Administrator

Administrator

ተወዳጅነትን ያተረፈው “ግጥም በጃዝ” ፕሮግራም 22ኛ ዝግጅቱን የፊታችን ሪቡዕ ምሽት በራስ ሆቴል እንደሚያቀርብ አዘጋጆቸ አስታወቁ፡፡ አንጋፋው አርቲስት ተፈሪ ዓለሙን ጨምሮ አንዱዓለም ተስፋዬ፣ ምንተስኖት ማሞ፣ ደምሰው መርሻና ይሄነው ቸርነት የግጥም ሥራቸውን ሲያቀርቡ ሀብታሙ ስዩም ወግ ያቀርባል ተብሏል፡፡ በኃይሉ ገ/መድህን በበኩሉ ዲስኩር እንደሚደሰኩር ታውቋል፡፡

መጋቢት 29 ቀን 2005 ዓ.ም ማለዳ እንግዶች ለመቀበል ቦሌ አለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ ነበርኩ፡፡ ግልፅ ባልሆነ ምክንያት እንግዶችን የሚቀበሉም ሆነ የሚሸኙ ሰዎች የሚገቡበት በር አልተከፈተም ነበርና ውጭ ለመቆም ተገደድኩ፡፡ ብዙ አውሮፕላኖች ስለአረፉ ተጓዦች፣ ሆስተሶችና ፓይለቶች ወደ ውጭ ይጎርፋሉ፡፡ ሆስተሶቹና አንዳንድ ፓይለቶች ቆመው ወደቤታቸው የሚወስዳቸውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ መኪና ይጠባበቃሉ፡፡ የሚጠብቁት መኪና ማቆሚያ ቦታ ላይ ሆነው ነው፡፡ ምንም መቀመጫ ስላልነበረም አንዳንዶቹ ሆስተሶች ሻንጣቸው ላይ ተቀምጠው አየሁ፡፡ ነገሩን ለመቀበል ስላዳገተኝ በሞባይሌ ጥቂት ፎቶዎች አነሳሁ፡፡

እነዚህ ሆስተሶች እዚህ የደረሱት ቢያንስ ከአራት ሰአት በረራ በኋላ ነው፡፡ ከዚያ በፊትም ዝግጅት ማድረግ ስለሚኖርባቸው ሌሊቱን ሳይተኙ ነው የመጡት ማለት ነው፡፡ በበረራው ጊዜም አንድ አውሮፕላን ህዝብ ሲንከባከቡ እንዳደሩ ግልጽ ነው፡፡ እንደኔ ግምት እነዚህ ሰዎች በዚያ ጠዋት የሚመኙት ዋና ነገር ቢኖር ወደቤታቸው ቶሎ ሄደው መተኛት ነው፡፡ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቢቻል እንደመጡ የሚወስዳቸው መኪና፣ባይቻል ደግሞ ከነክብራቸው የሚቆዩበት ማረፊያ ቦታ ማዘጋጀት ለምን ተሳነው? ነገሩን መቀበል ያቃተኝ እኔ ብቻ አልነበርኩም፡፡ አንድ ከፊቴ የቆመ ሰው “እስቲ አሁን ዝናብ ቢኖር እንዴት ነው እዚህ ሆነው የሚጠበቁት?” አለ፡፡

ሌላው ያስገረመኝ ነገር ደግሞ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሆስተሶቹንና ፓይለቶቹን ለማጓጓዝ የሚጠቀምበት ብዙ ዓመታት ያገለገሉ መኪኖችን ነው፡፡ እቃ መጫኛ ስለሌለው ሻንጣም ሰውም አብሮ ነው የሚጫነው፡፡ አንድ ከሻንጣ ጋር የተጫነ ፓይለት እያየሁ እንዲህ ስል አሰብኩ “በመቶዎች የሚቆጠር ሰዎችን በጥንቃቄ ሲያበር ያደረን ሰው እንዲህ መጫን ምን ይባላል?” ስንት ከባድ ነገሮችን አቅዶ ለሚያሳካው አየር መንገድ ምክር ካስፈለገው ከኋላቸው የሚከፈቱ ሚኒባሶች ቢኖሩት ሰዎቹ ከፊት ከነክብራቸው ሲቀመጡ፣ ሻንጣዎች ከኋላ እንዲሆኑ ማድረግ ይቻል ይሆናል፡፡ አየር መንገዱን የላቀ አየር መንገድ ለማድረግ፣ለሠራተኞቹ አያያዝ ትኩረት መስጠት እንደሚገባው ባስታውሰው ከአጉል ድፍረት እንደማይቆጠርብኝ በመተማመን ነው፡፡

የዛሬ አስር ዓመት የአስራ ሰባተኛ ዓመት የልደት በአሏን ለማክበር አንድ ቀን ሲቀራት ለስራ እንደወጣች አልተመለሰችም- አሜሪካዊቷ አማንዳ ቤሪ፡፡ ደብዛዋ ከመጥፋቱ በፊት ግን እህቷ ጋ ደውላ ከምትሰራበት ቦታ ወደ ቤት የሚመልሳት መኪና እንዳገኘች ተናግራ ነበር፡፡ የ14 ዓመቷ ጂና ደግሞ የዛሬ ዘጠኝ ዓመት ትምህርትቤት እንደሄደች አልተመለሰችም፡፡ ናይት ከሁለቱ ቀደም ብላ በ2002 ዓ.ም ደብዛዋ የጠፋ የ20 አመት ወጣት ነበረች፡፡ ሶስቱ ሴቶች በተለያዩ ጊዜዎች የጠፉ ቢሆንም ተመሳሳይ ታሪክ አላቸው፡፡ ሶስቱም ፔድሮ ካስትሮ በተባለ ግለሰብ ታግተው በመኖሪያቤቱ ምድርቤት ውስጥ የተለያዩ ስቃዮችን አሳልፈዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋለው ግለሰቡ ሴቶችን በመኪና ልሸኛችሁ (ሊፍት ልስጣችሁ) እያለ ነበር ወጥመድ ውስጥ ያስገባቸው፡፡

ሶስቱ ሴቶች እንደታገቱ በተለያዩ ክፍሎች ተነጣጥለው እንዲቀመጡ ያደረገ ቢሆንም በኋላ ላይ አንድ ላይ እንዳደረጋቸው ባለታሪኮቹ ይናገራሉ፡፡ በዓመታት የእገታ ቆይታቸው ተገደው ተደፍረዋል ፤ ለሳምንታት ምግብ ተከልክለዋል፤ ድብደባ ተፈፅሞባቸዋል ፤ በሰንሰለትም ታስረዋል፡፡ በፖሊስ መረጃ መሰረት ፤ ከሴቶቹ አንዷ አምስት ጊዜ ተገዳ ተደፍራ አምስት ጊዜ የፅንስ መጨናገፍ ደርሶባታል - በተፈፀመባት ድብደባ እና የምግብ ክልከላ የተነሳ፡፡ የሴቶቹ የመሰወር ምስጢር በቅርቡ እስኪታወቅ ታዲያ የተለያዩ ግለሰቦች ተጠርጥረው ፍርድ ቤት ቀርበዋል፡፡ እንስቶቹ ሞተዋል በሚል ግምትም ፖሊስ አስከሬናቸውን ለማግኘት ያልፈነቀለው ድንጋይ አልበረም፡፡ በቅርቡ ግን ሁሉም በህይወት ተገኝተዋል፡፡

ታጋቾቹ በእነዚህ ሁሉ ዓመታት ከክፍላቸው ወጥተው ውጭውን ያዩት አንድ ጊዜ ብቻ ነው - ያውም እዚያው ቤት ግቢ ውስጥ፡፡ ሰዎች ማንነታቸውን እንዳይለዩዋቸው መነጽር፤ ኮፊያ እና ዊግ እንዲጠቀሙ ተገደው እንደነበርም አስታውሰዋል - ለፖሊስ በሰጡት ቃል፡፡ በአሜሪካን ኦሃዮ ግዛት፤ ክሌቭላንድ ውስጥ ለ10 አመት ገደማ ታግተው የቆዩት ሴቶች ባለፈው ሰኞ ነው ነፃ የወጡት- ያገታቸው ግለሰብ ከቤት ሲወጣ አማንዳ ቤሪ ባሰማቸው የድረሱልን ጥሪ፡፡ ከዚያ በፊት ግን እንዲህ ያለ ሙከራ አድርገው እንደማያውቁ አማንዳ ለፖሊስ ገልፃለች፡፡ በመጀመርያ ሙከራዋ ውጤታማ መሆናም ጀግና አሰኝቷታል፡፡ ወደ ማገቻው መኖርያ ቤት የገቡት ሶስቱ ሴቶች ብቻ ቢሆኑም ሰሞኑን ነፃ ሲወጡ ግን የውጭውን ዓለም የማታውቅ የስድስት አመት ህፃንም አብራ ነበረች፡፡ ልጅቷ የቤሪ እንደሆነች የታወቀ ሲሆን አባቷ ማን እንደሆነ ለማወቅ ግን ምርመራ ይካሄዳል ተብሏል፡፡

የቤሪን ጩኸት ሰምቶ ሴቶቹን ነፃ እንዲወጡ የረዳቸው ቻርለስ ራምሴ የተባለ የካስትሮ ጎረቤት ነው፡፡ በዚህ መልካም ሥራውም ከመላው አሜሪካ ከፍተኛ አድናቆት እየጎረፈለት መሆኑ ታውቋል፡፡ ራምሴ የሚሰራበት ሬስቶራንት የፌስቡክ ገፅ ላይ የሰፈረው ፅሁፍ እንዲህ ይላል “በባልደረባችን መልካም ተግባር እጅግ ኩራት ተሰምቶናል፡፡ እሱ የክሌቭላንድ ጀግና ነው፡፡” ራምሴ ስለሁኔታው ሲገልፅም፤ “ድምፅ ሰምቼ ከቤቴ ስወጣ አንዲት ሴት ከጎረቤት ካለው ቤት ለመውጣት ስትታገል አገኘሁ፡፡ በሩን እየደበደበች ያለማቋረጥ የምትጮኸውን ሴት ከዚህ በፊት አይቻት አላውቅም፡፡ “እኔ ታግቼ ነው፡፡ እዚህ ቤት ለአመታት ተዘግቶብኝ ኖሬያለሁ፡፡ አሁን ነፃ መውጣት እፈልጋለሁ” አለችኝ ፡፡ ለምን 911 አትደውይም ስላት መውጣት እንደምትፈልግ አጥብቃ ነገረችኝ ፡፡ እኔና ሌላ ሰው በሩን በመክፈት ተባበርናት፡፡ እናም 911 በመደወል እኔና ቤሪ ሁኔታውን አስረዳን፡፡ ፖሊስ ሲመጣ ሌሎች ሁለት ሴቶች ውስጥ እንዳሉ ገልፃ ሁሉም ነፃ ወጡ” ብሏል፡፡ ራምሴ በአጋችነት የተጠረጠረውን ጎረቤቱን እንዲህ ያለ ተግባር ይፈፅማል ብሎ አስቦ አያውቅም፡፡

“ስለጎረቤቴ ምንም የተለየ ነገር አላውቅም ነበር፡፡ ብዙ ምሽቶችን ስጋ እየጠበስንና ሳልሳ ሙዚቃ እየሰማን አሳልፈናል፡፡ ግቢው ውስጥም ሁልጊዜ ከውሾቹ ጋር ሲጫወት ነው የማየው፡፡ ዛሬ ካየሁት ውጪ የሚያስገርም ነገር ሲያደርግ አይቼ አላውቅም” በማለት መገረሙን ገልጿል፡፡ የአውቶቡስ ሾፌሩ ካስትሮ፤ የፖርቶሪኮ ተወላጅ ሲሆን የላቲን ባንድ የሙዚቃ ተጫዋች ነበር፡፡ የዛሬ ስምንት ዓመት ገደማ በአሁኑ ወቅት አብራው በማትኖር ሚስቱ የድብደባ እና የግድያ ዛቻ ክስ ቢቀርብበትም ክሱ ውድቅ ተደርጓል፡፡ የፖሊስ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በ2000 እና በ2004 ዓ.ም ፖሊስ በደረሰው ጥቆማ በካስትሮ ቤት ላይ ፍተሻ አድርጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ምንም ፍንጭ ሳያገኝ ተመልሷል፡፡ አሁን የሶስቱ ሴቶች ህይወት ተቀይሯል፡፡ አማንዳ ቤሪ የ27 አመት ሴት እና የስድስት አመት ልጅ እናት ሆናለች፡፡ እናቷን በህይወት ለማግኘት አልታደለችም፡፡

በልጃቸው ድንገተኛ መሰወር ልባቸው ክፉኛ የተሰወረው እናቷ ከጠፋችበት እለት አንስቶ ህይወታቸው እስክታልፍ ድረስ ያለመታከት ልጃቸውን ሲያፈላልጉ ቆይተዋል ሆኖም የልጃቸውን ዓይን ሳያዩ በደረሰባቸው የጤና እክል ህይወታቸው አልፏል፡፡ ሚሸል ናይት የ30 አመት ሴት ሆናለች፡፡ እሷ ከታገተች በኋላ የተወለደች አዲስ እህት አግኝታለች፡፡ እናቷ በሰጠችው አስተያየት፤ “ልጄን በህይወት ማግኘቴ ታላቅ ስጦታ ነው፡፡ ቶሎ እንድታገግም አግዛታለሁ” ብላለች፡፡ ከትምህርት ቤት ወደቤት ለመመለስ ዘጠኝ አመታት የፈጀባት ጂና፤ ቤተሰቦቿን የተቀላቀለችው የ23 አመት ወጣት ሆና ነው፡፡ በእነዚያ ዓመታት ብዙ ስቃዮችን ብታሳልፍም ፊቷን በሹራቧ ሸፍና የአውራ ጣቷን ወደ ላይ በመቀሰር ዳግም ከቤተሰቧ ጋር መቀላቀሏ የፈጠረባትን ደስታ ገልፃለች፡፡

ሦስቱም ሴቶች ከደረሰባቸው የአካልና የሥነልቦና ጉዳት ለማገገም ሆስፒታል ገብተው የነበረ ሲሆን ሁለቱ ህክምናቸውን አጠናቀው ሲወጡ እናቷን በሞት ያጣችው ናይት ግን አሁንም እዚያው ትገኛለች፡፡ መርማሪዎች ወደ ሁለት መቶ የሚጠጉ ማስረጃዎችን ከካስትሮ ቤት ሰብስበዋል፡፡ የክሌቭላንድ ከንቲባ ፍራንክ ጃክሰን፤ ሶስቱ ሴቶች በህይወት መገኘታቸው እንዳስደሰታቸው ገልፀው ሆኖም ያልተመለሱ ብዙ ጥያቄዎች አሉ ብለዋል፡፡ ለምን ተወሰዱ? እንዴት ተወሰዱ? ይህን ያህል ጊዜስ ያሉበት እንዴት ሳይታወቅ ቀረ የሚሉና ሌሎችም፡፡ ከንቲባው እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ ምርመራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ቃል ገብተዋል፡፡ ምንም እንኳን ቤሪ እናቷን ለማየት ባትታደልም እናት ለመሆን በቅታለች፡፡ ጂና እና ናይት ደግሞ ከእናቶቻቸው ጋር ለመገናኘት ችለዋል፡፡ እናም ሦስቱ ሴቶች ከአስር ዓመት እገታ በኋላ ነፃ መውጣታቸው ነገ ለሚከበረው “የእናቶች ቀን” መልካም ስጦታ ሆኖላቸዋል፡፡

በቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኢትዮጵያ ቡና መካከል ከተደረገው የጥሎ ማለፍ ጨዋታ በፊት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች ይቅር ተባባሉ፡፡ ከወር በፊት የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች እና ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው አላግባብ በገቡት እሰጥ አገባ ተጠማምደው የነበረ ሲሆን ከትናንት በስቲያ በስታድዬም መላው ስፖርት አፍቃሪን ባስደሰተ ስፖርታዊ ጨዋነት ተታርቀዋል፡፡ በሌላ በኩል በኢትዮጵያ እግር ኳስ ከፍተኛ አስተዋፅኦ በማድረግ ከሚታወቁት ክለቦች ግንባር ቀደም ተጠቃሽ የሆነው የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ነገ 36ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን በድምቀት ያከብራል፡፡የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እና የክለቡ ደጋፊዎች ማህበር ‹‹የኢትዮጵያ ቡና በአዲስ ጎዳና›› በሚል መርህ ከኮንታክት መልቲ ሚድያ ጋር በመተባበር ሰፊ የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም እንዳዘጋጁ ታውቋል፡፡

ክለቡ በያዘው አዲስ አቅጣጫ ያለውን የደጋፊ ብዛት በመጠቀም በፕሮፌሽናል መንገድ በመደራጀት በስፋት ለመንቀሳቀስ ትኩረት እንዳደረገ ለማወቅ ተችሏል፡፡ኢትዮጵያ ቡና የተመሰረተው በ1975 ዓ/ም በቡና ቦርድ ስር ሆኖ ቡና ገበያ ስፖርት ክለብ በሚል ስያሜ ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ ክለቡ የቡና ላኪዎች ማህበር ከምርት ገበያ ጋር በመሆን በጀት እየመደቡለት በቦርድ በመመራት እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ለ36 ዓመታት በኢትዮጵያ የክለብ ውድድሮች በነበረው ተሳትፎ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮናነት አንድ ጊዜ ብቻ በ2003 ዓ.ም ሲያስመዘግብ ሌሎች የዋንጫ ድሎቹ 1 ጊዜ በኢትዮጵያ ሻምፒዮና 4 ጊዜ በኢትዮጵያ ጥሎ ማለፍ ሻምፒዮና ፤3 ጊዜ በኢትዮጵያ የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ እንዲሁም 1 ጊዜ የክለቦች ህብረት አሸናፊነት የተመዘገቡ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ ቡና በአራት የአፍሪካ ውድድሮች የመሳተፍ እድል ያገኘ ክለብ ሲሆን በኢትዮጵያ ጥሎ ማለፍ ውድድሮች በየጊዜው ሻምፒዮን የመሆን ልምድ አለው፡፡ ክለቡ ከዋናው ቡድን በተጨማሪ ተጠባባቂ የተስፋ ቡድን፤ በወጣት እና በሴቶች ቡድኖቹም እየሰራ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ በኢትዮጵያ እግር ኳስ የሚታወቀው ስታድየምን በማስዋብና በማድመቅ በሚታወቁት ደጋፊዎቹ ነው፡፡ የክለቡ ደጋፊዎች በአዲስ አበባ ስታድየም ቀኝ ጥላ ፎቅ፣ ካታንጋ እና ሚስማርተራ በብዛት ገብተው አስደናቂ የድጋፍ አሰጣጥ፤ ዝማሬ እና ህብረት በማሳየት የስፖርቱ አለኝታ ሆነው የቆዩ ናቸው፡፡

የሰውነትየምንግዜም ምርጥ አሰልጣኝነት? ለ3 አስርት ዓመታት በአህጉራዊ ውድድሮች አንቀላፍቶ የኖረውን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወደ ተሳትፎ በማምጣት ውጤታማ በማድረግ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው አየተሳካላቸው ነው፡፡ የ61 ዓመቱ ሰውነት ቢሻው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለአንድ አመት መንፈቅ ሲያሰለጥኑ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ እና ዋና ውድድር፤ በዓለም ዋንጫ ማጣርያዎች እና በወዳጅነት በድምሩ 12 ጨዋታዎችን በማድረግ ከ10 አገራት ብሄራዊ ቡድኖች ጋር ተጋጥመዋል፡፡ በውጤታቸውም 6 ድል፤ 4 አቻ እና ሁለት ሽንፈት አስመዝግበዋል፡፡ ከቤኒን እና ከሱዳን ብሄራዊ ቡድኖች ጋር 2 ጨዋታዎችን ሲያደርጉ ሌሎቹ አንድ አንድ ጊዜ የገጠሟቸው ብሄራዊ ቡድኖች ደግሞ ሶማሊያ፤ ደቡብ አፍሪካ፤ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ፤ ቱኒዚያ ፤ዛምቢያ፤ቡርኪናፋሶ ፤ናይጄርያ እና ቦትስዋና ናቸው፡፡ ዘ ኢንስቲትዩት ኦፍ ፉትቦል ኮቺንግ የተባለ ተቋም ለዓለም አሰልጣኞች በሚያወጣው የብቃት ደረጃ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ባለፈው 1 ዓመት ተኩል ከነበሩበት የ350ኛ ደረጃ አሁን 120ኛ ላይ መድረሳቸውንም ያመለክታል፡፡

በትራንስፈርማርከት ድረገፅ ላይ በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ስኬት ላይ በተሰራ አሃዛዊ ስሌት መሰረት የአሰልጣኝነታቸው ስኬትም ድል በ33.33 በመቶ፤ አቻ በ41.67 በመቶ እንዲሁም ሽንፈት በ25 በመቶ በመቶ ተተምኗል፡፡ ከ31 ዓመት በፊት በሊቢያው የአፍሪካ ዋንጫ በመንግስቱ ወርቁ አሰልጣኝነት ከተሳተፈች በኋላ 17 ዋና አሰልጣኞች በብሔራዊ ቡድኑ ኃላፊነት የተፈራረቁ ሲሆን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ባለፈው 1 ዓመት ተኩል ባስመዘገቡት ውጤት የኢትዮጵያ እግር ኳስ የምንግዜም ውጤታማው አሰልጣኝ እየሆኑ መምጣታቸውን እያረጋገጡ ናቸው፡፡ ከ1 ዓመት ተኩል በፊት የቤልጄማዊው ቶም ሴንትፌይት ረዳት የነበሩት አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የብሄራዊ ቡድኑ ዋና አሰልጣኝ በመሆን መስራት የጀመሩት ለ2ኛ ጊዜ ነው፡፡

ከ2004 እሰከ 2006 እኤአ ብሄራዊ ቡድኑን በዋና አሰልጣኝነት ሲመሩ በ2005 እ.ኤ.አ በሩዋንዳ ላይ በዋና ብሔራዊ ቡድን እንዲሁም በ2004 እ.ኤ.አ ደግሞ አዲስ አበባ ላይ በወጣት ብሔራዊ ቡድን ሁለት የሴካፋ ዋንጫዎችን አሸንፈዋል፡፡ በ2001 እ.ኤ.አ ደግሞ በረዳት አሰልጣኝነት ከብሔራዊ ቡድኑ ጋር የሴካፋን ዋንጫ ማግኘትም ችለዋል፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ከ7 ዓመት በፊት በብሔራዊ ቡድኑ ሲሰሩ በ5 ዓመት ውስጥ 3 የሴካፋን ዋንጫ ማግኘታቸው ትልቅ ስኬት ነበር፡፡ በተጨማሪም አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የታዳጊ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው በመስራት ቦትስዋና ጋብሮኒ ላይ በተደረገ የአፍሪካ ታዳጊዎች ሻምፒዮና አራተኛ ደረጃ ለማግኘትም በቅተዋል፡፡ ባለፈው 1 ዓመት ተኩል ደግሞ ብሔራዊ ቡድኑን በኃላፊነት ይዘው ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ትንሳኤ የሚሆን ውጤት በማስመዝገብ እየተሳካላቸው ነው፡፡ የመጀመርያው ስኬታቸው ብሄራዊ ቡድኑ ከ31 ዓመታት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፍ ማስቻላቸው ነው፡፡

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከ31 ዓመት በኋላ በአፍሪካ ዋንጫ ሲሳተፍ 3 ግጥሚያዎችን አድርጎ አንድ አቻ እና ሁለት ሽንፈት ፤ አንድ ጎል አግብቶ 7 ጎል ተቆጥሮበት ከምድቡ በጊዜ መሰናበቱ የሚታወስ ቢሆንም በውድድሩ ከፍተኛ አህጉራዊ ትኩረት ሊያገኝ የበቃ ነበር፡፡ በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የሚመራው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እያገኘ ባለው ስኬት ከፍተኛ የሽልማት ገንዘብ፤ በስፖንሰርሺፕ የገቢ ምንጭ በመፍጠር እና ደረጃውን በማሻሻልም ሆኖለታል፡፡ሼህ መሃመድ አልአሙዲ ለብሄራዊ ቡድኑ 5 ሚሊዮን ብር ከመሸለማቸውም በላይ የቡድኑ አብይ ስፖንሰር የሆነው በደሌ ቢራ በስፖንሰርሺፕ ውል ለ2 ዓመት እስከ 24 ሚሊዮን ብር በመክፈል ቡድኑን ማጠናከር ተችሏል፡፡ ኤምቲኤን የተባለ ኩባንያም በ6 ሚሊዮን ብር ብሄራዊ ቡድን ስፖንሰር ማድረጉም ይታወቃል፡፡ በአሁን ጊዜ በ50ሺ በር ወርሃዊ ደሞዛቸው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ውዱ ተከፋይ የሆኑት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው 280 ሺ ብር የሚያወጣ ሊፋን መኪና በውጤታማነታቸው በማግኘትም ተጠቅመዋል፡፡

በአሰልጣኝ ሰውነት ሃላፊነት ዘመን በዋልያዎቹ ስብስብ ያሉ ተጨዋቾች በነፍስ ወከፍ በአማካይ 300ሺ ብር ለመሸለም እንደበቁም ይታወቃል፡፡ በሰውነት ቢሻው የሚመራው ብሄራዊ ቡድን ከአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ ባሻገር በ2014 እ.ኤ.አ ብራዚል ለምታስናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ በሚደረገው የምድብ ማጣሪያም በተስፋ ሰጭ ውጤት በመጓዝ ላይ ይገኛል፡፡ በዓለም ዋንጫ ማጣርያው ደቡብ አፍሪካ፤ ቦትስዋና እና መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክ የሚገኙበትን ምድብ የሰውነት ቢሻው ብሄራዊ ቡድን በ3 ጨዋታዎች ሰባት ነጥብ እና 3 የግብ ክፍያ በመያዝ እየመራ ነው፡፡

በብራዚል 2014 ላይ ለሚስተናገደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ የሚደረገው የምድብ ማጣሪያ በ4ኛ ዙር ሲቀጥል የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሰኔ መጀመርያ ላይ ከቦትስዋና ጋር ከሜዳው ውጭ ይጋጠምና በሳምንቱ ደግሞ ከደቡብ አፍሪካ ጋር በአዲስ አበባ ይጫወታል፡፡ በዓመቱ መገባደጃ ላይ ደግሞ በመጨረሻው የማጣርያ ጨዋታ ከሜዳው ውጭ ከመካከለኛው አፍሪካ ጋር ይጋጠማል፡፡ ዋልያዎቹ በቀሪዎቹ 3 ጨዋታዎች ያለሽንፈት ከተጓዙ ከአንድ ብሄራዊ ቡድን ጋር በደርሶ መልስ የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ድልድል በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ የሚሳተፉበትን እድል ይወስናሉ፡፡ ይህን ማሳካት ደግሞ ለዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የምንግዜም ምርጥ አሰልጣኝነት ሁነኛ ማረጋገጫ ይሆናል፡፡

ሰር አሌክስ ፈርጉሰን ለ26 አመታት በከፍተኛ ስኬት አሰልጣኝ ሆነው ከሰሩበት ማንችስተር ዩናይትድ በ71 ዓመታቸው በጡረታ መሰናበታቸው ዓለም አቀፍ ትኩረት አግኝቷል፡፡ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች በህትመት፤ በኤሌክትሮኒክስ፤ በኢንተርኔት የመረጃ መረቦች እና ማህበራዊ ድረገፆች የፈርጊ ጡረታ መውጣት ከፍተኛ ሽፋን ተሰጥቶታል፡፡ በርካታ ዘገባዎች የዓለም እግር ኳስ እጅግ ታላቅ ባለሙያ ሳይታሰብ ማጣቱን፤ የፈርጊ ዘመን ማብቃቱን፤ እግር ኳስ የለወጡ እና ያሳደጉ መሆናቸውን በመጥቀስ ለሰር አሌክስ ፈርጉሰን ስንብት ሰፋፊ ሃተታዎችን በማቅረብ ዘክሯቸዋል።

ታላቁን የእግር ኳስ ጌታ ፈርጊ ለማስታወስ የሚከተሉትን 20 እውነታዎች ይመልከቱ፡፡ ስኮትላንዳዊ ዜግነት ያላቸው ሰር አሌክስ ፈርጉሰን በ6 የስኮትላንድ ክለቦች የአጥቂ መስመር ተጨዋችነት 317 ጨዋታዎች አድርገው 170 ጎሎች አስመዝግበዋል፡፡ ማን ዩናይትድን ከመያዛቸው በፊት በ3 የስኮትላንድ ክለቦች እና በስኮትላንድ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ሰርተዋል፡፡ በ1986 እኤአ ላይ ፈርጊ ማን ዩናይትድን በዋና አሰልጣኝነት ለመምራት ሲረከቡ የክለቡ የዋጋ ግምት 31 ሚሊዮን ዶላር የነበረ ሲሆን ከ26 አመታት በኋላ ክለቡን ሲለቁ ግን ክለቡ የዋጋ ግምቱ 3.2 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል፡፡

ክለቡን በ1986 እኤአ ላይ በሃላፊነት ሲረከቡ በየትኛውም ውድድር ለ19 ዓመታት ምንም አይነት ዋንጫ አላገኘም ነበር፡፡ ከ26 አመታት ስራ በኋላ በጡረታ ሲሰናበቱ ማን ዩናይትድ 39 ዋንጫዎችን ሰብስቧል፡፡ እነዚህ የዋንጫ ድሎች በትልልቅ የእንግሊዝ እና የአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ውድድሮች ሲመዘገቡ 13 በፕሪሚዬር ሊግ፤ 2 በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ 1 በፊፋ የዓለም ክለቦች ዋንጫ፤1 በአውሮፓ ካፕ ዊነርስ ካፕ፤ 1 በአውሮፓ ሱፕር ካፕ፤ 1 በኢንተርኮንትኔንታል ካፕ፤ 5 በኤፍ ኤ ካፕ እንዲሁም 10 በኮሚኒዊቲ ሺልድ የተገኙ ናቸው፡፡ ፈርጊ በማንችስተር ዩናይትድ እና ከዚያም በፊት በአሰልጣኝነት በሰሩባቸው ክለቦች በድምሩ 49 ዋንጫዎችን በማግኘት በእግር ኳስ ክለቦች የውድድር ታሪክ በዓለም አቀፍ ደረጃ በተለይ በመላው ብሪታኒያ ከፍተኛውን የስኬት ክብረወሰን አስመዝግበዋል፡፡ በፕሪሚዬር ሊግ የውድድር ታሪክ ፈርጊ ማን ዩናይትድን ለ26 አመታት ሲያሰለጥኑ በ44 ሌሎች ክለቦች 175 አሰልጣኞች ተፈራርቀው ሰርተዋል፡፡ እነዚህ 175 አሰልጣኞች በበተለያዩ ክለቦች በድምር በሰሩባቸውቨ 405 የውድድር ዘመናት 8 ጊዜ የሊጉን የሻምፒዮናነት ክብር ሲያገኙ ፈርጊ በ21 የውድድር ዘመናት 13 ጊዜ የፕሪሚዬር ሊግ ዋንጫን በማሸነፍ አስደናቂ ክብረወሰን አስመዝግበዋል፡፡

ፈርጊ በማን ዩናይትድ አሰልጣኝነት ከሰሩባቸው 9680 ቀናት በፊት አሁን በክለቡ የሚጫወቱ 17 ተጨዋቾች ገና አልተወለዱም ነበር፡፡ ከማን ዩናይትድ በጡረታ ሲሰናበቱ በእንግሊዝ እግር ኳስ አራት ዲቪዚዮኖች በሚወዳደሩ ክለቦች 1146 አሰልጣኞች ተፈራርቀዋል፡፡ ለ27 የውድድር ዘመናት በአንድ ክለብ አሰልጣኝነት በመስራት በሃላፊነት ለረጅም ጊዜ የቆዩ አሰልጣኞችን በአንደኛ ደረጃ ይመራሉ፡፡ በፈርጊ የሚሰለጥነው ማንችስተር ዩናይትድ በተለያዩ ውድድሮች ካደረጋቸው 1500 ጨዋታዎች 894 ድል ሲያደርግ ሽንፈት የገጠመው 267 ጊዜ ነው፡፡ በትራንስፈርማርከት ስሌት መሰረት ፈርጊ በአሰልጣኝነታቸው ያላቸው ስኬት እንደተመዘገበው 62.96 በመቶ ድል፤20.78 አቻ እንዲሁም 16.26 በመቶ ሽንፈት ነው፡፡

በእንግሊዝ ፕሪ ሚዬር ሊግ የተሳትፎ ታሪካቸው 2045 ነጥብ ሰብስበዋል፡፡ በፈርጊ ዘመን በአርሰናል፤ቼልሲ፤ ሊቨርፑል፤ ማን ሲቲ እና ቶትንሃም ክለቦች 51 አሰልጣኞች ተፈራርቀዋል፡፡ ፈርጊ ለ26 አመታት ማን ዩናይትድን ሲያሰለጥኑ ሪያል ማድሪድ 21፤ ኢንተር ሚላን 19፤ ቼልሲ 15፤ ባየር ሙኒክ 14፤ ጁቬንትስ 14፤ ማን ሲቲ 14፤ ኤሲ ሚላን 13 እንዲሁም ባርሴሎና 11 አሰልጣኞችን በሃላፊነት መንበር አፈራርቀዋል፡፡ በሙሉ ቡድኑ 29 ተጨዋቾች እና 15 ከእንግሊዝ ውጭ ዜግነት ያላቸው ያሰባሰበው የፈርጊ ማንዩናይትድ ቡድን በትራንስፈርማርከት ያገኘው የዋጋ ተመን 370 ሚሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ የቡድኑ አማካይ እድሜ 27.5 አመት ሲሆን የአንድ ተጨዋች አማካይ ዋጋ 14.36 ሚሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ በክለቡ የ26 ዓመታት ቆይታቸው 104 ተጨዋቾችን በግዢ ኦልድትራፎርድ ያመጡት ፈርጊ በክለቡ ባፈሯቸውና ዘ ፈርጊ ቤቢስ በተባሉ ምርጥ ተጨዋቾቻውም ይታወሳሉ፡፡

የፈርጊ ውጤት የሆኑት እውቆቹ ተጨዋቾች ራያን ጊጊስ፤ ፖል ስኮልስ፤ ዴቪድ ቤካም፤ ጋሪ ኔቭል፤ ኒኪ በት እና ዌልቤክ ይጠቀሳሉ፡፡ ፈርጊ በተጨዋቾች ግዢ በ26 ዓመታት ውስጥ 546.5 ሚሊዮን ፓውንድ ሲያወጡ በሽያጭ ደግሞ 226.5 ሚሊዮን ፓውንድ ገቢ አድርገዋል፡፡ በማንችስተር ዩናይትድ ዋና አሰልጣኝነት ከ26 ዓመት በፊት ሲቀጠሩ የዓመት ደሞዛቸው 60ሺ ፓውንድ ነበር፡፡ በ2013 እኤአ በዓመታዊ ደሞዝ 7 ሚሊዮን ፓውንድ የሚታሰብላቸው ፈርጊ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የዘንድሮ ሻምፒዮናነት ባገኙ ማግስት በሰንደይ ታይምስ ተሰርቶ በወጣ የእንግሊዝ እግርኳስ ሃብታሞች ዓመታዊ ደረጃ በ34 ሚሊዮን ፓውንድ ሃብት አንደኛ ናቸው፡፡ ፈርጊ እግር ኳስን በቲቪ የመመልከት ልማድ ያላቸው ሲሆን በምእራቡ ዓለም የተሰሩ የጦርነት ፊልሞችን መመልከትም ያዘወትራሉ፡፡ ክላርኔት የተባለ ሙዚቃ መሳርያ መጫወትም ይችላሉ፡፡

ፈርጊ ጡረታቸውን ባሳወቁ በኢንተርኔት የማህበረሰብ ድረገፆች ከፍተኛ ትኩረት ስበው ነበር፡፡ ጡረታቸው በታወጀ 24 ሰዓት ውስጥ በጉዳዩ ላይ 6 ሚሊዮን የቲውተር መልክቶች ተሰራጭተዋል፡፡ ፈርጊን ለመተካት ጡረታ በወጡበት ማግስት የኤቨርተኑ ዴቭድ ሞየስ ቅድሚያ ግምት ቢወስድም፤ በሪያል ማድሪድ ያሉት ጆሴ ሞውሪንሆና የጀርመኑ ክለብ ዶርትመንድ አሰልጣኝ ጀርገን ክሎፕ በእጩነት ተጠቅሰዋል፡፡ ከእነዚህ አሰልጣኞች ባሻገር በምትክነት የታጩት በፈርጊ የሰለጠኑትና ከፈርጊ ቤቢስ አባላት መካከል የሆኑት የቀድሞ ተጨዋቾች ራያን ጊግስ፤ ኦሌ ጉናር ሶልሽየር እና ፖል ስኮልስ ነበሩ፡፡ ፈርጊ እንዲተካቸው የሚፈልጉት ራያን ጊጊስ እንደሆነ ተናግውም ነበር፡፡ በመጨረሻም ምትኩ ዴቪድ ሞይስ ሆኗል፡፡ በኤቨርተን ክለብ ለ11 ዓመት ያሰለጠነው ዴቪድ ሞዬስ የማን ዩናይትድ ቦርድ በሙሉ ድምፅ የፈርጊ ምትክ አድርጎ እንዲሰራ በመምረጥ የ6 ዓመት ኮንትራት ሰጥቶታል፡፡ የ50 ዓመቱ ዴቪድ ሞይስ በማን ዩናይትድ አሰልጣኝነት መስራት ሲጀምር በሳምንት 80 ሺ በዓመት 4 ሚሊዮን ፓውንድ ይከፈለዋል፡፡

በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ኢትዮጵያን በመወከል እስከ 2ኛ ዙር ማጣርያ የመልስ ጨዋታ ተጉዞ በግብፁ ክለብ ዛማሌክ የተሸነፈው ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ኮንፌደሬሽን ካፕ ጥሎ ማለፍ ተሸጋግሮ ከሌላው የግብፅ ክለብ ኢኤንፒፒአይ ጋር ተደለደለ፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ውጭ የሆነው ከሳምንት በፊት ከግብፁ ዛማዜክ ጋር አዲስ አበባ ላይ የመልስ ጨዋታውን አድርጎ 2-2 አቻ በመለያየቱ ነው፡፡ ሁለቱ ክለቦች በሻምፒዮንስ ሊጉ የሁለተኛ ዙር ማጣርያ የደርሶ መልስ ጨዋታ በአጠቃላይ ውጤት 3ለ3 ቢሆኑም ዛማሌክ ወደምድብ ድልድል የገባው ከሜዳ ውጪ ብዙ ባገባ በሚለው ህግ ነው፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ሻምፒዮንስ ሊጉ የምድብ ድልድል ለመግባት ሳይችል ቢቀርም በውድድር ዘመኑ በአፍሪካ የክለብ ውድድር ያለውን ተሳትፎ ቀጥሏል፡፡

በኮንፌደሬሽን ካፕ ጥሎ ማለፍ 16 ክለቦች የሚሳተፉ ሲሆን የመጀመርያው ዙር ግጥሚያዎች ከሳምንት በኋላ ይካሄዳሉ፡፡ ጊዮርጊስ ከግብፁ ክለብ ጋር በኮንፌደሬሽን ካፑ ጥሎ ማለፍ የመጀመርያ ጨዋታውን የዛሬ ሳምንት በሜዳው ያደርጋል፡፡ በሌሎች ጨዋታዎች የማሊው ስታድ ዴማሊ ከብሩንዲው ኤልኤል አካዳሚ፤ የናይጄርያው ኢኑጊ ሬንጀርስ ከ ቱኒዚያው ሳፋክሲዬን፤ የሞሮኮው ኢፍዩኤስ ራባት ከሌላው የሞሮኮ ክለብ ኤኤስኤፍ ራባት፤ የቱኒዚያው ቤዘርቲን ከግብፁ ኢስማኢሊያ፤ የአልጄርያው ሴቲፍ ከጋቦኑ ዩኤስ ቢታም እንዲሁም የዲሞክራቲክ ኮንጎው ቲፒ ማዜምቤ ከሞዛምቢኩ ሊጋ ሙኩሉማና ይገናኛሉ፡፡

ጊዮርጊስ ከግብፁ ክለብ ኢኤንፒፒአይ ጋር በአፍሪካ ደረጃ ሲገናኝ ለሁለተኛ ጊዜ ነው፡፡ ሁለቱ ክለቦች በ2006 እኤአ ላይ በሻምፒዮንስ ሊግ የመጀመርያ ዙር ተገናኝተው ነበር፡፡ በወቅቱ የመጀመርያው ጨዋታ ካይሮ ላይ ሲደረግ ያለምን ግብ አቻ የተለያዩ ቢሆንም በመልሱ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሜዳው ኢኤንፒፒአይን 1ለ0 አሸንፎ ወደ ሁለተኛ ዙር ለመሸጋገር እንደበቃ ይታወሳል፡፡2 የውጭ ፕሮፌሽናሎችን ጨምሮ 27 ተጨዋቾችን በስብስቡ የያዘው የግብፁ ክለብ ኢኤንፒፒአይ በ48 ዓመቱ ግብፃዊ ታሬክ ኤልአሽሪ ዋና አሰልጣኝነት የሚመራ ነው፡፡

ተጨማሪ የሙስና ተጠርጣሪዎች ዛሬ እንደሚታሰሩ ምንጮች ተናግረዋል

የጉምሩክና ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ መላኩ ፈንቴና ምክትል ዳሬክተሩ አቶ ገብረዋህድ ወ/ጊዮርጊስ፣ እንዲሁም የ“ኬኬ” ኩባንያ ባለቤት አቶ ከተማ ከበደን ጨምሮ አስራ ሁለት ግለሰቦች በሙስና ተጠርጥረው አርብ ዕለት በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ዋሉ፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ባለሥልጣናትና ባለሃብቶች አርብ ጠዋት ከያሉበት በፖሊስ ተይዘው እንደተወሰዱ የገለፁ ምንጮች፤የቤት ብርበራ ሲካሄድ ማምሸቱንም ተናግረዋል፡፡ የፀረሙስና ኮሚሽን ማታ ሁለት ሰዓት ላይ በኢቴቪ በሰጠው መግለጫ፤ የጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳሬክተርና የሚኒስትሮች ካቢኔ አባል አቶ መላኩ ፈንቴ እና ምክትል ዳሬክተር አቶ ገብረዋህድ ወ/ጊዮርጊስ በሙስና ተጠርጥረው እንደታሰሩ ተገልጿል፡፡ ከሁለቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት በተጨማሪ ባለሃብቶችም በቁጥጥር ስር እንደዋሉ ኮሚሽኑ ገልፆ፤ ከብሔራዊ የመረጃና ደህንነት ጋር በመተባበር ምርመራ ማካሄዱን ተናግሯል፡፡

ከበርካታ ባለሃብቶችና ነዋሪዎች የቀረቡ አቤቱታዎችና ጥቆማዎች ለምርመራው እንዳገዙት ኮሚሽኑ ጠቅሶ፤ ተጠርጣሪዎቹን ወደ ፍ/ቤት በማቅረብ ክስ እመሰርታለሁ ቢልም ዝርዝር መረጃ አልሰጠም፡፡ በአገሪቱ አሉ ከሚባሉት ባለሃብቶች መካከል የሚጠቀሱት አቶ ከተማ ከበደ፤ ተጠርጥረው ከታሰሩት ባለሃብቶች አንዱ ሲሆኑ በበርካታ የኢንዱስትሪና የንግድ መስኮች የተሰማራው “ኬኬ” ኩባንያ ባለቤት ናቸው፡፡ ከ20 ዓመት በፊት የተመሠረተው “ኬኬ” ኩባንያ፤ አጀማመሩ ከትንሽ ደረጃ ላይ የተነሳ ስለነበር ሥራው የሚመራውና አብዛኛው ሥራ የሚከናወነው በድርጅቱ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ ከተማ ከበደ እንደነበር የድርጅቱ ይፋዊ መረጃ ይገልፃል፡፡

በልብስና በቀለም ምርት የተሰማራው “ኬኬ”፤ የከባድ ማሽነሪዎች አስመጪ በመሆንም በስፋት ይታወቃል፡፡ ከጊዜ በኋላም በቡና ኤክስፖርት እንዲሁም በእርሻ ኤክስፖርትና በማዳበርያና ተባይ ማጥፊያ ምርቶች አስመጪነት በመሰማራት ሥራውን እንዳስፋፋ የድርጅቱ መረጃ ይዘረዝራል፡፡ የሚኒስትሮች ካቢኔ የሆኑት አቶ መላኩ ፈንቴ ከሥልጣናቸው ይነሳሉ ተብለው ለወራት ሲወራ የነበረ ሲሆን ምክትላቸው አቶ ገብረዋህድ ደግሞ ባለፈው የካቲት ወር በፓርቲው ውስጥ ከነበራቸው ሃላፊነት መነሳታቸው ይታወሳል፡፡ በተያያዘ ዜና፣ አርብ እለት ከተፈፀመው እስር እንዲሁም ሌሊቱን ሙሉ ከተካሄደው የተጠርጣሪዎች ቤት ብርበራ በተጨማሪ፣ ዛሬ ቅዳሜ እለትና በቀጣዮቹ ቀናት በቁጥጥር ስር የሚውሉ ሎሎች ተጠርጣሪዎች እንደሚኖሩ ምንጮች ጠቁመዋል።

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ፓርቲ ዋና ጸሐፊ በመሆን ለአስር አመታት ያገለገለው አቶ ማሙሸት አማረ “በፓርቲው ህልውና ላይ ጉዳት አድርሰሀል” በመባል እሱን ጨምሮ 17 የፓርቲው አመራሮች ከፓርቲው የታገዱት የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ ነው፡፡ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት በመውሰድ ሲከራከሩ የነበሩት እነ ማሙሸት አማረ እና እነ ኢንጂነር ሃይሉ ሻውል ሲሆኑ ፍ/ቤቱም ተከሳሽ የነበሩ እነ ማሙሸት “ምንም አይነት ሁከት አልፈጠሩም” በማለት ወደ ፓርቲው እንዲመለሱ መስጠቱ ይታወሳል። ሆናም ትዕዛዙ ተግባራዊ ሳይሆን አንድ ዓመት አልፎታል፡፡ “ፓርቲው ውስጣዊ ችግሮች አሉበት” በማለት የሚናገሩት እነ አቶ ማሙሸት፤ ዛሬ የፓርቲውን ችግር በውይይት ለመፍታትና “ጠቅላላ ጉባኤ ይጠራ” በማለት ከምርጫ ቦርድና ከኢንጂነር ኃይሉ ሻውል ጋር እየተነጋገሩ ነው፡፡ ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው በእነዚህ ጉዳዮች ዙሪያ አቶ ማሙሸት አማረን አነጋግራለች፡፡

ከመኢአድ ከታገድክ ስንት ጊዜ ሆነህ?

በ2003 ዓ.ም በተደረገ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ነው የዚህ ፓርቲ ዋና ፀሐፊ በመሆን የተመረጥኩት። ከዚያ በኋላ ነው የታገድኩት፡፡ በአቶ ሃይሉና በአቶ ያዕቆብ ከፓርቲው ውጪ በሄደ ደንብ የውስጥ አለመግባባት ተፈጥሮ አቶ ኃይሉ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት ወስዶ ክርክር ከተደረገበት በኋላ ፍ/ቤቱ የተከሰስንበት ጉዳይ ስህተት መሆኑን አውቆ ወደ ፓርቲያችን እንድንመለስና ጠቅላላ ጉባኤው ተሰብስቦ የመጨረሻ እልባት እንዲሰጥ ተወሰነ፡፡ ከሳሾች ፍ/ቤቱ ትክክል አልፈረደም ብለው ለከፍተኛ ፍ/ቤት ይግባኝ ጠይቀው ነበር፡፡ ሆኖም ፍ/ቤቱ የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ አጸና፡፡ አቶ ሀይሉና ሌሎቹ ግን የችሎቱን ትዕዛዝ ማክበር ባለመቻላቸው፣ ምርጫ ቦርድ ውሳኔውን እንዲያስፈጽም ትዕዛዝ ሰጠልኝ፡፡ ቦርዱም ይህንን መነሻ በማድረግ ለአቶ ሃይሉ በ2004 ዓ.ም ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠሩ ትዕዛዝ ቢሰጥም ጉባኤው ሳይጠራ ቀረ፡፡ እኛም ትግላችንን በህጋዊ መንገድ በመቀጠል ያላሰለሰ ጥረት አደረግን፡፡ ይኼም ተቀባይነት ሊያገኝ አልቻለም፡፡ እንግዲህ እንደምንሰማው አቶ ሃይሉ “አባረናል አጥርተናል” ይላሉ፡፡ ሆኖም እሳቸው የማባረርም የማጽዳትም ስልጣን የላቸውም፡፡

የመኢአድ አባል ስትሆን ምኑን መርጠህ ነው?

ከ1984 ሚያዚያ 15 ጀምሮ መ.አ.ህ.ድ ነበርኩ። ኢህአዴግ ከገባ በኋላ በአማራው ተወላጅ ላይ በየክልሉ ከፍተኛ በደል ሲያደርግ ይሄ በደል ይቁም በማለት በዚህ እንቅስቃሴ ለመሳተፍ ነው አባል የሆንኩት፡፡ ከዚህ በኋላ የታገልንለት ህዝብ ለምን ለአማራው ብቻ ትታገላለችሁ ሁሉም ብሔሮች ችግር እየደረሰባቸው ነው ያሉት፤ ለምን ለሁሉም ብሔር አትታገሉም የሚል ከፍተኛ አስተያየት በመኖሩ አባላቱ በሰጡት ውሳኔ መሠረት በ1995 ዓ.ም መአህድ ወደ መኢአድ ተቀየረ፡፡ መአህድ ወደ መኢአድ ከተቀየረ 10 አመት ሆኖታል፡፡ በዚህ ጊዜ የፕሬዚዳንቱን ችግር አታውቁም ነበር? በዚህ ፓርቲ ውስጥ በርካታ ችግሮች ይታዩ ነበር፡፡ ነገር ግን የሚፈቱት በውይይት ነበር፡፡ አንድ ሰው ችግር አለበት ተብሎ ከታሰበ ውይይት ላይ ይቀርባል፡፡ ያ ውይይት የቀረበበት አጀንዳ፣ የፓርቲው ስራ አስፈፃሚ በጊዜያዊነት ያግድና ለላዕላይ ምክር ቤት ያቀርባል፡፡ ም/ቤቱም ያይና የመጨረሻ ውሳኔ በመስጠት በጠቅላላ ጉባኤ ላይ ያሳውቃል፡፡ የእኛ መታገድ ግን ከዚህ የተለየ ነበር፤ በፕሬዚዳንቱ ደብዳቤ ብቻ ነው “ሁከት ፈጥራችኋል” ተብለን ወደ ፍ/ቤት የሄድነው መጀመሪያም ወደ ፍ/ቤት የሄድነው ያለ አግባብና ከመተዳደሪያ ደንቡ ውጪ ነው፡፡ በመተዳደሪያ ደንቡ መሠረት ሄደው ሳይሳካ ሲቀር ነው ፍ/ቤት የሚኬደው፡፡ ሌሎች በህገደንቡ መሠረት ከፓርቲው ከታገዱና ከተሰናበቱ ለምን እናንተ በህገወጥ መንገድ ሆነ ትላላችሁ?

እኛ ያቀረብነው መከራከሪያ ሃሳብ ትክክለኛ መረጃ ይዘን ነው፡፡ ለምሳሌ ከታህሳስ 15-17 2003 ዓ.ም በተካሄደ ጠቅላላ ጉባኤ፣ አቶ ሃይሉ አቶ ያዕቆብን ከመተዳደሪያ ደንቡ ውጭ ተቀዳሚ ሊቀመንበር አድርጌ ሾሜዎአለሁ አሉ፤ እሳቸው ይህንን ማድረግ አይችሉም፡፡ እሳቸው የሚችሉት ከሌላ ስራ አስፈፃሚዎች ጋር ሆነው ሌላ ስራ አስፈፃሚ የሚሆኑትን በመምረጥ ለላይዕላይ ም/ቤት ያቀርባሉ፤ ላዕላይ ም/ቤቱ ነው የሚያፀድቀው፡፡ ይኸ ሹመት ነው፡፡ በሊበራል ስርዓት በአንድ ግለሰብ የሚመረጥ ሹመት የሚባል ነገር የለም፡፡ በምርጫ ነው የሚደረገው፤ ባላቸው የስራ ልምድና የትምህርት ሁኔታ ነው፡፡ በዚህ ከተመረጠ ያልፋል፡፡ ካልተመረጠ ይወድቃል፡፡ እሳቸው ግን ቀጥታ አምጥተው አቶ ያዕቆብን ተቀዳሚ ሊቀመንበር አድርገው ሾሙ፡፡ ይሄ ነው ችግሩ፡፡ አንደኛ አቶ ያዕቆብ የድርጅቱ አባል አልነበሩም፡፡ የዕለቱ ዕለት ነው ለላዕላይ ም/ቤት ቀርቦ አባል ነው የተባለው፤ ዛሬ አባልነቱ ቀርቦ ወዲያውኑ ፕሬዚዳንት የሚሆንበትን ስርዓት ደንባችን አይፈቅድም፡፡ ይሄ ታዲያ በአቶ ሃይሉ ዘንድ እንደቂም ተወሰደ፡፡ እንዴት እኔ የምለውን አያከብሩም ብለው ተቆጡ፡፡ እኛ ደግሞ ማንም ከመተዳደሪያ ደንባችን ውጭ ከሆነ ስለምንታገል፤ ዋና አላማችንም ይሄ ስለሆነ እስከ መጨረሻው ፀንተናል፡፡ አቶ ሃይሉ አንድ አባልን ማገድ እንኳን የሚችሉት ለሁለት ወር ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እኛ ደግሞ አመራሮች ነን፤ በእሳቸው ልንታገድ አንችልም፡፡ ወሳኙ ደግሞ ጠቅላላ ጉባኤው ነው፡፡ ከ105 የላዕላይ ም/ቤት ውስጥ በተለያዩ ችግሮች 82 ሲቀሩ፣ ከነዚህ ውስጥ 57 የሚሆኑት አባላት ከእኛ ጋር ናቸው፡፡ ስለዚህ ይሄንን ሃሳባቸውን ለም/ቤቱ አቅርበው የሚያፀድቅላቸው ስለሌለ ነው አኩርፈው የተቀመጡት፡፡ አሁንም ለመነጋገር የማይፈልጉትም ለዚህ ነው፡፡ አሁንም “በውይይት እንፍታ ሲባሉ አልፈልግም” ያሉት ለዚህ ነው፡፡ የተቃወምነውን ትክክል ነው ብለን ሲቃወሙን ከቆዩ በኋላ አቶ ያዕቆብን በደብዳቤ አባረዋል፡፡ እናንተ በፓርቲው ውስጥ አመራር በነበራችሁ ጊዜ የኢንጂነር ኃይሉ ተቀናቃኞች ኢንጂነሩ ስልጣናቸውን ይልቀቁ ይሉዋችሁ ነበር፡፡

እናንተ ይሄን ችግር በወቅቱ አታውቁም ነበር?

ሌሎች ከፓርቲው ወጥተው ነገሩን ይተውታል አሊያም ሌላ ፓርቲ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ቅልውጥና ነው፤ ሌላ ነገር አይደለም፤ ማንም የፖለቲካ ሰው ላሰበበት ዓላማ መሳካት እስከመጨረሻው መታገል አለበት፡፡ አንድም አባል ግን እኛን ይሄንን ችግር አደረሳችሁብኝ ብሎ አጀንዳ ያስያዘ የለም፡፡ የመጀመሪያው እኔ ነኝ፡፡ እኛን ብዙ ጊዜ ሲሰድቡን አውቃለሁ፡፡ እኔ ግን ለግለሰብ አጐብድጄአለሁ፡፡ በፍፁም ሌሎቹ በጭቆና አይደለም የሚወጡት፡፡ እኛ ብቻ ነን በጭቆና የታገድነው፤ ስለዚህ እስከዚያ ድረስ በፓርቲው ውስጥ ትልቅ ችግር የሚባል አልነበረም፡፡ የእናንተ ቅሬታ ኢንጂነር ኃይሉ አቶ ያዕቆብን በመሾማቸው ነው፡፡

ኢንጂነር ሃይሉ እንዲመረጡ ደግሞ አንተ በአባላቱ ላይ ግፊት አድርገሃል፡፡ ታዲያ አሁን ለምን ችግር አለ ትላለህ?

በመጀመሪያ አቶ ያዕቆብ በምርጫ ባለመመረጣቸው ነው ቅሬታ ያቀረብነው፡፡ አቶ ያዕቆብን ያመጡዋቸውም አቶ ሃይሉ ናቸው፡፡ ይሄ ስንቃወም ስልጣን ፈልጋችሁ ነው ተብለናል፡፡ ከ400 በላይ ለሆኑ የጠቅላላ ጉባኤ አባላት አቶ ሃይሉን ምረጡ ብዬ የቀሰቀስኩት እኔ ነኝ፡፡ በዛን ሰአት እኔን ምረጡኝ ማለት እችል ነበር፡፡

ለምን ኢንጂነር ሃይሉ እንዲመረጡ አደረግህ?

ፓርቲው ላይ ትንሽ ችግር ነበር፡፡ አቶ ሃይሉ ለስምንት ወራት ከ2002 ምርጫ በኋላ ወደ ፓርቲው አልመጡም፡፡ ለዶ/ር ታዲዮስ ውክልና ሰጥተው ነበር የሚፈረመው፡፡ ጠቅላላው ጉባኤው ይጠራ ብለን ወጥረን ስንይዝ፣ አቶ ያዕቆብ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ አልፈለጉም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ጠቅላላ ጉባኤው አቶ ያዕቆብን አያውቃቸውም፡፡ በዚህ መሃል አቶ ኃይሉ ወደ ቢሮ እንዲመለሱ አቶ ያዕቆብ ግፊት እያደረጉ ነበር፡፡ አንተ ለአባላቱ ከነገርክልኝ ልመረጥ እችላለሁ ማለታቸውን ያወቅነው ከጠ/ጉባኤ አባላቱ ሲወጡ “እንዲህ እየተባልን ነው፤ አቶ ሃይሉ ደውለው አቶ ያዕቆብን ምረጡ እያሉን ነው” የሚል ነገር ነገሩን፡፡ የላዕላይ ም/ቤቱ የሚያቀርብላችሁን ሰው እጃችሁን አውጥታችሁ ስትመርጡ ነው እንጂ በጐን እየተደወለ ምረጡ ስለተባላችሁ ብትመርጡ አይሆንም አልን፡፡ ስለዚህ እንደዚህ አይነት ችግር ከመጣ ሠላማዊ ሽግግር ስለሚያስፈልግ ተብሎ አቶ ሃይሉ ይሄንን ፓርቲ ለስድስት ወር መምራት አለባቸው በሚል የጠቅላላ ጉባኤውን አባላት ምርጫችሁ ኢንጂነር ሃይሉ መሆን አለበት ብያቸው ነበር፡፡ ሁሉም በደስታ ተቀብለው የተባሉትን አደረጉ፡፡ እሳቸውም መድረክ ላይ ወጡና ደከመኝ ስል አልሰማም ብላችሁ እኔን መርጣችኋል፤ ስለዚህ እኔን እንዲያግዙኝ አቶ ያዕቆብ ልኬን ወክያለሁ ሲሉ ችግር ተፈጠረ፡፡

ችግር የፈጠሩት ኢንጂነር ሃይሉ ናቸው እያላችሁ ነው፤ ቀድማችሁ አቶ ያዕቆብን ምረጡ ማለታቸውንም ታውቃላችሁ፡፡ ይሄንን እያወቃችሁ ለምን እንዲመረጡ ፈለጋችሁ?

ጠቅላላ ጉባኤ የምንጠራበት ጊዜ ሊያልፍብን በመሆኑ ሳያልፍ ነበር ለማካሄድ ያስፈለገው። በወቅቱ ደግሞ ለፕሬዚዳንትነት የተሾመ ሰው አልነበረም፡፡ ስለዚህ አቶ ሃይሉን ስንመርጥ በህመምና በመሰልቸት ምክንያት ቤታቸው ቀሩ ብለን አስበን እንጂ እንዲህ አይነት ተንኮል ለማድረግ አስበዋል ብለን አልገመትንም። ይሄንንም የሰማነው አባላቱ ተጠቃለው አዲስ አበባ ከገቡ በኋላ ነው፡፡ ችግር እየፈጠሩ መሆናቸውን የሰማኸው ጠቅላላ ጉባኤው ሊካሄድ ሁለት ቀን ሲቀረው ነው ብለሃል። ነገር ግን ችግሩን ከመፍታት ይልቅ መልሳችሁ እሳቸውን መርጣችኋል፡፡ አሁን ደግሞ ችግር ፈጠሩ እያላችሁ ነው፡፡ ሌሎች ደግሞ ማሙሸት እራሱን በአቶ ያዕቆብ ቦታ ለመተካት አስቦ ስለነበር ነው ይላሉ… ይሄ ከእውነት የራቀ የሞኞች ሃሳብ ነው። እኔ የስልጣን ጥም የለብኝም፡፡ ብፈልግ ደግሞ እኔ እራሴን አስመርጥ ነበር እንጂ አቶ ሃይሉን አላስመርጥም ነበር። ይሄንን ለማድረግ ለእኔ ቀላል ነው፡፡

አቶ ያዕቆብ ለጠቅላላ ጉባኤ ምርጫ በዕጩነት ባለመቅረባቸው ነው ችግራችሁ ወይስ ሙሉ በሙሉ ለዕጩነት መቅረብ አይችሉም ነው ተቃውሟችሁ?

አቶ ያዕቆብ አይደለም ለአመራርነት ለፓርቲ አባልነትም አይበቁም፡፡ በጣም ችኩል ናቸው። የቆዩትም በብዙ ችግር ነው፡፡ አቶ ያዕቆብ የፓርቲ አባል ሆነው አያውቁም፡፡ ዛሬ ጠዋት የመኢአድ የላይላይ ም/ቤት አባል ሆነው፣ ነገ ደግሞ ስራ አስፈፃሚ ሆነው መሾም አይችሉም፡፡ ደንቡም አይፈቅድም፡፡ ሌላው ደግሞ አቶ ሃይሉ መሾም አይችሉም፤ ይሄ የአልጋ ወራሽነት አሠራር አይደለም። እሳቸው ትልቅ ጂም ሠርተዋል፤ ከፈለጉ የዚያ ሃላፊ ሊያደርጓቸው ይችላሉ።

አቶ ያዕቆብ እንዲመረጡ ካልፈለጋችሁ ኢ/ር ሃይሉ ደከመኝ እያሉ ከምትመርጡ ለምን ፓርቲው በም/ፕሬዚዳንቱ እንዲመራ አላደረጋችሁም?

እኛም ያንን ነበር የጠበቅነው፤ ከደከማቸው ለሌላኛው ም/ፕሬዚዳንት መስጠት ይችላሉ፤ ያንን ባለማድረጋቸው እና አባል ላልሆነ ሰው ስልጣን በመስጠታቸው ነው ትልቁ ችግራችን፡፡ ካላወቁት መልአክ የሚያውቁት ሰይጣን ይሻላል ነው የሚለው ቃሉ፡፡ ከፓርቲው ከተለያችሁ ሁለት አመት ሆኗችኋል።

በዚህ ጊዜ ምን ሠራችሁ? የጠ/ጉባኤ ጥሪያችሁ ምን ይመስላል?

ፓርቲን የማደራጀት ስራ ነው እየሰራን የቆየነው፡፡ ፓርቲያችንን ለማንቃት እየሰራን ነው፡፡ 320 የሚሆኑ የፓርቲው ጠቅላላ ጉባኤ አባላት ፈርመው ለምርጫ ቦርድም አስገብተዋል ግን እስካሁን የተወሰነ ነገር የለም፡፡ እናንተ የምትጠይቁትን ነገር ኢንጂነር አልቀበልም ቢሉስ? የፓርቲው አባላት ይሰበሰባሉ፤ ውይይት ያደርጋሉ። ከዚያም ሁለት አመት ሙሉ የሔደበትን ለዚህ አጣሪ ጉባኤ ሪፖርት ያቀርባል፡፡ ስራ የሰራም ከሆነ የሰራውን፣ ያልሠራም ከሆነ ያልሠራበትን፤ ችግሮች ካሉ ችግሮቹን በሙሉ ያቀርብና ምርጫ ይካሄዳል፡፡ ከዚያ ከአምስት እጩዎች ውስጥ አንድ ለፕሬዚዳንትነት፣ ሌሎቹ ለምክትል ፕሬዚዳንትነት ይቀርባሉ፡፡ አቶ ሃይሉ በዚያ ጠቅላላ ጉባኤ ካልተመረጡ ውድቅ ይሆናሉ፡፡ ቦርዱም እውቅና እሚሰጠው በዚያን ጊዜ ለተመረጡት ፕሬዚዳንት እንጂ ለሌላ አይደለም፡፡ እለቃለሁ ስላሉ አይለቁም፤ አልለቅም ስላሉም አይቆዩም፡፡

አብዛኞቹ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ስለፓርቲያቸውና ስለአባላት ድክመት የሚናገሩት ፓርቲያቸውን ከለቀቁ በኋላ ነው፡፡ “ለምን በፓርቲው ውስጥ እያሉ ስለችግሮቻቸው አይናገሩም?” በሚለው ዙሪያ በቅርቡ ከአንድነት ፓርቲ የለቀቁት ኢንጂነር ዘለቀ ረዲን ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው አነጋግራለች፡፡

በአንድነት ፓርቲ ውስጥ ለምን ያህል ጊዜ ቆዩ?

አንድ አመት ከስምንት ወር ይሆነኛል፡፡ የ “ብርሃን ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ፓርቲ” መስራች ነበርኩ፡፡ በዛን ሠአት ነው የመበታተን ፖለቲካ ለአገሪቱ ስለማይጠቅም በሚል ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ደብዳቤ ያስገባነው፡፡ በጋራ ለመስራት ማለት ነው። አንድነትና መኢአድ ጥያቄያችንን የተቀበሉን ሲሆን መኢአድ ግን “አንድነት” ከመድረክ ካልወጣ የሚል ጥያቄ አቀረበ፡፡ ይሄኔ “አንድነት”ም ብዙ ዋጋ የከፈልኩበት ነው በሚል አልወጣም አለ፡፡ እኛም በዛ ተስማምተን በጋራ ለመስራት ተቀላቀልን፡፡ በፓርቲው ውስጥ ችግር እንዳለ የገለፁት ከአንድነት ከወጡ በኋላ ነው፡፡ ከዛ በፊት ለምን አልተናገሩም? እኔ ችግሮች እንዳሉ በስብሠባ ላይ እገልፃለሁ። በፅሁፌም እናገራለሁ፡፡ እኔ ነጋዴ ነኝ፡፡ ፓርቲ ውስጥ የገባሁት ለለውጥ ነው፤ ስለ ድክመቱ ሁሌም በፅሁፍ እተቻለሁ፡፡ ለውጥ እንዲመጣ ነው ቤተሠቤንና ጊዜዬን መስዋዕት አድርጌ እየሠራሁ ያለሁት፡፡

ከመፃፍህ ባለፈ ለሚዲያ አሁን እንደተናገርከው የገለፅከው የፓርቲው ችግሮች አሉ?

ከሌሉ አሁን መግለፁ ለምን አስፈለገ? አጠቃላይ ችግሮቻችንን በቃለ ጉባኤ አስይዤ አውቃለሁ፡፡ ለምሳሌ አንዳንድ ሠዎች “አቶ አስራት ሴረኛ ናቸው” ሲሉ ሴራውን አብራራው ብዬ እከራከራለሁ፡፡ አንድ ሠው ሴረኛ ነው የምለው” ፓርቲው እንዳያድግ ወደታች የሚያደርግ እና ብቻውን ጐልቶ ለመታየት የሚፈልግ ከሆነ ነው፡፡ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ መሪ፤ መንገድ ጠራጊ ዶዘር እንጂ እራሱን ለማሳየት የሚጥር መሆን የለበትም፡፡ ስራዎች እንዳይሠሩ ወይም ከፓርቲው መውጣት የሚፈልጉ ሠዎች እንዳይወጡ መሰናክል የምትፈጥሪ ከሆነ፣ ይሔ ነው ሴራ ማለት፡፡ ቁጭ ብለሽ ነገር ትጐነጉኛለሽ አትወጪም፤ ሊወጡ የሚፈልጉትን ደግሞ ነገር እየፈለግሽ ስስ ብልታቸውን በመምታት ብሎናቸውን ፈተሽ እንዲወድቁ ታደርጊያለሽ። ይሔንን በሚዲያ ከመናገር ይልቅ በውይይት ይፈታል ብዬ ስላሠብኩ ችዬው ኖርኩ፡፡ አሁን ግን ወቅቱ በመሆኑ ተናግሬያለሁ፡፡ እስቲ ሴራ ስለሚሉት ጉዳይ ያብራሩልኝ … ሰሜን ጐንደርን እኔ ስረከበው ለሁለት የተከፈለ ቡድን ነበር፡፡ ያንን ለማስታረቅ ከሠባት ጊዜ በላይ በአውሮፕላንና በመኪና ተጉዘናል፡፡ ግን ሊታረቁ አልቻሉም፡፡ ይሔም የሆነው ደግሞ አቶ አስራት በሠሩት ሴራ ነው፡፡ በመሀል ገብተው አንደኛውን ቡድን በማቅረብ፣ ሌላኛውን ቡድን በማራቃቸው ችግሩን መፍታት አልቻሉም፡፡ እኛ ስንገባበት ደግሞ ችግሩን ለመፍታት የሚያስፈልግ ገንዘብ እንዳይወጣ አቶ አስራት ከለከለ፡፡

\ስለዚህ ከእኔና ከሌሎች ስራ አስፈፃሚዎች ገንዘብ ተወስዶ፣ ልጆቹ ፆማቸውን እያደሩ ችግሩ በንግግር ተፈታ፡፡ አጣዬ የምትባል ቦታም ተመሳሳይ ችግር ተፈጥሮ ነበር፡፡ እኛ ግጭታችን ከፓርቲ ጋር ነው እንጂ የድንበር ግጭት አሊያም ሌላ የግል ግጭት የለብንም፡፡ በፊት ፓርቲው ለእንደዚህ አይነት ችግሮችና ለአባላት ስልጠና ገንዘብ መድቦ ይንቀሳቅስ ነበር፡፡ ልክ እኔ ስመጣ ገንዘቡን ከለከሉ፤ ምክንያቱ ደግሞ ሽባ እንድሆን ስለፈለጉ ነው፡፡ በእኛ እድሜ ያሉት ስራ እንዲሠሩ አይፈለግም፡፡ ስለዚህ ብሩን ከልክለው “ይሔው መስራት አልቻሉም” ለማለት ይፈልጋሉ፡፡ እናም “ፓርቲው ችግር ላይ ነው” ብዬ ሠዎችን አግባብቼ፣ ሠሌን ላይ እያደሩ ነው ስልጠና ወስደው ሀያ አምስት ቢሮዎች የከፈትኩት፡፡ ይሔ ሀቅ ነው፡፡ መተዳደሪያ ደንቡን በራሴ ወጪ ወደ ኦሮምኛ አስተርጉሜያለሁ፡፡ አሁን በፍኖተ ነፃነት ዌብሳይት ላይ የለቀቁት ነገር አለ፡፡ እኔ ኢህአዴግ እንደሆንኩ ገልፀዋል፡፡ ይሔን ጊዜ ይፈታዋል፡፡

ፓርቲው እንደ ኢህአዴግ እየሠራ ከሆነ ኢህአዴግ ነው ማለት ነው፡፡ ፓርቲው በርካታ የበሠሉና በእውቀት ያደጉ አባላቶችን የያዘ ነው፡፡ አመራሮቹ ግን በጣም ደካማ ናቸው፡፡ የፓርቲው አባላት በደንብ ቢሠራ ለውጥ የሚያመጡ ናቸው። ምንም ሳይሠራ ነው 25 ቢሮዎች የከፈትነው፡፡ ግን ፓርቲው እንዳያድግ የሚያደርጉ አመራሮች ናቸው። አመራሮቹ እኮ ስብሠባ ተከለከልን ብለው ዝም ብለው ይቀመጣሉ፡፡ ኢህአዴግ እስኪፈቅድ ነው የሚጠብቁት?

ከሆነስ መቼ ነው የሚፈቅድልን? እኔ በበኩሌ በየኤምባሲው እየሔዱ እንደራደር ማለታቸውን በፍፁም አልፈልገውም፡፡ የፓርቲውን ክብር ይነካል፡፡ ኢህአዴግ እራሱ እንዲደራደረን ነው መጥራት ያለብን እንጂ እኛ መሔድ የለብንም። ይሔ ከሴረኝነት የሚተናነስ አይደለም፤ ፓርቲውን ቁልቁል ይሰደዋል እንጂ አያሳድገውም፡፡ እኔ አሁንም ፓርቲውን አለቅም በአባልነት እቀጥላለሁ፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲ ማለት እኮ ሌላ መግስት ነው፡፡ ሌላ አገር ያሉት እኮ ይፈራሉ እንጂ ልመና አይገቡም፡፡ እዚህ ግን ሴራቸው ሲጋለጥ ይቆጣሉ፤ እኔ ደግሞ ውስጣቸውን ሸፍኜ የትውልድ ተወቃሽ መሆን አልፈልግም፡፡ የመልቀቂያ ደብዳቤ አስገብተህ ነው የወጣኸው? እኔ ህጋዊ መልቀቂያ አስገብቼ ነው የለቀቅሁት። እነሱ ቀንና ቁጥር የሌለው ደብዳቤ ሠጠን ይላሉ። መቼም ይሔን የሚያክል ፓርቲ የሚያስተዳድርና አስቀድሞ አገርን ይመሩ የነበሩ መሪ ደብዳቤ ሲወስዱ ቀንና ቁጥር አይተው ነው የሚሆነው፤ ግን እንደ ምክንያት ያወሩታል፡፡

አንዳንድ ሠዎች ንግግርህን ብታሳምረው ይላሉ፡፡ እኔ ግን አካፋን አካፋ፣ ዶማን ዶማ ማለት ነው የምፈልገው፡፡ ኢህአዴግ እነ አንዷለም አራጌ ስለ ነፃነት ሲናገሩ ግንቦት ሠባት አላቸው፡፡ አንድ ሠው ስለ አማራ ሲናገር፣ ነፍጠኛ፤ ስለ ኦሮሞ ሲናገር ደግሞ ኦነግ እያለ ኢህአዴግ ስም ይሠጣል፡፡ እነዚህ ደግሞ ሀሳቡን በነፃነት የተናገረንና ችግራቸውን የገለፀ ሠው ኢህአዴግ ነው ይላሉ፡፡ እንደውም ዶ/ር ነጋሶ ናቸው ኢህአዴግነታቸውን ይዘው የመጡት። ምክንያቱም የመናገር ነፃነታችንን እየነፈጉን ነው ያሉት፡፡ ለምሳሌ ፍኖተ ነፃነት ስለ እኔ የተሳሳተ ነገር በዌብሳይቷ ይዛ ወጥታለች፡፡ ታዲያ ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ በምን ለይቼ አያታለሁ፡፡ አዲስ ዘመን የአቶ ሀይለማርያምን ሃሳብ ይዞ ከወጣ በኋላ፣ የእኛን ግን አያወጣም፡፡ ፍኖተ ነፃነትም እያደረገ ያለው እንደዛ ነው፡፡ ችግሮችን ከፓርቲ ወጥቶ ከማውራት ለመፍታት መሞከር አሊያም ከወጡ አለመናገሩ አይሻልም? ለትውልድ እዳ ማስቀመጥ አልፈልግም። ለህዝብም ግልፅ ነገር ተናግሬ ነው መልቀቅ የምፈልገው፡፡ ከእኔ ብዙ ነገሮች የሚጠብቁ ሠዎች ይኖራሉ፡፡ ስለዚህ ችግሮቹን ለመፍታት ጥረት አደርጋለሁ፡፡ አልሳካም ካለኝ ደግሞ ችግሩን ለሚዲያ እናገራለሁ፡፡ ለምሳሌ ዶ/ር ነጋሶን እንውሠድ ዶ/ር ናቸው፡፡

ፒኤች ዲ የሚኮነው ከመሬት ተነስቶ አይደለም፤ የፊሎሶፊ ዶክተር ናቸው፡፡ አንድ እንደ እኔ በእድሜና በትምህርት የሚያንሳቸውን አርቅቆ ሠው ማድረግ መቻል አለባቸው፤ እሳቸዉ ግን እንዲማር ሳይሆን እንዲማረር ነው የሚያደርጉት። አንድ ሠው አንድ መፅሔት ላይ ስለ እኔ ፅፏል፡፡ በትልቅነታቸው ቢያከብራቸው ብሏል፤ ነገር ግን ፖለቲካ ላይ ሽማግሌ ብሎ ነገር የለም፤ እንደዚህ ያለው ነገር የሚሰራው ሠፈርና እድር ውስጥ ብቻ ነው፡፡ አብዛኞቻችን እኮ አገራችንን አንወድም። እዚህ አርግዘን አሜሪካን ወልደን ለመምጣት የምንፈልግ ነን፡፡ ሌሎቹ እኮ እዚህ አርግዘው ለመውለድ አገራቸው ነው የሚሔዱት፡፡ ለፓርቲው አድርጌለታለሁ የሚሉት ነገር ምንድነው? በገንዘብም በጉልበትም ብዙ ነገር አድርጌለታለሁ። ይሔንን መጥቀስ አያስፈልግም።

ዶ/ር ነጋሶ ለጀርመን ሬድዮ ሲናገሩ ገንዘቡን እንደፈለገ ሊረጨው ስለፈለገ ነው ብለዋል፡፡ እኔ ገንዘቡን ብረጨውና አባላቱ ከመጡ፣ እሳቸው የሚፈልጉት ይሔንን አይደለም እንዴ? ግን ያልሆነ ያልተደረገ ነገር ሲወራ ያሳዝናል፡፡ ፓርቲውን ቢመራው ብለው የሚያስቡት ማንን ነው? አቶ ተክሌ የፋይናንስ ሀላፊ ናቸው፡፡ እሳቸው ቢመሩት ከፍተኛ ለውጥ እንደሚመጣና የተሻለ ስራ እንደሚሠሩ አምናለሁ፡፡ ከዚህ በኋላስ ምን ለማድረግ አስበዋል? ፓርቲዬን አልተውም፤ በአባልነት እቀጥልላለሁ። እንደዚህ አይነት አመራሮች ፓርቲውን እንዳያሽመደምዱት የበኩሌን እጥራለሁ፡፡

የኛ ምኞት ጉዳዩ በሲኖዶስ ደረጃ እንዲታይ ነው

ቅዱስ ኤልያስ ሥልጣን፣ ሃብትና ንብረት አይፈልግም

አልመጣም ብንለውም መጥቷል ብንለውም የምንቀይረው ነገር የለም

ልቦናው ንፁህ ለሆነና እግዚአብሔር ለፈቀደለት ሰው በአካል ይታያል

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን አባል የሆነችበት “ማህበረ ስላሴ ዘደቂቀ ኤልያስ” የተባለው የጽዋ ማህበር አነጋጋሪ እየሆነ መምጣቱ ይታወቃል፡፡ ማህበሩ ከኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስያሜ አንስቶ መስተካከል ያስፈልጋቸዋል የሚላቸውን ጉዳዮች በይፋ እየገለፀ ነው፡፡ ከሁሉም በላይ የውዝግብ መነሻ የሆነው ግን ቅዱስ ኤልያስ ወደ ምድር ወርዷል ማለቱ ነው። ይህን ትምህርት በስፋት የሚሰጡት ደግሞ አባ ዮሴፍ ብርሃነ ናቸው። አባ ዮሴፍ ብርሃነ በ1984 ዓ.ም ከ4 ኪሎ ዩኒቨርስቲ በፊዚክስ ዲፓርትመንት በዲግሪ ከተመረቁ በኋላ ስለሃይማኖት መማር ስለሚፈልጉ፣ ድግሪያቸውን ስራ ሳይፈልጉበት አስቀምጠውት ደብረ ሊባኖስ ገብተው የቆሎ ትምህርት ተምረው በማጠናቀቅ ለ12 አመታት በጐንደርና በጐጃም ያገለገሉ ሲሆን በ2000 ዓ.ም የካቲት ወር ላይ በቀጥታ ወደ ማህበረ ስላሴ በመምጣት ማስተማር የጀመሩ ናቸው። እንዲሁም ጃማይካ ሁለት ጊዜ ሄደው ገዳም ገድመው የተመለሱ የሃይማኖት አባት ከእነዚህ አነጋጋሪ አጀንዳ ይዘው ብቅ ካሉ የማህበሩ አባላትና ከአባ ዮሴፍ ብርሃነ ጋር የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የማህበሩ አባል በሆኑት በፕሮፌሰር ይስማው አለሙ መኖሪያ ቤት የተለያዩ ጥያቄዎችን ይዞ በመቅረብ ተነጋግሯል፡፡

ኤልያስ ወርዷል እያላችሁ ነው፤ ማነው ኤልያስ?

የትስ ነው ያለው?

ይሄን ጥያቄ ከመመለሴ በፊት አንድ ነጥብ ላንሳ፡፡ ይሄ ማህበር የት የት ተሰብስቧል፤ የት ጉባኤ አድርጓል የሚለውን ካነሳን፣ በእርግጥም “ማህበረ ስላሴ ዘደቂቃ ኤልያስ” ስፍር ቁጥር በሌላቸው ገዳማትና አድባራት ጉባኤ አካሂዷል፡፡ የቅዱስ ኤልያስን መውረድ ለብዙ እልፍ አዕላፍ ምዕመናን ያስተማርንባቸው፣ ማህበሩም በእኩል ተገኝቶ ይህን ጉባኤ ያደረገባቸው በጐጃም፣ በጐንደር፣ በትግራይ ብዙ ገዳማት አሉ፡፡ በአለም ዙሪያም በኢየሩሣሌም፣ በአሜሪካና በብዙ ቦታዎች ላይ ማህበሩ ታላላቅ ጉባኤዎች አድርጓል፡፡ ቅዱስ ኤልያስ መውረዱ ከታወጀበት ጊዜ ወዲህ ማለት ነው፡፡ ይህቺ አራት ኪሎ የምትገኘው እግዚአብሔር የመረጣትና “የቤተልሄም ዋሻ” ተብላ በተሰየመች ቦታ ላይ ነው እስከዛሬ ስንሰባሰብ የነበረው፡፡

ወደ ጥያቄው ስንሄድ ቅዱስ ኤልያስ ማን ነው?

የት ነው ያለው ቢባል ቅዱስ ኤልያስ ማለት ከዛሬ ሶስት ሺህ አመት በፊት እግዚአብሔር ያስነሳው ለእግዚአብሔር አምልኮት ቀናኢ የሆነ ልዩ ክብር የተሰጠው፣ እግዚአብሔር በእሣት ሠረገላ ያሣረገውና በመጨረሻ ዘመን መጥተህ ይሄንን አለም ትፋረዳለህ ብሎ ቃል ኪዳን የሰጠው ነው። እና ጊዜው ደቂቃው የተቆጠረለት ሱባኤ ስለደረሰ በተነገረለት ቀነ ቀጠሮ መሠረት፣ እግዚአብሔር አምላክ በሙሉ ስልጣንና ሃይል ወደዚህ ምድር ልኮታል፡፡ የቅዱስ ኤልያስ መገለጫው ትክክለኛ ቀናኢ የሆነ አምልኮተ እግዚአብሔር ይስፈን የሚለው ነው፡፡ ይሄንን ነው የሚፈልገው፤ በዚህ ይታወቃል፡፡ ሌላ ደግሞ ክፉ ስራ ሲሰራ ዝም ብሎ የሚያይ አይደለም፤ ስልጣንና ሃይል ተሰጥቶታል። ሁለተኛ አስፈሪው ነገር ይሄ ነው፡፡ ተፈጥሮን ማዘዝ ይችላል፡፡ ማንኛውንም ነገር ማከናወን ይችላል፡፡

በእርግጥ ኤልያስን በአካል ማየት ይቻላል? የት ነው ያለው?

አዎ! እግዚአብሔር ፈቅዶላቸው እና ልቦናቸውን ንፁህ ላደረጉ ቅዱስ ኤልያስ ሊያነጋግራቸው ይችላል። እኛ ከልብ የምንወዳቸውና እውነትን እንደሚናገሩ የምናምናቸው በረሃ ላይ ወድቀው ያሉ አባቶቻችን ናቸው ይህ ታላቅ ነቢይ ሰአቱና ደቂቃው ደርሶ ወደዚህ ምድር መምጣቱን የነገሩን፡፡ እና አባቶቻችንን አነጋግሯቸዋል፡፡ እሱ እንግዲህ ረቂቅ እና እሣታዊ ስለሆነ በመላው አለም መንቀሳቀስና ሁሉን ሃይል ማሳየት የሚችል ነው። ልቦናው ንፁህ ለሆነና እግዚአብሔር ለፈቀደለት ሰው በአካል ይታያል፤ ያነጋግራል፡፡ እግዚአብሔር ላልፈቀደለት ግን አይታይም፡፡ ከዚህ ቀደም ብዙ ኤልያስ ነን የሚሉ ግለሰቦች በተለያዩ ሃገራት ተከስተው ነበር፡፡ አሁንም እናንተ የህዝቡን በኑሮ መጨነቅ፣ የፖለቲካ አለመረጋጋቶች፤ እና የመጨረሻው ዘመን ቀርቧል የሚሉትን አመለካከቶች መነሻ አድርጋችሁ ነው ኤልያስ መጥቷል እያላችሁ የምታስተምሩት ይባላል?

እንግዲህ አሁን እኛ ቅዱስ ኤልያስ መጥቷል ስላልን አይመጣም፣ አልመጣም ስላልነውም አይቀርም፡፡ መጥቷል በማለታችን ደግሞ የምናገኘው ትርፍ የለም። አልመጣም ስላልን ደግሞ የምናስቀረው ነገር የለም፡፡ ትልቁ ቁም ነገር ቅዱስ ኤልያስ መጣ ሲባል ምን ማለት ነው የሚለውን መረዳት ነው፡፡ አሁን በቤተክርስቲያናችን ቅዱስ ሚካኤል መጣ እንላለን፡፡ ዳንኤል በአንበሣ ጉድጓድ በተጣለ ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ ከአንበሳ ጉድጓድ አድኖታል፡፡ እነ ሰልስቱ ደቂቅ፤ እሣት ውስጥ ሲጣሉ ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ ከእሣት አድኗቸዋል፡፡ የቅዱስ ኤልያስ መምጣት ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ማንም ቅዱስ እኮ ከገነት ከብሔረ ህያዋን መጥቶ መሄድ ይችላል፡፡ አሁን ዋናው ጉዳይ መጥቷል አልመጣም የሚለው ክርክር አይደለም። የቅዱስ ኤልያስ መምጣት ዘመን፣ ሰአትና ደቂቃ ሲጠበቅለት ነበር፡፡ ያቺ ቀጠሮዋ ስትደርስ በ2000 ዓ.ም መጣ፡፡ መጣ ስንል ምን ማለት ነው፡፡ ለፍርድ ሃይል ለብሶ ስልጣኑ ተሰጥቶት አለምን ለመፋረድ መጣ ማለት ነው፡፡ አሁን በአለም ላይ ያለውን ትልቁን ስልጣን፣ በትረመንግስቱን ቅዱስ ኤልያስ ጨብጦታል፡፡ አለም በፍርድ ላይ ነው ያለችው፡፡ ማስጠንቀቂያ እየተሰጠ ነው፡፡ ትክክለኛውን መንገድ ተከተሉ፣ ሰንበትን አክብሩ፣ እውነተኛውን መስመር ያዙ እያለ ነው፡፡ ከዚህ የወጣውን ግን ይገስፀዋል፡፡ አሁን የኛ ጥረትና አባቶቻችን ያስረዱን ቅዱስ ኤልያስ የሚፈልገው ምንድን ነው የሚለውን ነው። ቅዱስ ኤልያስ ስልጣን አይፈልግም፣ የማንንም ሃብት ንብረት አይፈልግም፣ የሚፈልገው ትክክለኛ አምልኮተ እግዚአብሔር በአለም ላይ እንዲሰፍን ነው፡፡ አለም እሺ በጄ ብሎ ቢቀበል ያን ጊዜ በአክአብ ዘመን እንደነበረው በአለም ላይ ሠላም ይሰፍናል፣ በአንዲት ቅጽበት እግዚአብሔር ታላቅ ተአምራትን ያደርጋል፡፡ ስለዚህ እኛ አለም ሁሉ እንዲሰማው የሰው ልጆች እንዲገነዘቡት የምንፈልገው፣ ቅዱስ ኤልያስ በትልቅ ሃይልና ስልጣን መምጣቱን ነው፣ ማንም ከፍርዱ ሊያመልጥ አይችልም፡፡ አልመጣም ብንለውም መጥቷል ብንለውም እኛ የምንቀይረው ነገር የለም፡፡ እሱ ስልጣኑ ተሰጥቶት መጥቷል፡፡ ስለዚህ እያንዳንዱ መስመር ይያዝ፡፡ ሰንበትን ያክብር፣ እውነተኛ ተዋህዶን፣ ወልደአብ ወልደ አምላክ በተዋህዶ ከበረ፣ አንድ አምላክ አንድ ባህሪ የምትለዋን እውነተኛ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚፈፀምባትን ተከተሉ ጠብቁ እያለ ድምፁን እያሰማ ነው፡፡ አለም ይህን እሺ ብሎ ቢቀበል ከማንኛውም ጭንቀት ሊተርፍ እና ሊድን ይችላል፡፡ ይሄን እምቢ ካለ ግን ከፍርድ ሊያመልጥ አይችልም፡፡ ሌላው መታወቅ ያለበት ቅዱስ ኤልያስ ረዳት አይሻም፤ ለምሣሌ አንድ የፖለቲካ ቡድን ቢቋቋም ገንዘብ አዋጡልኝ ይላል ወይ የሰው ሃይል ስጡኝ ይላል፣ ቅዱስ ኤልያስ ግን ይሄን አይፈልግም፡፡ ተዋህዶ ብቻ ነው የምንከተለው፣ ኦርቶዶክስ የሚለውን አንቀበልም ትላላችሁ፡፡

ምንድን ነው ልዩነቱ?

አሁን ቤተክርስትያኗ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አይደለም እንዴ የምትባለው?

ለምንድን ነው ተዋህዶን ብቻ መነጠል ያስፈለጋችሁ?

ቅባት፣ ፀጋ፣ ሶስት ልደት እየተባለ በቤተክርስቲያናችን ውስጥ ከፍተኛ ችግር አለ። ነገር ግን ትልቁ ቁምነገር ከመጀመሪያው አንስቶ ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛዋን ሃይማኖት ካስተማረ በኋላ መናፍቃን ሲነሱ፣ እነ አርዮስ፣ መቅዶንዮስ፣ እነ ንስጥሮስ ሲነሱ፣ አባቶቻችን ጉባኤ ሠርተው እውነተኛዋ ንጽህት የሆነች ተዋህዶን አንድ አካል አንድ ባህሪ ወይም በሊቃውንት አባባል “ወልደ አምላክ ወልደ ማርያም በተዋህዶ ከበረ” የምትለዋን ሃይማኖት መስክረውልናል፤ ደንግገውልናል፡፡ ይህቺን እውነተኛ መስመር ተከትለን እንድንሄድ፣ የሰው ልጅ ድህነት አግኝቶ የዘላለም ህይወት ውስጥ የሚገባው፤ ወደ ዘለለማዊ ህይወት በር የሚሻገረው፣ በዚህች እውነተኛ ጠባብ መስመር ሲጓዝ ነው፡፡ ስለዚህ የተለያዩ ኑፋቄዎች በዙሪያችን ቢኖሩም ከነዚህ ሁሉ ተጠብቀን እውነተኛ መስመር እንድንጓዝ ነው የሚፈለገው፡፡ ነገር ግን አሁን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ተብሎ እዚያ ውስጥ ብዙ ኑፋቄ፣ የለየለት ክህደት እንዳለ፣ ውስጥ ለውስጥ ብዙ ክፉ ስራ እንደሚሰራ ሁሉም የሚያውቀውና የሚገነዘበው ነው፡፡ ቀናኢ ነብይ የሆነው ቅዱስ ኤልያስ ከዚህ ሁሉ እንክርዳድ ራሳችንን እንድንጠብቅ፤ እውነተኛ መስመር እንድንከተል ነው ያዘዘን፡፡ ይህ አቋማችሁ ቤተክርስቲያኗን አይከፋፍልም? የእናንተን አካሄድ ኑፋቄ ነው በሚል የሚነቅፉ የሃይማኖቱ መሪዎች አሉ?

ማለት … የቅዱስ ኤልያስን መውረድ ነው ኑፋቄ ነው የሚሉት?

የቅዱስ ኤልያስን መውረድም ሆነ አጠቃላይ የእናንተን አካሄድ ….

አዎ እንግዲህ እሱ አለ፡፡ የተለያየ ነገር እንደሚባል ሰምተናልም አይተናልም፡፡ ነገር ግን ቀደም ብዬ እንዳስረዳሁት ነው፡፡ ይሄ እውነታ ነው፤ እኛ ስለተናገርነው የምንጨምረው ነገር የለም፤ ስላልተናገርን ደግሞ የምንቀንሰው ነገር የለም፡፡ ማንም ሊሸፍነው የማይችለው እውነት ነው፡፡ እግዚአብሔር ፍቃዱ ሆኖ አንድ ጊዜ ቅዱስ ኤልያስ ወርዷል፡፡ አሁን ይህንን ማንም ሊሰውረው አይችልም፤ እኛም ተባብረን እንሰውረው ብንል አንችልም እና ይሄን አስተውሎ እውነቱን መከተል ነው እንጂ ኑፋቄ ነው እያሉ ምክንያት መደርደር ዋጋ የለውም፡፡ ጌታ ሰው በሆነ ጊዜ በዚህ ምድር ላይ ሲመላለስ ምን ነበረ ፀሐፍት ፈሪሳውያን ያሉት፤ “ይሄ ሰውዬ የናዝሬት ሰው ነው፤ ትንቢቱ የተነገረው ከይሁዳ ወገን ነው፣ ከዳዊት ወገን በይሁዳ ይወለዳል ነው የሚለው፤ እሱ ከናዝሬት የመጣ ነው አባቱም ዮሴፍ ነው እናውቀዋለን። ይሄ ሃሰተኛ ነው” ብለው የተቻላቸውን ያህል ተቃውሞ አንስተዋል፡፡ ሆኖም የጌታን ሰው መሆን ሚስጥር ሊሰውሩት አልቻሉም፡፡ እውነትን ወደ ሃሰት ሊቀይሩት አልቻሉም፡፡ አሁንም ኤልያስ መጥቷል፡፡ ኤልያስ የሚመጣው ከኢየሩሣሌም ነው፤ የሚመጣው ከአውሬው ጋር ነው፤ በዚህ ጊዜ ነው ምናምን የሚሉ ብዙ ምክንያቶች ይደረደራሉ፤ ግን ዋጋ የለውም፡፡ እግዚአብሔር በሚስጥር ስራውን አከናውኗል፡፡ ስለዚህ ፀሐፍት ፈሪሣውያን፣ ጌታን ተቃውመው እውነትን መሰወር እንዳልቻሉት፣ አሁንም ብዙ የቤተክርስቲያን ሰዎች ቢናገሩ፣ መጽሐፍት ቢጠቅሱ፣ ይሄንን ሃቅ ሊሰውሩት አይችሉም፡፡ አንዴ እውነቱ ወጥቷል። ትልቁ ቁም ነገር የሰው ልጅ ቆም ብሎ የቅዱስ ኤልያስን መልዕክት አስተውሎ መጓዙ ላይ ነው፤ እንጂ ሃሰተኛ ነው፤ ኑፋቄ ነው፤ ቤተክርስቲያንን ይከፋፍላል ቢባል እውነቱን መሰወር አይቻልም። ልክ ያን ጊዜ ፀሐፍት ፈሪሣውያን ሆነው እንደተገኙት ነው የሚሆነው እንጂ ሌላ ትርጉም አይኖረውም፡፡

ይህ አቋማችሁ ከማህበረ ቤተክርስቲያን ያገለናል የሚል ስጋት የላችሁም?

ቅዱስ ሲኖዶስስ ሊያወግዛችሁ አይችልም?

ይህ እንግዲህ እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ ደርሶ የመወገዝ ነገር እስካሁን የለም፡፡ በቅርቡ ግን መምህር ምህረተአብ አሰፋ ባወጡት ቪሲዲ፤ በተለይ ከየካቲት 28 ጉባኤ በኋላ፣ የጐሉ ተቃውሞዎችን አይተናል፡፡ እኛ ይሄንን መልዕክት መስጠት የጀመርነው ግን ጳጉሜ 1 ቀን 2003 ዓ.ም ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ፤ ለአባቶች፣ ለሲኖዶስ አባላት፣ ለተለያዩ ገዳማዊ አባቶችና መምህራን ትምህርቱን ሰጥተናል፤ ከብዙዎች ጋርም ተማክረናል፤ ከብዙ ደቀመዛሙርትና መምህራን ጋርም ጉዳዩን ተወያይተንበታል። መክረንበታልም። “ማህበረ ስላሴ” በተለያዩ ገዳማትና አድባራት ይህን ጉባኤ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ አሁን እንግዲህ ለሁለት አመት ያህል መሆኑ ነው። እርግጥ ያን ጊዜ ተቃውሞ የለም ማለት አይደለም፤ ሃሰተኛ ነው የሚሉም ነበሩ፡፡ እርግጠኝነቱን ተቀብሎ ዳግም ራሱን ከ“ማህበረስላሴ ዘደቂቅ ኤሊያስ” ጋር አሠልፎ የሚጓዝም አለ፡፡ ግን በሲኖዶስ ደረጃ ነገሩ የታየ አይመስለንም፤ የኛ ምኞት ግን እንዲታይ ነው። እውነቱ እንዲገለፅ ነው፡፡ ለምሣሌ አሁን መምህር ምህረተ አብ የሠጡት ምላሽ፣ የቤተክርስቲያን መልስ አሠጣጥ አይደለም፡፡ የቤተክርስቲያን መልስ አሠጣጥ ከታሪኩ እንደምንረዳው እነ አርዮስም ሲወገዙ ጉባኤ ፊት ይቀርባሉ፤ ሙሉ ሃሣባችሁን ግለፁ ይባላሉ። ለተነሣው ሃሣብ መልስ የሚሠጠው ሙሉ ጥያቄና መልስ ከተካሄደ በኋላ ነው፡፡ ይሄ ስህተት ነው፤ ይሄ እውነት ነው፤ የሚለው ፍርድ የሚሠጠው ከዚያ በኋላ እንጂ አንድ ቃል ቀንጭቦ ማጋጋል አይደለም፤ ይሄ አይነት አካሄድ የአባቶቻችን ይትበሃል እና መስመር አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ፈቃዱ ቢሆን ጳጳሣቱም ሆኑ የቤተክርስቲያን ሃላፊዎቹ አንድ ጉባኤ ሠርተው

“እስቲ ኤልያስ ይመጣል ተብሏል፤ ትንቢቱ እንዲህ ተነግሯል ጊዜው ነው?

መጥቷል ወይንስ አልመጣም?

እስቲ ምንድን ነው ምልክቶቹ?”

ሃሠት እና እውነቱ ሁሉ ለአለም ቢገለፅ የእኛም ምኞት ነው። ብዙዎቹ አሁን ይሄ ሲነገር አዕምሮአቸው የሚሄደው የስልጣን ሽሚያ፣ የሃብት ንጥቂያ ነገሮች ጋ ነው። እውነቱን ለመናገር ይሄን መልዕክት ለኛ እየነገሩን ያሉ አባቶቻችን በባዶ እግራቸው የሚሄዱ፣ እህል የማይቀምሡ፣ ራሣቸውን አሣልፈው ለእግዚአብሔር የሠጡ፣ የዚህን አለም ተድላ የናቁ ናቸው፡፡ ስለዚህ እነሡ መጥተው በጵጵስና በወርቅ ዙፋን ላይ ተቀምጠው የመኖር ሃሣብ የላቸውም፡፡ ሃሣባቸው የእግዚአብሔር አምልኮት በትክክል እንዲፈፀም ብቻ ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ የምትሠባሠቡት ከቤተክርስቲያን ውጪ በአዳራሾች ነው፡፡ ይህ ደግሞ በቤተክርስቲያን ተቀባይነት እንደሌለው ሊቃውንቱ ያስረዳሉ፡፡ ይህንንም ኑፋቄ ነው ብለው ይነቅፋሉ … እኛ ከቤተክርስቲያን አንድም ቀን ወጥተን አናውቅም። ይሄ እምነታችን ነው፤ እውነተኛም ነው፡፡ ምናልባት ቦታው የካቲት 28 ቀን 2005 ዓ.ም እንዳደረግነው በአዳራሽ ሊሆን ይችላል፡፡ በቤተክርስቲያን ውስጥ ሲባል ሚስጥሩ ሲመረመር ትርጓሜው ቤተክርስቲያን ማለት መንፈስ ቅዱስ የሠፈረበት፣ የደናግል መነኮሣት፣ የሠማዕታት የሃዋሪያት ማህበር ያለበት፣ የእነሡ አስተምህሮ የሚነገርበት፣ እነሡ በመንፈስም በአካልም ተገኝተው የሚባርኩት ጉባኤ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ እኛ ጉባኤያችንን ለእግዚአብሄር አምልኮት ቀናኢ ሆነን እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን ቅዱስ ኤልያስን ይዘን ጉባኤ እስካደረግን ድረስ እኛ ያለነው በእርግጥም በቤተክርስቲያን ውስጥ ነው፤ ቁም ነገሩ ቦታውና ህንፃው አይደለም።

በቤተክርስቲያን ውስጥ ነው ጉባኤያችንን በሙሉ ያደረግነው፤ በአካል ግን በቤተክርስቲያን ውስጥ ለምን አልተደረገም ለሚለው አስቀድሜ መልሻለሁ፡፡ በተለያዩ ገዳማትና አድባራት እንዲሁም በተለያዩ ቦታዎች እየተዟዟርን በምናስተምርበት ጊዜ ቅዳሴው፣ ካህናቱ አሉ፣ ማህሌቱ በተቆመበት ነው ይህ ጉባኤ የሚካሄደው። የቅዱስ ኤልያስ መውረድም የተነገረን እንደዚሁ ነው። እኛ አሁንም ቢሆን በቤተክርስቲያን ውስጥ ነን፡፡ ትሁታን ሆነው ለገዳማት ለቤተክርስቲያናት የተለያዩ እርዳታዎችን የሚያደርጉት ደግሞ በቤተክርስቲያን ውስጥ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያንን እየደገፉ ናቸው፡፡ ስለዚህ ከቤተክርስቲያን ተገልሎና ወጥቶ የራሱን ቡድን አቋቁሞ የሚሄድ ሠው የለም፡፡ ይህ እንደ ፖለቲካዊ ድርጅት የአመፃ አካሄድ አይደለም፡፡ እኛ በእውነተኛ ቤተክርስቲያን ውስጥ ሆነን ክፉ ነገር ከቤተክርስቲያን ይራቅ ነው የምንለው። እኛ በቤተክርስቲያን ውስጥ መሆናችንን ነው የምናውቀው። ለጊዜው በዚያች ቤት መሠባሠባችንም ሁኔታዎች ስላላተመቻቹ ነው እንጂ እኛ ቤተክርስቲያን መሄድ ጠልተን አይደለም፤ እዚያ የተለያየ ችግር አለ፡፡ እምቢተኝነት አለ፤ ሠአቱም አመቺ አይደለም፤ ማታ ማታ ስለምንሠባሠብ ያለ ሠአት ለምን ትገባላችሁ ትወጣላችሁ ማለት ይመጣል፡፡ ይሄ ሁሉ ችግር ስላለ ነው፡፡ ባጭሩ እኛ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዳለን ነው የምናውቀው፤ አባቶቻችን ከእኛ ጋር ናቸው፡፡ በብዙ ገዳማት አባቶች አሉን፣ ባህታውያን አሉን፣ በጳጳሣት ደረጃም ብዙዎች አሉን፡፡ እኔ ስማቸውን አልጠቅስም ግን ልቦናቸው ከዚህ ጋር የሆነ አብረውን በዚህ እውነት የሚጓዙ በአለም ዙሪያ ብዙ የእግዚአብሔር ወዳጆች አሉ። ከዚህም በላይ በአይን የማይታዩ ቅዱሣን ሁሉ ከእኛ ጋር መሆናቸውን በእርግጠኝነት እናምናለን አምነናልም፡፡

እርስዎ እንደሚሉት ሳይሆን የራሣቸውን ሃይማኖት ፈጥረዋል ነው የምትባሉት?

ከመካከላችሁ “እኔ ኤልያስ ነኝ” የሚል እንዳለም ይነገራል?

ለዚህ እንግዲህ የማቀርበው መልስ መድሃኒታችን ኢየሡስ ክርስቶስ በመጣ ሠአት ከህገ ኦሪት ወደ ህገ ወንጌል አሸጋግሮናል፡፡ ያን ጊዜ መድሃኒታችን ኢየሡስ ክርስቶስ አዲስ ሃይማኖት መስርቷል? ይሄን ነው ለነዚህ ወገኖች እንደ ጥያቄ የምናቀርበው፡፡ ከህገ ኦሪት ወደ ወንጌል ሲሸጋገር አዲስ ሃይማኖት አልመሠረተም። ሃይማኖት አንዲት ነች ለመላዕክት የተሠጠች፣ በህገ ልቦና የነበረች በህገ ኦሪት የተነገረች፣ በህገ ወንጌል የተመሠረተች፣ አለምን አሣልፋ የምትኖር አንዲት ሃይማኖት ነች፡፡ ስለዚህ አሁንም ለዘመናት ትንቢት ሲነገርለት የነበረ ነብይ ነበረ፡፡ ሠአቱ ደቂቃው ደርሶ እሡ ሲመጣ በቤተክርስቲያን ውስጥ ለዘመናት ተሸሽገው ሲሠሩ የነበሩ አጓጉል ነገሮች ነበሩ፡፡ ይሄ በተንኮል ነው የተሠራው፤ መስመሩን እንዲህ አድርጋችሁ አስተካክሉ፣ ቀጥተኛ የቀድሞውን መስመር ተከተሉ ብሎ መስመሩን ቅዱስ ኤልያስ አሣይቶናል፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ኤልያስ የሚፈልገው የቀደመችውን መስመር አጥርተን እንድንሄድ እንጂ አዲስ ሃይማኖትን አይደለም፡፡ ልክ ጌታ፤ ህገ ኦሪት ላይ ተመስርቶ ህገ ወንጌልን ብሩህ አድርጐ እንዳሣየ፣ ኤልያስም ለዘመናት ሲሠሩ የነበሩ ተንኮሎችና አጓጉል መስመሮችን አጥርቶ ትክክለኛውን መስመር እንድናይ አደረገ እንጂ አዲስ ሃይማኖት አይደለም የፈጠረው፡፡ ሃይማኖት አንዲት ናት እሷም ተዋህዶ፡፡ ኤልያስ ወረደ ማለት አዲስ ሃይማኖት አይደለም፡፡

ይልቅስ እነሡ ይወርዳል የሚል መፅሃፍ ነው የያዙት ማድረግ ያለባቸው እንዴትና መቼ የሚለውን በሚገባ መመርመር ነው። በአጭሩ እኛ የመሠረትነው አዲስ ሃይማኖት የለም። በማህበራችን ውስጥም እኔ ኤልያስ ነኝ ያለ አንድም የለም፡፡ ኤልያስ በመላው አለም ቦታና ስፍራ ሣይወስነው በእሣት ሠረገላ ያለ ነው፡፡ ሠንበት ቅዳሜ እንጂ እሁድ አይደለም ትላላችሁ? ይህን ለማለት መነሻችሁ ምንድን ነው? በእርግጥ ሠንበት አንዲት ናት እሷም ቅዳሜ ነች። ይህ እንግዲህ ቅዱስ ኤልያስ ተሠውረው የነበሩ እውነቶችን ሲገልጥ ከተገለጡት አንዱ ነው። ቅዳሜ እና እሁድ ሁለቱም ሠንበት እንዴት ሊባል ቻለ? የሚለውን ከታሪክ መዛግብት በሠፊው ማወቅና መገንዘብ ይቻላል፡፡ ከ4ኛው መቶ አመት ጀምሮ ነው ለ1600 አመታት እሁድ ሠንበት ሲባል የኖረው በተንኮል የገባ ነው፡፡ እግዚአብሔር ስድስት ቀን ፈጥሮ ሠባተኛ ቀን ላይ ያረፈባት ሠንበት ተብላ የተጠራችው ቅዳሜ ነች፡፡ እሁድ እሁድ ነው የራሱ ስም አለው፡፡ እሁድ ብሎ ጀምሮ ቅዳሜ ላይ ያበቃል። በኢትዮጵያም ከታሪክ እንደምንረዳው ሁለት ታላላቅ ጉባኤዎች ተደርገው ሠንበት የትኛው ነው የሚል ጥያቄ ተነስቶ ነበር። ነገስታቱ ማስታረቅ ስላቃታቸው እሁድ ሠንበት ይባል ማለታቸውን ታሪክ ያስረዳናል፡፡ እሁድ የጌታ ትንሣኤ ነው፤ የፅንሠት ቀንም ነው፤ ስለዚህ እሁድን በእሁድነቱ እናከብረዋለን፡፡

አርማችሁ ላይ የዳዊት ኮከብንና የ“ቶ” ምልክትን ነው የምትጠቀሙት ይህ ከአይሁድ እምነት ጋር አይቆራኝም?

እንግዲህ እግዚአብሔር አምላክ ለቅዱሣን ሁሉ ታላላቅ ምልክቶችን ሠጥቷቸዋል፡፡ በእርግጥ እስራኤል ይሄንን የዳዊት ኮከብ የሚባለውንና አሁን በቤተ መንግስታቸው ዙሪያ ያለውን ምልክት ይዘውታል፡፡ በሠንደቅ አላማቸው ላይም ይጠቀማሉ፡፡ ነገር ግን ኮከቡ ራሱን የቻለ ታላቅ ሚስጥር ያለው ነው፤ የመንፈስ ቅዱስ ሃይል ያለው ምልክት ነው፡፡ የስድስቱን ቀን ስነ ፍጥረት ስድስት ጫፎቹ ያስረዳሉ፤ መሃሉ ደግሞ ሠንበትን የሚያመለክት ነው፡፡ “ቶ” ሠባተኛዋ ፊደል ነች፡፡ ሠባት ቁጥር ትልቅ ትርጉም ያላት ነች ፍፁምነትን የምታመለክት ነች፡፡ ሠባተኛው ዙፋን የጌታ እንደሆነ፣ ሠባተኛው ቀን ሠንበት እንደሆነች፣ 7 ቁጥር ብዙ ሚስጥር አላት፡፡ “ቶ” ሠባተኛዋ ቁጥር በመሆኗ ፍፁምነትን የምታመለክት ነች፡፡ ክርስቶስን የምትወክል ነች፡፡ ክርስቶስ ለኛ ሲል በቀራኒዮ መስቀል ላይ ራቁቱን መሠቀሉን የምታመለክት ነች። ትልቁ ከዚህ በላይ ያለው ሚስጥር አባቶቻችን ከቅዱስ ኤልያስ የተረዱት ያን ጊዜ በመላዕክት አለም ውጊያ ተደርጐ ነበር፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ቅዱስ ገብርኤል ከሣጥናኤል ጋር ሲዋጉ ሁለት ጊዜ ተሸንፈዋል፡፡ በሶስተኛው እንዲያሸንፉ ሲልካቸው ይህን ቀስተደመና ቀርፆ፣ ይህን ምልክት የኮከቡን ቅርፅ የ“ቶ” ቅርፅ ያለው መስቀል በየክንፋቸው ቀርፆላቸዋል፡፡ አንዱ የሠጣቸው ትልቅ ሃይል ኮከቡ እና “ቶ” የሚለው ቅርፅ ነው፡፡ ስለዚህ ይህን ተዘንግቶ የነበረውን ቅዱስ ኤልያስ የኛ መሆኑን አውቀን እንድናነሣው አድርጐናል፡፡ ለክርስቲያኖች በሙሉ ዲያብሎስን ድል እንድንነሣበት የተሠጠን ነው እንጂ እንደተባለው ክርስቶስን ከሠቀሉት ጋር የማበርና በእነሡ መስመር የመጓዝ ነገር አይደለም። ነጭ ልብስ ነው መለበስ ያለበት የሚል አዋጅም አውጃችኋል? ይህ ነጭ ልብስና ቀስተ ደመና ያለበት ልብስ ሃይል ነው፡፡ ጥቁር ልብስን በተመለከተ ጥቁር ልብስ አጉል ነገር ነው፡፡ ተንኮል አለበት፡፡ በግብፅ አባቶቻችን ክርስቲያኖች ይኖሩ በነበረ ሠአት በሙስሊሞች ተፅዕኖ ነው ጥቁር ልብስ እንዲለበስ የተደረገው፡፡ ቅዱስ ኤልያስ በዘመናት የተሠራውን ተንኮል ስለሚያውቅ የክርስቲያኖች ልብሳቸው ነጭ መሆን እንዳለበት አውጇል፡፡ ይህም የተሠጣቸውን ተስፋ እና ትንሣኤ የሚያመለክት ነው። ስለዚህ ነው ጥቁር ልብስ ይቅር የሚል ታላቅ አዋጅ ከቅዱስ ኤልያስ የተነገረን፡፡ በተለይ ካህናት ነጭ ወይም ሌላ አይነት ቀለም ያለው ልብስ መልበስ አለባቸው፡፡ ጥቁር ልብስ መልበስ በሠይጣን አገዛዝ ስር ያለን መሆናችንን የሚያመለክት ነው፡፡ ከጥቁር ውጪ ሌላ አይነት መልበስ ይቻላል፡፡ የአንገታችን ማህተብ እና የልብሣችን ዘርፍ የቀስተደመና ቀለም መሆኑም ሃይል ያላብሠናል፡፡