Administrator

Administrator

* “ብዙ ብር ከፍለን የዓይን ብርሃናችንን አጥተን ተመልሰናል”  -ታካሚዎች
* ከመነሻው የማዕከሉ አደረጃጀት አዋጁን የሚቃረን ነው - - የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ
* ማዕከሉ በየዓመቱ የሚታደስ የህክምና አገልግሎት ፈቃድ አልተሰጠውም

             ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት የተሻለ የአይን ህክምና ለመስጠት፣ ለኢትዮጵያውያን ሀኪሞች የቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲያደርግና በዘርፉ ምርምርና ጥናት እንዲያካሂድ ታስቦ በዘውዲቱ ሆስፒታል ግቢ ውስጥ የተገነባው የህንድ የአይን ህክምና ማዕከል በታካሚዎች ላይ ጉዳት እያደረሰ መሆኑ ተገለፀ፡፡
ጉዳት የደረሰባቸው ታካሚዎች እንደተናገሩት በማዕከሉ በተሰጣቸው ህክምና ሳቢያ የዓይን ብርሃናቸውን አጥተዋል፡፡ በማዕከሉ የሚሰሩ ኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት የተሟላ የህክምና ቁሳቁስ፣ በዘርፉ በቂ እውቀት ያላቸው ባለሙያዎችና ደረጃውን የጠበቀ ግንባታ ሳያሟላ የሚሰጠው ጥራቱን ያልጠበቀ አገልግሎት ዜጎችን ለአይነ ስውርነት፣ ለተጋነነ ወጪና ለእንግልት እየዳረገ ነው፡፡
ማዕከሉ ለኢትዮጵያውያን ሃኪሞች የቴክኖሎጂ ሽግግር ያደርጋል ቢባልም ሁሉም የህክምና ቁልፍ ቦታዎች በህንዳዊያን በመያዛቸው እቅዱ እንዳልተሳካና ከስምምነት ውጪ በተጋነነ የደሞዝ ክፍያ ምዝበራ እንደሚፈፀም ተገልጿል፡፡
የአይን ህክምና ማዕከሉ ከተለያዩ ተቋማት ገምጋሚ ተመድቦለት የአንድ ዓመት ተኩል የስራ አፈፃፀሙ በተገመገመበት ወቅት ከግንባታው ጀምሮ ችግር እንዳለበት በመግለፅ ችግሩ ሳይቀረፍ የትኛውም የመንግስት አካል ለማዕከሉ ድጋፍ እንዳያደርግ ገምጋሚዎቹ ቢያስጠነቅቁም ፈቃድ አግኝቶ ደረጃ ሳይወጣለት፣ ጥራቱን ሳይጠብቅና ባለሙያና መሳሪያ ሳያሟላ ወደ ስራመግባቱ ተገቢ አልነበረም ተብሏል፡፡ መንግስት በተቋሙ ላይ አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ እንዳለበትም ገምጋሚዎችና የማዕከሉ ሰራተኞች አሳስበዋል፡፡
ከመነሻው የኢትዮጵያ ነዋሪዎች በጎ አድራጎት ድርጅት መሆኑ እየታወቀ የጤና ማዕከሉ፣ ሜዲካል ዳይሬክተር፣ ስራ አስኪያጁ፣ የሃብት ማፈላለጉና ሌሎች ከፍተኛ ኃላፊነቶች በውጭ ዜጎች መያዛቸው የፌደራል በጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ኤጀንሲ አዋጅን ፍፁም የሚቃረን ነው ያሉት በአዲስ አበባ ጤና ቢሮ የጤና ፕሮጀክት ክትትል እና ድጋፍ ባለሙያ አቶ ጥላሁን አለሙ፤ ማዕከሉ በርካታ  ዘርፈ ብዙ ችግሮች ያሉበት መሆኑንና የተጠቃሚን አቅም ያላገናዘበ፣ ባለሙያ ያልተሳተፈበትና በከተማ አስተዳደሩ ስልጣን በተሰጠው አካል ያልፀደቀ የክፍያ ተመን በማውጣት የተጋነነ ክፍያ የሚያስከፍል፣ በጤና ንግድ ስራ ላይ የተሰማራ ድርጅት ነው ብለዋል፡፡
የጤና ማዕከሉ ካሉበት ችግሮች ውስጥ የማዕከሉ የውጭ ሞያተኞች የጤና የስራ ፈቃድ ከመውሰዳቸው በፊት ከኦፕሬሽን ጀምሮ ሌሎች የህክምና አገልግሎቶችን እየሰጡ እንደሆኑ የገምጋሚዎቹ ሪፖርት ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም ማዕከሉ በየዓመቱ የሚታደስ የህክምና አገልግሎት ፈቃድ ያልተሰጠው ህገ-ወጥ ተቋም ነው ሲልም ሪፖርቱ ገልጿል፡፡
አቶ ወ/ፃዲቅ ማናዬ ይባላሉ፤ የ62 ዓመት አዛውንት ናቸው፡፡
አዲስ አበባ ቂርቆስ ክ/ከተማ ኦሎምፒያ አካባቢ ይኖራሉ፡፡ “አምና መጋቢት ወር ላይ ዓይኔን ታምሜ ወደ OIA የሄድኩት ህንዶቹ ጥሩ ህክምና ይሰጣሉ ተብዬ ነው ያሉት አዛውንቱ፤ በመጀመሪያ የሞራ ግርዶሽ ነው ተብለው 4250 ብር ከፍለው የቀዶ ህክምና ማድረጋቸውን ይናገራሉ፡፡ “በመጨረሻ እራሳቸው በፈጠሩት ስህተት ከአንድም ሶስት ጊዜ ኦፕራሲዮን ተደርጌ ሬቲናዬን አበላሹት” የሚሉት አዛውንቱ፤ ከዚያም በኋላ ያለ ምንም መድሃኒትና እርዳታ ዝም ብለው እንዲጠብቁ በመደረጋቸው ቀኝ አይናቸው ሙሉ ለሙሉ ከጥቅም ውጭ ሆኖ ማየት እንደተሳናቸው በምሬት ገልፀዋል፡፡
ያለ ምንም መድሃኒት ለሁለት ወር ቀጠሮ ሰጥተውኝ ስመለስ “ያንተ የሬቲና ችግር ነው አሉኝ” የሚሉት አቶ ወ/ፃዲቅ፤ “የሬቲና ችግር ከሆነ ለምን ሶስት ጊዜ አደንዝዛችሁ ሞራ ነው በማለት ኦፕሬሽን አደረጋችሁኝ” በማለት ህንዳዊ ሀኪሞቹን መጠየቃቸውን፤ ነገር ግን ከማመናጨቅ ውጭ ቀና ምላሽ ማጣታቸውን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ “ወደ ሌላ ህክምና ለመሄድ ሪፈር ፃፉልኝ፤ አለበለዚያም እናንተ ጋር ያደረግሁትን አጠቃላይ የህክምና መረጃ ስጡኝ” ብለው መጠየቃቸውን የሚናገሩት አዛውንቱ፤ የምናውቀው ነገር የለም የፈለጋችሁበት ሄዳችሁ ክሰሱን፤ ምላሽ እንሰጣለን” በማለት አመናጭቀው እንደሸኟቸውና እይታቸውን አጥተው ቤት ውስጥ ከተቀመጡ 10 ወር እንዳለፋቸው ገልፀው፤ ማንበብና መፃፍ ሁሉ እንደተሳናቸው ተናግረዋል፡፡
በዚሁ የአይን ህክምና ማዕከል የህክምና ስህተት ተፈጽሞብኛል ያሉት የ65 ዓመቱ አዛውንት አቶ ኮሬ ወ/ማርያም፤ ባለፈው ዓመት ግንቦት ወር ላይ ለህክምና ሲሄዱ የሞራ ግርዶሽ ነው ተብለው አምስት ሺህ ብር ከፍለው ኦፕሬሽን መደረጋቸውን አስታውሰው፣ በ15ኛው ቀን አይናቸው ሙሉ በሙሉ ጠፍቶ ወደ ማዕከሉ ተመልሰው መሄዳቸውን ይናገራሉ፡፡
“አይኔ መጥፋቱን እያወቁ አንድም ጠብታ ሳያዙልኝ ወደ ምኒልክ ሆስፒታል እንድሄድ ነገሩኝ” የሚሉት አዛውንቱ፤ ምኒልክ ሆስፒታል ሁለት ሶስት ጊዜ ቢመላለሱም ምንም እርዳታ ሳያገኙ ሲኤምሲ አትሌቲክስ ህንፃ ላይ በሚገኘው “ብሩህ ቪዥን” ክሊኒክ እንዲታከሙ እንደተነገራቸው ገልፀዋል፡፡
“ብሩህ ቪዥን አንዴ በመርፌ፣ ሌላ ጊዜ በመሳሪያ ይታይ እያሉ ለተጨማሪ 7ሺህ ብር ወጪ ተዳርጌያለሁ” ያሉት እኚህ ታካሚ፤ አራት ወር እንደሆናቸውና አይናቸውንም አጥተው፣ 12 ሺህ ብራቸውን በማፍሰስ ለተጨማሪ ችግር በመዳረጋቸው ተጨማሪ ወጪ እንደሚጠብቃቸው ተናግረዋል፡፡
“የተሟላ መሳሪያ ሳይኖር፣ በዘርፉ የሰለጠነ በቂ ሀኪም በሌለበት የህክምና ማዕከሉ እንዴት ፈቃድ ተሰጠው?” ሲሉ የሚጠይቁት አቶ ኮሬ፤ “መንግስት ለዜጎቹ የሚጨነቅ ከሆነ እንዲህ አይነቶቹን ተቋማትና ሰራተኞች ለፍርድ ማቅረብና ኢንሹራንስ ለተጎጂዎች እንዲከፍሉ፣ ከዚያም በአስቸኳይ ማዕከሉን ዘግቶ ከጥፋታቸው ማስቆም ያስፈልጋል” በማለት ብለዋል፡፡
ወደ ህክምና ማዕከሉ ከመሄዳቸው አስቀድሞ መኪና መንዳት ይችሉ እንደነበር የተናገሩት  የ66 ዓመቱ አዛውንት፤ ከአንድ ዓመት በፊት ህክምና መጀመራቸውን ይናገራሉ፡፡ “ችግሩ የሞራ ግርዶሽ ነው፤ ይህን በቀላሉ እንገፍልሃለን ብለው ኦፕሬሽን ካደረጉኝ በኋላ ጭራሽ አይኔ ማየት አቁሞ ቤት ተቀምጫለሁ” ሲሉ በምሬት የገጠማቸውን ችግር ገልፀዋል፡፡
“ከዚያ በኋላ አይኔ ጠፋ ብዬ በተከታታይ ብመላለስም ምንም መፍትሄ ሳላገኝ እስካሁን አለሁ” ያሉት አዛውንቱ፤ “እርግጥ እኔ የካርድ 40 ብር ከመክፈል በስተቀር ያወጣሁት ወጪ የለም፤ ምክንያቱም የነፃ ህክምና ወረቀት አፅፌ ነበር የሄድኩት” ብለዋል፡፡ እሳቸው ደግሞ የጨረር ህክምና ተደርጐላቸውም መሻሻል እንዳላሳየ ገልፀው ወደ ምኒልክ ሆስፒታል ሪፈር እንደተፃፈላቸው ይናገራሉ፡፡ “ሚኒልክ ሆስፒታል ሄጄ ስመረመር አይንህ ተበላሽቷል፤ የማየትም ተስፋ የለውም ብለው መለሱኝ” የሚሉት ተጎጂው፤ ተስፋ ቆርጠውና እይታቸውን ተነጥቀው ቤት መቀመጣቸውን ጠቅሰው ወዴት አቤት እንደሚባል ግራ እንደገባቸው፤ ይህን ላድርግ ቢሉም አቅምና የእይታ ችግር እንደማይፈቅድላቸው ተናግረዋል - “እግዜር ይክሰሳቸው” ሲሉም በምሬት ተናግረዋል፡፡
በአንድ የመንግስት የሚዲያ ተቋም ውስጥ የሚሰራ ጋዜጠኛ ነው፡፡ ለህክምና ወደ ማዕከሉ መሄዱንና መቶ ብር ከፍሎ ካርድ ማውጣቱን ይናገራል፡፡ እንደ ሌሎቹ የሞራ ግርዶሽ ችግር ሳይሆን ረጅም ርቀት እይታ ችግር እንዳለበት ተነግሮት፤ ለህክምናው መዘጋጀቱን ነገር ግን በመሃል ወረፋ ሲጠብቅ ስለ ማዕከሉ መጥፎ መጥፎ ነገሮች ሲነገሩ በመስማቱ ህክምናውን እንዳቋረጠ ይናገራል፡፡ “ችግሬን ከድጡ ወደ ማጡ አላደርግም ብዬ ህክምናውን አቁሜ ይልቁንም ክሊኒኩ ውስጥ አለ የተባለውን አሻጥር እየመረመርኩ ነው” ያለው ጋዜጠኛው፤ በማዕከሉ ከሚሰሩ ኢትዮጵያውያን የህክምና ባለሙያዎች የሰማው እጅግ የሚዘገንን ህገ-ወጥ አሰራር አይነ ስውር ከመሆን ያተረፈውን አምላኩን እንዲያመሰግን እንዳደረገው አጫውቶኛል፡፡
ማዕከሉ ከዚህ በተጨማሪም በብልሹ አሰራሮች መተብተቡን የግምገማ ሪፖርቶቹ ይጠቁማሉ፡፡ በሪፖርቱ ከተጠቀሱት ችግሮች መካከል የፋይናንስ፣ የግዢና የሰው ሃብት አስተዳደር ማኑዋሎች የሌሉትና ለምዝበራ የተመቻቸ መሆኑ፣ ማዕከሉ በአዋጅ ኃላፊነትና ስልጣን በተሰጠው ደረጃ መዳቢ አካል ደረጃ ያልወጣለት መሆኑና በምስራቅ አፍሪካ አንደኛ የተባለው ማዕከል ምንም አይነት የላብራቶሪ፣ የጠቅላላ ሰመመን፣ የድንገተኛና መሰል የአገልግሎት ክፍሎች ያልተሟሉለት መሆኑ ይገኙበታል፡፡
በሃገር ውስጥ ሊሟሉ የሚችሉ የቢሮ ቁሳቁሶች በከፍተኛና ወጪ ከውጭ ከመግባታቸው በተጨማሪ ተፈራራሚ አካላት ቢያንስ በፅሁፍ እንዲያውቁት አለመደረጉ የተጠቆመ ሲሆን የፕሮጀክት ክለሳ ሳይደረግ ከእቅድ ውጭ ለሆነ ግንባታ 634ሺ 986 ዶላር እንዲሁም ለህክምና መሳሪያና ለቢሮ ቁሳቁስ 315ሺ 171 ከ37 ሳንቲም በድምሩ 950ሺ 157 ከ37 ዶላር ያለ አግባብ ወጪ መደረጉን የገምጋሚው ኤክስፐርት ሪፖርት አመልክቷል፡
ጉዳዩን ለማጣራት ወደ ማዕከሉ ሄደን የተለያዩ ህንዳዊያን ሃኪሞችን ለማነጋገር የሞከርን ሲሆን የማዕከሉ ዋና ዳይሬክተር ወደ ህንድ በመሄዳቸው መረጃ ማግኘት የምንችለው እሳቸው ሲመለሱ ብቻ እንደሆነ ተገልፆልን ተመልሰናል፡፡

Saturday, 29 November 2014 11:42

ፍቅርተና የፍቅር ዲዛይኗ

በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪና ስነ አእምሮ ያጠናችው ፍቅርተ አዲስ፣ በአልባሳት ጥበብ (ፋሽን ዲዛይን) የተዋጣላት ባለሙያ ናት፡፡ ከአራት ሺ ብር ገደማ አንስቶ እስከ 20 ሺ ብር የሚያወጡ የሰርግ ልብሶችን ለበርካታ ደንበኞች ማዘጋጀት፣ በተለይም በሰርግ ወራት ፋታ እንደሚያሳጣ የምትናገረው ፍቅርተ፤ የአልባሳት ጥበብን ኑሮና መተዳደሪያዋ አድርጋዋለች፡፡ ከሞሮኮ እስከ ጃማይካ፣ ከፓሪስ እስከ ኒውዮርክ በርካታ ትርኢቶችን አቅርባም እውቅናና ሽልማት አትርፋበታለች፡፡ ነገር ግን የስነ አእምሮ ትምህርቷ ባክኖ አልቀረም፡፡ የስራዋና የህይወቷ አካል ሆኗል፡፡ ቢቻል ሁሉም ሰው፣ በተወሰነ ደረጃ የስነ አእምሮና የፍልስፍና እውቀት ቢኖረው ይመረጣል ብላ ስትናገር ለወጉ ያህል አይደለም፡፡ ከአለባበስና ከአረማመድ ጀምሮ፣ የጨርቅ ቀለም ምርጫና የልብስ ዲዛይን ፈጠራ፤ የሰርግ ውድ ልብስና የትምህርት ቤት ዩኒፎርም ሳይቀር ከስነ አእምሮ ጋር ይገናኛል፡፡ የስራ ባልደረቦች ግንኙነትና የቤተሰብ ሁኔታ፣ የደንበኞች ፍላጎትና መስተንግዶም እንዲሁ፡፡ የአገር ገፅታና የዓለም ገበያ፣ የፆታ ጥቃትና የልጆች አስተዳደግ ከስነ አእምሮና ከፍልስፍና ጋር የተያያዘ ነው ለፍቅርተ፡፡ ተወልዳ ባደገችበት አዲስ አበባ “የፍቅር ዲዛይን” የተሰኘ ቢዝነስ የከፈተችው ፍቅርተ፤ ስለ ልብስ ምርጫ እንዲህ ትላለች - ለአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ፡፡

ብዙ ሰው፤ ፋሽን ነው ተብሎ የሚመጣውን ነገር ሁሉ መልበስ ይፈልጋል፡፡ ነገር ግን ሁሉም ይስማማዋል ማለት አይደለም፤ የራስን የሰውነት ቅርፅና ቁመና መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ በዚያ ላይ ሁሉም ሰው የራሱ የሆነ የግል ማንነት አለው፡፡ ፕሮፌሽናል ዲዛይነር እነዚህን ነገሮች ያገናዘበ ምክርና አገልግሎት ለደንበኞቹ መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ ሙያዬ ስለሆነ ደንበኞችን በደንብ አስተናግዳለሁ፡፡ ደንበኞች ሲመጡ፣ ለሰውነታቸው ቅርፅና ቁመት፣ ለሚፈልጉት ፕሮግራምና ዝግጅት፣ ለሚለብሱበት ሰአትና ለማንነታቸው  የሚስማማ ልብስ  እሰራለሁ፡፡ አንዳንድ ሰዎች በጣም ጎበዞች ናቸው፣ የሚያምርባቸውን ያውቃሉ፡፡ ከነሱ ጋር የማይሄድ ነገር የሚመርጡትንም ሰዎች ማስተናገድና በሙያዊ ምክር ማስተማር በጣም ደስ ይለኛል፡፡ ለምሳሌ ጋቢ ወይ ቡፍ የሚል ቀሚስ፣ ወፈር ላለ ሰው አይመከርም፡፡ ይህን የሚመርጡ ሲመጡ፣ ቁጭ ብዬ ጊዜ ሰጥቼ በተለያዩ ጨርቆች የተሰሩ ልብሶችን እየሞከሩ እንዲያዩ እና እንዲመርጡ እረዳቸዋለሁ፡፡  እኔ በጣም የሚያረካኝ አንድ ልብስ ጀምሬ ስጨርስና  የሰራሁላቸው ሰዎች በጣም ሲደሰቱ ሳይ ነው፡፡

የስነ አእምሮ ትምህርት - የአልባሳት ጥበብ
የመጀመሪያ ዲግሪዬን በኤዱኬሽናል ሳይኮሎጂ፣ የሁለተኛ ዲግሪዬን ደግሞ በዴቨሎፕመንታል ሳይኮሎጂ አግኝቻለሁ፡፡ የስነ አእምሮ ትምህርት በዚያው መስክ ላይ ለመቀጠር ሳይሆን በአጠቃላይ ለህይወቴ ጠቅሞኛል፡፡ እንዲያውም ገና ተምሬው አልጠገብኩም፤ ወደ ላይ እቀጥላለሁ፡፡ በእርግጥ ትምህርቱ ከስራ እና ከቤተሰብ ሀላፊነት ጋር በጣም ይከብዳል ግን በየእለቱ ሀያ አራት ሰአት አለሽ፡፡ የኛ የሰዎች ፋንታ፣ ቅድሚያ ለምትሰጪው ነገር ሰዓት መስጠት ነው፡፡  ትምህርት ከጨረስኩ በኋላ አፕሪፍስ በተባለ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ተቀጥሬ፤ ጥቃት ለደረሰባቸውና በህገወጥ የሰዎች ዝውውር ለተጎዱ አማካሪ ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ ህፃናቱ ከቤተሰቦቻቸው እና ከማህበረሰቡ ጋር ከመቀላቀላቸው በፊት የስነልቦና ምክር በመስጠት እንዲዘጋጁ እረዳቸዋለሁ ማለት ነው፡፡ በዚህ ስራ ትልቁ የተማርኩት ነገር ምን መሰለሽ? ለነዚህ ልጆች የቱንም ያህል የስነልቦና እና ማህበራዊ ድጋፍ ብትሰጫቸው ኢኮኖሚው ላይ እሰካልተሰራ ድረስ ምንም ለውጥ አይመጣም፡፡

የዲዛይን ህይወትስ ከወዴት መጣ?
ዲዛይን ከልጅነቴ ጀምሮ ቀልቤን የምሰጠው ነገር ነው፡፡ የዘጠነኛ ክፍል ተማሪ በነበርኩበት ጊዜ ነው የንድፍ ስዕል መስራት የጀመርኩት፡፡ እናቴና አክስቴ ልብስ ስፌት ይማሩ ነበር፡፡ ሁለቱም እየረዱኝ፣ ቤት ውስጥ በእናቴ የልብስ መስፊያ ማሽን በመቀስና በስፌት ማሽን ተለማመድኩ፡፡ የራሴን ልብሶች መለማመጃ አደረኳቸው፡፡ ልብሶቼን በተለያየ መንገድ እየቀያየርኩ፣ ገና የልብስ ስፌት ትምህርት ቤት ከመግባቴ በፊት ልብስ መስፋት እችል ነበር፡፡ ለራሴ ለጓደኞቼ እና ለቤተሰቦቼ ስሰራ፣ ከዚያ እነሱ የሚያውቋቸው ሰዎች ሲያዩ፣ በሰው በሰው ስራ እየመጣልኝ … ለካ ሳላውቀው ስራው ውስጥ ገብቼያለሁ፡፡ ሰዎች በአጋጣሚ አግኝተው ለሰርግ ልብስ ሰርተሽልን ነበር ሲሉኝ እደነግጥ ነበር፡፡ ከዛሬ አምስት አመት በፊት ነው ሙሉ ለሙሉ ወደዚህ ሙያ ጠቅልዬ የገባሁት፡፡ የስነ ልቦና ስራዬንና የዲዛይን ሙያዬን ደርቤ መስራት አልፈልግም፡፡ ከልጆቼ ጋር ብዙ ጊዜ ማሳለፍ ስላለብኝም ጊዜዬን በራሴ መንገድ ለመጠቀም ወስኜ፤ ይኸው እስከአሁን እየሰራሁ ነው፡፡

ትልቁ ፈተና - ፋታ የሚያሳጣ ሙያ
 ሌሎች ዲዛይነሮችም የሚጋሩት ይመስለኛል፡፡ በጣም ፈታኙ ነገር ስራን እና የቤተሰብ ህይወትን አንድ ላይ አጣጥሞ የማስኬድ ፈተና ነው፡፡ የዲዛይን ሙያ በጣም ጊዜ ይፈልጋል፡፡ በተለይ የሰርግ ወቅቶች ሲመጡ ትንፋሽ ያሳጣል፡፡ ከዚያ ውጭ ተስማምቶና  ተከባብሮ፣ ሙያውን ከልብ አፍቅሮ የመስራት ጉዳይ ነው፡፡
“የፍቅር ዲዛይን” የራሱ መርህ አለው፡፡ የአገር ውስጥ ምርቶችን እንጠቀማለን፡፡ አማራጭ ሲጠፋ ብቻ፣ የተወሰኑ የውጪ ጨርቆች ብንጠቀምም፤ ልብሶቻችን ከዘጠና በመቶ በላይ ከጥጥ የተሰሩ ናቸው፡፡ በዚያ ላይ የተማርኩት ሳይኮሎጂ ስለሆነ፣ በህፃናት የጉልበት ብዝበዛ ላይ ብዙ ነገር አውቃለሁ፡፡ በአለም ላይ የህፃናት የጉልበት ብዝበዛ እጅግ ከተንሰራፋባቸው ዘርፎች ቀዳሚው የሽመና ዘርፍ ነው፡፡  የጨርቅ ምርት የሚያቀርቡልኝ ባለሙያዎች ከህፃናት ብዝበዛ የፀዱ ናቸው፡፡ ማህበራቸው “በህብረት እናምልጥ” ይባላል፡፡  ቦታ ተሰጥቷቸው ህጋዊ ሆነው የሚሰሩ በሙያው እጅግ የተካኑ ጎበዝ ሰራተኞች ናቸው፡፡ ከሁሉም ጋር ያለኝ ግንኙነት በመከባበርና በእኩልነት ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ እነሱም ይፈልጉኛል፤ እኔም እፈልጋቸዋለሁ፡፡ ራሴን የራሴ አለቃ ሳደርግ ያገኘሁትን ነፃነት ሌሎችም እንዲያገኙ እፈልጋለሁ፡፡ አንድ ሰው ከኔ ጋር አስር አመት ሰርቶ ጡረታ ይዞ ከሚወጣ፤ የራሱን ድርጅት ከፍቶ፣ እሱም በተራው ለሌሎች ሰዎች እድል ሲያመቻች ማየት ያስደስታል፡፡ የስራና የምርት አቅርቦት ሰንሰለት ይፈጠራል፤ ሰዎችም ያድጋሉ፡፡ ይሄ የዘወትር ህልሜ ነው፡፡ ጥልፍ እና ኪሮሽ ከሚሰሩ ሴቶች ጋር እንሰራለን፡፡ ከሴቶች ጋር መስራት እንፈልጋለን፡፡ ግን ሴቶች ማለት እናቶች መሆናቸውንም መርሳት የለብንም፡፡ በስራ ራሳችንን ጠምደን ልጆቻችን እንዴት ሊጠፉ እንደሚችሉ ሳስበው ያስጨንቀኛል፡፡ የየቀኑ ፈተናዬ ነው፡፡ ልጆች ትምህርት ቤት የተማሩትንና፣ የቤትስራ ይዘው የመጡትን፣ መከታተል የአባትና የእናት ሀላፊነት ነው፡፡  ያ ሳይሆን ሲቀር ነው፣ የተዛባ ባህርይ እየተስፋፋ አገር የሚያጠፋው፡፡ ስለዚህ እናቶች ከልጆቻቸው ሳይርቁ ቤታቸው ሰርተው በቀጠሮ ቀን እንዲያመጡ አደርጋለሁ፡፡ ለአንድ የጥልፍ ስራ እስከ 6 ሺ ብር ድረስ እከፍላለሁ፡፡

ሽልማቶች እና እድሎች
እንደጀመርኩኝ ብዙ ሾዎች ነበሩ፡፡ በዚያው አመት አሊያንስ በተዘጋጀ ውድድር ሁለተኛ ወጣሁ፡፡ ያን አጣጥሜ ሳልጨርስ፤ ሞሪሺየስ ላይ ከ12 የአፍሪካ አገሮች የተውጣጡ ዲዛይነሮች የተሳተፉበት “ኦሪጅን አፍሪካ” በተባለ ውድድር ላይ አንደኛ ወጣሁ፡፡ በ2011 ኒውዮርክ የሚካሄደውን “አፍሪካ ፋሽን ዊክ” ተመርጬ አዘጋጀሁ፡፡ በ2012 እዚያው ኒውዮርክ  ውድድሩን ዲዛይነሯ ማፊ በማሸነፏ እኔ ደግሞ እንዳዘጋጅ እንደገና ተመርጬ አዘጋጀን፡፡ አሁንም ለማሳየት እየተዘጋጀን ነው፡፡ ሌላው የአፍሪካ ኢንቨስትመንት ፎረም፣ አጎዋ ላይ ተሳትፈናል፡፡ ፕራግ፣ ፓሪስ፣ ጃማይካ እና ሌሎች ቦታዎችም አሳይቻለሁ፡፡ ሁልጊዜ የኢትዮጵያ ስም ሲነሳ በውጭው ዓለም የተቀረፀው መጥፎ ገፅታ ጎልቶ ይታያል፡፡ አንዳንዶቹ መጥፎ ገፅታዎች የእውነትም የሉም ማለት አይደለም፡፡ ለመለወጥ ብዙ መስራት አለብን፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ በጎ ገፅታዎችን ሳታጣ፣ መጥፎው ብቻ መጋነኑ ሚዛናዊ ስላልሆነ ያበሳጫል፡፡ በውጭ አገራት ትዕይንት ስናቀርብም የተጠቀምነውን የጨርቅ ምርትና ዲዛይኑን አይተው ሲደነቁ እጅግ ያስደስተኛል፡፡
ከሁሉም የሚበልጠው ሽልማት በስራው እውቅና ማግኘት ነው፡፡ ከዚያ ውጪ ያሉንን ባህላዊ እሴቶች መማር ለኔ ትልቅ ነገር ነው፡፡ ጨንቻ ሄጄ በተፈጥሮአዊ መንገድ ልብስ ሲያቀልሙ አይቻለሁ፡፡ ውጪ አገር ለተፈጥሮ ማቅለሚያ የሚከፈለው ገንዘብ ከአርቲፊሻሉ ይበልጣል፡፡ እነዚህን ጥበቦች መማሬ ያስደስተኛል፡፡
ገበያው ምን ይመስላል
የአገር ልብስ ተፈላጊነት እየጨመረ ነው፡፡ በፊት በጣም ጎበዝ ልጆች የነበሩ ቢሆንም ሁኔታዎች ምቹ አልነበሩም፡፡ በፊት ለመልስ ይፈለግ የነበረው የአበሻ  ልብስ፣ አሁን ለሰርግ የሚፈለግ ሆኗል፡፡ ዋጋው ከ3800 እስከ 20ሺህ ይደርሳል፡፡ አንድ ልብስ ስትሰሪ ለዛች ሴት ብቻ ነው የምትሰሪው፡፡ ለምሳሌ አስር ሴንቲ ሜትር ስፋት ያለው ጥልፍ፤ አንድ ጠላፊ ለወር ቁጭ ብሎ የሚሰራው ስራ ነው ለአንድ ወር ጊዜ ተሰጥቶ የተሰራው ስራ ዋጋው ከፍ እንዲል ያደርገዋል፡፡ ከሰርግ ውጪ የሚለበሱት ደግሞ 400፣ 500 ይሸጣሉ፡፡ ዋጋዬ ትንሽ ወደድ ይላል፡፡ ግን የስራው እና የጨርቁ ጥራት ነው፡፡ ማሰብ ያለብን የአገር ውስተር ገበያ ብቻ አይደለም፡፡ የአልባሳት ስራ በደንብ ከሰራንበት በአለም ገበያ ተፈላጊነቱ እንደሚጨምር እርግጠኛ ነኝ፡፡

የትምህርት ቤት ዩኒፎርም  ለምን ግራጫ ይሆናል?
የመጀመሪያው ነገር ምቾት ነው፡፡ የሴት  ተማሪዎች ቀሚስ ከጉልበት በታች ሲረዝም ምቾት አይሰጣቸውም፡፡ ምቾት እና ውበትን፣ አላማንና ስብዕናን አንድ ላይ ማምጣት ይቻላል፡፡ ልጆቼን ሁልጊዜ “ቆንጆ ንፁህ ሰው ሁኑ” እላቸዋለሁ፡፡ ዝርዝሩን እድሜያቸው በጨመረ ቁጥር ያውቁታል፡፡ ነገር ግን በንፅህና ስብእና ይቃኛል፡፡ “የመታጠብ ንፅህና የልብ ንፅህና” እንደሚባለው ማለት ነው፡፡ ደማቅ ከለሮች ደስ ይላሉ፡፡
ልጆች ይወዳሉ፡፡ ታዲያ ለተማሪዎች ዩኒፎርም ለምን ደማቅ ቀለማት አይመረጡም ልትይ ትችያለሽ፡፡ ነገር ግን የትምህርት ቤት ዩኒፎርም ምንን እንደሚወክል ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ዲሲፕሊን ወይም በስርዓት የመማር አላማን የሚያሳይ መሆን አለበት፡፡ ስለዚህም ነው የትምህርት ቤት የደንብ ልብሶች በአብዛኛው በግራጫ ወይም በደብዛዛ ሰማያዊ ጨርቆች ተሰርተው የሚቀርቡት፡፡ አላማቸውን ያሳኩ ቀለሞች ናቸው፡፡ ደግሞም ያምራሉ፣ ከጥጥ የተሰሩ ቢሆኑ ግን  ደስ ይለኛል፡፡

ዲዛይን እና ሳይኮሎጂ  
ማንም ሰው ቢችል በተወሰነ ደረጃ ታሪክን፣ ፍልስፍናንና ሳይኮሎጂን ቢያውቅ ጥሩ ነው እላለሁ፡፡ ሳይኮሎጂ የሰውን ባህርይ የሚያጠና ስለሆነ፣ የማይገባበት ነገር የለም፣ እሱን አወቅሽ ማለት፣ ህይወትን አንዴት እንደምትመሪ ቤተሰብ፣ ልጆች እንደምታሳድጊና በስራ ቦታ ባልደረቦችንና ደንበኞችን እንዴት እንደምታስተናግጂ አወቅሽ ማለት ነው፡፡ ከተፈጥሮዬም ጋር የሳይኮሎጂ ትምህርቴ ተጨምሮበት የደንበኞቼን አይን፣ የአካል እንቅስቃሴያቸውን አይቼ ስሜታቸውን ለመረዳት፣ እንዴት ልረዳቸው እንደምችል ለማሰብና መላ ለመፍጠር ትልቅ እድል ሰጥቶኛል፡፡
የኢትዮጵያውያን የልብስ ቀለም ምርጫ ከብዙ የአፍሪካ አገራት የደማቅ ቀለም ምርጫ የተለያየው ለምን ይሆን? ባህላዊና ዘመናዊ ልብሶች የተለያየ የቀለም ዝንባሌ እንዳላቸው ፍቅርተ ትናገራለች፡፡
ባህላዊ ልብሶቻችን በቀለማት የተሞሉና የደመቁ ናቸው፡፡ ዘመናዊ ልብሶች ቀለም በአመዛኙ ነው ደብዘዝ ይላል፡፡ ያ ደግሞ ከውጪው ዓለም ተፅዕኖ ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ የዘመናዊ ልብሶች ብዙ ጊዜ ከሁለት ወይም ከሶስት ቀለሞች በላይ አይሄዱም፡፡ ጥቁር፣ ነጭ እና ዝም ያለ ቀለም ነው ይበዛባቸዋል፡፡ የባህል ልብሳችን፡፡ ደግሞ ተመልከቺ፡፡ ጥለት ውስጥ ስንት ቀለም እንዳለ አስቢ፡፡
በየዓመቱ ለማቀርባቸው አዳዲስ የአልባሳት ፈጠራዎች ለመዘጋጀት ወደ ሀረር ሄጄ ነበር፡፡ የሀረሪን፣ የሶማሌን እና የአፋርን የአለባበስ ዘይቤ ያካተተ ፈጠራ  ለመስራት ነው የፈለግኩት፡፡ ሃረር ስትደርሺ ቀለሞች ይቀበሉሻል፡፡ ግንቡ፣ ቀይ ፒንክ ነው፡፡
ጀጎል ስትገቢ ቀለሞቹ ሙቀት ይሰጡሻል፡፡ ዲዛይን እራስን የመግለጫ መንገድ ነው፡፡ አለባበስ ማንነትን አጉልቶ መናገር ይቻላል፡፡
የሀና ጉዳይ
የሚያስከፋ ነገር ነው፡፡ የማህበረሰብ ጤንነት ማጣትን ያሳያል፡፡ ኮሌክቲቭ ኮንፈርሚቲ የሚባል ነገር አለ፡፡ አንድ ላይ ስትሆኚ የምታመጪው ባህርይ ልክ ነው ብሎ ማሰቡ ራሱ በስራዬ አውቃለሁ፡፡ በዚህ ጉዳይ ያልተነካ በጣም ጥቂት ነው፡፡
 ወንዶች ይደፈራሉ፡፡ የስነልቦና ጤንነት እንደሌለ ያሳያል፡፡ ስለማይወራ ዝም የተባሉ ብዙ ተመሳሳይ ኬዞች አሉ፡፡ ልጆቻችንን ስንቶቻችን እናስተምራለን? ስንቶቻችን መረጃ እንሰጣለን? ጥቃት ምን እንደሆነ ምን ምን ነገሮች ሲያጋጥማቸው ለቤተሰብ ማሳወቅ እንደሚገባቸው እናደርጋቸዋለን? ጥፋት ፈፃሚዎቹ እኮ የሆኑ ሰዎች ልጆች ናቸው፡፡ እንዴት ነው ያሳደግናቸው? ምን ያህል ጥበቃ ያደርጋል? መንገድ ላይ ትንኮሳ ሲያጋጥም እንዴት ይታለፋል? የማህበረሰብ የጤንነት ደረጃን ያሳያል፡፡ ከቅጣት በፊት መከላከል ይቀድማል ሁሉም በየቤቱ ልጆቹን ጥሩ እሴት ይዘው እንዲያድጉ ማድረግ አለበት፡፡   እኔ ምን ማድረግ እችላለሁ የሚለውን ራሳችንን መጠየቅ ያለብን ጊዜ ላይ ነን፡፡  ሁላችንም ራሳችንን ሀና ቦታ ላይ እናስቀምጥ፡፡
ያለፈችባቸውን ስቃዮች እናስባቸው፡፡ ለቤተሰቦቿ መፅናናትን እመኛለሁ፡፡

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ በትግራይ ክልል ሽራሮ ከተማና በአማራ ክልል አብርሃ ጅራ ከተማ አዳዲስ የምርት መቀበያ ቅርንጫፎችን መክፈቱን አስታወቀ፡፡
ሰሞኑን ተመርቆ  አገልግሎት መስጠት የጀመረው በትግራይ ክልል ሽራሮ የሚገኘው ቅርንጫፍ በፀለምቲ፣ አስገደ ፅምብላ፣ ታህታይ አድያቦ፣ ላዕላይ አድያቦ፣ መደባይ ዛና፣ ነአደር አዴት፣ መረብለኧ፣ ወኔለኧ፣ ቆላ ተምቤን፣ ጣንቋ አበርገሌ፣ ሰሀርቲ ሳምረ እና ወልቃይት አካባቢ የሚመረቱ ምርቶችን ለግብይት የሚያመቻች ነው ተብሏል፡፡ በተጨማሪም በአካባቢው ያሉ ሌሎች ወረዳዎችም ተጠቃሚ ይሆናሉ ተብሏል፡፡ በአማራ ክልል የሚከፈተው የአብርሃ ጅራ ቅርንጫፍ በምዕራባዊ አርማጭሆ በሚገኙት በአብርሃ ጅራ፣ አብደራፊ ኮርሁመር፣ ጐብላ፣ ግራር ውሃ፣ መሃሪሽ እና ዘመነ መሪኬ እንዲሁም በፀገዲ በሚገኙ አካባቢዎች የሚመረቱ ምርቶች የሚቀርቡበት ይሆናል ተብሏል፡፡
በምርት ገበያው አሠራር እነዚሁ ቅርንጫፎች እንደሌሎቹ ቅርንጫፎች ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የምርት ናሙና በመውሰድ፣ ክብደትና ጥራት የሚለኩበት እንዲሁም አስተማማኝ የመጋዘን አገልግሎት የሚሰጡ ይሆናሉ፤ ለአርሶ አደሮቹም ዘመናዊና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ለአገሪቱ ምርት ግብይት መሻሻል የጐላ አስተዋጽኦ ያበረክታሉ ተብሏል፡፡ ምርት ገበያው በአሁን ወቅት በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ የምርት ማስረከቢያ ማዕከላቱን ከ17 ወደ 19 ከፍ ማድረጉም ተጠቁሟል፡፡

Saturday, 29 November 2014 11:29

የምሬት ድምጾች

ሀና ላላንጎ የአስራ ስድስት አመት ታዳጊ ናት ፡፡ አየር ጤና አካባቢ  ከትምህርት ቤት ወደ ቤቷ ለመሄድ በተሳፈረችበት ሚኒባስ ታክሲ ተገዳ ከተወሰደች በኋላ በደረሰባት የቡድን የመደፈር ጥቃት ምክንያት ህይወቷ አልፏል፣ ጉዳዩ በህግ ተይዟል፡፡ የኢትዮጵያ ሴቶች ማህበራት ቅንጅት  ሰላም ለሴቶች ከጓዳ እስከ አደባባይ  በሚል መርህ ዘንድሮ ስለሚከበረው ዘመቻ በፆታዊ ጥቃት ዝግጅት እና በሃና ጉዳይ ላይ በራስ ሆቴል ፕሮግራም አዘጋጅቶ ነበር፡፡ በወቅቱ መድረኩ ላይ ስለሀና የተሰጡ አስተያየቶችን መርጠን ለጋዜጣው በሚመች መልኩ ኤልሳቤት ዕቁባይ አቅርባዋለች፡፡

“አውሬ ያለ ጫካ አይኖርም”
ዶክተር ምህረት ደበበ

ለሀና ቤተሰቦች መፅናናት እንዲሆን የሀና ሞት የብዙዎች ትንሳኤ እንዲሆን እመኛለሁ፡፡ ሁላችንም ራሳችንን አንድ ጥያቄ እንድንጠይቅ እፈልጋለሁ፡፡ ሀናን ማን ገደላት ሀና በአንድ ቀን አልሞተችም፡፡ ሀናን የገደሏት ሰዎች አንድ ቀን አልተጠቀሙም፡፡ አንደኛ፤ ሀናን የገደላት የሀናን ገዳይ የፈጠረ ህብረተሰብ ነው፡፡ ድርጊቱን የፈፀሙ ሰዎች ሲወለዱ እና በጨቅላ እድሜያቸው እንዲህ አይነት ሰዎች እንዳልነበሩ እናውቃለን፡፡ የእኛ የእጅ ስራ ናቸው፡፡ ሁለተኛ፤ ሀና የዛን ቀን አባቷ እንደተናገሩት በብዙ ሰዎች አጠገብ እና የማዳን ሀይል ወይም ችሎታ በነበረበት ሁኔታ ውስጥ ነው ያለፈችው፡፡ ሀና ላይ ይህን ድርጊት የፈፀሙ ሰዎችን ብዙዎች የኮነኑ ሲሆን፤ እንዲያውም ፌስቡክ ላይ አውሬዎች ተብለዋል፣ ግን አውሬ ያለጫካ አይኖርም፡፡ እያንዳንዳችን ጫካ ሆነናል፡፡ ይዘዋት የገቡበት ግቢ ሰፊ ነው፡፡ የነዛ ሰዎች ጎረቤቶች ገድለዋታል፡፡ ቸልተኝነት ሊሆን ይችላል የአካል ሊሆን ይችላል ግን ድፍረት ነው፡፡   ድፍረት ማለት የአንድን ሰው ክብር ማዋረድ ማለት ነው፡፡ የማዳን ሀይል ያላቸው ፍትህ ማስፈፀም የሚገባቸውም ገድለዋታል፡፡ ያንን መቀበል አለብን፡፡  በጣም የሚገርመው ነገር ደግሞ ሀናን ሆስፒታል ያሉ የጤና ባለሙያዎች ናቸው የገደሏት ፡፡ ደፍረዋታል፣ እኔ ሀኪም ስለሆንኩኝ አፍሬያለሁ፡፡ እኔ ግማሹን ጊዜዬን አሜሪካን ነው የምሰራው፡፡ እዛ ቢሆን ሊደረግ የሚችለውን ነገር ስለማውቅ ሀና ምንም ስለሆነች ብቻ ሳይሆን ሰው ስለሆነች፣ የማንም ልጅ ስለሆነች ሳይሆን ሰው ስለሆነች፡፡ ሀና የተገደለችው በደፈሯት ሰዎች ቤት ውስጥ አይደለም፡፡
በሆስፒታል ውስጥ ነው፣ ሰው እንዴት ሆስፒታል ውስጥ ይሞታል? መጨረሻ ላይ የምለው ሀናን የገደልኳት እኔ ነኝ፤ ነው፡፡
እዚህ ላይ ሶስት ትላልቅ ነገሮች አሉ አንዱ ፆታ ነው፡፡ ሁለተኛው ወሲብ ነው፡፡ ሶስተኛው ጥቃት ወይም ሀይል ነው፡፡ እያንዳንዳችን ስለወሲብ የምንናገረው እና ስለወሲብ የምናስበው ነገር እስኪስተካከል ድረስ እንዲህ አይነት ነገር አይቆምም፡፡  ህመሙ ያለው ሴቶች ላይ በተጫነው ነገር ብቻ አይደለም፡፡ ወንድነት መስተካከል እስካልቻለ ድረስ  እንደዚህ አይነት ነገር አይቆምም፡፡ ይህ አይነቱ ትልቅ ድፍረት ከመፈፀሙ በፊት መንገድ ላይ ብዙ ትንንሽ ድፍረቶች አሉ፡፡ ትልቁ ድፍረት በቋንቋችን ውስጥ ታጭቋል፡፡ ቋንቋችን ምን ያህል ቫዮለንት እንደሆነ ፣ ምን ያህል የሰዎችን ክብር የሚያዋርድ እንደሆነ ከቤት እስከ መንገድ ማየት ይቻላል፡፡
ወንዶች ለሚያደርጉት ነገር ብዙ ማብራሪያ ይሰጣል፡፡ዛሬ እስቲ ገልብጠን እንየው፡፡  ግን ለምን አብዛኛው ወንድ እንደዛ አልሆነም፡፡ ወንድነት ምንድን ነው? ጀግንነት ምንድን ነው? ደካማን ማገዝ ፣መርዳት  እኔ አንድ የምለው ነገር አለ ሰዎች ካንገት በላይ ካላደጉ ካንገት በታች ነው የሚኖሩት፣ ካንገት በታች ደግሞ ምንም ማሰብ የሚችል ነገር የለንም፡፡ ስሜትን መግዛት የሚችል ነገር የለንም፡፡ እዚህ ብንቆጠር ሴቶች ይበዛሉ፣ ሴቶች እዚህ የመጡት ስላጠፉ ነው፡፡ መቆጣት እና መሰብሰብ የነበረበት ማን ነው ፡፡ ልክ እንደ ሀኪም ባለሙያነቴ አሁንም በወንድነቴ አፍራለሁ፣ አብዛኛው ፖሊስ ማን ነው?  ወንድ ነው ሴት ነው፣ አብዛኛው የጤና ባለሙያ ማን ነው? የመገናኛ ብዙሀን ባለሙያ ማን ነው? ወንድ፡፡ እንደዚህ አይደለም ካልን ለምንድን ነው አክት የማናደርገው፡፡
 ይህ የሴቶች ጉዳይ ተብሎ ታይቶ ይሆናል፡፡ አይደለም፡፡ የወንዶች ጉዳይ ነው፡፡ እኔ ልክ ድርጊቱን ከፈፀሙት ሰዎች እኩል ሀላፊነት መሸከም አለብኝ፡፡ የማህበረሰብ ለውጥ እስኪካሄድ ድረስ ብዙ መስራት ይጠበቅብናል፡


“ከዚህ በላይ ምን ሽብር አለ”
ወ/ሮ ሰሎሜ ታደሰ

በጣም አዝኛለሁ፣ ሆድ ብሶኛል፣ ደክሞኛል፡፡ የልብ ድካም ነገር ካለ፣ ድሮ በሽታ ነበር የሚመስለኝ፤ አሁን ግን የሚረዳ ማጣት ማለት ነው፡፡ የዛሬ ሁለት አመት ልክ እንደዚህ በኢትዮጲያ አየር መንገድ በበረራ አስተናጋጅነት ትሰራ በነበረችው በአበራሽ ላይ በተፈፀመው ድርጊት ደንግጠን አሁን በአይኔ መጣ የሚል እንቅስቃሴ ጀምረን ልክ የዛሬውን አይነት ሂደት አልፈን ነበር፡፡ አሁን ደግሞ እዛው ተመለስን፡፡ ማንንም ከመውቀሳችን በፊት እያንዳንዳችን ራሳችንን እንጠይቅ እንደተባለው ራሴን ጠየቅኩ፡፡ እኛ እንግዲህ በተነፃፃሪ ተጠቃሚ ከሚባው የህብረተሰብ ክፍል ነን፡፡ እውቀት አለን፣ ብዙ ነገሮችን የማየት እድል አለን፣ከሌላ የተሻለ ገንዘብ አለን፡፡ ግን እየሰራን ያለነው ስራ ውጤት የማያመጣው በበቂ እየሰራን አይደለም ማለት ነው ወይስ አልቻልንበትም ወይስ ተንቀን ነው ብዬ አሰብኩ፡፡  ወጣቶቹን ሳይ፣ ዶክተር ምህረትን፣ ሀይሌ ገብረስላሴን ሳይ ደግሞ ደስ አለኝ፡፡  ሌላው ያሰብኩት ደግሞ እዚህ አገር ሰው ሁሉ የሚፈራው ፀረሽብር ህጉን ነው፡፡ ግን ከዚህ በላይ ምን ሽብር አለ? ለኔ ሽብር ማለት በሰላም ወጥቶ አለመግባት ማለት ነው፡፡ ህጉ ይቀየርልን ሳይሆን ወደ ፀረ ሽብር ሕጉ ይቀየርልን፡፡ እነሱ ስለሚፈሩ ነው ጸረ ሽብርተኛ ህግ ውስጥ የከተቱት፡፡ ትንሽ ቀን መንግስት ቀጥቀጥ ቢያደርግ ብዙ ነገር እንደሚጠፋ መገመት ይቻላል፡፡
ወ/ሮ ሰሎሜ ታደሰ

“ይቺን አገር ያጠፋት ምንአገባኝ ነው”
አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ

የሃና ቤተሰቦችን እግዚአብሄር ያፅናቸው፡፡ይህ ነገር ዜና ሆኖ የወጣው ለምን እንደሆነ ሳንግባባ የቀረን አይመስለኝም፡፡ እንዲህ አይነቱ ድርጊት ብዙ የለም ብላችሁ ታስባላችሁ እጅግ ብዙ አለ፡፡ ሀና ስለሞተች ነገ በማህበረሰቡ ውስጥ ስለማይጠቋቆሙባት እና ሌሎች ከዚህ ጋር የተያያዙ ነገሮች ስለማይፈፀምባት እንጂ የሀና አይነት ሺዎች ናቸው - ሁሉንም ነገር በውስጣቸው ይዘው የተቀመጡ፡፡ ይቺን አገር ያጠፋት ምንአገባኝ ነው፡፡ጥቃት ሲፈፀም ብናይ ይበላት እንዲህ ሆኖ ነው እንዲህ አድርጋው ነው ይባላል፡፡ መንገድ ላይ የሆነ ነገር አጋጥሞኝ ጣልቃ ስገባ ምን አገባው ምን ቤት ነው የሚሉ አሉ፡፡ እነሱ ምን አገባቸው? እንዴት አያገባኝም?! የምኖርባት አገር እኮ ነች፡፡ ይቺን አገር ነው ጥሩ ሆና ማየት የምፈልገው ፡፡ ሌላው በጣም ያስደነገጠኝ በአምስት ሰዎች የተፈፀመ መሆኑ ነው፡፡ አምስት ሰዎች እንዴት አንድ አይነት አስተሳሰብ ውስጥ ገብተው ይህን ድርጊት ሊፈፀሙ ቻሉ፡፡ አንዱ እንኳን ጥያቄ አይፈጠርበትም? በዚች አገር ብዙ የሚሰቀጥጡ ታሪኮች አሉ፡፡ ነገር ግን ድርጊቶቹ የኛ ድምር ውጤት ናቸው፡፡ ይህን ከሰማሁ ጀምሮ ልጆቻችንን ለምን አመጣናቸው የሚል ስጋት ውስጥ ገብቼያለሁ፡፡ መፍትሄውን ከፖሊስ፣ ከፍትህ አካል ብቻ አንጠብቅ፡፡ እኔ እንዲያውም እድሜ ልክ ከማሰር በአደባባይ አርባ ጅራፍ መግረፍ ውጤት ሳያመጣ አይቀርም፡፡


ከአበባው መላኩ ጋር ስለጐንደርና ስለ ጉዋሳ የተጨዋወትነው

“ከግጥም ከመሰንቆ ልጆች ጋር እንዴት ተዋወቃችሁ?” አልኩት፡፡
“ግጥም በመሠንቆዎች ስለ ፓኤቲክ ጃዝ የሚያውቁት ነገር የአለ መሰለኝ፡፡ ወርሃዊውን ዝግጅት የመካፈል ልማድ እንዳላቸው ነግረውናል፡፡ በመጀመሪያ የሰማሁት የግጥም በመሰንቆ ቡድኖች ለግጥም በጃዝ ስጦታ ለመስጠት ይፈልጋሉ - ነው፡፡ በ3ኛ ዓመት ዝግጅት ሰዓት ሳይሆን መድረክ መስጠት ይቻላል…ከጐንደር ድረስ መጥተው፣ የጐንደርን ስም ጠቅሰው እንዴት ብለው ይመለሳሉ? ሌላም የሽልማት ፕሮግራም አለንና ያንን መጠቀም ይችላሉ አልን፡፡ መጡ ተገኙ ነገር ግን በራሳቸው ምክንያት ስጦታውን ሊያከናውኑ አልቻሉም” አለኝ፡፡ እኔ የጐንደሮቹን ግጥም በመሰንቆ ቡድኖች ጠይቄያቸው ቴክኒካል ችግር ለሁኔታው አለመመቻቸት ምክንያት ሆኗል ነው ያሉኝ፡፡ ዞሮ ዞሮ ስጦታው በበረከት በኩል እንዲደርሳቸው አድርገናል ነው ያሉት፡፡ መንፈስ ለመንፈስ ግን ተግባብተዋል ብዬ ዘለልኩት፡፡
“ዋናው ነገር ተገናኝተናል፡፡ መስከረም ላይ እኔን ጋበዙኝ፡፡ በረከትን ጠየኩት “ለግጥም የተሰጡ ልጆች ናቸው” አለኝ፡፡ “የግጥም አገልጋዮች ናቸው” አለኝ፤ አለ አበባው፡፡
የግጥም ዲያቆናት፣ ምዕመናን - ማለቱ ነው፡፡
“ወጪያችንን ችለን ለምን እንደግሩፕ አንሄድም?” ተባባልንና ሁላችንም የፓኤቲክ ጃዝ አባላት ሄድን፡፡ አንዳንዶቹ ጐንደርን አይተው ስለማያውቁ ደስ አላቸው፡፡ ሌሎቻችን ደግሞ የምናውቀው እኔ በ98 አውቀዋለሁ ግሩሜም ያቀዋል - ምሥራቅና ምህረት ናቸው የማያውቁት፡፡ አቀባበላቸው ግሩም ነበር! በጣም ደስ ብሏቸው ነበር…ግጥም ንባቡን በዋናነት እኔ ደጋገምኩ እንጂ ሁላችንም አቅርበናል! አዳራሹ ግጥም ብሎ ነበር! ብዙ ህዝብ ነበር፡፡ የቆመው ከተቀመጠው ይበልጥ ነበር! እኔ እንደዚህ አልጠበኩም፡፡ በአውሮፕላን ችግር ፕሮግራም ተሰርዞ፣ ባዲስ መልክ አዘጋጅተውት ያለቀኑ ተዋውቆ በፌስቡክ፣ በአንዳንድ ቦታ ብቻ አስተዋውቀውት ነው፡፡ ብዙ ሰው መጣ! እነሱም ተደምመው ነበር፡፡ በጣም መልካሙ ነገር ጥሩ የሚሰሙ ሰዎች ነበሩ፡፡ ያየነውንም ትዝብት ተናገርን ጐንደርን ያህል አገር ይዘው፣ በውስጡ ያለውን ታሪክ፣ ላለፉት 250 ዓመት ዘመን ላይ የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ትምህርት፣ የአስተዳደር መዲና የሆነች አገር ይዘው ያን ያን እሚሸት ነገር የሌለበት ነገር ትርፉ  ድካም ነው፡፡ ዘጥ ዘጥ ነው፡፡ ዞር ዞር በሉ - ወላጆቻችሁን ጠይቁ፡፡ ወደአቅራቢያችሁ ገዳማትና አብያተ ክርስቲያናት ጐራ በሉ - መዛግብቱን እዩ፡፡ መዛግብቱ ምን ይላሉ፡፡ በዚያ መጠን ሥሩ፡፡ ታላላቆቻችሁን ጋብዙ - ከዚያ ምን ተገኘ የሚለውን እዩ!...መከርን፣ ሸጋ ነው!
“የባህል ቤቱን እንዴት አገኛችሁት?”
“…ዘመናዊውን ዘፈን እንኳ ወዝ ይሰጡታል፡፡ ሐማሌሌን እንኳ አሳምረው ነው የሚዘፍኑት፡፡ ሕብረ - ብሔራዊ ስሜት አላቸው፡፡ የሁሉ እናት የመሆን ስሜት ነው ያላቸው!... በጣም ቆንጆ ነው! ሴቶች ድራም ይዘው ማየት በጣም ትፍስህት ሰጥቶኛል፡፡ የመጨረሻ ሙድ አለ፡፡ የግጥሞቹ ይዘት ላይ እኔ ትንሽ ያዝ አድርጐኛል! ስሞች እያነሳች ታወድሳለች! ቀረርቶ ሽለላዋ መልካም ነው - ሌላው ግን የሥነ - ቃሉ የግጥሙ ባለቤቶች ሆነው ምንም አዳዲስ ይዘት የላቸውም ወይ? ብያለሁ!” አለኝ፡፡
“የስቴጅ ግጥም አንባቢዎችንስ ብስለት ነገር እንዴት አየኸው?”
“ከ12 ዓመት በፊት ፑሽኪን አዳራሽ ይቀርቡ የነበሩ ግጥሞች ነበሩ! በወጣቶች፣ በሁሉም አቅጣጫ ወጣት ናቸው! ነጠላ ሀሳብ ላይ የማተኮር ችግር አያለሁ! ያንን ጊዜ ያስታውሰኛል፡፡ የተወሰኑ ተስፋ የሚጣልባቸው ነበሩ - በተለይ የዕይታ ነገርን ያበሰሉ ገጥመውኛል…የመለመልነውም ልጅ አለ - ከውስጣቸው፡፡ ልሣን ይባላል፡፡ Talent Hunt ነው፡፡
ከየቦታው ለፓኤቲክ ጃስ ከምነመለምላቸው ለምሣሌ ከወሎ አካባቢ ሼህ ቡሽራ የሚባሉ ናቸው መንዙማ አዋቂ ጋብዘን ሆቴላቸውን አበላቸውን ችለን ነበር - ሌላ መንግሥቱ ዘገየ” ቀብድ የበላች አገር” የሚል መጽሐፍ የፃፈ ነበር - መጽሐፉን አይተን በአድራሻ አገኘነው! እሱንም ቀለቡን ችለን ጋብዘናል! ሀሳቦች አሉን፡፡ ለምሳሌ ደብረዘይት አካባቢ ቶራ ቡላ የሚባል የሥ/ጽሑፍ ማህበር ነበር፡፡ እነሱም እንዲያቀርቡ አስበን ነበር፡፡ እነ ምንተስኖት ማሞን የደብረዘይቶቹን ነግረን ነበር፡፡ ወደ አዋሳ አካባቢም “60 ሻማ” እሚባል ማህበር ነበር፡፡ ይሄ ሃሳብ እያለ ነው እንግዲህ ጐንደሮች ሲጠሩን የሄድነው! እንደነሱ በአውሮፕላን ባይሆን በመኪና ነው!”
በበኩሌ አልኩት፤ “የናንተ አዳራሽ - የእኔ ኦፕን - ኤር ነው! ልዩነቱ ያ ነበር፡፡”
የጉዋሣ ነገር
በረዶ አገር ሄጄ አቃለሁ - አውሮፓ፡፡ እንደ ጉዋሣ ያለ ቀዝቃዛ ቦታ በህይወቴ አጋጥሞኝ አያውቅም፡፡ በነገራችን ላይ ዘፈኑ ግጥም ላይ
“አገሯ ዋሳ መገና፤ አገሯ ዋሳ መገና
ምነው አልሰማ አለች፣ ብጣራ ብጣራ”
“ዋሣ” ይመስለን የነበረው “ጉዋሣ” ነው፡፡ “መገና”ም የመሰለን “መገራ” መሆኑን ልብ እንበል፡፡
ከአዲሳባ ለተነሳ ሰው ወደ ደብረ ብርሃን ይኬድና፤ ጉዶ በረትን አልፎ ወደ ደብረ ሲና አምርቶ (ደብረሲና እንግዲህ ዳኛቸው ወርቁ በአደፍርሱ “እግዜር አገሮች ሰርቶ ሰርቶ የተረፈውን ኮተት ያከተባት ከተማ” ያላት ናት) ጣርማ በር ጋ ሲደረስ ወደ ግራ እጥፍ ነው፡፡ 180 ኪ.ሜ ላይ ማለት ነው፡፡ መዘዞና ባሽ ይቀጥላል፡፡ ወደ ግራ ቢሉ ሞላሌ አለ፡፡ ቀጥታውን ሲኬድና ሲቀጠል ግን ይጋም (Yigam) ይገኛል፡፡ ይጋምን ሲያልፉ ጉዋሣ አጥቢያ ይደርሷል፡፡ በዚያ ወደቀኝ ወደ ካድሉ ወደ አጣዬ ያስኬዳል፡፡ ግራ ግራውን ማህል ሜዳ እንግዲህ ዙሪያ ገባውን አለ፡፡ በማህል ሜዳ ተሻግሮ ወደ ግሼ ይዘለቃል፡፡ እኛ ግን ወደ ማህል ሜዳ ስንሄድ ሰፌድ - ሜዳን አልፈን ነው፡፡
ይሄ ሙሉቀን የዘፈነለት ጉዋሣ ለአዲሳባ ሰሜን ነው፡፡ የቅዝቃዜውን ነገር አለማንሳት ነው፡፡ ከባህር ወለል በላይ ከ3200 -3700 ሜትር ከፍታ ላይ ነው፡፡ የተሰባበረ ተራራ ይታያል፡፡
ፀጋዬ ገ/መድህን “በአንኮበር” ግጥሙ “የፈፋ አነባበሮ” ያለው ነው፡፡
ወደ ምዕራብ የሚጓዙና ሰንጥቀውት የሚያልፉ ስምጥ ሸለቆዎችና የባህር ሸለቆዎች አሉ፡፡ በአባይና በአዋሽ ማህል ያለ ውሃ ማገቻ ነው፤ ቢባል ድፍረት አይሆንም፡፡ የጉዋሣ ምሥራቃዊ ወገን ተረተሩን ቁልቁል ወደሸለቆው ልኮ ታላቁን ስምጥ ገደል ድንገት ሲተረትር ከመነሻው ይርቃል፡፡ ከፍታው መርገብ ይጀምራል፡፡ በ50 ኪ.ሜ ርቀት ውስጥ በ2600ሜ ዝቅታ ደረጃ ባንዴ ውርድ የሚል ታምረኛ ሥፍራ ነው፡፡ ከዚያ ወደ አዋሽ ግርጌ ወርዶ የታላቁን ስምጥ ሸለቆ ወለል ይቀላቀላል፡፡ የጉዋሣ ምዕራብ ደግሞ በድልዳላዊ አካሄድ ወደማህል ሜዳ ይገባል (3000 ሜትር ግድም) መልክዐ - ምድሩና ሠፈሩ እንግዲህ ይሄ ነው፡፡
ከጉዋሣ የግቻ ሣር (Afro alpine) [በአፍሪካ የራሳችን የሣር - ዝርያ ነው] እና በተራራው ትዕይንት መካከል የጉዋሣ ማህበረሰብ ሎጅ (ማረፊያ - መናፈሻ) አለ፡፡ ለዚያ ቦታ እንደወፍ ጐጆ ማለት ነው፡፡ ክፍሎቹ፤ በትልቅ ቅጽ ተገነቡ እንጂ በልማዳዊ መንገድ የተሠሩ የወፍ ጐጆዎች ማለት ናቸው፡፡ የጉዋሣ ማህበረሰብ ነው የሚያስተዳድራቸው፡፡ አራት ባላመንታ - አልጋ ክፍሎች (“ጭላዳ”፣ “ቅልጥም - ሰባሪ”፣ ቀይ ቀበሮ” የሚባሉ የከፋ ቀን በአገሩ በሚገኙት ብርቅዬ እንስሳት የተሰየሙ) አይቻለሁ፡፡ ከኒህ በተለየ፣ የእሳት መሞቂያን ያካተተ እልፍኝ፤ ምግብ - ቤትና ማድቤት ያለው ትልቅ የእንግዳ  ማረፊያ ክፍል አለ፡፡ የትምህርትና የመረጃ ማዕከል ባንድ ወገን ያለ ሲሆን፤ የመታጠቢያና መፀዳጃ ያለው ዘርፍ - ክፍልም አለ፡፡ ለካምፕ አመቺ ቦታ አለው፡፡ የገዛ ድንኳን ይዞ አሊያም ከማህበረሰቡ ቱሪዝም ማህበር ተከራይቶ ደንኩኖ መሥፈር ይቻላል፡፡ ሰው የገዛ ምግቡን ሸክፎ መምጣት እንዳለበት መቼም ግልጽ ነው፡፡
የጉዋሣ ማህበረሰብ አካባቢ ጥበቃ አጥቢያ በመኪና መንገድ የሚደረስበት ነው፡፡ ከአዲሳባ ማህል ሜዳ በሚሄደው ህዝብ ማመላለሻ ሽር ማለት ይቻላል፡፡
ጉዟችን መጀመሪያ ከደብረ - ብርሃን 15 ኪ.ሜ የምትገኘው “አማፂዎቹ” የተባለ ቦታ ቁርስ በመብላት እንደሚጀምር የጉዞ - መሪያችን አብስሮናል፡፡ “አማፂዎቹ”ን ለማወቅ መቼም ከስማቸው መረዳት ነው ዋናው” ነው ያለን ጉዞ መሪው፡፡ በኋላ የደረስነው አንድ ጉብታጋ ነው፡፡ ከዚያ ሆነው ቁልቁል ሲያዩ የሚያምር መልክዓ ምድራዊ ትርዒት አለ፡፡ የኢትዮጵያ አብያተ - ክርስቲያናትና ቤተ - መንግሥቶች ለምን ከፍታ ላይ እንደሚሠሩ ተወያየን፡፡ ከፍታ አንድም ለማየት አንድም ለመታየት ነው - ተባባልን፡፡
ከዚያ እንግዲህ ጣርማ - በር ላይ ታጥፈን ማረፊያ - መናፈሻው (Lodge) ጋ ደረስን፡፡ ምሣ በላን፡፡
ከዚህ ወዲያ ነው ጉዱ! የእግር ጉዞ ተጀመረ፡፡ የእግር ጉዞ ታሪክ አስረጂ አጠገባችን አለ፡፡ እኔ ብዙም ሳልራመድ ዳገቱ ያደክመኝ ገባ፡፡ አንዴ አረፍኩ፡፡ ትንሽ ሄጄ ልቤ ያለልክ ትመታ ጀመር፡፡ “በቅሎ ቢመጣልኝ ይሻላል” አልኩ፡፡ መቼም ከተሜዎች ናቸውና መድከማቸው አይቀርም ብለው ነው መሰል፣ አገሬው በቅሎ እየነዳ ይከተለናል፡፡
አንዷን በቅሎ አመጡልኝ፡፡ በበቅሎ ተጉዤ አላውቅም፡፡ እንዴት ልውጣ? ወደ አንድ ከፍ ያለ አፋፍ በቅሎዋን አስጠጉልኝና ተደጋግፌ ወጣሁ፡፡ በቅሎዋን የሚስቡልኝ አንድ አጭር ቆፍጣና አዛውንት ናቸው፡፡ ነገረ- ዕንቆቅልሹ ገረመኝ፡፡ እኒህ የ81 ዓመት ሽማግሌ መንገዱን እንደወጣት ይሸነሽኑታል፡፡ እኔ ደግሞ ከሳቸው በጣም በዕድሜ የማንሰው ዘመኔኛ በቅሎ ላይ ነኝ! የበቅሎ አነዳድ መመሪያ ተሰጠኝ:-
ዳገት ሲሆን ወደ ኮርቻው ቀዳማይ ድፍት!
ቁልቁለት ሲሆን ወደኋላ ልጥጥ ማለት!
“ቁልቁል መሳብ፣ ሽቅብ መሳብ” እንዳለው ደራሲው፤ ወጣነው፡፡ ወረድነው፡፡ አሥራ ሰባቱን ኪሎ ሜትር ተጓዝነው!
መኪናችን ዕቃችንን ሸክፎ ቀድሞን ደርሷል፡፡ ቀድመው ለጥናት የመጡ ፈረንጆች እዚሁ ግድም መሥፈራቸውን ምልክት አየን፡፡
ሰው ሁሉ ደረስን ብሎ እፎይ ማለት ሲቃጣው፤ “ፍራሽና አንዳንድ የመኝታ ዕቃ ይዛችሁ ሽቅብ ውጡ፤ መድረሻችን ገና ነው” ተባለ፡፡ ያዳሜ ወሽመጥ ቁርጥ አለ! እዚሁ አይቀር ነገር ሁሉም አንዳንድ ፍራሽና የመኝታ ዕቃ እየያዘ ዳገቱን ተያያዘው፡፡ እንዳይደረስ የለም ተደረሰ፡፡ እኔ ሙላዬ ተላቋል፡፡ ብሽሽቴ ቀልቷል!
ካምፕፋየር ሊደረግ እሳት ተያያዘ፡፡ ፍልጥ ተደመረ፡፡ ነደደ፡፡ ሙቀት መጣ፡፡
ጉሙን ግን ማን በግሮት፡፡ አርድ አንቀጥቅጥ ነው፡፡ አገሬው አሁንም ዕቃ ያመላልሳል፡፡ ብርዱ -10 (ኔጋቲቭ 10) ዲግሪ ሴንቲግሬድ ነው፡፡
ስለ ጉዋሣ ለማወቅ አፈ - ታሪካዊ ትውፊቱን አንብቤያለሁ፡፡
እንደቀበሊኛው አፈ ታሪክ ከሆነ ጉዋሣ የተፈጠረው አንድ መነኩሴ ከተራገሙ በኋላ ነው፤ ብሎ ይጀምራል፡፡ በዚያን ጊዜ ይህ ቦታ እጅግ የበለፀገ የግብርና ቦታ ነበር ይባላል፡፡ በጣም ምርጥ የተባለ ጤፍ ይመረትበት ነበር፡፡ አንድ መልካምና ብልህ የሆኑ አቼ ዮሐንስ የተባሉ መነኩሴ እዚያ ቦታ ይኖሩ ነበር፡፡ ሥራቸውን በሚገባ እያከናወኑ መሬቱንም ባርከውት ነበር፡፡ ሆኖም አንዲት ሴት ከመነኩሴው ልጅ ፀንሻለሁ ብላ በማውራቷ በመነኩሴውና በአገሬው ፊት አረጋግጪ ተብላ ሸንጐ ፊት ቀረበች፡፡
“ዋሽቼ ከሆነ ድንጋይ ያድርገኝ” ስትል ማለች፡፡
ወዲያውኑ ወደ ድንጋይ ተቀየረች፡፡ መነኩሴው ግን በዚህ ብቻ አልረኩም፡፡ ሰው እሷን በማመኑም በጣም ቅር ተሰኙ፡፡ ስለዚህም ያንን ቦታ
“አንተ ቦታ ከእንግዲህ የተረገምክ ሁን!! የመጨረሻ ቀዝቃዛና ጨፍጋጋ ሁን!! የበለፀገው የግብርና ምርትህም ከእንግዲህ ግቻ ይሁን!!” ብለው ረገሙት፡፡ ይህን ሲሉ ወዲያው የአካባቢው አየር ተለወጠ፡፡ መሬቱም ዛሬ የሚታየው የጉዋሣ ቦታ ሆነ፡፡ አፍሮ አልፓይን የሣር ዘር መሆኑ ነው፡፡ ያ መርገምት መንደሩን ደሀ አደረገው፡፡ ከብዙ ዓመታት በኋላ ያገር ሽማግሌዎች ይቅርታ ብንጠይቅ ይሻላል ተባባሉ፡፡ እኒያን መነኩሴም ፍለጋ ያልሄዱበት ቦታ የለም፡፡ ሆኖም መነኩሴው ከረዥም ጊዜ በፊት አርፈው ኖሯል፡፡ ሰዎቹ ግን አፅማቸውንም ቢሆን መፈለግ አለብን ብለው ፍለጋቸውን ቀጠሉ፡፡ የመነኩሴው መንፈስ ቢታደገን እንኳ ብለው በአጥቢያቸው አፅማቸውን ሊያሣርፉ አስበው ነው፡፡ አፅማቸው ተገኘና ፍሩክታ ኪዳነ ምህረት ዳግመኛ ተቀበሩ፡፡ ለሠራኸው ጥፋት የምትከፍለው ብዙ ነው! መንፈሣዊ ፀጋ ድህነትን ለማሸነፍ አስፈላጊ ነው!
ሰዎቹ ራሳቸውን በመውቀስ የድህነታችን ዕንቆቅልሽ ታሪኩ ይሄ ነው ይላሉ፡፡     
እንግዲህ ከአበባው ጋር ወደ ጓሣ አብረን ሄደናል፡፡ “ስማ፤” አልኩት፡፡ እርግጥ ካንተ የምለየው፤ እኔ ጉራጌ አገር ዘሙቴ ማርያም ነበርኩ፤ ከዚያ ጐንደር ከዚያ ጓሣ መሄዴ ነው! የእኔ የጓሣ አመለካከት አለ ያንተስ? አልኩና ጠየኩት፡፡
“እኔ የሀረር ሰው ነኝ - ደጋ አደለም - ቆላ ነው - የሚስማማኝም ቆላ ነው!
ከመሄዳችን በፊት የተሰጡኝን ማስገንዘቢያዎች አንብቤአለሁ! አለባበስ -የእጅ ጓንት ወዘተ ያንን ማሳሰቢያ በአክብሮት ካነበቡት አንዱ እኔ ነኝ! እኔ ብርድ በኃይል እፈራለሁ - ለምን እንደሆነ አላውቅም! መድረስ አይቀርም ደረስኩ፡፡ ከከፍታ በላይ ከፍታ ላይ አስደንጋጭ ቪው ነው ያየሁት! ዓለምን በተዛማጅ ከፍታ ማየታችን እየተፈታልኝ ነው የተጓዝኩት - ደስ ብሎኛል፡፡
ቦታው አስደናቂ እንደሆነብኝ ጓሤዎችም አስደንግጠውኛል! ሰው መውደዳቸውና ትህትናቸው! ሁለተኛ እርስ በርስ ያላቸው መግባባትና መከባበር! በተፈጥሮአችን እኛ ከተሜዎቹ እራሳችንን እንለይና የበዛብን ሲመስለን በጣም አጉረምራሚዎችና ተናዳጆች፤ በተለመደው መከባበር፣ ጠባይ ውስጥ አደለም ሥራችንን የምናከናውነው! ብሶተኛ ይበዛል - ፉከራው ይበዛል! ያ ነገር እዚያ የለም! ሸክም ተሸክመው በቅንነት ይኖራሉ እነሱ! ሰዎችን ለማገልገል፣ ለመርዳት ያላቸው ጉጉት፤ መመራመር ሳያስፈልግ እነሱ ተፈጥሮን ተገዳድረውታል ብዬ እላለሁ! ሠርፀው ገብተዋል፡፡ በቅሎ ላይ መውጣቴ፤ በህይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው በቅሎ ላይ የወጣሁትና፤ ደስ ብሎኛል! ለመጀመሪያ ጊዜም ነው 3700 ከፍታ ላይ የወጣሁት እዚህ ስገኝ!
በቅሎ ላይ መውጣቴ ጥቅሙ በእግሬ እንቅፋት እያየሁ መሄዴ ቀረና በቅሎ ላይ ሆኜ አካባቢውን አያለሁ፡፡ ዞር ስልም የጓደኞቼ ቅፍለት በጉም ውስጥ የሚጓዙ ከሌላ ፕላኔት ድንገት የተከሰተ ስዕል ይመስላል፡፡ በቅሎ ላይ ሆነን ቁልቁለት ወገብ መለመጥ፣ ዳገት ማቀርቀር ነው ዘዴው፡፡ የበቅሎ ጉዞ ስርዓቱ! ወሳኝ መመሪያ! ላለመውደቅ ለማሸነፍ ለመድረስ! የህይወት ልምድ ተመክሮ ነው!
መቼም ውቴል የሚባል ነገር የለም፡፡ እንግዳነታችን ለተፈጥሮ ነው፡፡ የሚያስተካክለንም ተፈጥሮ ነው፡፡ በተፈጥሮ ዳገት ላይ ጉምና ብርድ ለብሶ ለማደር መዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡
አንድ ሁለቴ ውሃ ተጐንጭቻለሁ፡፡ በቅሎዋ ላይ ሆኜ ጉም ግን እየዳበሰኝ ያልፍ ነበር፡፡ ጢሜ እርጥበት ጤዛ አለው፡፡ ገርሞኝ አገሬውን ጠየኩ፡፡ “ይህ የጉም ሽንት ነው አሉኝ!” ጉሙ ሸናብኝ መቀበል አለብኝ! ይሄ የመጀመያዬ ቀዝቃዛ አገር ነው” አለኝ፡፡
“የእኔ የአውሮፓ ልምድ ይለያል፡፡ መኪናው በረዶ ለብሶ ባካፋ ይዛቃል፡፡ ትልቁ ልዩነት እዚያ ቤት ስትገባ ባየር ማረጋጊያ ሙቅ አየር አለ፡፡ ኮትህን ማውለቅ ይጠበቅብሃል፡፡
ሁሉንም አንድ ላይ እናስበው፡፡ ከNTOው ገላጭ ሌላ አገሬውም ይግለጥልን፡፡ እኔን የመሩኝ ሰውዬ “ነዶና ሰው ተጣላ፤ አዝመራው እምቢ አለ” አሉኝ፡፡
ሌላ እንደኔ ገርሞህ ከሆነ ህፃናትና ሴቶች አላየንም (ውሻም አላየንም ብዬ ነበር) የህብረተሰቡ Pillar የሚባሉትን ሁለት አካላት ህፃንና እናት አላየንም፡፡ ለምሣሌ ዘሙቴ ማርያም ስሄድ ግብዳ ግብዳ ሻንጣችንን ጩጬ ጩጩ ልጆች ናቸው አንከብክበው ዳገት ቁልቁለቱን ፉት ያሉት! ምናልባት ማህል ሜዳ እሚባለውጋ ገብተን ባለመሆኑ ሊሆን ይችላል! ወንድ ይበዛል - ምናልባት ሴቶችና ልጆች እንዴት ነበር ልናገኝ እንችል የነበረው? ቆይ አዘጋጁን እጠይቀዋለሁ፡፡ ዕድሜያቸው ከፍ ያሉ ሽማግሌዎች በቅሎ መሳባቸው ገርሞኛል፡፡ እኔ በቅሎ ላይ ሆኜ ስጠይቃቸው ዞርም ቀናም ሳይሉ፣ ወግ ባይን ይገባል ሳይሉ፤ መልስ እየሰጡኝ ወደፊት ይገሰግሣሉ በቃ! ተፈጥሮን እኔ አደንቃለሁ፡፡ ለነሱ ተፈጥሮ ተፈጥሮ ነው በቃ! የኑስ የተባለው መንገድ ገላጫችን ያስረዳን የፀሐይ መውጣት መግባት ለነዚህ ሰዎች ጉዳይ አደለም፡፡ ስለ ኢሮብ ሰዎች ስለአዲግራት ሳወራቸው ነበር መኪና ውስጥ ሆነን፡፡ ኢሮቦች ምን ይላሉ መሰለህ “አናንተ ከደርግ ሸሽታችሁ ለመጠለልና ለመዋጋት ነው እዚህ የምትመጡት፡፡ እኛ ግን እንኖርበታለን፡፡ ኑሯችን ይሄው ነው!”
እዚህ አገር ጅቡ እንዳንተ አገር እንደ ሐረር ለትርዒት አይታይም፡፡ ጉልበተኛና ከመጣ የማይመለስ ነው አሉ! ጭላዳ ዝንጀሮ፣ ቅልጥም - ሰባሪ፣ ቀይ ቀበሮ እንደሚኖርበት ጅብም ጓሣኛ ሆኗል!
ማታ ካምፕ ፋየር አደረግን፡፡ ዘቡ መሣሪያ ይዘናል ሳይል ሽለላ ጀመረ፣ ዋሽንት ነፋ ጣሰው! ቅዝቃዜ መሸነፍ ጀመረ፡፡ ይህ ነገር ቢቀረፅ እንዴት አሪፍ ነበር፡፡ ቆጨኝና “እኛን ዓይነት ሰዎች አምጥታችሁ፣ በጥበብ የማርያም መንገድ ምንም ሊፈጠር እንደሚችል እያወቃችሁ፣ ምንም የዶክመንቴሽን ሥራ አለመሠራቱ በጣም ያሳዝናል፡፡
የመጀመሪያ ትምህርታችሁ ይሁን!” ብዬዋለሁ ለሀላፊው ለኤፍሬም (ኤፍሬም ከበቅሎ ቀድሞ ዳገት አፋፍ የሚወጣ፣ ቁልቁለት ወርዶ ቀድሞ ሜዳውን የሚረግጥ፤ ሰው ደከመኝ ብሎ ሲያርፍ እሱ ድንኳን ተከላና ሸከማ የሚጀምር፣ ቀጭን ትዕዛዝ በትህትና መስጠት የሚችል እንደ ኤስኪሞ ጀቦንቦን የለ ልብስ የለበሰ አምበሳ ኃላፊ ነው!)
ለላው ደግሞ ከአገሬው ጋራ መዋሃድ፣ ገብሱ ከየት እንደሚመጣ ማየት ነበረብን፡፡ እንደገጣሚ ይሰማኛል፡፡ ሰውን ስታውቅ ነው ተፈጥሮ ሙሉ የሚሆነው፤ አልኩኝ በልቤ፡፡ “ሎጁ ላይ ገለፃውን ሳናዳምጥ አቋርጠን መሄዳችን ቅር ብሎኛል” አለ አበባው፡፡ ልጁ፣ ገላጩ ዐረፍተነገሩን እንኳ ሳይጨርስ ነው መንገድ የጀመርነው፡፡ አሰቅቀነዋል - እኛም ሙሉ ሳንሆን ነው መንገድ የጀመርነው ማለት ነው፡፡ ዕውነት የሚመጣው የሰው ትንፋሽ ሲጨመርበት ነው - እኔ በዚህ አምናለሁ - አልኩት፡፡ ጆሮህ ቅላፄ ይናፍቃል - መፃፍ ማለት ያ ነውና! እኔ ቁጭት ነው ያለኝ!...Next time መምጣታችን አይቀርም ግን 1st Impression is last Impression የሚባለውን የሚያክል የለም! ገላጩ ልጅ እንደዛ ተገናኝተን ተዘጋጅቶ ካፉ የሚወጣውን ሳንሰማ ሄድን! ሰውየውን ከነቃናው ከነትንፋሹ ማግኘት ነበረብን፡፡ መግባባት ማለት ያ ነውና! የታሪክ ነጋሪውንም History የሚናገረውን በመንገድ ላይ ሙሉ ነገር አላገኘንም! በዚያም አንፃር ጐሎብናል! እንደወዳጅ ቀርበነው ማውጋት ነበረብን! ያ ጅምላውን ነገር ሙሉ አያደርገውም፡፡ እንደ ጋዜጠኛም እንደ Poetም ይመለከተኛል!…ገበሬው ጋ ችግር እንዳለ በቅሎ ሳቢው ነዶና ሰው ተጣላ ካሉኝ በኋላ የዘይት ዋጋ፣ የጨው ዋጋ የኢኮኖሚ ችግር እያልን ከተማ የምናወራውን From The Horses Mouth ከግብርናው ጌታ ሰማነው፡፡ ዕድገት አለ የለም ያኔ ትወስናለህ!
እንደተመክሮ ድንቅ ነገር ነው! ሪፖርት ሳይሆን ህይወት ሊኖረው ይገባል! ስሜቴን ልቀጥልልህ:-
ጣሰው ስለዋሽንት ቢነግረኝ በጣም ድንቅ ይሆናል! ጠባቂዎቹ እንደወታደር ጠባቂ ነን ብለው አልራቁንም - አብረውን ካምፕ ፋየር አደረጉ፡ የዕውነት ህዝባዊ ስትሆን ልባዊ - ህዝባዊ ነው የምትሆነው! መሣሪያውም፣ እኛም፣ ጠባቂዎቹም፣ ዋሽንቱም…እኩል እሳት የሚሞቅበት ነው ጉዋሣ! ህዝባዊነት፣ ቱሪስትነት፣ የአካባቢ ጥበቃና ጥበብ ሁሉም ማዕቀፋቸው እሳት ነው! እሳት ወይ አበባ እዚህም አለ፡፡ ለዚህ ነው በየፓርኩ ግጥም ይነበብ የሚለው ሃሳብ ትርጉም የሚኖረው! እንደማሳሰቢያ፤ ለአዘጋጆቹ ይህን እላለሁ:-
ቅድመ - ማስገንዘቢያ ቢኖር፡፡ ከከባዱ ወደ ቀላሉ ከመሄድ ለአፍቃሬ - ግጥሙ የፓኤቲክ ጃዝ ተከታታይ ከቀላሉ ወደ ውስብስቡ ቢኬድ (Law of dialectics)፡፡ ብቁ ዶክመንቴሽን (ምስለ - ዘገባ) ቢኖር፡፡ የማህበረሰቡ ተሳትፎ በቂ ቦታ ቢያገኝ፡፡ የማህበረሰቡ ክህሎት ተጠንቶ ከገጣሚያኑ ቢዋሃድ፡፡ ከተፈጥሮ ጋር መጣረርም ኅብር - መፍጠርም የጥበብ አካል መሆኑ ልብ ቢባል፡፡ የቴክኖሎጂ ግብዓት ከተፈጥሮው ሁኔታ ጋር መጣጣሙ ቢታሰብበት የተሻለ ታሪክ የመዘገብ አቅም ይኖረናል!


         በድሮ ጊዜ አንድ አንቱ የተባሉ አገረ ገዢ በየክፍለ ሀገሩ እየተዘዋወሩ ህዝቡን እየሰበሰቡ ያነጋግሩ ነበር ይባላል፡፡ አብረዋቸው አዋጅ ገላጮች ነበሩ፡፡ አዋጅ ገላጮቹ በታወጁ አዋጆች ላይ ጥያቄ ቢነሳ የሚያብራሩ የሚገልጡ ናቸው፡፡
ህዝብ ከተሰባሰበ በኋላ፣ ባለሟሉ ይነሳና
“የአገራችን ህዝብ ሆይ! አገረ ገዢው እዚህ ድረስ የመጡት የእናንተን ማናቸውም ብሶት ሊያዳምጡ ነውና ጥያቄያችሁን አቅርቡ” ይላል፡፡
አንዱ ባላገር ይነሳል፡-
“ጌታዬ የግጦሽ መሬት አንሶናል” ይላል
አገረ ገዢው ወደ ፀሐፊው ዞረው
“ይመዝገብ፡፡ እናስብበታለን”
ሌላ ባላገር ይነሳል፤
“ማዳበሪያ ይሰጣችኋል ተብለን እስከዛሬ አልመጣልንም!”
አገረ ገዢው - “ይመዝገብ፡፡ እናስብበታለን”
ሌላ ባላገር ይነሳል - “የዘር  እህል ይታደላል ተብለን ዛሬም አልተሰጠንም”
አገረ - ገዢው - “ይመዝገብ፡፡ እናስብበታለን”
ሌላ ባላገር በንዴት
“ጌታዬ! ባለፈውም እንዲሁ እናስብበታለን ሲሉ ነበር፡፡ መቼ ነው በተግባር የሚፈፀምልን? ሁሌ እናስብበታለን ነው እንዴ?”
አገረ - ገዢው - “ይሄም ይመዝገብ፡፡ እናስብበታለን!”
ይሄ በጣም ያናደደው አንድ የጎበዝ - አለቃ አገሬውን በመወከል ይናገራል፡፡
“ጌታዬ ሆይ! በእኛ ላይ የደረሰውን በደል የሚያህል የትም አገር አይገኝም! ፍትህ ሲጠፋ አቤት የምንልበት ቦታ የለም! ጤና ሲጠፋ የምንታከምበት ቦታ የለም! ትምርት ሲጠፋ የምን ማርበት ቦታ የለም፡፡ መንገዱ ሲጠፋ አሳብረን የምንሄድበት አቋራጭ እንኳን የለም፡፡ እህል ሲጠፋ አንጀታችንን የምንጠግንበት፣ ውሃ ጥም ስንቃጠል ጥማችንን የምንቆርጥበት ምንም መፍትሄ የለንም! አሁን እናንተ እያስተዳደርን አገር እየመራን ነው ትላላችሁ? እኛ ህዝቡን ማስነሳትኮ አላጣንበትም! እናንተም ደግ ደጉን አርጋችሁልን፣ እኛም ደግ ደጉን አስበንላችሁ ብንኖር አይሻልም?” አለ፡፡
አገሬው አጨበጨበ!
አገረ ገዥውም፤
“የአገሬ ህዝብ ሆይ!
ይሄ የጎበዝ አለቃ ጥሩ ይናገራል ግን ዕድሜ የለውም! አሉ
አገሬው አሁንም አጨበጨበ!
ያ ጎበዝ - አለቃም ከዚያን ቀን በኋላ አልታየም፡፡”
ሁል ጊዜ “እናስብበታለን” አያዋጣም፡፡ አፈፃፀም ያስፈልጋል፡፡ በዘመንኛው ቋንቋ ቢሮክራሲያዊ ማነቆ (Bureaucratic red - tape) መበጠስ አለበት እንደ ማለት ነው፡፡ ጥንት ንጉሡ የወሰኑትን አስፈፃሚዎቹ ባለሟሎች “እሺ” “እሺ” እያሉ በተግባር ግን አንዷንም ነገር አያውሉም ነበር ይባላል፡፡ ይሄ ክፉኛ ያቆሰለው በደለኛ ንጉሡ ዘንድ ይቀርብና፤
“ጃንሆይ! ሁሉም ነገር ይቅርብኝና አንድ ሃያ አጋሠሥ ይሰጠኝ” ሲል አቤት ይላል፡፡
ጃንሆይም “ለምንህ ነው?” ቢሉት፣
“የሸዋን መኳንንት ‹እሺታ› የምጭንበት”፣ አለ ይባላል፡፡ ውሳኔዎች፣ መመሪያዎች፣ አዋጆች፣ ወዘተ በሥራ ላይ ካልዋሉ፣ ካለንበት ንቅንቅ አንልም፡፡ ጌቶች ቢያስነጥሱ መሀረብ የሚያቀብሉ ዓይነት ሰዎች መቼም፣ የትም ድረስ አያራምዱንም! ጉዳያችሁን ተናገሩ፡፡ ብሶታችሁን አውጡ፡፡ ጥያቄያችሁን አቅርቡ፤ ብሎ ‹እድሜህ አጭር ነው› ከሚል ይሰውረን፡፡ ለአጥቂውም ለተጠቂውም ከሚያጨበጭብ ተሰብሳቢም ይሰውረን፡፡
ያልተመለሰ ጥያቄ ያልተከፈለ ዕዳ ነው፡፡ ነገ ዋጋ ያስከፍለናል፡፡ ዛሬ አድበስብሰን የምናልፈው ጥያቄ የነግ የቂም ቋጠሮ ይሆንብናል፡፡ ያ ደግሞ ዕድገትን ተብትቦ ያሰናክለዋል፡፡ የበላይ ወደታች የሚመራውን የበታች እንደ “ኮምፒዩተር ጌም” ሲጫወትበት የሚውል ከሆነ፤ እንኳን ትራንስፎርሜሽን መደበኛውም ዕድገት አይገኝም፡፡ “ሩቅ አሳቢ ቅርብ አዳሪ” መሆን የሚመጣው ለትልቁ ስዕል አስተዋፅኦ የሚያደርጉት ትናንሽ ስዕሎች በቅጡ ካልተሳሉና ሥጋና ደም ሳይለብሱ የቀሩ እንደሆነ ነው፡፡ የበታች አካላት ማያያዣ ክር ናቸው፡፡ እነሱ ከተበጣጠሱ የበላይ አካላት የሉም፡፡ ይሄ በቢሮክራሲያዊው ዓለም ብቻ ሳይሆን በፖለቲካ ፓርቲዎችም ዘንድ ያው ነው፡፡ ትናንሽ ስህተቶች ለግዙፍ ስህተት አሳልፈው ይሰጡናል፡፡ ያኔ ውድቀት ቅርብ ይሆናል፡፡
ሱን ሱ የተባለ የቻይና ጦር መሪ “በጦርነት ድል ማድረግ የሚደጋገም ነገር አይደለም፡፡ ሁሉ ቅርፁን ይለውጣል፣ ውሃ ሁሌም አንድ አይነት ቅርፅ የለውም - እንደመያዣው ዕቃ ይለዋወጣል፡፡ እንደባላንጣህ አካሄድ ቅርፅህን እየለዋወጥክ ድል መቀዳጀት ረቂቅ - ሊቅ (genius) ይባላል” ይለናል፡፡ ስለ ህይወት፣ ስለማናቸውም ትግል፣ ስለ ምርጫ፣ ስለለውጥ ስናስብ ሁሌም እንደሁኔታው  አካሄድን ቀይሮ በብስለት መጓዝን አንርሳ፡፡  ረቂቅ - ሊቅ የመሆን ጥበብ ይሄ ነው፡፡ በሌሎች ድክመት ላይ ከመንተራስ በራስ መተማመን ብልህነት ነው! አንዴ የሆነው ነገር ላይ ከማላዘን ይልቅ ሁኔታዎችን በሌላ አቅጣጫ ለመለወጥ (Reversal) መሞከር አዲስ ቅያስ ለማየት ይጠቅመናል፡፡ ሳይታለም የተፈታን ጉዳይ (de facto) ደግመን ደጋግመን መወትወት ያው ውሃ ወቀጣ ነው፡፡ የተሰረቀው ተሰርቋል፡፡ የተሄደው ድረስ ተሄዷል፡፡ የባላንጣችን አቅም ታውቋል፡፡ ዘዴና መላው በተደጋጋሚ ታይቷል፡፡ ስለዚህ የታወቀን መንገድ ትቶ ያልተሄደበትን መንገድ ወይም ብዙ ያልተሄደበትን መንገድ (The Road Less Travelled) ማሰብና ማስላት ይሻላል፡፡ የሆነውማ ሆኗል - “ለሰጠውም አላሳነሰው፣ ላልሰጠውም አላቀመሰው!”  

ፈቃድ ለማግኘት ከ1ሚ. ብር በላይ ካፒታልና 2 ሚ. ብር ዝግ ሂሳብ ያስፈልጋል
ኤጀንሲዎች ከተጓዥ ክፍያ ሊጠይቁ አይችሉም፡፡ 8ኛ ክፍል ያላጠናቀቀና የሙያ ማረጋገጫ የሌለው መሄድ አይችልም፡፡
ባለፉት 7 ወራት 50ሺ ኢትዮጵያውያን በህገ ወጥ ጉዞ የመን ገብተዋል፡፡

ወደ አረብ አገራት የሚሄዱ ሰራተኞች ላይ የሚደርሰውን ችግርና እንግልት ለማስቀረት በሚል ከአንድ ዓመት በላይ ተቋርጦ የቆየውን አሰራር ለማስጀመርና ለመቆጣጠር የተዘጋጀው ረቂቅ አዋጅ ውዝግብ አስነሳ፡፡
በሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ወደ ውጭ አገር ሰራተኞችን የሚልኩ ኤጀንሲዎች፣ የግለሰብ ድርጅት ከሆነ አንድ ሚሊዮን ብር የሽርክና ማህበር ከሆነ ደግሞ አምስት ሚሊዮን ብር ካፒታል ሊኖረው ይገባል ይላል፡፡ ኤጀንሲው ለሰራተኛው መብትና ደህንነት ዋስትና ማስከበሪያ የሚውል 100 ሺህ ዶላር (ከሁለት ሚሊዮን ብር በላይ) በዝግ ሂሳብ የማስቀመጥ ግዴታ አለበት፡፡
 ኤጀንሲዎች ለስራ ወደ ውጭ አገር የላኳቸውን ሰራተኞች ለኢትዮጵያ ኤምባሲ በ15 ቀን ውስጥ ማስመዝገብና የስራ ፈቃድ ማግኘታቸውን የሚያረጋግጥ መረጃ ለሚኒስቴሩ ማቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡ ኤጀንሲዎች ለሚሰጡት አገልግሎት ምንም ዓይነት ክፍያን መጠየቅ አይችሉም፡፡ ረቂቅ አዋጁ በውጭ አገር ስራ ለመሰማራት የሚፈልጉ ዜጎችን ዕድል የሚያጠብና ህገ ወጥነትን የሚያባብስ ነው ሉ በውይይቱ ላይ ተሳታፊ የነበሩ ሰዎች ተናግረዋል፡፡ ኤጀንሲዎች በስራው ለመሰማራት የሚያስችሏቸውን መስፈርቶች በሙሉ አሟልተው ለመቅረብ በእጅጉ እንደሚቸገሩና ረቂቅ አዋጁ መሻሻልና መታረም እንደሚገባውም ተናግረዋል፡፡ የአረብ አገራት ጉዞ በመንግስት ከታገደ ወዲህ ባሉት ሰባት ወራት 50 ሺህ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን የመን መግባታቸውንና ባለፈው ጥቅምት ወር ብቻ በህገወጥ መንገድ የመን የገቡ ኢትዮጵያውያን ቁጥር ስምንት ሺህ መድረሱን የተባበሩት መንግስታት ሪፖርት አመልክቷል፡፡


      በአፍሪካ፣ ወደ ግጭት ቀጣናዎች እየተሰማራ በስነ-ምግባርና በሙያ ብቃት ስምካተረፉት መካከል የኢትዮጵያ መካከል ሃይል አንዱ እንደሆነ የገለፀው ዘኢኮኖሚስት መጽሔት፤ ኢትዮጵያና ሩዋንዳ በሰላም አስከባሪነት ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ዘገበ፡፡
ቀደም ሲል ለሰላም አስከባሪነት የአውሮፓ ወታደሮች ሲሰማሩ እንደነበር መጽሔቱ አስታውሶ፤ ከ20 አመታት ወዲህ ግን በርካታ የአፍሪካ አገራት የአህጉራቱን ግጭቶች ለማብረድ የሰላም አስከባሪነት ስራዎችን እየተረከቡ ነው ብሏል፡፡
በተለይ ኢትዮጵያ እና ሩዋንዳ፤ እምነት የሚጣልባቸው ሰላም አስከባሪ ሃይል በማሰማራት መልካም ስም እንዳተረፉ መጽሔቱ ገልጿል፡፡
በርካታ ሺ ወታደሮችንና ቁሳቁሶችን፣ ለሰላም ተልዕኮ እንዲያሰማሩ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት በኩል በተደጋጋሚ የሚመረጡት ኢትዮጵያና ሩዋንዳ፤ ለሚያሰማሩት ጦር የስልጠና እና የጦር መሳሪያ ወጪያቸው በተመድ እንደሚሸፈንላቸው ዘኢኮኖሚስት ገልፆ፤ ይህም የመከላከያ ሃይላቸውን ይበልጥ ዘመናዊ ለማድረግ ያግዛቸዋል ብሏል፡፡
በዚህም በተጨማሪ ብዙዎቹ የአፍሪካ አገራት በራሳቸው ወጪ ለጦር መሳሪያ ገዢ የሚያውሉት ገንዘብ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል፡፡
የአንጐላ መንግስት ባለፈው አመት የመከላከያ በጀቱን ከ4.5 ቢሊዮን ዶላር ወደ 6 ቢ ዶላር (ወደ 120 ቢሊዮን ብር ገደማ) እንዳሳደገ መጽሔቱ ጠቅሶ፣ የናይጀሪያ መንግስትም ለአዳዲስ የጦር አውሮፕላኖች ግዢ አንድ ቢሊዮን ዶላር መመደቡን ዘግቧል፡፡
ከፍተኛ ገንዘብ ለጦር ሃይል በመመደብ በአፍሪካ ቀዳሚነቱን የያዘችው አልጀሪያየ በአመት 10 ቢ ዶላር ታወጣለች ብሏል - ዘገባው፡፡
የዛሬ 25 አመት ገደማ ሶቪዬት ህብረት የምትመራው የሶሻሊዝም አምባገነንነት ሲፈራርስ፣ በአፍሪካም በርካታ መንግስታት ከስልጣን እንደተወገዱና አንዳንዶቹም የተቃውሞ ፓርቲዎች እንዲንቀሳቀሱ የሚፈቅድ ማሻሻያ ለማድረግ እንደተገደዱ የሚታወስ ሲሆን፣ የነፃ ገበያ እና የዲሞክራሲ ስርዓት ጅምር ማሻሻያ ላይ በማተኮር ለመከላከያ ሃይል የሚያወጡት በጀት ለ15 አመታት ሳይጨምር እንደቆየ መጽሔቱ ያመለክታል፡፡
ባለፉት አስር ዓመታት ግን፣ የሃይማኖት አክራሪነትና የሽብር አደጋ፣ በዘር የሚቧደኑ ታጣቂዎችና ቡድኖች ግጭት፣ እንዲሁም የባህር ላይ ውንብድና ከፍተኛ ስጋት የሆነባቸው የአፍሪካ መንግስታት ለመከላከያ ሃይል ከፍተኛ ገንዘብ መመደብ ጀምረዋል፡፡
በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር የነበሩት ዴቪድ ሺን ለመጽሔቱ በሰጡት ገለፃ፣ አንዳንድ የአፍሪካ መንግስታት ጉድ የሚያሰኙ የጦር መሳሪያዎች እየገዙ ነው ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ T-72 የተሰኙ ዘመናዊ ታንኮችን ከዩክሬን ማስገባት ጀምራለች፡፡ ደቡብ ሱዳን ደግሞ መቶ ታንኮችን፡፡
ሰፊ የባህር በር ያላቸው እንደ ካሜሩን እና ሞዛንቢክ፣ ሴኔጋልና ታንዛኒያ የመሳሰሉ አገራት የባህር ሃይላቸውን በጦር መሳሪያ እያፈረጠሙ መሆናቸውን ዘኢኮኖሚክስ ጠቅሶ፣ አንጐላ ደግሞ የጦር አውሮፕላኖችን የሚሸከም ተዋጊ መርከብ ለመግዛት የጀመረችው ድርድር አስገራሚ መሆኑን ጠቁሟል፡፡
የአፍሪካ አገራት ጦር፣ በስልጠናና በመሳሪያ ይበልጥ “ፕሮፌሽናል” ለመሆን እየተሻሻሉ መጥተዋል የሚለው ዘኢኮኖሚስት፣ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገባቸው ለመከላከያ ሃይል ደህና ገንዘብ እንዲመድቡ ከማስቻሉም በተጨማሪ እንደ ኢትዮጵያና ሩዋንዳ ደግሞ በሰላም አስከባሪ ሃይል ተልእኮ አማካኝነት የማይናቅ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጿል፡፡
እንዲያም ሆኖ የጦር መሳሪያ ግዢ በሁሉም አገራት ውጤታማ ሆኗል ማለት አይደለም፡፡ ኮንጐ ብራዛቪል ፈረንሳይ ሰራሽ ሚራዥ የጦር አውሮፕላኖችን ብትሸምትም፣ በብሔራዊ በዓላት የበረራ ትርዕት ከማሳየትና የበዓል ማድመቂያ ከመሆን ያለፈ ጥቅም አላስገኙም፡፡ ደቡብ አፍሪካም ከስዊድን 26 ተዋጊ አውሮፕላኖች ከገዛች በኋላ፣ በበጀት እጥረት ግማሾቹ ከአገልግሎት ውጭ የጋራዥ ሰለባ ሆነዋል፡፡
SU 30 አውሮፕላኖችን ከራሺያ የገዛችው ኡጋንዳ ደግሞ፤ ተስማሚ ሚሳይሎችን ስላልገዛች ዘመናዊዎቹን አውሮፕላኖች በአግባቡ ልትጠቀምባቸው አልቻለችም ብሏል መጽሔቱ፡፡   

ለአመት ያህል በበርሜር ወደ 110 ዶላር ንሮ የቆየው የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ፤ ካለፈው ሐምሌ ወዲህ እየወረደ በያዝነው ሳምንት ከ75 ዶላር በታች የደረሰ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ የነዳጅ ዋጋ ላይ መንግስት እስካሁን ቅናሽ አላደረገም።
በአመት በአማካይ ከሰባት በመቶ በላይ እየጨመረ የመጣው የኢትዮጵያ የነዳጅ ፍጆታ፣ ባለፈው አመት 3.4 ቢሊዮን ዶላር (ከ65 ቢሊዮን ብር በላይ) ወጪ እንዳስከተለ ታውቋል። ሸቀጦች ወደ ተለያዩ አገራት በመላክ የሚገኘው የውጭ ምንዛሬ ባለፉት አራት አመታት እድገት ባለማሳየቱ አመታዊው ገቢ ከሶስት ቢሊዮን ዶላር ገደማ ብዙም ፈቅ ባለማለቱ፣ የነዳጅ ግዢን እንኳ ለመሸፈን የማይበቃ ሆኗል።
በአለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ ባለፈው አመት በነበረበት ቢቀጥል ኖሮ፣ በቀጣዩ አመት ኢትዮጵያ ሩብ ቢሊዮን ዶላር (5 ቢሊዮን ብር) ተጨማሪ ገንዘብ ለነዳጅ ግዢ ለማውጣት መገደዷ አይቀርም ነበር። ይሁን እንጂ፣ ያለማቋረጥ እየወረደ የመጣው የነዳጅ አለማቀፍ ዋጋ በስድስት ወራት ውስጥ ሲሶ ያህል ስለቀነሰ፣ ኢትዮጵያ ለነዳጅ ግዢ የምታውለው የውጭ ምንዛሬ ዘንድሮ እንደማያሻቅብ ተገምቷል።
 እንዲያውም የድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በበርሜል ከ80 ዶላር በታች ሆኖ ከቀጠለ፣ የአንድ ቢሊዮን ዶላር (የ20 ቢሊዮን ብር ወጪ ቅናሽ ያስገኛል፡፡) በርካታ ነዳጅ አምራች አገራትን የሚቆጣጠሩ መንግስታት በአባልነት የተካተቱበት ኦፔክ የተሰኘው ማህበር፣ ሰሞኑን በነዳጅ ዋጋ ዙሪያ የተወያየ ቢሆንም፣ ውይይታቸው በአለም የነዳጅ ዋጋ ላይ ለውጥ እንደማያስከትል ትናንት ቢቢሲ ዘግቧል። እየወረደ የመጣው የነዳጅ ዋጋ፣ የበርካታዎቹን መንግስታት ገቢ እንደሸረሸረ የገለፀው ቢቢሲ፣ ከፍተኛ የበጀት ጉድለት ያጋጥማቸዋል ብሏል። “ዋጋ እንዲያንሰራራ የነዳጅ ምርት መቀነስ አለብን” የሚል ጥያቄ ከሁለት መንግስታት በኩል እንደቀረበ ዘገባው ጠቅሶ፣ ጥያቄው በአብዛኞቹ መንግስታት ተቀባይነት ሳያገኝ መቅረቱን አመልክቷል።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የነዳጅ ዋጋ መውረድ የጀመረው፣ በከፊል ከአለም ኢኮኖሚ መቀዛቀዝ ጋር በተያያዘ ምክንያት ቢሆንም፣ ዋናው ምክንያት ግን የአሜሪካ ኩባንያዎች ከፍተኛ የነዳጅ ምርትን የሚያስገኝ አዲስ ዘዴ በመፍጠራቸውና ተጨማሪ ነዳጅ ማምረት በመጀመራቸው እንደሆነ ፎርብስ መፅሔት ዘግቧል።
ከአለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ ውጣ ውረድ ጋር፣ የኢትዮጵያ መንግስት በንግድ ሚኒስቴር በኩል በየወሩ የነዳጅ ዋጋ ተመን የሚያወጣ ሲሆን፣ ከጥቂት ጊዜያት በስተቀር አብዛኛውን ጊዜ የዋጋ ተመኑ በነበረበት እንዲቀጥል አልያም የአለም ገበያን ተከትሎ እንዲጨምር ሲወስን መቆየቱ ይታወሳል።
ባለፉት ስድስት ወራትም እንዲሁ፣ በአለም ገበያ የነዳጅ ዋጋ በፍጥነት እየወረደ ቢመጣም፣ በኢትዮጵያ ግን የችርቻሮ ዋጋ በነበረበት ደረጃ እንዲቀጥል አልያም እንዲጨምር የተደረገ ሲሆን፣ በያዝነው ወር መጨረሻ የዋጋ ተመኑ ላይ ምን አይነት ለውጥ እንደሚደረግበት ገና አልታወቀም። በተለመደው የመንግስት አሰራር፣ የዋጋ ተመን ውሳኔው በይፋ እስከሚገለፅበት እለትና ሰዓት ድረስ በሚስጥር ተጠብቆ ነው የሚቆየው።

          14ኛው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ነገ 40ሺ ተወዳዳሪዎችን በማሳተፍ ይካሄዳል፡፡ የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫውን ከማካሄዱ በፊት ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ሰሞኑን ውድድሩን ያጀቡ የተለያዩ ዝግጅቶች ነበሩት፡፡ የመጀመርያው ባለፈው ረቡዕ በኤግዚብሽን ማእከል የተከፈተው የስፖርት ኤክስፖ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካ ለመጀመርያ ጊዜ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ስብሰባም ተስተናግዷል፡፡ የዓለም የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር የስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ስብሰባ ትናንት እና ከትናንት በስቲያ በቀነኒሳ ሆቴል ተካሂዷል፡፡ መስተንግዶውን ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከታዋቂው የአትሌቲክስ ስፖርት ፎቶግራፈር ዢሮ ሚሹዙኪ፤ ከቀነኒሳ በቀለ እና ከአትሌቲክስ ፌደሬሽን ጋር በመተባበር አከናውነዋል፡፡ በስብሰባው ላይ ለመገኘት ወደ ኢትዮጵያ የመጡት  ከ10 የተለያዩ አገራት የተውጣጡ 29 የስፖርት ባለሙያዎች ናቸው፡፡ ከመካከላቸው ከኦስትሪያ ፤ከዩክሬን፤ ከሮማንያ ፤ከፈረንሳይ፤ ከደቡብ ኮርያ፤ ከጃፓን፤ ከእንግሊዝ ከጣሊያን ከኬንያ እና ሌሎች የዓለም ክፍሎች የመጡ ባለሙያዎች ይገኙበታል፡፡

ባለፈው ረቡእ በቀነኒሳ በቀለ ሆቴል በተዘጋጀላቸው የእራት ግብዣ ላይ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ መስራች እና ሊቀመንበር ኃይሌ ገብረስላሴ ባሰማው ንግግር አትሌቲክስ ስፖርት ኢትዮጵያን ለዓለም ለማስተዋወቅ ሁነኛ አማራጭ እንደሆነ ትተዘባላችሁ ሲል ተናግሯል፡፡ በዚሁ የእራት ግብዣ ላይ የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ለእንግዶቹ የአገር ልብስ ስጦታ ያቀረበ ሲሆን የአትሌቲክስ ፌደሬሽን ተወካዮች በበኩላቸው ኢትዮጵያ በስፖርቱ የ65 ዓመታት ታሪክ ማሳለፏን ጠቅሰው የታላላቅ አትሌቶች መገኛ በሆነች አገር ለምታዘጋጅቱ ትልቅ ውድድራችሁ እናመሰግናለን በማለት ለታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ድጋፍ ሰጥተዋል፡፡
14ኛው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዛሬ በጃንሜዳ አካባቢ እስከ 4ሺ ህፃናትን በማሳተፍ በሚካሄደው ከ500 ሜትር እስከ 2000 ሜትር ውድድር ነው፡፡ ነገ ጠዋት በጃንሜዳ አካባቢ ውድድሩን የሚያስጀምሩት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ የተከበሩ አባዱላ ገመዳ ሲሆኑ የእለቱ የክብር እንግዶች እንግሊዛዊው የትራያትሎን አትሌት አሊስተር ብራውንና ኬንያዊቷ ማራቶኒስት ኤድና ኪፕላጋት አብረዋቸው ይኖራሉ፡፡ በዋናው የአትሌቶች ውድድር 40 ክለቦችን የወከሉ ከ600 በላይ አትሌቶች የሚፎካከሩ ሲሆን ፤ ለአንደኛ 40ሺ ለሁለተኛ 25 ሺ እንዲሁም ለሶስተኛ 12ሺ 500 ብር በሁለቱምፆታዎች በሽልማት ይበረከታል፡፡  ከ15 አገራት የመጡ 300 ስፖርተኞች ከ40ሺው ስፖርተኛ መካከል ሲገኙበት የ13 አገራት አምባሳደራት በኢትዮጵያን ኤርላይንስ አዋርድ ለማሸነፍ ይሽቀዳደማሉ፡፡ትናንት በሂልተን ሆቴል በተሰጠው መግለጫ ላይ  በ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው በጋራ እየሮጥን በጋራ እንደሰት በማለት መልዕክት ያስተላለፈው ኃይሌ ገብረስላሴ፤ የውድድሩ እድገት ገና ይቀጥላል ብሏል፡፡ የክብር እንግዶች ከሆኑት አንዷ ኬንያዊቷ ኤድና ኪፕላጋት ኃይሌን ከ16 ዓመቷ ጀምራ እንደምታውቀው ገልፃ በምታደንቀው አትሌት የተዘጋጀ ውድድርን ለማስጀመር መጋበዟ ታላቅ ክብር ነው ብላለች፡፡ ኤድና ኪፕላጋት ከ12 በላይ ማራቶኖችን ያሸነፈች አትሌት ስትሆን  በሀለት የዓለም ሻምፒዮናዎች በማራቶን አከታትላ በማሸነፍ ሁለት የወር ሜዳልያዎች የተጎናፀፈች እና ዘንድሮ የለንደን ማራቶንን ለማሸነፍ የበቃች ናት፡፡ በሌላ በኩል ሌላው የክብር እንግዳ በለንደን ኦሎምፒክ በትራይትሎን ስፖርት የወርቅ ሜዳልያ ያገኘው አሊስተር ብራውንሊ በውድድሩ ለመሳተፍ መጓጓቱን ይናገራል፡፡ ትራያተሎን 500 ሜትር በዋና፤ 40 ኪሎሜትር በብስክሌት ግልቢያ እንዲሁም 10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫን በማካተት የሚካሄድ ስፖርት ነው፡፡ ለታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያን በአጋርነት ሲደግፉ ከቆዩት አንዱ የሆነው የእንግሊዙ ኖቫ ኢንተርናሽናል ዲያሬክተር ዴቪድ ሊንግተን ውድድሩ ባለው ማራኪ ድባብ ከዓለማችን ምርጡ ነው ካሉ በኋላ የውድድር ተቋማቸው በመላው እንግሊዝ ካካሄዳቸው ውድድሮች አሸናፊዎቹን ይዞ በመምጣት ዘንድሮ ተሳትፎ እንደሚያደርግ ገልጿል፡፡ ኖቫ ኢንተርናሽናል አስከ 1 ሚሊዮን ተሳታፊዎች ያገኙ ውድድሮችን በማዘጋጀት በመላው ብሪታኒያ የሚንቀሳቀስ ነው፡፡ በሌላ በኩልየኢትዮጵያ ቱሪዝም ኦርጋናይዜሽን ዲያሬክተር አቶ ሰለሞን ታደሰ የሩጫ ውድድሩ የቱሪዝም እንቅስቃሴን የሚያቀላጥፍ ብለው ሲያደንቁ፤ የውድድሩ ስፖንሰር የሆነው የኢትዮጵዩ ንግድ ባንክ ሃላፊ አቶ ኤፍሬም መኩርያ የኢትዮጵያ ትልቁ ባንክ የአፍሪካን ታላቅ ውድድር ስፖንሰር በማድረጉ ደስተኛ ነው ብለዋል፡፡