላይ የተገኘችው የአዲስ አድማስ ከፍተኛ ሪፖርተር ናፍቆት ዮሴፍ፤ በተዘረጋው ሲስተም፣ በጠቀሜታውና በዋይፖ ትብብር ዙሪያ ከጽ/ቤቱ ዳይሬክተር አቶ ብርሃኑ አዴሎ ጋር ተከታዩን ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡

       የተዘረጋው አውቶሜሽን ሲስተም ጠቀሜታው ምንድን ነው?
እንግዲህ የዚህ ሲስተም በአገራችን መዘርጋት ጠቀሜታው በርካታ ነው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንዱና ዋነኛው በአዕምሮ ፈጠራ (ፓተንት)፣ በንግድ ምልክትና በዲዛይን (ንድፍ) ባለቤትነት  ጥበቃ ላይ አስተማማኝና ዘለቄታ ያለው ስራን ለመስራት ያስችላል፡፡
 ይህ ሲባል እስከዛሬ አመልካቾች በወረቀት ይዘው የሚመጡት የባለቤትነት ጥያቄ አንድ ጊዜ በዚህ ሲስተም ውስጥ ከገባ ካልተፈለገ የይገባኛል ጥያቄዎች፣ ከመጥፋት ጭቅጭቅና ከመሰል ጉዳዮች ተጠብቆ ይቀመጣል፡፡
ሁለተኛ አመልካቾችን ከጊዜ ብክነትና ከመጉላላት ይጠብቃል፡፡ ባሉበት ሆነው ጉዳያቸውን መከታተል እንዲችሉ ያደርጋቸዋል ማለት ነው፡፡ አንድ አመልካች ፈጠራውን፣ የንግድ ምልክቱን ወይም ዲዛይኑን ይዞ ሲመጣ ኮድ ይሰጠዋል፤ ፋይል ይከፈትና የፋይሉ ቁጥር ሲስተሙ ውስጥ ይመዘገባል፡፡ ሌላ ጊዜ ሲፈለግ ኮዱን ኮምፒዩተሩ ላይ አስገብቶ  በፍጥነት ለማግኘት ያስችላል፡፡ ይህ ቀልጣፋ አሰራርን ይፈጥራል፡፡ ባለንብረትነትን ያረጋግጣል፡፡ አንድ ምርትም በፓተንት፣ በንግድ ምልክትና በዲዛይን ይጠበቃል፡፡ እነዚህ ጥቅሞቹ ናቸው፡
ይህን ሲስተም ለመዘርጋትና ስራ ላይ ለማዋል የዓለም አዕምሮ ንብረት ድርጅት “WIPO” ወደ ሁለት ሚሊዮን ዶላር ወጪ ማድረጉ፣ ሰራተኞቹን በራሱ ወጪ እዚህ ድረስ መላኩና ሲስተሙን መዘርጋቱ ተገልጿል፡፡ ይህን ድጋፍ ያደረገው ለምንድን ነው?
የዓለም የአዕምሮ ንብረት ድርጅት ከUN ስፔሸላይዝድ ድርጅቶች አንዱና በአዕምሮ ንብረት ላይ አተኩሮ የሚሰራ ትልቅ ድርጅት ነው፡፡ መቀመጫውን ስዊዘርላንድ ጄኔቫ ያደረገው ይህ ድርጅት፤ በ60 የዓለም አገራትና በ20 የአፍሪካ አገራት ይሰራል፡፡ ድርጅቱ ከሚሰራባቸው የአፍሪካ አገራት ኢትዮጵያ አንዷ ናት፡፡ ድርጅቱ ሰራተኞቹን ሲልክ ይህ ሶስተኛ ጊዜው ነው፡፡
 ድርጅቱ በተለይ በማደግ ላይ ያሉ አገሮችን ለማገዝ በያዘው ፕሮጀክት፣ ታዳጊ አገሮችን አግዘን የአዕምሮ ንብረት ጥበቃቸውን ማጠናከር አለባቸው ብሎ በማመኑ ድጋፎችን ያደርጋል፡፡ በዚህ መሰረት ሰራተኞችን ወደዚህ ሲልክ፣ የአውሮፕላን ትኬት፣ ሆቴል… ሁሉን ነገር ችሎ ነው፤ ከእኛ የሚጠበቅ ነገር የለም፡፡
በማንኛውም ጊዜ ድጋፍ ስንጠይቅ ፈጣን ምላሽ ይሰጣሉ፡፡ ይህ የድጋፋቸው አንዱ ክፍል ነው፡፡
ሲስተሙን ለመጫን የሚያስፈልጉ ከላይ የጠቀስሻቸውን ንብረቶች ለመግዛት ወደ 2 ሚሊዮን ዶላር ወጪ አድርገዋል፡፡ በቀጣይ የቅጅ መብት ላይ ለምንሰራውም ድጋፍ ለማድረግ ሌላ ፕሮጀክት አላቸው፡
ከዚህ በፊት ምን ምን ድጋፎችን አድርገዋል?
እስካሁን ብዙ ፕሮጀክቶችን ሰጥተውናል፡፡ ለምሳሌ የብሔራዊ አዕምሮ ንብረት ፖሊሲ ድራፍት ይደረግ ብለን ጠይቀናቸው፣ አማካሪ በመቅጠር ድጋፍ ስለሰጡን አሁን ድራፍቱ አልቋል፡፡ እስካሁን በአገር አቀፍ ደረጃ ይህ ፖሊሲ የለም ነበር፤ ሁለት አማካሪ በመቅጠር ጥናቱን ጨርሰዋል፡፡
 በሚቀጥለው ጥር መጨረሻ ላይ ለውይይት ቀርቦ ይፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ሌላው የአዕምሮ ንብረት አካዳሚ (If Academy) ነው፡፡ ይህንንም ፕሮጀክት ቀርፀን አቅርበን ፈቅደውልናል፡፡ ይህ አካዳሚ በቅርቡ ስልጠናና የማስተርስ ስራ ይጀምራል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ የቅጅ መብትን አስመልክቶ የፊልም፣ የሙዚቃና የድርሰት ኢንዱስትሪው እያደገ መምጣቱን ተከትሎ ኢንዱስትሪው ለኢኮኖሚው እየጠቀመ ያለው ምን ያህል ነው የሚለውን እንዲጠናልን ጠይቀናቸው 70 ሺህ ዶላር አውጥተው አማካሪ ቀጥረውልን እየተጠና ነው፡፡ ጥናቱም የመጨረሻ ሪፖርት ላይ ደርሷል፡፡ እናም ድጋፍ በጠየቅን ቁጥር ፕሮጀክቶችን ይሰጣሉ፡፡ በተለይ በማደግ ላይ ያሉ አገሮችን በጣም ነው የሚያግዙት፡፡
በአሁኑ ወቅት ድርጅቱ ተወካዮቹን ሲልክ ለሶስተኛ ጊዜ ነው ብለዋል፡፡ ከዚህ በፊት የመጡባቸው ሁለት ምክንያቶች ምን ምን ነበሩ፤ የአሁኑ አመጣጣቸውስ በዋናነት ምን ላይ ያተኩራል?
ከዚህ በፊት ይህንኑ ሲስተም በተመለከተ ስራዎች ነበሯቸው፡፡ አሁን ግን ሶፍትዌሩን ጭነው ባለሙያዎች አሰልጥነውና አስፈላጊውን ነገር አሟልተው፣ ሲሰሙ ስራ ላይ መሆኑን ይፋ ያደረጉበት የመጨረሻ ቀን ነው፡፡ ከዚህ በኋላ የአዕምሮ ፈጠራ የንግድ ምልክትና የዲዛይን ባለቤቶች ሲያመለክቱ፣ በዚህ ሲስተም ነው የሚስተናገዱት ማለት ነው፡፡ በወረቀት የምንቀበልበት አሰራር አብቅቷል፡፡ ይህ አሰራር የመጨረሻ ተጠቃሚ የሚያደርገውም ባለንብረቱን ነው፡፡ ምክንያቱም ከዚህ በፊት በነበረው አሰራር ፋይል እየጠፋና እየተበላሸ መጉላላቶች ይደርሱ ነበር፡፡ አሁን ግን የወረቀት ምልልስ ቀርቶ አውቶሜትድ ሲስተም ስለምንጠቀም፣ ከሁሉም አቅጣጫ ጠቀሜታው የጎላ ነው ማለት ይቻላል፡፡
በአገር አቀፍ ደረጃ ሲስተሙ ሌላ ክልል አለ ወይስ እዚሁ ዋናው ጽ/ቤት ብቻ ነው?
እዚህ  ዋናው ጽ/ቤት ነው ሲስተሙ ያለው፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃ የሚሰራው እዚሁ ነው፤ ነገር ግን አሁን አሰራሩ ኤሌክትሮኒክ ስለሆነ የትኛውም አመልካች የአዕምሮ ፈጠራውን፣ የንግድ ምልክቱንና ዲዛይኑን (ንድፉን) ካለበት ሆኖ በኤሌክትሮኒክ ሲስተም መላክና መመዝገብ እንዲሁም መከታተል ይቻላል፡፡
ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶችን በክልል ከፍቶ ለመንቀሳቀስ የታሰበ ነገር አለ?
በቅርቡ በክልሎች ቅርንጫፎችን ለመክፈት ሃሳብ አለን፡፡ አማራና ደቡብ ክልሎችን መርጠናል፡፡ ሌላው አካባቢም በሂደት ለመክፈት ሃሳብ አለ፡፡
ሁለቱ ክልሎች ቅድሚያ ያገኙበት ምክንያት ምንድን ነው?
ሁለቱን ከሌሎች በቅድሚያ የመረጥንበት ምክንያት የሚይዙትን የአካባቢ ስፋት ግምት ውስጥ በማስገባት ነው፡፡
ለምሳሌ አማራ ክልልን ብትወስጂ አብዛኛውን የሰሜኑን ክፍል፤ እነ ትግራይን፣ ከፊል ቤኒሻንጉልንና ከአፋርም የተወሰነውን ክፍል ይዞ  እንዲሰራ በማሰብ ነው፡፡ የደቡቡ ደግሞ የደቡብን አካባቢ አጠቃልሎ እስከ ድሬደዋ ወደ ምዕራብ ጭምር ተንቀሳቀሶ እንዲሰራ ታስቦ ነው፡፡ ለወደፊቱ ግን ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶቹን ወደ አራት ከፍ ለማድረግና ስራችንን የበለጠ ለማቀላጠፍ እቅድ አለን፡፡
የቅጅ መብትን በተመለከተ ከዓለም አቀፍ የአዕምሮ ንብረት ድርጅት ጋር ልትሰሩ ያሰባችሁት ምንድን ነው?
ቅድም እንደገለፅኩት የቅጅ መብት አዋጅ በቅርቡ ፀድቋል፡፡ ይህ አዋጅ ባለ መብቶችን ሁሉንም ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው፡፡ እንግዲህ አዋጁን ተከትለን የቅጅ ባለመብቱን ጥቅም ለማስከበር በምን መልኩ ይሰራ የሚለውን የሲስተምና መሰል ድጋፎች ከዋይፖ ጠይቀናል፡፡
እነሱም ፕሮጀክቱን ፈቅደዋል፡፡ የሚሰሩት ስራዎች ወደፊት በሂደት በግልፅ  የሚታዩ ይሆናሉ፡፡ ዋናው ነገር እነሱ አሁንም በማደግ ላይ ያሉ አገራትን ለመርዳት ካላቸው ፍላጎት የተነሳ አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸው ነው፡፡

Saturday, 20 December 2014 12:38

የሴት ኮንዶም

     ኤች አይቪ ኤድስን ጨምሮ ሌሎች ጥንቃቄ በጎደለው የግብረ ሥጋ ግንኙነት ሳቢያ የሚተላለፉ በሽታዎችና ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችል የሴት ኮንዶም በዲኬቲ ኢትዮጵያ ወደ አገራችን አስመጥቶ ለገበያ ከቀረበ ቆየት ብሏል፡፡ ኮንዶሙን ሁልጊዜና በአግባቡ ከተጠቀሙበት በግብረ ስጋ ግንኙነት የሚተላለፉ በሽታዎችንም ሆነ ያልተፈለገ እርግዝናን የመካላከል አቅሙ አስተማማኝ እንደሆነም የጤና ባለሙያዎችን ይናገራሉ፡፡ ዲኬቲ ኢትዮጵያ ኮንዶሙን በወሲብ ንግድ ላይ የተሰማሩ ሴቶች እንዲጠቀሙበት በማድረግ አበረታች ውጤት አስገኝቷል ሲባል ሰማሁና ጉዳዩን ከራሳቸው ከተጠቃሚዎቹ አንደበት ለመስማት ወደ ስፍራው ተጓዝኩ፡፡
በአዲሱ የባቡር መንገድ ፕሮጀክት ሳቢያ ምስቅልቅሉ ከወጣው የመርካቶው ሰባተኛ መንደር የደረስኩት ባለፈው ማክሰኞ አመሻሹ ላይ ነበር፡፡ ስፍራው በወሲብ ንግድ ስራ ላይ የተሰማሩ ሴቶች በስፋት የሚገኙበት በመሆኑ በቂ መረጃዎችን እንደማገኝ እምነት ነበረኝ፡፡ ከአዲስ ከተማ የመሰናዶ ት/ቤት ፊት ለፊት የሚገኙት ቅያሶች በሙሉ ወደ እነዚሁ አካባቢዎች የሚያደርሱ በመሆናቸው አንዱን መንገድ ይዤ ቁልቁል ወረድኩ፡፡
በቆርቆሮና በጣውላ እርስ በርስ ተዛዝለው የተሰሩና በሮቻቸው አጫጭር የሆኑትን የሴተኛ አዳሪዎቹን ቤቶች እያለፍኩ ወደመሀል ዘለቅሁ፡፡ የቀድሞው ቀበሌ 12 በርካታ በወሲብ ንግድ የሚተዳደሩ ሴቶች የሚገኙበት አካባቢ ነው፡፡
ሴቶቹ ከተለያዩ የአገራችን ክልሎች የመጡ መሆናቸውንና በወሲብ ንግድ ለዓመታት ተሰማርተው እንደቆዩ ነገሩኝ፡፡ ስለኤችአይቪ/ ኤድስና ጥንቃቄ በጎደለው ወሲብ ሳቢያ ስለሚከሰቱ በሽታዎች በቂ ግንዛቤም አላቸው፡፡ ኮንዶምን ሁልግዜ የመጠቀም ፍላጎት ቢኖራቸውም አብዛኛውን ጊዜ ያለኮንዶም ወሲብ ለመፈጸም የሚፈልጉ አንዳንድ ግድየለሽ ደንበኞቻቸው ያለፍላጐታቸው ከኮንዶም ውጭ ወሲብ እንዲፈፅሙ እንደሚይስገድዷቸው አጫወቱኝ፡፡ “ብዙውን ጊዜ በኃይል እየተጠቀሙ ያለኮንዶም ወሲብ ለመፈጸም የሚፈልጉ ወንዶችን ጮኸን እናስይዛቸዋል፡፡ እርስ በርሳችን በመረዳዳት ሴቲቱን አስገድዶ ያለኮንዶም ሊገናኝ የሚፈልገውን ወንድ በፖሊስ እናሲዛለን፡፡ አንዳንዴ ግን ወንዶች ያለኮንዶም ወሲብ ለመፈፀም የሚያቀርቡልን ማባበያ እያታለለን እኛም በፍቃደኝነት እንፈፅማለን፡፡ አንዳንዱ ወንድ ደግሞ ተስማምተን በኮንዶም ወሲብ ማድረግ ከጀመርን በኋላ ያጠለቀውን ኮንዶም አውልቆ በመጣል ያለኮንዶም ይገናኛል፡፡ ምን ታደርጊዋለሽ፡፡ ህይወት እንዲህ ናት!”
ሴቶቹ ህይወታቸው ስቃይና ሐዘን የተሞላበት እንደሆነና ራሳቸውን እንደ ሰዉ ቆጥረው ተስፋ ለማድረግ እንደማይችሉ ነገሩኝ፡፡ በቅር/ጀ ወደ አገራችን መጥቶ ገበያ ላይ ስለወሰው የሴቶች ኮንዶም ያውቁ እንደሆነ ጠየቅኋቸው፡፡ ሁሉም ሴቶች ስለ ኮንዶሙ ያውቃሉ፡፡ ሞክረውታልም፡፡ እንዴት ነው ታዲያ ስል ጥያቄዬን ቀጠልኩ፡፡
“በወሲብ ንግድ ላይ ተሰማርተሽ በራስሽ ፍላጎትና አማራጭ መጓዝ አትችይም፡፡ ደንበኛሽ ገንዘቡን እስከከፈለ ድረስ እሱ በሚፈልገው መንገድ ማስተናገድ አለብሽ፡፡ ይህንን ስታደርጊ ታዲያ ራስሽን ለበሽታና ለሞት አጋልጠሸ አይደለም፡፡ የሴት ኮንዶም በመምጣቱ ሁላችንም ደስተኞች ነን፤ ምክንያቱም በእኛ ስራ ኮንዶም መጠቀም የደንበኛሽን በጎ ፍቃደኝነትን የሚጠይቅ ነው፡፡ ቅድም እንዳልኩሽ ወንዱ በወሲብ ላይ እያለን ኮንዶሙን በማውለቅ ያለኮንዶም ሊገናኘን ስለሚችል ይህ ኮንዶም ከእነዚህ ችግሮች ይታደገናል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ በስካር ኃይል ያለኮንዶም ሊያወጡን ከሚፈልጉ ወንዶች ይጠብቀናል፡፡ አንዳንድ ወንዶች ገንዘባቸውን ከፍለው ለወሲብ ዝግጁ መሆን ሲያቅታቸው ኮንዶሙን አውልቀው ያለ ኮንዶም ማድረግ ይፈልጋሉ፡፡ በዚህ ወቅት የሴት ኮንዶሙን አጥልቀን ዝግጁ ከሆንን ያለ ችግር እናስተናግዳቸዋለን፡፡ ኮንዶሙ እነዚህ ጠቀሜታዎች እንዳሉት ሁሉ ጉዳቶችም አሉት፡፡ የሴት ኮንዶሙ ለስምንት ሰዓታት በማህፀን ውስጥ ሊቀመጥ ይችላል ብለው ነገረውናል፡፡ ስለዚህ ኮንዶሙን ቀደም ብለን አጥልቀን ደንበኞቻችንን እንጠብቃለን፡፡ ደንበኞቻችን በአብዛኛው ደስተኞች አይደሉም፤ አንዳንዶቹ አስተማማኝ አይደለም በማለት ኮንዶም አጥልቀው ይገናኙናል፤ በዚህ ጊዜ ህመም ይሰማናል፡፡ ድርቀት ስለሚፈጠርም ምቾት ያለው ወሲብ አንፈፅምም፡፡ ረዘም ላለ ጊዜ በሰውነታችን ውስጥ ሲቀመጥና በተለይ ብዙ ስንቆም ምቾት ይነሳናል፡፡ ብዙውን ጊዜ የሴት ኮንዶሞችን የምንጠቀመው በበዓላት ዋዜማና ግርግር በሚበዛባቸው ጊዜያት ነው፡፡” ከሴቶቹ ጋር ስለሴት ኮንዶም ያደረግሁትን ቆይታ ካጠናቀቅሁ በኋላ ስለ ሴት ኮንዶም ምንነት ጠቀሜታና የጎንዮሽ ጉዳት እንዲያብራሩልኝ የማህፀን ፅንስ ስፔሻሊስት ዶክተር የኔነህ ታምራትን አነጋገርኳቸው፡፡
የሴቶች ኮንዶም በተለያዩ የዓለማችን አገራት በስፋት በጥቅም ላይ የሚውሉ ቢሆንም በአገራችን እምብዛም የማይታወቅና ከጥቂት ጊዜያት በፊት እንደገባ የገለፁልኝ ዶክተሩ፤ ህብረተሰቡ ስለሴት ኮንዶም ምንነትና አጠቃቀም እምብዛም ባለማወቁ በአግባቡ ጥቅም ላይ አልዋለም ብለዋል፡፡
የሴት ኮንዶሞች በተለያዩ አይነትና ብራንድ በዓለም ገበያ ላይ የሚገኙ ሲሆን  Femidom, Fc femeal condom, Reality, Dominiquie femy, Protectiv care, 7C2, 7C የተባሉት ይገኙበታል፡፡ በአገራችን ገበያ ላይ የሚገኙት 7C2 የተባሉት ኮንዶሞች ናቸው፡፡ የሴት  ኮንዶም ላቴክስ ከሚባልና ከጎማ ተክል ከሚመነጭ ፈሻሽ የሚሰራ ሲሆን በአግባቡና ሁልጊዜ ከተጠቀሙበት ያልተፈለገ እርግዝናንም ሆነ ኤችአይቪ/ ኤድስን ጨምሮ ሌሎች በግብረስጋ ግንኙነት የሚተላለፉ በሽታዎችን ለመከላከል ያስችላሉ፡፡የሴት ኮንዶሞች በመጀመሪያ አካባቢ ለአጠቃቀም  ምቹ አለመሆን፣ ምቾት አለመሰማት አይነት ችግሮች እንዳሏቸው ባይካድም ሲለመዱ ግን ይህ አይነቱ ስሜት እንደሚጠፋም ዶክተሩ ገልፀዋል፡፡ የሴት ኮንዶም ከተጠቀመች ሴት ጋር ወሲብ ለመፈፀም የሚዘጋጅ ወንድ ኮንዶም ማድረግ ይጠበቅበታል ወይ ለሚለው ጥያቄም ዶክተሩ ሲመልሲ ይህ እጅግ አደገኛና ሁለቱንም የወሲብ ተጓዳኞች ችግር ላይ የሚጥል ነገር ነው፤ ሴቷ ኮንዶሙን ከተጠቀመች ወንዱ መጠቀም አይኖርበትም፡፡ ሁለቱም ከተጠቀሙ ግን ድርቀት በመፍጠር ኮንዶሙ የመቀደድና የመላጥ ችግር ያስከትላል፤ ይህም በሽታ በቀላሉ ከአንዱ ወደ ሌላው እንዲተላለፍ ያደርጋል ብለዋል፡፡



አንድ ንጉሥ የመሞቻቸው ሰዓት ሲደርስ ሁለት ወንዶች ልጆቻቸውንና አንዲት ሴት ልጃቸውን ጠርተው፤ “ልጆቼ፤ እንግዲህ ዕድሜዬ እየገፋ፣ ጉልበቴ እየላመ፣ አቅሜም እየደከመ የመጣበት ሰዓት ነውና ከመንግሥቴ የት የቱን መውረስ እንደምትመርጡ ሀሳብ እንድትሰጡኝ እፈልጋለሁ” አሉ፡፡
ታላቅ ወንድም ምንም ሀሳብ ሳይሰጥ ዝም አለ፡፡
ሁለተኛው ወንድም፤
“አባቴ ሆይ! እርስዎ ራስዎ ይሄን ለትልቁ፣ ይሄን ለትንሿ፣ ይሄን ለትንሹ አውርሻለሁ ቢሉን አይሻልም ወይ?” ሲል ሃሳቡን አቀረበ፡፡
ሴቷ ልጅ ደግሞ፤
“አባቴ ሆይ! እኔ የምመኘውንና የማስበውን ብናገር፣ ሌሎቹም የሚያስቡትን ባውቅ በጣም ደስ ይለኛል፡፡ ስለሆነም አባቴ ያሉትን እደግፋለሁ” አለች፡፡
ንጉሡም፤
“አያችሁ ልጆቼ፤ አሁን ከተናገራችሁት የተረዳሁት ሦስት ነገር ነው፡፡
ከመጀመሪያው ልጄ - ዝምታን አየሁ፡፡
ከሁለተኛው ልጄ - ኃላፊነትን ለሌሎች መጣልን አየሁ፡፡
ከሦስተኛው ልጄ - በራስ መተማመንን ነው ያነበብኩት፡፡
በእርግጥ ያየሁዋቸው ሦስት ነገሮች የየራሳቸው ዋጋ አላቸው፡፡ ዝምታ ወቅቱን ከጠበቀ ዋና  ነገር ነው፡፡ ኃላፊነትን ለሌሎች መስጠት አቅምን ከማወቅና የሌሎችን ዋጋ ከማወቅ የመነጨ ከሆነ እጅግ ጠቃሚ እሴት ያለው ነው! በመጨረሻም በራስ መተማመን ከሁሉም የላቀ እሴት ነው፡፡ ያለራስ መተማማመን፤ መንግሥቴን ወዴትም ልታዘልቁት አትችሉም፡፡ በራስ መተማመን የሚመጣው ዕውቀት ሲኖር ነው፡፡ ዕውቀት የሚመጣው ለመማር ፈቃደኛ ከመሆን፣ ከልምድ ራስን ከማሻሻል፤ ሁልጊዜ ለለውጥ ዝግጁ ከመሆን ነው፡፡ እነዚህን ሁሉ አጢኜና መርምሬ ሳስተውል፣ መንግሥቴን መውረስ ያለባት ሴቷ ልጄ ናት” ሲሉ ደመደሙ፡፡
***
የአንድ ህብረተሰብ ዋና ኃይል ልበ - ሙሉነትና በራስ መተማመን ነው! የሀገራችንን የህብረተሰብ አወቃቀር ስናስተውል፤ በተለይ አሁን በደረስንበት የዕድገት ደረጃ፤ የሴቶችን ከባድ ሚና፣ ከባድ ጫና እና ከባድ የሀገር እናትነት ስሜት ማጤን አይሳነንም፡፡ ከተረቶቻችን፣ ከምሳሌዎቻችንና ከጥቅሶቻችን በሰፊው እንደምንረዳው፤ የሴትን የበታችነት አጠንክረው የሚያሰምሩ ቃለ - ኃይሎች እንዳሉ አይካድም፡፡
“በለው በለው ሲል ነው የወንድ አብነቱ
ሴትም ትዋጋለች ከረጋ መሬቱ”
የሚለውን አንድ ምሣሌ ብናይ እንኳ፣ ጉዳችንን በቀላሉ ይነግረናል፡፡ “ለፍታ ለፍታ ሴት ወለደች”ን ስናይ፣ ከንቀታችን ሶስት አራት እጥፍ የሴቶች ጫንቃ ላይ እያሳረፍን እንደከረምን ለማወቅ አያዳግትም፡፡ “ምን ሴት ብታውቅ በወንድ ያልቅ” የሚለውን አደገኛ ካንሠር አከል በሽታ ማስወገድ ይገባናል!! ሴቶችን የረሳ፣ ሴቶችን የናቀ፣ ሴቶችን ተሳታፊ ያላደረገ ሥርዓት ይዞ የትም አያደርስም፡፡ “እንስራዋን ጥላ ወንዝ ወረደች” የሚለው ተረትም አሁንም በሴት ጫንቃ ላይ የተንተራሰ ይሁን እንጂ ቁምነገሩን አንስተውም፡፡
ሀገራችን በተለያዩ የሥራና የህይወት ዘርፎች ያለ ሴት በሣልና ጠንካራ ተሳትፎ ካለመችበት ልትደርስ አትችልም፡፡ ከዚህ አንፃር ሴቷን የለውጥ መዘውር ለማድረግ ለአፍታም ሳንታክት ማሰብና ተግባራዊ ማድረግ ወሳኝ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በመፈክር ላይ በመንጠልጠልና በቀለም በማድመቅ ብቻ የትም እንዳልደረስን አይተነዋል፡፡ በሌላ በኩል ራሳቸውን ለትግል ያበቁ፣ የታገሉና ያሸነፉ ሴት ፋና - አብሪዎች፣ ለድል የበቁት አደራጅተው እንደሆነ እናውቃለን፡፡  በተለያዩ የሙያ ዘርፎች፣ በንግድና ኢንዱስትሪ እንዲሁም በባህላዊ ትሥሥር ዙሪያ ገፍተው ብቅ ብቅ ያሉቱ ምን ያህል ለውጥ ማምጣት እንደቻሉ እያየን ነው፡፡ ገና ግን ብዙ ማደግ፣ በየዘርፉ ብዙ መብቀል፣ ብዙ ማፍራት፣ ብዙ ማልማት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሌላውም የህብረተሰብ ክፍል እንቅስቃሴያቸውን ከአንጀቱ ማገዝና ማጐልበት፣ ትልቅ አስተዋፅዖ ማድረግ ይኖርበታል፡፡ በሙያና በብዙሃን ማህበራት፣ በቤተሰብና በግል ህይወት ውስጥ ሚናቸውን ማረጋገጥ ቁልፍ ጉዳይ ነው፡፡ ብርቱ ጉዞ ይጠብቀናል፡፡ በህብረተሰባችን ውስጥ ሁሉም ቦታ ቦታ እንዳለው አንርሣ! “ቦታ ቦታችሁ ግቡ ቢባል አሎሎ ወደ ጅረት፣ ኩበት ወደ አክንባሎ” የሚባለውም በየቦታው ሁሉም ባለዕሴት መሆኑን ሲነቁጥ ነው!  


  “ ቅ/ ሲኖዶሱ በአድባራት ሓላፊዎች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ
          ሕገ መንግሥቱን የሚፃረር ነው ”   /ፓትርያርኩ/
     የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ‹‹የቤተ ክርስቲያን አባቶችና ቤተ ክርስቲያን ዕውቅና በሰጠችው ማኅበር ላይ ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል›› ባላቸው አንዳንድ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አድባራት አስተዳዳሪዎች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ አፈጻጸም ‹‹ሕገ መንግሥቱንና ሰብአዊ መብትን የሚፃረር ነው›› በሚል ፓትርያርኩ ማገዳቸው ተገለጸ፡፡
ፓትርያርኩ ባለፈው ኅዳር 30 ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በጻፉት ደብዳቤ ‹‹አፈጻጸሙ እንዲቆይ›› በማለት ያገዱት የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና በጠቅላይ ቤተ ክህነት በተካሔዱ ጉባኤዎች÷ ‹‹ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል፤ ይህም አነጋገር ጉባኤውን ቅር አሰኝቷል፤›› ያላቸው የአድባራት አስተዳዳሪዎች፤ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው በአንድ ድምፅ ተስማምቶ ያሳለፈው እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ በመንበረ ፓትርያርክና በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሾች በተካሔዱት ስብሰባዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን መልካም አስተዳደርና ወቅታዊ ችግሮች የተመለከቱ የጉባኤተኞች አስተያየቶችና ሐሳቦች መቅረባቸውን በደብዳቤያቸው ያስታወሱት ፓትርያርኩ፤ ተሰብሳቢዎቹ ሐሳባቸውንና አስተያየታቸውን በግልጽ መናገራቸውና አሉ የተባሉ ችግሮች መፍትሔ እንዲያገኙ መጠየቃቸው ‹‹በዓለም አቀፍ ደረጃም ኾነ በሀገራችን ለሕዝብ የተፈቀደ ዴሞክራሲያዊ መብት መኾኑ አያጠያይቅም›› ብለዋል፡፡ ሐሳባቸውንና አስተያየታቸውን በግልጽ ያቀረቡ ሰዎችን መገሠጽና መውቀስም ሕገ መንግሥቱን እንደሚፃረር ጠቁመዋል፡፡
ጉባኤዎቹ በቤተ ክርስቲያን ጠሪነት የተካሔዱ እንደነበሩና ተሰብሳቢዎቹም የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት፣ አገልጋዮችና ሠራተኞች መኾናቸውን ፓትርያርኩ ጠቅሰው÷ የጎደለው እንዲሟላ የጠመመው እንዲቃና ያላቸውን አስተያየት በማቅረባቸው ተግሣጽና ማስጠንቀቂያ እንዲሰጣቸው ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳለፈው ውሳኔ ‹‹የስብሰባ ነፃነትንና መብትን ነፍጎ ሐቁ እንዳይነገር›› የሚከለክልና ውጤቱም ‹‹ጊዜ ያለፈበትን አፈና በማንገሥ ችግሮች ተባብሰው እንዲቀጥሉ የሚያደርግ ነው›› ብለዋል፡፡ “በውይይቱ ወቅት ‹‹የዳኅፀ ልሳን ወለምታ›› አጋጥሞም ከኾነ በወቅቱ ማብራሪያና ማስተካከያ ይሰጥበታል እንጂ እንደ ከባድ ጥፋት ተቆጥሮ ሰዎች ሊገሠጹበትና ሊወቀሱበት አይገባም፤ ሕግም አይፈቅድም፡፡” ሲሉ ገልጸዋል - በደብዳቤያቸው፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ‹‹ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል›› ያላቸው አንዳንድ የአድባራት አስተዳዳሪዎች በጠቅላይ ቤተ ክህነት በኩል ቀርበው ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው ያሳለፈው ውሳኔ ‹‹ሕግንና ሰብአዊ መብትን የሚፃረር›› ብቻ ሳይኾን ‹‹ትልቁን ጉባኤ በታሪክና በሕግ ዐዋቂዎች ዘንድ ግምት ውስጥ የሚጥለው እንዳይኾን አቡነ ማትያስ አስጠንቅቀው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ ጉዳዩን እንደገና በጥልቀትና ከሕግ አንጻር ፈትሾ እንዲያጤነው በማለት አፈጻጸሙ እንዲቆይ አስታውቀዋል፡፡
በሕገ ቤተክርስትያን ት/ሲኖዶሱ በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ ያሳለፈውን ውሳኔ ፓትርያርኩ የማገድ ሥልጣን እንደሌላቸው ያመለክታል፡፡ ሕገ መንግሥቱ ከተጠቀሰበት አግባብ አኳያም፣ “ቤተ ክርስቲያናችን በቂ ሕግጋት አሏት፤ እነዚህ ሕግጋት ማዕከሉ ተጠብቆ ሊሠራባቸው ይገባል፤” ሲልም ቅ/ሲኖዶሱ አሳስቧል፡፡
ባለፈው መስከረም መጨረሻ “የቤተ ክርስቲንን አስተዳደራዊ አስተሳሰብ ማበልጸግ” በሚል መርሕ በተካሔደው ስብሰባ አንዳንድ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፤ ‹‹ፈጣሪ የለም ይላል፤ አሸባሪና አክራሪ ነው፤›› በማለት ቤተ ክርስቲያኗ ዕውቅና የሰጠችውን ማኅበረ ቅዱሳንን ከዓለም አቀፍ ጽንፈኞች ጋራ እያመሳሰሉ መወንጀላቸው ተገቢ እንዳልኾነና የማኅበሩ አገልግሎት ለቤተ ክርስቲያን አስፈላጊ እንደኾነ ቅዱስ ሲኖዶሱ አረጋግጧል፡፡
‹‹ቆራጣ ደብዳቤ ይበቃዋል፤ ከመንግሥት ጋራ በመተባበር እስከ ጫፍ አድርሱልን፤ በቶሎ ቁረጡት›› እያሉ መጠየቅ፤ ሊቃነ ጳጳሳቱንም “ከፈለጉ ቆባቸውን አስቀምጠው ወደዚያው ይግቡ” እያሉ መዝለፋቸውስ በምን መመዘኛ ነው ዴሞክራሲያዊና ሕገ መንግሥታዊ የሚኾነው በማለት የሚገልጹ የስብሰባው ተሳታፊዎች በበኩላቸው፤ ፓትርያርኩ የውሳኔውን አፈጻጸም ማገዳቸው፣ አድሏዊ እንደሚያደርጋቸውና በካህናቱና በምእመናኑ ዘንድ መንፈሳዊ አባትነታቸውንና ታማኝነታቸውን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባው እንደሚኾን ጠቁመዋል፡፡

ኤልጂ ኩባንያ በኦሮሚያ ክልል ሰንዳፋ አካባቢ ለሚገኘው ሙዳ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት የተለያዩ የትምህርት መርጃ መሳርያዎች ድጋፍ ማድረጉን አስታወቀ፡፡
ኤልጂ ከወርልድ ቱጌዘር፣ መንግስታዊ ያልሆነ ዓለም አቀፍ የልማትና የግብረሰናይ ድርጅት ጋር በመተባበር እ.ኤ.አ ከ2012 ዓ.ም ጀምሮ በሰንዳፋ አካባቢ ዱግዴራ በተሰኘ መንደር የማህበረሰብ ልማት ፕሮጀክት በመተግበር ላይ እንደሚገኝም ተገልጿል፡፡ ፕሮጀክቱ “ኤልጂ ሆፕ ቪሌጅ” የሚል መጠሪያ ያለው ሲሆን የመንደሩ ነዋሪዎች እራሳቸውን ለዘለቄታው እንዲችሉ በእርሻና በእንስሳት እርባታ ስልጠናና ድጋፍ የሚያገኙበት ነው ተብሏል፡፡
ኤልጂ ግብርና ላይ ከሚያደርገው ድጋፍ በተጨማሪ የተለያዩ የልማት ስራዎችን በማስፋፋት በአካባቢው ለሚገኙ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤቶች የተለያዩ ድጋፎችን ሲያደርግ የቆየ ሲሆን በሰንዳፋ ወረዳ ለሚገኙ አራት ት/ቤቶች ከማስፋፊያ ግንባታዎች ጀምሮ እስከ ትምህርት መርጃ መሳሪያዎች ድረስ ድጋፍ አድርጓል፡፡
ኤልጂ በስሩ በሚገኘው ኢኖቴክ ኩባንያ አማካኝነት ላለፉት ወራት ለሙዳ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ድጋፍ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን አሁን ደግሞ ት/ቤቱን በማደስ እንዲሁም ለተማሪዎች ቦርሳ፣ የመማሪያ መፃህፍት፣ የመማሪያ ዴስኮች፣ ወንበሮችና ጥቁር ሰሌዳዎችን ባለፈው ሕዳር ወር መጨረሻ በት/ቤቱ በተሰናዳው ዝግጅት አበርክቷል፡፡
ት/ቤቱ ከከተማ ባለው ርቀት የተነሳ በአዲስ መልክ ለመገንባትና በተፈለገው መልኩ ለትምህርት አመቺ ለማድረግ አስቸጋሪ ቢሆንም የመማሪያ ክፍሎቹን ባሉበት በማደስ፣ የቀድሞዎቹን አሮጌና ለመማር ማስተማር አመቺ ያልነበሩትን ክፍሎች የተሻለ ብርሃን እንዲያገኙ፣ እንዲሁም የክፍሎቹ ወለሎችና ግድግዳዎች እንዲፀዱ ተደርጓል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የተማሪዎች መፀዳጃ በመማሪያ ክፍሎቹ አቅራቢያ እንዲሆን በማድረግ ከዚህ ቀደም ተማሪዎች መፀዳጃ ለማግኘት እስከ 10 ደቂቃ ይወስድባቸው የነበረውን የእግር ጉዞ አስቀርቷል ተብሏል፡፡

Saturday, 13 December 2014 11:24

የሀገሩን ሰርዶ በሀገሩ በሬ

በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ማህበራት ከማህበራዊ ህይወት ጅማሮ አንስቶ የሚሰፈር ዕድሜ አላቸው:: በመሆኑም ሰዎች ከአንድ በላይ ሆነው መኖር ከጀመሩበት ጊዜ እስካሁን ድረስ ህልውናቸው ጉልህ ሆኖ ይታያል፡፡ ዓይነታቸውና ቅርፃቸውም እንደ ዕድሜያቸው ሁሉ ለአሀዝ አዳጋች ነው፡፡ለዚህ ጽሁፍ ዓላማ ሲባል ሊቃኙ የታሰቡት በሰዎች የማህበራዊ ህይወት ውስጥ አይነተኛ ድርሻ ያላቸው ማህበራትን ነው፡፡ እነዚህ ማህበራት እንደ እድር፣ ዕቁብ፣ ደቦ፣ አፎሻ፣ ጅጌ፣ ወዘተ በመባል ይታወቃሉ፡፡ እነዚህና መሠል ማህበራት የሰዎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሰርዶ ከሥሩ በመመንገል የማህበራዊ ህይወታችን በሬዎች ለመሆናቸው የሚከራከር ቢኖር አንድም ጣዕማቸውን ያልቀመሰ አልያም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ አቀፍ ማህበራዊ ትሥሥር የከነፈ ሊሆን ይችላል፡፡
የሁላችንም የህይወት ተሞክሮ ከተለያዩ የባለሙያዎች ጥናቶች ጋር ተዳምሮ የሚያሳየን ዕውነታ - ዕድሮችና ማህበራት የሰዎችን የመረዳዳት፣ የመተጋገዝ፣ አብሮ የመስራት፣ አብሮ የማዘን፣ አብሮ የመደሰት፣ ወዘተ እሴት እያጎሉ ዘመናትን መሻገራቸውን ነው፡፡
አዎ! በርግጥም ማህበራቱ በዕለት ተዕለት የማህበራዊ ህይወታችን ጉልህ ድርሻን ይጫወታሉ፡፡ ከዚህም አልፎ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተወሰኑት በማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ልማት /socio-economic/ ዘንድ አንቱ የተባለ አስተዋጽዖ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ በኤች አይቪ ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር፣ በአካባቢ ንፅህናና ጥበቃ፣ በግጭት አፈታት፣ በህፃናት አስተዳደግ፣ ወዘተ ሚዛን የሚደፋ አስተዋጽኦ በማድረግ ላይ ናቸው፡፡ ለአብነት ያህል በኢየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት ድጋፍና እገዛ አማካኝነት ወደ አርባ የሚጠጉ ማህበራት ባለፉት ሁለት ዓመታት የሚከተሉትን ተግባራት አከናውነዋል፡፡
ሁለት ሽህ አምስት መቶ ያህል አስዳጊዎች የተለያዩ የንግድ ሥራ ክህሎት ሥልጠና በመስጠትና ከፊል ብድር ድጎማ በማቅረብ የራሳቸውንና የቤተሰባቸውን ህይዎት እንዲያሻሽሉ አግዘዋል፤
አምስት ሺህ ለሚደርሱ ህፃናት የትምህርት መርጃ ቁሳቁስ ደግፈዋል፤
ሁለት ሺህ ያህል አሳዳጊዎቻቸውን ያጡና ተጋላጭ ህፃናት የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ አድርገዋል፤
አንድ መቶ ስልሳ አምስት መደበኛ ትምህርት ቤት መግባት ያልቻሉ ህፃናትን የአማራጭ መሠረታዊ ትምህርት ተጠቃሚ አድርገዋል፤
የከፍተኛ ትምህርት ዕድል ላላገኙ ሰባ ስድስት ህፃናት አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ የከፍተኛ ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ አድርገዋል፤
ከአምስት መቶ በላይ የቤተሰብ አባላት የሚኖሩባቸውን ሃምሳ ሁለት ቤቶች አስጠግነዋል፤
በከፍተኛ ችግር ላይ ለነበሩ ሁለት ሺህ አምስት መቶ ያህል ህፃናት የአልባሳትና መሰል ድጋፎችን አድርገዋል፤
በተጨማሪም ለስድስት መቶ ያህል ሥራ አልባ ወጣቶች የተለያዩ የሙያ ሥልጠናዎችና የመሥሪያ ካፒታል ብድር በማገዝ ወደ ሥራ አሰማርተዋል፤
ይህንና መሠል ተግራባትን ያከናወኑ ማህበራት የነበሩ፣ ያሉና ምናልባትም የሚኖሩ ማህበራት ሲሆኑ ከነዚህ ውስጥ ዕድሮች፣ የእድር ህብረቶች፣ የአንድ አካባቢ ተወላጆች ማህበር፣ የተወሰነ ትምህርት ቤት የቀድሞ ተማሪዎች ማህበር፣ የመንግሥት ሠራተኞች በራሳቸው አነሳሽነት ለሌሎች ድጋፍ ለማድረግ የተቋቋሙ ማህራት፣ ወዘተ ይገኙበታል፡፡
እነዚህ ማህበራት በውስጣቸው የተሰባሰቡ በርካታ አባላት ያሏቸው ሲሆን በህብረተሰቡ ዘንድ በጣም ተቀባይነት ያላቸው፣ በመተማመንና በመተሳሰብ የሚሰሩ፣ የማህበረሰብ ጥቅምን የሚያስቀድሙ፣ ዲሞክራሲያዊነት - ግልፅነት - ተጠያቂነትን ያሰፈኑ፣ የሚያገለግሉትን የማህበረሰብ ክፍል ለማገልገል ቆርጠው የተነሱና በትትርና የሚሰሩ ማህበራት ናቸው፡፡ እንዲያው ባጠቃላይ ማህበራቱ ተገቢው እገዛ ቢደረግላቸው የሀገራችንን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሰርዶ ሲቻል የመመንገል አልያም የማጠውለግ ትልቅ አቅም ያላቸው የማህበረሰብ እንቁ ሀብት ናቸው፡፡
ይሁን እንጂ የሚመለከታቸው አካላት በተለይም መንግሥት፣ ለጋሽ ድርጅቶች፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት፣ ራሱ ማህበረሰቡ ማህበራቱን በሚፈለገውም ሆነ በሚጠበቀው መጠን ሲጠቀሙባቸው አይታዩም፡፡ ኢየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት የእነዚህ የማህበረሰቡ ምስርት ተቋማትን ልማታዊ አስተዋፅኦ አበክሮ በመገንዘብ በተለይም ካለፉት 15 ዓመታት ጀምሮ በማህበራት ዙሪያ በሥፋት በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡ በአሁኑ ሰዓት በላይ ጋይንት፣ አውራ አምባ፣ ባህር ዳር፣ ደ/ማርቆስ፣ አዲስ አበባ፣ ደ/ብርሃን፣ ደ/ሲና፣ ቢሾፍቱ፣ አዳማ፣ ድሬዳዋ፣ ሶማሌ ክልል ሽንሌ ዞን፣ መልካጀብዱ፣ ሻሸመኔ፣ አጄ፣ሃዋሳ፣ ቡታጂራ፣ እምድብር፣ ወልቂጤና ጅማ ከሚገኙ ከ140 ያህል የማህበረሰብ ምስርት ተቋማት/ ማህበራት ጋር እየሰራ ይገኛል፡፡ በመሆኑም የማህበራቱን ነባራዊ አቅም በማጎልበት ማህበራቱ ለየማህበረሰባቸው ከሚሰጡት ማህበራዊ አገልግሎቶች በተጨማሪ በማህበረሰቡ ውስጥ ተንሰራፍቶ የሚገኘውን የህፃናት፣ የወጣቶችና ሴቶች ችግር መፍታት እንዲችሉ ተደርጓል፡፡የኢየሩሳሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት የማህበራት ልማት / CBOs Development/ ተሞክሮ እንደሚያሳየው፣ የማህበራቱን አቅም በተለይ ፕሮጀክት የመፈፀም፣ ሂሳብ አያያዝና የአካባቢ ሃብት አጠቃቀም ስልትና መሰል ዘመናዊ አሰራሮች ረገድ የማህበራቱን አቅም በማጎልበት ማህበራቱ በፍትሃዊነት፤ ባነሰ ዋጋ፣ በተደራሽነት፣ ወዘተ በርካታ ችግር ፈቺና ልማታዊ ሥራዎችን እንዲሰሩ ማድረግ ይቻላል፡፡
አዎ! በመላ ሀገራችን ያሉ የህብረተሰቡ የሆኑ ማህበራትን በተቀናጀ መልክ ለልማት ማንቀሳቀስ ቢቻል የማይረታ የችግር ሰርዶ አይኖርም፡፡ እነዚህ በርካታ ቁጥር ያላቸው ማህበራት በትንሽ ሀገር በቀል ዕገዛ፣ በሀገርኛ መንገድ፣ ሀገራዊ ችግሮችን የመፍታት ዕምቅ ችሎታና ሀይል አላቸው፡፡ ስለሆነም የኢየሩሳሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅትና የሌሎችንም ጥቂት ተሞክሮዎች መነሻ በማድረግ የተቀናጀ ድጋፍና እገዛ በማድረግና እንዲሁም ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር ማህበሮቻችንን ለማህበረሰቡ ፋይዳ እንጠቀም!!
ተስፋዬ ይሁኔ

Saturday, 13 December 2014 11:13

የትራንስፖርት ገጠመኝ

ወያላው    ተሳፋሪ! ተሳፋሪ!
አዲስ አባ በፈሪ

አባት    ምን ማለቱ ይሆን?
ልጠይቅ ምስጢሩን…
ደገመ አሁንም አምርሮ፣
ማንን ፈርቶ ቃል ጨምሮ፡፡
ምን ማለቱ እንደሆን ልጠይቀው ብዬ፣
ጠጋ እያልኩ እየፈራሁ እቃዬን አዝዬ፡፡

ወያላው    ግቡ! ግቡ! ፋዘር መኪናው ፈሪ ነው፣
ሰውም እየበዛ ሲሄድ ቀስ ብሎ ነው፡፡
አትጠራጠሩ በልኩ ይጭናል፣
ሹፌሩ ፈሪ ነው ቀስ ብሎ ይነዳል፡፡
መንገድ ላይ መንከርፈፍ ሁሌ ልማዱ ነው፣
ምናልባት - ምናልባት ነገ ቢገባ ነው፡፡

አባት       ስለዚህ ብሎ… ብዙ ሳያወራ፣
ካፉ ላይ ቀማሁት ይሄን ወሮበላ፡፡
ምን ማለትህ ይሆን? ግራ ገባኝ ባክህ፣
ማከላከልህ ነው ቋንቋ ማሳመርህ፡፡
ዞር በል ከበሩ - ሰው እጠይቃለሁ፣
ከአንተ ጋር ሳወራ - ጊዜ አቃጥያለሁ፡፡

ወያላፋዘር ይቅርቦ ለርሶ አዝኜ ነው፣
መኪናው ቀርፋፋ ነገ ቢደርስ ነው፡፡

አባትምን ታዝንልኛለህ - የትስ ታውቀኛለህ?
በጣም ነው የማዝነው ለካስ ደላላ ነህ፡፡

ወያላይኸው ሚኒባሱ - ፋዘር በዚሂዱ፣
ስለ ንግግሬ ብዙ አይናደዱ፡፡
ወዲያው ይደርሳሉ ካሰቡበት ቦታ፣

አባትብሎ ሳይጨርስ ይሄንን ወስላታ፣
በለው! በለው! አለኝ ወኔዬ መጣና፡፡
እሱ መቼ ፈርቶ ማንንስ አክብሮ፣
መለፍለፍ ቀጥሏል መሬት አቀርቅሮ፡፡

አሠለፈች አበበ ደሳለኝ
አዳማ (ናዝሬት)