Administrator

Administrator

       ኧርነስት ሚለር ሄሚንግዌይ፡ 1899 – 1961 - አሜሪካዊው ደራሲ ሄሚንግዌይ፤ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥነፅሁፍ  ከመግባቱ በፊት በጋዜጣ ሪፖርተርነት የሰራ ሲሆን በአንደኛው የዓለም ጦርነት ወቅት  ለአሜሪካ ቀይ መስቀል በአምቡላንስ ሹፌርነትም አገልግሏል፡፡ ወደ ድርሰቱ ዘልቆ ከገባ በኋላ Men without Women በሚል ርእስ  የአጭር ልብወለድ ሥራዎቹን አሰባስቦ ያሳተመ ሲሆን  በመቀጠልም A Farewell to Arms በሚል ርእስ ረዥም ልብወለዱን አሳትሟል፡፡
በልብወለድ ሥራ የፑልቲዘር ሽልማት ያሸነፈበት The Old Man and the Sea ከአስር  ዓመት በፊት በደራሲና ተርጓሚ መስፍን አለማየሁ ወደ አማርኛ ተመልሶ ለአንባቢያን የደረሰ ሲሆን ብዙዎች ማራኪ ሆኖ መተርጎሙን መስክረውለታል፡፡ በነገራችን ላይ የአገራችን አንባቢያን ለብዙዎቹ የሔሚንግዌይ ሥራዎች በተለይ ለአጭር ልብወለዶቹ  እንግዳ አይደሉም፡፡ ጥቂት የማይባሉ አጭር ልብወለዶቹ ወደ አማርኛ የተተረጎሙ ሲሆን የተወሰኑት በእዚሁ ጋዜጣ ላይ መውጣታቸው ይታወሳል፡፡
በተሲያት በኋላው ሞቃት አየር ሳቢያ  ጠዋት ጠዋት መፃፍ እንደሚያዘወትር የገለፀው ደራሲው፤ በቀን አንድ ገፅ ከሩብ ገደማ ይፅፍ ነበር፡፡ ሥነፅሁፍ በብዛት በማምረት ትጋቱ የሚታወቀው ሄሚንግዌይ፤ መቼ መስራትና  መቼ ማቆም እንዳለበትም ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ እ.ኤ.አ በ1934 ዓ.ም ለጓደኛው ለኤፍ. ስኮት ፊትዝጌራልድ በፃፈው ደብዳቤ “አንድ ገፅ ምርጥ ሥራና ዘጠና አንድ ገፆች  ዝባዝንኬ እፅፋለሁ፡፡ ዝባዝንኬውን ታዲያ የቆሻሻ ቅርጫት ውስጥ ለመጣል እሞክራለሁ” በማለት የአፃፃፍ ልማዱን ጠቁሞታል፡፡ ዝነኛው ደራሲ ሄሚንግዌይ፤ በፑልቲዘር ሽልማት ብቻ ግን አልረካም፡፡ እናም  እ.ኤ.አ በ1954 ዓ.ም የሥነፅሁፍ የኖቤል ሽልማት ለማሸነፍ በቃ፡፡

ትሩማን ካፖቴ፡ 1924-1984 - አሜሪካዊው የረዥም ልብወለድ፣ የፊልም ፅሁፍና የቴአትር ደራሲ የነበረው ካፖቴ፤ እ.ኤ.አ በ1966 ዓ.ም በፃፈው In Cold Blood የተሰኘ ዝነኛ ኢ-ልብወለዱ  ይታወቃል፡፡
ይሄ ሥራው ለአንባቢ በበቃ በዓመቱም ወደ ፊልም ተቀይሮ ለተመልካች ቀርቧል- በተመሳሳይ ርእስ፡፡ እውነተኛ ታሪኮችን በልብወለድ የአፃፃፍ ቴክኒክ በማቅረብ ዝነኝነት ያተረፈው ደራሲው፤ ኒው ጆርናሊዝም የተሰኘ አዲስ የአፃፃፍ ስልትን እንዳስተዋወቀ ይነገርለታል።
ካፖቴ በጀርባው ተንጋሎ በአንድ እጁ ሼሪ የተቀዳበት ብርጭቆ፣ በሌላ እጁ ደግሞ እርሳስ ከያዘ ሊፅፍ ተዘጋጅቷል ማለት ነው፡፡ በ1957 ዓ.ም ለፓሪስ ሪቪው በሰጠው ቃለ-ምልልስ፤ ካልተጋደምኩ በቀር ማሰብ አልችልም ብሏል። “አልጋ ላይ ወይም ሶፋ ላይ ሰውነቴን ዘርግቼ በእጄ ሲጋራና ቡና መያዝ አለብኝ፡፡ እያጨስኩና ፉት እያልኩ ነው ለመፃፍ የምዘጋጀው፡፡” ሲል የአፃፃፍ ልማዱን ገልጿል፡፡ እንደ አብዛኞቹ ፀሃፍት ከአዕምሮው የመጣለትን ሃሳብ በቀጥታ በመተየቢያ ማሽን ላይ መፃፍ እንደማይሆንለት የተናገረው ካፖቴ፤ የመጀመሪያ ረቂቅ ፅሁፉን በእርሳስ እንደሚፅፍ፣ ከዚያም ሙሉውን  እየከለሰ በእርሳስ ከፃፈ በኋላ ወደ ታይፕ እንደሚገባ በቃለ-ምልልሱ ወቅት አስረድቷል፡፡

ፍላነሪ  ኦ’ኮኖር፡ 1925-1964 – በ20ኛው ክ/ዘመን የአሜሪካ ሥነፅሁፍ ውስጥ ጉልህ ሥፍራ ከሚሰጣቸው ምርጥ የአጭር ልብወለድ ደራሲያን መካከል  ትጠቀሳለች፡፡ የመጀመርያ የአጭር ልብወለድ መድበሏ A Good Man is Hard to Find ይሰኛል፡፡ እ.ኤ.አ በ1972 ዓ.ም The Complete Stories በሚል ሥራዋ የናሽናል ቡክ አዋርድስ ተሸላሚ ሆናለች፡፡ ዘ ሃቢት ኦፍ ቢይንግ በተባለው መፅሃፍ ላይ ስለአፃፃፍ ልማዷ ስታስረዳ፤ “በየቀኑ ለሁለት ሰዓታት ብቻ ነው የምፅፈው፤ ምክንያቱም ከዚያ በላይ አቅም የለኝም፤ በእነዚህ ሁለት ሰዓታት ውስጥ ግን ምንም ነገር ከሥራዬ እንዲያናጥበኝ አልፈቅድም” ብላለች፡፡  
ፍራንሲን ፕሮዝ፡  የBlue Angel መፅሃፍ ደራሲና የፔን አሜሪካ ማዕከል ፕሬዚዳንት የነበረችው ፕሮዝ  ለየት ያለ የአፃፃፍ ልማድ አዳብራለች። ምንም ጊዜም ስትፅፍ፤ የባለቤቷን ቀይና ጥቁር ስኩዌር ያለው ፒጃማ ሱሪና ቲ-ሸርት እንደምትለብስ ለዴይሊ ቢስት ተናግራለች፡፡ “በመታደልም ይሁን ባለመታደል ለየት ባለ አፓርትመንት ውስጥ ነው የምንኖረው፡፡ 120 ጫማ ከፍታ ያለው መስኮታችን፤ ፊቱን የሰጠው ለተንጣለለ ባህር ወይም ጥቅጥቅ ደን አይደለም፡፡ ከመስኮቱ በአንድ ጫማ ተኩል ርቀት የጡብ ግድግዳ ተገትሯል፡፡ ስለዚህ ምንም ዓይንንና ቀልብን የሚሰርቅ ነገር የለም፡፡ ልፅፍ ስቀመጥ ትኩረቴ ሳይከፋፈል ልሰራ እንደምችል ይሰማኛል” ብላለች- አሜሪካዊቷ ደራሲ ፍራንሲን ፕሮዝ፡፡

Saturday, 31 May 2014 14:42

6ቱ ላጤዎች

የኔ አይን እዚች ላይ
የዚች አይን እሱ ላይ፤
የሱ አይን እዛች ላይ
የዛች አይን እኔ ላይ፤
አቤት ክፉ እጣ
የሃብታም ቤት ጠኔ፡፡
ሶስቱ ኮረዳዎች
ሶስቱ ኮበሌዎች
ይኸው ስንት ዘመን መለያ ስማችን “ስድስቱ ላጤዎች”
(አንድነት ግርማ)


=========

እኔና እሱ
የኔ አበቃቀል፤
በጌሾና ብቅል፡፡
በጥንስስ መጥቼ፤
እሱኑ ጠጥቼ፤
አለሁት በዋዛ፤
እንዲሁ ስንዛዛ፡፡
ያ…ግን ጐረቤቴ፤
ያለው ፊት ለፊቴ፤
ጥንስሱ በወተት፤
ዕድገቱ በእሸት፡፡
እሱ ማር ወተቱን፤
ብርቱካን ካሮቱን፤
ክትፎና ዱለቱን፡፡
አኗኗሩን አውቆ፤
አካሉን ጠብቆ፤
አምሮበታል ፋፍቶ፤
ቦርጩ ከፊት ገፍቶ፡፡
እኔ ግን መጥጬ፤
ቡቅርን ለጥጬ፤
ጨጓራዬን ልጬ፤
በጌሾ ለፍልፌ፤
በሱ ተለክፌ፤
በጥንስስ መንምኜ፤
እንዲሁ ባክኜ፤
ይኸውና አለሁት፤
እሱን እያየሁት፡፡
በመጨረሻ ግን ጥሎ አይጥለኝ ጌታ፤
ድንገት አሳስቦኝ እንዲያ ወደ ማታ፤
አስታወሰኝና ሰጠኝ መፅናናቱን፤
እኔም እሱም ሞተን ከሳጥን መግባቱን፡፡
(ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ)

         በደቡብ ክልል በሰገን አካባቢ ህዝቦች ዞን፣ በኮንሶ ወረዳ በካራት ከተማ የተዘጋጀው የባህል ፌስቲቫል ዛሬ ይከፈታል፡፡ የኮንሶ ወረዳ አስተዳደር ባለፈው አመት ተመሳሳይ የባህል ፌስቲቫል ያዘጋጀ ሲሆን የፌስቲቫሉ አላማ ኢትዮጵያን ከአፍሪካ ቀዳሚ ያደረጋትን በዓለም ቅርስ መዝገብ የተመዘገበውን የኮንሶ ባህላዊ መልክአ ምድር ጨምሮ በወረዳው ያለውን ታሪካዊና ባህላዊ ቅርሶች ወደ ኢኮኖሚ ለመቀየር እንዲሁም የአለም አቀፍ ጐብኚዎችን ትኩረት ለመሳብ እንደሆነ የኮንሶ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ በራቆ በላቸው ተናግረዋል፡፡
ዛሬ በሚከፈተው በዚህ የባህል ፌስቲቫል ላይ የተለያዩ ዝግጅቶች የሚቀርቡ ሲሆን የኮንሶ ዲስትሪክት ሆስፒታል ምረቃ፣ በተለያዩ ባህላዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሲምፖዚየም፣ የመሰረተ ልማት ጉብኝት፣ የጐዳና ላይ የባህል ትዕይንትና ኮንሶን ለአለም የሚያስተዋውቁ ሌሎች ትርኢቶች ይገኙበታል ተብሏል፡፡ ፌስቲቫሉ ከዛሬ ጀምሮ እስከ ፊታችን ሰኞ የሚካሄድ ሲሆን በርካታ የአገር ውስጥና የውጭ እንግዶች ይታደማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ላለፉት 40 ዓመታት በማህበረሰብ እድገትና በህፃናት ላይ ትኩረት አድርጐ እየሰራ ሲሰራ የቆየው “ኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች ኢትዮጵያ”፤ ለአርቲስቶችና ጋዜጠኞች የጉብኝት ፕሮግራሞችን ያዘጋጀ ሲሆን ጉብኝቱ የድርጅቱን 40ኛ ዓመት በዓል በማስመልከት የተዘጋጀ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ድርጅቱ የሚከተለው የህፃናት አስተዳደግ ፍልስፍና፤ አርቲስቶች፣ ጋዜጠኞችና ታዋቂ ግለሰቦች በጉዳዩ ላይ የበለጠ እንዲሰሩ የሚያነሳሳቸው እንደሚሆን ኤስ ኦ ኤስ የላከው መግለጫ ይጠቁማል፡፡ ግንቦት 29 ከጠዋቱ 2፡30 በዋናው የድርጅቱ ቢሮ በጋዜጣዊ መግለጫ የሚጀመረው ፕሮግራሙ፤ በአዲስ አበባ የሚገኙ ተቋማቱን በማስጐብኘት እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስነ - ጥበባት ኮሌጅ የማስተርስ ዲግሪ ተማሪዎች ከህንድ ኤምባሲ ጋር በመተባበር፣ በአገራችን የመጀመሪያ የተባለውን የአጫጭር ፊልሞች ፌስቲቫል ያካሂዳሉ፡፡ ፌስቲቫሉ ዛሬና ነገ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስድስት ኪሎ ካምፓስ በሚገኘው የባህል ማዕከል የሚካሄድ ሲሆን አላማውም የአጫጭር ፊልሞችን ጥበብ ለአገራችን ተመልካቾች ለማስተዋወቅና በአገራችን ለሚገኙ የአጫጭር ፊልም ፀሐፊዎች፣ አዘጋጆች፣ ፕሮዱዩሰሮችና ተዋንያን እውቅናና ክብር ለመስጠት እንዲሁም ሙያቸውን ለማበረታታት እንደሆነ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቴአትር ጥበባት ትምህርት ክፍል በላከው መግለጫ አስታውቋል፡ 

የኒታ የቀለም ማዕከል ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ በሆኑት በኬሚካል መሐንዲስ ጌታሁን ሔራሞ ባለፉት አስር ዓመታት ከወጣት ሠዓሊያን የተሰበሰቡ 80 የሥዕል ስራዎች የተካተቱበት ዐውደ ርዕይ የፊታችን ሐሙስ በአለ የሥነ ጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት ተመርቆ ይከፈታል፡፡ “የማይሸጡ ሥዕሎች” በሚል ርዕስ የተዘጋጀው አውደርዕይ ላይ የሚቀርቡት የሥዕል ሥራዎች፤ ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ በተመረቱ የዘይትና አክሪሊክ የሥዕል ቀለሞች የተሰሩ መሆናቸው አውደርዕዩን ልዩ ያደርገዋል ብለዋል አዘጋጁ፡፡ አውደ ርዕዩ እስከ ሰኔ 13 ቀን 2006 ዓ.ም ድረስ ለተመልካቾች ክፍት ሆኖ ይቆያል ተብሏል፡፡ 

በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቴአትር የተዘጋጀው “ቅጥልጥል ኮከቦች” የተሰኘ ቴአትር የፊታችን ሰኞ ይመረቃል፡፡ ቴአትሩ የሙሉ ሰዓት ሲሆን ሰኞ ከቀኑ 10 ሰዓት ጀምሮ ለጥበብ ባለሙያዎችና ጥሪ ለተደረገላቸው እንግዶች በቴአትር ቤቱ አዳራሽ እንደሚቀርብ ታውቋል፡

በካህሳይ አብርሃ በተፃፈው “የአሲንባ ፍቅር” መፅሃፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ መፃህፍትና ቤተ-መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ውይይት እንደሚደረግ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ አስታወቀ፡፡
ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡ ሲሆን ተጨማሪ የውይይት ሀሳቦች በፕ/ር ገብሩ ታረቀ እንደሚቀርብ ታውቋል፡፡

ርዕስ - ውለታ ለነብስ (የግጥም መድበል)
ደራሲ - እዩኤል ደርብ
የመፅሃፉ መጠን - በ89 ገፆች 88 ግጥሞች
ዋጋ - 46 ብር
*          *           *
ርዕስ - የነጎድጓድ ልጆች (ልብወለድ)
ደራሲ - ቃልኪዳን ኃይሉ
የመፅሃፉ መጠን -208 ገፆች
ዋጋ - 46ብር

Saturday, 31 May 2014 14:32

የጸሐፍት ጥግ

የአንዱ ደራሲና የሌላው ደራሲ ቃል አንድ አይደለም፡፡ አንዱ ሃሞቱን ቀዶ ሲያወጣ፣ ሌላው ከካፖርቱ ኪስ መዥርጦ ያወጣል፡፡
ቻርልስ ፔጉይ
በጣም ልታነበው የምትፈልገው መፅሃፍ ካለና ገና ያልተፃፈ ከሆነ፣ ራስህ ልትፅፈው ይገባል፡፡
ቶኒ ሞሪሰን
ከጥሩ ፀሐፊ የምወድለት የሚለውን ሳይሆን የሚያንሾካሹከውን ነው፡፡
ሎጋን ፒርሳል
ወረቀትህን በልብህ እስትንፋሶች ሙላው፡፡
ዊሊያም ዎርድስ ዎርዝ
የጨረቃዋን መፍካት አትንገረኝ፤ የብርሃኑን ፍንጣቂ በተሰበረ መስተዋት ላይ አሳየኝ፡፡
አንቶን ቼኾቭ
አንዳንዴ ቀለምና ወረቀት እፍ ፍያሉ ፍቅረኛሞች ይሆናሉ፡፡ ብዙ ጊዜ ግን ወንድምና እህት ናቸው። አልፎ አልፎ ደግሞ የለየላቸው ጠበኞች፡፡
ቴሪ ጉሌሜትስ
ተለዋጭ ዘይቤዎች (Metaphors) ግዙፉን እውነት በትንሽዬ ቦታ የመያዝ ብልሃት አላቸው።
ኦርሶን ስኮት ካርድ
የምፅፈው ታሪክ አዲስ አይደለም፤ ያለነው፤ በወጉ ተፅፎ የተቀመጠ፤ የሆነ ቦታ፤ አየሩ ላይ። ከእኔ የሚጠበቀው ፈልጐ መገልበጥ ብቻ ነው።
ጁሌስ ሬናርድ