Administrator

Administrator

50ሺህ ብር በጥሬ ገንዘብና 100ሺህ ብር ግምት ያለው ቁሳቁስ ተበረከተ
የተለያዩ ድርጅቶች ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን ማዕከል 50ሺህ ብር በጥሬ ገንዘብ ሲያበረክቱ 200ሺህ ብር ለመስጠት ቃል ገቡ፡፡ እንዲሁም 100ሺህ ብር ግምት ያላቸው የተለያዩ ቁሳቁሶች ተበረከቱ፡፡
ዜማ ብዕር የኢትዮጵያ ሴቶች ማኅበር የአዲሱን ዓመት መቀበያ ከመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን ጋር ለማክበር ጳጉሜ 3 ቀን 2005 ዓ.ም ባዘጋጀው ፕሮግራም የተሳተፉ ድርጅቶችና ግለሰቦች የተለያዩ ስጦታዎች በዓይነት የሰጡ ሲሆን 200ሺህ ብር ለመስጠት ቃል ገብተዋል፤ 50ሺህ ብር አሰባስበው ሰጥተዋል፡፡
ቼሬአሊያ ብስኩትና ዱቄት ፋብሪካ፣ ዲ ኤች ገዳ፣ አዲካ፣ ቢጂአይ የተለያዩ ቁሳቁሶች በዓይነት የሰጡ ሲሆን ሆም ቤዝ የእንጨት ሥራ 50ሺህ ብር ሰጥቷል፡፡ የአፍሪካ ጤና ኮሌጅ ደግሞ የተለያዩ አልባሳትና የፅዳት ቁሳቁሶች የሰጠ ሲሆን ያለማቋረጥ ሙያዊ ድጋፍ ለማበርከት ቃል ገብቷል፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ማኅበራት አንድ ሺህ ብር የሰጡ ሲሆን ጂኤም የወጣቶች ማዕከልና ሴንትራል ጤና ኮሌጅ የገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ ቃል ገብተዋል፡፡
መቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን ማዕከል በአሁኑ ወቅት 200 አረጋውያንና የአዕምሮ ሕሙማን እየረዳ ሲሆን፣ በአዲሱ ዓመት ደግሞ 200 ተጨማሪ ሰዎች ለመቀበል ተዘጋጅቷል፡፡

ዛሬ የምድብ 1 የሞት ሽረት ፍልሚያዎች በኮንጎ ብራዛቪል ሴንተራል አፍሪካ ሪፖብሊክ ከኢትዮጵያ እንዲሁም ደርባን ላይ ደቡብ አፍሪካ ከቦትስዋና በሚገናኙባቸው ጨዋታዎች ይደረጋሉ፡፡ በምድብ 1 የደረጃ ሰንጠረዥ ኢትዮጵያ በ5 ጨዋታዎች ምንም ሳትሸነፍ በ1 ጨዋታ በቅጣት 3 ነጥብ ተቀንሶባት በ10 ነጥብና በ1 የግብ ክፍያ ምድቡን ትመራለች፡፡ ደቡብ አፍሪካ በ8 ነጥብና በ4 የግብ ክፍያ 2ኛ ደረጃ ላይ ናት፡፡ ቦትስዋና በ7 ነጥብና በ1 የግብ ክፍያ ሶስተኛ ነች፡፡ የኢትዮጵያ ተጋጣሚ የሆነችው መካከለኛው አፍሪካ በ3 ነጥብና በ6 የግብ ዕዳ መጨረሻ ነች፡፡
ዛሬ ከመካከለኛው በአፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር በኮንጎ ብራዛቪል የሚፋለመው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባለፈው ሐሙስ ምሽት በኢንተር ኮንቲኔታል ሆቴል አሸኛኘት ሲደረግለት የአግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዚዳንት አቶ ሳህሉ ገብረወልድ ‹‹የፈፀምነውን ታሪካዊ ስህተት በታሪካዊ ድል በመመለስ ድሉን ለህዝባችን የአዲስ አመት ስጦታ እናደርገዋለን ›› ብለው የተናገሩ ሲሆን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በበኩላቸው ቡድናቸው ወሳኙን ጨዋታ አሸንፎ ለመውጣት የሚያስፈልገውን ዝግጅት እንዳደረገ፤ ተጨዋቾቻቸው በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡ የብሄራዊ ቡድኑ አምበል የሆነው ደጉ ደበበ ‹‹የህዝብ አደራ ተቀብለን እንደምንጓዝ እናውቃለን በድል አድራጊነት የተጓዝንበትን የ2005 ዓ.ም በድል እንደምናጠናቅቀው እምነቴ ነው›› ብሏል፡፡ ዋልያዎቹ ሞቃታማ የሆነውን የኮንጎ ብራዛቪል የአየር ጠባይ ለመላመድ በአዳማ ዝግጅታቸውን ሲያደርጉ ሰንብተዋል፡፡ ዋልያዎቹ በዛሬው ጨዋታ የሚኖራቸው ውጤታማነት አዲሱን ዓመት በታላቅ ተስፋ ለመጀመር ከማስቻሉም በላይ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ስፖርት አፍቃሪው ኢትዮጵያ በታሪኳ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ የዓለም ዋንጫ የምታልፍበትን እድል በስፋት እንዲነጋገርበት ምክንያት ይሆናል፡፡
ጎል የተባለው የስፖርት ድረገፅ ከምድብ 1 የዓለም ዋንጫ የምድብ ማጣርያ የመጨረሻ ትንቅንቆች በፊት ከአንባቢዎቹ ድምፅ በማሰባሰብ ባወጣው ትንበያ በኢትዮጵያ እና መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ ጨዋታ ሙሉለሙሉ የአሸናፊነቱ ግምት ለዋልያዎቹ አድልቷል፡፡ ኢትዮጵያ ሴንተራል አፍሪካ ሪፖብሊክን 3ለ1 ታሸንፋለች ያሉት 30.1 በመቶ፤ 2ለ1 ያሉት 15.53 በመቶ እንዲሁም 2ለ0 ያሉት 14.56 በመቶ ናቸው፡፡ ለሌላው የምድቡ ጨዋታ በተሰጠ ግምት ደቡብ አፍሪካ ከቦትስዋና 1ለ1 አቻ ይወጣሉ ያሉትቨ 13.04 በመቶ ያህሉ ሲሆኑ 17.39 በመቶው 2ለ0 እንዲሁም 21.74 በመቶ 3ለ1 ደቡብ አፍሪካ እንደምትረታ ተንብየዋል፡፡
ዋልያዎቹ እና
የምድባቸው ቡድኖች ዝግጅት
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባለፈው 1 ዓመት በዓለም ዋንጫው የ3 ዙር ማጣሪያዎች ባደረጋቸው 7 ጨዋታዎች አልተሸነፈም፡፡ በተጋጣሚዎቹ ላይ 11 ጐል አግብቶ የቆጠረበት 5 ነው፡፡ በእያንዳንዱ ተጋጣሚው ላይ በአማካይ 1.57 ጐል ያገባል፤ 0.71 ጐል ይገባበታል፡፡ በማጣሪያዎቹ በአጠቃላይ 12 ቢጫ ካርዶች የዋልያዎቹ ተጨዋቾች ተቀጥተዋል፡፡ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከጋና ብሄራዊ ቡድን ጋር የወዳጅነት ጨዋታ የሚያደርግበት ግብዣ ከወር በፊት ቀርቦለት የነበረ ቢሆንም ብዙዎቹ ተጨዋቾች እረፍት ላይ በመሆናቸው እና ቅዱስ ጊዮርጊስ በኮንፌደሬሽን ካፕ ከነበረው ተሳትፎ በተያያዘ እድሉን ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል፡፡ ከዚያ በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ለአቋም መፈተሻ የሚሆኑትን ሁለት የወዳጅነት ጨዋታዎች ከሱዳን እና ብሩንዲ ጋር ለማድረግ ጥያቄ ቢያቀርብም ምላሽ አላገኘም፡፡ የመካከለኛው አፍሪክ ሪፖብሊክ ቡድን ከኢትዮጵያ ጋር ከሚያደርገው ጨዋታ በፊት ለአቋም መፈተሻ የሚሆነውን ግጥሚያ ከሊቢያ ጋር በማድረግ 0ለ0 ተለያይቷል፡፡ ዛሬ ከሴንትራል አፍሪካ ሪፖብሊክ ጋር ለሚደረገው ወሳኝ ፍልሚያ ለዋልያዎቹ 23 ተጨዋቾች ተመርጠዋል፡፡ ከተለያዩ አገራት ለብሄራዊ ቡድኑ የተመረጡ ፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ሳላዲን ሰኢድ ከስኬርቴ ክለብ ቤልጅዬም፤ ጌታነህ ከበደ ከዊትስ ክለብ ደቡብ አፍሪካ፤ሽመልስ በቀለ ከአሊትሃድ ክለብ ሊቢያ እንዲሁም አስራት መገርሳ ከራህማት ክለብ እስራኤል ናቸው፡፡8 ተጨዋቾችን ለብሄራዊ ቡድኑ ያስመረጠው የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ነው ሲሆን ሳምሶን አሰፋ ፣ ሳላዲን በርጌቾ ፣አበባው ቡጣቆ ፣ቢያድግልኝ ኤልያስ፣ ምንያህል ተሾመ፣ በኃይሉ አሰፋ፣ አዳነ ግርማና ኡመድ ኡክሪ ናቸው፡፡ ከዘንድሮው የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ደደቢት አምስት ተጨዋቾች ሲመረጡ እነሱም ሲሳይ ባጫ ፣ ብርሃኑ ቦጋለ ፣ስዩም ተስፋዬ፣ ዳዊት ፍቃዱ እና ማይክል ጆርጂ ናቸው፡፡ ቶክ ጀምስና ፋሲካ አስፋው ከኢትዮጵያ ቡና፤መድሃኔ ታደሰና ሽመልስ ተገኝ ከመከላከያ ፤ዮናታን ከበደና ደረጀ ዓለሙ ከዳሸን ቢራ፤ ሙሉዓለም መስፍንና አንተነህ ተስፋዬ ከአርባምንጭ ተመልምለዋል። የተቀሩት ሞገስ ታደሰ ከመድን፤ በረከት ይስሃቅ ከመብራት ሃይል፤ ተክሉ ተስፋዬ ከንግድ ባንክ ናቸው፡፡ባፉና ባፋዎቹ ለመጨረሻው የሞት ሽረት ትንቅንቅ በፕሮፌሽናል ቡድናቸው ተጠናክረዋል። 4 ተጨዋቾች ከእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ፣ ሁለት ወጣት አማካዮች ከሆላንዱ ኤር ዲቪዜ፣ ከፍተኛ ልምድ ያለው የቀኝ ተመላላሽ ከቤልጅዬም ክለብ እና ምርጥ የመሀል ተከላካይ ከሩስያ ፕሪሚዬር ሊጋ በመጥራት ሲሰሩ ቆይተዋል፡፡ ቦትስዋና በአመዛኙ በደቡብ አፍሪካ አብርሣ ፕሪሚዬር ሊግ በሚወዳደሩ ክለቦች ውስጥ ያሉ ከ10 በላይ ተጨዋቾች አሰባስባለች፡፡
የደቡብ አፍሪካው አሰልጣኝ ጐርደን ሌጀንሰንድ ከቦትስዋና ጋር በሚደረገው ጨዋታ በዓለም ዋንጫ ማጣሪያው ማናቸውንም ነፍስ የምንዘራበት ውጤት እና ሂሳባዊ ስሌትን ከቡድኔ እፈልጋለሁ ብለዋል፡፡ ከአጀማመር ይልቅ አጨራረስን ማሰብ ይሻላል ብለው የሚሰሩ አሰልጣኝ መሆናቸውን ሱፐር ስፖርት በዘገባው ገልጿል፡፡ ጎርደን ሌጀሰንድ አስተያየታቸውን ሲቀጥሉ ‹‹ቦትስዋናን ካሸነፈን በተከታታይ ካደረግናቸው 4 ጨዋታዎች 3 አሸንፈን ማለት ነው፡፡ ይህ በውድድር አንድ ብሔራዊ ቡድን ሊያገኝ የሚቻለው ከፍተኛ ውጤት ነው። ዋናው ነገር ቦትስዋን እንደምናሸንፍ እርግጠኞች መሆናችን ነው፡፡ በተቀረ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ ኢትዮጵያን በማሸነፍ ትረዳናለች ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ” ሲሉ ተናግረዋል፡፡ የቦትስዋና ብሄራዊ ቡድን በሞግዚት አሰልጣኙ ስታንሌ ቶሶሄኔ የሚመራው ሲሆን በዛሬው ጨዋታ ቡድናቸው ያልተጠበቀ ድል ማስመዝገቡ እንደማይቀር እምነቴ ነው ብለው ተናግረዋል፡፡አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በጨዋታው ላይ አስተያየት ሲሰጡ‹ የሞት ሽረት ፍልሚያ ነው፡፡ ብሄራዊ ቡድናችን በፊፋ ቅጣት 3 ነጥብ በተቀነሰበት ሰሞን ከሩዋንዳ ጋር ለቻን ውድድር ለማለፍ የደረሰውን የደርሶ መልስ ትንቅንቅ በማሸነፍ ጥንካሬው ታይቷል፡፡ በተቀነሰብን ነጥብ ምክንያት ለደቡብ አፍሪካ እና ቦትስዋና በማጣርያው የማለፍ ተስፋን ፈጥሯል፡፡ ይሁንና በኛ ተጨዋቾች ያለው ጠንካራ መንፈስ ሙሉ ለሙሉ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክን በማሸነፍ ላይ የሚያተኩር ነው። ሙሉ 3 ነጥብ በመውሰድ እናሸንፋለን። በማለት ተናግረዋል፡፡ የመካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ አሰልጣኝ የሆኑት ሄርቬ ሉጁዋንጂ‹‹ ብራዛቪል የገባነው ኢትዮጵያን ለማሸነፍ ነው፡፡ በምድቡ ሁሉም የሚገርፈው ቡድን የእኛ መሆኑን የሚያስቡ አሉ፡፡ ይህን አስተሳሰብ ፉርሽ ማድረግ እንፈልጋለን። በሁሉም የምድብ ጨዋታዎች ጥሩ ነበርን፤ ውጤት ያጣነው በእድለቢስነት ነው። ኢዮጵያን እናከብራታለን እንጅ እንፈራትም፡፡›› በማለት ለሱፕር ስፖርት አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
አስሩ ምድቦች ያሉበት ሁኔታ
በዓለም ዋንጫ የተሳትፎ ታሪካቸው እስከ ሩብ ፍፃሜ በመድረስ የአፍሪካን ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡት ጋና እና ሴኔጋልን ጨምሮ 5 አገራት ዛሬ እና ነገ በሚደረጉ የመጨረሻ ዙር የማጣርያ ግጥሚያዎች ምድቦቻቸውን በመሪነት ጨርሰው ለማለፍ አንድ ነጥብ ብቻ የሚፈልጉ ናቸው። ጋና፤ ናይጄርያ፤ ሴኔጋል፤ ካሜሮንና ቱኒዚያ ምድቦቻቸውን በመሪነት ለመጨረስ በሜዳቸው በሚያደርጓቸው ጨዋታዎች አቻ ውጤት ይበቃቸዋል፡፡ በምድብ 1 ኢትዮጵያ ለማለፍ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክን ማሸነፍ ግድ ይሆንባታል፡፡ የኢትዮጵያ አቻ መውጣት ለደቡብ አፍሪካ ቦትስዋናን አሸንፎ የማለፍ እድል የሚፈጥር ሲሆን መሸነፍ ደግሞ ደቡብ አፍሪካን ማሸነፍ ከቻለች ለቦትስዋናም ማለፍ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ በምድብ 2 ከፍተኛ የማለፍ እድል ያላት በ11 ነጥብና በ6 የግብ ክፍያ የምትመራው ቱኒዚያ ነች፡፡ ከምድብ 3 አይቬሪኮስት ማለፉ አረጋግጣለች፡፡ በምድብ 4 ጋና በ12 ነጥብና በ2 የግብ ክፍያ መሪነቱን ብትይዝም ዛምቢያ በ1 ነጥብ ብቻ ተበልጣ በተመሳሳይ የግብ ክፍያ እየተከተለች ነው፡፡ በምድብ 5 ኮንጐ በ10 ነጥብ 5 በ1 የግብ ክፍያ እየመራች ነው፡፡ ቡርኪናፋሶ በ9 ነጥብና በ4 የግብ ክፍያ እንዲሁም ጋቦን በ7 ብር በ5 የግብ ክፍያ የማለፍ ዕድል እንደያዙ ናቸው፡፡ በምድብ 6 ናይጄሪያ በ9 ነጥብና 3 የግብ ክፍያ ብትመራም ማላዊ በ7 ነበር በ3 የግብ ክፍያ እንዳደፈጠች ነው፡፡ ግብጽ ከምድብ 7 ከመጨረሻዎቹ ግጥሚያዎች በፊት ማለፏን ያረጋገጠችው በ15 ነጥብና በ5 የግብ ክፍያ በማስመዝገብ ነው፡፡ አልጀሪያ ደግሞ ምድብ 8ን በ12 ነጥብና በ4 የግብ ክፍያ ከ6ኛው ጨዋታ በፊት በመቆጣጠር ማለፏን አረጋግጣለች፡፡ በምድብ 9 መሪነቱን ካሜሮን በ10 ነጥብና በ3 በግብ ክፍያ ብትይዘውም ሊቢያ በ9 ነጥብና በ2 የግብ ክፍያ ትከተላታለች፡፡ በመጨረሻም በምድብ 10 ሴኔጋል በ9 ነጥብና 4 የግብ ክፍያ መሪነቱን ስትይዝ ኡጋንዳ በ8 ነጥብና 5 የግብ ክፍያ ተናንቃለች፡፡ በማጣሪያው የኮከብ ግብ አግቢነት ፉክክር በ5 ጐሎቻቸው ሦስት ተጨዋቾች ሲጠቀሱ፤ እነሱም ኢስማን ሱሊማን በ5 ጨዋታዎች 293 ደቂቃዎች በመጫወት፣ ጌታነህ ከበደ በ5 ጨዋታዎች 312 ደቂቃዎች በመጫወት እንዲሁም የግብፁ መሃመድ ሳላህ በ5 ጨዋታዎች 450 ደቂቃዎች በመጫወት ነው፡፡ ሌላው ኢትዮጵያዊ ሳላዲን ሰይድ በ4 ጨዋታዎች 347 ደቂቃዎችን ተጫውቶ ባስመዘገበው 4 ጐል ከሌሎች 7 ተጨዋቾች ጋር በማጣሪያው የኮከብ ግብ አግቢው ፉክክር የደረጃ ዝርዝር ተጠቅሷል፡፡
የ3ኛው ዙር የጥሎ ማለፍ
የዓለም ዋንጫው የመጨረሻው ጥሎ ማለፍ ትንቅንቅ የማጣሪያው 3ኛ ዙር ምዕራፍ ነው፡፡ በ2ኛው ዙር በምድብ ድልድል ላለፈው 1 ዓመት ሲደረግ በቆየው ፉክክር በአስሩ ምድቦች አንደኛ ደረጃ የያዙት 10 ብሔራዊ ቡድኖች ወደ ዓለም ዋንጫ የማለፍ ዕድላቸውን በደርሶ መልስ ጨዋታዎች ይወስኑበታል፡፡ ከምድብ ማጣሪያው የመጨረሻ 6ኛ ግጥሚያዎች በፊት ከምድብ 3 አይቬሪኮስት ከምድብ 8 ግብጽ እንዲሁም ከምድብ 9 አልጀሪያ ወደ 3ኛው ዙር ጥሎ ማለፍ መሸጋገራቸውን አረጋግጠዋል፡፡ ለቀሩት የ7 ብሔራዊ ቡድኖች ኮታ ዛሬና ነገ በሚደረጉ የምድብ ማጣርያው የመጨረሻ ፍልሚያዎች ይታወቃሉ፡፡ ኢትዮጵያ በዛሬው ጨዋታ ለዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ ማጣሪያ ከበቃች በውድድሩ የተሳትፎ ታሪክ ትልቅ ውጤት ይሆናል፡፡ በታሪካዊው የጥሎ ማለፍ ምዕራፍ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከአፍሪካ 10 ብሔራዊ ቡድኖች አንዱ ሲሆን ከምዕራብና ከሰሜን አፍሪካ ብሔራዊ ቡድኖች የሚገናኝበት እድል ያመዝናል፡፡ ከአይቬሪኮስት፣ ከጋና ወደ ከናይጀሪያ ወይም ከአልጀሪያ፣ ከግብፅ ወይም ከቱኒዚያ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሊገናኝ ይችላል፡፡ የ3ኛው ዙር የጥሎ ማለፍ ድልድል ለ10ሩ ብሔራዊ ቡድኖች የሚወጣው ከሳምንት በኋላ በካይሮ ነው፡፡ አስሩ ብሔራዊ ቡድኖች ለጥሎ ማለፍ ድልድል የሚወጣላቸው በሁለት ማሰሮዎች ሆነው አምስት አምስት ሆነው በመቧደን ሲሆን በሁለቱ ማሰሮዎች የሚገቡት ቡድኖች ማንነትን የሚወስነው በሚቀጥለው ሰሞን በፊፋ ይፋ በሚሆነው ወርሃዊ የእግር ኳስ ደረጃ ነው፡፡የ3ኛው ዙር የጥሎ ማለፍ የደርሶ መልስ ጨዋታዎቹ ከወር በኋላ በኦክቶበር 11-15 የመጀመርያዎቹ ጨዋታዎች እንዲሁም ኖቬምበር 15-19 ላይ የመልስ ጨዋታዎቹ ይደረጋሉ። አፍሪካን ወክለው በ2014 እ.ኤ.አ ብራዚል ወደምታስተናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ የማያልፉ 5 ብሔራዊ ቡድኖች በ3ኛው ዙር የጥሎ ማለፍ ትንቅንቅ ተለይተው ይታወቃሉ፡፡

የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የትያትር ትምሕርት ክፍል ለመክፈት በቅድመ ዝግጅት ላይ መሆኑ ታወቀ፡፡ ለዚሁ ቅድመ ዝግጅት ይረዳ ዘንድ የዩኒቨርሲቲው የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ትምሕርት ክፍል ምሁራን እና ሌሎች ጉዳዩ የሚመለከታቸው ኃላፊዎች፤ የሀገሪቱን ከፍተኛ የትምሕርት ተቋማት እየጎበኙ ነው፡፡ የአዲስ አድማስ ምንጮች የትምሕርት ክፍሉ በ2006 ዓ.ም የትምሕርት ዘመን እንደሚከፈት የገለፁ ሲሆን በዩኒቨርሲቲው የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነጽሑፍ አማርኛ ትምሕርት ክፍል ኃላፊ አቶ አማረ ተሾመ ግን “አንድ ባልደረባችን ባቀረቡት ፕሮፖዛል መሠረት የቅድመ መነሻ ሀሳብ ለማቅረብ በዝግጅት ላይ ነን፡፡ በትክክል መቼ እንደምንከፍት አልወሠንንም” ብለዋል፡፡

Saturday, 07 September 2013 11:52

“መልክዐ ስብሐት”

ነገ ለውይይት ይቀርባል
በአርታዒ አለማየሁ ገላጋይ የተዘጋጀው “መልክዐ ስብሐት” ነገ ለውይይት እንደሚቀርብ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ አስታወቀ። “ስብሐትን ከሌላ ማእዘን” በሚል የትኩረት ሀሳብ መነሻ በማቅረብ ውይይቱን የሚመሩት አርኪቴክት ሚካኤል ሽፈራው ናቸው፡፡ ውይይቱ በብሄራዊ ቤተመፃህፍት ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ ለሦስት ሰዓት ይካሄዳል፡፡

በሲሳይ መንግስቴ አዲሱና አለሙ ካሳ ረታ የተዘጋጀው በራያ ሕዝብ ላይ ያተኮረ መጽሐፍ ዛሬ እንደሚመረቅ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ “የራያ ሕዝብ የማንነት ጥያቄና የማእከላዊ መንግስታት ምላሽ፤ ከአጼ ዮሐንስ ፬ኛ እስከ ኢህአዴግ” በሚል ርእስ የተፃፈው መጽሐፍ የሚመረቀው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ በሚገኘው ራስ መኮንን አዳራሽ ነው፡፡

በራስ ሆቴል ትልቁ አዳራሽ እየቀረበ ያለው “ግጥም በጃዝ” 26ኛ ዝግጅቱን በመጪው ረቡዕ መስከረም ፩ እንደሚያቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ። በረቡዕ ልዩ ዝግጅት አበባው መላኩ፣ ግሩም ዘነበ፣ ደምሰው መርሻ፣ ነቢይ መኮንን የግጥም ሥራዎቻቸውን ፋቡላ የኪነጥበባት ማሕበር “ከነፃ አውጪ” ባንድ ጋር በመሆን የሥነ ቃል ትርዒት ያቀርባሉ፡፡ ከቀኑ 11 ሰዓት ጀምሮ በሚቀርበው ዝግጅት የፍልስፍና ምሁሩ ዶር. ዳኛቸው አሰፋ ዲስኩር ያቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ፒያሳ አካባቢ የሚገኘውና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዓላትን ከነትውፊታዊ ይዘታቸው በማክበር የሚታወቀው ኤልቤት ሆቴል የ2006 ዓ.ም መጀመርያ ዐውደዓመትን ዋዜማ በባሕላዊ ይዘት እንደሚያከብር አስታወቀ፡፡ ከቀኑ 11 ሰዓት በመጀመር በሚቀርበው ዝግጅት ወጣቶች የባህል ልብስ ለብሰው “አበባየሆሽ” ብለው የሚዘፍኑበት ሲሆን የዘመን አቆጣጠርን አስመልክቶ ማብራሪያ በባለሙያ ይሰጣል፡፡ በዝግጅቱ የባሕል ዘፈኖች፣ ግጥሞችና መጣጥፍ እንደሚቀርቡና የችቦ ማብራት ሥነ ሥርአትም እንደሚኖር ይጠበቃል።

በደራሲ አለማየሁ ገላጋይ የተጻፈው ‘የብርሃን ፈለጎች’ የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ ባለፈው ሰኞ ለንባብ በቃ፡፡ ከዚህ በፊት አጥቢያ፣ ቅበላ፣ ስብሃት ገብረ እግዚያብሄር - ህይወትና ክህሎት፣ ኩርቢት፣ የፍልስፍና አጽናፍና ኢህአዴግን እከስሳለሁ የተሰኙ መጽሃፍትን ለአንባብያን ያቀረበው ደራሲው፣ በቅርቡ ለንባብ የበቃውንና በደራሲ ስብሃት ገብረ እግዚያብሄር ዙሪያ የሚያጠነጥነውን ‘መልከዓ ስብሃት’ የተሰኘ መጽሃፍም በአርታኢነት አዘጋጅቷል፡፡
248 ገጾች ያሉትና ለደራሲው ስምንተኛ ስራው የሆነው የብርሃን ፈለጎች የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ፣ በተለያዩ የመጽሃፍት መደብሮችና በአዟሪዎች በ45 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
ደራሲ አለማየሁ ገላጋይ በአዲስ አድማስና በሌሎች ጋዜጦች እንዲሁም መጽሄቶች ላይ ለረጅም አመታት የተለያዩ ስነጽሁፋዊ፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጽሁፎችን በማቅረብ ይታወቃል፡፡

በ40 ዎቹ መጨረሻ ዕድሜዋ ላይ የምትገኘው አንጋፋዋ ድምፃዊ ሐመልማል አባተ፤ ሰሞኑን ዘጠነኛ አልበሟን ለጆሮ አብቅታለች፡፡ በአዲሱ አልበሟ ምን አዲስ ነገር ይዛ መጣች? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው ከሐመልማል አባተ ጋር ተከታዩን ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡

ብዙ ጊዜ አልበም የምታወጪው የበአላት ሰሞን ነው፡፡ ይሄ በአጋጣሚ ነው ወይስ ሆን ብለሽ?
አጋጣሚ ነው፡፡ ከዚህ በፊት “አውደ አመት” የሚል ካሴት ለአዲስ አመት አውጥቼ ነበር፡፡ ከዛ በኋላ ሠው ሁልጊዜ ለአዲስ አመት ካሴት የማወጣ ይመስለዋል፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ የአሁኑም አልበሜ ሄዶ ሄዶ አዲስ አመት ጋ ደረሠ፡፡ በዚህ ደሞ ደስተኛ ነኝ፡፡
ከኮፒ ራይት ጥሰት ጋር በተገናኘ በቀዳሚነት “ካሴት አላወጣም” ያልሽው አንቺ ነሽ፡፡ ውሳኔሽ አልጐዳሽም?
እርግጥ አንድ ነገር ስትፈልጊ አንድ ነገር ታጫለሽ፡፡ በፊት የሚሠራው ከቨር ነበር፤ ከቨር ይሠራና ይላካል፡፡ በዚህ ጊዜ ሁሉም ሰው አንድ አይነት ጥራት ያለው ስራ አያገኝም፡፡ ምክንያቱም ሁሉም በራሱ ቴፕ ነበር የሚቀዳው፡፡ አንዳንዴ ክፍለ ሀገር ሔጄ የተቀዳውን ድምፄን ስሠማው፣ የህፃን ልጅ ድምፅ የሚመስልበት ጊዜ አለ፡፡ አንዳንድ ቦታ ደግሞ የወንድ ድምፅ ይመስላል፡፡ ያኔ ነው ውሳኔ ላይ የደረስኩት። “ከቨር የሚባል ነገር አይታተምም፤ ካሴቱ በፋብሪካ ነው የሚታተመው” ብዬ ወሠንኩ። ምክንያቱም ሠው የሚከፍለው ገንዘብ እኩል ነው፤ ግን የተለያየ ጥራት ነው የሚያገኘው። አሁን ካሴቱን እራሱ በፋብሪካ አሳትሜ ሁሉም ሠው አንድ አይነት ጥራት ያለው ሥራ እንዲያገኝ እየጣርኩ ነው። ለእኔ ምናልባት ሊጐዳኝ ይችላል፡፡ ቢሆንም ይሔንን ማድረግ የግድ ነው፡፡ በኮፒ ራይት ጥሰት ዙሪያ መንግስት መፍትሔ እንዲሰጠን ብዙ ጊዜ ጠይቀናል፡፡ ለረጅም ጊዜ ጠብቀናል፡፡ ህጉ ተፈፃሚ መሆን ነበረበት፡፡ ነገር ግን የኮፒራይት ጥሰት ፈጽመው የምናሳስራቸው ሠዎች ቶሎ ይፈታሉ፡፡ ይሄ ተገቢ አይደለም፡፡ አሁን ትንሽ ለውጥ እየታየ ነው፡፡ የሚመለከተው ወገን ለጉዳዩ ትኩረት ቢሠጠው እኮ አርቲስቱ ብቻ ሳይሆን ሁሉም ተጠቃሚ ነው፡፡ እኛ ሀብታም ስንሆን መንግስትም ሀብታም ይሆናል፡፡ እና አሁንም ተስፋ አንቆርጥም፡፡
የአሁን ዘመን ድምፃውያን በቴክኖሎጂ ይታገዛሉ። ይሄ ነገር ጥቅሙ ነው ጉዳቱ የሚያመዝነው?
ቴክኖሎጂ ጥቅም እንዳለው ሁሉ ጉዳትም አለው፡፡ የድሮ አሠራር አድካሚ ቢሆንም ደስ ይላል፡፡ ሁሉም ሙዚቀኛ እኩል አጥንቶ፣ እኩል ሠርቶ ቀጥታ ነበር የሚቀዳው፡፡ አንድ ዘፈን ሰርተን ሰርተን ሊያልቅ ሲል ከተሳሳትን፣ እንደገና ሀ ብለን ነበር የምንጀምረው፡፡ ግን ቀጥታ እየሠሙ መቀዳት በጣም ደስ የሚል ነገር አለው። አሁን ደግሞ ቴክኖሎጂው በጣም አግዞናል፡፡ ብሳሳት እዛችው የተሳሳትኩበት ቦታ ብቻ ነው የምንቀዳው። ግን ኦሪጅናሉን የድምፅ ቅላፄ እየወሠደው ነው። እርግጥ እንደ ድምፃዊው ችሎታ ይለያያል፡፡ ለምሳሌ ቴክኖሎጂ እንዳለ ሆኖ በጥንቃቄና በጥራት መስራት ይቻላል፡፡ ይሄ ግን በባለሙያው ብቃት ይወሰናል፡፡ አንዳንዴ የሚዘገንን ነገር እሠማለሁ፡፡ አንዴ ሰምተሽው ሆ ብሎ የሚጠፋ ነገር ይሆናል፡፡ እናም ቴክኖሎጂ ጥቅምም ጉዳትም አለው፡፡
በኮምፒውተር ታግዘው አልበም የሚያወጡ አርቲስቶች በተለይ መድረክ ላይ ያንኑ ድምጽ ለማውጣት ሲቸገሩ ይታያል…
ልክ ነው፤ ድምፅ ላይ በጣም ችግር ያመጣል። ለዚህ ነው በተፈጥሮ ድምፅ መቀዳት ያለብን። አንድ ዘፋኝ ያልሆነ ሠው የድምፅ ልምምድ በማድረግ ዘፋኝ መሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን በእነዚህ የኮምፒውተር ሲስተሞች ታግዞ ከሰራ እንደምናየው ነው፤ መድረክ ላይ ያስቸግራል፡፡
አልበም በማውጣት ረገድ ከአሁኑኑ ከድሮው አሰራር የትኛው ቀና ነው? ለአርቲስቱ ማለቴ ነው…
የመጀመሪያ ካሴቴ የወጣ ጊዜ እኮ እንደ አሜሪካ ሰለብሪቲ ነበር የምንሠራው፡፡ ሁሉም ነገር በአሳታሚው በኩል ነው የሚያልቅልሽ። አሁን ግን በኮፒራይት ጥሰት የተነሳ ነጋዴው ከስራው ወጥቷል፡፡ ያሉትም ቢሆኑም በጣም እየከበዳቸው ነው፡፡ ብዙ ብር ካወጡ በኋላ ስራው ኮፒ ስለሚሆን አይደፍሩትም፡፡ አሁን ትንሽ ለውጥ አለ፡፡ በ2006 ደግሞ የተሻለ ለውጥ ይመጣል ብዬ አስባለሁ፡፡ እስከዛው ግን በግላችን እየሞከርን ነው። አልበም ሲሰራ ብዙ ወጪዎች አሉ፡፡ አልበሙን ካስደመጥን በኋላ ከኮንሠርት እናገኛለን በሚል ነው የምንሰራው፡፡
እስቲ ስለአዲሱ አልበምሽ ንገሪኝ…ወጪውን፣ አሳታሚውንና ስለ ስራዎችሽ ይዘት…
አልበሜ መጠሪያው “ያደላል” የሚል ነው። ስያሜው ብዙ ትርጉም አለው፡፡ አርቲስቱን ቤቱ ቁጭ ብሎ የሚዘርፈውን የሚመለከት ሊሆን ይችላል፡፡ ሰሙ ደግሞ እግዚአብሔር በአምሳሉ ሲፈጥረን ለሠው አድልቷል የሚል ነው፡፡ ወርቁን እንደተፈለገ መተርጐም ይቻላል። በዚህ አልበም ሳይካተቱ የቀሩ ብዙ ትላልቅ ስራዎች አሉ፡፡ ሁሉም ነገር ሊወጣ ስለማይችል ያልተሠሩት ከተሠሩት በላይ አሉ። ለአዲሱ አልበሜ ብዙ ወጪ ነው ያወጣሁት፡፡ በዚህ አጋጣሚ መግለጽ የምፈልገው ካሴቱ ላይ ከተለመደው ውጭ ብዙ ስራዎች መካተታቸውን ነው፡፡ ሌላ ጊዜ የተለመደው ሲዲ ላይ ነበር፡፡ አሁን ግን ካሴቱን “C80” አድርጌ 16 ዘፈኖች ተካተውበታል፡፡ ሲዲው ላይ 14 ዘፈኖች አሉ፡፡ አሁን በአሜሪካ ካሴት ፋሽን ሆኗል፡፡ የእኛ አገር ሲዲ ጥራቱ ብዙም አይደለም፡፡ ስለዚህ ካሴቱን ተመራጭ አድርጌያለሁ፡፡ ሙዚቃውን ሙሉ በሙሉ ያቀናበረው አበጋዝ ነው፡፡ በግጥምና በዜማ አዳዲስ ደራሲዎችን አሳትፌያለሁ:- ምስክር አወል፣ ማስረሻ ተፈራ፣ የእኔው አካሉ፣ ፀጋዬ ስሜ (ጥሩ ጉራጊኛ ሠጥቶኛል) የሸዋ ኦሮሞ ባህላዊ ዘፈንም ሠርቼአለሁ። እስከዛሬ የሀረር ኦሮሞን ባህላዊ ዜማዎች ነበር የምሰራው፡፡ አሳታሚዋ እኔ ነኝ፡፡ ለዚህ ስራ ከ500ሺ ብር በላይ ወጪ አድርጌአለሁ። አከፋፋዩ ደግሞ ትልቅ ስም ያለው ሮማርዮ ሪከርድስ ነው። በጣም ቆንጆ ስራ ነው። አንድን ስራ እኔ ካላመንኩበት አላወጣውም፡፡ ያለዚያ እኮ በየአመቱ ካሴት አወጣ ነበር፡፡
ጳጉሜ 5 ለአዲስ ዓመት ዋዜማ በሚሊኒየም አዳራሽ ትዘፍኛለሽ፡፡ ዝግጅት ምን ይመስላል?
የምንችለውን ያህል እያደረግን ነው። ከአዳዲሶቹ ዘፈኖችም የተወሰኑትን እጫወታለሁ። በአዲስ አመት ያልተደሠተ ሰው አመቱን ሙሉ አይደሠትም ይባላል፡፡
በ2005 ዓ.ም በአገር ደረጃ ምን ለውጥ አስተውለሻል?
ሁሌም መጥፎ ጐን ብቻ ማውራት ጥሩ አይደለም፤ በጐ ጐንም መወራት አለበት። ለምሳሌ ከአሠራር ለውጥ ብንነሳ፣ የውልና ማስረጃ ቢሮ ትልቅ አርአያ ነው፡፡ ልክ እንደ ውጪ አገር ቁጥር እየሰጠ ነው የሚያስተናግደው፡፡ ያለ ወረፋው የሚገባ የለም፡፡ በዚህ ረገድ አቶ ይርጋን በጣም ማመስገን ነው የምፈልገው፡፡ ምክንያቱም ሌላ ቦታ እኛ ቁጭ ብለን ስንጠብቅ፣ ነጮች በቅድምያ ሲስተናገዱ ነው የምናየው። ቅር ያለኝ የቦሌ መንገድ ነው፡፡ እርግጥ ነው የቦሌ መንገድ በጣም አምሮበታል ፤ ነገር ግን ባለ ህንፃዎቹ ፓርኪንግ አለመስራታቸው እንዳለ ሆነ የፓርኪንግ ችግር ተፈጥሯል፡፡ እዚያ አካባቢ መኪና አቁሞ እቃ መግዛት አልተቻለም። ድሮ ቦሌ የሚታወቀው ካፌዎቹ በረንዳ ላይ ሠዎች ቁጭ ብለው ሲዝናኑ ነበር፡፡ አሁን ከሠኞ እስከ አርብ ጭር ብሎ ነው የሚውለው፡፡ ሌላው የመንገዶቹ አሠራሮችና የመብራት ሁኔታ አካል ጉዳተኛን ያማከለ አይደለም፡፡ እነሱም ዜጐች ናቸው፡፡ ይሄን ጉዳይ በተመለከተ ሁለት ቀን በግሌ መንገድ ትራንስፖርት ሄጄ ነበር፡፡ ግን የማናግረው ሰው ማግኘት አልቻልኩም፤ ስብሠባ ናቸው በሚል ምክንያት፡፡ በኪነጥበብ ዘርፍ ግን ምንም ለውጥ የለም፤ አርቲስቱ እየደከመ ነው ያለው፡፡ እኔ ውጪ ሀገር ሠርቼ የመጣሁትን ነው እየበላሁ ያለሁት እንጂ፤ ኪነ ጥበብ ቀዝቅዟል፡፡
በትርፍ ጊዜሽ ምን ትሰርያለሽ?
የቤት ስራ ያስደስተኛል፤ አበስላለሁ። አትክልቶችን እንከባከባለሁ፡፡ የሁለት ልጆች እናት ነኝ፡፡ ትልቋ ልጄ ማክዳ ትባላለች። በዚህ አመት ከአሜሪካ፣ ፖኖን ዩኒቨርስቲ ትመረቃለች፡፡ አሜሪካን አገር ጐበዝ ተማሪዎችን ለማበረታታት የምርቃት ሰርተፍኬታቸውን ፕሬዚዳንቱ ናቸው የሚሰጡት - በኋይት ሀውስ፡፡ የእኔም ልጅ ከክሊንተን፣ ከቡሽ እና ከኦባማ እጅ ወስዳለች። ይሔ ደስ ይላል፡፡ አሁን በአንትሮፖሎጂ ትመረቃለች፡፡ ከዚያ ወደ አገሯ መጥታ የመስራት ፍላጐት አላት፡፡
ሀመልማል ትዳር ትፈራለች እንዴ?
ምን ያስፈራል? እግዚአብሔር ላለለት ሠው በጣም ይመከራል፡፡ ከመጣ ደግሞ ሠርግ መደገስ ይቻላል፡፡ ልጆቼም አንዳንዴ ያሾፉብኛል፤ “እኛ ሚዜ እንሆናለን፤ አንቺ ደግሺ፤ ግን ባል የለም” ይሉኛል፡፡ አሁንም ከመጣ እሰየው ነው፡፡
ምን ዓይነት ሙዚቃዎችን ማድመጥ ትወጃለሽ?
ማናቸውንም የትዝታ ዘፈኖች አደምጣለሁ። ከበፊቶቹ ሙሉቀን ለእኔ ልዩ ነው፤ ከወጣት የጐሳዬን ዘፈኖች እወዳለሁ፡፡ ሁሉም ግን የራሱ የሆነ ጣዕም አለው፡፡
በ2005 ዓ.ም ያስደሰቱሽንና ያስከፉሽን ጉዳዮች ጥቀሺልኝ…
የጥበብ አጋራችን የነበረውን ድምፃዊ እዮብን ማጣታችን አሳዝኖኛል፡፡ የእዮብን መልካምነት ለማወቅ የቀብር ስነስርዓቱን መመልከት በቂ ነው፡፡ እንደ አንጋፋዎቹ ነው በበርካታ ህዝብ የተሸኘው፡፡ ሌላው በመብራት ሃይል ችግር ቤቴ ተቃጥሎ ነበር። ምንም እንኳን ራሱ መብራት ኃይል ቢሠራውም። እንደዚህ አይነት ስህተት እንዳይከሠት መብራት ሀይል ጥንቃቄ ማድረግ አለበት፡፡ ካሴቴ አልቆ ለ2006 አዲስ ዓመት መድረሱ ደግሞ በዓመቱ ካስደሰቱኝ ነገሮች ዋነኛው ነው፡፡
ሞሃ ለስላሳ እንዴት 500ሺህ ብር ስፖንሰር አደረገሽ?
ይሄ ገና ያልተሰራና ያልተጣራ ነገር ነው፤ ስለዚህ በዚህ ጉዳይ ላይ ምንም መናገር አልፈልግም፡፡
ቀጣይ ዕቅድሽ ምንድነው?
በሙዚቃው መገስገስ ነው የምፈልገው፤ከራሴ ስራ አልፌ የሌሎችን ፕሮዲዩስ ማድረግ እፈልጋለሁ። አመል ፕሮዳክሽን የተባለ ድርጅት አቋቁሜያለሁ፤ በዛ በኩል የሌሎችን ስራዎች ለማሳተም እቅድ አለኝ።
ለዋዜማ ኮንሰርት ምን ያህል ተከፈለሽ?
ይሄ የግል ጉዳይ ነው፤ መናገር ይከብዳል፤ ምክንያቱም እኔ እንደሌሎች ያልተከፈለኝን ተከፈለኝ ብዬ አጋንኜ ማውራት አልፈልግም፡፡ ከአዘጋጆቹም ጋር ጉዳዩ በግል እንዲያዝ ተነጋግረናል፡፡ ስለዚህ መናገሩ አስፈላጊ አይደለም፡፡

“...እስከአሁን የማልረሳው አንድ አጋጣሚ አለኝ፡፡ አንዲት እናት በቤትዋ ሳለች ምጥ ጀምሮአታል፡፡ ከዚያም ይበልጥ ስትታመምባቸው እኔ ወዳለሁበት በሲዳማ ዞን ቦና ዙሪያ ወረዳ ባለው የጤና ጣቢያ ያመጡአታል፡፡ እኔም ስመለከታት የማህጸን መተርተር ደርሶባታል፡፡ አጋጥሞኝ ስለማያውቅ እጅግ በጣም ነበር የደነገጥኩት፡፡ በእርግጥ በኦፕራሲዮን ማህጸንዋ ይወጣል። ነገር ግን እሱም እርምጃ ቢወሰድ እና ሕይወቷ ቢተርፍ ማህጸንዋ ሲወጣ ወደፊት ልጅ መውለድ ስለማትችል ባለችበት ሕብረተሰብ አስተሳሰብ የምትገለል ትሆናለች፡፡ ምክንያቱም ልጅ ለወደፊቱ መውለድ ስለማትችል የነበራት ባልም ይፈታታል... ሌላ ባልም አያገባትም፡፡ በህብረተሰቡም ዘንድ ተቀባይነት ስለማይኖራት ዝም ብላ የምትኖር ትሆናለች፡፡ይሄንን ነገር ዛሬ ላይ ሳስበው ይቆጨኛል፡፡ ምክንያቱም እንደአሁኑ እውቀቱ ቢኖረኝ ኖሮ ወደከፍተኛ ሕክምና ጊዜ ሳልፈጅ አስተላልፌ በሴትየዋ ላይ የደረሰው ችግር ሊቃለል ይችል ነበር…”
ከላይ ያነበባችሁት ገጠመኝ ከአንድ የጤና መኮንን የቀረበ ነው፡፡ የጤና መኮንኑን ያገኘነው በሐዋሳ በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር እና በዞኑ የጤና መምሪያ እንዲሁም በፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ትብብር WATCH (women & their child health) የእናቶችና ሕጻናት ጤናን ለማሻሻል በተነደፈው ፕሮጀክት ድጋፍ ስልጠና ሲወስድ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር WATCH (women & their child health) የተሰኘው ፕሮጀክት አስተባባሪ የሆኑት አቶ ቢንያም ጌታቸው እንደሚገልጹት ድጋፍ የሚገኘው ከካናዳ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ሲሆን በዋናነት የሚሰራውም የእናቶችን እና ሕጻናትን ሞት መቀነስ ነው፡፡ ስለዚህም ከዚህ ማህበር ጋር በመተባበር የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር Basic emergency obstetric & new born care (መሰረታዊ የሆነ አጣዳፊ የእናቶችና የህጸናትን ሞት መቀነስ) የሚባለውን የስራ እንቅስቃሴ ስልጠና እና ለጤና ጣቢያዎች የአቅም ድጋፍ የማድረግ ስራ እየሰራ ይገኛል፡፡ የWATCH ፕሮጀክት በኢትዮጵያ ውስጥ በሶስት ክልል ውስጥ በሚገኙ 8/ ስምንት ወረዳዎች ተግባሩን እያከናወነ ሲሆን ይኼውም በደቡብ ሲዳማ ዞን፣ በኦሮሚያ ጅማ ዞን፣ በአማራ ክልል በሰሜን ወሎ ዞን ነው፡፡
በካናዳ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አማካኝነት በተዘረጋው በዚህ ፕሮጀክት ከውጭ በመጡ ባለሙያዎች የኢትዮያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አባል ለሆኑ ከፍተኛ ሐኪሞች ስልጠና ተሰጥቶ የነበረ ሲሆን እነዚህ የሰለጠኑ ባለሙያዎችም ከተለያዩ ወረዳዎች ለመጡ የጤና ባለሙያዎች መሰረታዊ የሆነ አጣዳፊ የእናቶችና የህጸናትን ሞት በመቀነስ ረገድ ክህሎትን እያስጨበጡ ይገኛሉ ብለዋል የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ ቢንያም ጌታቸው፡፡
በማሰልጠን ተግባር ላይ ከተሰማሩት የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት ዶ/ር ይፍሩ ብርሀን እንደሚሉት ለእናቶች ሞት ምንክያት የሚሆኑት ነገሮች በሶስት ወይንም በአራት ሊከፈሉ ይችላሉ፡፡
1/ እናቶችና ቤተሰቦቻቸው የጤና አገልግሎት ለማግኘት አለመፈለግ፣
እነዚህ እናቶች የጤና ችግር ሲያጋጥማቸው በአካባቢው አዋላጅ ነርሶች አማካኝነት ለመውለድ መዘጋጀት ወይንም ምንም ክትትል አለማድረግ እንዲሁም የጤና ችግር ሲገጥማቸው በአፋጣኝ ወደ ጤና ተቋም ወይንም ሆስፒታል አለመምጣት ነው፡፡
2/ በሚኖሩበት አካባቢ የህክምና አገልግሎት የሚሰጥ ተቋም አለመኖር ፣
3/ ወደጤና ተቋም ከመጡ በሁዋላ የጤና ባለሙያው የደረሰባቸውን ችግር ለይቶ አለማወቅ፣...ይህ በአሁኑ ወቅት እንደከፍተኛ ችግር የሚቆጠር ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ የሚያሳየው የእውቀት ችግር መኖሩን ሲሆን በዚህም ምክንያት ለእናቶቹ በጊዜው አስፈላጊው ሕክምና የማይሰጥ እና ወደከፍተኛ ሕክምና እንዲተላለፉ አለመደረጉን ነው፡፡ አንዳዶች ሕመም ሲጠናባቸው ወደአቅራቢያው ጤና ተቋም ሲሄዱ በዚያ በሚፈጠረው አላስፈላጊ መዘግየት ምክንያት ሕይወታቸው ከአደጋ ላይ ይወድቃል፡፡ አልፎ አልፎም አግባብ ያልሆነ ሕክምና የሚሰጥበት አጋጣሚ ስለሚኖር ይህንን ክፍተት የሚሞላ አሰራር መኖር አለበት፡፡ ስለዚህም እስከአሁን ባየነው የስልጠና ሂደት ሰልጣኞቹ ሲመጡ የነበራቸው የእውቀት ደረጃ እና ሲጨርሱ የሚኖራቸው ደረጃ በጣም ይለያያል ብለዋል ዶ/ር ይፍሩ ብርሀን፡፡
ሌላው አሰልጣኝ ዶ/ር እንዳለ ሲሳይ ይባላሉ፡፡ ዶ/ር እንዳለ በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ የማህ ጸንና ጽንስ ሐኪምና አስተማሪ ናቸው።
“...ይህ ሆስፒታል ሪፈራል ሆስፒታል ስለሆነ ከሌሎች የህክምና ተቋማት የተላኩ ታካሚ እናቶችን ያስተናግዳል፡፡ ነገር ግን በአብዛኛው የሚመጡ እናቶችን ለማዳን በጣም ፈታኝ የሚሆን ሲሆን ይህም ወደሆስፒታሉ የሚልኩ የጤና ተቋማት ጊዜን በአግ ባቡ አለመ ጠቀማቸው ነው፡፡ ለባለሙያዎቹ ስልጠና የሚሰጠው በሚሰሩበት ጤና ተቋማት ባላቸው አቅም ሊያክሙ የሚችሉትን እንዲያክሙና ከአቅማቸው በላይ የሆነውን ግን ጊዜ ሳይ ፈጁ ወደከፍተኛ ሕክምና እንዲልኩ የሚያስችል ነው። ምን አይነቱ የጤና ችግር በጤና ጣቢያ ሊታከም ይችላል? የሚለውን የመለየትና አቅምን የማወቅ ክህሎት አብሮ በስል ጠናው ይሰጣል፡፡ በእርግጥ ስልጠናው አዲስ እውቀትን ከመስጠት የሚጀምር ሳይሆን የነበራቸውን እውቀት እንዴት በስራ ላይ እንደሚያውሉት አቅጣጫ የሚያሳይ ነው፡፡ ነገር ግን ሰልጣኞች አንዳንድ ጊዜ በሚሰጣቸው የልምምድ ተግባር አድናቆት ሲያሳዩ ይታያሉ፡፡ ምክንያቱም በተግባር እንዴት እንደሚፈጽሙት አያውቁምና ነው፡፡ አንዲት እናት እነርሱ ወዳሉበት ጤና ተቋም ስትመጣ በምን መንገድ እንደሚረዱዋት ወይንም በፍጥነት ወደከፍተኛ ህክምና ተቋም እንደሚልኩዋት ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ያለውን አሰራር በሚያዩበት ጊዜ እንደ አዲስ ትምህርቱን ሲቀበሉ ይታ ያሉ፡፡ ይህ ማለት ቀደም ብሎ የነበራቸው ልምድ ምን ያህል እንደነበርና አሁን ምን ያህል እውቀት እንዳገኙ የሚያሳይ ስለሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ክፍተት እንደነበረ የሚያ ረጋግጥ ነው፡፡ ልምምድ የሚያደርጉት በሞዴልነት በተሰሩ የሰውነት ክፍሎች ሲሆን ወደሰው ከመቅረባቸው በፊት ተገቢውን ያህል ስራ እንዲሰሩ ይደረጋል። ከዚያም ወደሆ ስፒታሉ በመግባት ከባለሙያዎች ጋር በመሆን ሰዎችን እንዲረዱ ይደረጋል፡፡ በዚ ህም ከቀን ወደቀን የመስራት ፍላጎትና ብቃታቸው እያደገ ሲሄድ ይስተዋላል፡፡ ስለ ዚህ ስል ጠናው የብዙ እናቶችና ሕጻናት ሕይወት እንዲተርፍ ያስችላል የሚል እምነት አለ ብለዋል ዶ/ር እንዳለ ሲሳይ፡፡
ከሲዳማ ዞን ሸበዲኖ ወረዳ የመጣ ክሊኒካል ነርስ ቀደም ሲል በስራው አለም የገጠ መውን ሲያስታውስ፡-
“...እኔ በምሰራበት ጤና ተቋም አንዲት እርጉዝ ሴት ከእግር እስከራስዋ እየተንቀጠቀጠች እራስዋን ስታ በሰዎች ሸክም ትመጣለች፡፡ እርግዝናው ቀኑን የገፋ ነው፡፡ አብረዋት የመጡ ቤተሰቦችዋ እርስ በእርስ አልተስማሙም፡፡ ገሚሱ የቤት ጣጣ ነው ይላል፡፡ ገሚሱ ደግሞ ለጸበሉ ይደረስበታል መጀመሪያ ሐኪም ይያት ይላል፡፡ እኔ ግን እንደዚያ አይነት ነገር አይቼ ስለማላውቅ ግራ ገባኝ፡፡ ነገር ግን ለማንኛውም ብዬ... ግፊትዋን ስለካ ደምዋ በጣም ከፍ ብሎአል፡፡ በጊዜው ለእሱ የሚሆን መድሀኒትም አልነ በረኝም፡፡ ጊዜ ወስጄ...ያለውን ነገር ፈላልጌ እንደምንም ሰጥቼ በስተመጨረሻው እጄ ላይ ሳትሞትብኝ ወደሆስፒታል ይዘው እንዲሄዱ አደረግሁኝ፡፡ ነገር ግን ሆስፒታል ስትደርስ ሁኔታው እጅግ አስቸጋሪ እንደነበር አውቄአለሁ፡፡ አሁን እንደተማርኩት ቢሆን ኖሮ ...ሁኔታው ከእኔ አቅም በላይ ስለሆነ ምንም ጊዜ ሳልፈጅ በአስቸኳይ ወደከፍተኛ ሕክምና እልካት ነበር፡፡ ወደፊት ግን በሰለጠንኩት መሰረት የምችለውን ሕክምና እሰጣለሁ...እኔ የማልችለውን ግን አላስፈላጊ መዘግየትን አስወግጄ ቶሎ ወደ ከፍተኛ ሕክምና እልካለሁ...” ብሎአል፡፡
ደቡበ ሲዳማ ዞን ሐዋሳ ውስጥ ስልጠና ሲወስዱ ከነበሩት መካከል አቶ ሳምሶን ሰንበቶ ከቦና ዙሪያ ወረዳ እንደገለጸው የእናቶችን ጤንነት በተመለከተ በሐዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል እየ ሰለጠኑም ተግባሩንም ከቀደምት ሐኪሞች ጋር በመሆን በመስራት ተገቢውን ልምምድ እያደረጉ ነው፡፡ በተለይም የእናቶችንና የህጸናትን ጤንነት በተመለከተ የተሰጠው ስልጠና መሰረታዊና ህብረተሰቡንም ለማገልገል የሚያስችል ነው እንደ አቶ ሳምሶን ሰንበቶ አስተያየት፡፡ እኔ ባለሁበት አካባቢ እናቶችም ሆኑ ጨቅላ ሕጻናቶች ብዙውን ጊዜ የሚሞቱት ከወሊድ ጋር በተያያዘ ሲሆን በዚህ ምክንያት የሚፈጠረውን ክፍተት ለመዝጋት ሙሉ በሙሉ ባይሆንም በተቻለ መጠን የሚያግዝ እውቀትን ጨብጠናል ብዬ አምናለሁ ብሎአል አቶ ሳምሶን ሰንበቶ፡፡
የWATCH ፕሮጀክትን ተግባራዊ በማድረግ ረገድ ከESOG ጋር በትብብር የሚሰራው የፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ የደቡብ ማስተባበሪያ ጽ/ቤት የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ገዳምነሽ ደስታ ትባላለች፡፡ ፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ከፕላን ካናዳ እና ከሲዳ ያገኘውን ብር Berehan integrated community development organization በመስጠት ይህ ፕሮጀክት በተያዘለት አላማ መሰረት በሲዳማ ዞን በሶስት ወረዳ ላይ በትክክል በመሰራት ላይ መሆኑን ይቆጣጠራል፡፡ የኢትዮያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበርም ቴክኒካል አማካሪ በመሆን በሶስቱ ወረዳዎች ለሚገኙ እና በዞኑ የጤና መምሪያ ክትትል ምርጫው ተካሂዶ ሰልጣኞች ሲላኩ የስልጠናውን ሂደት በማከናወን የድርሻውን ይወጣል፡፡ በተጨማሪም ሰልጣኞቹ ወደሚሰሩበት ጤና ጣቢያ በሚመለሱበት ጊዜ ስራ ላይ የሚያውሉትን የህክምና መገልገያ መሳሪያና መድሀኒትን ግዢ በሚመለከትም ESOG ያማክራል፡፡ ስለዚህም ፕሮጀክቱ በአሁኑ ወቅት የሚሰራው ሁለት ነገር ላይ ሲሆን አንደኛው አቅም ማጎልበት እንዲሁም ሌላው ደግሞ በመንግስት ተዘርግቶ ባለው የጤና ስርአት ውስጥ ያሉ ክፍተቶችን ማሟላት ነው። ስለዚህም እናቶችና ሕጻናት የሚገጥ ማቸውን የጤና ችግር ለማቃለል በትብብር መሰረታዊ ስራ እየተሰራ ያለበት ደረጃ ላይ ነን ብለዋል ከፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ገዳምነሽ ደስታ፡፡
ይቀጥላል